Administrator

Administrator

         በሀገሪቱ የሚታየው የእርስ በእርስ ግጭትና ህዝባዊ አመፅ ሀገር ከመበታተኑ በፊት የሃይማኖት አባቶች ተሰሚነታቸውን ተጠቅመው የሰላም ጥሪ እንዲያቀርቡ ተጠየቁ፡፡
የመግባባት አንድነትና ሰላም ማህበር (ሰላም) ባወጣው መግለጫ፤ በሌሎች ሀገራት የሚታየው የእርስ በእርስ ግጭት ያስከተለው ጉዳትና ቀውስ በአገራችን እንዳይፈጠር የሃይማኖት አባቶች የሽምግልና ሸንጎ በማቋቋም፣ በሀገሪቱ ከጫፍ እስከ ጫፍ የብሄራዊ እርቅ ጥሪ እንዲያቀርቡ ተማፅኗል፡፡
ሀገርና ዜጎች ከዚህ ቀደም እንዲህ ዓይነት ጭንቀት ውስጥ የገቡበት አጋጣሚ አለመከሰቱን የጠቆመው ማህበሩ፤ የሃይማኖት አባቶች በሀገሪቱ የሚታየው በዘር፣ በጎሣ፣ በሃይማኖትና በቀዬ የመከፋፈል አባዜ እስራትና ስደት እንዲሁም፣ ግጭትና ጦርነት መፍትሔ ይበጅለት ዘንድ እንዲተጉ ጠይቋል፡፡ በሃይማኖት አባቶች መካከል ያለው ግጭትም እልባት እንዲያገኝ ማህበሩ ተማፅኗል፡፡
ኢትዮጵያ አንፃራዊ ሰላም ሰፍኖባት መቆየቷ ባይካድም ያልተቋረጠ ግጭት እያስተናገደች ባለበት በአሁኑ ሰዓት “ፍፁም ሰላም የሰፈነባት አገር ናት” በሚል ከእውነታው መሸሽ ተገቢ አይደለም ያለው ማኅበሩ፤ “በሀገሪቱ የበቀል እርምጃ እየሰፋና እየከፋ በመምጣቱ ምክንያት ማብቂያ ወደሌለው የጥፋት ጎዳና እያመራን እንገኛለን” ብሏል፡፡
“አስከፊ የእርስ በእርስ ግጭትና ህዝባዊ አመፅ እንደሚመጣ አስቀድመን ስጋታችንን ተናግረን ነበር” ያለው ማህበሩ፤ ሆኖም ለእርቀ ሰላም ስንማፀን “በሀገሪቱ ፍፁም ሰላም ሰፍኗል” በሚል ሰሚ ጆሮ ሳናገኝ ቀርተናል ብሏል፡፡ የሃይማኖት ተቋማት በመተባበር ሀገሪቱ አሁን ከገባችበት አስጊ ሁኔታ ትወጣ ዘንድ እንዲፀልዩና የሀገር ሽማግሌዎች ሸንጎ ለማቋቋም ለሚደረገው ጥረትም እገዛ እንዲያደርጉ ማኅበሩ ጥሪውን አስተላልፏል፡፡

