Administrator

Administrator

   አንድ ኪ. ሜትር ያሽከረከረ፣ 25 ሳንቲም ይሸለማል
    ማሳሮሳ የተባለችው የጣሊያን ከተማ ወደ ስራ ገበታቸው ሲጓዙ ከመኪና ይልቅ ብስክሌት የሚጠቀሙ ነዋሪዎቿን በወር እስከ 50 ዩሮ የሚደርስ ሽልማት እንደምትሰጥ ማስታወቋን ቢቢሲ ዘገበ፡፡የከተማዋ አስተዳደር ምክር ቤት፤ ብስክሌት ለሚጠቀም ነዋሪ በአንድ ኪሎ ሜትር 25 ሳንቲም ሂሳብ እየተሰላ ሽልማት እንዲሰጠው መወሰኑን የጠቆመው ዘገባው፣ አንደመነሻም ለ50 ሰራተኞች የአንድ አመት ሽልማት ለመስጠት ማሰቡንና በቀጣይም ሽልማቱን ለማስፋፋት ማሰቡን ገልጧል፡፡
በሽልማት መልክ የሚሰጠው ገንዘብ፣ ከትራፊክ ክፍያ ትኬት ከሚሰበሰበው የከተማዋ ገቢ እንደሚገኝ የተገለጸ ሲሆን፣ የከተማዋ አስተዳደር ሽልማቱን ለመስጠት ያሰበው ብስክሌት መጠቀም የትራፊክ መጨናነቅን ያስቀራል፣ የጤና ጠቀሜታም አለው በሚል መነሻ እንደሆነም ታውቋል፡፡ ባለፈው አመት በፈረንሳይ ተመሳሳይ የማበረታቻ ሽልማት መሰጠት ተጀምሮ እንደነበር ያስታወሰው ዘገባው፣ ይህም የብስክሌት ተጠቃሚዎችን ቁጥር ከፍ አድርጎት እንደነበር አክሎ ገልጧል፡፡

አሜሪካ በ3 ወር ውስጥ ከ26 ሺህ 500 በላይ ተጠቃሚዎቼን መረጃ ጠይቃኛለች
     ታዋቂው የማህበራዊ ድረገጽ ፌስቡክ፣ የተጠቃሚዎቹን የግል መረጃዎች አሳልፎ እንዲሰጣቸው የሚጠይቁት መንግስታት ቁጥር እያደገ መሆኑን ማስታወቁን ሲኤንቢ ኒውስ ዘገበ፡፡
መሰል መረጃዎችን አሳልፎ እንዲሰጣቸው ከመንግስታት የሚቀርቡለት ጥያቄዎች ቁጥር በ2015 የመጀመሪያዎቹ ሶስት ወራት ካለፈው አመት ተመሳሳይ ጊዜ ጋር ሲነጻጸር በ18 በመቶ ማደጉን የገለጸው ፌስቡክ፣ ባለፉት የጥር፣ የካቲትና መጋቢት ወራት ብቻ ከተለያዩ የአለም አገራት መንግስታት 41 ሺህ 214 ጥያቄ እንደቀረበለት አስታውቋል፡፡
የተጠቃሚዎቹን የግል መረጃ እንዲሰጡት ከጠየቁት መንግስታት መካከል የአሜሪካ መንግስት ቀዳሚውን ስፍራ እንደሚይዝ የጠቆመው ፌስቡክ፣ የአሜሪካ መንግስት በሶስቱ ወራት ከ26ሺህ 500 በላይ የሚሆኑ የፌስቡክ ተጠቃሚዎችን መረጃ አሳልፌ እንድሰጠው 17 ሺህ 577 ጥያቄዎችን አቅርቦልኛል ሲል ገልጧል፡፡
በተጠቀሰው ጊዜ ውስጥ ህንድ 5 ሺህ 115፣ እንግሊዝ 3 ሺህ 384፣ ፈረንሳይ 2 ሺህ 520፣ ጀርመን 2 ሺህ 344 መሰል ጥያቄዎችን እንዳቀረቡለት ያስታወቀው ፌስቡክ፣ የምመራበት ፖሊሲ የተጠቃሚዎቼን የግል መረጃ አሳልፌ እንድሰጥ ስለማይፈቅድልኝ ጥያቄያቸውን አላስተናገድኩም ብሏል፡፡

