Administrator

Administrator

 • “ርካሽ ዝና ከኔ ትወስዳለች እንጂ ልጆቼን አታሳየኝም”
      • “የልጆቼ እናት ለማኝ ሆና እንቅልፍ የሚወስደው አዕምሮ የለኝም”
      • “እህቴ ለእርሷ እንጂ ለኔ አድልታ አታውቅም”

   ከአዘጋጁ
ለውድ አንባቢያን፡- ባለፈው ሳምንት የታዋቂው ደራሲ ይስማዕከ ወርቁ ባለቤት ፀጋ አንዳርጌ ምህረት ዝግጅት ክፍላችን ድረስ መጥታ “ህዝብ ብሶቴን ይስማ” በማለት፣ ደረሰብኝ ያለችውን በደል መዘገባችን ይታወሳል፡፡ ወደ ማተምያ ቤት ከመሄዳችን በፊት ግን ደራሲ ይስማዕከ ወርቁን አግኝተን ምላሽ ወይም ማብራሪያ እንዲሰጠን ጥረን ነበር፡፡ ያደረግነው ሙከራ ግን ሳይሳካ ቀርቷል፡፡ በዚህ ሳምንት ይስማዕከ ፈቃደኛ ሆኖ፣ ለጥያቄዎቻችን በፅሑፍ ምላሽ ሰጥቷል፡፡ በኢ-ሜይል የላከልንን ከሞላ ጎደል እንዳለ አቅርነበዋል፡፡ ጥንዶቹ ችግሮቻቸውን በመነጋገር ይፈቱታል ብለን ተስፋ እናደርጋለን፡፡
ስለ ባለቤትህና ስላንተ ግንኙነት ባጭሩ ብትነግረኝ?
እኔም በትምህርትና በመፃፍ ነው ሕይወቴን ያሳለፍኩት። ሕይወቴ ከታመምኩ በኋላ ምስቅልቅሉ መውጣቱም ይህን ያሳያል፡፡ ጋብቻችንን የፈፀምነው ከክርስቶስ ልደት በፊት ነው ብትልም በጣም ጥሩ ነው፡፡ በ02/02/2008ዓ.ም-በተራ ቁጥር 031883፣ በክብር መዝገብ ላይ ተመዝግቦ ነው፡፡ የሚገኘው ጋብቻችን፡፡ ከዛም በኋላ አንድ ወንድ ልጅ፣ አንዲት ደግሞ ሴት ልጅ ወለድን፡፡ የጠቀሰችው ዓመተ ምህረት ግን ትክክል አይደለም፡፡ የሚገርመው ለዚህ ጋዜጣ የሰጠችውና ለፍርድ ቤት ያቀረበችው ተመሳሳይ አይደለም፡፡ በተለይም መላ ቤተሰብዋን ምስክር አድርጋ ካቀረበቻቸው ላይ ሁለቱ በጠቀሰችው አመተ ምህረት ይወለዳሉ ወይ ነው ጥያቄው፡፡ የልጆቼ እናት ናትና ምን እላለሁ፡፡
ባለቤትህ ባለፈው ሳምንት በአዲስ አድማስ ላይ ያቀረበችውን ቅሬታ እንዴት ታየዋለህ?
