Administrator

Administrator

   በምስራቅና ደቡባዊ አፍሪካ አገራት የሚገኙ 1 ሚሊዮን ያህል ህጻናት የኤሊኖ ክስተት ባስከተለው ድርቅ ሳቢያ የከፋ የምግብ እጥረት ተጠቂዎች መሆናቸውንና አስቸኳይ እርዳታ እንደሚያስፈልጋቸው ዩኒሴፍ አስታወቀ፡፡ በአካባቢው አገራት የሚገኙት እነዚህ ህጻናት የምግብና የውሃ እጥረት እንዳለባቸውና የክብደት መጠናቸው እየቀነሰ እንደሚገኝ የጠቆመው ተቋሙ፣ የምግብ ዋጋ መናር ቤተሰቦች ሳይመገቡ እንዲውሉና ንብረቶቻቸውን ሽጠው ምግብ እንዲገዙ እያስገደዳቸው ነው ብሏል፡፡መንግስታት ችግሩን ለመቋቋም የራሳቸውን ጥረት እያደረጉ ቢሆንም፣ በህጻናቱ ላይ የተከሰተው የከፋ የምግብ እጥረት አሳሳቢ ነው ተብሏል፡፡ሌሴቶ፣ ዚምባቡዌና አብዛኞቹ የደቡብ አፍሪካ አገራት ድርቁን ተከትሎ አስቸኳይ እርዳታ እንደሚፈልጉ ማስታወቃቸውን የዘገበው አጃንስ ፍራንስ ፕሬስ፣ በኢትዮጵያም የምግብ እርዳታ የሚያስፈልጋቸው ሰዎች ቁጥር በዚህ አመት ከ10 ሚሊዮን ወደ 18 ሚሊዮን ከፍ ይላል ተብሎ እንደሚጠበቅ ገልጧል፡፡ማላዊ ባለፉት 9 አመታት የከፋ በተባለው የምግብ እጥረት እንደተጠቃች ያስታወሰው ዘገባው፣ 15 በመቶ ያህል ህዝቧ የርሃብና የከፋ የምግብ እጥረት ችግር እንዳንዣበበበት አክሎ ገልጧል፡፡

“ትራምፕ በምርጫው አሸንፎ የአሜሪካ ፕሬዚዳንት አይሆንም!...” ባራክ ኦባማ
             “በአሜሪካ ታሪክ እጅግ ቀሽሙ ፕሬዚዳንት ኦባማ ነው!...” ዶናልድ ትራምፕ
    ፕሬዚዳንት ባራክ ኦባማና በመጪው የአሜሪካ ምርጫ ሪፐብሊካንን ወክለው ለመወዳደር በምርጫ ክርክር ተጠምደው የሰነበቱት አነጋጋሪው የሪልስቴት ከበርቴ ዶናልድ ትራምፕ የቃላት ጦርነት ውስጥ መግባታቸው ተዘገበ፡፡
ኦባማ ባለፈው ሰኞ ካሊፎርኒያ ውስጥ በተካሄደ ስብሰባ ላይ ከጋዜጠኞች ለቀረበላቸው ጥያቄ፣ ትራምፕ በምርጫው አሸንፈው ቀጣዩ የአሜሪካ መሪ ሊሆኑ አይችሉም፤ ምክንያቱም አገርን መምራት ዕቃ ዕቃ ጨዋታ አይደለም! የአገሬ ህዝብ እንዲህ ያለ ሰው እንዲመራው እንደማይፈቅድ ስለማውቅ፣ ትራምፕ አሸንፎ ፕሬዚዳንት እንደማይሆን አምናለሁ ሲሉ መተቸታቸውን ቢቢሲ ዘግቧል፡፡“የአሜሪካ ፕሬዚዳንት መሆን፣ የቶክ ሾው መምራት አይደለም!... በምርጫ ማሸነፍም፣ ሰፊ ማስታወቂያ የመስራትና የገበያ ጥናት የማድረግ ጉዳይ አይደለም፡፡ ከባድ ተልዕኮ ነው!...” ብለዋል ኦባማ የትራምፕን አካሄድ በመተቸት፡፡ኦባማ ይሄን ማለታቸውን ተከትሎም፣ በምርጫ ክርክር ተወጥረው የሰነበቱት ዶናልድ ትራምፕ፤ በነጋታው ረቡዕ ለኦባማ ትችት መረር ያለ የአጸፋ ምላሽ መስጠታቸውን ሲኤን ኤን ዘግቧል፡፡“በአሜሪካ ታሪክ እጅግ ቀሽሙ ፕሬዚዳንት ባራክ ሁሴን ኦባማ ነው!... እሱ የሚሰራውን ነገር የማያውቅ፣ የአገር መሪ ነኝ የሚል ቀሽም ሰው ነው!... በ2012 ምርጫ በዕጩ ተወዳዳሪነት ብቀርብ ኖሮ፣ ኦባማን በቀላሉ ዘርሬ ስልጣኑን እይዝ እንደነበር ቅንጣት ታህል አልጠራጠርም!” ብለዋል ትራምፕ፡፡

ቫይረሱ በ39 አገራት ተሰራጭቷል
    የዓለም የጤና ድርጅት፤ ነፍሰጡሮችን በማጥቃት የጭንቅላት መጠናቸው አነስተኛና የአእምሮ እድገታቸው ውስን የሆኑ ህጻናት እንዲወለዱ የሚያደርገውን ዚካ ቫይረስ ለመዋጋት ለሚከናወኑ ስራዎች 56 ሚ ዶላር ያስፈልጋል ማለቱን ሮይተርስ ዘገበ፡፡
ገንዘቡ በተለይ በደቡብ አሜሪካ አገራት በመስፋፋት ላይ ለሚገኘው ዚካ ቫይረስ በአፋጣኝ ክትባት ለመፍጠር፣ በቫይረሱ የተጠቁትን ለመመርመርና በጉዳዩ ዙሪያ ዘላቂ መፍትሄ የሚያመነጩ ምርምሮችን ለማድረግ እንደሚውል የጠቆሙት የድርጅቱ ጄኔራል ዳይሬክተር ማርጋሬት ቻን፣ ቫይረሱ ወደ 39 የአለማችን አገራት በመስፋፋቱ በአፋጣኝ መፍትሄ መፈለግ እንደሚገባ ተናግረዋል፡፡
ድርጅቱ የሚፈለገውን ገንዘብ ከአባል አገራትና ከለጋሾች አገኛለሁ ብሎ እንደሚጠብቅ የገለጹት ቻን፣ ሰሞኑን ቫይረሱ ክፉኛ ወደተስፋፋባት ብራዚል አምርተው ድርጅቱ የቫይረሱን ስርጭት ለመግታት እያከናወነ የሚገኘውን ስራ እንደሚገመግሙና ከአገሪቱ የጤና ሚኒስትር ጋር በጉዳዩ ዙሪያ እንደሚወያዩም ተናግረዋል፡፡