 አይሲስ የተባለው አሸባሪ ቡድን ባሳለፍነው ሳምንት አርብ በፓሪስ ስድስት የተለያዩ አካባቢዎች የሰነዘረው የሽብር ጥቃት፣ 136 ያህል ሰዎችን ለህልፈተ ህይወት ዳርጓል፡፡ የመቁሰል አደጋ ከደረሰባቸው 352 ሰዎች መካከልም ከ100 በላይ የሚሆኑት ክፉኛ በመጎዳታቸው በአስጊ ሁኔታ ላይ ይገኛሉ፡፡የፈረንሳይ መንግስት፣ የአርቡን የሽብር ጥቃት ተከትሎ የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ በማውጣት በሽብር ድርጊቱ የተሳተፉ ተጠርጣሪዎችን የማፈላለግ ዘመቻ ጀምሯል፡፡ እስካሁንም አራት ያህል ተጠርጣሪዎችን በቁጥጥር ስር እንዳዋለ ሲኤንኤን ዘግቧል፡፡
ሌሎች የሽብር ጥቃቶች ሊሰነዘሩ ይችላሉ የሚል ስጋት ያደረበት የፈረንሳይ መንግስት፣ የጥቃት ኢላማ ሊሆኑ ይችላሉ ባላቸው የተለዩ የአገሪቱ አካባቢዎች ተጨማሪ 1 ሺህ 500 ያህል ወታደሮችን አሰማርቶ፣ ጥብቅ ጥበቃ እያደረገ ይገኛል፡፡ በድንበር አካባቢዎችም የተለየና የተጠናከረ ጥበቃ እየተደረገ ነው፡፡
የሽብር ጥቃቱ ካደረሰው ሰብአዊ ጥፋት በተጨማሪ በስደተኞችና በአገሪቱ የቱሪዝም መስክ ላይ የራሱ የሆነ ጉልህ አሉታዊ ተፅዕኖ እየፈጠረ እንደሆነ  ዘገባዎች ያስረዳሉ፡፡
የስደተኞች ጉዳይ
የፓሪሱ ጥቃት ከፈረንሳይ አልፎ የመላ አውሮፓ ብሎም የሌሎች አገራት ጉዳይ ሆኗል፡፡ ተጽዕኖውም ድንበር መሻገር ይዟል፡፡ ጥቃቱ የአውሮፓ አገራት የድንበር ላይ ቁጥጥርን ለማቆም ያሳለፉትን ውሳኔ ቀጣይነት ጥያቄ ውስጥ ጥሎታል፡፡ ይሄው ውሳኔ ካለፈው ሰኞ ጀምሮ በብዙዎቹ የአውሮፓ አገራት ተጥሷል፡፡ የጥቃቱ ዋነኛ ሰለባ ፈረንሳይ የድንበር ላይ ቁጥጥሯን እንደገና የጀመረች ሲሆን፤ ስዊድን፣ ጀርመንና ስሎቫኒያም የድንበር ላይ ቁጥጥራቸውን ከጥቃቱ አስቀድመው ዳግም አጠናክረው ጀምረዋል፡
የአውሮፓ አገራት በመካከላቸው ያለውን ድንበር ብቻም ሳይሆን፣ የአህጉሪቱን ድንበሮች ለሶርያና ለሌሎች አገራት ስደተኞች ወደ መዝጋት ተሸጋግረዋል፡፡ ምክንያታቸው ደግሞ፣አይሲስ ለሽብር የመለመላቸውን አባላቱን ከስደተኞች ጋር ወደ አውሮፓ አገራት እያስገባ ነው የሚል ነው፡፡
ኒውዮርክ ታይምስ እንዳለው፤የፓሪሱ ጥቃት አውሮፓ በስደተኞች ላይ ያላትን አቋም እንድትቀይርና ትኩረቷን ስደተኞችን ከማቋቋም ወደ ጥብቅ ቁጥጥር ማድረግ እንድትለውጥ እያስገደዳት ነው፡፡ በፓሪሱ ጥቃት ከተሳተፉት አሸባሪዎች አንዱ ወደ ፈረንሳይ የገባው በሶርያ ፓስፖርት መሆኑን የሚያሳይ መረጃ መገኘቱ በስፋት መነገሩን ተከትሎ፣ የአውሮፓ አገራት መሪዎች ድንበራቸውን አልፈው ወደ ግዛቶቻቸው የሚገቡ ስደተኞች ጉዳይ ክፉኛ እያስጨነቃቸው ነው ይላል ዘገባው፡፡
ሲቢኤስ ኒውስ በበኩሉ፤ የፓሪሱ ጥቃት በስደተኞች ላይ የፈጠረው ተጽዕኖ ከአውሮፓ አልፎ አሜሪካ መግባቱን ዘግቧል፡፡ ግማሽ ያህሉ የአሜሪካ ግዛቶች፣ የሶርያን ስደተኞች ወደ ግዛቶቻቸው ከመግባት የሚያግድ ውሳኔ ለማሳለፍ እየተንቀሳቀሱ እንደሆነ አስታውቀዋል፡፡ ፖላንድ ከአውሮፓ ህብረት የደህንነት ዋስትና እስካልተሰጣት ድረስ፣ ከአሁን በኋላ ስደተኞች ወደ ግዛቷ እንዲገቡ እንደማትፈቅድ መግለጧን ዘገባው አመልክቷል፡፡
ፓሪስ የቱሪስቶች መናኸሪያ ሆና ትቀጥል ይሆን?
ከአለማችን የቱሪስት መዳረሻ ከተሞች በቀዳሚነት የምትጠቀሰው ፓሪስ፣ በዚህ አመት ብቻ ሁለት አሰቃቂ የሽብር ጥቃቶችን አስተናግዳለች፡፡ ይህም የከተማዋን ነዋሪዎች ብቻ ሳይሆን ከመላ አለም ወደ ከተማዋ ለመጓዝ ያሰቡ በርካታ ቱሪስቶችንና የንግድ ጉዞ ለማድረግ ቀጠሮ የያዙ ኩባንያዎችን በድንጋጤ ክው አድርጓል፡፡
ፎክስ ኒውስ እንደዘገበው፤ ከአጠቃላዩ የአገር ውስጥ ምርቷ 7.4 በመቶ ያህሉን በቱሪዝም የምታገኘው ፈረንሳይ፣ በተሰነዘሩባት የሽብር ጥቃቶች ሳቢያ የቱሪዝም መስክ ገቢዋ እንደሚቀንስ እየተነገረ ነው፡፡የሰሞኑ ጥቃት መፈጸሙን ተከትሎ ወደ ፈረንሳይ ለመሄድ ተመዝግበው የነበሩ የተለያዩ አገራት ቱሪስቶች ጉዟቸውን ሰርዘዋል፤ ፓሪስ ውስጥ የነበሩ ቱሪስቶችም በድንገተኛው ጥፋት ተደናግጠው ባፋጣኝ ከተማዋን ለቅቀው ወጥተዋል፡፡ ከጥቃቱ በኋላ ታዋቂውን ኤፍል ታወር ጨምሮ በአገሪቱ የሚገኙ ዋነኛ የቱሪስት መስህቦች እስከ አራት ቀናት ያህል ለጎብኝ ዝግ እንዲደረጉ መወሰኑ በአገሪቱ ቱሪዝም ላይ የፈጠረው ተጽዕኖ እንዳለ ሆኖ፣ ፕሬዚዳንት ሆላንዴ የአገሪቱ ድንበሮች እንዲዘጉ ማዘዛቸውም፣ ፈረንሳይ ከቱሪዝም የምታገኘውን ገቢ ክፉኛ እንደሚጎዳውና ጥቃቱ በቀጣይም በአገሪቱ ቱሪዝም ላይ አሉታዊ ተጽዕኖ መፍጠሩ እንደማይቀር እየተነገረ ነው፡፡
ዘ ጋርዲያን ባለፈው ሰኞ ያወጣው ዘገባ ግን፣ የፓሪሱ ጥቃት የከተማዋንና የአገሪቱን ብቻ ሳይሆን የመላ አውሮፓን የጉዞና የሆቴል ዘርፍ ኢንቨስትመንት ክፉኛ እንደሚጎዳ ይገልጻል፡፡
የፓሪሱ ጥቃት ከተፈጸመ በኋላ በነበሩት ሶስት ቀናት ብቻ፣ ጥቃቱ በመላው የአውሮፓ አገራት ቱሪዝምና በተጠቃሚዎች ላይ  ተጽዕኖ ያሳድራል የሚል ስጋት በኢንቨስተሮች ላይ በመፈጠሩ፣ የአህጉሪቱ የጉዞና የሆቴል ዘርፍ ኢንቨስትመንት ከ2 ቢሊዮን ፓውንድ በላይ አጥቷል ይላል ዘገባው፡፡
ሌሎች የሽብር ጥቃቶች ሊሰነዘሩ ይችላሉ የሚለው ስጋት እንዲሁም በድንበር ላይ ያለው ጥብቅ ቁጥጥር የመንገደኞችንና የንግዱን ማህበረሰብ እንቅስቃሴ ሊያስተጓጉለው ይችላል ከሚለው ግምት ጋር ተዳምሮ፣ ኤር ፍራንስ - ኬኤልኤምን የመሳሰሉ አየር መንገዶች እንዲሁም ቶማስ ኩክን የመሳሰሉ ታላላቅ የጉዞ ወኪል ኩባንያዎች የአክሲዮን ድርሻ በከፍተኛ ሁኔታ እንዲቀንስ አድርጎታል ብሏል ዘገባው፡፡