     በንግድ ትርኢትና የተለያዩ ገጽታዎች ባሏቸው የመዝናኛ ዝግጅቶች ለ12 ቀናት የሚካሄደው “ሚሊኒየም የገና ገጸ በረከት” ፌስቲቫልና ኤክስፖ በመጪው ሳምንት ቅዳሜ ይከፈታል፡፡ የቅዱስ ጊዮርጊስ ስፖርት ማኅበርም በቀጣዮቹ 12 ቀናት፣ የተመሠረተበትን 80ኛ ዓመት በተለያዩ ዝግጅቶች እንደሚያከብር የፌስቲቫሉ አዘጋጅ ኮሚቴ ሰብሳቢ አቶ ዳዊት ውብሸት ለአዲስ አድማስ ተናግረዋል፡፡
ፌስቲቫሉና ኤክስፖው ከበዓል ዕቃዎች ግብይት በተጨማሪ የተለያየ ፋይዳ ያላቸው አዝናኝና ቁምነገር አዘል ሁነቶች ይካሄዱበታል የተባለ ሲሆን ከነዚህም መካከል የንባብ ባህልን ለማስፋፋት በርካታ መጻሕፍት ቤቶች እንደሳተፉና “ንባብ ለሕይወት” በሚል መርሕ በርካታ መጻሕፍት በሽልማት እንደሚበረከቱ የኮሚቴው ሰብሳቢ ገልጸዋል፡፡
የአዘጋጅ ኮሚቴው ሰብሳቢ ጨምረው እንደገለፁት፤ አንጋፋው የቅዱስ ጊዮርጊስ ስፖርት ማኅበር ከኢትዮጵያ ቀይ መስቀል ማኅበር ጋር በመተባበር ከፌስቲቫሉ መክፈቻ አንስቶ እስከሚጠናቀቅበት ዕለት ድረስ የደም ልገሳ ፕሮግራም ያካሂዳል፡፡
ፌስቲቫሉ ኪነ - ጥበብን በማበረታታቱ ላይ የበለጠ ትኩረት ማድረጉን የተናገሩት አቶ ዳዊት፣ ለዚህም ሲባል በሚሊኒየም አዳራሽ ግቢ ትልቅ አርት ቪሌጅ መሠራቱን፣ ሠዓሊያን ሥራዎቻቸውን እንዲያቀርቡ ከፍተኛ ዕድል መስጠቱን ጨምረው አብራርተዋል፡፡ ከወላጆቻቸው ጋር የሚመጡ ልጆችም እየተዝናኑ የሚማሩበት የራሳቸው ቦታ ተከልሎ መዘጋጀቱም ተገልጿል፡፡
የሚድሮክ ግሩፕ በርካታ ኩባንያዎች በሚሳተፉበት በዚሁ ፌስቲቫል የሙዚቃ ኮንሰርቶች የሚካሄዱ ሲሆን ድምፃውያኑ አብነት አጎናፍር፣ ማዲንጎ አፈወርቅ፣ ጸደንያ ገ/ማርቆስ፣ ሸዋንዳኝ ሀይሉ፣ ሀመልማል አባተ፣ አለማየሁ እሸቴ፣ “የማያውቁት አገር አይናፍቅም” በሚል ዘፈኑ የሚታወቀው የጥላሁን ገሰሰ የበኩር ልጅ ምንያህል ጥላሁን ገሰሰና ከ16 ዓመታት የውጭ ቆይታ በኋላ ለመጀመሪያ ጊዜ ስራዋን የምታቀርበው ማርታ አሻጋሪ ይሳተፉበታል፡፡ የኮንሰርቱ ገቢም ለስፖርት ማህበሩ ማጠናከሪያና ለሚያሰራው ግዙፍ ስታዲየም ግንባታ እንደሚውል ተጠቁሟል፤ ፌስቲቫሉ ከተዘጋም በኋላ ማህበሩን ይበልጥ የሚያስተዋውቁ ፕሮግራሞች ዓመቱን ሙሉ እንደሚካሄዱ የኮሚቴው ሰብሳቢ አስታውቀዋል፡፡
የቅዱስ ጊዮርጊስ ስፖርት ማህበርን የ80 ዓመት ታሪክ የሚያወሳ መፅሀፍ ተዘጋጅቶ በቅርቡ እንደሚመረቅ የገለፁት ሰብሳቢው፤ የማህበሩን አጠቃላይ እንቅስቃሴ ጨምሮ በ80 ዓመት ጉዞው የተሸለማቸው ዋንጫዎችና ሜዳሊያዎች የሚታዩበት ዐውደ ርዕይም የፕሮግራሙ አካል ሆኖ እንደሚቀርብ አቶ ዳዊት ውብሸት ተናግረዋል፡፡