    በኢትዮጵያ የህብረት ስራ ማህበራት ታሪክ 50 ዓመታትን ያስቆጠረ ቢሆንም ማህበራቱ በስርአት ተደራጅተው፤ በፖሊሲ ታቅፈው ሥራ ከጀመሩ ከሁለት አስርት ዓመታት በላይ አልሆናቸውም፡፡ በአሁኑ ሰዓት የግብርና ምርቶች ላይ እሴት በመጨመርና ወደ ውጪ በመላክ ለአገሪቷ ገቢ ያስገባሉ፡፡ ምርጥ 10 ከሆኑት ቡና ላኪዎች ውስጥ አብዛኞቹ የህብረት ሥራ ማህበራት ናቸው፡፡ ነገር ግን የሚጠበቅባቸውን ያህል እየሰሩ አይደለም ይባላል፡፡ በሌላ በኩል ለማህበራቱ ተገቢው ትኩረት አልተሰጠም የሚል ቅሬታ ይሰነዘራል፡፡ የአዲስ አድማስ ጋዜጠኛ ማህሌት ኪዳነወልድ፤ የፌደራል ህብረት ሥራ ማህበር ኤጀንሲ ዋና ዳይሬክተር አቶ ኡስማን ሱሩርን በማህበራቱ እንቅስቃሴ፣ችግሮችና የወደፊት ትልሞች ዙሪያ አነጋግራቸዋለች፡፡  
የማህበራቱ አላማ ምንድን ነው?
እንግዲህ ማህበራት ለአርሶ አደሩ፣ ለአርብቶ አደሩ፣ እንዲሁም ለዝቅተኛው ማህበረሰብ ትልቅ ጠቀሜታ አላቸው፡፡ የግብይት ሰንሰለቱን በማሳጠር፣ አርሶ አደሩ ላመረተው ምርት ተመጣጣኝ ዋጋ እንዲያገኝ፣ በገጠር የፋይናንስ ስርአት ቅርፅ እንዲይዝ… በአጠቃላይ የአንድ አገር ኢኮኖሚ እድገት ዘላቂ እንዲሆን ከተፈለገ፣ የማህበራቱ ሚና በተለይም በግብርናው ዘርፍ መተኪያ የለሽ ነው፡፡
አጠቃላይ እንቅስቃሴያችሁ ምን ይመስላል?
እንግዲህ በአጠቃላይ ማህበራቱ ከ15.8 ቢ. ብር በላይ ካፒታል አላቸው፡፡ ከ802ሺ በላይ ለሚሆኑ ዜጎችም የስራ እድል ፈጥረዋል፡፡ በተለይም የግብርና ምርቶች ላይ እሴት በመጨመርና ወደ ውጪ በመላክ ለአገሪቷ ገቢ ያስገባሉ፡፡ በተለይ በቡናና ሰሊጥ ምርቶች፡፡ ምርጥ 10 ከሆኑት ቡና ላኪዎች ውስጥ አብዛኞቹ የህብረት ሥራ ማህበራት ናቸው፡፡
ከዚያም በላይ መንግስት ፖሊሲና ስትራቴጂዎችን በመቅረፅ ሚናቸውን በማያሻማ መልኩ አስቀምጧል፡፡ እንግዲህ ይህን ያልኩት ጠቀሜታቸውን በአጭሩ ለማሳየት ነው፡፡ ሆኖም የሚጠበቅባቸውን ያህል እየሰሩ አይደለም፡፡ በርካታ ቀሪ ነገሮች አሉ፡፡ በፖሊሲው ላይ እንደተቀመጠው ከሆነ፣ አሁን የምናየው ውጤት በቂም ብቁም አይደለም፡፡ ትልቅ የአመለካከት ችግር አለ፡- በአመራሩ፣ በተደራጀው ክፍል፣ በአደራጁ… በሁሉም በኩል፡፡ አንዳንዱ ማህበራቱን የደርግ ሶሻሊስት ስርአት ማስፈፀሚያ አድርጎ የማሰብ፣ የደሃ መሰብሰቢያ እንዲሁም ከእድርና ከእቁብ የተለየ ተቋም አድርጎ ያለማየት ችግሮች አሉ፡፡ ይህ ችግር ማህበራቱ ማግኘት ያለባቸውን ድጋፍ እንዳያገኙ እያደረገ ነው፡፡ የመሰረተ ልማት አቅርቦት ችግር አለባቸው፡፡ መጋዘን የላቸውም፡፡ መስሪያ ቦታ፣ ቢሮ የለም፡፡ ይህንን ማቅረብ ያለበት አካልም የዝግጅት ችግር አለበት፡፡ ፖሊሲው አንድ ሆኖ፣ ከክልል ክልል አፈፃፀሙ ይለያያል፡፡ ወደ ዞንና ወረዳ ስትወርጂ ደግሞ ችግሩ እጅግ የከፋ ነው፡፡ ሌላው ነገር ብድር ነው፡፡ በቂ ብድር የለም፤ የብድር ጉዳይ ትልቅ ማነቆ ነው፡፡ ማህበራቱ ብድር የሚያገኙበት ማእቀፍ የለም፡፡ ስለሆነም ለአገሪቱ ኢኮኖሚ ማበርከት ያለባቸውን አስተዋፅኦ አላበረከቱም፡፡ በተጨማሪም ብዙዎቹ ማህበራት በኮሚቴ እንጂ በባለሙያ አይመሩም፡፡ ምርቱ ተወዳዳሪ ቢያደርጋቸውም ወደ ተግባር የሚቀይር ባለሙያ ያስፈልጋቸዋል፡፡ እንግዲህ ፖሊሲውን በማስፈፀም የመሰረተ ልማት ችግርን ለመፍታት እየሰራን ነው፡፡ ፋይናንስ አካባቢ ግን ገና መታየት አለበት፡፡ አማራጮች ሊቀመጡ ይገባል፡፡
መንግሥት ለዘርፉ ተገቢውን ትኩረት አልሰጠም እያሉኝ ነው?
መንግሥት በፖሊሲ ማእቀፍ ያስቀመጠው አቅጣጫ፣ የሰጠው ትኩረት አለ፡፡ ትኩረት ስንል ከፌደራል እስከ ክልል ነው፡፡ እንግዲህ መንግስት ስንል፤ ክልል፣ ዞን፣ ወረዳ፣ ቀበሌ እያለ ይወርዳል፡፡ ያው ትኩረት አሰጣጡ ከክልል ክልል ይለያያል፡፡ ትኩረቱ በእርግጥ በቂ አይደለም፡፡ እንደውም ወደ ታች ከክልል ወረዳ እያለ ሲወርድ… ጭራሽ የለም ማለት ይቻላል፡፡ አንዳንዱ ክልል የህብረት ስራ ጉዳይን የመጨረሻ አጀንዳው ያደርገዋል፡፡ እንግዲህ በGTP2 የተሻለ ነገር ለማየት ተስፋ እናደርጋለን፡፡ በተለይ የአዲስ አበባ አስተዳደር ከማህበር አገልግሎትና ብዛት እንዲሁም ከተማዋ ዋና የገበያ ማእከል ከመሆኗ አንፃር፣ ለማህበራት የሰጠው ትኩረት እጅግ አናሳ ነው፡፡
ብዙ ጊዜ ማህበራቱ ከዘይትና ስኳር ስርጭት ጋር በተያያዘ በረጅም ሰልፍና አንዳንዴም የለም በማለት ነው የሚታወቁት …?
ህብረት ስራ ማህበራት በዋናነት የሚደራጁት ለዘይት፣ ስኳርና ዱቄት ብቻ አይደለም፡፡ በርካታ ምርቶችን ያቀርባሉ፤ በተለይ ግብርናው ላይ፡፡ ምንድነው --- መንግስት በድጎማ የሚያቀርባቸው እነዚህ ምርቶች ላይ የአቅርቦትና የፍላጎት ያለመጣጣም ችግር አለ፡፡ ስለሆነም አነስተኛ ገቢ ላለው ህብረተሰብ በተመጣጣኝ ዋጋ በማህበራት በኩል ያቀርባል፡፡ በመዲናዋ ከ130 የሚበልጡ ማህበራት አሉ፡፡ ከእነዚህ ውስጥ ከ30 በማያንሱት ላይ ኪራይ ሰብሳቢነት ሊታይ ይችላል፡፡ በጓሮ በር እያወጡ የሚሸጡ መኖራቸው አይካድም፤ተከታተለንም እርምጃ እየወሰድን ነው፡፡ ነገር ግን በጅምላ መጥላትና መንግስት ለራሱ ጥቅም ያደራጃቸው ተቋማት አድርጎ ማየቱ ተገቢ አይደለም፡፡ ይህንን ነው እንግዲህ ቅድም የአመለካከት ችግር አለ ያልኩሽ፡፡ የማህበራቱ መልካም ስራ አብሮ መነሳት አለበት፡፡ ለምሳሌ አዲስ አበባ ፒያሳ፣ ማህበራቱ አንድ ኪሎ የቁርጥ ስጋን ከ80-90 ብር ይሸጣሉ፡፡ ሌላ ቦታ ከ180-200 ብር ሲሸጥ እያየን ነው፡፡ 1 ኪሎ ሽንኩርት ከ6-7 ብር ይሸጣሉ፡፡ በሌላው ገበያ 12 እና 14 ብር እየተሸጠ ነው፡፡ ማህበራቱ ከ30 እስከ 120 በመቶ የዋጋ ልዩነት አላቸው፡፡
እንግዲህ ማህበራቱ ባለፈው ዓመት 4.5 ቢ. ብር ምርት ሸጠዋል፡፡ ከ30 እስከ 120 በመቶ የዋጋ ልዩነት አላቸው ካልን፣ በአማካይ ወስደን በ60 ብናበዛው እንኳን ብዙ ሚሊዮን ብሮች ተጠቃሚ ኪስ ገብቷል ማለት ነው፡፡ ይህ ደግሞ የሀብት ክፍፍሉን ፍትሃዊ ያደርገዋል፡፡
ወደተለያዩ የውጭ አገራት በመሄድ ተሞክሮ ወስዳችኋል፤ ተሞክሮው ምን ይመስላል?
እነ ጃፓን፣ ኦስትሪያ፣ ታይላንድ፣ ማሌዢያና አውሮፓ… ለህብረት ስራ ማህበራት የድጋፍ ማእቀፎች አሏቸው፡፡ የፋይናንስ ችግርን ለመፍታት የተለየ ባንክ ፣ የተለየ የፖሊሲ ማእቀፍ አላቸው፡፡ ለምሳሌ ደቡብ ኮሪያ ሦስት አይነት ባንክ አላት፡- ንግድ ባንክ፣ ህብረት ስራ ባንክና ፖሊሲ ባንክ ናቸው፡፡ የትኛውም ማህበር የገንዘብ እጥረት ሲገጥመው ቢዝነስ ፕላን አቅርቦ ብድር ያገኛል፡፡ የሚሰራበት ቦታ ይሰጠዋል፡፡ ግብር ነፃ ነው፡፡ ሌላም ሌላም፡፡ በእኛ ሀገር አንዳንዱ አዋጁ ላይ አለ፤ ነገር ግን አተገባበር ላይ ችግር አለ፡፡ አንዳንድ አዋጆችም ማሻሻያ እንዲደረግባቸው እየጠየቅን ነው፡፡ ማህበራቱ የዜጎቻቸውን ፍትሃዊ ተጠቃሚነት የሚያረጋግጡ መሆን አለባቸው፡፡ መንግስታት ሲቀያየሩ የኢኮኖሚ እድገትን የሚያስቀጥሉ ሊሆኑ ይገባል፡፡
ከ5 እና 6 ዓመታት በፊት አውሮፓና አሜሪካ የፋይናንስ ችግር ሲገጥማቸው ማህበራት ግን ሳይነኩ ወጥተዋል፡፡ ጃፓን ግብርናዋ የሚመራው በህብረት ስራ ነው፡፡ ሰሞኑን ያዘጋጀነው ኤግዚቢሽንና ባዛር ከነሱ በወሰድነው ተሞክሮ፣ የገበያ ትስስርን ለመፍጠር ያለመ ነው፡፡ በሌሎች አገራት ማህበራት በ50 እና 60ሺ ካሬ ላይ ያረፈ ትልልቅ የገበያ ማዕከላትም አሏቸው፡፡ እንግዲህ ቅድም 13.3 ሚ. ዜጎች የማህበራት አባል ናቸው ብዬሻለሁ፤ ይህንን ቁጥር በ5 ቤተሰብ እንኳን ብናበዛው እያወራን ያለነው ስለ 60ሚ. ህዝብ ነው፡፡ ስለዚህ ኃላፊነታቸውን እንዲወጡ ከተፈለገ የአመለካከት ችግሮች ተቀይረው የሚገባቸውን ትኩረት ሊያገኙ ይገባል፡፡ በእርግጥ ማስተዋወቁ ላይ እኛ ዘንድም ክፍተት አለ፡፡ በቀጣይ የምንሰራበት ይሆናል፡፡
በአሁኑ ወቅት ስንት የህብረት ሥራ ማህበራት አሉ?
ከ71 ሺህ በላይ መሰረታዊ የህብረት ስራ ማህበራት፣ ከ353 ሺህ በላይ የህብረት ስራ ዩኒየኖች አሉ፡፡ በኢትዮጵያ ከ13.3 ሚ. በላይ ዜጎች የህብረት ስራ ማህበራት አባል ናቸው፡፡

