Administrator

Administrator

 ፕሬዚዳንት ዶናልድ ትራምፕ፤ የሌሎች አጋር አገራት መሪዎችን በማስተባበር፣ ቬንዙዌላን ለመውረር ሲያሴሩ እንደነበር የሚያሳይ መረጃ ይፋ መደረጉን ተከትሎ፣ የአገሪቱ ፕሬዚዳንት ኒኮላስ ማዱሮ፣ የጦር ሃይላቸው የአሜሪካን ወረራ ለመመከት በተጠንቀቅ እንዲቆም ማዘዛቸውን አሶሼትድ ፕሬስ ዘግቧል፡፡
ፕሬዚዳንት ትራምፕ፤ ከአራት የላቲን አሜሪካ አገራት መሪዎች ጋር ባለፈው አመት ባደረጉት የድብቅ ስብሰባ፣ በቬንዙዌላ ላይ ወታደራዊ ጥቃትና ወረራ የማድረግ ሃሳብ በማቅረብ፣ ከከፍተኛ ባለስልጣናት ጋር መምከራቸውን የሚያሳይ መረጃ በአሶሼትድ ፕሬስ ባለፈው ረቡዕ ይፋ የተደረገ ሲሆን፣ ከአሜሪካ ጋር ባላንጣ ሆነው የዘለቁት የቬንዙዌላው ፕሬዚዳንት ማዱሮም በይፋ የአሜሪካንና የአጋሮቿን ጥቃት ለመመከት፣ ከመቼውም ጊዜ በበለጠ እንዲታጠቅና ራሱን እንዲያዘጋጅ ለጦር ሃይላቸው መመሪያ ሰጥተዋል ተብሏል፡፡
የታጠቃችሁ ሁሉ፣ ለአንዲት ሰከንድም ቢሆን ተዘናግታችሁ ጠመንጃችሁን እንዳታወርዱ፣ ምክንያቱም ሰላማችንን ለማደፍረስ የሚመጣብንን ወራሪ ሃይል ለመመከትና ሉአላዊነታችንን ለማስከበር በጀግንነት የምንዋደቅበት ታሪካዊ ጊዜ ላይ ደርሰናል ብለዋል- ፕሬዚዳንት ማዱሮ፡፡ ትራምፕ፤ቬንዙዌላን የመውረር ሃሳብ አቅርበዋል የሚለውን መረጃ በተመለከተ አስተያየቱን እንዲሰጥ የተጠየቀው የዶናልድ ትራምፕ አስተዳደር፣ “በግለሰብ ደረጃ በተደረገ ውይይት ላይ ምላሽ ለመስጠት ፈቃደኛ አይደለሁም” ማለቱንም ዘገባው አመልክቷል፡፡
ፕሬዚዳንት ዶናልድ ትራምፕ ባለፈው ነሃሴ ወር ላይ ባደረጉት ንግግር፣ ”ዲሞክራሲን ያጠፋውና የህዝቡን መብት በአደባባይ የጣሰው የለየለት አምባገነን የሆነው ማዱሮ፤ በስልጣን ላይ መቀጠል የለበትም፤ የኒኮላስ ማዱሮን አምባገነን መንግስት አደብ ለማስገዛት የተለያዩ አማራጮችን መውሰድ እንችላለን፤ አስፈላጊ ሆኖ ሲገኝ ወታደራዊ እርምጃ መውሰድም ከእነዚህ አማራጮች መካከል አንዱ ነው” ማለታቸውንም ዘገባው አስታውሷል፡፡
ማዱሮ በበኩላቸው በወቅቱ በሰጡት ምላሽ፤ ትራምፕ ጦሩን አዝምቶ እንዳይወጋን እርዱን በሚል ለአለማቀፉ ማህበረሰብና ለሮማው ሊቀጳጳስ ፍራንሲስ ጥሪ ማቅረባቸውንም ዘገባው አስታውሷል፡፡


 በ2018 የፈረንጆች አመት ያለፉት ስድስት ወራት ጊዜ ውስጥ በሊቢያ በኩል በማድረግ በሜዲትራኒያን ባህር ሲጓዙ ለሞት የተዳረጉ አፍሪካውያን ስደተኞች ቁጥር ከ1000 በላይ መድረሱን ዘ ጋርዲያን ዘግቧል፡፡
የተባበሩት መንግስታት ድርጅት የስደተኞች ጉዳይ ጽህፈት ቤት ያወጣውን መረጃ ጠቅሶ ዘገባው እንዳለው፣ ባለፉት ስድስት ወራት ጊዜ ውስጥ በሊቢያ በኩል አድርገው ወደተለያዩ የአውሮፓ አገራት ለመግባት ሊቢያ ከደረሱ የተለያዩ የአፍሪካ አገራት ስደተኞች ውስጥ ተሳክቶላቸው ወደ አውሮፓ መግባት የቻሉት ግማሽ ያህሉ ብቻ ናቸው፡፡ በተጠቀሰው ጊዜ ውስጥ ወደ አውሮፓ ሊጓዙ አስበው ሊቢያ ከደረሱ አፍሪካውያን ስደተኞች መካከል 44 በመቶው በሊቢያ የድንበር ጠባቂዎች በቁጥጥር ስር መዋላቸውን የጠቆመው ተቋሙ፤ 4.5 በመቶ የሚሆኑት ደግሞ ለህልፈተ ህይወት መዳረጋቸውን ወይም ጠፍተው መቅረታቸውን አመልክቷል፡፡
በሳምንቱ የመጀመሪያዎቹ ሶስት ቀናት ውስጥ ብቻ ወደ አውሮፓ አገራት ለመግባት በጉዞ ላይ የነበሩ ከ200 በላይ አፍሪካውያን ስደተኞች በሜዲትራኒያን ሰምጠው መሞታቸውን የጠቆመው ዘገባው፤ ባለፈው ሰኔ ወር ወደ አውሮፓ ለመጓዝ አስበው ሊቢያ ከደረሱ ስደተኞች መካከል 10 በመቶው ለህልፈተ ህይወት መዳረጋቸውንም አክሎ ገልጧል፡፡

