Administrator

Administrator

Saturday, 29 September 2018 13:46

ሴቶች በግላቸው እራሳቸውን…

 ሴቶች በተፈጥሮአቸው ከሚኖራቸው የስነተዋልዶ ባህርይ አንዱ የወር አበባ ነው፡፡ ሴት ልጆች በአስራዎቹ እድሜ ክልል ሲደርሱ የሚያዩት የወር አበባ የሚፈጠረው የማህጸን ግድግዳ ጽንስ ይፈጠራል ከሚል ከተዘጋጀ በሁዋላ ጽንሱ መፈጠሩ ሲቀር ይፈራ ርስና ወደፈሳሽነት ተለውጦ ንጹህ ያልሆነ ደም ይፈሳል፡፡ የወር አበባ የሚቆየው ከ3-5 ቀን ድረስ ነው፡፡ የወር አበባ ተፈጥ ሮአዊ ሲሆን በመፍሰሱ ምክንያት በሰውነት ላይ የሚያደርሰው ጉዳት የሌለው ሲሆን በትክክ ለኛው ሁኔታ ካልፈሰሰ ግን በመጠኑ ያለመመቸትና የሕመም ስሜት ሊያስከትል ይችላል፡፡ በእ ርግጥ አንዳንድ ሴቶች በከፍተኛ ሁኔታ የሕመም ስሜት እንዳላቸው ይናገራሉ፡፡
የወር አበባ በሚመጣበት ወቅት የሚከሰተው የህመም ስሜት በሁለት ይከፈላል፡፡
primary dysmenorrhea፡- ይህ አይነቱ የህመም ስሜት በ90% ያህል ሴቶች ላይ የሚከሰት ሲሆን ይህ በአብዛኛው ሴቶቹ ሲያገቡ ወይም ልጅ ሲወልዱ መፍትሔ የሚያገኝ ነው፡፡
secondary dysmenorrhea ፡- ይህ ሁለተኛው የሕመም አይነት ሲሆን በዳሌ አካባቢና ከማህጸን ጋር በተያያዘ የሚከሰት ሕመም ነው፡፡ በእርግጥ መፍትሔው የሚገኘው የሚያማቸው ሴቶች በሕክምና ከተረዱ ነው፡፡
አንዳድ ሴቶች የወር አበባ በወር ሲመጣ ቀኑን ሳያስተካክል የሚመጣ መሆኑን ሲገልጹ ሌሎች ደግሞ በፍሰቱ የማነስና የመብዛት ሁኔታን ያስተውላሉ፡፡ ነገር ግን የወር አበባ የሚበዛባቸው ሴቶች ልብ ሊሉት የሚገባቸው ነገር አለ፡፡
በተፈጥሮ ጭንቀታም መሆን፤
በማህጸን ዙሪያ እጢ ወይንም ኢንፌክሽን ካለ እና ሌሎች ተያያዥ በሆኑ ምክንያቶች የወር አበባ በሚመጣበት ጊዜ መብዛትንና ሕመምን ሊያስከትል የሚችል መሆኑን ነው፡፡
ከወር አበባ ጋር በተያያዘ ሕመም ይሰማናል የሚሉ ሴቶች የሚገልጹትን ስሜት ከአንዲት ሴት በደረሰን መልእክት መመልት ይቻላል፡፡
‹‹…እኔ በእድሜዬ ወደ 32/ሰላሳ ሁለት አመት ይሆነኛል። የወር አበባ ከመጀመሪያውም እንደሌሎች ሴቶች በወቅቱ ወይንም በቶሎ ያላየሁ ሲሆን መምጣት የጀመረው በ18/አመት እድሜዬ ነው፡፡ ከዚያ ጊዜ ጀምሮም ልክ በወር አንድ ጊዜ ታማሚ ሆኛለሁ፡፡ አስቀድሞውኑ የሚጀምረኝ ሕመም አለ፡፡ ወገቤን ይከተክተኛል፤ማህጸኔ አካባቢ ጨምድዶ ይይዘኛል፤ የእራስ ምታት ጭምር ስለሚያመኝ በዚህ ጊዜ ሰው ባያናግረኝ እመርጣለሁ፡፡ ይህንን ሁኔታ ባለቤቴ ለረጅም ጊዜ ሊረዳው አልቻለም ነበር፡፡ እንዲያው አመልሽ ተለውጦ እንጂ የወር አበባ መም ጣት ባንቺ ብቻ አልተጀመረም ይለኝ ነበር። ነገር ግን አንድ ጊዜ …ተነሽና ወደሐኪም ቤት እንሂድ አለኝ፡፡ እኔም እሺ ብዬ ሔድኩ፡፡ ሐኪሙ እሱንም እኔንም አስቀምጦ ሁኔታውን ሲያ ስረዳ እዚያው ሐኪሙ ፊት ነበር ይቅርታ የጠየቀኝ፡፡ ከዚያ በሁዋላ ባለቤቴ በደንብ ይረዳኝ ጀመር፡፡ ባል አግብቼም ሆነ ልጅ ወልጄ ሕመሙ ግን አልተሻለኝም፡፡››
    ቤተልሔም ብስራት ከቤተል
በአንድ ወቅት ያነጋገርናቸው የማህጸንና ጽንስ ሕክምና እስፔሻሊስት ዶ/ር መብራቱ ጀምበር የሚከተለውን ብለው ነበር፡፡
…ከወር አበባ ጋር በተያያዘ የሚከሰተውን የህመም ስሜት በተለያየ መንገድ መግለጽ ይቻላል፡፡ ለሕክምና የሚመጡት ሴቶች እንደሚገልጹት ከሆነ የጡት ሕመም፤ የእራስ ምታት፤ የእግር ማበጥ፤ በወገብና በማህጸን አካባቢ የሚሰሙ ሕመሞች የመሳሰሉትቸ  ሊከሰቱ ይችላሉ፡፡ ለምሳሌም የማህጸን በር ጠባብ ከሆነ የሚፈሰውን ደም እንደልብ ስለማያስተላልፍ ማህጸን ደሙን ለማስወጣት ሲል በሚያደርገው ትግል በሴቶቹ ላይ ሕመም ሊያስከትል ይችላል፡፡ ይህ አይነቱ ሕመም ምንም አይነት ምክንያት ሳይኖር የሚፈጠር የህመም ስሜት ሲሆን እንደእጢ የመሳሰሉ ችግሮች ባሉበት ሁኔታ ግን ምክንያታዊ የሆነ ሕመም ነው፡፡ በእርግጥ ብዙውን ጊዜ ከወር አበባ ጋር ተያይዞ የሚከሰት ችግር በጋብቻ እና ልጅ በመውለድ ምክንያት ሊወገድ የሚችል ሲሆን አንዳንድ ሴቶች ላይ ያለው አጋጣሚ ግን መድሀኒት ከመውሰድ እስከ ቀዶ ሕክምና የሚያደርስ ሕክምና ሊያስፈልጋቸው የሚችል ይሆናል፡፡ ነገር ግን የወር አበባን ለማስወገድ ሲባል ብቻ ጋብቻ እና ያልተፈለገ እርግዝና እንዳይኖር መጠንቀቅ እንደሚያስፈልግ በወቅቱ ዶ/ር መብራቱ ጀምበር ገልጸው ነበር፡፡
በወር አበባ ጊዜ ለሚከሰት ሕመም እንደማስታገሻ ከሚታሰቡት መካከል የአመጋገብ ሁኔታዎ ችም ቸል የማይባሉ ናቸው፡፡ አንዳድ ሴቶች እንደሚመሰክሩት የአመጋገብ ሁኔታን በመለወጣ ቸው ምክንያት ሕመሙ እንደታገሰላቸው ያሳያል፡፡ የአስተሳሰብ ሁኔታን ለማስተካከል የሚረዱ እንቅስቃሴዎች ለምሳሌም እንደ ዮጋ የመሳሰሉት ሊረዱ ይችላሉ፡፡
አመጋገብ፡-
በካልሲየም የበለጸጉ ምግቦችን መመገብ… ባቄላ፤ ጥቁር አረንጉዋዴ ቀለም ያላቸው አትክልቶች እንደ..ጎመን የመሳሰሉ ..ወዘተ…
ከሰውነት ውስጥ መመረዝን የሚያስወግዱ ምግቦችን መመገብ…ፍራፍሬዎች… ቲማቲም…ወዘተ…