    የተባበሩት የአረብ መንግሥታት ንብረት የሆነው ፍላይ ዱባይ አየር መንገዱ ከወር በፊት በተጠናቀቀው የፈረንጆች ዓመት ባደረገው እንቅስቃሴ ስኬታማ እንደነበር አስታወቀ፡፡
 አየር መንገዱ በዓመቱ ውስጥ 81,530 በረራዎችን በማድረግና 9.04 ሚሊዮን ተሳፋሪዎችን በማጓጓዝ፣ 27.4 ሚሊዮን ዶላር ያገኘ ሲሆን የተጓዞቹ ብዛት ከ2014 ጋር ሲነፃፀር በ1.8 ሚሊዮን ሰዎች ብልጫ (25 በመቶ መጨመሩን) እንዳለውና ለ4ኛ ዓመት ትርፋማ መሆኑን ገልጿል፡፡
አጠቃላይ ገቢው 1.33 ቢሊዮን ዶላር ሲሆን ከ2014 ጋር ሲነፃፀር የ11 በመቶ ዕድገት አሳይቷል፡፡ በአንዳንድ መዳረሻ መስመሮች በሚፈጠሩ እገዳዎች ብዙ መስተጓጎሎች መፈጠራቸውንና ከአዳዲስ የበረራ መስመሮች ጋር በተያያዘ ከፍተኛ ግፊትና ጫና እንደነበረበትም አመልክቷል፡፡
የፍላይ ዱባይ ዋና ስራ አስፈፃሚ ሚ/ር ጋኢዝ አል ጋኢዝ፤ አጠቃላይ የንግድ ሁኔታው ፈታኝ ቢሆንም የዕድገት ታሪካችንን በመጠበቅ ዓመቱን በስኬት አጠናቀናል ብለዋል፡፡ 

“ዘ ዊክንድ” በሚል ቅጽል ስሙ የሚታወቀውና ከቅርብ ጊዚያት ወዲህ አለማቀፍ ዝናን በማትረፍ ላይ የሚገኘው ትውልደ ኢትዮጵያዊው ድምጻዊ አቤል ተስፋዬ፣ በሳምንቱ መጀመሪያ በተካሄደው የዘንድሮው የግራሚ ሽልማት ስነስርዓት በሁለት ዘርፎች ተሸላሚ ሆኗል፡፡
በዘንድሮው የግራሚ ሽልማት በሰባት ዘርፎች ለሽልማት ታጭቶ የነበረው አቤል ተስፋዬ፤ ሎሳንጀለስ ውስጥ በተከናወነው 58ኛው የግራሚ ሽልማት ስነስርዓት ላይ፣ “ቤስት ኧርባን ኮንቴምፖራሪ አልበም” እና “ቤስት አር ኤንድ ቢ ፐርፎርማንስ” በተሰኙት ሁለት ዘርፎች አሸናፊ በመሆን ሽልማቱን ተቀብሏል፡፡
“ቢዩቲ ቢሃይንድ ዘ ማድነስ” የተሰኘው አልበሙ በ“ቤስት ኧርባን ኮንቴምፖራሪ አልበም”፣ “ኧርንድ ኢት” የተሰኘው ስራው ደግሞ  በ“ቤስት አር ኤንድ ቢ ፐርፎርማንስ” ዘርፎች ለሽልማት እንዳበቁት የተዘገበ ሲሆን፣ ባለፈው ሰኞ ምሽት በተካሄደው የሽልማት ስነስርዓቱ ላይ የሙዚቃ ስራዎቹን ለተመልካቾች አቅርቧል፡፡
በዘንድሮው የግራሚ ሽልማት ካሸነፉት ድምጻውያን መካከል ቴለር ስዊፍት፣ ኬንድሪክ ላማር እና ኤሚ ዋይንሃውስ ይገኙበታል፡፡