Monday, 09 July 2018 00:00

ማዕከላዊን በጨረፍታ

 ማዕከላዊ፤ አዲስ አበባ ከተማ ውስጥ፣ ከአራዳ ጊዮርጊስ ወደ ሰሜን ሆቴል በሚወስደው መንገድ የሚገኝ ግቢ ነው፡፡ ብዙ ሰው ላያውቀው ይችላል፤ ቢያውቀውም ብዙ ትኩረት አይሰጠውም። ስለ ማዕከላዊ ሳስብ የሚያሳዝነኝ አንድ ጉዳይ አለ። ማዕከላዊ ፊት ለፊት  በተለምዶ “ዳትሰን” የሚባል ሲደለቅበት የሚያድር ሰፈር አለ፡፡ በርካታ ወጣቶችም በአንድ ቤት ውስጥ ታጭቀውና ራሳቸውን ረስተው የሚዘሉበት ሰፈር ነው፡፡ ፊት ለፊቱ ደግሞ፣ ወጣቶች በበርካታ መርማሪ ተከበው፣ ሲገረፉ የሚያድሩበት ማዕከላዊ አለ፡፡
ከአንድ ኪሎ ሜትር በላይ በማይሆን ርቀት ውስጥ እጅግ የተለያየ ተግባር ሲፈጸምባቸው ያድራል፡፡ በጣም የሚያሳዝነው ታዲያ፣ ከሚዝናኑት አብዛኞቹ ይህን ማዕከላዊ ተብሎ የሚጠራውን ቦታ የሚያውቁት አለመምሰላቸው፣ ቢያውቁት ኖሮ፣ እነዛ ጭፈራ ቤቶች፣ አንድም ወጣት ባልገባባቸው ነበር። በርካቶች፣ ማዕከላዊ የሚባለውን ቤት እንደ ተራ መስርያ ቤት ብቻ አስበው በጥጉ ያልፋሉ፡፡ ማዕከላዊ ግን፣ መስርያ ቤት ይደለም፡፡ በማዕከላዊ የስቃይ ሕይወት ያሳለፉት የዋልድባው ገዳም መነኩሴ፣ አባ ገ/ኢየሱስ ኪ/ማርያም፤ “ማዕከላዊ የሚባል ቤት” እያልኩ ሳወራ፣ “ልጄ፣ ማዕከላዊ ቤት አይደለም” ብለው አርመውኛል፡፡ እውነት ነው፣ ማዕከላዊ ቤት አይደለም! አባ ወ/ኃይማኖት፣ ስለ ማዕከላዊ ጠይቄያቸው፤ “የማዕከላዊን ነገር አታንሳው” ብለውኛል፡፡ መነኮሳቱ በማዕከላዊ ተገርፈዋል፡፡ ለምሳሌ፣ አባ ገ/ስላሴ ወ/ኃይማኖት፤ ሰውነታቸውን በሚስማር እንደበሳሷቸው አጫውተውኛል፡፡ የዛን ነውረኛ “ቤት” ጉዳይ ስለማውቅ፣ “ልብስዎን አስወለቁዎት” ብዬ ጠይቄያቸው፣ “ብዙ ጊዜ አውልቁ ይሉናል፡፡ ሁለት ቀን ከአቅሜ በላይ ሆኖብኝ፣ አውልቀውብኛል” ብለው አዝነው ነግረውኛል። ማዕከላዊ፣ የመነኮሳትን አይደለም፣ የእግዚአብሔርን ክብር የሚያዋርድ “ቤት” ነው፡፡
ሳይቤርያ
ታሳሪዎቹ ብዙ ጊዜ የመጀመርያ መቆያቸው ከሳይቤርያ ይጀምራል፡፡ ሳይቤርያ የሚለው ቤት፣ በሩሲያው ሀገር ውስጥ፣ ቀን ቀን ሞቃት፣ ሌሊት ሌሊት ደግሞ፣ በጣም ቀዝቃዛ በሆነው ግዛት ስም የተሰየመ ነው፡፡ ሰማይ እንዲመስል ጣራው ሰማያዊ ቀለም ተቀብቷል፡፡ ሳይቤርያ በምርመራ ላይ ያለ እስረኛ የሚታሰርበት ሲሆን 2፣3፣4፣5፣6፣7፣8፣9 እና 10 የተባሉ ቁጥር የተሰጣቸው ቤቶች አሉት፡፡ 1 ቁጥር ዝግ ነው፡፡ ከ8 ቁጥር ውጭ ያሉ እስከ 25 እስረኞች የሚታሰሩበት ሲሆን ከ6፣7 እና 8 ውጭ ያሉ ክፍሎች ስፋታቸው በግምት፣ 3 ነጥብ 8 ሜትር በ4 ሜትር ቢሆን ነው። 6 እና 7 ቁጥር ከእነዚህ ክፍሎች በአንፃራዊነት ስፋት አላቸው። አራት በአራት የማይሆን ክፍል ውስጥ እስከ 20 የሚደርሱ እስረኞች እቃ ይቀመጣል፡፡ ሽንት ቤት፣ በቀን ከሁለት ጊዜ ውጭ ስለማይፈቀድ፣ የሽንት ማስቀመጫ ፕላስቲክ ኮዳዎች ይቀመጣሉ። የሚያሳዝነው፣ ከቦታ ጥበት የተነሳ፣ የውሃ ፕላስቲክ ኮዳዎች እና ምግብ የሚቀመጠው አንድ ላይ ነው፡፡
ክፍሉ ለመኝታ ስለማይበቃ፣ ቀን ቀን የተወሰኑ እስረኞች ሲተኙ ቀሪው ቁጭ ይላል፡፡ ሌሊት ራስና እግር እየሆነ (አንደኛው ራሱን ከጎኑ ወደተኛው እስረኛ እግር አድርጎ)፣ በአንድ ጎን ብቻ እስኪነጋ ይተኛል። የሁሉም ክፍል ዝግ ስለሆኑ እስረኛ ሲበዛ ከመጠን በላይ ይሞቃሉ፡፡ መስኮታቸው ከሁለት ሜትር የሚርቅ ሲሆን መብራት የሚገባው በመስኮቱ በኩል ነው። በዚህም ምክንያት ጨለማ ቤት ተብለው ይጠራሉ። የአንድ ክፍል እስረኛ ከሌላኛው ክፍል እስረኛ ጋር መረጃ እንዳይለዋወጥ በሮቹ ይዘጋሉ፡፡ በተመሳሳይ ጉዳይ ተጠርጥረው የገቡ እስረኞችን፣ አንደኛውን በሌላኛው ላይ ለማውጣጣት ሲባል፣ ወይም መረጃ እየተለዋወጡ ለምርመራ እንዳያስቸግሩ ለማድረግ፣ አንደኛው ክፍል የታሰረ ከሌላኛው ክፍል ከታሰረው ጋር እንዳይገናኝ ብርቱ ጥንቃቄ ያደርጋሉ፡፡ ሲያወራ የተገኘም ቅጣት ይጠብቀዋል፡፡ አየር ለማግኘት እንኳ በሮቹ የሚከፈቱት በልመና ነው፡፡
ሳይቤርያ የታሰረ እስረኛ በአንድ ቀን ውስጥ ሁለት ጊዜ ብቻ ሽንት ቤት እንዲወጣ ይፈቀድለታል፡፡ ሌሊት 11 ሰአት የየክፍሉ እስረኛ በተራ ሽንት ቤት ይጠቀማል። ክፍሎቹ በየተራ እየተከፈቱ ከ10 እስከ 15 ባለ ደቂቃ፣ 20 እና ከዛ በላይ እስረኛ ሽንት ቤት ተጠቅሞ ይገባል። በቀን አንድ ጊዜ ለ10 ደቂቃ ፀሐይ መሞቅ ይፈቀዳል። ጨለማ ቤት ባደከመው አይኑም በዛች ትንሽ ደቂቃ የተከለከለው ሰማይ ላይ የተለየ ነገር ይፈልጋል፡፡ ደመና የተለየ ነው። ጨረቃ አትገኝም፡፡ ኮከብ ብርቅ ነው፡፡ አሞራ እንደ ብርቅ ነገር ይታያል፡፡ ሰማይ ይናፍቃል!
በሳምንት አንድ ቀን፣ ቤቶቹ በየተራ እየተከፈቱ፣ እስረኞች ልብስ እንዲያጥቡ ይደረጋል፡፡ ምንም አይን ከለላ የሌለው ቦታ ላይ፣ ህጻናት ወንዝ ወርደው እንደሚታጠቡት፣ እየተጋፉ “ሻወር” ይወስዳሉ፡፡ ከአንድ የዛገ ብረት የሚወርደውን ውሃ “ጠፋ! መጣ!” እያሉ እየተጋፉ፣ ሳምንት ጠብቀው ያገኙትን “ሻወር” ይወስዳሉ፡፡ ሽንት ቤቶቹ ከለላ የላቸውም፡፡ አንዱ ሲጠቀም ሌሎች እስረኞች በር ድረስ ተኮልኩለው ተራ ይጠብቃሉ፡፡ በዚህ መሃል ፖሊስ ከሽንት ቤቶቹ ውጭ ያለውን ዋናውን በር በዱላ እየነረተ፣ እስረኛው ወደ ክፍሉ እንዲገባ ያዝዘዋል፡፡ ሌላ ቤት ተከፍቶ ተረኛ ይጠቀማል፡፡ ቤቱ እንደተከፈተ የተረኛው ክፍል እስረኞች፣ በእጃቸው በሀይላንድ ቤት ውስጥ የዋለውን ሽንት ሳይሳቀቁ ተሸክመው፣ ወደ ሽንት ቤት ያመራሉ፡፡
“8” ቁጥር
ማዕከላዊ ውስጥ ካሉት የሚታወቁት ጨለማ ቤቶች አንዱና ዋነኛው ነው፡፡ አንዱ ክፍል ለ4 ተከፍሎ 1፣2፣3፣4 የሚባሉ ንዑስ ክፍሎች አሉት፡፡ ክፍሎቹ ኮሪደር መሃል ካለው መብራት ውጭ ሙሉ በሙሉ ጨለማ ሲሆኑ እያንዳንዱ ክፍል አንድ ሰው ብቻ ይታሰርበታል፡፡ በእነዚህ ክፍሎች የሚታሰሩ እስረኞች ከፍተኛ በደል የሚደርስባቸው፣ ሁሉም ሌሊት እየተጠሩ የሚደበደቡና ስቃይ የሚደርስባቸው ናቸው፡፡ በምርመራ ወቅት አናምንም ያሉ እስረኞች ለወርና ለሁለት ወር ያህል በእነዚህ ጠባብ ክፍሎች ይታሰራሉ፡፡ ሽንት ቤት የሚሄዱት፣ ፀሃይ የሚሞቁት ብቻቸውን ነው፡፡ ከሳይቤርያ ታሳሪዎች ሁሉ ከፍተኛ የአካልና የስነ ልቦና ጥቃት ይደርስባቸዋል፡፡ ያመነ እስረኛ ወደ ሳይቤርያ ሌሎች ክፍሎች፣ ወይ ደግሞ ወደ “ሸራተን” ይዛወራል፡፡
መርማሪዎች ፈፅማችኋል ያሏቸውን እንዲያምኑ 8 ቁጥር ከሚገቡት በተጨማሪ፣ የዐቃቤ ሕግ ምስክሮች ሆነው በሌሎች ተጠርጣሪዎች ላይ ቃላቸውን እንዲሰጡ የሚፈለጉ ተጠርጣሪዎችም በዚህ ክፍል ይታሰራሉ፡፡ ሰዎች መጀመርያ በወንጀል ተጠርጥረው ገብተው መረጃ ሲጠፋ፣ በሌላ ሰው ላይ በሀሰት እንዲመሰክሩ ሲጠየቁ፣ ካልተስማሙ 8 ቁጥር ይታሰራሉ። እንመሰክራለን ካሉ ግን ወደ ጣውላ ቤት ይዛወራሉ፡፡ 8 ቁጥር ከሳይቤርያ ቀሪ ክፍሎችም የባሰ ነው፡፡ በዚህኛው ክፍል ደግሞ ከሰው ጋር መብላት፣ የሰው ድምፅ መስማትም ይናፍቃል፡፡
ምርመራውን የጨረሰ፣ ቃል ሰጥቶ የፈረመ እስረኛ የሚታሰርበት የእስር ቤት ክፍል ነው፡፡ 12 ክፍሎች ያሉት ጠባብ ክፍል ሲሆን ቤቶቹ ክፍት ሆነው ይውላሉ፡፡ እስረኞች ወደ ሌሎች ክፍሎች እየተዘወዋወሩ መጫወት ይችላሉ፡፡ ቤቶቹ በር ላይ ሆኖ ፀሀይ መሞቅ ይቻላል፡፡ ይህም ከሳይቤሪያ ጋር ሲነፃፀር ሸራተን የሚል ስያሜ  አሰጥቶታል፡፡ ይህ እስር ቤት፣ በቤቶች መካከል የተወሰነ የሰማይ ክፍልን ያሳያል፡፡ በር ላይ ቁጭ ብሎ ፀሀይ መሞቅ፣ አየር ማግኘት ይቻላል፡፡ እስረኛው እንደ ሳይቤሪያ በፖሊስ እየተጠበቀና “ጨርስ” እየተባለ ሳይሆን በፈለገው ሰዓት ወደ መፀዳጃ ቤት መሄድ ይችላል፡፡ ወደ ሌላ ክፍል ገብቶ ከጓደኞቹ ጋር መጫወት ይችላል። አንድ እስረኛ ተጨማሪ መረጃ ከተገኘበት ወይም በሌላ ሰው እንዲመሰክር ተጠይቆ አልመሰክርም ካለ ከሸራተን ወደ ሳይቤርያ፣ ብሎም ወደ 8 ቁጥር ይመለሳል፡፡
ጣውላ ቤት
ከወንጀል ምርመራ ቢሮዎች ስር የሚገኙ ክፍሎች ናቸው። ሴቶችና ምስክሮች የሚታሰሩበት ሲሆን አራት ክፍሎች አሉት። ሁለቱ የሴቶች፣ ሁለቱ የምስክሮች ሲሆኑ ክፍሎቹ ተከፍተው ስለሚውሉ አየር ያገኛሉ፡፡ በር ላይ ቁጭ ብለው ፀሀይ መሞቅ ይችላሉ፡፡
  ምርመራ
ማዕከላዊ 24 ሰዓት ምርመራ የሚደረግበት እስር ቤት ነው፡፡ ድብደባ የሚፈፀመው በአብዛኛው ሌሊት ነው፡፡ ይህም የሚደረገው ጩኽት እንዳይሰማና ድብደባ ሲፈፅሙ ብዙ እስረኛ እንዳያይና እንዳይሰማ ነው፡፡ አንድ እስረኛ እስከ 6 በሚደርሱ መርማሪዎች ሊመረመር ይችላል፡፡ ሁሉም ያዋክቡታል፡፡ ፊት ለፊት ካለው ጋር እየተነጋገረ፣ ከኋላም መጥተው ይደበድቡታል፡፡
ግድግዳ ላይ መስቀል፣ ከአቅም በላይ ስፖርት በማሰራት እስረኛው ተዝለፍልፎ እንዲወድቅና እንዲሰቃይ ማድረግ፣ ስፖርት በሚሰራበት ወቅት ሳያስበው መትቶ መጣል፣ በገመድ መግረፍ፣ ሁለት ጠረጴዛዎች ላይ “ወፌ ላላ” መስቀል (መገልበጥ)፣ በእንጨት፣ በጥፊ፣ በእርግጫ መደብደብ፣ ስድብና ዛቻ የተለመዱ ናቸው፡፡ የኤሌክትሪክ ንዝረት፣ ጥፍር መንቀል፣ ርቃን መመርመር፣ ብልትን በሴቶች እያስነኩ ማሸማቀቅ፣ የውሃ ኮዳ ማንጠልጠል፣ በሽጉጥ ማስፈራራት፣…ፀያፍ ነገር ማስፈራሪያ ማድረግና የመሳሰሉት የተለመዱ የምርመራ ክፍሎቹ መገለጫዎች ናቸው፡፡
(በጌታቸው ሺፈራው “የሰቆቃ ድምጾች”፤ ሰኔ 2010 ዓ.ም)