ባለፈው ሳምንት እትም የጨቅላ ሕጻናት ጤንነትን ለመጠበቅ ከሚደረጉ እንቅስቃሴዎች ውስጥ

በአገሪቱ ሪፈራል በመሆን የሚያገለግለውን የጥቁር አንበሳ ሆስፒታልን አሰራር ለአድማጮች ማስነበባችን ይታወሳል፡፡ ይህንን ሕክምና ለመመልከት በባህርዳር ፈለገሕይወት ሆስፒታል ቆይታ ያደረግን በመሆኑ ለዚህ እትም ከጥቁር አንበሳ ሪፈራል ሆስፒታል የጨቅላ ሕክምና ክፍል ካላጠናቀቅነው ማብራሪያ ጋር አክለነዋልና ታነቡ ዘንድ ጋብዘናችሁዋል፡፡
ከሰሀራ በታች ባሉ የአፍሪካ አገራት የሚወለዱ ሕጻናት ባደጉት አገራት ካሉት ይበልጥ 15 እጥፍ ይሞታሉ፡፡ የ2013 ዓ.ም ጥናት እንደሚያሳየውም 6.3 ሚሊዮን ያህል ህጻናት እድሜያቸው 5 አመት ሳይደርስ ሞተዋል፡፡ ከጠቅላላው ሞት ወደ 45 በመቶ የሚሆነው ሞት በቂ ምግብ ባለማግኘት መሆኑንም ጥናቶች ያረጋግጣሉ፡፡ በተለይም ገና እንደተወለዱ በጨቅላነት እድሜያቸው የሚያልፉት ሕጻናት ቁጥር በየአመቱ ወደ 3 ሚሊዮን የሚጠጋ ሲሆን ይህም በአንድ ወር እድሜያቸው ነው፡፡ በተመሳሳይም ሲወለዱም ሕይወት የሌላቸው ጨቅላዎች ቁጥር ቀላል አይደለም፡፡ ከሚሞቱት ግማሽ ያህሉ በ24 ሰአት እድሜያቸው ሲሆን ወደ 75 በመቶ የሚሆኑት ደግሞ በመጀመሪያ ሳምንታቸው ለህልፈት ይዳረጋሉ፡፡  
እናቶች በሰለጠነ የሰው ኃይልና በጤና ተቋማት በሚወልዱበት ጊዜ ግን ይህ የተገለጸው አደጋ በእጅጉ እንደሚቀንስ አያጠራጥርም፡፡ እናቶች በጤና ተቋማት ሲወልዱ ለጨቅላው ጤንነት የሚበጅ ብዙ ነገር አለ ባለሙያዎች እንደሚጠቅሱት፡፡
ልጁ እንደሚተነፍስ እና እንደማይተነፍስ ማረጋገጥ፣
ጡት መጥባት መቻል አለመቻሉን ማየት ፣
ልጁ ተገቢውን ሙቀት እንዲያገኝ እና ልጁን ከመንካት በፊት እጅን መታጠብ አስፈላጊ መሆኑ ጭምር ለእናትየውም ሆነ ለቤተሰቡ ትምህርት ይሰጣል፡፡
ቀደም ሲል የተጠቀሱትና ሌሎችም ለተወለደው ጨቅላ የሚጎዱና የሚጠቅሙ ነገሮች በደንብ ተለይተው እንዲታወቁና ልጁም በጤንነት እንዲቆይ እናቶች በጤና ተቋም እንዲወልዱ ይመከራል፡፡
ዶ/ር ባዘዘው ፈቃድ በባህርዳር በፈለገሕይወት ሆስፒታል የጽንስና ማህጸን ሕክምና እስፔሻሊስት ሲሆኑ በሆስፒታሉ የማዋለጃውንና የጨቅላ ሕጻናቱን ክፍል የሚመሩ ናቸው፡፡ እንደእሳቸው ማብራሪያ፡-
“...ሁሉም ሕጻናት መጀመሪያ እንደተወለዱ እንክብካቤ የሚደረግላቸው በጽንስና ማህጸን ሕክምና ክፍሉ ዘርፍ ውስጥ ነው፡፡ ስለዚህ ያዋለዱት የህክምና ባለሙያዎች ለተወለደው ልጅ አስፈላጊውን ክትትል ካደረጉ በሁዋላ ምናልባትም ልጁ ተጨማሪ የህክምና እርዳታ የሚያስፈልገው ከሆነ ወይንም እናቱ ብትታመም አሊያም ከማደንዘዣም ያልነቃች ከሆነ ሕጻኑን ወደ ሕጻናት ማቆያ ክፍል እንዲሄድና አስፈላጊው ክትትል እንዲደረግለት ይደረጋል፡፡”
በፈለገ ሕይወት ሆስፒታል ያለው የጨቅላ ሕጻናት መተኛ ክፍል ያለበትን ሁኔታ እንዴት ያዩታል በሚል ስለክፍሉ ሁኔታ ለቀረበላቸው ጥያቄ ዶ/ር ባዘዘው የሚከተለውን መልስ ሰጥተዋል፡፡
“...እንደሚታወቀው ሆስፒታሉ በማዋለጃው ክፍልም ሆነ በህጻናት ክፍሉ በሚሰጠው አገልግሎት በአካባቢው ብቸኛው ሆስፒታል ነው ማለት ይቻላል፡፡ ከዚህም የተነሳ የወላጆች ቁጥር መጨመር እንዲሁም ሪፈራል ሆስፒታል እንደመሆኑ ከየአካባቢው ችግር ያለባቸው እርጉዝ እናቶች ተመርጠው ወደ ሆስፒታሉ ሪፈር ስለሚባሉ ችግር ያላቸው ሕጻናት የመወለድ እድላቸውም ሰፊ     ነው፡፡ ስለዚህም ካለቀናቸው ወይንም ከክብደት በታች ሆነው የሚወለዱ እንዲሁም የተለያዩ የጤና ችግሮች ያሉባቸው ጨቅላዎች በሙሉ ለተወሰኑ ጊዜያት እንዲቆዩ ስለሚደረግ ክፍሉ     በጣም ይጠባል፡፡ ስለዚህም ወደፊት እንደመፍትሄ የተያዘው፡-
1ኛ/ የሕጻናት ሐኪሞችን ቁጥር ማበራከት፣
2ኛ/ የህክምና ክፍሉን ሰፋ ማድረግ፣
ዋነኛው የትኩረት አቅጣጫ ሲሆን በተጨማሪም ሕጻናት ካለቀን መወለድ ወይንም የክብደት ማነስ እንዲሁም ሌሎች ችግሮች ቢገጥሙዋቸው በተገቢው መንገድ በተሟላ ሁኔታ ሕክምናውን ለመስጠት አስፈላጊ የህክምና መሳሪያዎች ግዢ በመፈጸም ላይ ነው፡፡
አሁን ባለንበት ሁኔታ ግን ክፍሉ ሰፋ ያለ ችግር የሚታይበት ነው፡፡ የክፍል ጥበት የሰው ኃል እጥረት እንዲሁም የማቴሪያል እጥረት ያለበት ነው፡፡”