Saturday, 20 February 2016 09:44

የዘላለም ጥግ

(ስለ ዲሲፕሊን)
- ዲሲፕሊን በግብና በስኬት መካከል ያለ
ድልድይ ነው፡፡
ጂም ሮህን
- አንድ ጊዜ ቁርጠኝነቱ ካለህ ያሰብክበት
ለመድረስ ዲሲፕሊንና ተግቶ መስራት
ይኖርብሃል፡፡
አትሌት ኃይሌ ገ/ሥላሴ
- ያለ ዲሲፕሊን ህይወት ጨርሶ የለም፡፡
ካታሪን ሄፕበርን
- ማህበራዊ ሚዲያ ጊዜህን እንዳይሰርቅብህ
ዲሲፕሊን ያስፈልግሃል፡፡
አሌክሲስ ኦሃንያን
- በራስ መተማመን የሚመነጨው
ከዲሲፕሊንና ከልምምድ ነው፡፡
ሮበርት ኪዮሳኪ
- ስኬት የሚለካው ባለህ ዲሲፕሊንና
በውስጣዊ ሰላምህ ነው፡፡
ማይክ ዲትካ
- ጥሩ ዲሲፕሊን ቢኖረኝ ኖሮ ወደ ሙዚቃ
ሙያ እገባ ነበር፡፡
ክሊንት ኢስትውድ
- ዲሲፕሊን ማለት የምትፈልገውን ነገር
ማስታወስ ነው፡፡
ዴቪድ ካምቤል
- አንዳንድ ሰዎች ዲሲፕሊንን እንደ ሥራ
ይቆጥሩታል፡፡ ለእኔ በነፃ እንድበር
የሚያደርገኝ የስርዓት ዓይነት ነው፡፡
ጁሊ አንድሪውስ
- የስኳር በሽታ ዲሲፕሊንን አስተምሮኛል፡፡
ሶንያ ሶቶማዮር
- ጥቂት ሰዎች ጀግና ሆነው ይወለዳሉ፡
፡ ብዙዎች የሚጀግኑት በልምምድና
በዲሲፕሊን ኃይል ነው፡፡
ፑብሊዩስ ፍላቪዩስ ቬጄቲዩስ ሬናቲዩስ
- ዲሲፕሊን? የቃሉን ትርጉም አላውቀውም፡፡
ሊያም ጋላግሄር
- አማፂ ለሆነ ሰው ዲሲፕሊን ከባድ ነው፡፡
ጆናታን ዊንተርስ

    ስሙ ያልታወቀ ፀሐፊን ጠቅሶ አንድ የኛ ፀሐፊ ያቀረበውን ለዛሬ ተረት እናርገው
ዐጼ ቴዎድሮስ አንድ ቀን አንድ የሚያምኑትን ዘበኛ ይዘው፣ አልባሌ መስለው ከጨለመ በኋላ በሠፈሩ ይዞሩ ጀመር፡፡ በየጐጆው እየተጠጉ ያደምጡ ነበር፡፡ እኩሉ ያልተኛ እኩሉም ተኝቶ፡፡ ከዝያ ወዲያ ካንድ ወታደር ጐጆ ተጠግተው ቢያደምጡ ባልና ምሽት በግብረ - ሥጋ ሲጣሉ ሰሙ፡፡ ወንዱ ይለምናል፡፡ ሴቲቱ አይሆንም ትላለች፡፡ ከዝያ ወዲያ ወንድየው፤
“በማርያም”፣ በሥላሴ፣ “በጻድቃን በቅዱሳን” እያለ ቢለምን፤ ሴትዮዋ፣
“እምቢ አይሆንም” ትላለች፡፡
ሰውየው፤
“ኧረ በሥላሴ ይሁንብሽ?”
“በጭራሽ ስልህ? አሻፈረኝ አልኩኮ!”
“በጻድቃን በቅዱሳን?”
“ሰውየው፤ እምቢ ማለት አይገባህም?”
ሰውየው የመጨረሻ ሙከራ አደረገ፡፡
“በይ በቴዎድሮስ ሞት…” አላት፡፡
“ቴዎድሮስማ ከሚሞት፣ ጐንደር አይታረስም” አለችና ፈቀደች፡፡
ንጉሡ ይሄንን ከሰሙ በኋላ እየሳቁ ወደ አዳራሻቸው ገቡና፣ ያን አብሮአቸው የነበረ ዘበኛ፤ ያችን ጐጆ እንዳታሳስትህ አስተውላት ብለውት ነበረና በነጋታው ያንን ዘበኛ፤
“ባልና ሚስቱን ጠርተህ አምጣቸው” ብለው ሰደዱት፡፡
ባልና ሚስቱም፤
“ምን ተገኘብን ይሆን?” ብለው እየተንዘፈዘፉ፣ እየተንቀጠቀጡ መጡና ከጃንሆይ ፊት ቆሙ፡፡
ንጉሡም፤
“እንዴት አደራችሁ?” አሉ፡፡
እነዚያም እየተብረጀረጁ ሳይሰሙ ቀርተው ኖሮ ባጠገባቸው የቆመ ቢነግራቸው በግንባራቸው ተደፍተው እጅ ነስተው ቆሙ፡፡
ቀጥለውም ንጉሡ፤
“ትላንት ማታ በምኝታ ጊዜ ከቤታችሁ ሆናችሁ ተናገራችሁ?” ብለው ጠየቋቸው፡፡
“ጃንሆይ የተናገርነው የለም፡፡ ጠላት ነገር ሠርቶብን እንደሆነም ያጋጥሙኝ፤ ድኻ ወታደር ባሪያዎ ነኝ፡፡”
“ከመኝታችሁ ላይ ጥቂት የተናገራችሁት ነገር እንዳለ አስበህ ንገረኝ አይዞህ” አሉት፡፡
እሱም ሰውነቱን አጠናከረና አስቦ፣ ያንን ምሽቱ ያደረገችውን ነገር ነገራቸው፡፡ ንጉሡም ሳቁ፡፡ ሴቲቱም አፈረች፡፡
***
“በኃይለስላሴ አምላክ ተወኝ!”፣ “በንጉሥ ይዤሃለሁ ተወኝ”፣ “በህግ አምላክ” ዱሮ ቀረ፡፡ የንጉሥ ስም ተጠርቶ አትንካኝ፣ አትምታኝ፣ መብቴን አትንካ፣ ማለት ጥንት የተለመደ ነበር፡፡ ዛሬ ያ ልማድ ቀርቷል፡፡ ማንም አይሰማም፡፡ ነገሥታቱ በህዝቡ የየዕለት ህይወት ውስጥ ይገቡ ነበር፡፡ የመፈራታቸውም መጠን ወሰን የለውም፡፡ ዛሬ ህጉ እየተለወጠ፣ ዘመኑ ጤና እያጣ መጥቷል፡፡
ዛሬ ከሽማግሌው ይልቅ ወጣቱ ጤና አጥቷል፡፡ በቀላሉ ይሸነፋል፡፡ የትምህርት አቅሙ ደካማ በመሆኑ ዕውቀቱ አገም ጠቀም ነው፡፡ ከመማር ማማረር የሚመርጠው እየበረከተ፤ የሚያመረው እየሳሳ መጥቷል፡፡ ቁርጠኝነት ጠፍቷል፡፡ ለሱስ ተገዥነት የማያጠያይቅ አደጋ ነው፡፡ የወሲብ ማጠናከሪያ ዕንክብል ካዋቂው ይልቅ የለጋው ወጣት ማዳበሪያ ሆኗል፡፡ ዛሬ በሪህ በሽታ የሚያዘው ወጣቱ ሆኗል፡፡ ንቅዘት (degeneration)  የወቅቱ ትዕዛዝ ይመስላል፡፡ ይቅር ይበለን እንጂ ምን ይባላል፡፡ እጅግ አሳሳቢ ነው!
“አረጋዊውን ባንቀልባ፣ ከምንሸከም እንኮኮ
ጐልማሳውን ከወኔ ጣር፣ ካልፈታን ከፍርሃት ምርኮ” የሚለን ነው ፀጋዬ ገ/መድህን፡፡
ሌላው ጣራችን ዲሞክራሲ ነው፡፡ ማንም መንግሥት፣ ገዢ ፓርቲ ወይም ተቃዋሚ ድርጅት ልብ ሊል የሚገባው ዲሞክራሲ የትግል ሂደት ውጤት እንጂ መና እንዳልሆነና አሸናፊ ከተሸናፊ ጋር የመቻቻል ግዴታ እንዳለበት ነው፡፡ በዚህ ረገድ ስለባለጋራዎቻችን ኡምቤርቶ ኢኮ የሚለንን ማዳመጥ እጅግ ተገቢ ነው፤
“መልካም ምግባር የሚከሰተው የባለጋራዎቻችንን መኖር በመካድ ሳይሆን፣ ባላጋሮቻችንን በቅንነት በመረዳት፣ በነሱ ቦታ ሆነን ነገሮችን በመመልከት ነው፡፡ ሌሎችን በቅንነት መረዳት ማለት ልዩነትን ሳንክድ ወይም ቸል ሳንል፣ የአድልኦ አስተያየቶችን ማስወገድ ማለት ነው”
አንድ የሀገራችን ፀሐፊም “መቻቻል መቻል ነው፡፡ መቻል ሳይኖር መቻቻልን ማሰብ ከባድ ነው” ይለናል፡፡ ትላንት ያሳደግነውን ቂም በቀል ነቅለን መጣል አለብን፡፡ ከዓመት ዓመት አንድ ዓይነት መላ ምት እየተለምን፣ በ21ኛው ክፍለ ዘመን በአቦ ሰጡኝ መጓዝ፣ ባለበት ሂድ እንጂ ወደፊት አያራምደን፡፡ One step forward two steps back እንደሚሉት እንዳይሆን እንጠንቀቅ፡፡ አንድ ወደፊት ሁለት ወደኋላ ጐታች ጉዞ ነው፡፡ የለማውን ግብ ለማድረስ ሙስና ማነቆ ከሆነ፣ የለማውን ፍሬ ሳንበላ ኢ - ፍትሐዊነት ካገደን፣ የለማውን ወደበለጠ ደረጃ እንዳናደርስ “የአብዬን እከክ ወደምዬ ልክክ” እንቅፋት የሚሆንብን ከሆነ አካሄዳችን ውሽልሽል ነው፡፡ ዕድገታችን ቁልቁል ነው፡፡ በወጉ ያልተንከባከብነው ዕድገት ለወሬ እንጂ ለተግባር አይመችም፡፡ ከጐረቤቶቻችን በዚህ በዚህ እንበልጣለን፤ በዚህ በዚህ እንሻላለን፤ በዚህ በዚህ በአብዛኛው አብረን እየተጓዝን ነው፣ ማለት በተጨባጭ ዕድገትና ማንነታችንን አያሳይም፡፡ ይልቁንም፤ “ተንከባክባ ያላሳደገችውን ልጅ፣ የእከሌ ልጅ እኩያ ነው ትላለች” የሚለውን ተረት ነው የሚያረጋግጥ!  