 እንደ ሥነ-ተረት በሀገራችን የሚነገር አንድ ታሪክ አለ፡፡
ከዕለታት አንድ ቀን የጎረቤቱን አገር በመውረር የታወቀ አንድ ንጉሥ ነበረ፡፡ ይህ ንጉሥ እንደለመደው አንድ ዓይነት ጎሣ የሚኖርበትን ጎረቤት አገር ወረረና አገሬውን አስገብሮ ገዥ ሆኖ ያስተዳደር ጀመር፡፡ ያም ሆኖ የአገሬው ህዝብ የተገዛለት እየመሰለ አንድ ቀን እንደሚያጠፋው እየዶለተ መሆኑን መረጃ ደረሰው፡፡ ስለሆነም ንጉሡ ያንን ህዝብ ለማጥፋት ዘዴ ያውጠነጥን ገባ፡፡ በመጨረሻም ህዝቡ ሁሉ ግብር የሚበላበት አንድ ታላቅ ድግሥ ደገሠና፤
“ህፃን፣ ሽማግሌ፣ ወጣት፣ ጎልማሳ፣ ወንድ፣ ሴት ሳይባል ሁሉም ሰው ከንጉሥ ግብር እንዳይቀር” ሲል አወጀ፤ አዘዘ፡፡
አገሬው አንድም ሳይቀር ወደ ድግሱ መጉፍ ጀመረ፡፡
በዚያ አገር ላይ አንድ እጅግ ብልህና አብራሄ ህሊና ያለው ዐይነ ሥውር ሰው ነበረ፡፡ በዚያው አገር ከሴት ልጁ ጋር ይኖራል፡፡ የዚህን ዐይነ-ስውር አስተዋይነትና ጠቢብነት ያ ክፉ ንጉሥ ያውቃል፡፡ ስለዚህም የቅርብ ሰዎቹን ጠርቶ፤
“ያ ዐይነ-ስውር ሰው ወደ ድግሴ መጥቷል ወይ?” ሲል ጠየቀ፡፡
ሰዎቹም፤
“ንጉሥ ሆይ! እስካሁን አልታየም” አሉት፡፡
ንጉሡም፤
“በሉ፤ እስከመጨረሻው መምጣት አለመምጣቱን አጣርታችሁ እንድታሳውቁኝ” ሲል አዘዘ፡፡
ዐይነ ስውሩ ብልህ ሰው ከልጁ ጋር እቤቱ ነበረ፡፡ ሴት ልጁም፤
“አባዬ፤ ንጉሡ ወደ ግብሩ ማንም እንዳይቀር” ብሎ አዟልና እንውጣ? አለችው፡፡
ብልሁ ዐይነስውርም፤
“እስቲ ብቅ በይና ወድ ድንኳኑ የሚሄደውን ሰው ሁኔታ አጣሪና ትነግሪኛለሽ?” አላት፡፡
ልጅቱ አባቷ እንደነገራት ወደጎዳናው ወጥታ የህዝቡን አካሄድ ተመለከተችና ተመለሰች፡፡
“እህስ? ምን አየሽ?” አላት አባቷ፡፡
“ህዝቡ ወደማብሩ እንደጉድ ይጎርፋል” ስትል መለሰችለት፡፡
ዐይነ-ስወሩ አባትም፤
“ለመሆኑ የሚሄድ እንጂ የሚመለስ ሰው አይተሻል?”
ሲል ጠየቃት፡፡
ልጅቱም ትንሽ አስባ፤
“ኧረ አባዬ፤ ማንም ሲመለስ አላየሁም” ስትል መለሰችለት፡፡
ዐይነ-ስውሩ አባትም፤
“በይ ተነሽ ወደ አንድ ስውር ሥፍራ ውሰጂኝ”
“ለምን?”
“ለመደበቅ”
“ከማን ነው የምንደበቀው?”
“ከንጉሡ ጋሻ-ጃግሬዎች”
“ለምን?”
“አየሽ የኔ ልጅ፤ ህዝቡ ሁሉ ወደ ድግሱ እየሄደ ማንም ሰው ሳይመለስ ከቀረ፤ ነገር አለ ማለት ነው፡፡ ንጉሡ እኔና አንቺ መቅረታችንን ሲያውቅ ጋሻ- ጃግሬዎቹን ወደ ቤታችን መላኩ አይቀርም፡፡ አስገድደው ሊወስዱን ይችላሉና መጠንቀቁ አይከፋም፡፡”
“ግንኮ ድግስ ነው አባዬ፡፡ ከመብላት ከመጠጣት በስተቀር ምን ይኖራል ብለህ ነው?”
“አየሽ ልጄ፤ ህዝብ እንዲህ ጥርግርግ ብሎ ወደ አንድ አቅጣጫ ሲነጉድ መጠራጠር ጥሩ ነው፡፡ አገሬው አንድ ችግር ቢገጥመው እንኳን እኛ አንተርፋለን፡፡
አባትና ልጅ አንድ ጉድጓድ ውስጥ ተደበቁ፡፡
*    *    *
ዕውነትም ንጉሡ የዐይነ-ስውሩን ሰው አለመምጣት ሲገነዘብ፤
“ሂዱና ቤቱ ፈልጉት፡፡ ቤቱ ካጣችሁ ሰፈሩን አስሱ” አለና ጋሽ አጃግሬዎቹን ላከ፡፡ ፈረሰኞች ወደ ዐይነ-ስውሩ መንደር መጡ፡፡
ዐይነ-ስውሩ ብልህ ሰው፤
“ልጄ የምሰማው ድምፅ ምንድነው?” ሲል ጠየቃት፡፡
ልጅቱም፣
“አባዬ፤ ፈረሰኞች እየመጡ ነው!”
“በይ ብዙ ጠጠሮች ልቀሚና ያዥ”
“ከዚያስ?”
“አንድ ፈረሰኛ ሲያልፍ አንድ ጠጠር ትጥያለሽ፡፡ ለሁሉም እንደዚህ ካደረግሽ በኋላ፤ ሲመለሱም እነዚያን የጣልሻቸውን ጠጠሮች እያነሳሽ ትቆጥሪያቸዋለሽ፡፡ ያለፉት ፈረሰኞች መመላለሳቸውን በዚያ ታረጋግጫለሽ!”
ልጅቷ አባቷ ያላትን አደረገች፡፡ ያለፉት ፈረሰኞች መመለሳቸውንም በትክክል አረጋግጣ ለአባቷ ነገረችው፡፡
አባቷም፤
“አየሽ ፈልገው አጥተውን ተመለሱ ማለት ነው!”
* * *
ንጉሡ ባዘጋጀው ግብር እጅግ የሚያሰክር፣ የዝሆን ሐሞት የተቀላቀለበት ጠጅ ተዘጋጅቷል፡፡ ድንኳን የተሠራው እገደል አፋፍ ላይ ነው፡፡ ሰው በልቶ ጠጥቶ እንዲወጣ የተደረገው ወደ ገደሉ ነው! ሰክሮ የሚወጣው ህዝብ እየተንገዳገደ ገደል ገባ! በፈቃዱ ገደል እንደገባ ተቆጠረ፡፡ ማንም አልተረፈም፡፡
ዐይነ-ስውሩና ልጅ ወደ አቅራቢያው አገር ተሰደዱ፡፡ ከዚያም፤
“እንግዲህ ልጄ የእኛ አገር ሰው አለቀ፡፡ የቀረነው እኔና አንቺ ብቻ ነን፡፡ ስለዚህ ተጋብተን፣ ተዋልደን ትውልዳችንን ማቆየት አለብን” አላት፡፡
ልጅቱም፤ “አባዬ አገር ጉድ ይለናል! እኔ አላረገውም!” አለች፡፡
“እንግዲያው የጅብ ቆዳ ፈልጊና አምጪ” አላት፡፡
ፈልጋ፣ ገዝታ አመጣች፡፡
“በይ አሁን እኔ ያልኩሽን ታደርጊያለሽ? ቃል ግቢልኝ”
“እሺ” ብላ ቃል ገባች፡፡
“የጅብ ቆዳውን ለብሰሽ ወደ ገበያ ሂጂ” ብሎ አዘዛት፡፡ ቃል ገብታለችና ለብሳ ሄደች፡፡ ገበያተኛው “ጉድ! ጉድ!” እያለ ተበተነ። በሣምንቱ አባት ልጁ አሁንም የጅቡን ቆዳ ለብሳ እንድትሄድ አዘዛትና ሄደች፡፡ አሁን ደግሞ ሶስት አራተኛው ገበያተኛ ተበተነ፡፡ ልጅቱ ለአባቷ የሆነውን ነገረችው። አባትዬው በሶስተኛው ሳምንትም የጅቡን ቆዳ ለብሳ እንድትሄድ አደረጋት፡፡ አሁን ደግሞ ግማሹ ገበያተኛ ብቻ ተበተነ፡፡ ቀስ በቀስ፣ በአምስተኛው ሳምንት፤ ማንም ገበያተኛ የጅብ ቆዳ የለበሰችው ልጅ ከጉዳይ ሳይጥፋት ገበያውን ቀጠለ፡፡ ይሄንኑ የሆነውን ተመልሳ ነገረችው፡-
“አባዬ ዛሬ ማንም አልሸሸኝም፡፡ ሰው ሁሉ ዝም ብሎ መገበያየቱን ቀጠለ!
አባትዬውም፤
“ይሄውልሽ ልጄ፤ “ጉድ አንድ ሰሞን ነው!” እኛ ብንጋባ ዘራችንን እናተርፋለን፡፡ ከዚያም ልጆቻችን ከሌሎች ሰዎች ጋር ይጋባሉ”
ልጅቷም፤
“ታዲያ በመጨረሻ ያው ከሌሎች ከተጋባን ተደባለቅን አይደለም እንዴ?”
አባትዬውም፤
“ልክ ነሽ ልጄ! ሰው ሆኖ ከሌላ ዘር ያልተደባለቀ የለም፡፡ የኔ ዘር ነው ንፁህ የሚባል ነገር ፈፅሞ የለም!” አላት፡፡
* * * * *
 “አሰላም አሌኩም አሁንም አሁንም ያለንበት ዘመን አያስተማምንም” ይላል የመንዙማው ግጥም! ያለንበት ዘመን ከምንም ነገር በላይ ጥንቃቄን የሚጠይቅ ነው፡፡ ፍቅር ወደ አምልኮተ- ሰብ (Cult) እንዳያመራ ጥንቃቄን የሙጥኝ ማለት ያለብን ዘመን ነው፡፡ የምንወድደው መሪ አስተሳሰብ ላይ ድክመት ብናይ፤ ያቀዋል፣ አውቆ ነው፣ ሳያስብበት አይቀርም ማለትን መፆም ይኖርብን ይሆናል፡፡ አብዛኛውን ጊዜ ስህተት የሚከሰተው የአላስፈላጊ መላላት ሰለባ በምንሆንበት ጊዜ ነው! ሰዎችን ከእሥር ቤት አስፈታን ማለት ከእንግዲህ እሥር ደህና ሰንብች ማለት አይደለም፡፡ ህዝብ እንዳሻው ሊተረጉም ይችላልና ፍፁም ህገ-ወጥ ድርጊት ሲፈፅሙ የተገኙ ግለሰቦች፤ አግባብ ያለው ህጋዊ እርምጃ ቢወሰድባቸው፤ “ይሄዋ መሪያችን ራሱ ሲቃወም የነበረውን ነገር፣ ገና በሩብ ዓመት ውስጥ ገብቶ ተዘፈቀበት”፤ “ያመኑት ፈረስ፣ ጣለ በደንደስ!”
ከተማረ ፉከራ
ያልተማረ እንዴት አደርክ?” ይሻላል ወዘተ ይባላል። ያለንበት ዘመን የገዛ ደጋፊያችን እገዛ፤ “አያድን ጋሻ ቂጥ ያስወጋል” እንዳይሆን በተቻለ የምንጠነቀቅበት ነው!
“አይዞህ” ለመባባል እንኳ ሰዓት የምናጣበት ጊዜ ሊፈጠር ይችላል፡፡ ነፃነትን የመራብ፣ ዲሞክራሲን የመጠማት፣ ፍትህን የማጣት በደል የነበረበትን ህዝብ፤ ሁሉን በአንዴ ተጎናፅፈሃል ሲባል ከባድ የመሳከር ስሜት ውስጥ የመስጠም አደጋ ላይ ሊወድቅ ይችላል፡፡ ሚዛን ይጠፋል፡፡ ሳይግባቡ በስሜት መነዳት ይከተላል፡፡ ጓዳና ገመናን ግልጥልጥ አድርጎ መዋረድን ያመጣል፡፡ ትፍሥሕተ- ገነትን የተጎናፀፍን ይመስል በሀሴት ማዕበል እንጥለቀለቃለን!! ይሄ አደጋ ነው! ያለንበት ዘመን አንዱ ልል ገፅታ ይሄ ነው!
የቋንቋ መወራረስ ሌላው አስገራሚ ባህሪ ነው! የደርግ ዘመን ካድሬያዊ ልሣን ነበረው፡፡ ከላይ እስከ ታች የሚፈስ፣ ከተመሳሳይ ጣር የሚፈልቅ የሚመስል የቃላት ጋጋታ- እንደ በቀቀን መትከንከን፤ ይውደም ብሎ ይለምልም እስኪባል ድረስ የሚደጋገም ፈሊጥ፡፡ ከዝቅተኛው መደብ ሰው እስከ አብዮታዊ ጓድ  ድረስ በክሊሼ የቁም ቃላት ውርስ መጥለቅለቅ! መሸቀጫ አሰልቺ ሐረጎችን ማነብነብ! አርቲፊሻል የቃላት የደም ቧንቧ የተገጠመልን እስኪመልስ ድረስ መንደቅደቅ!
አድሃሪ፣ አብዮተኛ፣ ንቃት፣ ትግላችን መራራ፣ ሂስና ግለሂስ፣ ዘመቻ  ወ.ዘተ… ከዚያ የኢሕአዴግ ዘመን መጣ! ሁሉም የፖለቲካ ቃላት ከአንድ ፋብሪካ የተፈለፈሉ ይመስል በግምገማ ቢጋር ውስጥ ያሉ- “ይሄን አልወስደውም”፣ “ጉዳዩን አጥርተን እንየው”… “ሥራውን አላደማኸውም”… “በሂደት ይረጋገጣል”… “ዝግጁነት ይጎድለናል”… “መንቀልያዋን (ሥራ መሠረቷን) አምጣት፡፡” “ድክመትን የመሸፋፈን አካሄድ ተንፀባርቆበታል”… “ጓዱ የባህሪ ለውጥ አሳይቷል” ወዘተ ሆነ የቋንቋው ወጀብ! እያንዳንዱ ዘመን የየራሱን የቋንቋ ወረት መቀፍቀፉን ዛሬም እናያለን፡፡ “ስቴሪዮታይፕ” /Stereotype/ cliché/ በቀቀናዊነት፤ አሻራው ፍጥጥ ብሎ እንደጎረምሳ ብጉር ይታያል!
ፍቅር…ሰላም…አንድነት…መቻቻል…መግባባት…በጠረጴዛ ውይይት መፍታት…እርቅ…ምህረት…ይቅርታ ወዘተ የዘመኑ ፈርጣ ፈርጦች ሆነዋል! የሚገርመው እነዚህ ቃላት “በራሳቸው ጊዜ” የመጡ እንጂ፣ ማንም ማንንም ይህን ተናገር ብሎ አሊያም በዚህ ልሣን ካልተናገርክ ትቀጣለህ ብሎ መንግስት አዞ/አስፈራርቶ አይደለም! የየዘመኑ ቋንቋ ያለማንም መመሪያዊ ተፅዕኖ በየራሱ አሸንዳ ውስጥ ይፈስሳል! በየድጋፍ ሠልፉ የምንታዘበው ድግግሞሽ ይህ መሆኑ ያስገርማል!
ሌላው የዘመኑ ተመሳሳይ ባህሪ የቢሮክራሲው መሣሪያ (bureaucratic apparatus) ተመሳሳይ ጎራዊ ዘዴ ነው። የሥራ ማቀዛቀዝ፣ በዱሮው ቋንቋ sit-down-strike እና አቅጣጫ የማጣት ግራ-ገብ አካሄድ አሊያም መላ-ማጣት (obscurantism) ደርጋማነት ነው! በወገናዊነት ድርና-ማግ የተተበተበ ቢሮክራሲ፣ በአዲስ ደም ሥርዐት (new-blood-injection) እና መተካካት ቡድናዊ ዝምድና (partisan nepotism) ውስጥ በመቆላለፉ አሁን ለታሰበው ሽግግር እንቅፋት አይፈጥርም ብሎ ማሰብ ቢያንስ የዋህነት ነው! በአሮጌ ጋን አዲስ ጠላ መጥመቅ (old wine in a new bottle) አባዜው ብዙ ነው!! ነባሩ ሥርዓት የፈጠራቸው ሙሉ በሙሉም ባይሆን በመንገድ ላይ ያሉ ኢ-ዲሞክራሲያዊ /ሀሳዊ-ዲሞክራሲያዊ ተቋማት (Pseudo-democratic institutions) ዕጣ- ፈንታ አለመታወቁ፣ የሂደቱ ድንግዝግዝ ውዥንብር ነፀብራቅ ነው፡፡ ሰፋ ያለ አዲስ ዕይታን (a new vista) ይጠይቃል፡፡ አልፎ አልፎ እንደተወርዋሪ ኮከብ ፍንጥቅ ፍንጥቅ ያሉትን ግለሰቦች ተመልከተን፣ የአሮጌውን ቢሮክራሲ አዋሽ በርሜል (ጋን) ስፋትና ከዚህ አብራክም ሊወለድ የሚችለውን አዲስ አራስ ሙሉ በሙሉ መቀበል (ማመን) ፈታኝ ነው! አዲስ ምንጊዜም አሸናፊ ነው /the new is invicible/ የሚለውን ዲሌክቲካዊ ዕውነታ ብናበረታታም፣ የጎታቹን ቢሮክራሲ አቅም የምንንቀው አይሆንም፡፡ በተለይም ከአቀባባይ ነጋዴ ጋር ፋይናንሳዊ ትሥሥር እንዳለው ስናሰምርበት፣ ቢሮክራሲያዊ ከበርቴው ምን ያህል አንገቱን ቀና አድርጎ እንደሚጓዝ እንመሰክራለን! በዚህ አንፃር በአሮጌ ጋን አዲስ ጠላ መጥመቅ፣ ወይስ በአዲስ ጋን አሮጌ ጠላ መጥመቅ ወይስ ጋኑም ጠላውም አዲስ ነው የሚል ጥያቄ መጠየቅ ይታሰበን! ይታሰብበት!

