Administrator

Administrator

 ከዕለታት አንድ ቀን አንድ የሜዳ ቴኒስ ተጫዋች ክንዱ ላይ ክርኑን በጣም ያመውና ለጓደኛው “.ምን ባደርግ ይሻለኛል?..” ይልና ይጠይቀዋል፡፡ ጓደኛውም “..አንድ ዋሻ ውስጥ የሚኖር አዋቂ ሰው አለ፡፡ እሱ ጋ ሄደህ ችግርህን ብታስረዳው መፍትሔ ይፈልግልሃል..” አለው፡፡
“ስንት ያስከፍለኛል?”
“አስር ብር ብቻ፡፡”
“ምን ምን ዓይነት ምርመራ ያደርግልኛል?” ሲል ጠየቀ ታማሚው፡፡
“የሽንት ምርመራ ብቻ ነው የሚያደርግልህ፡፡ ዋሻው በራፍ ላይ በዕቃ ሽንትህን ታስቀምጣለህ፡፡ እሱ ይደግምበታል፡፡ ይመሰጥበታል፡፡ ከዚያ መድኃኒቱን ይነግርሃል፡፡ አለቀ፡፡”
ታማሚው ጓደኛው እንዳለው ዋሻው ደጃፍ ላይ ሽንቱን በዕቃ ያኖርና አብሮ አስር ብር ያስቀምጣል፡፡
በሚቀጥለው ቀን ወደ ዋሻው ደጃፍ ሲሄድ አንድ ማስታወሻ ተጽፎለት ያገኛል፡፡ እንዲህ
.. በሜዳ ቴኒስ ጨዋታ ምክንያት ክንድህ ላይ ክርንህን ተጎድተሃል፡፡ ስለዚህ ክንድህን ለብ ያለ ውኃ ውስጥ ከተህ ታቆየዋለህ፡፡ ከባድ ዕቃ አታንሳ፡፡ በሁለት ሳምንት ውስጥ ይሻልሃል ..
ታማሚው ማታ ቤቱ ገብቶ ነገሩን ሲያስበው፤ “የገዛ ጓደኛዬ ቢሆንስ ማስታወሻውን የጻፈው? ከዚያ አስር ብሬን ወስዶ አታሎኝ ቢሆንስ?” ደጋግሞ አሰበበትና በሚቀጥለው ቀን ወደ ዋሻው ደጃፍ ይሄዳል፡፡ አሁን ግን የራሱን የሽንት ዕቃ ሳይሆን የሚስቱንና የወንድ ልጁን የሽንት ምርመራ ናሙና፣ የውሻውን ፀጉርና የቧምቧ ውሃ ደባልቆ፤ በአንድ ዕቃ ዋሻው ደጃፍ ላይ ከአስር ብር ጋር ያስቀምጣል፡፡
ከዚያም ወደ ጓደኛው ይሄድና እንደገና ወደ ዋሻው ደጃፍ ሄዶ፣ የሽንት ናሙና በትልቅ ብልቃጥ እንዳስቀመጠ ይነግረዋል፡፡ ጓደኛውም፤ “አሁን ደግሞ ለምን አስቀመጥክ?”. ብሎ ይጠይቀዋል፡፡
“ጤንነት አይሰማኝምና እንዳለፈው ጊዜ መፍትሔ እንዲሰጠኝ ፈልጌ ነው” ይለዋል፡፡ ጓደኝዬውም፤ “ጥሩ፡፡ እንግዲያው ነገ ሄደህ የምርመራውን መልስ ካወቅህ በኋላ እናወራለን..” ብሎት ይለያያሉ፡፡
በነጋታው ታማሚው ሰው ወደ ዋሻው ደጃፍ ሲሄድ እንደጠበቀው ሌላ ማስታወሻ ያገኛል፡፡ እንዲህ የሚል ጽሑፍ ፡- .. “የቧምቧህ ውሃ በጣም ወፍራምና ከባድ ነው፡፡ ስለዚህ የሚያቀጥነውና የሚያሳሳው ኬሚካል ግዛ፡፡
ውሻህ የሚያሳክክ ቅንቅን አለበት፡፡ ስለዚህ ቪታሚን ገዝተህ ስጠው፡፡ ወንድ ልጅህ የአደንዛዥ ዕጽ ተጠቂ ሆኗል፡፡ ስለዚህ ከዚህ አባዜ እንዲላቀቅ ወደ ማገገሚያ ማዕከል ወስደህ ለተወሰነ ጊዜ እዚያ እንዲቆይ አድርገው፡፡ ሚስትህ አርግዛለች፡፡ ያውም መንታ ልጆች ነው ያረገዘችው፡፡ ልጆቹ ግን ያንተ አይደሉም፡፡ ስለዚህ ጠበቃ ግዛ፡፡ እንዲህ ስትጠራጠርና በራስህ ስትቀልድ የክርንህ ህመም እየባሰብህ ነው የሚሄደው፡”
*    *    *