ኢህአዴግ - አንድነት - ወህኒ ቤት

* ከ20 በላይ ሠላማዊ ሠልፍ ብመራም አንዲት ጠጠር አልተወረወረችም
* ኢህአዴጎች ለልጅ ልጆቻቸው የማይቆጭ ነገር ትተው ቢያልፉ መልካም ነው
* ከፖለቲካ ጋር የተዋወቅሁትና የተጠመቅሁት በአብዮታዊ ዲሞክራሲ ነው

 የአንድነት ፓርቲ አመራር የነበረው ወጣቱ ፖለቲከኛ ሃብታሙ አያሌው፤በሽብር ወንጀል ተጠርጥሮ አንድ አመት ከ8 ወር ያህል በእስር ላይ የቆየ ሲሆን ባለፈው ማክሰኞ በዳኛ ትዕዛዝ ከማረሚያ ቤት ሊለቀቅ ችሏል፡፡ ከፖለቲካ ጋር የተዋወቅሁት በአብዮታዊ ዲሞክራሲ ነው የሚለው ሃብታሙ፤የመጀመሪያ ፓርቲውም ኢህአዴግ መሆኑን ይናገራል፡፡ ከኢህአዴግ ጋር በምን ተቀያየመ? ተቃዋሚዎች እንዴት ተቀበሉት? ለእስር የዳረገው ምንድን ነው በአንድነት እጣፈንታ ምን ተሰማው? ወጣቱ ፖለቲከኛ ሃብታሙ አያሌው፤ ከአዲስ አድማስ ጋዜጠኛ አለማየሁ አንበሴ ጋር ከእስር በተፈታ ማግስት በፖለቲካ ህይወቱ፣እምነቱና ፈተናዎቹ ዙሪያ አውግተዋል፡፡