የፌደራል ፖሊስ የደንብ ልብስ ለብሰውና በመሣሪያ ታግዘው፣ ከአንድ ግለሠብ ቤት ውስጥ 1.5 ሚሊዮን ብር እና መጠኑ በትክክል ያልታወቀ ዶላር የዘረፉ ተጠርጣሪዎች በፖሊስ ቁጥጥር ስር ዋሉ፡፡ ፖሊስ በተጠርጣሪዎቹ ላይ ምርመራ እያካሄደ ሲሆን ግለሰቦቹ የፌደራል ፖሊስ አባላት ይሁኑ አይሁኑ፣ በምርመራ እንደሚያረጋግጥም ተገልጿል፡፡
ሰኔ 27 ቀን 2010 ዓ.ም ቀትር ላይ በአዲስ አበባ ንፋስ ስልክ ላፍቶ ክፍለ ከተማ፣ ሃና ማርያም አካባቢ፣ ሁለት የፌደራል ፖሊስ የደንብ ልብስ የለበሡ ሰዎች፣ የግለሰብ መኖርያ ቤት ውስጥ በመግባት ዝርፊያውን እንደፈፀሙ ምንጮች ጠቁመዋል፡፡
ሁለቱ ግለሠቦች የዘረፉትን ገንዘብ ይዘው ሲንቀሳቀሱ  የተመለከቱ የአካባቢው ነዋሪዎች “የድረሱልኝ ጩኸት” በማሠማት፣ ተጠርጣሪዎቹ በፖሊስ ቁጥጥር ስር እንዲውሉ ማድረጋቸውን ለማወቅ ተችሏል፡፡ ተጠርጣሪዎቹ ዘረፋውን ከፈፀሙ በኋላ የተመለከቷቸውን ሰዎች በመሳሪያ ሲያስፈራሩ እንደነበር የተናገሩት ምንጮች፤ ወዲያውኑ በፖሊስ በተደረገባቸው ክትትል፣ ከአካባቢው ሳይርቁ መያዛቸውን ጠቁመዋል፡፡
ፖሊስ በበኩሉ፤ ተጠርጣሪዎቹ የፌደራል ፖሊስ አባላት ይሁኑ አይሁኑ ማረጋገጥን ጨምሮ፣ ምርመራ እያደረገ መሆኑን አስታውቋል፡፡

በያዝነው ሣምንት በሰሜን ምዕራብ እና በደቡብ ኢትዮጵያ በሚገኙ ሁለት የጠረፍ ከተሞች በተለያዩ መነሾዎች የተከሰቱት ጠንከር ያሉ ግጭቶች በሰው እና በንብረት ላይ ጉዳት ማስከተላቸውን ምንጮች አመለከቱ፡፡ ግጭቱቶቹ የተከሰቱትም በአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ የተዘጋጀው የጠረፍ ከተሞችን ችግሮች የመዳሰስና የፖሊሲ ምክረ ሐሳቦችን የመቀመር  ዓላማ ይዞ የተካሄደው አውደ ጥናት በተጠናቀቀ ማግስት ነው፡፡   
በዚህ አውደ ጥናት ላይ ኢትዮጵያ ሞያሌ እና መተማን ከመሳሰሉ የጠረፍ ከተሞች የመጡ ሰዎች የተሳተፉ ሲሆን እነዚሁ ተሳታፊዎች ጉባኤውን አጠናቀው ወደየመጡበት በመመለስ ላይ ሳሉ ግጭቶቹ መከሰታቸውን የጠቀሱት ምንጮቻችን፤ የመተማው ግጭት ሰኔ 27 ቀን 2010 ዓ.ም፣ የኢትዮጵያ ሞያሌው ደግሞ በማግስቱ ሰኔ 28 ቀን 2010 ዓ.ም በተከታታይ ቀናት መከሰታቸውን ጠቁመዋል፡፡ ውጥረት ተለይቷት በማታውቀው የኢትዮጵያ ሞያሌ ከተማ የተከሰተው ጎሣን መሠረት ያደረገ ግጭት መሆኑንና የመተማው ደግሞ ከእርሻ መሬት ጋር የተያያዘ እንደሆነ የጠቀሱት ምንጮች፤ ከሁለቱ ከተሞች የመጡት የጉባዔው ተሳታፊዎች፣ በስብሰባው ላይ ከሰጡት አስተያየት መረዳት እንደሚቻለው በተደጋጋሚ ግጭቶች ይከሰታሉ፡፡
በኢትዮጵያ ሞያሌ ከተማ ከሁለት ወር በፊት ሚያዚያ 28 ቀን 2010 ዓ.ም ተፈጥሮ በነበረ የጎሣ ግጭት በርካታ ሰዎችን ለጉዳት የዳረገና ንብረትም ያወደመ ግጭት መከሰቱ የሚታወስ ሲሆን፤ ከትናንት በስቲያ ሐሙስ ሰኔ 28 ቀን 2010 ዓ.ም ከሰዓት በኋላ ዳግም ባገረሸው ጎሣን መሠረት ያደረገ ግጭት ከሁለቱም ወገን ሰዎች መሞታቸውንና ከመሐል ሐገር ወደ ሞያሌ የሄዱ ዘጠኝ የጭነት መኪኖችም መጋየታቸውን አመልክተዋል፡፡
በሞያሌ በሚገኘው የፌደራል ገቢዎች እና ጉምሩክ ቅርንጫፍ መስሪያ ቤት ላይ ጉዳት መድረሱን የጠቀሱት ምንጮቻችን፤ በገሪ እና ቦረና ጎሣዎች መካከል የተከሰተውን ይህን ግጭት ለማብረድ የጸጥታ ኃይሎች ጥረት ማድረጋቸውን ጠቁመው፤ ግጭቱ በዘመናዊ መሣሪያ የተደገፈ በመሆኑ ጉዳቱን ከፍ እንደሚያደርገውና የጸጥታ ኃይሎች ግጭቱን ለመቆጣጠር የሚያደርጉትን ጥረት አስቸጋሪ እንደሚያደርገው አስውቀዋል፡፡
በኦሮሚያና በኢትዮ-ሶማሌ ክልል ሥር ለሚተዳደሩ ሁለት ወረዳዎች መቀመጫ በመሆን በምታገለግለውና የአንዳንድ የፌዴራል መስሪያ ቤቶች መቀመጫ በሆነችው የሞያሌ ከተማ፤ ከሁለት ወራት በፊት ከአስፋልት ግራና ቀኝ በመሆን ባካሄዱት የተኩስ ልውውጥ  በርካታ የከተማው ነዋሪዎች ለአካል ጉዳትና ለሞት መዳረጋቸውን እንዲሁም ንብረት መውደሙን ያስታወሱት እነዚሁ ምንጮች፤ ከተማዋ ዘወትር በውጥረት የምትኖርና ባልረባ ምክንያት ግጭት እንደሚቀሰቀስ፤ ሁለቱ ጎሣዎች በመበቃቀል መንፈስ እንደሚጠቃቁ፤ የከብት ዝርፊያ እንደሚካሄድና በከተማው በሰፊው በሚታዩ የሞተር ሳይክሎች የታገዘ የሰዎች ጠለፋ አንደሚፈጸም ተናግረዋል፡፡
በአንድ የአስፋልት መንገድ ግራና ቀኝ ተለያይተው በሚገኙት በሁለቱ መስተዳድሮች የሚታዘዙ የጸጥታ ኃይሎች፣  በግጭቱ ተሳታፊ እንደሚሆኑ የተናገሩት ምንጮቻችን፤ የሶማሌ ክልል ልዩ ኃይልና የኦሮሚያ ክልል አድማ በታኝ አባላት እንዲሁም የቀበሌ መስተዳድር ሚሊሻዎችን በስም ይጠቅሳሉ፡፡ የገሪ ጎሣ አባላት (ሶማሌ) እና የቦረና ጎሣ አባላት በፈጠሩት ግጭት፣ ከሁለቱም ወገን ሁለት-ሁለት ሰዎች ለህልፈተ ህይወት መዳረጋቸውንም አመልክተዋል፡፡
በሌላ በኩል፤ ሱዳንን ከኢትዮጵያ በሚያዋስነው የምዕራብ ጎንደር ዞን፣ መተማ አካባቢ የሚገኝ የእርሻ መሬት ይገባኛል ጥያቄ ለግጭቱ ምክንያት መሆኑን የጠቀሱት የዞኑ ዋና አስተዳዳሪ አቶ ዘላለም ልጃለም፤ ‹‹ሱዳኖች በኢትዮጵያ መሬት ላይ የሚያነሱት የይገባኛል ጥያቄ ትክክል አይደለም›› ብለዋል፡፡
‹‹የእርሻ ስራ በሚያከናውኑ የአካባቢው የኢትዮጵያ አርሶ አደሮች ላይ ትንኮሳ በመፈጸማቸው ምክንያት ግጭቱ ተከስቷል›› ያሉት ኃላፊው፤ የአካባቢው አርሶ አደሮችም የመከላከል አጸፋ መውሰዳቸውንና አሁን የኢትዮጵያ መከላከያ ሰራዊት በቋራ እና መተማ ጥበቃ እያደረገ መሆኑንም ገልጸዋል፡፡ የዞኑ አስተዳዳሪና አርሶ አደሮች እንደተናገሩት፤ አሁን ላይ ግጭቱ የተረጋጋ ቢመስልም፤  በሱዳን ወታደሮች ትንኮሳ ምክንያት በአካባቢው ባሉ ሌሎቹ የኢትዮጵያ መሬቶች ላይ የእርሻ ስራ ማከናወን አልተቻለም ፡፡
ከአማራ ብዙሃን መገናኛ የተገኘው መረጃ፤ በግጭቱ ምክንያት በመተማ ደለሎ በኩል የሚገኝ የሱዳን ጦር የተደመሰሰ ሲሆን፤ አንድ የሱዳን ሻለቃ አመራር ህይወቱ አልፏል፡፡ በቋራ ነፍስ ገበያ በኩል በተፈጠረው ግጭትም 7 የሱዳን ወታደሮች መሞታቸውንና 2 መኪናዎችንና 7 የጦር መሳሪያዎችም መማረካቸውን አቶ ዘላለም ተናግረዋል፡፡
ሶስት የኢትዮጵያ አርሶ አደሮችና ሁለት የመከላከያ ሰራዊት አባላት ህይወታቸው ማለፉንም ሰምተናል፤ 6 ሰዎች ደግሞ ጉዳት ደርሶባቸው ሆስፒታል መግባታቸው ታውቋል። ከነዚህም መካከል ሁለቱ የመከላከያ ሰራዊት አባላት ናቸው። ለጣምራ የጸጥታ ቁጥጥር በሚል በአካባቢው የሰፈረው የሱዳን ጦር፣ በተለያዩ ጊዜያት ትንኮሳ እንደሚፈጽም የአካባቢው ነዋሪዎችና ዋና አስተዳዳሪው አስረድተዋል። በተደጋጋሚ በሰላማዊ መንገድ ቦታውን ለቀው እንዲወጡ ጥረት ቢደረግም ፈቃደኛ አለመሆናቸውም ታውቋል፡፡
(የድንበር ጉዳዮችን የሚፈትሸውንና በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ሰሞኑን የተካሄደውን ወርክሾፕ የተመለከተ የቅኝት ዘገባ በሚቀጥለው ዕትም ለንባብ ይቀርባል፡፡)

 • “ርካሽ ዝና ከኔ ትወስዳለች እንጂ ልጆቼን አታሳየኝም”
      • “የልጆቼ እናት ለማኝ ሆና እንቅልፍ የሚወስደው አዕምሮ የለኝም”
      • “እህቴ ለእርሷ እንጂ ለኔ አድልታ አታውቅም”