በአጠራጣሪ ሁኔታ ውስጥ መኖርና ኮስተር ብሎ ጉዳይን አለመጨበጥ ሌላ ጉድ ያሰማል፡፡ ..አሳ ጎርጓሪ ዘንዶ ያወጣል.. እንዲሉ፡፡
በአጠራጣሪ ዓለም እየኖርን ዕቅዶች ስናወጣ፣ ዕቅዶችም አጠራጣሪ ይሆናሉ፡፡ ለዚያውም ነገን በማናውቅበት ዓለም፡፡ ውዲ አለን የተባለው ኮሜዲያን “..ሰው ሲያቅድ እግዚሃር ይስቃል..” (when man plans God laughs እንዲል) ታዋቂው ሳይንቲስት አልበርት አነስታይን ደግሞ “በተጨባጭ ዓለም ውስጥ እየኖረ ..ዕውነትና ዕውቀት ላይ ፍርድ ሰጪ ዳኛ ነኝ የሚል ሰው፤ መርከቡ፤ አማልክቱ ሲስቁ ትንኮታኮታለች.”. ይለናል፡፡ ማንም ፍፁም ነኝ አይበል ነው ነገሩ፡፡ በገዢና በተገዢ መካከል ያለው ግንኙነት ፍፁምና ንፁህ ስምምነትና መተማመን መሆን አለበት ብሎ ግትር ማለት ቢያዳግትም፣ በመተማመን ላይ የተመሠረተ ሊሆን ይገባዋል፡፡ በተለይ ..እናቱ የሞተችበትም፣ እናቱ ወንዝ የወረደችበትም እኩል የሚያለቅስበት አገር.. ከሆነ አለመተማመንና መጠራጠር የታከለበት እንደሆነ በቡሃ ላይ ቆረቆር ይሆናል፡፡ ከዚህ ይሰውረን፡፡
ቲ ኤስ ኢሊየት ያለንን አለመርሳት ነው ፡- Oh my soul…be prepared for him Who knows how to ask questions ..ነብሴ ሆይ  ተዘጋጂ አደራ አውጪኝ ከዛ ጣጣ  ጥያቄ መጠየቅ የሚችል ሲመጣ.. እንደማለት ነው፡፡)
ዛሬ በሀገራችን ስለተጠያቂነት ብዙ ይነገራል፡፡ ከዚህ ተነጣጥሎ የማይታይ ግን ቸል የተባለው ጉዳይ  ..ጠያቂውስ ማነው?.. የሚለው ነው፡፡ ታሪክ፣ ጊዜና ህዝብ ናቸው ቢባል መልሱን ይጠቀልለዋል፡፡ እንጠየቃለን ብለ አለመስጋት ማናለብኝን ያስከትላል፡፡ ማናለብኝ ደሞ ኢ - ዲሞክራሲያዊና ኢ- ፍትሐዊ ነው፡፡
ጥርጣሬ አገር ጐጂ እክል ነው፡፡ እርስ በርስ አለመተማመንና ኑሮን አለማመን ያስከትላልና፡፡ ፖለቲካዊም ኢኮኖሚያዊም መረጋጋትን ያጫጫል፡፡ የሩሲያው መሪ ጆሴፍ ስታሊን፤ የጥርጣሬ መናኸሪያ ነበር ይባላል። ሁሉንም ሰው ሌባና አጭበርባሪ፤ ሁሉንም ሰው ክፉና መጥፎ አድርጐ የማየት ባህሪ ነበረው፡፡ ሁሉን በመጥፎ ስለሚፈርድም ራሱን ጥሩ አድርጐ ይደመድማል፡፡ መጥፎዎቹ ሁሉ በእኔ ላይ ይነሳሉ የሚል ጥርጣሬ ይወርረዋል፡፡ ስለዚህም ብዙ ሰው ላይ ግፍ እንዲፈጽም ይገደዳል፡፡ ፀረ - ዲሞክራሲ ተግባራቱ በይፋ ታይተዋል፡፡ ሩሲያ ለሆነችው ሁሉ ትልቅ አሉታዊ አስተዋጽኦ አድርጓል፡፡ ከዚህም ይሰውረን፡፡
አንድ ፀሐፊ እንዳለው፤  ..ዕድገት ማለት ለውጥ ማለት ነው፡፡ ለውጥ ቢያዋጣም ባያዋጣም ደፍሮ መግባትን ይጠይቃል፡፡ ይህም ማለት ከሚታወቀው በመነሳት ወደማይታወቀው ዕመር ብሎ እንደመግባት ነው.. ለውጥ ለማምጣት አያሌ ፖለቲካዊ፣ ኢኮኖሚያዊና ማህበራዊ መስዋዕቶችን ይጠይቃል፡፡ ለዚህ ነው ለውጥ በተግባር እንጂ በአፍ አይገባም፤ የሚባለው፡፡ በተጨባጭ ከየት ተነስተን የት ደርሰናል? የሚል ጥያቄ መነሳት አለበት፡፡ የትምህርት ጉዳይ፣ የጤና ጉዳይ፣ የፍትህ ጉዳይ፣ የግንባታ ጉዳይ፣ የንግድና የግብር ጉዳይ፣ የዚህ ሁሉ ድምር የኑሮ ጉዳይ የት ደርሷል መባል አለበት፡፡