በእርግጥ በባህርዳር ፈለገ ሕይወት ሆስፒታል የተመለከትነውና ዶ/ር ባዘዘውም የመሰከሩለት የክፍል ጥበትና የሕክምና አሰጣጥ አለመሟላት በዚያ የሚቀር ሳይሆን በአዲስ አበባ ጥቁር አንበሳ ሆስፒታልም የሚስተዋሉ አንዳንድ ችግሮች አሉ፡፡
ዶ/ር አስራት ደምጸ በጥቁር አንበሳ ሪፈራል ሆስፒታል የህጻናት ሐኪምና ኒዎናታሎጂስት ለሕጻናቱ በሚሰጠው እንክብካቤ ጉድለት ነው ያሉትን እንደሚከተለው አብራርተዋል፡፡  
“...የጥቁር አንበሳ ሸክም ከባድ ነው፡፡ አልጋ የለምና ይዛችሁ ወደሌላጋ ሂዱ የማይባልበት ነው፡፡     መጀመሪያውኑም የሚመጡት የተሻለ ሕክምና ፈልገው ስለሆነ ወደሌላ ሂዱ አይባሉም፡፡     ምናልባት እንኩዋን ቀለል ያለ ነው ሂዱ ቢባልም ታካሚዎችም እሺ አይሉም፡፡ አልተለመደም፡፡ ስለዚህም ጨቅላዎቹ ምናልባት አልጋ እንኩዋን ቢያጡ በአንድ አልጋ ላይ እስከ ሁለት ልጅ የምናስተኛበት ሁኔታ ነው ያለው፡፡ የነርስ አገልግሎቱን በሚመለከትም ያለው ነርስና ታካሚ     ጨቅላ ቁጥር ተመጣጣኝ አይደለም፡፡ አንዲት ነርስ ለስምንት እና አስር ልጅ ነው አገልግሎት የምትሰጥበት ሁኔታ ነው ያለው፡፡ አንድ ነርስ ለአምስት ወይንም ለሶስት ቢሆን ጥሩ ነበር ነገር     ግን ያ ስላልሆነ ከባድ ነው፡፡”
ሌላው ነገር የእናቶች መኝታ ጉዳይ ነው፡፡ በአዲስ አበባ በጥቁር አንበሳ ሆስፒታል የጨቅላ ሕክምና ክፍል እናቶችን በሚመለከት የታዘብነው ነገር ጨቅላው ሙቀት ፈልጎ ወይንም ክብደቱ እስኪሟላ አሊያም ለኦፕራሲዮን... ወዘተ እንዲተኛ ሲደረግ እናቶቹ ግን መተኛ አልጋ የላቸውም፡፡
“...ወርቄ እባላለሁ፡፡ ልጄን በወለድኩ በሁለተኛ ቀኔ ነው ከሆስፒታል የገባሁት፡፡ ከወንበሬ ላይ እያንቀላፋሁ... ልጄ ጡት ስትጠባ እያጠባሁ አሁን ሶስት ቀን ሆኖኛል፡፡ ልጅትዋ  ሙቀት ስለሚያስፈልጋት ይበቃታል እስክትባል ድረስ የምቆየው በዚሁ ሁኔታ መሆኑ ነው የተነገረኝ፡፡ በወንበር ላይ፡፡”
በባህርዳር ፈለገ ሕይወት ሆስፒታልም የተመለከትነው ነገር እናቶቹ አልጋ እንደሌላቸውና ነገር ግን ባለው ክፍት ቦታ ሁሉ ...ማለትም በየኮሪዶሩ የእስፖንጅ ፍራሽ ዘርግተው መተኛት እንደሚችሉ ነው፡፡ ይህ ድርጊት በተጨማሪነት በክፍሉ ላይ የመጣበብ ነገር ቢኖረውም ግን ከወለደች ገና በቀናት እድሜ ያለች ሴት ከወንበር ላይ ውላ ከምታድር ይሻላል ይላሉ ዶ/ር ባዛዘው፡፡
“...እናቶቹ ከዚህ እንዲቆዩ መደረጋቸው የሚመጡበት አካባቢ በአብዛኛው እራቅ ያለ በመሆኑም ጭምር ነው፡፡ ለሕጻናቱ ጡት ቢያስፈልግ ወይንም አንዳንድ የሚፈለግ ነገር ቢኖር እርቀው ከሄዱ ለማግኘት አስቸጋሪ ስለሚሆን እንደምንም ተጣበን ለእግር መተላለፊያ እስኪጠፋ ድረስ ኮሪደሩ ሁሉ በፍራሽ ተጣቦ ይታያል፡፡ ይህ እንግዲህ ትክክለኛው አሰራር ስላይደለ ወደፊት በሚሰሩ የማስፋፊያ ስራዎች ለእነዚህ እናቶችም ማረፊያ ይኖረናል ብለን እንገምታለን፡፡”
ሌላው በጥቁር አንበሳ ሪፈራል ሆስፒታል ያየነው ችግር የመጸዳጃ አገልግሎት ጉዳይ ነው፡፡ አንዲት እናት በወለደችበት ወቅት ለተወሰነ ጊዜ የተሟላ እና የተመቻቸ የመጸዳጃ አገልግሎት ማግኘት አለባት፡፡ ምናልባት እንደኑሮው ደረጃ ቢለያይም ነገር ግን ማንኛዋም እናት በቂ ውሀ ኖሮአት በብረት ምጣድ ላይም ይሁን በሻወር መልክ እየታጠበች ለልጅዋም ይሁን ለእራስዋ ጤና ጥንቃቄ ማድረግ ይጠበቅባታል፡፡ በጥቁር አንበሳ ያየነው ነገር ግን ከዚህ ይለያል፡፡ ዶ/ር አስራት ደምጸ የሚከተለውን አስተያየት ሰጥተዋል፡፡
“...ሆስፒታሉ ብዙ ተገልጋይ ያለውን ከተሰራም ረዥም ጊዜ የሆነው ነው፡፡ ከዚህም የተነሳ ይመስላል የመታጠቢያ ቤቱ ቶሎ የሚበላሽ ሲሆን አሰራሩንም ስንመለከት ለዚያ ሁሉ እናት አንድ መጸዳጃ ቤት ያለበት ሁኔታ ነው፡፡ እውነቱን ለመናገር ንጽህናቸውን በአግባቡ እየጠበቁ ነው ለማለት ያስቸግራል፡፡ ወደጨቅላ ሕጻናቱ መግቢያ ላይ ግን የእጅ     መታጠቢያና ሳሙና ስላዘጋጀን ማንኛውም ሰው ሲገባ እንዲታጠብ ይደረጋል፡፡ እሱም ቢሆን ደግሞ አብዛኛውን ጊዜ ውሀ  የለውም፡፡ ስለሆነም በበርሜል ውሀ አዘጋጅተን     ተግባራዊ እንዲሆን እያደረግን ነው፡፡ እናቶችም እጆቻቸውን ሳይታጠቡ ልጃቸውን አይነኩም፡፡ አሁን ሆስፒታሉ በእድሳት ላይ ያለ ስለሆነ ይሄ ችግር ከግንዛቤ ገብቶ  ለእናቶች ምቹ የሆን  መጸዳጃዎች መታጠቢያ ቤቶች ቢሰሩልን በዚሁ ጥሩ ይሆናል፡፡