ባለፈው ሳምንት ጋዜጣ ላይ አሜሪካ ለኮሪያ ወይም ለራሺያ የማትሰጠው አቲካራ ሆኖ ባገኘውም የሰጠችው ቃለ ምልልስ፣ ምንም ብንለያይም፣ የልጆቼ እናት ናት፡፡ ምንም ማድረግ አይቻልም፡፡ ልጆቼን የሚጎዳ ነገር እዚህ ላይ መናገር አልፈልግም፡፡ ልጆቼ በእኔ እንዲያፍሩ አላደርግም። ሁሉም ያልፋል፡፡ እኛም ራሱ እናልፋለን፡፡ ግን መጥፎ ታሪክ ሰርተን፣ ወይም የማይጠፋ ቃል ተናግረን ካለፍን፣ የእኛ ሸክም ልጆቻችን ላይ ይከመራል፡፡ እነሱ በማያውቁት ነገር ሲጎዱ ይኖራሉ፡፡ ስለዚህ አቀራረቡ ቢያሳዝነኝም አልፈዋለሁ፡፡ ሌላው ...የተካሰስነው እኔ እና እርሷ ነን፡፡ በእኔ ዙሪያ ማንንም እንድታይ ፈቃደኛ አይደለችም፡፡ ግን የመጨረሻ የማሳስባት ነገር ቢኖር፣ ከኮሚቴው ራስ ላይ ትውረድ፡፡ አንዱ ወይም መላ ኮሚቴው በስም አጥፊ ቢከሳት የለሁበትም፡፡ ሽመልስ አበራ ጆሮ ነው ሚያጭበረብር? ኮሜዲያን ደረጀ ኃይሌ ነው እሚያጭበረብር? መንገሻ ተሰማ ነው እሚያጭበረብር? ፍርያት አትክልት ነው እሚያጭበረብር? መሳይ ወንድሜነህ ነው እሚያጭበረብር?  እስከ ዛሬ ከሰማኋቸው ዜናዎች “አዬ ጉድ” የሚያስብል ወሬ ነው... እራሷ ገንዘብም ቆጥሬ አላውቅም፡፡ አዲስ አበባ ያሉትን ጓደኞቼን ... እስክድን እንኳ አቅቶሽ፣ ያለ ስሜ ስም ሰጥተሽ፣ ለጉዋደኞቼ ተናግረሽ ሲርቁኝ ጥሎኝ ያልሄደውን ፍርያትን “የእርሱ አፈ ጉባኤ” በማለትሽ ፀፀቱ ለራስሽ ነው፡፡  ሰይፉ ፋንታሁንም እስከ ዛሬ ተገናኝተን፤ “ህዝቡን እንዴት መዝረፍ አለብን” በሚለው ላይ ተገናኝተን አውርተን አናውቅም:: በኮሚቴው ላይ ያነሳሽው አሰስ ገሰስ ወሬ ጊዜውን ጠብቆ ትከፍይበታለሽ። ኮሚቴዎቸን በተመለከተ የራሳቸው ዝና ያላቸው ናቸው፡፡ እንኳን እርሷ ልታጎድፋቸው፣ እኔም ብሆን ቀና ብዬ ለማየት የማፍር፣ ከእነርሱ ጋር ብጣላ ከመላው ኢትዮጵያ ህዝብ ጋር እንደምጣላ አውቀዋለሁ፡፡ እነሱ ሲጠይቁኝ ነው መኖሬ የሚሰማኝ፡፡
ኮሚቴው ራሱ “እኛ ገንዘቡ ቢገባ እንተማማለን፣ በአንተ ስም በተከፈተ አካውንት ይግባ” ተብዬ ነው በእኔ ስም የተከፈተው፡፡ ከሰይፉ ሾው በሁዋላም አንዲት ሳንቲም ነክቼ አላውቅም፡፡ ሂዱና በብርሃንና ሰላም ቅርንጫፍ ንግድ ባንክ ተመልከቱ፡፡ የባህር ዳር ልጆች ምስክር ሊሆኑ ይችላሉ፡፡ ገንዘቡን በባንክ አስገቡ ሲልዋቸው፡፡ እኔ ጋ ቼኩ አልደረሰም። ቢጠፋበት አንድ ሰው ብለው፤ ተመንዝሮ ነው የተላከው፡፡ እኔም ለጤናዬ እንጂ ገንዘቡ የሚውለው፣ በፍፁም የኢትዮጵያ ህዝብን አላጭበረብርም፡፡ አንቺ እኮ እኔን ስታጭበረብሪ ነበር፡፡ ሁሉንም ባንቺ ሂሳብ አትለኪ። ፍርድ ቤቱ ባግባቡ ይፍረድና፣ እኔ ጤናዬን እንጂ ሁሉም ነገር ለልጆቼ ይውላል፡፡ እርሱንም በእኔ በአባታቸው ስም ከተጠሩ ብቻ ነው፡፡
ከባለቤትህ ጋር ለፍቺና ለፍርድ ቤት ያበቃችሁ ነገር ምንድን ነው?