ጭቦ አትናገሩ ይላሉ አበው፡፡ ነገ በራሳችሁ ይደርስባችኋል ለማለት ነው፡፡
የሌለውን አለ፣ ያላደገውን አድጓል፣ የደረቀውን አልደረቀም በማለት ልንከላከለው ብንሞክር ..ሆድን በጐመን ቢደልሉት ጉልበት በዳገት ይለግማል.. ነው ውጤቱ፡፡ የዕውነቱ ለት ማነከሳችን ይታያልና። በሀገራችን በተደጋጋሚ የምናየው ሌላው አባዜ ተቻችሎ አለመኖር ነው፡፡ አለመቻቻልን ለመሸፈን የምናደርገው ጥረትም ሌላው ተጨማሪ አባዜ ነው፡፡ እኔ ፃድቅ ነኝ ለማለት ሌላውን መኮነን የሚመጣው እዚህ ላይ ነው፡፡ ተግባብቶ ሳይጠላለፉ መኖር የሚያቅተውም ለዚህ ነው፡፡
ሔንሪ ቫን ዳይክ እንዲህ ይለናል፤ ..ኤደን ገነት ዳግመኛ ብትሰጠን እንኳ በትክክል አንኖርም፣ ተስማምተን አንዝናናባትም ወይም ለዘለዓለም አንቆይባትም.. ይህ አባባል በእኛም ሳይሠራ አይቀርም፡፡ እንዲህ ኢኮኖሚያችን ቆርቁዞ፣ አስከፊ ድርቅ መትቶን፣ የኑሮ ውድነት ናጥጦብን ቀርቶ ..ለምለሟን..፣ ..የዳቦ ቅርጫቷን..፣ ..የአፍሪካ ኩራቷን.. ኢትዮጵያን ብናገኝ በትክክል አንኖርባትም፣ ተስማምተን አንዝናናባትም፤ አንቻቻልባትም እንደማለት ነው፡፡
በታሪክ እንደሚነገረው፤ ታሊያርድ የተባለው የፈረንሳይ ዲፕሎማት በየስብሰባው ላይ “..ቢዝነስ የምትሠሩ ሰዎች እጃችሁ ንፁህ መሆን አለበት..” ይል ነበር አሉ፡፡ ንፁህ ያልነበረው እጅ ግን የሱ የራሱ ነው። ያንን በመናገሩ ሌሎች ንፁህ እንዳልሆኑ ጥርጣሬን ይፈጥራል፡፡ አለመተማመንን ያሰፍናል፡፡ መፈራራትንና ሥጋትን ያሰለጥናል፡፡ ጥርጣሬን ይፈጥራል፡፡ እሱ ግን ከጥርጣሬው በላይ ተረጋግቶ ይቀመጣል፡፡ በጥርጣሬ ውስጥ የሚኖሩ ሰዎች ለፍርሃት፣ ላለመረጋጋት፣ በዕቅድ ላለመኖር፣ ለሙስና፣ ምሬትን ለማመቅ፣ በኑሮ ተስፋ ለመቁረጥ እጅግ የተጋለጡ ናቸው፡፡ ይሄን ሁኔታ የሚፈጥሩ ወገኖች ደሞ በአጋጣሚው ለመጠቀም ወደ ኋላ አይሉም፡፡ ወትሮም ሰበብ ይፈልጋሉና ባገኙት ቀዳዳ ይገለገላሉ፡፡ ሙስናቸውን ያስፋፋሉ፡፡ ያለገንዘብ ንቅንቅ የማይሉ ቢሮክራቶችን ይፈለፍላሉ፡፡ እየቦረበሩ ስለ ድል ያወራሉ፡፡ በአሸበረቁ ፖሊሲዎች ይምላሉ ይገዘታሉ፡፡ ብዙ ግብረ አበሮችን በመረብ ያደራጃሉ፡፡ የማይቀለበስ ደረጃ ደረስን ይላሉ፤ ከአጋጣሚ አጋጣሚን ይወልዳሉ፡፡ እንኳንስ ነጠላ አግኝታ ዱሮም ዘዋሪ እግር አላት ይሏል እኒህ ናቸው፡፡

ቅዱስ ሲኖዶሱ ለአዊ ዞን ሀገረ ስብከት በከፍተኛ ድጋፍ መርጧቸው ነበር

      የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስ፣ በኤጲስ ቆጶስነት ማዕርግ እንዲሾሙ በቅርቡ ከመረጣቸው ቆሞሳት አንዱ፣ “የጀመርኩት ሥራ አለብኝ” በሚል ዕጩነቱን እንዳልተቀበሉት፣ የመንበረ ፓትርያርኩ ምንጮች አስታወቁ፡፡
የቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ፣ ግንቦት 10 ቀን ባካሔደው ምርጫ ተወዳድረው ካለፉት ዕጩ ቆሞሳት አንዱ የሆኑት፣ አባ ገብረ ሥላሴ ተስፋ፣ በኢየሩሳሌም የቤተ ክርስቲያኒቱ ገዳማት አገልጋይ እንደሆኑና ከቅዱስ ሲኖዶሱ በደብዳቤና በስልክ ለተላለፈላቸው ጥሪ፣ የጀመሩት ሥራ እንዳለ በመጥቀስ፣ ዕጩነቱን እንደማይቀበሉትና በሹመቱም ለመገኘት እንደማይችሉ ማስታወቃቸውን ምንጮቹ ተናግረዋል፡፡
በዕጩ ኤጲስ ቆጶሳት የምርጫ ሥርዓት ደንብ መሠረት፣ በአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት፣ የንፋስ ስልክ ላፍቶ ክፍለ ከተማ ቤተ ክህነት ጽ/ቤት ሥራ አስኪያጅ ከሆኑት መልአከ ጽዮን አባ ኅሩይ ወንድይፍራው ጋራ በምዕራብ ጎጃም - አዊ ዞን ሀገረ ስብከት ለውድድር የቀረቡት አባ ገብረ ሥላሴ፣ ድምፅ ከሰጡት 38 አጠቃላይ የምልአተ ጉባኤው አባላት 31ዱን በማግኘት በከፍተኛ ድጋፍ ተመርጠው እንደነበር ታውቋል፡፡
በቦታቸው ስለሚተኩት ዕጩ፣ ለጊዜው የታወቀ ነገር ባይኖርም፣ በቀጣዩ ዓመት ጥቅምት በተጨማሪነት ይካሔዳል ከተባለው ምደባ ጋራ ጉዳዩ እንደሚታይ ምንጮች ጠቁመዋል፡፡  የአዊ ዞን ሀገረ ስብከትን በአሁኑ ወቅት ደርበው እየመሩ ያሉት፣ ብፁዕ አቡነ አብርሃም ናቸው፡፡ ሊቃነ ጰጳሳት በሌሉባቸው አህጉረ ስብከት ምደባ ለማካሔድ፣ ከሀገር ውስጥና ውጭ የተጠቆሙና በቅዱስ ሲኖዶሱ በተቋቋመው አስመራጭ ኮሚቴ አማካይነት፥ ዕውቀታቸው፣ የቆየ ታሪካቸውና ሥነ ምግባራቸው ተገምግሞና ተመዝኖ ብልጫ ያገኙ 16 ዕጩ ቆሞሳት በቅዱስ ሲኖዶሱ እንደተመረጡ፣ ብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርኩ ባለፈው ግንቦት 14 ቀን መግለጫቸው አስታውቀዋል፡፡
የፊታችን ሐምሌ 9 ቀን ኤጲስ ቆጶስነት የሚሾሙት ዕጩ ቆሞሳት፣ ከመጪው ሁለት ሳምንት በኋላ፤ በቤተ ክርስቲያኒቱ ቀኖና፣ ትምህርተ ኖሎት፣ ሕግና ታሪክ፣ አስተዳደር፣ የቅርስ አያያዝ፣ ማኅበራዊ ኑሮና ወቅታዊ ጉዳዮች ላይ ያተኮሩ ሴሚናሮች እንደሚሰጣቸውና እስከ ሰኔ 15 ቀን ወደ መንበረ ፓትርያርኩ ተጠቃለው በመግባት ሪፖርት እንዲያደርጉ በቅ/ሲኖዶሱ ጽ/ቤት መታዘዛቸው ታውቋል፡፡

  በቦሌ አለም አቀፍ አውሮፕላን ማረፊያ፤ ከ778 ሺህ ዩሮ በላይ በሆነ ወጪ ለመጀመሪያ ጊዜ ዘመናዊ የአውሮፕላን ማቆሚያ ቴክኖሎጂ ተገጥሞ፣ አገልግሎት መስጠት መጀመሩ ተገለጸ፡፡