  ዝነኛው የፊልም ተዋናይ ግሩም ኤርምያስ፤ሰሞኑን በተጠናቀቀው 10ኛው ኢትዮ ኢንተርናሽናል የፊልም

ፌስቲቫል፣በ“ላምባ” ፊልም በምርጥ መሪ ተዋናይነት ተሸልሟል፡፡ አዲሱ ዓመት ከጠባ አርቲስቱ በዚህ ፊልም በመሪ ተዋናይነት ሽልማት ሲያሸንፍ የሰሞኑ ለሦስተኛ ጊዜ መሆኑ ነው፡፡ ግሩም በ5ኛው ኢትዮ ኢንተርናሽናል ፊልም ፌስቲቫል በ“ትዝታህ” ፊልም፣ በ8ኛው ደግሞ በ“አራት መቶ ፍቅር” ፊልም በምርጥ መሪ ተዋናይነት መሸለሙ ይታወሳል፡፡ የአዲስ አድማስ ጋዜጠኛ ናፍቆት ዮሴፍ፤አርቲስት ግሩም ኤርሚያስን ተወዳጅነትን ባተረፈው የ“ላምባ; ፊልም ትወናው፣ ባሸነፋቸው ሽልማቶችና በኩላሊት እጥበት ማዕከል አምባሳደርነቱ ዙሪያ አነጋግራዋለች፡፡       ዘንድሮ ብቻ ሦስት ሽልማቶችን አሸንፎበታል