   ከአዘጋጁ
ለውድ አንባቢያን፡- ባለፈው ሳምንት የታዋቂው ደራሲ ይስማዕከ ወርቁ ባለቤት ፀጋ አንዳርጌ ምህረት ዝግጅት ክፍላችን ድረስ መጥታ “ህዝብ ብሶቴን ይስማ” በማለት፣ ደረሰብኝ ያለችውን በደል መዘገባችን ይታወሳል፡፡ ወደ ማተምያ ቤት ከመሄዳችን በፊት ግን ደራሲ ይስማዕከ ወርቁን አግኝተን ምላሽ ወይም ማብራሪያ እንዲሰጠን ጥረን ነበር፡፡ ያደረግነው ሙከራ ግን ሳይሳካ ቀርቷል፡፡ በዚህ ሳምንት ይስማዕከ ፈቃደኛ ሆኖ፣ ለጥያቄዎቻችን በፅሑፍ ምላሽ ሰጥቷል፡፡ በኢ-ሜይል የላከልንን ከሞላ ጎደል እንዳለ አቅርነበዋል፡፡ ጥንዶቹ ችግሮቻቸውን በመነጋገር ይፈቱታል ብለን ተስፋ እናደርጋለን፡፡
ስለ ባለቤትህና ስላንተ ግንኙነት ባጭሩ ብትነግረኝ?
እኔም በትምህርትና በመፃፍ ነው ሕይወቴን ያሳለፍኩት። ሕይወቴ ከታመምኩ በኋላ ምስቅልቅሉ መውጣቱም ይህን ያሳያል፡፡ ጋብቻችንን የፈፀምነው ከክርስቶስ ልደት በፊት ነው ብትልም በጣም ጥሩ ነው፡፡ በ02/02/2008ዓ.ም-በተራ ቁጥር 031883፣ በክብር መዝገብ ላይ ተመዝግቦ ነው፡፡ የሚገኘው ጋብቻችን፡፡ ከዛም በኋላ አንድ ወንድ ልጅ፣ አንዲት ደግሞ ሴት ልጅ ወለድን፡፡ የጠቀሰችው ዓመተ ምህረት ግን ትክክል አይደለም፡፡ የሚገርመው ለዚህ ጋዜጣ የሰጠችውና ለፍርድ ቤት ያቀረበችው ተመሳሳይ አይደለም፡፡ በተለይም መላ ቤተሰብዋን ምስክር አድርጋ ካቀረበቻቸው ላይ ሁለቱ በጠቀሰችው አመተ ምህረት ይወለዳሉ ወይ ነው ጥያቄው፡፡ የልጆቼ እናት ናትና ምን እላለሁ፡፡
ባለቤትህ ባለፈው ሳምንት በአዲስ አድማስ ላይ ያቀረበችውን ቅሬታ እንዴት ታየዋለህ?
ባለፈው ሳምንት ጋዜጣ ላይ አሜሪካ ለኮሪያ ወይም ለራሺያ የማትሰጠው አቲካራ ሆኖ ባገኘውም የሰጠችው ቃለ ምልልስ፣ ምንም ብንለያይም፣ የልጆቼ እናት ናት፡፡ ምንም ማድረግ አይቻልም፡፡ ልጆቼን የሚጎዳ ነገር እዚህ ላይ መናገር አልፈልግም፡፡ ልጆቼ በእኔ እንዲያፍሩ አላደርግም። ሁሉም ያልፋል፡፡ እኛም ራሱ እናልፋለን፡፡ ግን መጥፎ ታሪክ ሰርተን፣ ወይም የማይጠፋ ቃል ተናግረን ካለፍን፣ የእኛ ሸክም ልጆቻችን ላይ ይከመራል፡፡ እነሱ በማያውቁት ነገር ሲጎዱ ይኖራሉ፡፡ ስለዚህ አቀራረቡ ቢያሳዝነኝም አልፈዋለሁ፡፡ ሌላው ...የተካሰስነው እኔ እና እርሷ ነን፡፡ በእኔ ዙሪያ ማንንም እንድታይ ፈቃደኛ አይደለችም፡፡ ግን የመጨረሻ የማሳስባት ነገር ቢኖር፣ ከኮሚቴው ራስ ላይ ትውረድ፡፡ አንዱ ወይም መላ ኮሚቴው በስም አጥፊ ቢከሳት የለሁበትም፡፡ ሽመልስ አበራ ጆሮ ነው ሚያጭበረብር? ኮሜዲያን ደረጀ ኃይሌ ነው እሚያጭበረብር? መንገሻ ተሰማ ነው እሚያጭበረብር? ፍርያት አትክልት ነው እሚያጭበረብር? መሳይ ወንድሜነህ ነው እሚያጭበረብር?  እስከ ዛሬ ከሰማኋቸው ዜናዎች “አዬ ጉድ” የሚያስብል ወሬ ነው... እራሷ ገንዘብም ቆጥሬ አላውቅም፡፡ አዲስ አበባ ያሉትን ጓደኞቼን ... እስክድን እንኳ አቅቶሽ፣ ያለ ስሜ ስም ሰጥተሽ፣ ለጉዋደኞቼ ተናግረሽ ሲርቁኝ ጥሎኝ ያልሄደውን ፍርያትን “የእርሱ አፈ ጉባኤ” በማለትሽ ፀፀቱ ለራስሽ ነው፡፡  ሰይፉ ፋንታሁንም እስከ ዛሬ ተገናኝተን፤ “ህዝቡን እንዴት መዝረፍ አለብን” በሚለው ላይ ተገናኝተን አውርተን አናውቅም:: በኮሚቴው ላይ ያነሳሽው አሰስ ገሰስ ወሬ ጊዜውን ጠብቆ ትከፍይበታለሽ። ኮሚቴዎቸን በተመለከተ የራሳቸው ዝና ያላቸው ናቸው፡፡ እንኳን እርሷ ልታጎድፋቸው፣ እኔም ብሆን ቀና ብዬ ለማየት የማፍር፣ ከእነርሱ ጋር ብጣላ ከመላው ኢትዮጵያ ህዝብ ጋር እንደምጣላ አውቀዋለሁ፡፡ እነሱ ሲጠይቁኝ ነው መኖሬ የሚሰማኝ፡፡
ኮሚቴው ራሱ “እኛ ገንዘቡ ቢገባ እንተማማለን፣ በአንተ ስም በተከፈተ አካውንት ይግባ” ተብዬ ነው በእኔ ስም የተከፈተው፡፡ ከሰይፉ ሾው በሁዋላም አንዲት ሳንቲም ነክቼ አላውቅም፡፡ ሂዱና በብርሃንና ሰላም ቅርንጫፍ ንግድ ባንክ ተመልከቱ፡፡ የባህር ዳር ልጆች ምስክር ሊሆኑ ይችላሉ፡፡ ገንዘቡን በባንክ አስገቡ ሲልዋቸው፡፡ እኔ ጋ ቼኩ አልደረሰም። ቢጠፋበት አንድ ሰው ብለው፤ ተመንዝሮ ነው የተላከው፡፡ እኔም ለጤናዬ እንጂ ገንዘቡ የሚውለው፣ በፍፁም የኢትዮጵያ ህዝብን አላጭበረብርም፡፡ አንቺ እኮ እኔን ስታጭበረብሪ ነበር፡፡ ሁሉንም ባንቺ ሂሳብ አትለኪ። ፍርድ ቤቱ ባግባቡ ይፍረድና፣ እኔ ጤናዬን እንጂ ሁሉም ነገር ለልጆቼ ይውላል፡፡ እርሱንም በእኔ በአባታቸው ስም ከተጠሩ ብቻ ነው፡፡
ከባለቤትህ ጋር ለፍቺና ለፍርድ ቤት ያበቃችሁ ነገር ምንድን ነው?
ከዛ በፊት ታስሬ ነበር፡፡  ምክንያት በሌለው ምክንያት። በእርስዋ ምክንያት፡፡ ወይ ሐምሌ መጀመሪያ ላይ ወይም ሰኔ መጨረሻ ላይ፡፡ ሐምሌ ላይ ታሰርሽ ማለት ደግሞ ጉዳይሽ ጥቅምት መጨረሻ ላይ ነው የሚታይልሽ፡፡ መንግሥት በምን  ልሰረው እያለ፣ ወስዳ ከተተችኝ ሚስቴ፡፡ ብታሰር አሪፍ ነበር፡፡ ይህን ሁሉ ፈተና አላይም ነበር፡፡ ከባድ የመኪና አደጋ ያስተናገድኩትም ከዛ በኋላ ነው፡፡ ያው በእርሷ ምክንያት ማለት ይቻላል፡፡ ለምን? ሀዋሳ ውስጥ ነኝ ብላ ለእህቴ ተናገረች፡፡ እኔ እዚህ አዲስ አበባ ውስጥ ነበርኩ ማተሚያ ቤት፡፡ ባንክ ቤት ሄድኩና “ወይ ሸጣችሁ ክፈሉ ወይም እኛ ጨረታ ልናወጣው ነው ቤቱን” ተባልኩ። ለባንኮቹ እንኩዋን ቤቱን ራሴንም ቢሸጡኝ ክብር አለኝ፡፡ አከብራቸዋለሁ፡፡ ረቡዕ ነበር፡፡ ወደ ሀዋሳ በዛው ነዳሁት፡፡ እህቴ ቤት አደርኩ፡፡ ሐሙስ በጥዋት ገዢ ፍለጋ ተነሳሁ፡፡ ዘጠኝ ሰዓት ላይ ገዢ አገኘሁ፡፡ ከዛ ወደ ሻሸመኔ ሄድን፡፡ ወደ እህቴ ደወልኩና “በዓይኔ እየሄደብኝ ነው፣ ልጄን አሳይኝ፡፡” እላለሁ እኔ፡፡ “ሀዋሳ ሪፈራል ሆስፒታል ናት ሰው ታሞባት” ትለኛለች እርሷ፡፡ “ትጨርስና አምጥቼ ልጅህን አሳይሃለሁ።” ከዛ ከጆሮዬ ጥልቅ አለ አንድ ነገር፡፡ ሀዋሳ ውስጥ የለችም፡፡ አብረን ለገዢው ብንሸጥለትስ? አዲስ አበባ ናት፡፡ እንዲያውም ለሃያ ሁለት ቀናት አዲስ አበባ ናት፡፡ ከዛ ወደ ይርጋለም እየነዳሁት ነበር፡፡ ያደፈጠ መኪና መጥቶ እስኪጋልበኝ ድረስ፡፡ ከዛ በኋላ ጥቁር አንበሳ ሆስፒታል ነቃሁ፡፡ መናገር አልችል፣ መጻፍም አልችልም ነበር፡፡ ቀስ ቀስ እያልኩ ነው የተለማመድኩት፡፡ እንዲያውም… መቆም አይችልም ብለው ነበር አሉ ሀኪሞች፡፡ ይቅርታ አድርጉልኝና ከሰማይ ከምድር ያህል የሚከብደኝ ቂጤ ነበር፡፡ ሽንት ቤት አንድ ቀን ገባሁና ተቀመጥኩ፡፡ መነሳትም አልችልም፡፡ አልናገርም፡፡ እንዴት እህቴን ልጥራት፣ ብልጎመጎም፣ ብልጎመጎም፡፡ ከብዙ ሰዓት በኋላ እህቴ መጣች፡፡ ከዚሁ ጋር… ወንድሟ ሰው ገጨ ተብሎ ብትሰማ፣ እንባዋ ማባሪያ ጠፋው፡፡ ወንድሟ ታልቅስ፡፡… እንዲያውም በእኔ ጊዜ፣ አዲስ አበባ ሰምታ፣ “ኢየሱስን አመስግኑ” በማለት … አሁን ወደ ኋላ ታሪኬን ሳጠና፣ መላ የሀዋሳ ህዝብ አዝኖ፣ እነሱ ግን አልመጡም … ፀሎት ላይ ነበሩ፡፡ የልጃቸው አባት ነበርኩ፡፡
አዲስ አበባ ውስጥ ከቅርብ ጓደኛዬ ጋር ለ22 ቀናት ነበረች፡፡ እኔና እሱ በቀን በቀን እየተገናኘን ነበር፡፡ ለ22 ቀናት ባለቤቴን እንዳስቀመጠ ግን አልነገረኝም፡፡ አሁን የሚለው ግን “ልጅህ ታሞ” ብላ ደውላልኝ መጣች፣ እርሱ በችግሩ ጊዜ ከእኔ እንደማይወስድ፣ ልጅህን ላሳክምልህ ነው” የሚለኝ፡፡ ሆኖም እንደ እኔ ባጋጣሚ ሳይሆን፣ የሚፈልገውን ላሟላለት ነው ልጄን የወለድኩት፡፡ ደሜ የፈሰሰውም ለእርሱ ነው፡፡ የአራት ሰው ደም ነው የወሰድኩት፡፡ በዛ ላይ ቆንጆ ልጅ ነው፡፡ እንደምወደው እያወቀ፣ ሌሊት ሌሊት በህልሜ ከእርሱ ጋር እንደማድር እያወቀ፣ ባለቤቴን ከቤቱ እንዳስቀመጠ ሳላውቅ…፡፡ እሷ እሱ ቤት ሆና እንድትከሰኝ አመቻችቷል፡፡ እኔ ሳላዉቅ፡፡ እኔ ከጥቁር አንበሳ ሆስፒታል ወጥቼ እያገገምኩ፣ ጠበቃ የሆነ አንድ ጓደኛ ነበረኝ፡፡ “አራዳ ፍርድ ቤት ባለቤትህ ስትመላለስ ነበር” አለኝ፡፡ ቅርብ ስለሆነ ሄድኩ፡፡ ቦርዱ ላይ ሳየዉ ከሳኛለች፡፡ ወደ ላይ ስወጣ፣ “ጥቁር አንበሳ ሆስፒታል ነው ያለው፡፡ እና ጉዳቱ የጭንቅላት ነው ይህን መስጠት የለብሽም፤” … ከብዙ ድራማ በሁዋላ ወደ መዝገብ ቤት ተመለሰ፡፡ “ለምን እኔ አልጠይቃትም” ብዬ ትዳር እኮ ማቆየት እንጂ አደጋው፣ ለማፍረስ ምንም እኮ ችግር የለውም፡፡ ትዳሩ ደበረኝ ብሎ እኮ ማፍረስም ይቻላል። እንኳን ይህ ሁሉ ምክንያት እያለኝ” እኔም በዛው ቀን የፍታህ ብሄር ክስ ይዤላት መጣሁ፡፡ እኔም ስለማልስራ አንቺም ስለማትሰሪ ፍርድ ቤቱ “ይህ ያንቺ፣ ይህ የእኔ” እስኪለን ድረስ አብረን እንኑር፤ ተባብለን አብረን መኖር ጀመርን፡፡ ማድረግ ያልነበረብኝ ነገር ነው … እስከ መጋቢት 29/2010 ድረስ፡፡ ወይ አንሰለጥን፣ ወይም ደግሞ…፡፡
ወደ ፍርድ ቤት ከመሄዳችሁ በፊት ችግራችሁን በሽምግልና ለመፍታት አልሞከራችሁም?
እኔ ከአስራ አምስት  ጊዜ በላይ ሽምግልና ሞክሬአለሁ። እነ ዶክተር እዝራ፣ እነ አየለ እምሩ፣ እነ ብርሃኔ ዘርው፣ እነ ሽመልስ አበራ ጆሮ…፡፡ እኔ እርሷን አልከሰስኳትም፡፡ ክስዋን የሰጠችው ለፖሊስ ነው፡፡ እኔ ታምሜ ምንም አላይም፡፡ ከዛ ወደ መዝገብ ቤት ተመለሰ፡፡ ደግሞ እኮ ይነገራል፡፡ እኔ ሄጄ ባየው ጊዜ በጣም ነው የተናደድኩት፡፡ ደግሞ ወዲያውኑ ነው የወሰንኩት፡፡ ሰው ከጠላቱ ጋር አይኖርም፡፡ እሷም ያሰበችው ይኖራል፡፡ እንዲህ በቀላሉ ትዳር የሚያስፈታ ነገር ምን አለ? እኔን ጨካኝ አድርገው የሳሉ ሰዎች ይኖራሉ፡፡ ምንም የማላውቀው ነገር  ስላለ ነው፡፡ ድርጅት ነበረን፣ እኔ ስተኛ አብሮ ተኛ፡፡ ሠራተኞች ነበሩ፤ እየነቃሁ ስመጣ ግን በሙሉ ተበትነዋል፡፡ ምን አለ አሁን ተቀምጦ ሂሳብ ከመስራት፤ እንደ ባለትዳር የማታስተዳድረው ድርጅቱን?... በጣም አሳዛኝ ነው፡፡ ሽምግልናው ሰልችቶኛል፡፡  ቃል ተጠብቆ፣ ይህን ያሉኝን አላደርግም ብሎ አይሆንም፡፡ ቂም አንድ ቀን እስኪያስተምራት መጠበቅ ነው፡፡
ፍቺ ከጠየቅህ በኋላ ከአንዴም ሁለት ጊዜ ፍርድ ቤት ያልቀረብክበት ምክንያት ምንድን ነው?
ይህን ህጻን ልጅም ይመልሰዋል፡፡ በውክልና፣ እራሴን ሆኖ ሚከራከር ጠበቃ ጉዳዩን ሰጥቻለሁ፡፡ እኔ አልናገርም። ዳኛዋን እንደ እርሷዋ በእንባ ለመብላት ነው እንዴ? ሳልናገር ተቀምጬ፣ ዳኛዋን ትክክለኛ ፍትህ እንዳትሰጥ አላደርጋትም። ለፍትህ መዛባት ሲሉ፣ የማይደረግ ነገር የለም።  ናፈቅኳት እንዴ?... ይህ የምትለውን ስታጣ ግራ ገብቷት ነው፡፡
ሰኔ 26 ለተያዘው ቀጠሮስ ትቀርባለህ?
እንዳልኩሽ ነው፡፡ ግን ጠበቃዬ በህመም ወይም በሌላ ነገር ከቀረ፣ እኔ ሄጄ በፅሁፍ የምጠየቀውን ልመልስ እችላለሁ፡፡ የከበደኝን “ጠበቃዬን ላማክርና እርሱ ይመልስላችኋል” ልል እችላለሁ፡፡ እኔ በፅሁፍ ይመለስ ወይም አይመለስ አላነበብኩም፡፡
በአሁኑ ሰዓት ባለቤትህና ልጆችህ በምን ሁኔታ ላይ እንዳሉ ታውቃለህ?