የኢትዮጵያ ኤርፖርቶች ድርጅት ለአዲስ አድማስ በላከው መረጃ፤ ከዚህ ቀደም አውሮፕላኖችን በቦታቸው ለማቆም አገልግሎቱ በሰው ኃይል ይሰጥ እንደነበረ ጠቅሶ፤ ይህ አሰራር ከአየር መንገዱ ዘመናዊ አሰራር ጋር የማይሄድ በመሆኑ በዲጂታል ቴክኖሎጂ መቀየር አስፈልጓል ብሏል፡፡
አንድ አውሮፕላን በማኮብኮቢያ ሜዳ ላይ ካረፈ በኋላ እስከ ማቆሚያው ወይም የመንገደኞች መሸጋገሪያ ድልድይ ድረስ ከፓይለቱ ጋር በመነጋገር አውሮፕላኑን የማቆም ስራ ይሰራ እንደነበር ጠቁሞ፤” ይህ አይነቱ አሰራር በፓይለቱና በመረጃ ሰጪው መካከል አለመግባባት ይፈጥር ነበር፤ ቴክኖሎጂው ይህን ችግር ሙሉ በሙሉ ይቀርፋል” ሲል አብራርቷል፡፡  
ቴክኖሎጂውን ሴፍ ጌት የተባለ የስዊድን ኩባንያ ያቀረበ ሲሆን በቦሌ ዓለም አቀፍ አውሮፕላን ማረፊያ ከሚገኙ 52 የአውሮፕላን ማቆሚያዎች መካከል ለጊዜው 14ቱ ላይ መሳሪያው ተተክሎ አገልግሎት መስጠት እንደጀመረ ተጠቁሟል።
ቴክኖሎጂው የአውሮፕላን ማረፊያውን አገልግሎት በማዘመን፣ አለማቀፍ ደረጃውን የጠበቀ አገልግሎት ለመስጠት ያስችላል ተብሏል።  

የኢትዮጵያ አየር መንገድ ዘንድሮ ለ2ኛ ጊዜ የዓመቱ ምርጥ የአፍሪካ አየር መንገድ ተባለ፡፡
ሰሞኑን በደቡብ አፍሪካ ጆሃንስበርግ በተካሄደው 26ኛው ዓመታዊ የአየር መንገዶች ጉባኤና ኤግዚቢሽን ላይ አየር መንገዱ “ከአፍሪካ ሀገራት አየር መንገዶች ምርጡ መስተንግዶ አቅራቢ” ተብሎ ከአፍሪካ አቪዬሽን የእውቅና ሽልማት ተበርክቶለታል፡፡
አየር መንገዱ በተከታታይ ያስመዘገበውና እያስመዘገበ ያለው ፈጣን እድገት፣ ትርፋማነቱና ለአፍሪካ አቪዬሽን ኢንዱስትሪ ያበረከተው አስተዋፅኦ ተመራጭ እንዳደረገው ታውቋል፡፡ አየር መንገዱ፤ በርካታ ኩባንያዎችና አየር መንገዶች በከፍተኛ የፋይናንስ ችግር ውስጥ በወደቁበት ወቅት አቅሙን ማጠናከሩና የበለጠ ትርፋማ መሆኑም ተመራጭ አድርጎታል ተብሏል፡፡
ባለፈው የፈረንጆች ዓመት የ70 በመቶ ትርፍ ማስመዘገቡን የጠቀሰው የሽልማት ተቋሙ፤ 265 ሚሊዮን ዶላር የተጣራ ትርፍ ማግኘቱንና የተጓዦችን ቁጥር ቀድሞ ከነበረው በ18 በመቶ ማሳደጉን ጠቁሟል፡፡

 ካንትሪሳይድ ሆቴልስ ግሩፕ የተባለው የስዊድን ሆቴል ከቅርንጫፎቹ በአንደኛው ለተወሰነ ጊዜ በማረፍ አገልግሎቱን የሚጠቀሙ የተኳረፉ ባለትዳሮች፣ በሆቴሉ ቆይታቸው ችግራቸውን የማይፈቱና በአንድ አመት ጊዜ ውስጥ ፍቺ በመፈጸም ትዳራቸውን የሚያፈርሱ ከሆነ ካሳ እንደሚሰጥ ማስታወቁ ተዘግቧል፡፡
በትዳር ውስጥ የሚፈጠሩ አለመግባባቶችንና ግጭቶችን በውይይት የመፍታት ባህልን የማዳበር ተልዕኮ ያነገበው ሆቴሉ፤ በተለያዩ ምክንያቶች የተኳረፉ ጥንዶች ከቅርንጫፎቹ ወደ አንደኛው ጎራ በማለት፣ እየተዝናኑ ችግራቸውን በውይይት እንዲፈቱና ትዳራቸውን ከመፍረስ እንዲያድኑ ምቹ ሁኔታን የሚፈጥር ሲሆን፣ በቆይታቸው ችግራቸውን መፍታት ካቃታቸውና በ1 አመት ጊዜ ውስጥ የሚፋቱ ከሆነ፣ ለተፋቺዎቹ የሁለት ቀን አዳር ሙሉ ወጪያቸውን በካሳ መልክ እንደሚሰጥ ቢቢሲ ዘግቧል፡፡