      በ“ላምባ“ ፊልም ሽልማቶችን እየሰበሰብክ ነው -----
እውነት ነው፤እስካሁን በፊልሙ ሦስት ሽልማቶችን ወስጃለሁ፡፡ አንዱ፣ በሸገር ኤፍ ኤም 102.1 የለዛ አድማጮች ምርጫ ላይ፣ በመሪ ተዋናይነት የተሸለምኩት ነው፡፡ ሌላው በዛሚ 90.7 ኤፍ ኤም በዲጄ ቤቢ የአድማጮች ምርጫ ላይም፣ “ላምባ” በምርጥ ፊልም ዘርፍ ሲያሸንፍ፣ እኔ በምርጥ መሪ ተዋናይነት አሸንፌያለሁ፡፡ ሦስተኛውን ባለፈው ሰኞ ምሽት በተደረገው የኢትዮ ኢንተርናሽናል ፊልም ፌስቲቫል መዝጊያ ላይ በምርጥ መሪ ተዋናይነት አሸንፌያለሁ፡፡ ይሄ ለእኔ ብቻ ሳይሆን ለሁሉም አድናቂዎቼ፣ ለቤተሰቦቼና ለሙያ አጋሮቼ በጣም የሚያስደስት ነው፡፡ ፊልሙ በተከታታይ አሸናፊ ለመሆን የቻለበት ምሥጢር ምንድን ነው? በጣም የሚያሳዝን በመሆኑና የወቅቱን ችግር በማንሳቱ ነው? ወይስ አጠቃላይ የፊልም አላባዊያን የሚባሉትን ያሟላ በመሆኑም ነው?ፊልሙ በሁሉም መልኩ ማኅበረሰቡ ላይ የፈጠረው ትልቅ ነገር አለ፡፡ አንደኛ የወቅቱን አንገብጋቢ ችግር የኩላሊትን ጉዳይ አንስቶ በብዙዎች ዘንድ ግንዛቤን ፈጥሯል፡፡ ፊልሙ ከፊልምም ፈቀቅ ብሎ አንዳንድ ለውጦችንም አምጥቷል፡፡ ለውጥ ስንል አንዱ ቀደም ብዬ የነገርኩሽ የግንዛቤ ጉዳይ ነው፡፡ ግንዛቤው ደግሞ ከእኔው ከራሴ ይጀምራል፡፡ ለምሳሌ
እኔ ስለ ኩላሊት ህመም የነበረኝ ግንዛቤ አሁን ካለኝ ጋር ሳነፃፅረው ምንም ነበር፡፡ ስለ ኩላሊት ሲወራ ‹ውሃ ጠጣበት፤ ውሃ ጠጪበት፣› ከማለት የዘለለ እውቀት አልነበረኝም፡፡ በተመሳሳይ ሌላውም ኅብረተሰብ የችግሩን አስከፊነት በደንብ የተገነዘበ ይመስለኛል፡፡ የዚህ ማሳያ ደግሞ ኅብረተሰቡ ለዚህ ጥሪ የሰጠው ምላሽ ነው፡፡ ለኩላሊት እጥበት ማዕከሉ በኤስኤምኤስና በሌሎች መንገዶች ምላሹን እየሰጠ ነው፡፡
ሌላ ባነሳው ሃሳብ፣ በዳይሬክቲንጉ፣ በአጠቃላይ ሥራው ---- አንድ ፊልም ሊያሟላቸው የሚገባውን ነገሮች ሁሉ
በብቃት የያዘ በመሆኑ፣ በችግሩ ዙሪያ ማንሳት የሚገባንን እንድናነሳ አስችሎናል፡፡ መቼም በዓለም ላይ መቶ በመቶ ትክክል የሆነ ነገር አይኖርም፡፡ ምንም ነገር ሲሠራ ጥቃቅን ስህተቶች ሊኖሩ ይችላሉ፡፡ ሆኖም፣ “ላምባ; ባነሳው ሃሳብም በቴክኒኩም በኩል ሁሉን ያሟላ በመሆኑ ሽልማቶችን እየወሰደ ነው፡፡ ሰኞ ምሽትም አራት አዋርዶችን ሲወስድ
ተመልክተሻል፡፡ ይህን የምነግርሽ ከሙያ አኳያ ነው፡፡ ፊልሙን ዝም ብለሽ ስትመለከቺ ከጽሑፍና ከዳይሬክቲንግ ባለፈ የፊልሙ ባለሙያዎች ሁሉም ምን ያህል እንደጣሩበትና እንደለፉበት ትመለከቻለሽ፡፡ ላይት የሠሩት፣ ሜካፑን የሠሩት፣ ሲኒማቶግራፊውም አለ፡፡ ይህን ሁሉ ሲሠሩ ታዲያ ከታሪኩ ፍሰት ጋር ተዋኅዶ እንዲሄድ አመጣጥነውታል፡፡ አየሽ እነዚህ ሥራዎች ጥሩ ሲሆኑ ታሪኩን ያግዙታል፣ያጐለብቱታል፡፡ በዚህ ምክንያት ተዋንያኑ እያንዳንዱ ስሜት ገብቷቸው፣ በደንብ ወደውት ስለሠሩት ፊልሙ ተወዳጅ ሆኗል፡፡ ለረጅም ጊዜ ነበር ስንለማመድና ስናሸው የነበረው፤ ከትዕይንት ትዕይንት በደንብ አድርገን ነው የሠራነው፡፡ ለምን ብትይ ---- ከባድ ሃሳብ ነው፣ ከባድ ስሜትም ይጠይቃል፡፡ በአጠቃላይ የሁላችንም አስተዋጽኦ በደንብ የታየበት ነው፡፡ በዚህም የታለመለትን ግብ መትቷል፡፡ ብዙ ጊዜ ግሩም ሥራ ስለመጣለት ብቻ አይቀበልም፤ሥራ ይመርጣል፣ ይባላል፡፡ ይህን ፊልም ባትሠራ ይቆጭህ ነበር?
በእርግጠኝነት ይህንን ፊልም ባልሠራ ከሚቆጩኝ ፊልሞች አንዱ ይሆን ነበር፡፡ ሌላው ቀርቶ ከምሠራበት ዋጋም በጣም ቀንሼ የሠራሁት፣ ሃሳቡን --- የፊልሙን ዓላማ ስለወደድኩት ነው፡፡ ይህን ፕሮዲዩሰሮቹም ሊነግሩሽ ይችላሉ፡፡ እውነት ለመናገር በነፃም ብሠራው ደስ ይለኝ ነበር፡፡ ነገር ግን የእኔ ህይወት ሙሉ ለሙሉ የተመሠረተው በፊልም ላይ ነው፤ሌላ ምንም ሥራ አልሠራም፤ የሕይወት ጉዳይ ሆኖ እንጂ በነፃ ብሠራው ብዬ ነበር፡፡ ያም ሆኖ ባልሠራው ግን እጅግ በጣም ይቆጨኝ ነበር፡፡ በጣም ወድጄው ነው የሠራሁት፡፡
በፊልሙ ታሪክ እህትህ የምትሞትበት ትዕይንት ላይ ራስህን መቆጣጠር እንዳቃተህ ሰምቻለሁ፡፡ እስኪ የነበረውን ስሜት ንገረኝ ----
እንግዲህ የዚህ ፊልም የመጨረሻው ትዕይንት ለብዙ ጊዜ የታመምኩበት ነው ማለት እችላለሁ፡፡ ትዕይንቱ ከመቀረፁ በፊትም ሆነ ከተቀረፀ በኋላ ለተወሰነ ጊዜ ታምሜ ነበር፤ልክም አልነበርኩም፡፡ ይህ የሆነበት ምክንያት ከመጀመሪያው አንስቶ ተዋናይ ሊዲያ ሞገስ ታናሽ እህቴ፣ የእውነት እህቴ ነበር የምትመስለኝ፤ በጣም ጥሩ፣ ትሁት ልጅ ናት፤
ወደፊትም ተስፋ የሚጣልባት ናት፡፡ ስንሠራ እንደ ታላቅ ወንድምና እንደ ታናሽ እህት ነበር የተያየነው፡፡ ከሥራው በፊት ያንን ስሜት የሚፈጥረውን መቀራረብ ነበር ያዳበርነው፡፡ ይህ ቅርርብ ከፊልሙም ውጭ ነበር፡፡ እንደ ታላቅና እንደ ታናሽ ነበር የምናወራው፡፡ ከቀረፃው በፊት በማንኛውም ጊዜ ለታላቅ ወንድም የሚጠየቀውን ትጠይቀኛለች፡፡ ይህ ነገር ከፊልሙም ባሻገር ሆነና ያቺ የመጨረሻ ትዕይንት (እሷ የምትሞትባት) ስትሠራ የእውነት እንዳጣኋት ነበር የተሰማኝ፡፡ ከመቀረፁ በፊት ራሱ ስሜቴን መቆጣጠር አቅቶኝ ሰውነቴ ይንቀጠቀጥ ነበር፡፡ በጣም ከባድ ጊዜና ከባድ ትዕይንት ነበር፡፡ እስከዛሬ ብዙ ከባድ ከባድ ትዕይንቶች ገጥመውኛል፤ እንደዚህ ግን አልከበደኝም፡፡ ያም ሆኖ የተወጣሁት ይመስለኛል፡፡
ፊልሙን ከምትሠራበት ዋጋ በጣም ቀንሰህ እንደሠራህ ነግረኸኛል፡፡ ስንት ተከፈለህ?
ይሄ ብዙ ቁምነገር የለውም፤ዋናው ነገር ሃሳቡና የሃሳቡ መሳካት ነው፡፡ በቃ ሌላ ጊዜ ከምጠይቀው በጣም መቀነሴንና አስተዋጽኦ ማድረጌን ከነገርኩሽ ይበቃል፡፡
የኩላሊት ዕጥበት ማዕከሉ አምባሳደር እንደመሆንህ በአሁኑ ሰዓት ምን አይነት እንቅስቃሴዎችን እያደረግህ ነው? ሰሞኑን በማዕከሉ ላይ ስለሚባለውስ ምን አስተያየት አለህ?
እኔ በማዕከሉ ትልቁ ድርሻዬ፣ ያለኝን እውቅና በመጠቀም ሕዝቡን ከማዕከሉ ጋር ማገናኘት ነው፡፡ ሰሞኑን በሚወራው ጉዳይ ላይ ማኅበሩ የራሱ የቦርድ አባላትና አመራሮች አሉት፤ በዝርዝር ጉዳዩን የሚያውቁት እነሱ ናቸው፡፡ ምንም እንዲህ ነው የምልሽ ነገር የለም፡፡
እንደው የገንዘብ ምዝበራ ምናምን የሚለውን ስትሰማ አልደነገጥክም?
በፍፁም አልደነገጥኩም፡፡ ዋናው ነገር የእኔ ድርሻ ምን እንደሆነ ነግሬሻለሁ፡፡ ከሚገባው ገንዘብ ጋር ግንኙነት የለኝም፤ አንድም ሽራፊ ሳንቲም በእኔ በኩል አያልፍም፡፡ የማውቀውም ነገር የለም፡፡ ነገር ግን እንደማንኛውም ሰው ስሰማው
አላስደነገጠኝም፤ ምክንያቱም እነዚህ ሰዎች ይህን ያደርጋሉ የሚል እምነት የለኝም፡፡ ይሄ የግል ስሜቴ ነው፡፡ ማዕከሉ የሚመራው በበላይ ጠባቂ ነው፡፡ ጤና ጥበቃ ራሱ አለበት፤ ዘውዲቱ ሆስፒታልም አለበት፤በሶስትዮሽ ወገን በጥብቅ የሚንቀሳቀስ ማዕከል ነው፡፡ ስለዚህ በነዚህ ዋና ዋና ምክንያቶች ክፍተቱ ይፈጠራል ብዬ አላምንም፡፡ እንግዲህ ሁሉንም ወደፊት የምናየው ይሆናል፡፡
“ላምባ” በፌስቲቫሉ መዝጊያ ላይ በአራት የውድድር ዘርፎች አሸንፏል፤ ይገባዋል ትላለህ?
ምናለ መሰለሽ ---- የሠራ ሁሉ ይገባዋል ባይ ነኝ፡፡ በዕለቱ ውድድር ሆነና የመምረጥ ጉዳይ ሆነ እንጂ ለእኔ እዛ ቦታ በዕጩነት የቀረቡት ፊልሞችም፣ ባለሙያዎችም አሪፎችና ምርጦች ናቸው፡፡ የምርጫው ጉዳይ ደግሞ የዳኞች ነው፡፡ ቀደም ሲል በነገርኩሽ አሪፍ አሪፍ ምክንያቶች “ላምባ” ይገባዋል፡፡ ያ ማለት ሌሎቹ አይገባቸውም ማለቴ አይደለም፡፡ እኔ ሙያውን አክብሮ፣ ህብረተሰቡን አክብሮ፣ ከልቡ በአግባቡ የሚሠራ ባለሙያ ተሸላሚ ነው ባይ ነኝ፡፡ ሽልማት የግድ በዝግጅቶችና በውድድሮች መድረክ ላይ ወጥቶ መሸለም ብቻ አይደለም፡፡ ለሙያውና ለህብረተሰቡ ታማኝ ሆኖ፣ ክብር ሰጥቶ፣ መሥራትም ራሱን የቻለ ትልቅ ሽልማት ነው ባይ ነኝ፡፡