Saturday, 19 December 2015 09:46

የዘላለም ጥግ

(ስለ ሰላም)

• መጀመሪያ ከራስህ ጋር ሰላም ፍጠር፤
ከዚያ በኋላ ለሌሎች ሰላምን ማምጣት
ትችላለህ፡፡
ቶማስ ኤ ኬምፒስ
• ዓይን ላጠፋ ዓይኑን ማጥፋት የሚለው ህግ
መጨረሻው መላውን ዓለም ዓይነስውር
ማድረግ ነው፡፡
ማሃትማ ጋንዲ
• ሰላም በሃይል ሊጠበቅ አ ይችልም፤ ሰላም
ሊሰፍን የሚችለው በመግባባት ብቻ ነው፡፡
አልበርት አነስታይን
• ሰላም የግጭት አለመኖር አይደለም፤
ግጭትን በሰላማዊ መንገድ የመፍታት
አቅም ነው፡፡
ሮናልድ ሬገን
• በሰላም አምናለሁ፤ በይቅርባይነት
አምናለሁ፡፡
ማላላ ዩሳፍዛይ
• ከራሷ ጋር ሰላም የፈጠረች አፍሪካን
አልማለሁ፡፡
ኔልሰን ማንዴላ
• ሁላችንም በሰላም እንኖር ዘንድ ሁላችንም
ሰላምን መፍጠር አለብን፡፡
ዣን በርትራንድ አሪስቲዴ
• መላዕክት የሚዘምሩት የመጀመሪያ ነገር
ሰላምን ነው፡፡
ጆን ኬብሌ
• የሰው ልጅ ማስታወስ ያለበት ሰላም
እግዚአብሔር ለፍጡራኑ የሚያበረክተው
ስጦታ አለመሆኑን ነው፤ ሰላም አንዳችን
ለሌላችን የምናበረክተው ስጦታ ነው፡፡
ኢሊ ዊስል
• ሰላምና ፍትህ የአንድ ሳንቲም ሁለት
ገጽታዎች ናቸው፡፡
ድዋይት ዲ. ኢዘንሃወር
• ጦርነትን ማወጅ የለብንም ማለት ብቻ
በቂ አይደለም፤ ሰላምን መውደድና
መስዋዕትነት መክፈልም ይናርብናል፡፡
ማርቲን ሉተር ኪንግ
• ሰላምን እናፈቅራለን፤ ነገር ግን በማንኛውም
ዋጋ የተገኘ ሰላምን አይደለም፡፡
ዳግላስ ዊሊያም ዴሮልድ
• ተስፋ ልክ እንደ ሰላም ነው።
ከእግዚአብሔር የሚበረክትልን
ስጦታ አይደለም፡፡ አንዳችን ለሌላችን
የምናበረክተው ስጦታ ነው፡፡
ኢሊ ዊስል
• ከጦርነት አውድማ ወደ ሰላም ጠረጴዛ
ለመድረስ ረዥም መንገድ ተጉዣለሁ፡፡
ሞሼ ዳያን