ተፈጥሮአዊ ይዘታቸውን የለወጡ… እንደ የተፈተገ ስንዴ ከመሳሰሉ የሚሰሩ ምግቦችን … ነጭ ዳቦ… ፓስታ እና ስኩዋር የመሳሰሉትን አለመመገብ…
ቀይ ስጋን መመገብ አለማብዛት እና በቀዝቃዛ ውሀ ውስጥ የሚገኝ አሳን እንዲሁም ፕሮቲን ለማግኘት የሚረዳውን እንደ ባቄላ የመሳሰሉትን መመገብ…
ጤናማ የሆኑ የአትክልትና የወይራ ዘይት መጠቀም…
በአመጋገብ ውስጥ የአኩሪ አተር ወተትን ማካተት፤ ስብ ያላቸውን ምግቦች መቀነስ፤
በንግድ ሱቆች የተደረደሩ …ተዘጋጅተው የሚሸጡ እንደ ኩኪስ፤ ኬኮች፤ የተጠበሰ ድንች፤ እና ባጠቃላይም በኢንደስትሪ ተሰርተው የሚቀርቡ ምግቦችን እና ቅቤ የመሳሰሉ ትን ነገሮች አለመመገብ…
እንደ ቡና ያሉ፤ አልኮሆል እና ሲጋራ ማጤስ የመሳሰሉትን ከልምድ ማስወገድ…
በቀን ከ6-8/ብርጭቆ የተጣራ ውሀ መጠጣት…
በቀን ውስጥ ለ30/ደቂቃ ያህል በሳምንት ለ5/ቀናት የአካል ብቃት እንቅስቃሴ መስራት፤
ከላይ የተጠቀሰው የአመጋገብ ልማድ ለማንኛውም ሰው የሚመከር ሲሆን በተለይም የወር አበባ በሚመጣበት ወቅት ሕመም የሚሰማቸው ሴቶች አመጋገባ ቸውን በተቻለ መጠን በተጠቀሰው መልክ ማስተካከል ቢችሉ ሕመሙ እንደሚቀንስላቸው መረጃዎች ይጠቁማሉ፡፡ ከዚህ በተጨ ማሪም አመጋገብን ለመደገፍ ሲባል ከሚወሰዱ መካከል የሚከተሉት ተጠቃሾች ናቸው፡፡
ኦሜጋ -3/ ለምሳሌ የአሳ ዘይት በቀን 6/ግራም ቢወሰድ በወር አበባ ጊዜ የሚሰማውን ሕመም ሊቀንስ ይችላል፡፡ ነገር ግን ለምሳሌ እንደ ደም ማቅጠኛ ያሉ መድሀኒቶችን ለሚወስዱ ሰዎች አደገኛ ሊሆን ስለሚችል ሐኪምን አስቀድሞ ማማከር ይገባል፡፡  
ካልሲየም በወር አበባ ጊዜ የሚከሰትን ሕመም ከማስታገስ በተጨማሪ ለጤናማ አጥንት እና ጡንቻዎች መገንባት አስፈላጊ ነው፡፡ አንዳንድ ጥናቶች እንደሚያሳዩት ካልሲየም ሲትሬት ማለትም በካልሲየም መልክ የተሰራው ሰውነት በቀላሉ የሚቀበለው ስለሆነ የወር አበባ ሕመምን ለማስታገስ ይረዳል፡፡ አንዳንድ ጥናቶች እንደሚጠቁሙት ግን የወር አበባው ከጀመረ በሁዋላ ቢወሰድ ጥቅም ላይሰጥ ይችላል፡፡
በአጠቃላይም ቫይታን ዲ፤ ቫይታሚን ኢ፤ እና ማግኔዥየም የወር አበባ ከመጀመሩ አስቀድሞ ቢወሰድ የህመም ስሜትን ሊቀንሱ እንደሚችሉ መረጃው የሚጠቁም ሲሆን ለማንኛውም ግን ሐኪምን ማማከር እንደሚጠቅም ይገልጻል፡፡
የወር አበባ ሕመም የሚሰማቸው ሴቶች በግላቸው እራሳቸውን መርዳት ይጠበቅባቸዋል፡፡ ሙቀት እንዲሰማቸው ማድረግ፤ጀርባን ጫን ጫን እያሉ መግፋት ወይንም እንደመታሸት ማድረግ፤ ሴትየዋ የህመሙ ስሜት እንዳይሰማት ማረሳሳት፤ሕመሙን እረስታ እንድትረጋጋ ማድረግ፤ የመሳሰሉት ዘዴዎች ይጠቅማሉ፡፡
ከዚህ ውጭ የአካል ብቃት እንቅስቃሴ ማድረግ በወር አበባ ወቅት ለሚሰማ ሕመም ማስታገ ሻነት ብቻ ሳይሆን በማንኛውም ወቅት የሚጠቅም በመሆኑ የእግር ጉዞን ጨምሮ ሌሎች እንቅ ስቃሴዎችን ማድረግ ለጤናማነት ይረዳል፡፡

 ጃማይካዊቷ ዜላ ግሪፍትስ ጌይል  ከክሁል ሆሊስቲክ ዴቨሎፕመንት ማዕከል ጋር በመተባበር ‹‹ኢነር ዚል ሬጌ ሮቢክስ›› የሚባለውን ልዩ የዳንስና ኤሮቢክስ እንቅስቃሴ ልታሰለጥን ነው፡፡ ልዩ የዳንስና ኤሮቢክስ እንቅስቃሴ  ስልጠናው ደምበል አካባቢ በሚገኘው ሬቲና ህንፃ 9ኛ ፎቅ ላይ ነገ በ10 ሰዓት የሚጀመር ሲሆን በየሳምንቱ እሁድ እንደሚቀጥል የዳንስ አሰልጣኟ ዜላ ግሪፍትስ ጌይል ለአዲስ አድማስ ገልፃለች፡፡
 ነገ በክሁል ሆሊስቲክ ዴቨሎፕመንት ማዕከል ለስልጠናው በተዘጋጀው የመክፈቻ ስነስርዓት የአፍሮ ቢትና የአፍሮ ሬጌ ዳንስ አሰልጣኞች እንዲሁም የዮጋ ኢንስትራክተር በተጋባዥነት ይሳተፉበታል፡፡ የ‹‹ኢነር ዚል ሬጌ ሮቢክስ›› ስልጠናው ለሁሉም የእድሜ ደረጃ እና ፆታ እንደሚሆን ሲታወቅ ክፍያው በግለሰብ ለአንድ ቀን 200 ብር እንዲሁም ለአንድ ወር 600 ብር እንደሆነ ተገልጿል፡፡  ዜላ ግሪፍትስ ጌይል  በእንግሊዝ ሳውዝሃምፐተን ከሚገኘው ዩኒቨርስቲ ኦፍ ዊንቸስተር በዳንስ ሙያ ማሰትሬት ዲግሪዋን ያገኘች ሲሆን ‹‹ኢነር ዚል ሬጌ ሮቢክስ›› የምትለውን ልዩ አይነት የዳንስ እንቅስቃሴ በመፍጠር ስትንቀሳቀስ ከ15 ዓመታት በላይ ሆኗታል፡፡ ‹‹ኢነር ዚል ሬጌ ሮቢክስ›› በዳንስ ችሎታ እያንዳንዱ ሰው ያለውን ውስጣዊ  ኃይልና ፈጠራ ከኤሮቢክስ በማጣመር እየተዝናና የሚንቀሳቀስበት ነው፡፡ በኢትዮጵያ መኖር ከጀመረች ከ8 ዓመታት በላይ የሆናት ዜላ ግሪፍትስ ጌይል፤ በዳንስ አሰልጣኝነት እና አስተማሪነት በሳንፎርድ ኢንተርናሽናል ስኩል፤ በላዮንሃርት፡ በማያ እና በአንድነት አካዳሚዎች ስታገለግል ቆይታለች፡፡

  • ድርጊቱ አሳፋሪና የኢትዮጵያውያን የውርደት ታሪክ ነው
       - ጠ/ሚ ዐቢይ
     • በተፈጸመው ጥቃት እንደ ኢትዮጵያዊነቴ አፍሬአለሁ
       - ፕ/ር ብርሃኑ ነጋ
     • ከኢትዮጵያዊነት ባህል የዘለለና ከሰው ልጅ ሞራል ያፈነገጠ ነው
        - ቴዲ አፍሮ
     • ኢትዮጵያውያን የተፈተንበት ነው፤አይዟችሁ እናልፈዋለን
       - አርቲስት ታማኝ
 