Saturday, 21 November 2015 13:54

የህጻናት ጥግ

አንድ አባትና ትንሽ ልጁ፣ በዱር እንስሳ
መጠበቂያ (zoo) ውስጥ ነብር በሚንጎራደድበት
የብረት ፍርግርግ ፊት ለፊት ቆመዋል፡፡ አባት
ለልጁ ነብር ምን ያህል ሃይለኛና ጉልበተኛ
እንስሳ እ ንደሆነ ያ ስረዳዋል፡፡ ል ጅም ኮ ስተር
ብሎ አባቱ የሚለውን በትኩረት ሲሰማ ቆየና፤
“አባዬ” አለ በመጨረሻ፤ “አባዬ፤ነብሩ
ከብረቱ ወጥቶ ከበላህ ---”-
“እ ---ልጄ ከብረቱ ወጥቶ ከበላኝ ----
ምን?” ሲል ጠየቀው፤ የሚለውን ለመስማት
ጓጉቶ፡፡
ልጅም፤ “ወደ ቤት የሚወስደኝ አውቶብስ
ስንት ቁጥር ነው?”










Saturday, 21 November 2015 13:49

የኪነት ጥግ

(ስለሙዚየም)
- ቤተ ክርስቲያን የቅዱሳን ሙዚየም
ሳይሆን የኃጢአተኞች ሆስፒታል ነው፡፡
ሬንዞ ፒያኖ
- የስዕል ካታሎግ፤ ግድግዳ የሌለው
ሙዚየም ማለት ነው፡፡
አንድሪ ማልሮክስ
- ጥበብ መፈጠር ያለበት ለህይወት እንጂ
ለሙዚየም አይደለም፡፡
ዣን ኑቬል
- አንድ ሰው የሙዚየምን ስኬታማነት
እንዴት ነው የሚለካው?
ጄ ፖል ጌቲ
- በፓሪስ፣ ለንደን ወይም ኒውዮርክ የግል
ሙዚየም ብከፍት ደስ ይለኛል፡፡ ግን
ገንዘብ የለኝም፡፡ ቢል ጌትስን ወይም ፖል
አለንን ብሆን መጀመሪያ የማደርገው
ነገር ቢኖር፣ ሙዚየም መገንባት ነው፡፡
ዣን ፒጎዚ
- ቀኑን ሙሉ የማሳልፈው በሙዚየም
ውስጥ ነው፡፡ ምሳዬን እንኳን የምበላው
ሙዚየም ነው፡፡ ለአንድ ሰዓት ያህል
የማሸልበውም እዚያ ነው፡፡
ጆን ጎኮንግዊ
- በከኒውዮርክ ብቻ ከ65-70 የሚደርሱ
የፎቶግራፍ ጋለሪዎች አሉ፡፡ በእንግሊዝ
ግን ከአምስት አይበልጡም፡፡ ሁሉም
ደግሞ ለንደን ውስጥ ነው ያሉት፡፡
ማርቲን ፓር
- በለንደን እጅግ በ ጣም ብዙ ግ ሩም
ጋለሪዎችና ሙዚየሞች አሉ፡፡ ግን ቀን
ላይ በጣም ሊጨናነቁ ይችላሉ፡፡
ዛሃ ሃዲድ
- ከትላልቅ ጋለሪዎች ፊት ለፊት መሆን
ያስደስተኛል፡፡
ናታሊ ጉልቢስ
- የማታ ማታ ሁሉም ድንቅ ስዕሎች
መጨረሻቸው ሙዚየም ነው፡፡
ጃኪውስ ባርቢው
- የሙዚየም ዋና ዓላማ የዘመናችንን
የዕይታ ጥበቦች ሰዎች እንዲያጣጥሙት፣
እንዲረዱትና እንዲጠቀሙበት ማገዝ
ነው፡፡
አልፍሬድ ኤች.ባር ጄአር.
- በሙዚየም ውስጥ ስትሆኑ በዝግታ
ተራመዱ፤ መራመዳችሁን ግን ቀጥሉ፡፡
ጌርትሩድ ስቴይን
- በዓለም ላ ይ ካ ሉ ማ ናቸውም ነ ገሮች
የበለጠ ጅል አስተያየቶችን የሚሰማ
በሙዚየም ውስጥ ያለ ስዕል ሳይሆን
አይቀርም፡፡
ኢድሞንድ እና ጁሌስ ዲ ጎንኮርት