የእርሷን መኖሪያ አላውቅም፣ ልጆቼን ብታሳየኝም ጥሩ ነበር፡፡ አዲስ አበባ ነች ስላት ሌላ ሀገር ትሄዳለች፡፡ የአንተ ልጆች አይደሉም ነው የምትለኝ፡፡ ርካሽ ዝና ከእኔ ትወስዳለች እንጂ ልጆቼን አታሳየኝም፡፡ ለምሳሌ እስከ 17,000 ብር ይከራይ ነበር ቤቱ፡፡ ባለፈው እዚህ ጋዜጣ ላይ፣ ሰብራ ገባሁበት ያለችው፡፡ የኪራዩ ውልም እኔ ዘንድ አለ፡፡ እኔ ታምሜአለሁ፡፡ ነገርን ከማፋፋም ተቆጥባ፣ ሰብራ ከምትገባ እህቴ ሙሉ ውክልና አላት፡፡ እሷ አከራይታው መኖር አትችልም ነበር?... ወይስ የእኔን ስም ካላጠፋሁት ነው?... ስንቱ የተጣላ እየታረቀ፣ ፍርድ ቤት ንብረት አከፋፍሎ፣ ሰማኒያችንን እስኪቀደው ድረስ ለምን ሰላም ማጣት ያስፈልጋል? … እህቴ ለእርሷ እንጂ ለእኔ አድልታ አታውቅም። ግልፅ ናት፡፡ ሰከን ብላ ማሰብ አለባት፡፡ መካሪዎች ምንም ሊያደርጉላት አይችሉም፡፡ በባለፈው ጋዜጣ ላይ የመካሪ ቃላት ተሞልታ እንደ መጣች ግልፅ ነበር፡፡ ሁሉንም ስድብ ባለቤት ባለቤቱን እያወቅኩት ነበር፣ ይቺ የእገሌ ናት…ወዘተ።  ...አዶኒ ይስማዕከ፣ እና መልእክተ ይስማዕከ ብዬ ለልጆቼ ስም አውጥቼ ነበር፡፡ ሳልጠራችሁ ቀረሁ እንጂ፡፡ እነሱን ግን “ልጆችህም የአንተ አይደሉም” ብላለች፡፡ … አዲስ የእናቶችና የህፃናት ሆስፒታል ሂዱና አረጋግጡ (ከቀበና ገባ ብሎ ነው ያለው)… “Baby Tsega Andarge” የሚል ነው ስሙ፡፡ እኔ አባታቸው ቆሜ ነው ያዋለድኳቸው፡፡ የሚያስፈልገውን ነገር አደርጋለሁ ለልጆቼ፡፡ ልጆቼ ሲታመሙም፣ ትኩሳት ሲኖራቸውም ወስጄ አሳክማለሁ፡፡ እስከ ዛሬም ድረስ ያው በእኔ ስም አይጠሩም፡፡ ወደ ሶስት አመት ሊሆነው ነው፡፡ እኔ ግን አንገቴን ደፍቼ ነበር የማሳክመው፡፡ በጣም ነውሩን የሚያውቁት ብልህ ሴቶች ናቸው፡፡ አባታቸውን በመጠየቅ ሲያድጉ፣ መከራዋን የሚያበሏት እሷን፡፡ በጥቅሉ…  በሌላ ነገር ቢያስጠረጥራትም፣ እኔ ግን ልጆቼን ማንም አይነጥቀኝም፡፡  
የሚላስ የሚቀመስ በሌለበትና ለመኖሪያ በማይመች ቤት ውስጥ እንዳለች ነው የነገረችን …
ሰብራ የገባችበት ቤት ነው? በህግ ያስጠይቃታል፡፡ በቁጥጥር ስር ያዋለችው ሆቴል፣ ያው ከእንጀራ እናቱዋና ከአባቱዋ ቤት አጠገብ ነው፡፡ እኔ እኮ በፍትሀ ብሄር ነው የከሰስኩዋት፡፡ ፍርድ የእርሷ ነው ካለ፣ የእርሱዋ ነው አይደለም; … “እግዚአብሔር ሲያሸነፍህ፣ ራስህን ነው ቀድሞ ስህተት የሚያሰራህ” …የንግድ ቤት ነው፡፡ “መስተዋቱ ያንፀባርቅብኛል፣ መስተዋቱ ረበሸኝ” ብላለች፡፡ ሆቴል ነበረ። እኔ እንኳ ለመኖሪያ ቤት ተመኝቸው አላውቅም፡፡ ከባንክም ባለፈው ዓመት ተበድረንበታል፡፡ እኔ አዲስ አበባ ውስጥ ከከተማ እርቄ ተከራይቼ እኖራለሁ፡፡ እሷ ደግሞ ተከራይቶ ለባንኩ በሚከፈልበት ቤት ውስጥ ትኖራለች፡፡ እስከ 17,000 ብር ድረስ ይከራያል፡፡ የአንተ አይደሉም የምትለኝ ልጆቼ፣ በዚህ ያድጉበት ነበር፡፡ ይህ ሆኖ እያለ፣ ለልጆቼ ክፈል ትላለች፡፡ ብዙ የተከራየ እቃ ያለበት ነው፡፡ ነገ ለሚነሳው ጥያቄ መልሷ ምን ይሆን; ጥበቃውንም አባራዋለች፡፡ “እዛ ግድም አትድረስ ተብያለሁና፣ እኔ ለህይወቴ አደገኛ ነው” ብሎናል፡፡
ዋና መንገድ ላይ ያለ እና ለሆቴል ሲባል ነው የተሰራው እንጂ ለመኖሪያ አይደለም፡፡  መልእክቱ እሱን ለእኔ ስጠኝ እኮ ነው - የባለፈው ጋዜጣ ላይ የወጣው፡፡
1ኛ. እኔ ታምሜ እያለሁ ድርጅቴን ዘጋችው- ወደ ሶስት መቶ ሺህ ብር የቤት ኪራይ እያለበት፡፡
2ኛ. ቤት ሰብራ ገባችበት- የሚከራየውንና ለልጆቼም ለእኔም የሚያኖረንን፡፡
3ኛ.ከዚህ በፊት የወሰደችው 110,000 ብር አለ፡፡ ምስክሮች አሉ፡፡
4ኛ. በኢትዮጵያ ውስጥ የሚገኙትን የባንክ አካውንቴን አሳግዳብኛለች፡፡ ይህ ራሱ በቂ ነው ለእሷ ላለመክፈሌ፡፡ በየትኛውም ባንክ ያለህ፣ ይስማዕከ ብለህ ግባማ አንድ ጊዜ ታግዷል አለህ? ..በቃ፡፡
ይህ ጭራሽ ምቀኝነት፣ ካልሆነ በቀር፣ ባለፀጋዋ ነው በእንባ አባብላ የነገረቻችሁ፡፡ እውነቱ ይውጣና ለልጆቼ እንጂ ለራሴ ምንም አልፈልግም፡፡ እኔ ከዳንኩ ከዜሮ ጀምሬ እጥራለሁ። አብረን ባንኖርም፣ የልጆቼ እናት ለማኝ ሆና እኔ እንቅልፍ የሚወስደው አዕምሮ የለኝም፡፡ ለዚህ ሁሉ ምክንያቱ ራሷ በመክሰሱዋና አብረን ስንት ወራት ስንኖር አለመናገሩዋ ነው፡፡ የቤቱ ጉዳይ ግን እየተከራየ ለባንክ ተከፍሎ ቢሆን ጥሩ ነው፡፡ አለበዚያ ነገ ደግሞ ሊሸጠው እንዳይመጣ፡፡ እኔ ታምሜአለሁ። በአስማት የምሰራ ይመስለዋል ሰው? እሱ “የኦጋዴን ድመቶች” ላይ ብቻ ነው ያለው፡፡ እኔ ደግሞ ደሙን በብድር ነው የወሰድኩት፡፡ የአራት ሰው ደም ተቀብያለሁ ማለቴ ነው፡፡  
መጨረሻ አካባቢ ትኖሩበት ከነበረው ባሻ ወልዴ ችሎት የጋራ መኖሪያ በሌለችበት ቤት ቀይረህ መሰወርህንና የማተሚያ ማሽኖችን ማሸሸህን ተናግራለች፡፡ እውነቱ ምንድን ነው?
በመጀመሪያ ፋሲካ ሲደርስ፣ “አንተ ካልሄድክ ወደ ሀዋሳ እኔ እሄዳለሁ” አለችኝ፡፡ መናገር አልችልም፣ አብረን ሄድን ሀዋሳ። አዲስ አበባ ሳለሁ የሚደውሉልኝን በነጋታው አገኘቻቸው። በሴት እንባዋ አደረቀቻቸው፡፡ (ፈፅሜ ካላዘንኩ እኔ እንባዬ አይመጣም)፡፡ ብዙዎቹ ደነገጡ፡፡ በእኔም ላይ አዘኑ፡፡ የእኔን መልስ ሳይሰሙ ማለት ነው፡፡ አንዳንዶቹ መደወል የጀመሩት አዲስ አድማስ ጋዜጣን ካነበቡ በኋላ ነው፡፡ ለእኔ እኮ እንደዚህ ነበር ያለችኝ፡፡ አሁን እሱን ገልብጣ ጋዜጣ ላይ አወጣቸው፡፡ የስራዋን ይስጣት፡፡ አስገድዶ ወሰደኝ ማለት ምን ማለት ነው; እኔ እኮ ግማሽ ጭንቅላቴ ባዶ ነው፡፡ ጠጠር ቢያገኘኝ እሞታለሁ። ውጪ አገር ቀዶ ጥገና የሚካሄደውም ለእርሱ ነው፡፡ የእኔን በሽታ ለማረጋገጥ ሆስፒታሎቹ ሁሉ ክፍት ናቸው፡፡ ጥቁር አንበሳ ለአይኔ በምኒልክ ሆስፒታል እንዲሰራ ሪፈር ፅፎ ነበር፡፡ የዓይኔ ቀዶ ጥገና ለሚጥለኝ በሽታ የምወስደውን ለሁለት ዓመት በቀን ሶስት ጊዜ፣ ማደንዣውን በመፍራት፣ ሌሎች ይደረጉ በሚል የምኒልክ ሆስፒታል ሌሎች እስኪደረጉ እየጠበቀ ነው፡፡
ሀ) አስቸኩዋይ የጭንቅላት ቀዶ ጥገና (Cranioplasy)
ለ) ለሚጥል በሽታ ጭንቅላት ውስጥ የሚወጣ (Eplepsy)
ሐ) የመናገር ልምምድ (Speech Therapy)
መ) የማገገምያ ህክምና (Rehablitation)
ይህ እውነት ለመሆኑ ጥቁር አንበሳ ሆስፒታል፣ ማንም ሰው ሄዶ ማረጋገጥ ይችላል፡፡ በተጨማሪም ለእኔ ማስረጃ ተሰጥቶኛል፡፡ ሁሉን ነገር ይዤ በተጠየኩት ቦታ ሁሉ እቀርባለሁ። …የጥቁር አንበሳ ሆስፒታልን ማስረጃ ማጣጣል ግን፣ በህግም ያስጠይቃል፡፡
እግዚአብሔር ልቦና ይስጣት፡፡ አንድ ሳምንት ብለምናት ወደ አዲስ አበባ አልሄድም አለች፡፡ እንዲያውም የሚጥል በሽታዬ ተነስቶ ጣለኝ፡፡ ቤታችንም ኪራዩ እየደረሰ ነው ወር በገባ በ16 ነው የቤት ኪራይ የምንከፍለው፡፡ የሦሥት ወር ነው 22,500 ብር ይህን ገንዘብ መክፈል አልችልም፡፡ በዚህ ጭንቀት ላይ እያለሁ፣ “ሀዋሳ ቤተሰቦቿ ጋር ሆና “ልብሴን ላኩልኝ፣ እኔ አልመጣም። የህፃናቶቹንም አንድም ሳታስቀሩ” ብላ ለእህቴ ደወለች። ጠበቃዬን ወዲያው አማከርኩ፡፡ የእለት ስለሆነ ትውሰድ አለኝ፡፡ ከአጎትዋ ጋር ናርዶስ የምትባል የአክስቷ ልጅ መጣች። መኪናው ሞላ ብለው አንዳንድ እቃ አስቀሩ፡፡ ከዛ ይመለሱ ከሆነ ቢሮ አስቀምጪላቸው አልኩዋት፤ ለእህቴ ነገርኩዋት፡፡ ከዚህ በኋላ እኔ ልጆቼን አሳድግበታለሁ ብዬ እንጂ ለእኔማ ምን ይሰራልኛል ብዬ ቤቱን ለቅቄአለሁ፡፡ በፍጹም የሱዋን እቃም አልነካሁም፡፡ ፖሊስ ይዤ ነው እቃውን ያወጣሁት፡፡  ይህን ነገር አታሎኝ መጣ ምናምን ያለችው ይህንን ነው፡፡ የሚገርመው ነገር፣ የእኔ ግማሽ ጭንቅላቴ በህመሙ ምክንያት ታውኳል፡፡ “እኔ አልመጣም” ብላ አታሎኝ ነው የምትለው? በእጅ በእግሬ ገብታ /እባክህ/ ብላ ቤተሰቦቹዋ ጋር ለወሰድኳት! እንዴት እኔ ከፈታኋት ሚስቴ ጋር አቲካራ እገጥማለሁ? እንደለመደችው ታሳስረኝ እንዴ? አንድ ነገር ብናገራት ስልኳ ላይ እኮ የፖሊስ ስልክ አለ፡፡ በአምስት ደቂቃ ውስጥ ነው የምታሳስረኝ፡፡
የሚጥል በሽታ ከመኪና አደጋው ጋር ካጋጠመኝ ወዲህ ጊዜ፤ “ልጄን በፍፁም ቆመህ እንዳትታቀፈው፡፡…ምን እንደ ህጻን ትንተባተብብኛለህ? ... ይህ ያልከው ነገር፣ አስተርጓሚ ይፈልጋል… ወዘተ” ትለኛለች በእናቴ ፊት፣ በእህቴ ፊት፡፡ ቢያንስ ህዝብ ይወቅውልኝ፡፡ ኧረ ብዙ ነው፡፡
ለህክምናህ አራት መቶ ሺህ ዶላር ያስፈልጋል። መባሉና መናገር ያለመቻልህ ጉዳይ እያነጋገረ ነው። ባለቤትህን ጨምሮ ሌሎችም መናገር ይችላል የሚል አስተያየት ይሰጣሉ። ለህክምና የተጠቀሰውን ያህል ገንዘብ እንደሚያስፈልግህና በትትክክል መናገር እንደማትችል የሚያረጋግጥ የሀኪም ማስረጃ አለህ?
በመጀመሪያ ለህዝብ ብለው በመቆርቆራቸው ደስ ይላል፡፡ ነገር ግን ይህን ራሳቸውም ያድርጉት፡፡ እኔ ህዝቤን ያስተማርኩ ሰው ግን እስከ ወዲያኛው ያሳዝናል፡፡ “የኦጋዴን ድመቶ”ን ስፅፍ እንኳ በመጀመሪያ ታስሬ፣ ተገርፌአለሁ፡፡ ለእኔ ከትርፉ ላይ ሰላሳ አምስት ከመቶ ነው የሚደርሰኝ፡፡ ግን ካልፃፍኩት አይኖርም ነበር፡፡ ከእኔ ውጪ ደግሞ ለማንም አልተሰጠምና አይፅፈውም፡፡ ነገር ግን እኔ የረካሁት አሁን በዘመነ አቢይ ነዳጅ ተገኘ ስባል ነው፡፡ በገንዘብ ማንም ኢትዮጵያዊ ደራሲ አይጠቀምም፡፡  ዶ/ር አቢይ እኔን ያስበኛል ብዬ አስባለሁ። ነገር ግን እኔ አንድ ልብ ወለድ ብፅፍ፣ የማንንም እጅ አላይም ነበር፡፡ በአሉ ግርማም አሳክሙኝ ቢል አንድ ቀን አሰብኩ። በእኔ ግምት ማንም አያሳክመውም  እላለሁ፡፡ ጠፋ ጠፋ ሲባል ጊዜ እንጂ ያሁኑን ያህል ዝነኛ እንደማይሆን እጠራጠራለሁ። ለእኔ ድንቁ መፅሐፍ አደፍርስ ነውና፡፡ ምን ማለቴ ነው? … መጋቢት 29/2010 ዓ.ም ሚስቴን አብሬአት የነበርኩት፡፡ ለ3 ወራት አይታመምም ያለው ማነው?... እንኳን እንደዚህ እንድሞት በጋዜጣችሁም በፌስ ቡክም ያለ ስሜ ስም ሰጥታ ህዝቡን ግራ ስታጋባው?... ሌሎች እኔን ለአንድ ቀን እንኳ አይተውኝ አያቁም። ሌሎችም የዘወትር ጠላቶቼ ናቸው። ጠላት አያሳጣን ነው፡፡ ወያኔን ያህል ጠላት ባይኖር ኖሮ፣ እኔ እኮ 13 መፅሀፍ አልፅፍም ነበር፡፡ እንኩዋን ለሁለቱ ብቻ፣ እንኩዋ እስከዛሬ 10 ወር ሞላኝ። አስቸኩዋይ የጭንቅላት ቀዶ ጥገና (Cranioplasy)፣ ለሚጥለኝ በሽታ ጭንቅላት ውስጥ የሚወጣ (Eplepsy)… እንኳ አልሳካልኝ ብሎ ነው፡፡  ግን የማያይዝልሽን (Attach) ሁሉንም እንዲያዩ ብታደርጊልኝ ጥሩ ነበር (የዶክተሮችን የምስክር ወረቀት)፡፡
ሌላው … አራት መቶ ሺህ ዶላር ብሎ የጠየቀኝም የለም። አዲስ አበባ ውስጥ እንኳ ህክምና ይለያያል፡፡ የኮሪያ ሆስፒታል እና የጥቁር አንበሳ እንኳ በገፍ ይለያያል፡፡ ስለዚህ እንዲያውም እስከ አምስት መቶ ሺህ ዶላርም ያለ የህክምና ሆስፒታል አለ። ይህን የኢንተርኔት አገልግሎትን በውል የሚያውቅ ሰው ይመልከተው፡፡ 400ሺ ብር ነው ያለችው? … “እንዲያውም ለሕዝብ ብላ አሳግደዋለች፡፡” ለካ፡፡ እኔ የህዝብ ጠላት ነኝ ለካ። ጥሩ ነው፡፡ ይህ ቀን ያልፍና ወይም ይገድለኝና እንተዛዘባለን፡፡  
ልጆችህን ለመጨረሻ ጊዜ ያየሀቸው መቼ ነው?
መጋቢት 29/2010 ዓ.ም፡፡ ከዚያ በኋላ ልታሳየኝ አልፈለገችም፡፡ ስልኬን አደለም በቃሉዋ…በሰይፉ ሾው ላይ አገር ያወቀው ነው፡፡
አፍሪ ሄልዝ ያመቻቸለትን ህክምና አልተቀበለም የሚል ነገር ተሰምቷል፡፡ በዚህ ላይ ምን ምላሽ አለህ?
አንድ የሚያቋቁሙት ቻናል  አላቸው መሰለኝ፡፡ የእኔ የጤና ጉዳይ አላሳሰባቸውም፡፡  ደግሞ ቃላቸውን አጥፈዋል፡፡ ለቻናላቸው ርካሽ ዝና ፈላጊዎች በመሆናቸው … አሁን ስናየው በእያንዳንዱ ስብሰባ ላይ ቃላቸውን ማጠፋቸው አስደንቆናል። እኔ ልሙት ተውኝ፡፡ አንዳንድ ሰዎች ግን ቃላችሁን አትጠፉ፡፡ ቃል ክቡር ነው፡፡ አምላክ እኮ መፍጠሪያው የነበረ ነው፡፡