     በቡራዩ በዜጐች ላይ ለደረሰው አሠቃቂ ግድያ፣ ዘረፋና መፈናቀል መንግሥት የማያዳግም ሕጋዊ ርምጃ እንዲወስድ የፖለቲካ መሪዎች፣ዝነኛ አርቲስቶች፣ አክቲቪስቶችና ታዋቂ ግለሰቦች የጠየቁ ሲሆን፣ በሺዎች የሚቆጠሩ የጥቃት ተጎጂዎችንና ተፈናቃዮችን ሲጎበኙና ሲያጽናኑ ሰንብተዋል፡፡
የአዲስ አበባ ነዋሪዎች በተለይም ወጣቶች ከተፈናቃዮቹ ሳይለዩ ላሳዩት ኢትዮጵያዊ ፍቅርና ሰብአዊነት ከተጎጂዎቹም ሆነ ከጎብኚዎች ከፍተኛ ምስጋና ጎርፎላቸዋል፡፡
ወትሮም ኢትዮጵያዊነት ሲመቱት እንደሚጠብቀው ምስማር፣ በመከራ የሚጸና ነው፡፡ በቡራዩና አካባቢው የተፈጸመው ግፍ አሳዛኝ ቢሆንም የታየው የወገናዊነትና የብርታት መንፈስ ኢትዮጵያዊነት በመከራ የሚጸና መሆኑን አስመስክሯል፡፡ ተጎጂዎቹን በተጠለሉበት ሥፍራዎች ተገኝተው የጎበኙት የፖለቲካ መሪዎችና የጥበብ ባለሙያዎች የተንጸባረቀው ስሜትና መልዕክትም ይኸው ነው፡፡ ኅዙነ ልብ ቁፅረ ገጽ ሆነው ተጎጂዎችን በመድሃኔአለም ት/ቤት የጎበኙት ጠ/ሚኒስትር ዐቢይ አህመድ፤ “ድርጊቱ አሳፋሪና የኢትዮጵያውያን የውርደት ታሪክ ነው፤” ብለዋል፡፡ መንግሥታቸው ተፈናቃዮችን ለማቋቋም የሚቻለውን ሁሉ እንደሚያደርግ የጠቆሙት ጠ/ሚኒስትሩ፤ ከእንግዲህ ጉልበተኞችን እንደማይታገሥም አስጠንቅቀዋል፡፡
በአካባቢው ለተፈጠረው ግጭትና ጥቃት መነሻ ምክንያቱ የአንዲት የ6 ዓመት ሕፃን በአሠቃቂ ሁኔታ ተገድላ መገኘት መሆኑን የጠቆሙት የኦሮሚያ ክልል ርዕሰ መስተዳድር አቶ ለማ መገርሳ፤ ይህን አጋጣሚ ለውጡን ለመቀልበስ የሚፈልጉ ኃይሎች ተጠቅመውበታል፤ ብለዋል። የክልሉ መንግሥት ከእንግዲህ ለእንዲህ ያለው ብሔር ተኮር ጥቃት ትዕግሥት እንደሌለው የጠቆሙት ፕሬዚዳንት ለማ፤ ድርጊቱም የኦሮሞን ሕዝብ አይወክልም፤ ብለዋል፡፡
ተጐጂዎችን በርካታ የፖለቲካ መሪዎችና ታዋቂ ግለሰቦች በተጠለሉበት ተገኝተው የጐበኙ ሲሆን፤ ከእነዚህ መካከልም የአርበኞች ግንቦት 7 አመራሮች ፕ/ር ብርሃኑ ነጋ እና አንዳርጋቸው ጽጌ ይገኙበታል፡፡ ድርጊቱ ዲሞክራሲን ያለ አግባብ መጠቀም በመሆኑ፣በኢትዮጵያዊነቴ አፍሬአለሁ፤ ብለዋል፡፡ በአጥፊዎች ላይም ህጋዊ እርምጃ እንዲወሰድ አሳስበው፤ለዚህም መንግስት የሚከፍለው መስዋዕት ካለ ለመክፈል ዝግጁ እንደሆኑ ተናግረዋል፡፡
አርቲስትና አክቲቪስት ታማኝ በየነም በተጎጂዎቹ መጠለያ ተገኝቶ እያነባ ሃዘኑን ከገለጸ በኋላ “አሁን ኢትዮጵያውያን የተፈተንበት ወቅት ላይ ነን፤ አይዟችሁ እናልፈዋለን” በማለት ተጎጂዎቹን ያጽናና ሲሆን ኢትዮጵያውያን Go Fund me በተሰኘው የማኅበራዊ ድረ ገፅ የእርዳታ ማሰባሰቢያ አማካኝነት ወገኖቻቸውን እንዲያቋቁሙ በተማጸነው መሰረት፣በ24 ሰዓት ውስጥ ከ2 መቶ ሺህ ዶላር በላይ (9 ሚ. ብር ገደማ) ማሰባሰብ መቻሉ ታውቋል፡፡  
አርቲስት ቴዎድሮስ ካሣሁን (ቴዲ አፍሮ) በበኩሉ፤በተጎጂዎች ላይ በደረሰው ጥቃት ማዘኑን ገልጾ፤ድርጊቱ ከኢትዮጵያዊነት ባህል የዘለለና ከሰው ልጅ የሞራል ህግም ያፈነገጠ ነው፤ከዚህ በኋላ መደገም የለሌበት” ብሏል፡፡ ከባለቤቱና ጓደኞቹ ጋር ተጎጂዎቹን የጎበኘው አርቲስቱ፤ለጥቃቱ ተጎጂዎች ማቋቋምያ ይሆን ዘንድ የ1 ሚሊዮን ብር ድጋፍ ያደረገ ሲሆን ለዚህ ሳምንት ተላልፎ የነበረውን የሙዚቃ ኮንሰርቱንም እንደሰረዘ አስታውቋል - “ወገኖቼ ባዘኑበት ሁኔታ ኮንሰርት የማቀርብበት አንጀት የለኝም” በማለት፡፡
ፖሊስ በበኩሉ፤ እስካሁን ከጥቃቱ ጋር በተገናኘ ከ500 በላይ ተጠርጣሪዎችን በቁጥጥር ስር ማዋሉን ገልጾ፤ ከዚህ በኋላ ለሚፈጠር ተመሳሳይ ችግር ምህረት የለሽ እርምጃ እንደሚወስድ አስታውቋል፡፡

 ከዕለታት አንድ ቀን ጅቦች በጠፍ ጨረቃ ተርበው የሚበላ ፍለጋ ሲዘዋወሩ አንድ ግዙፍ ዝሆን ገደል ገብቶ ሞቶ አዩ፡፡
አንደኛው ጅብ - በረሀብ ከምንሞት እንግባና እንብላው
ሁለተኛው ጅብ - ገደሉ በጣም ሩቅ ነው፡፡ እንኳን ገብተን ሆዳችን ሞልቶ እንዲሁም ለመውጣት አዳጋች ነው፡፡ ስለዚህ መዘዋወራችንን እንቀጥልና የረፈደበት አህያ እንፈልግ፡፡
ሦስተኛው ጅብ - እንግባና ከበላን በኋላ እንደጋገፍና አንዳችን አንዳችን ትከሻ ላይ እየወጣን ከገደሉ እንወጣለን፡፡
አራተኛው ጅብ - ከገባን በኋላ እናስብበታለን
አንደኛው ጅብ - በድምፅ ብልጫ እንለየው
ሁሉም በድምፅ ብልጫ ይሁን በሚለው ሀሳብ ተስማሙ፡፡
አንደኛው ጅብ - እሺ፤ እንግባና በልተን እናስብበታለን የምትሉ?
ሁሉም እጃቸውን አወጡ፡፡
በሙሉ ድምፅ እንብላው አሉና ተግተልትለው ገቡ፡፡
ለአንድ ሁለት ሦስት ቀን ፈንጠዝያ ሆነ፡፡ ዋለ አደረና የዝሆን መቀራመቱ ጥጋብ አበቃና፣ ረሀብ በተራው ይሞረሙራቸው ጀመር፡፡
እንደተገመተውም ከገደሉ መውጫው ዘዴ ሊገኝ አልተቻለም፡፡
እየተራቡ መተኛትም ሆነ ዕጣ-ፈንታቸው፡፡ አንድ ሌሊት አንደኛው ጅብ ጐኑ ላለው ጅብ፤ “በጣም የተኛውንና ዳር ያለውን ጅብ ለምን አንበላውም?” ሲል ሀሳብ አቀረበ፡፡ አንዱ ለአንዱ እያማከረ፣ ዳር ላይ ለጥ ያለው ላይ ሰፈሩበት፡፡ ለአንድ ሁለት ቀን ፈንጠዝያ ሆነ፡፡
እንደገና ረሀብ ሆነ፡፡ በዚያው ተዘናግቶ በተኛው ተረኛ ጅብ ላይ እየፈረዱ፣ በመጨረሻው ሁለት ቀሩ፡፡ ብዙ ለሊት እየተፋጠጡ አደሩ፡፡ ሆኖም መድከም አይቀርምና አንዱ ደክሞት ተኛ። የነቃው በላው፡፡ ጥቂት ሰነበተና እራሱም በረሀብ ሞተ!