ከአንድነት ፓርቲ ብንጀምርስ? እንዴት ነበር ፓርቲውን የተቀላቀልከው?
በኢትዮጵያ ውስጥ በወቅቱ ከነበሩ ፓርቲዎች የተሻለ ነው ብዬ ነበር የተቀላቀልኩት፡፡ በወቅቱ በሠላማዊ ትግሉ ላይ የተሻለ ነገር ማምጣት ይችላል የሚል እምነት ነበረኝ፡፡ አንደኛ የሊበራል አስተሳሰብ ይዞ ወደ ግራ ሆነ ወደ ቀኝ ጠርዙ ሳይሄድ መካከለኛውን የያዘ ነበር፡፡ ይሄ አስተሳሰብ ደግሞ ኢትዮጵያ ውስጥ የሚጠየቁ የፖለቲካ መብቶችን፣ የቡድን ጥያቄዎችን ይመልሣል፡፡ ማዕከሉን ሊብራሊዝም አድርጓል፡፡ መካከለኛ ፓርቲ ሆኖ መሄዱ ለምርጫዬ አንዱ መሠረት ነበር፡፡ ሌላው በኢትዮጵያ ሉአላዊነትና አንድነት ላይ ያለው አቋም ጥሩ ነበር፡፡ በተጨማሪም በፓርቲው ውስጥ ተስፋ የሚጣልባቸው ወጣት አመራሮች ነበሩ፡፡ ከነሱ ሥር በመሆን በኢትዮጵያ ውስጥ ዘመናዊ የሆነ የዲሞክራሲ ሥርዓት ለመገንባት እድል ይኖራል፡፡ ስለዚህ ከነዚህ ሰዎች ጋር መታገል አለብኝ ብዬ፣ ጥያቄው ሲቀርብልኝ ቀጥታ በብሔራዊ ም/ቤት ደረጃ ነበር አባል የሆንኩት፡፡  
ከዚያ በፊት ግን በአብዮታዊ ዲሞክራሲ ርዕዮተ ዓለም የሚመራው ኢህአዴግ አባል ነበርክ፡፡ ከአብዮታዊ ዲሞክራሲ ወደ ሊበራል ያደረግኸው ሽግግር አላስቸገረህም?
የኢህአዴግን አብዮታዊ ዲሞክራሲ ከማወቄ በፊት የፖለቲካ እውቀቱም እምብዛም አልነበረኝም፡፡ ከፖለቲካ ጋር የተዋወቅሁበት ጊዜ ነው ማለት ይቻላል፡፡ በ1997 በአጠቃላይ በኢትዮጵያ ውስጥ ያለውን የለውጥ እንቅስቃሴ ከሚከተሉና ከሚፈልጉ ወጣቶች አንዱ ነበርኩ፡፡ በእርግጥ ከ3 ዓመታት በላይ በውጭ ሀገር በትምህርትም በስራም ቆይቼ የተመለስኩት በ1997 አጋማሽ ላይ ነበር፡፡ ስመጣ የለውጡን እንቅስቃሴ በሚገባ ተከታትያለሁ፡፡ በወቅቱ የበኩሌን አስተዋጽኦ ለማድረግም ጥረት አድርጌያለሁ፡፡ ከምርጫው በኋላ ቅንጅት ላይ የተፈጠረው ሁኔታ ወደ ሌላ ምዕራፍ አሸጋገረኝ፡፡ እንደ ማንኛውም ኢትዮጵያዊ የራሴን ስራ እየሠራሁ ኑሮዬን ቀጠልኩኝ፡፡
በ1999 ዓ.ም መጨረሻ ላይ የአዲስ አበባ ወጣቶች ፎረም ሲመሠረት፣ በወቅቱ የሚያውቁኝ አመራሮች ጥሪ አድርገውልኝ፣ ምስረታው ላይ እንድገኝ አደረጉኝ፡፡ የፎረሙ ምስረታ በጣም ሳቢ ነበር፡፡ በኋላ የሚከተለው አካሄድ የተሳሳተ መሆኑን አውቀን፣ መታገል እስከጀመርንበት ድረስ መነሻው ላይ ባይቀለበስ ጥሩ ነበር፡፡ ከመንግስት ጋር መቀራረብ፣ መመካከር፣ በሀገር ጉዳይ ላይ ወጣቱ ተሣታፊ እንዲሆን ማድረግ ነበር ዓላማው፡፡
 የመንግስት አመራሮች ተጠያቂ መሆን በሚገባቸው መጠን ተጠያቂ እንዲሆኑ የሚከታተል፣ የሚቆጣጠር የህብረተሰቡ በተለይም የወጣቱ ተወካይ እንዲሆን ነበር የታሰበው፡፡ ጥቅሙንም ተሣትፎውንም ማስከበር የሚችል፣ ከማንኛውም የፖለቲካ ወገንተኝነት የፀዳ በሚል ነበር የተመሠረተው፡፡
እየቆየን ስንሄድ በፎረሙ አመራር ላይ ለነበርን ወጣቶች የፓርቲ አባልነት ጥያቄ እየቀረበልን መጣ፡፡ ፖለቲካን ለመካን ደግሞ አብዮታዊ ዲሞክራሲ ምንድን ነው እየተባለ እንድንሰለጥን ተደረግን፡፡ ያኔ የኢህአዴግን ፖሊሲዎች በዝርዝር ለማንበብ ሞከርኩኝ፡፡ ከእኔ ውስጣዊ አቋም ጋር ይሄዳል አይሄድም የሚለውን ስገመግም ቆየሁ፡፡
የሶሻሊዝሙ ጐራ ምንድን ነው? የሊበራሊዝሙስ? አብዮታዊ ዲሞክራሲ ከእነዚህ ጋር ያለውን አንድነትና ልዩነት ሠፊ ጊዜ ወስጄ አጠናሁ፡፡ በ2001 ዓ.ም ኢህአዴግ ከፍተኛ አመራሮችን አላጌ ወስዶ ባሰለጠነ ጊዜ ተሣታፊ በመሆን በአጠቃላይ በድርጅቱ አስተሳሰብ ላይ በቂ ግንዛቤ ያዝኩኝ፡፡
በኢህአዴግ ውስጥ የነበረህ ተሳትፎ ምን ያህል ነበር?
በአብዮታዊ ዲሞክራሲ ላይ ሠፊ ክርክሮች ሲደረጉ በንቃት ከሚሳተፉት አንዱ ነበርኩ፡፡ በኢህአዴግ ቤት ውስጥ የማይነኩ የሚባሉ እንደ የመሬት ፖሊሲው፣ በቋንቋ ላይ የተመሠረተው ፌደራሊዝም --- የመሳሰሉ ጉዳዮችን አንስቼ እከራከራቸው ነበር፡፡ በተለይ የቋንቋ ፌደራሊዝም እነ ራሺያን ከመበታተን እንዳላዳናቸው በመረዳቴ፣የኢህአዴግ ፌደራሊዝም እንደማይጠቅመን ፊት ለፊት እነግራቸው ነበር፡፡ ሌላው “ዲሞክራሲያዊ ማዕከላዊነት” የሚባል ነገር አለ፤ ግለሰቦችን ፈላጭ ቆራጭ የሚያደርግ ነው፡፡ አንድ መሪ የተናገረውን ከመቀበል ውጪ ሌላ ሃሳብ ማራመድ የማይቻልበት አካሄድ ነው፡፡ በኢህአዴግ ቤት ውስጥ አማራጭ ሃሳብ ማቅረብ እንደማይፈቀድና ከነውር እንደሚቆጠር ተረዳሁኝ፡፡ እነዚህንና መሠል ጉዳዮችን በየትኛውም መድረክ ላይ በድፍረት እቃወማቸው ነበር፡፡ ጠቅላይ ሚኒስትር መለስ በነበሩበት ስብሰባ ላይም በግልጽ “ተሳስተሃል” ብዬ አውቃለሁ፡፡ አቶ መለስ “ይሄን አስተያየት እንቀበለዋለን” ያሉበት ጊዜ አለ፡፡ “ለምን እንዲህ ያለ ጥያቄ ይጠይቀኛል” ብለው የተቃወሙበት ጊዜም አለ፡፡
በኢህአዴግ ውስጥ ምን ያህል ቆየህ?
ከ2001 እስከ 2002 አጋማሽ ድረስ በኢህአዴግ ውስጥ ቆይቻለሁ፡፡ በወቅቱ ፖሊሲውን በዝርዝር ለመረዳት ችያለሁ፡፡ እነዚህን በሂደት የተረዳኋቸውንና ያላመንኩባቸውን ጉዳዮች ይዤ ዲሞክራሲያዊ ትግል ማድረግ ነበረብኝ፡፡ ኢህአዴግ ጭፍንና አምባገነናዊ አካሄድ ነው የሚከተለው፡፡ በኢህአዴግም ሆነ በተቃዋሚዎች ጐራ የተሠለፉ ጫፍ የረገጡ የ60ዎቹ ፖለቲካ አራማጆች አሉ፡፡ ይሄን ጭፍንነት ይዘው ትግሉን እየጐተቱ ያሉ ሰዎች ስፍራውን ለአዲሱ ትውልድ እንዲለቁ መሠራት አለበት የሚል ጽኑ እምነት ነበረኝ፡፡
አንድነት ውስጥ ዘመናዊ የሚባሉ፤ ለዚህች ሀገር የሚጠቅሙ ወጣቶች ወደፊት እንዲመጡ ከገባሁበት ጊዜ ጀምሮ ታግያለሁ፡፡ አማራጮች እንዲፈልቁ፣ ፓርቲው ከህዝብ ጋር የበለጠ እንዲተዋወቅ ጥረት አደርግ ነበር፡፡ ለኔ ትልቅ ስልጣን ከተባለ ከተቃዋሚ ፓርቲ ይልቅ ኢህአዴግ ቤት ውስጥ የነበረኝ ነው፡፡ ኢህአዴግ ውስጥ ባለስልጣን ሆነህ የፈለከውን በኩርኩም እየመታህ ትሄዳለህ፡፡ አንድነት ጋ ባለስልጣን ስትሆን ግን እንደዚህ እስር ቤት ነው የምትወረወረው፡፡ ይሄን ጠንቅቄ አውቅ ነበር፡፡
እኔ ውስጣቸው አባል ሆኜ ብዙ ነገር ለማስተካከል፣ በሃሳብ ለመሞገት ጥረት አድርጌያለሁ፡፡ ፈጽሞ ሃሳብ የሚስተናገድበት ሁኔታ ኢህአዴግ ቤት ውስጥ የለም፡፡ የምችለውን ሁሉ ከጣርኩ በኋላ በተአምር የሚቀየር ነገር ባለመኖሩና በሮች በሙሉ በመዘጋታቸው ከፓርቲው ወጥቼ የጥሞና ጊዜ ወሰድኩ፡፡ ከዚያ ደግሞ የባለራዕይ ወጣቶች ማህበርን መሠረትን፡፡ በወቅቱ የኢትዮጵያዊነት ስሜት እየተሸረሸረ መሆኑ ያሳስበኝ ስለነበር ማህበሩ በዚህ ረገድ አስተዋጽኦ እንዲያበረክት ነበር የመሠረትነው፡፡ የፌደራሊዝም ስርአት ለኢትዮጵያ እንደሚያስፈልጋት አምናለሁ፤ ነገር ግን አሁን ቋንቋን፣ ዘርን --- መሠረት ያደረገው ስርአት ሃገሪቱ ወደማትወጣው ችግር ውስጥ የምትገባበት እንዳይሆን እፈልጋለሁ፡፡ በኢህአዴግ አካሄድ ሀገሪቱ አደጋ ላይ ትወድቃለች የሚል እምነት ነበረኝ፡፡ ደግሞም የያዝኩት እምነት ትክክል እንደነበር አሁን እያየነው ያለው ውጤት ምስክር ነው፡፡ የልዩነቱ ድንበር መድመቅ አልነበረበትም፡፡
በ1983 ኢህአዴግ ሲገባ ይዞት የመጣው አስተሳሰብ ጊዜው በሚጠይቀው ልክ የነበረ ነው፡፡ በወቅቱ በብሔር ጥያቄ ነፍጥ ያነገቡ ከ18 ድርጅቶች በላይ ነበሩ፡፡ እነዚህን “አንዲት ኢትዮጵያ” ቢሏቸው ኖሮ አስቸጋሪ ነበር፡፡ እንደገና ጦርነቱ ይቀጥላል፡፡ ነገር ግን በየጊዜው የማህበረሰቡን እድገትና ስነልቦናዊ አንድነት እየተመለከተ፤ የነበሩትን ስጋቶችና አለመተማመኖችን እየሰበረ፣  ብሔራዊ አስተሳሰብን መገንባት ነበረበት፡፡ ቆይተው ተቃውሞው ሲበረታ ነው “የሰንደቅ አላማ ቀን” የመሳሰሉትን የጀመሩት፡፡ ኢህአዴጐች፤ “ልዩነታችን አንድነታችን፣ አንድነታችን ውበታችን” የሚሉት ነገር አላቸው፤ ግን ከልዩነታችን አንድነታችን ይበልጣል ብለን ብንይዘው፣ ሰው ውስጥ የአንድነት ሃሳብን ማሳደግ ይቻላል፡፡ በባለራዕይ ወጣቶች ማህበር ውስጥ በዚህ መልኩ ብዙ ጥረት አደረግን፤ግን ኢህአዴግ አንድ የተሰባሰበ አካል ሲያይ ይፈራል፡፡ እናም ማህበሩን እንዳይንቀሳቀስ አደረገው፣ እኛም ስንታሰር ስንፈታ ቆየንና --- በመጨረሻም ማህበሩ ተዳክሞ ተበተነ፡፡ ከዚያ በኋላ የያዝኩት አላማና አስተሳሰብ ለሀገሬ ይጠቅማል፤ ግን እንዴት ልታገል ብዬ ሳስብ አንድነት ፓርቲን አማራጭ አድርጌ መታገል ጀመርኩ፡፡ በዚህች ሀገር ከጦርነት በመለስ ያለው ትግል መኖር አለበት፡፡ አንዱ ሌላውን በሃይል የሚጥልበት አካሄድ መቆም አለበት፡፡ በሃይል የሚመጣ አካል፣ በሃይል ብቻ ነው የሚወድቀው፡፡ “ሰይፍ የሚያነሳ በሠይፍ ይሞታል” ነው የሚለው መጽሐፍ ቅዱስም፡፡ ስለዚህ ሰይፍ ማንሳት ሳያስፈልግ፣ በሠላማዊ ትግል መንግስት መቀየር አለበት የሚል ጽኑ እምነት አለኝ፡፡