ሆቴሉ ይህንን ያልተመለደ አሰራር የቀየሰው ባለትዳሮች በመካከላቸው ግጭትና አለመግባባት ሲከሰት፣ ከመደበኛው ህይወታቸውና በግርግር ከተሞላው አለም ለተወሰነ ጊዜ በመውጣት ገለል ብለው እየተዝናኑ በትዳራቸው ጉዳይ ላይ በሰከነ መንፈስ እንዲመክሩና ትዳራቸውን ከአደጋ እንዲታደጉ ለማበረታታት ነው ተብሏል፡፡
ከሆቴሉ ቅርንጫፎች በአንደኛው የተወሰነ ጊዜ ቆይተው በመካከላቸው ያለውን አለመግባባት ለመቅረፍ ያልቻሉና ፍቺ የፈጸሙ ባለትዳሮች፣ ከሚመለከታቸው የመንግስት አካላት የተሰጣቸውን ህጋዊ ፍቺ መፈጸማቸውን የሚያረጋግጥ ሰነድ  ለሆቴሉ በማቅረብ የተጠቀሰውን የካሳ ክፍያ ማግኘት እንደሚችሉ ተነግሯል፡፡

 ታዋቂው የፊዚክስ ሊቅ ፕሮፌሰር ስቴፈን ሃውኪንግ፤ ቨርጂን ጋላክቲክ የተባለቺው መንኩራኩር ወደ ጠፈር ልታደርገው ባቀደቺው ታሪካዊ ጉዞ ከሚካተቱ መንገደኞች አንዱ ሆኖ ወደ ጠፈር እንደሚጓዝ በይፋ ማስታወቁን ዘ ኢንዲፔንደንት ዘግቧል፡፡
“ተሳክቶልኝ ይህቺን ምድር ለቅቄ ወደ ጠፈር ርቄ እጓዛለሁ ብዬ በህይወት ዘመኔ ሙሉ አንድም ቀን አስቤ አላውቅም፤ ቨርጂን ጋላክቲክ የተባለው የጠፈር ጉዞ ኩባንያ ባለቤት የሆነው ሪቻርድ ብራንሰን የጉዞው አካል እንድሆን ሲጋብዘኝ ሳላቅማማ ነው በደስታ ተውጬ ግብዣውን የተቀበልኩት” ብሏል ስቴፈን ሃውኪንግ፡፡ ምንም እንኳን ኩባንያው መንገደኞችን በማሳፈር ወደ ጠፈር የንግድ ጉዞ ለማድረግ ያቀደው ከስምንት አመታት በፊት ቢሆንም፣ በተለያዩ ሰው ሰራሽና ተፈጥሯዊ እንቅፋቶች ሳቢያ ዕቅዱ ለአመታት መጓተቱን ያስታወሰው ዘገባው፣ ስቴፈን ሃውኪንግን ያካትታል የተባለው የጠፈር ጉዞም በቅርቡ ይከናወናን ተብሎ እንደሚጠበቅ እንጂ ጉዞው የሚደረግበት ትክክለኛ ጊዜ አሁንም ይፋ አለመደረጉን አክሎ ገልጧል፡፡
ሶስቱ ልጆቹ በህይወቱ አይቶት የማያውቀውን ጥልቅ ደስታ እንዳጎናጸፉት የሚናገረው ስቴፈን ሃውኪንግ፣ በቅርቡ ወደ ጠፈር የሚያደርገው ጉዞ የተለየ ደስታን ይሰጠኛል ብሎ እንደሚያስብ መግለጹንም ዘገባው አመልክቷል፡፡

 ቻይና በማምረትም በመሸጥም አለምን ትመራለች

    ያለፈው የፈረንጆች አመት 2016 በአለማችን የመኪና ሽያጭ ታሪክ አዲስ ክብረ ወሰን የተመዘገበበትና ከፍተኛ ቁጥር ያላቸው መኪኖች የተሸጡበት እንደነበር የጠቆመው ቢዝነስ ኢንሳይደር ድረገጽ፣ በአመቱ 88.1 ሚሊዮን ያህል መኪኖች መሸጣቸውን ዘግቧል፡፡
በ2016 በአለማቀፍ ደረጃ የተመዘገበው የመኪኖች ሽያጭ መጠን በ2015 አመት ከነበረው ጋር ሲነጻጸር የ4.8 በመቶ እድገት ማሳየቱን የጠቆመው ዘገባው፣ የሽያጭ እድገቱ ባለፉት አራት አመታት ከተመዘገቡት ከፍተኛው እንደሆነም ገልጧል፡፡