*   *   *
የሀገራችን የሙስና ደረጃ ገና ያልተጠረገ በረት ነው፡፡ “አህያም የለኝ ከጅብም አልጣላ” ብለን የምንዘልቀው እንዳልሆነ ካወቅነው ውለን አድረናል፡፡ “ሙስናው በአዲስ መልክ ሥራ ቀጥሏል፡፡” እንዳንል፣ መረር ከረር ብሎ መገታት እንዳለበት መገንዘብ ያሻል፡፡ ብርቱ ጥንቃቄና ብርቱ እርምጃ ግድ ነው፡፡ “ግርግር ለሌባ ያመቻልና” የህዝቡን ፀጥታ የሚያደፈርስን ሁኔታ በችኮላም ሳንደናገር፣ በመኝታም ሳንዘናጋ በአስተውሎት መጓዝና ፍሬ ያለው ሥራ መስራት ያሻል፡፡ በየትኛውም አገር ለውጥን ተከትሎ የሚመጣ አደናጋሪ ሁኔታ ይከሰታል፡፡ “የምጣዱ እያለ የእንቅቡ መንጣጣቱም” ሆነ፤ “የቆጡን አወርድ ብላ የብብቷን ጣለች” መባሉ የነበረ፣ ያለና ወደፊትም የሚኖር በመሆኑ፤ ነፃ አስተሳሰቡን እጅግ ልቅ ሳናደርግ፣ ግትርነቱንም (die-hardism) እጅጉን ሳናከርረው፣ በሥነ ሥርዓትና በዲሲፕሊን መራመድ ብቻ ነው የሚጠበቅብን። የረፈደ ነገር ያለ ቢመስለን አይገርምም! የአጭር ጊዜ ለውጥ ነውና! አመለካከታችን እስኪጠራ፣ በሀገራችን ህዝብ ዘንድ ብትሰራም ትኮነናለህ - ባትሰራም ትኮነናለህ (Do, damned! Don’t damned) ነውና፣ የያዝነውን መንገድ አለመልቀቅ ረብ ያለው እርምጃ ነው፡፡ ሰላምን ማደፍረስም ለሙስና ማራመጃም መከላከያም ሊሆን የሚችል አደገኛ መሣሪያ ነው! ዞሮ ዞሮ “ከጅብ ጅማት የተሰራ ክራር ቅኝቱ ልብላው - ልብላው ነው” ከሚለው ተረት አይዘልም! ወንጀሎችን እንቆጣጠር! የመሣሪያ ዝውውርን በሕግ የበላይነት ሥር እናድርግ! “ጦር ሜዳ ማህል ግጥም አታነብም” እንደሚባል አንዘንጋ! ዘረፋን እንቋቋም! ያለ መስዋዕትነት ድል የለም! ከመጠምጠም መማር ይቅደም! የዕውቀትንና የባለሙያን ግብዓት በየፕሮግራሞቻችን ውስጥ ቀዳሚ እናድርግ፣ ከዘርና ከጐሣ ግጭት ወጥተን፣ በዲሞክራሲና በሕግ የበላይነት ራሳችንን እንገንባ! የዴሞክራሲያዊነት እንጂ የገዥነትና የተረኝነት ስሜት የትም አያደርሰንም!

 የኢትዮጵያ የጽንስና ማህጸን ሀኪሞች ማህበር በአሜሪካ ከሚገኘው የአሜሪካን የጽንስና ማህጸን ሐኪሞች ኮሌጅ ጋር በመተባበር የተለያዩ ፕሮጀክቶችን ቀርጾ ደጋፍ በሚያደርጉ ድርጅቶች አጋዥነት ስራ ከጀመረ እነሆ ሁለት አመታት ተቆጥረዋል፡፡ በእነዚህ ሁለት አመታት ጊዜ ውስጥ የተሰሩ ስራዎችን በሚመለከት አንዳንዶቹን እንደሚከተለው ለንባብ ብለናል፡፡
RESIDENCY: -
ከጠቅላላ ሐኪምነት ወደ ጽንስና ማህጸን ሕክምና እስፔሻሊስትነት የሚሰለጥኑ ባለሙያዎች በአገር አቀፍ ደረጃ በተመሳሳይ የትምርት መመሪያ እንዲሰለጥኑና ብቃት እና ጥራት ባለው መንገድ ለህብረተሰቡ አገልግሎት እንዲሰጡ የሚያስችል ስራ ከጤና ጥበቃ እና ከትምህርት ሚኒስቴር ጋር በመሆን በጋራ ስራ ተሰርቶአል፡፡ ለሚማሩ ሰዎች ጥሩ ትምህርት መስጠት፤ ጥሩ ጥናትና ምርምር ማድረግ ፤የተሻለና ጥሩ የሆነ ሕክምና መስጠት የሚሉትን ነጥቦች ተግባራዊ ማድረግ የሚያስፈልግበት ምክንያትም የድህረ ምረቃ ትምህርቶቹ ከበሽተኛ ጋር የተገናኙ በመሆናቸውና ሐኪሙ ብዙ እናቶችን በሕክምናው አገልግሎት የመርዳት ኃላፊነት ስለአለበት በጥሩ ሁኔታ መሰራት እንዳለበት ስለታመነ ነው፡፡
ETHICS: -  
ሌላው የፕሮጀክቱ ዘርፍ የጽንስና ማህጸን ህክምና ባለሙያዎች የስነምግባር መመሪያን መቅረጽ ነው፡፡ የማህጸን እና ጽንስ ሐኪሞች ለሕመምተኛው መደረግ ያለበት የትኛው ነው ?የሚለውን ለመወሰን የሕመም ተኛው ፈቃድ፤ የሚኖረው አቅም የመሳሰሉት ሁሉ የሚያስፈልጉ ሲሆን ይህንን በትክክ ለኛው መን ገድ ለመምራት የሚያስችል የስነ ምግባር መመሪያ  በመዘጋጀት ላይ ነው ፡፡
CME: -
የህክምና ባለሙያዎች በስራ ላይ ባሉባቸው ጊዜያት እውቀታቸውን ከተለያዩ ሳይንሳዊ ግኝቶች እና አሰራሮች አንጻር የሚፈትሹባቸው ቀጣይነት ያለው ስልጠና እንዲያገኙ ማገዝ አንዱ  የESOG_ACOG ፕሮጀክት አቅጣጫ ነው፡፡ የጽንስና ማህጸን ሐኪሞች በዚህ ዘርፍ ጊዜው በሚፈቅደው የአገልግሎት አሰጣጥ ውስጥ እንዲያልፉ የሚያስችል አሰራር ነው፡፡
LEADERSHIP: -
የአመራር ብቃትን ማጎልበት ለጽንስና ማህጸን ሐኪሙ እጅግ ጠቃሚ በመሆኑና በስራ ላይ ያሉ ጉድለቶችን ለማስተካከል የሚረዳ በመሆኑ ባለሙያዎቹ በተወሰኑ ጊዜያት ስልጠና እንዲወስዱ እየተደረገ ነው፡፡ Transformational leadership በሚል የማህጸንና ጽንስ ሕክምና ባለ ሙያዎች መሰልጠናቸው በተለይም በተለያዩ ዩኒቨርሲቲዎች ውስጥ የማህጸንና ጽንስ ሕክምና ሙያን በማስተማር ላይ ለሚገኙት እጅግ ጠቃሚ ነው፡፡
ከተጠቀሱት በተጨማሪ የኢትዮጵያ የጽንስና ማህጸን ሐኪሞች ማህበር ቀደም ብሎ የጀመራ ቸውን ሳይንሳዊ ምርም ሮችን የሚያሳትምበት ጆርናልና ፤በተለያዩ የመገናኛ ብዙሀን ለህብረ ተሰቡ ስለጤንነቱ እንዲያ ውቅና አስቀድሞ እራሱን እንዲከላከል የሚያስችል ስራ የሚሰራባ ቸውን የመገናኛ ብዙሀን ስራዎች ማሳደግና የተሻለ ጥራት እንዲኖራቸው እገዛ ከማድረግ ባሻገር ሐኪሞች ባሉበት ቦታ ሆነው በኢንተርኔት አማካኝነት ትምህርትና መረጃዎችን እንዲያገኙ የማድረግ እና ሌሎችንም ተያያዥነት ያላቸውን ስራዎችን በመተግበር ላይ ነው፡፡
የኢትዮጵያ የጽንስና ማህጸን ሐኪሞች ማህበር ከሚቺጋን ዩኒቨርሲቲ (CIRHT) The Central For International Reproductive Health Training Of The University of Michigan ) በሚገኝ የገንዘብ ድጋፍ ለአምስት አመት ሊተገብረው የታሰበው ፕሮጀክት በሁለት አመቱ ወደ ኢትዮጵያ ፌደራላዊ ዲሞክራሲያው ጤና ጥበቃ ሚኒስቴር እንዲዛወር የመደረጉን ምክንያት ፕሮጀክቱ ስራውን ሲጀምር የኢሶግ ቦርድ ፕሬዝዳንት የነበሩት የማህጸንና ጽንስ ሕክምና እስፔሻሊስት  የሆኑት ዶ/ር ደረጀ ንጉሴ ለዚህ እትም አብራርተዋል፡፡