  የአይሲሱ መሪ አቡበከር አል ባግዳዲ ሁለተኛ ደረጃን ይዘዋል
    በአለማችን በየአመቱ ስማቸው በክፉም ሆነ በደግ በስፋት የተነሳና አነጋጋሪ የሆኑ ግለሰቦችን እየመረጠ ይፋ የሚያደርገው ታዋቂው ታይም መጽሄት፣ የጀርመን መራሄ መንግስት አንጌላ መርኬልን የ2015 የታይም መጽሄት የዓለማችን ተጽዕኖ ፈጣሪ በማለት መምረጡን አስታወቀ፡፡
ታይም መጽሄት ረቡዕ ዕለት በድረ-ገጹ ይፋ ባደረገው መረጃ እንዳስታወቀው፣ ለዘንድሮው የታይም መጽሄት የአመቱ ምርጥ ሰው ምርጫ የመጨረሻ ዙር ከደረሱት ስምንት ዕጩዎች መካከል የመጽሄቱን አዘጋጆች አብላጫ ድጋፍ ያገኙት አንጌላ መርኬል አሸናፊ በመሆን ተመርጠዋል፡፡
ባለፉት 29 አመታት የታይም መጽሄት የአመቱ ምርጥ ለመባል የበቁት ብቸኛዋ ሴት የሆኑት አንጌላ መርኬል በዘንድሮው አመት በዩሮዞን ከተከሰተው የኢኮኖሚና የስደተኞች ቀውስ ጋር በተያያዘ ሰፊ የመገኛኛ ብዙሃን ሽፋን ያገኙ መሪ ሆነው መዝለቃቸው ለመመረጥ እንዳበቃቸው ተነግሯል፡፡
በዕጩነት ከቀረቡት ግለሰቦች መካከል አለማችንን በሽብር ተግባሩ እያመሳት የሚገኘው የአሸባሪው ቡድን አይሲስ መሪ አቡበከር አል ባግዳዲ ሁለተኛውን ደረጃ ሲይዙ፣ አነጋጋሪው የአሜሪካ ፕሬዚዳንታዊ ምርጫ የሪፐብሊካን ፓርቲ ዕጩ ዶናልድ ትራምፕ ሶስተኛ ደረጃን ይዘዋል ተብሏል፡፡
የኢራኑ ፕሬዚዳንት ሃሰን ሩሃኒ፣ እንዲሁም አይሲስ የተባለውን የሽብር ቡድን አጠፋለሁ ብለው ጦራቸውን ያዘመቱት የሩስያው ፕሬዚዳንት ቭላድሚር ፑቲንም በእጩነት ቀርበው ነበር፡፡
ባለፈው አመት የታይም መጽሄት ምርጥ ተብለው የተመረጡት በምዕራብ አፍሪካ አገራት የተከሰተውን የኢቦላ ቫይረስ በቁጥጥር ስር ለማዋል ያላሰለሰ ጥረት ያደረጉ ባለሙያዎች እንደነበሩ ያስታወሰው መጽሄቱ፣ በ2013 ደግሞ የሮማው ሊቃነ ጳጳስ ፖፕ ፍራንሲስ ተመርጠው እንደነበር አክሎ ገልጧል፡፡
ታይም መጽሄት የአመቱ ምርጦቹን መምረጥ የጀመረው እ.ኤ.አ በ1927 ሲሆን በወቅቱ የተመረጡትም ቻርለስ ሊንድበርግ የተባሉ አውሮፕላን አብራሪ እንደነበሩ መጽሄቱ አስታውሷል።
ግርማዊ ቀዳማዊ ኃይለ ስላሴ፣ ማህታማ ጋንዲ፣ አዶልፍ ሂትለርና ኦባማን የመሳሰሉ የአገር መሪዎች፣ ፖለቲከኞችና ታዋቂ ግለሰቦች ከዚህ ቀደም የታይም መጽሄት የአመቱ ምርጦች መካከል የሚጠቀሱ ናቸው፡፡