በአመቱ 24.38 ሚሊዮን መኪኖችን በመሸጥ ከአለማችን አገራት ቀዳሚዋ ቻይና ስትሆን፣ ከአመቱ አለማቀፍ የመኪና ሽያጭ ገበያ የ13 በመቶ ድርሻን የያዘቺው አገሪቱ፣ ባለፈው አመት ከሸጠቻቸው የ3.2 ሚሊዮን መኪኖች ጭማሪ ማሳየቱንም ዘገባው አስረድቷል፡፡
ቻይና በአመቱ ከአለማችን አገራት ከፍተኛውን የመኪና ሽያጭ ለማስመዘገቧ በምክንያትነት ከሚጠቀሱ የተለያዩ ጉዳዮች መካከል በአነስተኛ መኪኖች ላይ የ50 በመቶ የታክስ ቅናሽ ማድረጓ አንዱ እንደሆነም ዘገባው አብራርቷል፡፡
በ2009 የፈረንጆች አመት ከተከሰተው አለማቀፍ የገንዘብ ቀውስ በኋላ በነበሩት አመታት፣ የአለማችን የመኪኖች ሽያጭ መሻሻል እያሳየ መቀጠሉንም አክሎ ገልጧል፡፡ ስታቲስታ የተባለው አለማቀፍ የመረጃ ትንተና ተቋም በበኩሉ፣ ባለፈው የፈረንጆች አመት 2016 በአለማቀፍ ደረጃ 72 ሚሊዮን ያህል የህዝብ ትራንስፖርት አገልግሎት የሚሰጡ የተለያዩ አይነት መኪኖች መመረታቸውን ይገልጻል፡፡
የአለማችን የመኪና ምርቱ በ2015 ከነበረው የአምስት በመቶ ያህል እድገት እንዳሳየ የጠቆመው ድረገጹ፣ በአመቱ 24 ሚሊዮን መኪኖችን ያመረተቺው ቻይና ከአለማችን አገራት በአንደኛነት መቀመጧንና ከአለማችን የህዝብ ትራንስፖርት አገልግሎት የሚሰጡ መኪኖች ምርት 34 በመቶውን ያህል እንደምትይዝ ገልጧል፡፡
ከቻይና ታላላቅ ትርፋማ የመኪና አምራች ኩባንያዎች መካከል ከታዋቂው የአሜሪካ መኪና አምራች ኩባንያ ጄኔራል ሞተርስ ጋር በጥምረት የሚሰራው ሲያክ ሞተር ኮርፖሬሽን እንደሚገኝበትም አክሎ ገልጧል፡፡

  ኢትዮጵያ ባለመረጋጋት ከአፍሪካ 10ኛ ደረጃ፤ ፊንላንድ በመረጋጋት ከአለም 1ኛ ደረጃ ይዘዋል ተብሏል

      ፈንድ ፎር ፒስ የተባለውና ተቀማጭነቱ በአሜሪካ የሆነው የጥናት ተቋም በቅርቡ ይፋ ባደረገው የ2017 የዓለማችን አገራት ያለመረጋጋት ደረጃ ሪፖርት መሰረት፣ ደቡብ ሱዳን ከአለማችን መረጋጋት የራቃትና የመፈራረስ ከፍተኛ ዕድል ያላት ቀዳሚዋ አገር ሆናለች፡፡
አስራ ሁለት ያህል ፖለቲካዊ፣ ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ቁልፍ አመልካቾችን መሰረት አድርጎ የአለማችንን አገራት የመፈራረስ ዕድል ተጋላጭነት ደረጃ የሚያስቀምጠው ተቋሙ፣ በ2017 ሪፖርቱ ካካተታቸው 178 የአለማችን አገራት ደቡብ ሱዳንን እጅግ በከፋ ሁኔታ ላይ የምትገኝ ሲል በቀዳሚነት አስቀምጧታል፡፡ ባለመረጋጋት ከደቡብ ሱዳን ቀጥሎ በቅደም ተከተላቸው እስከ አስረኛ ያለውን ደረጃ የያዙት የአፍሪካ አገራት ሶማሊያ፣ መካከላዊ አፍሪካ ሪፐብሊክ፣ ሱዳን፣ ዲሞክራቲክ ሪፐብሊክ ኮንጎ፣ ቻድ፣ ጊኒ፣ ናይጀሪያ፣ ዚምባቡዌ እና ኢትዮጵያ መሆናቸውንም ሪፖርቱ ገልጧል፡፡