ዶ/ር ደረጀ እንደገለጹት ‹‹… ከአሜሪካ የማህጸንና ጽንስ ሐኪሞች ማህበር  ጋር የተጀመረው ፕሮጀክት ጽንሰ ሐሳብ ኢሶግ  ከነበሩት ስትራቴጂክ ዶክመንቶች ውስጥ አንዱ በተለይም እንደውጭው አቆጣጠር ከ2012-2016/ የነበረውን የአምስት አመት ተግባራት በሚያመላክተው ውስጥ ማህበሩ በዚህ ፕሮጀክት ስንፈጽማቸው የነበሩትን ተግባራት እና ሌሎችንም ማህበሩ ከነበረው ራእይና ተልእኮ ጋር የተያያዘ ስለሆነ ይህንን ተግባር ዋነኛ ማድረግ ይገባል የሚል እቅድ ነበረ፡፡ስለዚህም እኔ የቦርድ ፕሬዝዳንት ሆኜ ስመረጥ ከ2014/እንደውጭው አቆጣጠር ጀምሮ ዶክመንቱን በመፈተሸ ከላይ የተዘረዘሩትን ተግባራት ለመምራት የሚያስችለን የኢትዮ ጵያ የማህጸንና ጽንስ ሕክምና ኮሌጅ መመስረት ያስፈልጋል የሚል እምነት አደረብን፡፡ ስለዚ ህም ሶስት ልምድ ያላቸው ሐኪሞች ተመድበው ስራውን እንዲከታተሉ ሲደረግ እኔም ነበርኩ በት፡፡ ይህንን ጉዳይ በስራ ከምናገኛቸው የተለያዩ የማህጸንና ጽንስ ሕክምና ባለሙያዎች  ጋር በመመካከር ስራው ከአሜሪካ የማህጸንና ጽንስ ኮሌጅ ጋር የምንሰራበት መንገድ ስለተመቻቸ June/ 2016/  የመግባቢያ ሰነዱ ተፈርሞአል፡፡
ዶ/ር ደረጀ ንጉሴ አስከትለው እንደተናገሩትም በኢሶግ ስትራቴጂክ ዶክመንት ላይ የተገለጸው በውጭው አቆጣጠር በ2020/ የኢትዮጵያ የማህጸንና ጽንስ ኮሌጅ እንደሚመሰረት ነው፡፡ የተጀ መሩት ስራዎች በአምስት አመት ጊዜ ውስጥ ሲያልቁ እራሱን የቻለ ኮሌጅ ተመዝግቦ ስራ ይጀምራል የሚል እቅድ ተነድፎ ነበር፡፡ ነገር ግን ከድጋፍ አድራጊዎች ወገን ባልታሰበ ሁኔታ የሚገኘው እገዛ በውጭው አቆጣጠር ከሴፕቴምር 30/2018/በሁዋላ እንደማይቀጥል ስለተነገረን ይህ ዱብእዳ እንደሚባለው አስደንጋጭ ዜና ነበር፡፡ ይህ ሁኔታ በአለምአቀፍ ደረጃ ካለው ድጋፍ የማድረግ እንዲሁም የገንዘብ አሰጣጥ ፍሰትና በተወሰነ መልኩም የጤና ጥበቃ ሚኒስቴርም ከአሁን በሁዋላ ስራውን እየመራ መቀጠል ይችላል ከሚል እምነት ጋር የተያያዘ ነው፡፡ ስለ ዚህም የአሜሪካው የማህጸንና ጽንስ ኮሌጅ የሚያገኘው የገንዘብ ድጋፍ ስለሚቋረጥ በቀጣይነት ከኢሶግ ጋር ለመስራት ምቹ ሁኔታ አለመኖሩን ተነግሮን ፕሮጀክቱ እንዲቋረጥ ተገድዶአል፡፡›› ብለዋል፡፡
የተጀመሩት ስራዎችን ቀጣይነት በሚመለከት ዶ/ር ደረጀ እንዳሉት‹‹…ኢሶግ ላለፉት 27/ አመ ታት በኢትዮጵያ የስነተዋልዶ ጤና ላይ ብዙ ሰርቶአል፡፡ በዚህም የተነሳ በተለያዩ የስነተ ዋልዶ ጤና ዙሪያ ከተለያዩ ድጋፍ አድራጊዎች ጋር የሰራ በመሆኑ ጥሩ አጋር መሆኑን ማሳ የት የቻለ ማህበር ነው፡፡ ስለዚህም አሁን የተጀመሩትን በጎ ስራዎች ከሌሎች አጋር ድርጅቶች ጋር በመሆን መቀጠል ይቻላል፡፡ አሁን ፕሮጀክቱ ተቋርጦአል ቢባልም ለተወሰኑ ወራት ድጋፉ እንደሚቀጥል ቃል የገቡ በመሆኑ ለወደፊትም ከእነሱው ጋር ይቀጥል ወይንም ስራውን እየሰራን ሌሎች ድጋፍ አድራጊዎችን ማፈላለግ ያስፈልጋል የሚለውን የምናየው ይሆናል፡፡ ዶ/ር ደረጀ ንጉሴ በስተመጨረሻው እንደገለጹት በኢትዮጵያ የህክምና ታሪክ በተለይም ሙያውን በልዩ ደረጃ በማሰልጠን ረገድ የኢትዮጵያ የማህጸንና ጽንስ ሕክምና ማህበር ባለፉት ሁለት አመታት በተደረገለት የገንዘብም ሆነ የሙያ ድጋፍ የሰራው ስራ የመጀመሪያ ነው፡፡  
ኢትዮጵያ ውስጥ የማህጸንና ጽንስ ሕክምና ትምህርትን የሚሰጡ ተቋማት በሙሉ አንድ አይነት የሆነ የትምህርት መርሐ ግብር እንዲኖራቸው ለማስቻል ከጤና ጥበቃ እና ከትምህርት ሚኒስቴር ጋር በመሆን ስራ ተሰርቶአል፡፡ ደረጃውን የጠበቀ ፈተናን መስጠትን በተመለከተም ተሳክቶ ተካሂዶአል፡፡ ጥራቱን የጠበቀ ተከታታይ የህክምና ትምህርት መስጠትን በተመለከተም ባለሙያዎችን ለልዩ ሙያ በማሰልጠን ረገድ ካሉ ሌሎች ተቋማት በተሻለ መስራት ተችሎአል፡፡ የህክምና ስነምግባርን በተመለከተም ዶክመንት እየተዘጋጀ ነው፡፡ እነዚህንና ሌሎች ጠቃሚ ስራዎች በማህበሩ እየተሰሩ በመሆናቸው እና የተሰሩም በመኖራቸው ማህበረሰቡን በበቂ ሁኔታ ለማገልገል ዝግጁ ነን ማለት ይቻላል፡፡ ወደፊትም የማህበሩ አባላት በተሰለፍንባቸው የተለያዩ መስኮች የተሻለ ስራ በመስራት ህብረተሰቡን በተሻለ ሁኔታ ማገልገል ይጠበቅብናል ብዬ አምናለሁ ብለዋል ዶ/ር ደረጀ ንጉሴ፡፡››

 የገጣሚ፣ ተወዛዋዥና ኬሮግራፈር ኤፍሬም መኮንን (ኤፊማክ) ሁለተኛ ሥራ የሆነው “የወፍ ጐጆ ምህላ” የግጥም መፅሐፍ፣ ነገ ከቀኑ 9፡00 ጀምሮ ናዝሬት አዳማ በሚገኘው ተስፋዬ ኦሎምፒክ ሆቴል የስብሰባ አዳራሽ ይመረቃል፡፡ በስነ ስረዓቱ ላይ ገጣሚያን አዳም ሁሴን፣ ሰለሞን ሳህለና በላይ በቀለ ወያን ጨምሮ በርካታ ገጣሚያን ስራዎቻቸውን የሚያቀርቡ ሲሆን፤ ከመፅሐፉ የተመረጡ ግጥሞችም ይነበባሉ ተብሏል፡፡ “ፍራሽ አዳሽ” የተሰኘ የአንድ ሰው ተውኔት በተስፋሁን ከበደ ለታዳሚ እንደሚቀርብም ገጣሚ ኤፍሬም መኮንን ገልጿል፡፡
“ግጥም በውዝዋዜን” ለመጀመሪያ ጊዜ በመድረክ ያስተዋወቀው ኤፍሬም፤ ነገም ግጥምን በውዝዋዜ ለታዳሚ እንደሚያቀርብ አስታውቋል፡፡ የግጥም መፅሐፉ በተለያዩ ጉዳዮች ላይ የሚያጠነጥኑ 61 ግጥሞች ያሉት ሲሆን፤ በ94 ገጾች ተቀንብቦ በ-------------- ብር ለገበያ ቀርቧል፡፡ ገጣሚው ከዚህ ቀደም “ለባለ ቅኔው ቅኔ አጣሁለት” የተሰኘ የግጥም መፅሐፍ በግሉ ያሳተመ ሲሆን፤ “ሰሚ ያጡ ብዕሮች” እና “የግጥም ከተራ” የተሰኙ የግጥም መፅሐፎችን ከሌሎች ገጣሚዎች ጋር በጋራ አሳትሞ ለንባብ ማብቃቱ አይዘነጋም፡፡