    ከዕለታት አንድ ቀን ውሻና አውራ ዶሮ ውድ ጓደኛሞች ሆኑ፡፡ ከዚያም ረዥም መንገድ ለመሄድ ተስማሙና ጉዞ ጀመሩ፡፡ ማታ ላይ አውራዶሮ አንድ ትልቅ ዛፍ ቅርንጫፍ ላይ ወጣና መኝታውን እዚያ ላይ አደረገ፡፡
ውሻው ደግሞ የዛፉ ግንድ ከሥር በኩል ተፈልፍሎ ስለነበር እዚያ ውስጥ ገብቶ ጥቅልል ብሎ ተኛ፡፡
አውራ ዶሮ ሊነጋ ሲል እንደተለመደው መጮህ ነበረበትና ኩኩሉ… አለ፡፡
በአቅራቢያው የነበረ አንድ ቀበሮ ድምፁን ሰማና፤
“ኦ ዛሬ ምርጥ ቁርስ አገኘሁ ማለት ነው!” እያለ ድምፁን ወደሰማበት አቅጣጫ ገሰገሰ፡፡ ከትልቁ ዛፍ ዘንድ ሲደርስ ከቅርንጫፉ ሥር ቆመና፤
“እባክህ ውረድና አጫውተኝ፡፡ ይህን የሚያምር ዜማህንም አሰማኝ” እያለ ሊያማልለውና ሊያታልለው ይሞክር ጀመር፡፡
አውራ ዶሮም፤
“ዕውነትም እኔም ወርጄ ባጫወትኩህ በጣም ደስ ባለኝ ነበር፡፡ ግን አሁን ገና በጣም ጠዋት ነው፡፡”
ቀበሮ፤
“ነግቷል‘ኮ፡፡ ይልቅ ውረድና ቁርስም ልጋብዝህ” አለው፡፡
አውራ ዶሮም፤
“የለም ገና ነው፡፡ እኔ እኮ ነኝ የጊዜ አዋቂ፡፡ ረሳህ እንዴ? ይልቅ አንተ ዛፉ ላይ ወጥተህ ለምን ትንሽ አረፍ አትልም?”
“እኔ ዛፍ መውጣት‘ኮ አልችልም”
“ምንም ችግር የለም ዘበኛዬ ታች ተኝቷል፡፡ ቀስቅሰውና በሩን ይከፍትልሃል”
ቀበሮ እንደተባለው ግንዱን እየጫረ አንኳኳ፡፡
ይሄኔ ውሻ ነቃና ዘሎ አንገቱን አንቆ ብጭቅጭቁን አወጣው፡፡
***
ብልሃት ከሁሉ የተሻለ መሣሪያ ነው፡፡ ብልሃት ጊዜን ማወቅ ነው፡፡ ብልሃት የኃይል አጠቃቀምን ማወቅ ነው፡፡ ብልሃት ቅልጥፍናንና የችግር አፈታት ዘዴን እንዴት እንደምናቀናጅ ማወቅ ነው፡፡ ብልሃት ድንገተኛ ችግር ሲያጋጥም ረጋ ብሎና ጥሞና ገዝቶ ሳይደናገጡ ችግሮችን መፍታት ነው፡፡ የሀገራችን ችግሮች የተወሳሰቡና አንዱ ካንዱ ጋር የተሳሰሩ ናቸው፡፡ ሁሉንም ባንዴ ለመፍታት አይቻልም፡፡ ስለዚህ ቅደም ተከተል ማበጀት ግድ ነው፡፡ አደገኞቹንና አጣዳፊዎቹን ከፊት ለፊት፣ ሌሎቹን ከኋላ አድርጐ መሰደር ያስፈልጋል፡፡ ከፊት ያሰለፍናቸውን ጊዜ አለመስጠትና ሳያወላዱ መምታት ከብዙ ጣጣ ይገላግለናል፡፡ ይህ ማለት ግን ያለጥንቃቄ መጋለብና መዝመት ማለት አይደለም፡፡ በዕውቅ እና በጥንቃቄ (Cautiously and consciously እንደሚሉት ነው ፈረንጆቹ፡፡ አያሌ የተጠላለፉ የሙስና ተግባራት አሉ፡፡ እንደ ዳንቴል አንዷ ክር ስትሳብ መዓት ክር ይተረተራል፡፡ ሙሰኛ ኢ-ፍትሐዊም ነው፡፡ ሙሰኛ ኢ ዲሞክራሲያዊም ነው፡፡ ሙሰኛ ኢ-መልካም አስተዳደር ነው፡፡ ሙሰኛ በስልጣን ባላጊ ነው፡፡ ሙሰኛ ዘማዊ የሚሆንበት ጊዜ አለ፡፡ ሁሉም ተጠራቅመው የተሰጡት አሉ፡፡ አንዳንዶቹ ብቻ እንደ ካንሰር የሆኑበት አለ፡፡ ካንዱ ወደአንዱ የሚዘምትም አለ፡፡ ስለዚህ ጉዳይ የፖለቲካ ምሁራን የሚሉንን መስማት ደግ ነው፡፡ “አልፎ አልፎ ስህተት ይፈጠራል፡፡ ዓለም ይህ ይሆናል ብለን ለመተንበይ በጣም አዳጋች ናት፡፡ ያም ሆኖ ሥልጣን ላይ ያሉ ሰዎች ጉድ እሚሆኑት ስህተት በመፈፀማቸው ሳይሆን ስህተቶቹን ለማስተካከል በሚጠቀሙበት ዘዴ ምክንያት ነው፡፡ እንደቀዶ ጥገና ሐኪም የተበላሸውን ክፍል ቆርጠው መጣል አለባቸው፡፡ ይቅርታ መጠየቅና ሰበብ አስባብ መፍጠር ደነዝ ቢላዎች ናቸው፡፡ ሰበባ ሰበቦች ማንንም አያረኩም፡፡ ይቅርታ ሲበዛም ብቃት ማነስን ነው የሚጠቁመው፤” ይለናል ሮበርት ግሪን የተባለው ፀሐፊ፡፡
ቆራጥ እንሁን፡፡ አጋርን ለማዳን ጋንግሪን መቁረጥና የመርዝን ሰንኮፍ መንቀል ዛሬ ግዴታ ነው፡፡ ማንኛውም ዓይነት ሙሰኛ የዕድገት ጠላት ነው፡፡ ፖለቲከኛ ስለሆነ ሙሰኛ ሊሆን አይችልም ብሎ ማሰብ የዋህነት ነው፡፡ ነጋዴም ቢሆን እንደዚያው ነው፡፡ አለቃም ሆነ ምንዝር ከሞሰነ ሙሰኛ ነው፡፡ በመሬት፣ በቤት፣ በቢሮ አሻጥር ሙስና ሙስና ነው፡፡ አገር በድርቅ ይጠቃል እየተባለ አያሌ ድጋፍ በሚያስፈልግበት ሰዓት እየመዘበረ በዋንጫ ጋጋታ በሠፊ ገበታ፣ አሸሸ ገዳሜ ሲል ይፋ የሚታየው ሙሰኛ፣ አልታየን ካለ ከተጠያቂነት አናመልጥም፡፡ ጠባቂውን ማን ይጠብቀው (Who guards the guard) የሚለውን ሳንዘነጋ ነው ታዲያ! የያዝ ለቀቅ አሠራር አገራችንን እጅግ አድርጐ ጐድቷታል፡፡ ያለው አማራጭ “ጅግራ ያዝ፤ ሩጫ ከፈለግክ ልቀቃት፣ ሥጋ ከፈለግክ እረዳት” የሚለውን ተረት በቅጡ መረዳት ነው፡፡

- በግለሰቡ ላይ የደረሱ የመብት ጥሰቶች በአፋጣኝ እንዲስተካከሉ ጠይቋል
- የዞን ዘጠኝ ጦማርያንን ሽልማት ለመቀበል ወደ ፓሪስ ሊጓዝ ነበር