 አንድ የቱርኮች ተረት እንዲህ ይላል፡፡ ከዕለታት አንድ ቀን፤ አንድ ዛፍ ጥላ ሥር ተቀምጠው እናትና ልጅ ይወያያሉ፡፡


ልጅ:- እማዬ?
እናት:- ወዬ
ልጅ:- ስንት አባቶች ናቸው ያሉኝ?
እናት:- ሰባት ናቸው
ልጅ:- መቼ መቼ አገባሻቸው?
እናት:-የመጀመሪያውን ሰኞ ለታ
ልጅ:- ሁለተኛውንስ?
እናት:- ማክሰኞ
ልጅ:- ሦስተኛውንስ?
እናት- ዕሮብ ለታ
ልጅ:-አራተኛውንስ?
እናት:-ሐሙስ ለታ
ልጅ:-አምስተኛውንስ?
እናት:-ዓርብ ለታ?
ልጅ:- ስድስተኛውንስ?
እናት:-ቅዳሜ ለታ
ልጅ:- ሰባተኛውንስ?
እናት:- እሑድ ለታ
ልጅ:- እማዬ ትንሽ አልቸኮልሽም?
እናት:- ምን ይደረግ፤ ጊዜው ነው
ልጅ:- የመጀመሪያውን አባቴን ለምን ፈታሽው?
እናት፡- ሁለተኛውን ላገባ
ልጅ፡- ሁለተኛውንስ ለምን ፈታሽው?
እናት፡- ሦስተኛውን ላገባ
ልጅ፡- ሦስተኛውንስ?
እናት- አራተኛውን ላገባ
ልጅ- እሺ አራተኛውንስ?
እናት፡- አምስተኛውን ላገባ
ልጅ- አምስተኛውንስ?
እናት- ስድስተኛውን ላገባ
ልጅ- ስድስተኛውን ለምን ፈታሽው?
እናት- የመጨረሻውን ላገባ
ልጅ፡- አልተጣደፍሺም እማዬ?
እናት- ጊዜው የፈቀደው ነው
ልጅ- ከመጨረሻው ጋር ለምን ቆየሽ/ ታዲያ?
እናት፡- የመጀመሪያውን እስካገኝ
ልጅ፡- ብታገኚው ልታገቢው?
እናት፡- አዎን!
ልጅ፡- ዞረሽ ዞረሽ ያው እዚያው ተመለስሽኮ? ያው ባልሽ አይደለም እንዴ?
እናት፡- አይ ያው አይደለም
እናት፡- እንዴት?
እናት፡- እሱ ያው ባል አይደለም፡፡ እኔም ያቺው ሚስት አይደለሁም
ልጅ፡- እንዴት አስረጂኝ!!
እናት፡- አየህ ልጄ፤ አሁን እሱ ፊት ሆኖ፣ ያለ ሚስት የመኖር ልምድ ያለው ባል ሆኗል፡፡ ተለውጧል፡፡ እኔ ደሞ አሁን ብዙ ባሎች የማግባት ልምድ ያላት ሚስት ሆኛለሁ፡፡ ተለውጫለሁ፡፡ ጊዜ የማይለውጠው ማንም የለም! ዋናው ይሄንን ማሰብና ከስህተት መማርና መገንዘብ መቻል ነው!
*    *    *
ጊዜ የለውጥ መዘውር ነው! ሁኔታዎች አይለወጡም ብሎ መዘናጋት የመጨረሻ የዋህነት ነው፡፡ የሰው ልጅ ጭንቅላት ውስን መሆኑን የምናውቀው፤ አይሆንም ያልነው ሲሆን፣ ይሆናል ያልነው ሲሆን፣ ነው። ሁሉም ነገር የራሱ ዘመን አለው!
“አይመጣምን ትተሸ ይመጣልን ጨምሪበት” የሚለው የአበው አባባል፤ ሁልጊዜ በቀጥታ የምናስበውን ብቻ እንደ መጨረሻ መደምደሚያ አለመውሰድና ትንሽ ቀዳዳ መተው፣ “ያ ባይሆንስ ምን አደርጋለሁ”? ብሎ ለሀሳብ መንሸራሸሪያ ቦታ ማስቀመጥ ተገቢ መሆኑን የሚያፀኸይልን ነው፡፡ በፖለቲካ ህይወታችን ውስጥ በተለይ ጊዜንና ከሱ ጋር የሚመጣውን ለውጥ ማስላት ተገቢ ነው፡፡ ማቀድ የጊዜ ተገዢ ነው፡፡ ማናቸውንም ዕቅድ ዳር ማድረሳችንን ማረጋገጥ ዋናው የመንቀሳቀሻችን አውታር መሆኑን ልብ ማለት አለብን፡፡ ዕቅዳችንን፣ መመሪያችንን፣ መሪ ፍልስፍናችንን ለህዝብ አበክሮ ማሳወቅ፣ ማንቃትና የራሴ ብሎ አምኖ እንዲጨብጠው ማድረግ ወሳኝ ነው፡፡ ቀጥሎ እንግዲህ፤ የጨበጠውን አስተምህሮት እንደምን በተግባር በሥራ ላይ ያውለዋል? የሚያደርገውንስ እነማን ይመሩታል? ያርቁታል? ይመክሩበታል? የሚለውን በቅጡ ማውጠንጠን ይገባል፡፡
ጊዜን ካጤንን፣ ጊዜ ሊያመጣና ላያመጣ የሚችላቸውን እሳቤዎች ከመረመርን፤ መንገዱ አልጋ በአልጋ አለመሆኑን፣ በየደረጃው የየራሱን መስዋዕትነት መጠየቁን፣ እናስተውላለን፡፡ መገንዘብ ያለብን፤ እንቅፋት ሁሌም ይኖራል፡፡ ዋናው ፍሬ ተግባር ግን የመጣውን ክፉ ሁሉ ተጋትሮና ተጋፍጦ ለማለፍ ስነ ልቡናዊም፣ ፖለቲካዊም ማህበራዊም ዝግጁነት ምንጊዜም መኖር እንዳለበት ማሰብ ላይ ነው፡፡ ካፊያ ዝናብ ሲታይ ከመደናገጥ ይልቅ፣ የተዘጋጀሁት ለዶፍ ዝናብ እኮ ነው፤ ብሎ የሚያስብ ልብ ማንገብ ነው፡፡ ትዕግሥትን፣ ጥንካሬንና ኢ-ስሜታዊነትን እንደ ዕለት ፀሎት ማዘውተር ነው፡፡
እስከ ዛሬ በሀገራችን ለውጥን የሚያመጣው የግራ ፅንፉ ወይም የቀኝ ፅንፍ ወገን ነው የሚል ቀኖናዊ ዕምነት ነበር፡፡ በዚሁ እሳቤ ሳቢያ በማህል ያለውን ሰፊ ህብረተሰብ ከጉዳይ አንፅፈውም ነበር፡፡ ሁሌም ወይ ጥቁር ወይ ነጭ ወገን እንጂ፤ የመካከሉን ግራጫ ክፍል “እህ?” ብለን አናደምጠውም ነበር! ከሰፊው የህብረተሰብ ክፍል የሚገኘው ሰፊ አስተሳሰብ፣ እውቀት፣ ምክር፣ ማስገንዘቢያና “እስቲ ረጋ በሉ” የሚል ማሳሰቢያ፣ ነገሬ አንለውም ነበር፡፡ ዛሬ መካከለኛው ሜዳ ላይ የታደመውን ባህር ህዝብ “ምን ታስባለህ?” የምንልበት ሰዓት መጣ!! ይሄ የለውጥ ደወል፣ የደወል ሰዓት ነው፡፡ እኛም ከደራሲው ሄሚንግዌይ ጋር “For whom the bell tolls?” (ደወሉ የተደወለው ለማን ነው?) እንደማለት ማለት አለብን!
አንድ ነገር ግን ልብ እንበል፡- የብዙሃኑን ፍላጎትና ሀሳብ አበጥሮና አንጥሮ፣ መላ መላ የሚያበጅ ንቁ ተግባራዊ ቡድን (Conscious Action Group) መፍጠር ያሻናል፡፡
ይህ ቡድን ፍፁም አድራጊ- ፈጣሪ ሳይሆን አሳቢና አመቻቺ ኃይል፣ ማለት ነው!
አንድን መሪ፤ የአገሬው ሰዎች፤
“የአገራችን የኢትዮጵያ አብዮት (ለውጥ) ቅመሙ የወጣለት ቡና (decaffeinated) ዓይነት ሆኗል የሚባለውን እንዴት ያዩታል?” ብለው ጠየቁት፡፡
መሪውም፤
“እኔ እንኳን የማየው፤ ቅመሙ የወጣለት ቡና አድርጌ ሳይሆን፤ እየበሰለ በመሄድ ላይ ያለ ወይን አድርጌ ነው (a fermenting wine)” ብሎ ነበር፡፡
ይሄ መልካም መርህ ነው፡፡ ምንጊዜም እየመረቀነ፣ እየጣፈጠ፣ እያማረ የሚቀጥል ለውጥ እንጂ አንድ ጊዜ ፈልቶ፣ በአፍታ ፈንድቶ ሁሉን ደረማምሶ፣ ሥር-ነቀል እና “በእነእገሌ መቃብር ላይ ቆመናል!” የሚያሰኝ አሊያም መፈንቅለ- መንግሥታዊ ክሳቴ አያሻም፡፡ አበው፤ “ፈልተህ ከምትገነፍል፣ እያደር ብሰል!” የሚሉት ይሄንኑ ነው፡፡ የጀመርነውን ሰላም ያብስልልን!!