    ሚዩዚክ ሜይ ዴይ ከኢትዮጵያ ኮሌጅ ጋር በመተባበር ነገ ከቀኑ 8፡00 ሰዓት ጀምሮ በብሔራዊ ቤተ-መፃህፍትና ቤተ-መዛግብት ኤጀንሲ አዳራሽ በአርክቴክት ሚካኤል ሽፈራው “የሞሮኮ አገር እውነት” መፅሐፍ ላይ ውይይት ያካሂዳል፡፡ ለውይይቱ የመነሻ ሀሳብ የሚያቀርቡት ገጣሚና ጋዜጠኛ ዮሐንስ ገ/መድህን ሲሆኑ መድረኩም በሰለሞን ተሰማ ጂ እንደሚመራ ታውቋል፡፡
ደራሲው አርክቴክት ሽፈራውም በፕሮግራሙ ላይ የሚታደም ሲሆን፤ በውይይቱ ላይ ፍላጐት ያለው እንዲሳተፍ አዘጋጁ ጋብዟል፡፡



    በመላ ሃገሪቱ ከአርማና ባንዲራ ጋር በተያይዞ እየተፈጠሩ ያሉ ውዝግቦች ዘላቂ ሕጋዊ መፍትሄ እንደሚያሻቸው የገለፁት ሰማያዊ ፓርቲና ኦፌኮ፤ ሁኔታዎች ከቁጥጥር ውጭ ወጥተው ወደ ሁከትና ብጥብጥ ከማምራታቸው በፊት መንግስት አፋጣኝ የእርምት እርምጃ እንዲወስድ አሳስበዋል።
ከአርማና ሠንደቅ አላማ ጋር ተያይዞ የሚፈጠሩ ሁከቶችን ለማስቆም የሃይማኖት አባቶችና፣ አባገዳዎች፣በየአካባቢው ወጣቶችን  የማረጋጋት ስራ እንዲሰሩም ፓርቲዎቹ በጋራ በሰጡት ጋዜጣዊ መግለጫ ጠይቀዋል፡፡
“የለውጡን ሂደት መደገፍና አገሪቱን እንደ አገር የማስቀጠል ጉዳይ ቅድሚያ ሊሰጠው ሲገባ፤ በየአካባቢው የሚታዩ ግጭቶችና ሥርአት አልበኝነት አሳሳቢ ደረጃ ደርሷል” ያሉት ፓርቲዎቹ፤ “በተለይ ሰሞኑን በአዲስ አበባ ከባንዲራ ጋር በተያያዘ የተፈጠረው ውዝግብ ከምንም በላይ አሳሳቢ ነው፤ አስቸኳይ እልባት ያስፈልገዋል” ብለዋል፡፡
ሁሉም አካል የሌላውን ባከበረ መልኩ የየራሱን አርማ መያዝ እንደሚችል የተረጋገጠ ሁኔታ መፈጠሩን የጠቀሱት ፓርቲዎቹ፤ በዚህ ሰበብ የሚፈጠሩ ግጭቶችን በፅኑ እናወግዛለን ብለዋል፡፡
በሃገሪቱ በአሁን ወቅት እየታየ ያለው ፖለቲካዊ ለውጥ ተስፋ ሰጪ መሆኑን የጠቆሙት «ሰማያዊ» እና «ኦፌኮ»፤ ሁሉም የፖለቲካ ቡድን ይህን ተስፋ ወደተሻለ ለውጥ የማሸጋገር ኃላፊነት አለበት ብለዋል፡፡
ወደ ሃገር ውስጥ የሚገቡ የትኞቹም ድርጅቶች ያለ አድልኦና መገለል በመላው ህዝብ በፍቅር አቀባበል ሊደረግላቸው እንደሚገባም ፓርቲዎቹ ገልፀዋል፡፡
የባንዲራ ጉዳይ ሃገሪቱ ካለባት ውስብስብ ፖለቲካዊ ችግሮች አንፃር በቀጣይ በህዝብ ውሳኔ እልባት ሊያገኝ የሚችል መሆኑንም በመጠቆምም ሁሉም ወገን ለውጡ እንዳይቀለበስ የበኪሉን መወጣት ይገባዋል፤ ብለዋል፡፡



    አንድ የፋርስ ገጣሚና ነገን ተንባይ (Philosophizing the Future) ከአንድ ሌላ የጊዜው ባለሙያ ጋር፤
አንደኛ - “የመጣነውን መንገድ ጨርሰነዋል ወይ?”
ሁለተኛ - ጥያቄዎቹን አንጥረን ስናወጣ (Crystallized Questions)፤ መፍትሄ የሚያገኙ ንጡር ጥያቄዎች ናቸው ወይ?
ሦስተኛ - “ድንገት ወደ መልስ ካመሩ ወዴት ያምሩ?” ሲል ይጠይቀዋል፡፡
ባለሙያውም፤
1ኛ/ “ትናንትን ለመጨረስ ዛሬን መጀመር ብቻ በቂ ማረጋገጫ አይሆንም፡፡ ቢያንስ ነገን ማሰብን ይጠይቃል! ስለዚህ ካሁኑ ስለ ነገ መመራመር ጀምር!”
2ኛ/ የነጠረ ጥያቄ ለማውጣት አስቀድመን ፍላጐታችን ምንድነው? ብለን እንጀምር፡፡ ከዚያ ጥያቄዎቻችንን እናሰባስብ፡፡ ቀጥለን አንኳር አንኳሮቹ የትኞቹ ናቸው? እንበል፡፡
3ኛ/ “አንኳር አንኳሮቹን ጥያቄዎች ለማን እናቅርባቸው? ስትል ወዴት ማምራት እንዳለባቸው ራሳቸው ይመሩሃል፡፡ ሁሉንም ስታደርግ ግን በሁለት ቢላዋ ከሚበሉ ሰዎች ተጠንቀቅ!” ብሎት ባለሙያው መምህር ሄደ፡፡ ፋርሳዊው ገጣሚም “ነገን ለመጀመር ትናንትናን ጨርስ” የሚለውን ሀሳብ ዕድሜ ልኩን ይዞት ኖረ!
*   *   *
የነገ ጉዟችን ትላንትና እንደተጀመረ አንርሳ፡፡ ለዚያ ጅምር አስተዋፅኦ ያደረጉትን ሁሉ አንዘንጋ፡፡ የነገ ጉዟችን አጭር ርቀት እንዳልሆነ እናስተውል፡፡ ይህ ጉዞ ከባድ የዕውቀት መሰናዶን ይጠይቃል፡፡ መማር፣ መማር፣ አሁንም መማር ሲባል የነበረው ለትምህርት ጥማት ብቻ ሲባል አልነበረም፡፡ አንድም ትላንትናን ለመማርና ልምድን ለማካበት፣ አንድም በዛሬ ላይ ለመንቃት፣ አንድም ድግም ነገን ለመተንበይ ነው። መማርን ወደ ዕውቀት፣ ዕውቀትን ወደ ጥበብ ስናሳድግ የተግባር ብልሃት ይገባናል። ያኔ አገርን ማሳደግ ፍንትው ብሎ ይታየናል፡፡ ከአሮጌው አስተሳሰብ መፅዳት እንዴት እንደሚቻል ግንዛቤው ከእነ ዘዴው ይመጣልናል! የትምህርትን ነገር ዘንግቶ ስለ ዕውቀት ማውራት ዘበት ነው፡፡ ትምህርታችንን በየዕለቱ መቀጠል እንዳለብን አስተውለን፣ ምን እናድርግ? እንበል፡፡ “ከመጠምጠም መማር ይቅደምከ የሚሉት አበው፣ ጧቱኑ ነገሩ ገብቷቸው ነው፡፡ አውቀናል ብለን ከተኮፈስን፣ አዲስ ዕውቀት ያመልጠናል፡፡ አስበን መኖር ይጠፋናል፡፡ ነገን መጨበጥ ዛሬውኑ ከእጃችን ይወጣል፡፡ ሥጋቶቻችንን እንምከርባቸው እንጂ አንሽሻቸው፡፡
ከአገረ-ዳንኪራ በጊዜ እንገላገል፡፡ የጥንቱ ሥነ-ተረት ስድስት ቅዳሜና አንድ እሁድ ስለነበራቸው ድንክዬዎች የሚያወጋ ነው፡፡ ወደ ሥራ፣ ወደ ማሰብ፣ ወደ ተግባር ለመሄድ ሰባት የሥራ ቀንም አይበቃንም፡፡ በአሉባልታና በጫጫታ የፈረሰችውን እያሪኮ ሳይሆን የጠንካራዋን ኢትዮጵያን አዲስ መሠረት ለመጣል እንነሳ፡፡ አዕምሮ ለአዕምሮ በመናበብ አዕምሮ ላይ እንሥራ፡፡ ሌትና ቀን እንጣር፡፡ የማይታየንን ለማየት እንሞክር፡፡ እንዳናይ ማን ጋረደን እንበል፡፡ በግርግር ጊዜ አናጥፋ፡፡ ከአገረ-ዳንኪራ ወደ አገረ-ኮሰታራ እንቀየር፡፡ አዲስ የተባለን ሁሉ በመነካካት የተለወጥን አይምሰለን፡፡ ለውጥ ጊዜ-ወሳጅና አዳጊ ሂደት እንጂ ሙቅ ማሞቅ አይደለም! ሼከስፒር “Uneasy Lies the head that wears the crown” ይለናል፡፡ ዘውድ የጫነ ጭንቅላት ጭንቀት ይጫነዋል፤ እንደማለት ነው፡፡ ለመጪዎቹ የምናደርገው መስተንግዶ ሁሉ ዘውድ ለመጫን ከሆነ፣ ጭንቀቱንም መጋራት አይቀሬ ነው፡፡ ይህን ልብ እንበል! እግረ-መንገዳችንን ገጣሚው፡-
የሄድንበትን ቦይ፣ እንጠይቅ እንመርምር
ጅምሩን ሳንጨርስ፣ አዲስ አይጀመር
ያለውን በአዕምሯችን እንያዝ!!