    ተቀማጭነቱን በፈረንሳይ ያደረገው ሪፖርተርስ ዊዝአውት ቦርደርስ የተሰኘ አለማቀፍ ተቋም፣ የኢትዮጵያ መንግስት በቅርቡ ከእስር ከተለቀቁት የዞን ዘጠኝ ጦማርያንና ጋዜጠኞች አንዱ የሆነውን ዘላለም ክብረት፤ ከአገር እንዳይወጣ መከልከሉ እንደሚያሳስበው አስታወቀ፡፡
የዞን ዘጠኝ ጦማርያን በዘንድሮው የሪፖርተርስ ዊዝአውት ቦርደርስ የፕሬስ ነጻነት ሽልማት “የሲቲዝን ጆርናሊስት” ዘርፍ አሸናፊ ሆነው መመረጣቸውን ያስታወሰው ተቋሙ፣ ዘላለም ክብረት ጦማርያኑን ወክሎ ሽልማቱን ለመቀበል ባለፈው ሰኞ ወደ ፈረንሳይ ፓሪስ ሊሄድ ሲል፣ በኢትዮጵያ መንግስት የኢሚግሬሽን ሃላፊዎች ፓስፖርቱን በመቀማት ወደ አውሮፕላኑ እንዳይገባ መታገዱን ገልጿል፡፡ ከትናንት በስቲያ ባወጣው መግለጫው፡፡
የኢሚግሬሽን ባለስልጣናቱ ዘላለምና ሌሎች የዞን ዘጠኝ ጦማርያን ከዚህ በፊት ታስረው መቆየታቸውን በምክንያትነት በመጥቀስ ከአገር መውጣት አትችልም እንዳሉት የጠቆመው ተቋሙ፣ በጦማሪው ላይ የተጣለውን የጉዞ እገዳ በተመለከተ በአዲስ አበባና በፓሪስ ከሚገኙ የኢትዮጵያ መንግስት ባለስልጣናት ተጨማሪ መረጃ ለማግኘት ተደጋጋሚ ሙከራ ቢያደርግም እንዳልተሳካለት ገልጿል፡፡“በዘላለም ክብረት ላይ የተጣለው የጉዞ እገዳ ያልጠበቅነው ነው፤ አስደንግጦናል፡፡ ከእስር በተፈታበት ወቅት እንቅስቃሴውን የሚገድብ ምንም አይነት ክልከላ አልተጣለበትም፣ የተቀሩት የዞን ዘጠኝ አባላትም ባለፈው ጥቅምት ከተመሰረተባቸው የሽብር ክስ ነጻ ተደርገዋል፤ ፓስፖርቱን የተቀማበት ምክንያት አልገባንም፣ የሚመለከታቸው አካላት የተጣሱትን የዘላለምን መብቶች በአፋጣኝ  እንዲያስከብሩ እንጠይቃለን” ብለዋል የተቋሙ የአፍሪካ ዴስክ ሃላፊ ክሊ ካን ስራይበር፡፡ ዘላለምፓስፖርቱን በተቀማ ማግስት ወደ ፖሊስ ጣቢያ እንዲሄድ በተሰጠው መመሪያ መሰረት ወደ ፖሊስ ጣቢያ ማምራቱን፣ ምርመራ እየተደረገበት እንደሚገኝና ምርመራው እስካልተጠናቀቀ ድረስም ፓስፖርቱየማይመለስለት እንደተነገረው ተቋሙ በመግለጫ አስታውቋል፡፡


“በህገ መንግሥቱ የተደነገገውን የሳንሱር ክልከላ
የሚተገብር ውል ነው” አሳታሚዎች

   ብርሃንና ሠላም ማተሚያ ድርጅት፤ ጋዜጣ አሳታሚዎች እንዲፈርሙ ያዘጋጀው የህትመት ውል በህገመንግስቱ የተደነገገውን የሳንሱር ክልከላ የሚተገብር ነው ሲል የተቃወመው ዋቢ የግል ፕሬስ አሳታሚዎች የዘርፍ ማህበር፤ ጉዳዩን መንግስት በአጽንኦት እንዲመረምረው በደብዳቤ ማመልከቱን አስታወቀ
ብርሃንና ሰላም ማተሚያ ድርጅት በበኩሉ፤ የተዘጋጀው ውል ከሳንሱር መቅረት ህግ ጋር የሚያገናኘው ነገር የለም ብሏል፡፡
ብርሃንና ሠላም ማተሚያ ድርጅት በማተሚያ ቤቱ ለሚጠቀሙ የጋዜጣ አሣታሚዎች ህዳር 2 ቀን 2008 ዓ.ም በፃፈው ደብዳቤ፤ የተወሰኑ አሣታሚዎች ማተሚያ ቤቱ ያወጣው ደንብ ላይ የጋራ ውይይት እንዲደረግ በጠየቁት መሠረት በተደጋጋሚ ውይይት ተደርጐ ድርጅቱ ከአሣታሚዎቹ በተነሱ ነጥቦች ላይ ተገቢ ማብራሪያ የሰጠ ቢሆንም አሣታሚዎች እስካሁን ድረስ ውሉን እንዳልፈረሙ ጠቁሞ፣ እስከ ህዳር 30 ቀን 2008 ዓ.ም ውሉን ፈርመው እንዲልኩ አሳስቧል፡፡
ባለፈው ረቡዕ በውሉ ጉዳይ መወያየቱን ያስታወቀው የአሣታሚዎቹ ማህበር፤ ድርጅቱ ውል እንፈራረም ማለቱ ተገቢ መሆኑንና እንደሚያምንበትም ገልፆ፤ ነገር ግን በውሉ ከተዘረዘሩት አንቀፆች ውስጥ በህገመንግስቱ አንቀፅ 29 የተነሳውን ቅድመ ምርመራን የሚቃረን አንቀፅ በመካተቱ ውሉን ለመፈረም እንቸገራለን ብሏል፡፡ በህገ መንግሥቱ አንቀፅ 29 የአመለካከትና ሀሳብን በነፃ የመያዝና የመግለፅ መብት በንኡስ አንቀፅ 3 በተራ ቁጥር ሀ፤ “የቅድመ ምርመራ በማንኛውም መልኩ የተከለከለ ነው” የሚለውን የጠቀሱት አሳታሚዎቹ፤ የብርሃንና ሠላም ውል ይሄን ህግ የሚጥስ ነው ብለዋል፡፡
ማህበሩ የተቃወመው የውሉ አንቀፅ 10ኛ ቁጥር 1፤ “አታሚው በአሣታሚው እንዲታተም የቀረበለት የጽሑፍ ስክሪፕት ህግን የሚተላለፍ ስለመሆኑ ለማመን በቂ ምክንያት ካለው አላትምም የማለት መብት አለው” የሚለውንና በአንቀፁ ቁጥር 2፤ “አሣታሚው የህግ ተጠያቂነትን የሚያስከትል የህትመት ይዘት የማውጣት ዝንባሌ ያለው መሆኑን ለማመን በቂ ምክንያት ካለው በማናቸውም ጊዜ ውሉን ለማቋረጥ ወይም ለመሰረዝ ይችላል” የሚለውን ነው፡፡
ማህበሩ በውሉ ውስጥ የተካተቱትን እነዚህን ሁለት ንኡስ አንቀፆች እንደማይቀበልና ከውሉ መውጣት አለባቸው ብሎ እንደሚያምን ጠቁሟል፡፡
ለመንግስት ኮሙኒኬሽን ጉዳዮች ጽ/ቤት ሚኒስትር አቶ ጌታቸው ረዳ በላከው ደብዳቤም፤ እነዚህ የውል አንቀፆች በህገ መንግሥቱ የተከለከለውን ቅድመ ምርመራን የሚተገብሩ ስለሆነ መንግስት ጉዳዩን በአጽንኦት መርምሮ አንቀፆቹ ከውሉ እንዲወጡለት ጠይቋል፡፡
ማህበሩ ለብርሃንና ሠላም ማተሚያ ድርጅት በላከው ደብዳቤ፤ ቀደም ሲል በተካሄዱ ውይይቶች ላይ እነዚሁ አንቀፆች እስካልተወገዱ ድረስ ውሉን ለመፈረም እንደማይችሉ መግለፃቸውን በማስታወስ፣ በድጋሚ ፈርሙ የሚል ማሳሰቢያ መተላለፉ ተገቢ እንዳልሆነ ጠቁመው፤ ችግሩን ለመፍታት የሚያስችል ቀጣይ ውይይት እንዲካሄድም ሃሳብ አቅርበዋል፡፡
በማተሚያ ድርጅቱ የተዘጋጀው ውል ለፊርማ ከቀረበ ወደ 4 ዓመት ገደማ ሲሆነው አሳታሚዎችና ማተሚያ ቤቱ በጉዳዩ ላይ ተደጋጋሚ ውይይት ቢያደርጉም በውሉ ላይ ሙሉ ለሙሉ መግባባት አልቻሉም፡፡
የማተሚያ ድርጅቱ ሥራ አስኪያጅ አቶ ተካ አባዲ በበኩላቸው፤ የተዘጋጀው ውል አለማቀፍ ባህሪ ያለው መሆኑ ታምኖበት ሁሉም የመንግሥት ማተሚያ ድርጅቶች ተወያይተውበት ተግባራዊ የተደረገ ነው ብለዋል፡፡
አሳታሚዎቹ የተቃወሙት አንቀፅ፤ “አገርን የሚያፈርስ ዘገባ ካለ አላትምም” የሚል ነው ያሉት አቶ ተካ፤ እንደ አንድ የመንግሥት ተቋም፣ የህዝብንና የሀገርን ደህንነት የመጠበቅ ሃላፊነት ስላለብንና በህግም ስለምንጠየቅ ውሉን ለማስፈረም እንገደዳለን ብለዋል፡፡ “ውሉ በህገ መንግሥቱ ከተደነገገው የሣንሱር መቅረት ህግ ጋር የሚያገናኘው ነገር የለም፤ ሌሎች የመንግሥት ጋዜጦች ውሉን ፈርመው አገልግሎት እያገኙ ነው” ያሉት ሥራ አስኪያጁ፤ የግል ፕሬስ ባለቤቶችም ጉዳዩን የፖለቲካ ፍላጎት ማንፀባረቂያ ሊያደርጉት አይገባም ብለዋል፡፡
“አሁንም ያለ ውል መስራታችን ተገቢ አይደለም፤ ውሉን በተመለከተ ያቀረቡትን ቅሬታ የድርጅቱ ሥራ አስፈፃሚ ይመክርበትና ይወስናል፤ ከመንግሥት የሚሰጥ አቅጣጫ ካለም እናያለን” ብለዋል፤ አቶ ተካ አባዲ፡፡