የተቃዋሚ ፓርቲ አመራር ከሆንክ በኋላስ ችግሮች ቀነሱልህ?
በተቃውሞው ጐራና በኢህአዴግ መካከል ያለው ልዩነት በራሱ ለወጣቱ እጅግ በጣም ፈተና ነው፡፡ በሁለቱም ውስጥ ጫፍና ጫፍ የረገጡ ሃይሎች አሉ፡፡ ያንን መስበር እጅግ ከባድ ነው፡፡ እነዚህን አመራሮች የሠለጠነ አስተሳሰብ ባላቸው ሰዎች መቀየር አንዱ አማራጭ ነው፡፡ እኔ ኢህአዴግ ውስጥ ሃሳብ እንደልብ ማንሸራሸር አይቻልም ብዬ ወደዚኛው ስመጣ፣ “ወያኔ” በደንብ አሠልጥኖ ልኮብናል” የሚል አቋም ይዘው አላሠራም ያሉበት ሁኔታ ነበር፡፡ ይሄን ሁሉ ታግለን ፓርቲው እየተጠናከረና ለስርአቱ አደጋ እየሆነ ሲመጣ፣ኢህአዴግ “እነዚህን ከጀርባ ሆኖ የሚገፋ አለ” ብሎ ከፍተኛ ስጋት ውስጥ ገባ፡፡
እኔ ወደ ተቃውሞ ጐራ ከገባሁ በኋላ ከ20 በላይ ሠላማዊ ሠልፍ መርቻለሁ፡፡ አንዲት ጠጠር አልተወረወረችም፡፡ በሆስፒታሎች አካባቢ ስናልፍ በፍፁም ጨዋነትና ፀጥታ ነበር፡፡ ግን በመጨረሻ አሸባሪ ነው የተባልነው፡፡ በተቃውሞው ጐራ ደግሞ “ወያኔ ነው የላከብን” እየተባልኩ በመሃል ላይ በሁለት እሣት እየተጠበስኩ ነው ትግል ሳደርግ የነበረው፡፡ ሌላው በተቃውሞ ጐራ ያለው ችግር አንዳንዱ ዝም ብሎ የጡረታ ጊዜውን የሚያሣልፍበት ነው የሚመስለው፡፡ ምንም ለውጥ አያመጣም ግን ዝም ብሎ እየተቃወመ መኖርን የመረጠ ነው፡፡ ይሄ መለወጥ አለበት፤ አካሄዱ ትክክል አይደለም፡፡ ዘመናዊ ዲሞክራሲያዊ ስርአት እንገንባ ባልን ነው መከራ የምናየው፡፡ እኔም ሆንኩ አብረውኝ የታሠሩ ጓዶቼ ይሄ ነው አመለካከታችን፤ ግን ያልተገባ ዋጋ እንድንከፍል ነው እየተደረግን ያለነው፡፡ ነገ ይህቺን ሀገር ሁሉም ትቷት ይሄዳል፤ ግን ለልጅ ልጆቻቸው የማይቆጭ ነገር ትተው ቢያልፉ መልካም ነው፡፡
ወደ እስር የተወሰድክበት ሁኔታ እንዴት ነበር?
እኔና ጓደኞቼ የተያዝነው ለምርጫ 2007 ዝግጅት በሚደረግበት ወቅት ላይ ነው፡፡ ምንም ጥርጥር የለውም፤ ኢህአዴግ እኛን ደጅ ትቶ ምርጫ ማካሄድ አልፈለገም፡፡ ወደፊትም የሚፈልግ አይመስለኝም፡፡ በወቅቱ ኢህአዴግን በሃሳብ ማሸነፍ እንደሚቻል እኛ በተግባር ማሳየት እንችል እንደነበር ምንም ጥርጥር የለኝም፡፡ ሃሳብ በማንፀባረቅ ብቻ ኢህአዴግን እንበልጠዋለን፡፡ ስለዚህ ከአነሣሣችን ከኢህአዴግ በተሻለ የህዝቡን ቀልብ እንደምንገዛ፣ ሌላ አማራጭ ይዘን እንደምንቀርብ ጥርጥር አልነበረኝም፡፡
በምን አይነት ሁኔታ ነበር በቁጥጥር ስር የዋልከው?
እኔ በወቅቱ ባንክ ቤት ነበርኩኝ፡፡ የፓርቲያችንን ፕሬዚዳንት ጨምሮ 6 አመራሮች ወደ አሜሪካን ሀገር ሄደን፣ በስድስት ስቴቶች ላይ ከዳያስፖራው ጋር ለመወያየት መድረክ ተዘጋጅቶ ነበር፡፡ ለዚህም የመጨረሻውን የቪዛ ክፍያ ጨርሼ፣ የሁሉንም አመራሮች ፎርም አንድ ላይ ይዤ ለአሜሪካን ኤምባሲ 4 ሰአት ላይ ለማቅረብ ልሄድ ባልኩበት ቅጽበት ነው ከእነ ፓስፖርቱ መጥተው የያዙኝ፡፡ አያያዛቸው በጣም የሚገርም ነበር፡፡ አንድ ተራ ሰው የሚይዙ አይመስሉም፡፡ ኦሣማ ቢላደን ያለ ነበር የሚመስለው፡፡ በወቅቱ የተሰማኝ፤ “ወይኔ ታሰርኩ በቃ” የሚል አይደለም፡፡ እኛ በገዛ ሀገራችን መታሰር ችግር የለውም፤ ስንቱ እየተሰደደ የበረሃ ሲሳይ ሆኖ የለም እንዴ፡፡ ልጄ 1 አመት ከ4 ወሯ ነበር፤ ከሷና ከባለቤቴ ነጥለው ወሰዱኝ፡፡ ቤቴን ፈተሹ፤ ምንም የተገኘ ነገር አልነበረም፡፡ ማዕከላዊ ለ4 ወር ቆየሁ፡፡ እኔ ፊት ለፊት የግንባር ስጋ ሆኜ የምታገል ሰው ነኝ፡፡ ከጀርባ ሆኖ የሚታገል ሰው እኮ አደባባይ አይወጣም፡፡ ሲይዙኝ እንፈጥረዋለን ብለን ያሰብነው የመድብለ ፓርቲ ስርአት ወደ ኋላ መመለሱ አሳዝኖኝ ነበር፡፡ የማታ ማታም ያው እንደሚታወቀው ፓርቲያችን እንዲፈርስ ተደረገ፡፡
በምርጫ ቦርድ ውሣኔ የአንድነት ፓርቲ አመራር ሲለወጥ ምን ተሰማህ?
እኔ በመሠረቱ ከድርጅት (ፓርቲ) ጋር የተለየ ፍቅር የለኝም፡፡ ኢትዮጵያ ውስጥ የመጠፋፋትና የጥላቻ ፖለቲካ እንዲቆም፣ በተቻለ መጠን ለሌላው አለም ምሣሌ የሚሆን ዲሞክራሲያዊ ስርአት እንዲገነባ ነው ፍላጎቴ፡፡ ይሄን ማምጣት የሚችል ድርጅት ለመገንባት ነበር ስንጥር የነበረው፡፡ ግን አንድነት በዚህ ሁኔታ እንዲበተን ሲደረግ የፖለቲካ ስርአቱ አንዳች መደምደሚያ እየተሠራለት መሆኑ ገባኝ፡፡ አንድነት ስለተበተነና እኔ ስለታሠርኩ የኢትዮጵያ መድብለ ፓርቲ ስርአት ግንባታ አበቃለት ማለት አይደለም፡፡ በሠላማዊ ትግሉና በህዝብ ላይ ተስፋ እንደመቁረጥ አድርጌ ስለምወስደው፣ የበለጠ መስራትና ዋጋ እየከፈልን መቀጠል አለብን የሚል እምነት አለኝ፡፡
ኢህአዴግ እግር ያወጣውን ፓርቲ እግሩን ሲቆርጥ የተቃዋሚ አመራሩ ደግሞ በቀላሉ የሚወድቅ የተልፈሰፈሰ መሆኑ፤ ቁርጠኛ የሆነ ታጋይና አመራር አለመፈጠር የመሳሰሉት ክፍተቶች ነበሩ፡፡ ኢህአዴግ ኩርኩም በሰደደ ቁጥር የምንፈርስ ሆነን ነው የተገኘነው፡፡ የኢህአዴግን ኩርኩም መቋቋም የሚችል ድርጅት ለመገንባት ባለመቻላችን በራሳችን በጣም አዝኛለሁ፡፡ እውነት አብሬያቸው ስታገል የነበረው ከነማን ጋር ነው? የሚለውን ሳስብ ነበር፡፡
 የማረሚያ ቤት ቆይታህን በምን ነበር የምታሳልፈው?
መፃህፍት አነብ ነበር፡፡ አብዛኛውን ጊዜዬን ያሳለፍኩት በማንበብ ነው፡፡ ወዳጆቼ የማረሚያ ቤቱን ሳንሱር ያለፉ መፃህፍትን ያስገቡልኝ ነበር፡፡ መፃህፍቶች በአስገራሚ ሁኔታ ሳንሱር ይደረጋሉ፤በማረሚያ ቤቱ፡፡ በሀገሪቷ ታትመው የተሠራጩ መፃህፍት ሁሉ ማረሚያ ቤት ለመግባት ለምን እንደሚከለከሉ አይገባኝም፡፡
 ከዚያ ውጪ እንግዲህ ቴሌቪዥን ያለ አማራጭ እንከታተላለን፡፡ የመልካም አስተዳደር ጉዳይ ተነስቶ ጠ/ሚኒስትሩ ጭምር እንዲያ ሲናገሩ የተስፋ ጭላንጭ ታይቶኝ ነበር፤ነገር ግን ወዲያው በማረሚያ ቤቱ የሚፈፀመው ተግባር እንኳን እየተጠናከረ ሄደ፡፡ መጽሐፍቶች ላይ የሚደረገው ክልከላም ተጠናከረ፡፡ ሽብርተኛ ተብለን እንደተከሰስነው ሁሉ፣ልክ እንደ አሸባሪ ከሰው እንድንገለል ተደረግን፡፡ ይሄ ይገርመኛል፡፡ እዚያ ያለው አካል ለለውጥ ዝግጁ እንዳልሆነ ነው የተረዳሁት፡፡ ከማንበብ ውጪ የሚተርፈኝን ጊዜ እዚያ ለሚገኙ ታራሚዎች የህግ ድጋፍ አገልግሎት በነፃ እሰጥ ነበር፡፡ የክስ ማቆሚያ ንግግራቸውን ማዘጋጀት፣ መሪና መስቀለኛ ጥያቄያቸውን ማደራጀት የመሳሰሉ የህግ አገልግሎት በነፃ እሰጥ ነበር፡፡
በማረሚያ ቤት ቆይታህ የሀገሪቱን የፖለቲካ ሁኔታ በEBC ስትከታተል እንደነበር ነግረኸኛል፡፡  ምን ታዘብክ ታዲያ?
አንዱ እንግዲህ የወቅቱ የኢህአዴግ አጀንዳ የሆነው የመልካም አስተዳደር ጉዳይ ነው፡፡ በመልካም አስተዳደር ውስጥ ችግሩን የፈጠረው ሰው ችግሩን አይፈታም፡፡ እኔ እንደዚህ አይነት እምነት አለኝ፡፡ ኢህአዴግ የመልካም አስተዳደር ችግር ፈጥሯል፡፡ መልካም አስተዳደር ግን ማምጣት አልቻለም፡፡ ችግሩን ራሱ መፍታት ይችላል ወይ ስንል? ኢህአዴግ ራሱን መፈተሽ አለበት፡፡ ሙስና አለ ከተባለ ሙሰኞች አይደሉም ችግሩን የሚፈቱት፡፡ ስለዚህ መጀመሪያ ማድረግ ያለበት የችግሩን ፈጣሪዎች ለይቶ ማውጣት ነው፡፡ ከዚህ በኋላ ነው ስለ መልካም አስተዳደር ማውራት ያለበት፡፡ ጠ/ሚኒስትሩም ተስፋ ቆርጠው፤ “ከዚህ ስትወጡ ወደ የኔት ዎርኮቻችሁ ነው የምትሄዱት” ብለ
ዋል፡፡ እንግዲህ ሁሉንም ወደፊት የምናየው ይሆናል፡፡
ከአሁን በኋላ ምን አሰብክ? በፖለቲከኝነቱ ትቀጥላለህ … ?
እውነቱን ለመናገር ገና አላወቅሁም፡፡ አሁን ምንም ማለት አልችልም፡፡ ዝም ብዬ ተራ የፖለቲካ ታጋይ ሆኜ ነው የምቀጥለው? ወይስ  የሚለውን አልወሰንኩም፡፡ ገና ብዙ ማየትና ማገናዘብ አለብኝ፡፡
በመጨረሻ…ምን ትላለህ ?
 እናንተ ከእስር መልስ ሃሳቤን ሰው እንዲሠማው ስላደረጋችሁ አመሰግናለሁ፡፡
እየታሠርን ሁሌም ስንፈታ ስራችን መደሰት ቢሆንም ጓደኞቼ አብረውኝ ባለመውጣታቸው ደስታዬ ሙሉ እንዳይሆን አድርጐታል፡፡ ከዚያ በተረፈ ግን ባለቤቴ ቤተልሄም አዛናውና ልጄ ኤማንዳ ሃብታሙ፣ እህቴ ገነት አያሌውና ወንድሞቿ ከባድ ዋጋ ከፍለዋል፡፡
ጠበቃ ተማም አባቡልጉና አመሃ መኮንን ላደረጉልኝ ድጋፍና ትብብር በሙሉ አመሰግናለሁ፡፡ ከእግዚአብሔር ቀጥሎ ለመላው የኢትዮጵያ ህዝብ፣ በሀገርም በውጪም ላሉት ምስጋናዬ ይድረስ፡፡