  በአውዳመት ምድር የደቡብ ሱዳንን ቅጡ የጠፋው የሰላም ስምምነት ወይም የቻይናና አሜሪካን የንግድ ጦርነት መካረር ወይም ሌላ አለማቀፍ ዜና ከማቅረብ ይልቅ፣ ከአዲስ አመት አከባበር ጋር በተያያዘ የተለያዩ የአለማችን አገራትን አስገራሚ ልማዶችና ባህሎች በማሰባሰብ ልናስቃኛችሁ ወደድን፡፡
እነሆ!...
“የጎመን ምንቸት ውጣ፤ የገንፎ ምንቸት ግባ” እንዲል ሐበሻ መስከረም ሲጠባ፣ የዌልስ አባወራዎችም በተመሳሳይ መልኩ በአዲስ አመት ዋዜማ እኩለ ሌሊት ላይ የቤታቸውን የጓሮ በር ከፍተው መልሰው በፍጥነት ይዘጋሉ፡፡ ያለፈው አመት ወደ ቤታቸው ይዞት የገባው መጥፎ ዕድል ሹልክ ብሎ ይወጣ ዘንድ ነው በውድቅት ሌሊት በራቸውን መክፈታቸው፡፡ በዚህም አያበቁም፤ ልክ ሲነጋ ደግሞ ያንኑ በር መልሰው ይከፍቱታል፡፡ አባወራዎቹ ሲነጋ በሩን የሚከፍቱት አዲሱ አመት መልካም ዕድልን፣ ብልጽግናንና ሰላምን ይዞ ወደ ቤታቸው እንዲገባ ነው፡፡
ጃፓናውያን በበኩላቸው፤ ኦሾጋትሱ ብለው የሚጠሩትን የአዲስ አመት በዓል የሚያከብሩት ቤታቸውን ከወትሮው በተለየ በማጽዳትና በማሸብረቅ ነው፡፡ የጃፓናውያኑን የአውዳመት ጽዳት ለየት የሚያደርገው ግን፣ ቤታቸውን ከቆሻሻ ብቻ ሳይሆን ራሳቸውንም ከዕዳ ማጽዳታቸው ነው፡፡ ሁሉም የቤተሰብ አባል ያለበትን የገንዘብ ዕዳ በሙሉ ከፍሎ፣ ከተቀያየመውና ከተጣላው ሰው ጋር እርቅ አውርዶ፣ ከቂምና ከዕዳ ከነጻ በኋላ ነው አዲስ አመትን በደስታ ማክበር የሚጀምረው።
ስፔናውያን ደግሞ በአዲስ አመት የመጀመሪያዋ ቀን ሰዓታቸውን እያዩ ልክ አንድ ሙሉ ሰዓት ሲሆን አንድ ወይን የሚበሉ ሲሆን፣ ቀኑን ሙሉ የሚበሏቸው 12 የወይን ፍሬዎች፣ በአዲሱ አመት 12 ወራት፣ መልካም ዕድልንና ደስታን ያመጡልናል ብለው ያምናሉ፡፡
አየርላንዳውያን የአዲስ አመትን አከባበር የሚጀምሩት፣ በዋዜማው ምሽት፣ በየቤታቸው ግድግዳና በር ላይ ዳቦ በማንጠልጠል ነው። ዳቦው የተትረፈረፈ ጸጋን እንደሚስብና መጥፎ መንፈስንና ክፉ እድልን ከቤታቸው እንደሚያስወጣ ያምናሉ፡፡ በዚህም አያበቁም። ከቤታቸው በዳቦ ያባረሩት መጥፎ መንፈስና ክፉ እድል ከደጃፍ እንዳይጠብቃቸው በመስጋት በእኩለ ሌሊት ከቤታቸው በመውጣት፣ ጆሮ የሚበጥስ ሃይለኛ ጩኸት ያሰማሉ፡፡
ሁሉም በየደጃፉ ቆሞ አቅሙ በፈቀደው መጠን እሪታውን ያቀልጠዋል፡፡ ህጻን አዋቂው ጉሮሮው እስኪደርቅ በመጮህ፣ ከደጃፉ ያደፈጠውን መጥፎ መንፈስና ክፉ እድል፣ ከአገር ምድሩ ጠራርጎ ያስወጣና፣ አዲስ አመትን “በል እንግዲህ ሰተት ብለህ ግባ!!” ብሎ ይቀበላል፡፡
አንዲት ብራዚላዊት በአውዳመት ምድር፣ የወርቅና የአልማዝ ጌጣጌጦቿን አወላልቃ፣ ወደ ባህር ስትወረውር ቢያዩ፣ ጤንነቷን ሊጠራጠሩ ይችላሉ፡፡ አይጠራጠሩ! ጤነኛ ናት፡፡ ጌጣጌጦቿን ወደ ባህር የምትወረውረውም፣ ያለፈውን አመት በሰላም በጤና እንዳሳለፈችው ሁሉ፣ አዲሱ አመትም የሰላምና የጤና እንዲሆንላት አምላኳን ለመለመን ነው፡፡
ኮፓካባና ተብሎ የሚጠራው የብራዚል ባህር ዳርቻ፣ አመቱን ሙሉ በቱሪስቶች የሚጥለቀለቅ ታዋቂ የመዝናኛ ስፍራ ነው፡፡ ኮፓካባና ከአመት አመት የመዝናኛ፣ ከአመት አንድ ቀን ደግሞ የአውዳመት ማክበሪያና የመማጸኛ ባህር ነው፡፡
ብራዚላውያን በዘመን መለወጫ ዋዜማ በሚያከናውኑት ‘ፌስታ ዲ ኢማንጃ’ የተባለ ባህላዊ ክብረበዓል፣ ወደ ባህሩ አቅንተው ‘ኢማንጃ’ የተባለችዋን የባህር አምላክ ይለማመናሉ። አዲሱን አመት መልካም እንድታደርጋቸው ይጸልያሉ። በስተመጨረሻም ወደ ባህሩ እጅ መንሻ ይወረውራሉ፡፡ በአዲስ አመት ዋዜማ ወደ ባህሩ የሚወረውሩት ጌጣጌጦች ብቻም አይደሉም፡፡ ውድ ዋጋ የሚያወጡ ሽቶዎች፣ አበቦችና ፍራፍሬዎች ጭምር እንጂ፡፡
ድሮ ድሮ ወደ አገራችን መጥቶ በጥምቀት በዓል የታደመ እንግዳ ደራሽ ዴንማርካዊ፣ ኮበሌው ወደ ልጃገረዷ ደረት ሎሚ ሲወረውርና ጡቷን ሲመታ ቢያይ ግራ ሊጋባ ይችላል፡፡ ውርወራው ፍቅር መግለጫ እንደሆነ አያውቅምና፡፡ ወደ ዴንማርክ አቅንቶ የዘመን መለወጫ በዓላቸውን የታደመ የኛ አገር ሰው በተራው፣ ስኒ እንደ ድንጋይ ወደየቤቱ ደጃፍ ሲወረወር ቢያይ፣ በተመሳሳይ ግራ መጋባቱ አይቀርም፡፡ ውርወራው ፍቅር መግለጫ እንደሆነ አያውቅምና፡፡
ዴንማርካውያን በአዲስ አመት ዋዜማ እኩለ ሌሊት ላይ፣ የማጀት እቃዎቻቸውን ለቃቅመው ወደ ጎዳና ይወጣሉ፡፡ በጨለማ ውስጥ ተደብቀው ማንም ሳያያቸው፣ ወደመረጡት ጎረቤት ወይም ወዳጅ ዘመድ ቤት ያመራሉ፡፡ ከዚያስ?... በደረቅ ሌሊት በወዳጅ ዘመዳቸው ቤት ጣራ ላይ የማጀት እቃዎቻቸውን እንደ ድንጋይ ይወረውራሉ፡፡
በዚህች የዴንማርክ ምሽት ብርጭቆ፣ ትሪ፣ ሰሃን፣ ጭልፋ፣ ማንኪያ፣ ድስትና ሌላ ሌላው የቤት እቃ በሙሉ ከየመደርደሪያው ወርዶ ወደየቤቱ ደጃፍ ይወረወራል፡፡ ከግድግዳ እየተጋጨ፣ ከመስኮት እየተፋጨ፣ በየበሩ ሲሰባበር፣ በየደጃፉ ሲነካክት ያመሻል፡፡
ንጋት ላይ… ሁሉም ከቤቱ በመውጣት በየራሱ ደጃፍ የተጠራቀመውን ስብርባሪ የማጀት እቃ በማየት ደስታን ይጎናጸፋል፡፡ የተሰባበረው እቃ የመልካም ነገሮች ምሳሌት ተደርጎ ይወሰዳል። ምሽቱን ወደ ቤቱ ብዙ እቃ ሲወረወርበት ያደረ፣ ሲነጋ ከደጃፉ ብዙ ስብርባሪ ተጠራቅሞ ያገኘ ቤተሰብ፣ በሌሎች ዘንድ የበለጠ ተወዳጅ እንደሆነና መጪው አመትም በተለየ ሁኔታ የደስታ፣ የብልጽግናና የጤና እንደሚሆንለት ይታሰባል፡፡