 - ማሻሻያው ድጋፍ ካገኘ፣ ካጋሜ ለመጪዎቹ 19 አመታት በስልጣን ላይ ሊቆዩ ይችላሉ
    የሩዋንዳው ፕሬዚዳንት ፖል ካጋሜ በ2017 በሚካሄደው የአገሪቱ ፕሬዚዳንታዊ ምርጫ ላይ እንዲሳተፉ ለማስቻል ታስቦ በህገ መንግስቱ ላይ የተደረገውን ረቂቅ ማሻሻያ በተመለከተ በመጪው ሳምንት ህዝበ ውሳኔ እንደሚደረግ ቢቢሲ ዘገበ፡፡
በህገ መንግስቱ ላይ ሊደረግ የታሰበው ማሻሻያ በህዝበ ውሳኔው አብላጫ ድጋፍ ካገኘ፣ ፕሬዚዳንት ፖል ካጋሜ እስከ 2034 ድረስ በስልጣን ላይ መቆየት የሚችሉበት ዕድል ይፈጠርላቸዋል ያለው ዘገባው፣ የአገሪቱ ሴኔትም ፕሬዚዳንቱን በስልጣን ላይ ለማቆየት ታስቦ የተዘጋጀውን የህገ መንግስት ማሻሻያ ባለፈው ወር እንደተቀበለው አስታውሷል፡፡
አሜሪካ በ2017 የስልጣን ዘመናቸው ለሚያበቃው ለሩዋንዳው ፕሬዚዳንት ፖል ካጋሜ፣ #እባክዎት በሰላም ስልጣንዎን ይልቀቁና ለአካባቢው አገራት መንግስታት አርአያ ይሁኑ” ስትል ጥሪዋን ብታስተላልፍም፣ ካጋሜ ግን የአሜሪካንም ሆነ የሌሎች አገራትን መሰል ጥያቄ፣ በምስራቅ አፍሪካ አገራት የውስጥ ጉዳዮች ላይ የሚደረግ ጣልቃ ገብነት ነው ሲሉ ማጣጣላቸውን ዘገባው አስታውሷል፡፡
አጃንስ ፍራስ ፕሬስ በበኩሉ÷ የህገ መንግስት ማሻሻያው በመጪው ሳምንት በሚደረገው ህዝበ ውሳኔ ድጋፍ አግኝቶ የመጽደቅ ዕድሉ ከፍተኛ ነው ሲል ዘግቧል፡፡

ለ700 ጊዜያት ያህል ታጥቦ፣ አገልግሎቱን አላቋረጠም
    ኪዮሴራ የተባለው የጃፓን የሞባይል አምራች ኩባንያ በአለማችን የስማርት ፎን ታሪክ በአይነቱ የመጀመሪያው የሆነውን በውሃና በሳሙና መታጠብ የሚችል ዲንጎ ራፍሪ የተሰኘ አዲስ የሞባይል ቀፎ አምርቶ ትናንት በገበያ ላይ ማዋሉን ሪያሊቲ ቱዴይ ድረገጽ ዘገበ፡፡ ምንም እንኳን ሶኒ ኩባንያን የመሳሰሉ የሞባይል አምራቾች ከዚህ ቀደም ውሃን መቋቋም የሚችሉ ሞባይል ስልኮችን ቢያመርቱም፣ ሞባይሎቹ ሳሙና ከነካቸው የሚበላሹ ነበሩ ያለው ዘገባው፣ ኪዮሴራ ያመረተው አዲስ ሞባይል ግን የሳሙና አረፋ ውስጥ ተዘፍዝፎ ቢውል አይበላሽም ብሏል፡፡
“ይህንን በአይነቱ ልዩ የሆነ ሞባይል ስልክ ያመረቱት የኩባንያችን ተመራማሪዎች፣ የስልኩን ብቃት ለማረጋገጥ ከ700 ጊዜያት በላይ ያጠቡት ሲሆን አንዳችም ችግር ሳይፈጠርበት አገልግሎት መስጠት መቀጠሉን አረጋግጠዋል” ብለዋል የኩባንያው ቃል አቀባይ፡፡ 465 ዶላር የተተመነለት ይህ የሞባይል ስልክ፣ በተለይም ልጆች ለሚበዙባቸው ቤተሰቦች ታልሞ የተመረተ እንደሆነ የጠቆመው ዘገባው፣ ሞባይሉ ውሃና የሳሙና አረፋን መቋቋም የሚችል ሽፋን ያለው መሆኑንና፣ ስፒከሮቹን ጨምሮ የተገጠሙለት አካላት በሙሉ በፈሳሽ የማይበላሹ መሆናቸውን ዘገባው ገልጧል፡፡