     ኢትዮጵያና ኬንያ በሶማሊያ የተሰማራው የአፍሪካ ህብረት ጦር (አሚሶም) ከአልሻባብ ጋር የሚያደርገውን ውጊያ ለማገዝ፣ የጦር ሂሊኮፕተሮችን ሊሰጡ ነው ሲል የኬንያው ዘ ስታር ትናንት ዘገበ፡፡አሚሶም የአልሻባብ ታጣቂዎችን ለመደምሰስ በሚያደርገው ውጊያ፣ ተጨማሪ የጦር መሳሪያዎች አስፈላጊ ሆነው በመገኘታቸው፣ አገራቱ  ሄሊኮፕተሮችን ለማቅረብ መፍቀዳቸውን ዘገባው አስታውቋል፡፡ የሄሊኮፕተሮችና ብዛት ባይገለጽም፣ የሰላም አስከባሪው ወታደሮች በአየር ላይ ድጋፍ እጦት ሳቢያ የገጠሟቸውን እንቅፋቶች ለማስወገድ ያገለግላሉ መባሉን ዘገባው ገልጿል፡፡
ኡጋንዳ ለሰላም አስከባሪው አራት ሄሊኮፕተሮችን ለመስጠት ቃል ገብታ የነበረ ቢሆንም፣ ሶስቱ ሄሊኮፕተሮች በ2012 ወደ ሶማሊያ በመብረር ላይ ሳሉ ከተራራ ጋር ተጋጭተው መከስከሳቸውን ተከትሎ ሃሳቧን መቀየሯንም ዘገባው አስታውሷል፡፡
የሰላም አስከባሪ ወታደሮችን በማሰማራት እንዲሁም የጦር መሣሪያና ቁሳቁስ በማቅረብ፣ ከፍተኛ የውጭ ምንዛሬ የሚያገኙ የአፍሪካ አገራት ኢትዮጵያና ሩዋንዳ እንደሆኑ ዘኢኮኖሚስት መዘገቡ ይታወሳል፡፡