በተቋሙ ሪፖርት መሰረት፤ እንደ አምናው ሁሉ ዘንድሮም በመረጋጋት ከአለማችን አገራት የአንደኛ ደረጃን የያዘቺው ፊላንድ ስትሆን፣ ኖርዌይ፣ ስዊዘርላንድ፣ ዴንማርክና አየርላንድ ይከተላሉ፡፡
ከፍተኛ ያለመረጋጋት ችግር ካለባቸው የአለማችን አገራት መካከል ሶማሊያ፣ መካከላዊ አፍሪካ ሪፐብሊክ፣ የመንና ሶርያ እንደሚጠቀሱ የገለጸው ሪፖርቱ፣ ከአምናው ደረጃቸው አንጻር የመረጋጋት ሁኔታቸው በከፍተኛ ሁኔታ ካሽቆለቆለባቸው የአለማችን አገራት መካከል ሜክሲኮ፣ ኢትዮጵያና ቱርክ እንደሚገኙበትና ኢትዮጵያ ባለመረጋጋትና ለመፈራረስ ተጋላጭ በመሆን ከአፍሪካ አገራት 10ኛ ደረጃ መያዟንም አመልክቷል፡፡
ተቋሙ አመታዊ ሪፖርቱን ማውጣት ከጀመረ 13 አመታት ያህል ቢሆነውም፣ ከአጠናን ስልቱ፣ ከሚዛናዊነቱና ሊገመቱ የሚችሉ ሁነቶችን ወይም ክስተቶችን ቀድሞ ከመተንበይ አቅሙ ጋር በተያያዘ በስፋት እንደሚተች ዘገባዎች ያመለክታሉ፡፡

  አለማቀፍ የሆቴሎች ኔት ወርክ የተሰኘው ተቋም፤እንግዶች የሰጧቸውን የግብረ መልስ አስተያየት መነሻ በማድረግ፣ ሒልተን አዲስ ሆቴልን “የኢትዮጵያ የአመቱ ምርጥ ሆቴል” ሲል ሽልማት አበርክቶለታል፡፡
በመላው ዓለም በአለማቀፍ ሆቴሎች የሚጠቀሙ ደንበኞች በሚሰጡት የአገልግሎት እርካታ አስተያየት፤ ከኢትዮጵያ ሒልተን ሆቴል ጥሩ መስተንግዶ እንዳለው መመስከራቸውን ተከትሎ የእውቅና ሽልማት እንደተበረከተለት፣ የሆቴሉ የማርኬቲንግና የህዝብ ግንኙነት ኃላፊ ወ/ሮ ሃበን ክልሞን ለአዲስ አድማስ አስታውቀዋል፡፡ ለሽልማቱ ሆቴሉ ያለው አለማቀፍ እውቅና አስተዋፅኦ እንዳበረከተ ኀላፊዋ አልሸሸጉም፡፡  
ባለፈው ዓመት በተደረገው የኢትዮጵያ ሆቴሎች የደረጃ ምዘና፣ሒልተን አዲስ ባለ 3 ኮከብ ደረጃ ማግኘቱ አይዘነጋም፡፡

  በደራሲና ጋዜጠኛ መልሰው በሪሁን የተሰናዳው ‹‹እኔ የሌለው እኔ›› የተሰኘ መፅሐፍ ሰሞኑን ለንባብ በቃ፡፡ መፅሀፉ ‹‹ክብ ታሪኮች››፣ ‹‹አበቃቀል›› እና ‹‹መብተክተክ›› በሚሉ ሶስት ዋና ዋና ክፍሎች የተከፈለ ሲሆን እነዚህ ሶስት ሀሳቦች በአንድም በሌላም መንገድ የሚገናኙና የሚሰናሰሉ በመሆናቸው ‹‹Tripod of life›› የሚለው ሃረግ እንደሚገልፃቸው ደራሲው በመግቢያው አስፍሯል፡፡
ሶስቱም ክፍሎች በሶስቱ ክብ ሀሳቦች የተሳሰሩ ፍልስፍናዊ ሀሳቦች ያሉበት፤ በመብተክተክ ሀሳቦችን የሚፈትሹ ናቸው ተብሏል፡፡ በመፅሀፉ ‹‹የኔ ፊርማ በታችም መስመር በላይም መስመር አለው››፣ ‹‹የፊት ቅርፅ እና እሳቤ››፣ ‹‹የማፍቀር አርኪ ገፅታ››፣ ‹‹የአባቴ ሱሪዎች›› የተሰኙና ሌሎችንም ወጎች አካትቷል፡፡ ደራሲው መልሰው በሪሁን በአሁኑ ወቅት በአማራ ክልል ቴሌቪዥን በጋዜጠኝነት እያገለገለ ይገኛል፡፡