 ፔኔዛ በተባለችው የሩስያ ከተማ የሚንቀሳቀሰው ኮሙኒስት ፓርቲ፤ አምባገነኑን የቀድሞው የሩስያ መሪ ጆሴፍ ስታሊንን ለመዘከርና ብዙዎች እንደሚሉት ሰውዬው አምባገነን መሪ አለመሆናቸውን የሚያሳዩ ጥናቶች የሚሰሩበት የጥናት ማዕከል በስማቸው ለመክፈት ማቀዱን አስታወቀ፡፡
ፓርቲው 2016ን የስታሊን አመት በሚል ለማክበር ማቀዱን እንዳስታወቀ የዘገበው ቢቢሲ፣ አመቱን ሙሉ የሚከናወኑ የተለያዩ ስታሊንን የሚዘክሩ ዝግጅቶችን ለማሳካት እየተንቀሳቀሱ እንደሚገኙና በስታሊን ስም ሊቋቋም የታሰበው የጥናት ማዕከልም ሰውዬውን በአምባገነንነት በመወንጀል ያለ አግባብ ስማቸውን የሚያጠፉ አካላትን ፕሮፓጋንዳ የሚያከሽፉ ፊልሞች እንደሚታዩበት የፓርቲው ሃላፊ ጂኦርጂ ካሜኔቭ መናገራቸውን ገልጧል፡፡
የስታሊን አመት ክብረ በዓል ከሁለት ሳምንታት በፊት በሚከፈት የፎቶ ግራፍ ኢግዚቢሽንና የስታሊን የልደት በዓል ስነስርአት የሚጀመር እንደሆነ የጠቆመው ዘገባው፣ በመጋቢት ወር መጀመሪያም ስታሊን የሞተበት ዕለት በተለያዩ ዝግጅቶች እንደሚከበር አስታውቋል፡፡
መጪው የፈረንጆች አዲስ አመት የስታሊን ህገ መንግስት በመባል የሚታወቀው የሩስያ ህገ መንግስት የጸደቀበት 80ኛ አመት መሆኑን ያስታወሰው ዘገባው፣ ኮሙኒስት ፓርቲውም በስታሊን ታላቅነት ዙሪያ ምርምር ለሚያደርጉ ወጣት ተመራማሪዎች የገንዘብ ድጋፍ ለማድረግ ማቀዱን አመልክቷል፡፡

     በሪል ኢስቴትና በኮንስትራክሽን ግብአቶች ላይ ያተኮረ ዓለም አቀፍ ኤግዚቢሽን ለሦስት ቀናት ሊካሄድ ነው፡፡
አጀት ፕሮሞሽን ከመከር ሪል ስቴት ጋር በመተባበር ያዘጋጀውና Home up የተሰኘው ይኸው ኤግዚቢሽን፣ በኮንስትራክሽኑ ዘርፍ የተሰማሩ አካላትን እርስ በርስ ለማገናኘትና የገበያ ትስስርን እንዲፈጥሩ ለማድረግ ከማስቻሉም በላይ ልምድና ተሞክሮአቸውን እንዲለዋወጡ እንዲሁም ከአዳዲስ ቴክኖሎጂዎች ጋር እንዲተዋወቁ በማድረግ በከተሞች ውስጥ የሚታየውን የመኖሪያ ቤት ችግር ለመቅረፍ ጥረግ በማድረግ ላይ የሚገኙትን የዘርፉን አካላት እንደሚያግዝ ተገልጿል፡፡
በሀርመኒ ሆቴል በተዘጋጀ ጋዜጣዊ መግለጫ ላይ ኤግዚቢሽኑ የግሉን ዘርፍ ከመንግስት አካላት ጋር በማገናኘትና በማወያየት በዘርፉ የሚታዩ ችግሮችን ለማስወገድ እንደሚረዳ የጠቆሙት የአጀት ፕሮሞሽን ዋና ሥራ አስኪያጅ ወ/ሪት ኤልሳቤጥ አድነው፣ ከዚህ በተጨማሪም በኮንስትራክሽኑ ዘርፍ እየታየ ያለውን የመረጃ ክፍተት በመሙላት ኢንዱስትሪው አድጎ ዓለም አቀፍ ተወዳዳሪ እንዲሆን ያግዛል ብለዋል፡፡
በኤግዚቢሽኑ የአገር ውስጥና የውጭ አገር የሪል ኢስቴት አልሚዎች፣ የኪንስትራክሽን ግብዓት አቅራቢዎች፣ ፈርኒቸር አምራቾችና የፋይናንስ ተቋማት ተሳታፊ እንደሚሆኑም ተገልጿል፡፡ 

    በቴዎድሮስ በየነ የተዘጋጀው “ህብረ ኢትዮጵያ” የተሰኘ የጠቅላላ እውቀት መፅሀፍ ሰሞኑን በገበያ ላይ ዋለ፡፡ መጽሐፉ ስለኢትዮጵያ ታሪክ፣ ባህል፣ ስፖርት፣ ቱሪዝምና በአጠቃላይ ከ20ሺህ በላይ መረጃዎችን ያከተተ ሲሆን በየትኛውም የእውቀት ደረጃ ላይ ለሚገኝ፣ ማንኛውም አይነት ሰው፣ ያሻውን መረጃ ለማግኘት እንደሚረዳ ተገልጿል፡፡ በ328 ገፆች ተቀንብቦ የተሰናዳው ይህ መጽሐፍ፤ በ69 ብር ለገበያ ቀርቧል፡፡