   የኢትዮጵያ አየር መንገድ ለመጀመሪያ ጊዜ በኢትዮጵያውያን ሴት አውሮፕላን አብራሪዎች ብቻ ከአዲስ አበባ ወደ ታይላንድ ባንኮክ የደርሶ መልስ በረራ ከትናንት በስቲያ ማድረጉን አስታወቀ፡፡
አየር መንገዱ ዋና አብራሪም ሆነ ረዳት አብራሪ፣ ቴክኒንና የበረራ በቦይንግ 767 አስተናጋጆቹ እንዲሁም ተቆጣጣሪዎች ሙሉ በሙሉ ሴቶች ብቻ የሆኑበትን በረራ ለመጀመሪያ ጊዜ ያካሄደው “ቀጣይነት ላለው ልማት ሴቶችን ማብቃት” በሚል መርህ ነው ተብሏል፡፡በበረራው ወቅት ቲኬት ቆራጮች፣ የበረራ ደህንነት ባለሙያዎችና የደንበኞች እቃ ጫኞች ጭምር ሙሉ ለሙሉ ሴቶች ብቻ የነበሩ ሲሆን ተሳፊሪዎቹ ግን አብዛኞቹ ወንዶች እንደነበሩ ታውቋል፡፡
በቦይንግ 767 የተከናወነውን በረራ በዋና አብራሪነት ካፒቴን አምሣለ ጓሉ በረዳት አብራሪነት ሠላም ተስፋዬ መርተውታል፡፡አየር መንገዱ የተመሰረተበትን 70ኛ ዓመት በሚያከብርበት ዋዜማ በሴቶች ብቻ የተመራ በረራ ማከናወኑ ታላቅ ስኬት ነው ያሉት ዋና ሥራ አስፈፃሚው አቶ ተወልደ፤ ከአየር መንገዱ ሠራተኞች 30 በመቶዎቹ ሴቶች መሆናቸውንም ጠቁመዋል፡፡በሌላ በኩል የወንዶች የበላይነት የገነነበት እንደሆነ በሚነገርለት የዚምባቡዌ አየር መንገድ ባለፈው ማክሰኞ  ሙሉ በሙሉ በሴቶች የተመራ የአገር ውስጥ በረራ ከመዲናዋ ሀራሬ ወደ ቪክቶሪያ ፏፏቴ ማድረጉ ታውቋል፡፡ቦይንግ 737 – 200 አውሮፕላን በሀራሬ ሰማይ ላይ ያበረሩት ካፒቴን ቺና ማቲምባና ካፒቴን ሲምቢ ጴጥሮስ ሲሆኑ ዋና አብራሪዋ ካፒቴን ማቲምባ ከበረራው በኋላ ለጋዜጠኞች በሰጠችው አስተያየት፤ “ታሪክ ሰርተናል” ብላለች፡፡ ረዳት አብራሪዋ ሲምቢ በበኩሏ፤ “እንዲህ ያለውን ታሪካዊ በረራ በማከናወኔ እድለኛ ነኝ” ስትል ስሜቷን ገልፃለች፡፡የሁለቱን እንስቶች የተሳካ በረራ ያደነቁት የሀገሪቱ መገናኛ ብዙሃን፤ አየር መንገዳቸው የሴቶችን ድርሻ የበለጠ ለማስፋት መስራት እንዳለበት ጠቁመዋል፡፡በዚምባቢዌያኑ እንስቶች ኩራት እንደተሰማው የገለፀው አለማቀፉ የሴት አብሪሪዎች ማህበር፤ በአለም ላይ ካሉ አብራሪዎች የሴቶቹ ድርሻ 6 በመቶ ብቻ መሆኑን አመልክቶ፣ አገራት በዘርፉ በርከት ያሉ ሴት ባለሙያዎችን ማፍራት እንዳለባቸው ተናግሯል፡፡