ዴንማርካውያን ከዚህ በተጨማሪም በአዲሱ አመት ዋዜማ እኩለ ሌሊት ላይ፣ ወንበር የመዝለል ባህል አላቸው፡፡ ይህም ከአሮጌው አመት ወደ አዲሱ አመት፣ ከችግር ወደ ስኬት በሰላማዊ ሁኔታ የመሸጋገር ተምሳሌት ተደርጎ ይወሰዳል፡፡
“ቺሊያውያን የዘመን መለወጫን በዓል ከዘመድ አዝማድ ጋር ነው የሚያከብሩት” ብዬ ስነግርዎት፣ “ታዲያ ይሄ ምን ይገርማል?… እኛስ ከዘመድ አዝማድ ጋር አይደል እንዴ የምናከብረው?!” እንደሚሉኝ አላጣሁትም፡፡
ነገሩ ወዲህ ነው…
የቺሊያውያንን የዘመን መለወጫን በዓል ከዘመድ አዝማድ ጋር የማክበር ባህል ከእኛ የሚለየው ዋናው ጉዳይ፣ ወደ ዘመዶቻቸው የሚሄዱት በዋዜማው ምሽት መሆኑም አይደለም - በህይወት ወደሌሉ ዘመዶቻቸው መሄዳቸው እንጂ!! ቺሊያውያኑ በሞት የተለዩዋቸው ዘመዶቻቸው ወዳረፉበት መካነ መቃብር በአዲስ አመት ዋዜማ ምሽት ያመራሉ፡፡ በድቅድቅ ጨለማ በተዋጠው የወዳጅ ዘመዳቸው መቃብር ውስጥ አረፍ ብለውም፣ ከወዳጅ ዘመዳቸው ጋር በዓሉን በዝምታ ጨዋታ ሞቅ ደመቅ አድርገው ያከብራሉ።
አዲሱ አመት የሰላም፣ የደስታና የብልጽግና እንዲሆንላቸው የሚመኙ ሜክሲኳውያን፤ በዋዜማው ምሽት ቀይ ወይም ቢጫ የውስጥ ሱሪ የማድረግ ልማድ አላቸው፡፡ ቀዩ ለብልጽግና፣ ቢጫው ደግሞ ለፍቅርና ለሰመረ ትዳር ይመረጣል።
በአዲስ አመት ጥሩ ፍቅርና የሰመረ ትዳርን ስለ መሻት ካነሳን አይቀር፣ የአየርላንዳውያን ሴቶችን ልማድ እንመልከት፡፡ በአዲሱ አመት ጥሩ ፍቅርና የሰመረ ትዳር ይገጥማት ዘንድ የምትመኝ አየርላንዳዊት ሴት፣ በበዓሉ ዋዜማ ሚስትሌቶ የሚባል የተክል አይነት በትራሷ ስር ሸጉጣ ታድራለች፡፡
በአገራችን ስራ ተፈትቶና ዘና ተብሎ የሚከበረው የዘመን መለወጫ በዓል፣ በኮሎምቢያና በሜክሲኮ ከዋዜማው እኩለ ሌሊት አንስቶ ከባድ ሸክም በመሸከም እንደሚከበር ሲሰሙ ምን ይሉ ይሆን?
የኢኳዶር ዜጎች በበኩላቸው፤ በአዲስ አመት ዋዜማ ምሽት ከየቤታቸው ተጠራርተው ደጃፍ ላይ ይሰባሰባሉ - ለደመራ፡፡ ታዲያ ይሄ ምን ይገርማል ሊሉ ይችላሉ፡፡ የሚገርምዎት ኢኳዶራውያኑ በደመራ መልክ የሚያነድዱት እንጨት ሳይሆን ፎቶግራፍ መሆኑ ነው፡፡
እናት፣ አባት፣ እህትና ወንድም ሁሉም ባለፈው አመት ያጋጠማቸውን ማንኛውንም መጥፎ ነገርና ገጠመኝ የሚያሳዩ ፎቶግራፎቻቸውን ከአልበሞቻቸው ውስጥ በርብረው በማውጣት፣ እንደ ችቦ ደመራ አድርገው በእሳት ያጋዩዋቸዋል፡፡ ፎቶው ሲቃጠል፤ ያ መጥፎ አጋጣሚም ከአሮጌው አመት ጋር ከውስጣቸው ወጥቶ ያልፋል - እነሱ እንደሚያምኑት፡፡
ከኢኳዶር ሳንወጣ ሌላ የአዲስ አመት አከባበራቸው አካል የሆነ ልማዳቸውን እናክል፡፡ በአዲሱ አመት የመጀመሪያ ቀን፣ ምንም የሌለበት ባዶ ሻንጣ ይዘው ረጅም ርቀት የሚጓዙ በርካታ ኢኳዶራውያንን ጎዳና ላይ መመልከት የተለመደ ነገር ነው፡፡ ባዶ ሻንጣ ይዘው ርቀው የሚጓዙት፣ እንደዚያ ካደረጉ በአዲሱ አመት በብዛት ጉብኝት እንደሚያደርጉ ወይም ወደ ሌሎች ቦታዎች እንደሚጓዙ ያምናሉ፡፡
ሩስያውያን በበኩላቸው፤ በዋዜማው ምሽት በአንድ ላይ ይሰባሰቡና በአዲሱ አመት ሊያሳኩት የሚፈልጉትን ነገር በሙሉ በዝርዝር በየራሳቸው ወረቀት ላይ ይጽፋሉ፡፡ ጽፈው ከጨረሱ በኋላ፣ ወረቀቱን በእሳት ያቃጥሉትና አመዱን ከሻምፓኝ ጋር ቀላቅለው እኩለ ሌሊት ከማለፉ በፊት ጭልጥ አድርገው ይጠጡታል - በዚህም አዲሱ አመት ያሰቡት የሚሳካበት ይሆናል ብለው ያስባሉ፡፡
እንደ ሩስያውያን ሁሉ ደቡብ ኮርያውያንም የአዲስ አመት ህልምና ምኞትን በወረቀት ላይ የማስፈር ልማድ አላቸው፡፡ የእነሱን ለየት የሚያደርገው ግን፣ በአዲሱ አመት የመጀመሪያዋ ቀን ንጋት ላይ ከደጃፍ ቆመው፣ ጎህ ሲቀድ እያዩ፣ ህልምና ምኞታቸውን በወረቀት ላይ ጽፈው፣ በፊኛ ውስጥ አድርገው ወደ ሰማይ መላካቸው ነው፡፡
ወደ ስኮትላንድ እናምራ…
ስኮትላንዳውያን ቤተሰቦች፣ የአሮጌው አመት የመጨረሻ ዕለት ተጠናቅቃ፣ የአዲሱ አመት የመጀመሪያ ቀን ስትጠባ፣ ማልደው በር በሩን ማየት ይጀምራሉ፡፡ ቀጣዩ የበዓል አከባበር የሚደምቀውና የሚሞቀውም ሆነ የቤተሰቡ የአዲስ አመት እጣ ፈንታ የሚወሰነው በዚያች ማለዳ ቀድሞ ወደ ቤታቸው በሚመጣው ሰው ነው፡፡
በዚያች ማለዳ ደጃፋቸውን ቀድሞ የረገጠው ሰው፣ ቁመተ ሎጋና መልከመልካም ወንድ ከሆነ፣ አዲሱ አመት የደስታ ይሆናል ብለው ስለሚያምኑ አብዝተው ይፈነጥዛሉ፡፡ በአንጻሩ በዚያች ማለዳ ቀይ ጸጉር ያላት ሴት አልያም ህጻን ልጅ ቀድመው ወደ ቤታቸው ከመጡ ደግሞ አመቱ ለቤተሰቡ ይዞት የሚመጣው አንዳች መከራ አለ ተብሎ ይታመናል፡፡
የሚመጣውን አዲስ አመት ወደ ቤታቸው በሚመጣው ሰው የሚተነብዩት ስኮትላንዳውያን ወንዶች፣ የዘመን መለወጫ በአልን በአጉል ጨዋታ ነው የሚያከብሩት - በልባል እሳት እንደ ኳስ እያንጠባጠቡና በሰራ አካላቸው ላይ እያሽከረከሩ በመንገድ ላይ እየተደሰቱ በመጓዝ፡፡
አዲሱ አመት እንደ ስኮትላንዳውያኑ በእሳት ሳይሆን እንደ ባህላችን ከሳቅ ጋር እየተደሰታችሁ የምትጓዙበት ይሁንላችሁ!!