“ልጆቹ ይመጣል እያሉ በየቀኑ በጉጉት ይጠብቁታል” - (ፕ/ር በየነ ጴጥሮስ)

   በኢትዮ ኤርትራ ጦርነት ወቅት በኤርትራ ጦር ከተማረኩ በኋላ አድራሻቸው የጠፋው የኢትዮጵያ አየር ሃይል ባልደረባ ኮሎኔል በዛብህ ጴጥሮስን የማፈላለግ ስራ መንግስት እንዲያከናውን ቤተሠቦችና ኢትዮጵያውያን እየጠየቁ ነው፡፡
ከሠሞኑ በተለያዩ ከተሞች በተካሄዱ የድጋፍ ሠልፎች ላይ ከተንፀባረቁ መልዕክቶች አንዱ፤ “ባለ ከፍተኛ ጀብዱው ኮሎኔል በዛብህ ጴጥሮስን የኤርትራ መንግስት የት እንዳደረሠው መጠየቅ አለበት፤” የሚል ነው፡፡
የኢትዮጵያ እና የኤርትራ የ17 ዓመታት ፍጥጫ አብቅቶ ሰሞኑን ዲፕሎማሲያዊ ግንኙነት መጀመሩን ተከትሎ፣ በኮሎኔሉ የትውልድ አካባቢ ሆሳዕና ላይ ለጠ/ሚኒስትር ዐቢይ አህመድ በተደረገ የድጋፍ ሰልፍ ላይ፤ “የጀግናው ኮሎኔል በዛብህ ጴጥሮስ ይመለስልን ጥያቄ፣ በጠቅላይ ሚኒስትር ዶ/ር ዐቢይ አህመድ ምላሽ ያገኛል!” የሚሉ መፈክሮች በሰልፈኞች ተስተጋብተዋል፡፡
አዲስ አድማስ ያነጋገራቸው የኮሎኔል በዛብህ ጴጥሮስ ታላቅ ወንድም፣ አንጋፋው ፖለቲከኛ ፕ/ር በየነ ጴጥሮስ በሰጡት አስተያት፤ “የህዝቡ ጥያቄ የቤተሠቦቹም ጥያቄ ነው፤ መንግስት የወንድማችንን ጉዳይ በትኩረት እንዲይዘው እንፈልጋለን፤” ብለዋል፡፡
እስካሁን ኮሎኔሉን ለማስመለስ የኢትዮጵያ መንግስት ያደረገው ጥረት እንደሌለ አረጋግጠናል፣ ያሉት ፕ/ር በየነ፤ በግላቸው በተዘዋዋሪ መንገድ ለማፈላለግ ሙከራ አድርገው እንደነበረ ጠቁመው፤ “በዚህ ጉዳይ የኢትዮጵያ መንግስት እንጂ እናንተን አይመለከታችሁም፤” ተብለው ጉዳዩን በእንጥልጥል እንደተዉት ተናግረዋል፡፡
“ከኢትዮጵያ መንግስት ስለ ኮሎኔሉ ጥያቄ አልቀረበልንም፤ ፍቱልንም ሆነ መረጃ ስጡን ያለን የለም፤” ተብዬ ነበር ያሉት ፕ/ር በየነ፤ ቤተሠቦቹ በህይወት መኖሩንና አለመኖሩን እንኳ ማረጋገጫ ማግኘት ተስኗቸው፣ ለስነ ልቦና ቀውስ መዳረጋቸውን ገልፀዋል፡፡
“ልጆቹ በየቀኑ ይመጣል እያሉ በጉጉት ይጠብቁታል፤” ያሉት ፕ/ር በየነ፤ መላ ቤተሰቡም ቁርጥ ያለ መረጃ ባለማግኘቱ፣ በጉጉት ከመጠበቅ ወደ ኋላ አላለም፤ ብለዋል፡፡ በአልጀርሱ ስምምነት መሠረት፤ የምርኮኛ ልውውጥ ይደረጋል ያሉት ፕ/ር በየነ፤ በጦርነቱ ተማርከው የነበሩ ኤርትራውያን ሲለቀቁ፣ የኛ ወገኖች አልተለቀቁም፣ ኮሎኔሉም በዚህ ምክንያት አድራሻው ሳይታወቅ ቀርቷል፤ ብለዋል፡፡
“ህዝቡ የሚያቀርበው ጥያቄ የቤተሰቦቹም ነው፤ ጠቅላይ ሚኒስትር ዶ/ር ዐቢይ አህመድ ጉዳዩን እንደ አንድ አጀንዳ እንዲይዙት እንፈልጋለን፤ ኮ/ል በዛብህ የቤተሰቦቹ ብቻ ሳይሆን የሃገር ጀግና ነው፤” ብለዋል ፕ/ር በየነ፡፡
የኮ/ል በዛብህ ጴጥሮስ ጉዳይ በቅርቡ ምላሽ ያገኛል፤ የሚል እምነት እንዳላቸውም ፕሮፌሰሩ ለአዲስ አድማስ አስታውቀዋል፡፡
ኮሎኔል በዛብህ ጴጥሮስ፤ ከደርግ መንግስት ጀምሮ የኢትዮጵያ አየር ሃይል የተዋጊ ጀት አብራሪ የነበሩ ሲሆን፣ በሶማልያ ወረራና በኢትዮ ኤርትራ ጦርነት ወቅት በፈፀሟቸው ጀብዱዎች ዝናቸው የናኘ መሆኑ ይታወቃል፡፡

- የአገልጋዮችን ሥነ ምግባርና የምእመናንን ጥያቄዎች ይመለከታል
   - የሀገረ ስብከቱ ሥራ አስኪያጅ ተነስተው አዲስ ተመድበዋል

   በኢ/ኦ/ተ/ቤተ ክርስቲያን የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት ካህናትና ሠራተኞች፣ ቅዱስ ፓትርያርኩ፣ በሀገረ ስብከቱ አሠራሮችና የምእመናን አቤቱታዎች ጉዳይ ላይ ሰብስበው እንዲያነጋግሯቸው ጠየቁ፡፡
ካህናቱ ባለፈው ረቡዕ ለፓትርያርኩ በጻፉት ደብዳቤ፣ ቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን በራሷ የውስጥ አስተዳደራዊ ችግር ምክንያት፣ ክብሯና ልዕልናዋ እየተዳከመ፣ ተደማጭነቷና ተጽዕኖ ፈጣሪነቷ እየቀነሰ ነው፤ ብለዋል፡፡
የቤተ ክርስቲያኒቱን የቀደመ ስም ለመመለስና መንፈሳዊ ተልእኮዋን በአግባቡ እንድትወጣ ለማስቻል፣ የአስተዳደር ችግሮቿን መፍታት ወሳኝ መኾኑን የጠቀሱት ካህናቱ፤ በአጠቃላይ በቤተ ክርስቲያኒቱ ወቅታዊ ችግሮች ላይ፣ ከቅዱስ ፓትርያርኩ እና ከቅዱስ ሲኖዶሱ ጋራ መወያየት እንፈልጋለን፤ ብለዋል፡፡
በዋናነትም በአገልጋዮች ሥነ ምግባር፣ በሠራተኞች የሥራ ላይ መብቶች እንዲሁም በሕዝበ ክርስቲያኑ መንፈሳዊና አስተዳደራዊ ጥያቄዎች ላይ መነጋገር እንደሚፈልጉ አመልክተዋል - ካህናቱ፡፡
ቤተ ክርስቲያኒቱ በአገልጋዮች አስከፊ የሥነ ምግባር ብልሽት ምክንያት ክብሯን እያጣች ነው፤ ያሉት ካህናቱ፤ ይህን ችግር ለማረም ጥልቅ ውይይትና በመዋቅራዊ ለውጥ የተደገፉ የለውጥ እርምጃዎችን እንሻለን፤ ብለዋል፡፡
የሀገረ ስብከቱ የዋና ክፍሎች ሐላፊዎች በሙሉ እንዲነሡና የጥቅም መረቦቻቸው ተለይተው በሕግ እንዲፈተሽ የጠየቁት ካህናቱ፤ ከግለሰቦች መነሣት ባሻገር ሥርዓታዊ መፍትሔን መሠረት ባደረገና የቤተ ክርስቲያኒቱን ክብርና ሃይማኖታዊ ተልእኮ በሚመጥን ደረጃ፣ ከዘረኝነትና ጥቅመኝነት የጸዳ ሥር ነቀል የአስተዳደር መዋቅር፣ አደረጃጀትና አሠራር እንደ አዲስ እንዲዘረጋ ጠይቀዋል፡፡
ከ150 ባላነሱ የአድባራት አስተዳዳሪዎች፣ ጸሐፊዎች፣ ካህናትና ልዩ ልዩ ሠራተኞች ፊርማ የተደገፈው ይኸው ጥያቄ፣ ባለፈው ሳምንት ረቡዕ በተካሔደው የቋሚ ሲኖዶስ ሳምንታዊ ስብሰባ ላይ በንባብ እንደተሰማና ሀገረ ስብከቱን በበላይነት በሚመሩት በፓትርያርኩ በኩል ምላሽ እንደሚሰጥበት በቅዱስ ሲኖዶስ ጽ/ቤት ተገልጾልናል፤ ብለዋል - ካህናቱ፡፡
በተደጋጋሚ ከሀገረ ስብከቱ ካህናትና ሠራተኞች፣ አቤቱታ የቀረበባቸውና ከሥራ አስኪያጅነታቸው ባለፈው ሳምንት ዐርብ፣ በፓትርያርኩ የታገዱት የሀገረ ስብከቱ ሥራ አስኪያጅ መ/ር ጎይትኦም ያይኑ ከሓላፊነታቸው ተነሥተው፣ በምትካቸው መ/ር ይቅር ባይ እንዳለ ባለፈው ረቡዕ መመደባቸው ታውቋል፡፡
የሀገረ ስብከቱ ካህናትና ሠራተኞች፣ በመጪው ሰኞ ለአዲሱ ሥራ አስኪያጅ ከሚያደርጉላቸው አቀባበል በኋላ፣ ጽ/ቤቱን ጨምሮ የ7ቱ ክፍላተ ከተማ ቤተ ክህነትንና የአጥቢያ አብያተ ክርስቲያናት አገልጋዮችን ያሳተፈ ተከታታይ ውይይት ይደረጋል ተብሎ ይጠበቃል፡፡