ከዛ በፊት ታስሬ ነበር፡፡  ምክንያት በሌለው ምክንያት። በእርስዋ ምክንያት፡፡ ወይ ሐምሌ መጀመሪያ ላይ ወይም ሰኔ መጨረሻ ላይ፡፡ ሐምሌ ላይ ታሰርሽ ማለት ደግሞ ጉዳይሽ ጥቅምት መጨረሻ ላይ ነው የሚታይልሽ፡፡ መንግሥት በምን  ልሰረው እያለ፣ ወስዳ ከተተችኝ ሚስቴ፡፡ ብታሰር አሪፍ ነበር፡፡ ይህን ሁሉ ፈተና አላይም ነበር፡፡ ከባድ የመኪና አደጋ ያስተናገድኩትም ከዛ በኋላ ነው፡፡ ያው በእርሷ ምክንያት ማለት ይቻላል፡፡ ለምን? ሀዋሳ ውስጥ ነኝ ብላ ለእህቴ ተናገረች፡፡ እኔ እዚህ አዲስ አበባ ውስጥ ነበርኩ ማተሚያ ቤት፡፡ ባንክ ቤት ሄድኩና “ወይ ሸጣችሁ ክፈሉ ወይም እኛ ጨረታ ልናወጣው ነው ቤቱን” ተባልኩ። ለባንኮቹ እንኩዋን ቤቱን ራሴንም ቢሸጡኝ ክብር አለኝ፡፡ አከብራቸዋለሁ፡፡ ረቡዕ ነበር፡፡ ወደ ሀዋሳ በዛው ነዳሁት፡፡ እህቴ ቤት አደርኩ፡፡ ሐሙስ በጥዋት ገዢ ፍለጋ ተነሳሁ፡፡ ዘጠኝ ሰዓት ላይ ገዢ አገኘሁ፡፡ ከዛ ወደ ሻሸመኔ ሄድን፡፡ ወደ እህቴ ደወልኩና “በዓይኔ እየሄደብኝ ነው፣ ልጄን አሳይኝ፡፡” እላለሁ እኔ፡፡ “ሀዋሳ ሪፈራል ሆስፒታል ናት ሰው ታሞባት” ትለኛለች እርሷ፡፡ “ትጨርስና አምጥቼ ልጅህን አሳይሃለሁ።” ከዛ ከጆሮዬ ጥልቅ አለ አንድ ነገር፡፡ ሀዋሳ ውስጥ የለችም፡፡ አብረን ለገዢው ብንሸጥለትስ? አዲስ አበባ ናት፡፡ እንዲያውም ለሃያ ሁለት ቀናት አዲስ አበባ ናት፡፡ ከዛ ወደ ይርጋለም እየነዳሁት ነበር፡፡ ያደፈጠ መኪና መጥቶ እስኪጋልበኝ ድረስ፡፡ ከዛ በኋላ ጥቁር አንበሳ ሆስፒታል ነቃሁ፡፡ መናገር አልችል፣ መጻፍም አልችልም ነበር፡፡ ቀስ ቀስ እያልኩ ነው የተለማመድኩት፡፡ እንዲያውም… መቆም አይችልም ብለው ነበር አሉ ሀኪሞች፡፡ ይቅርታ አድርጉልኝና ከሰማይ ከምድር ያህል የሚከብደኝ ቂጤ ነበር፡፡ ሽንት ቤት አንድ ቀን ገባሁና ተቀመጥኩ፡፡ መነሳትም አልችልም፡፡ አልናገርም፡፡ እንዴት እህቴን ልጥራት፣ ብልጎመጎም፣ ብልጎመጎም፡፡ ከብዙ ሰዓት በኋላ እህቴ መጣች፡፡ ከዚሁ ጋር… ወንድሟ ሰው ገጨ ተብሎ ብትሰማ፣ እንባዋ ማባሪያ ጠፋው፡፡ ወንድሟ ታልቅስ፡፡… እንዲያውም በእኔ ጊዜ፣ አዲስ አበባ ሰምታ፣ “ኢየሱስን አመስግኑ” በማለት … አሁን ወደ ኋላ ታሪኬን ሳጠና፣ መላ የሀዋሳ ህዝብ አዝኖ፣ እነሱ ግን አልመጡም … ፀሎት ላይ ነበሩ፡፡ የልጃቸው አባት ነበርኩ፡፡
አዲስ አበባ ውስጥ ከቅርብ ጓደኛዬ ጋር ለ22 ቀናት ነበረች፡፡ እኔና እሱ በቀን በቀን እየተገናኘን ነበር፡፡ ለ22 ቀናት ባለቤቴን እንዳስቀመጠ ግን አልነገረኝም፡፡ አሁን የሚለው ግን “ልጅህ ታሞ” ብላ ደውላልኝ መጣች፣ እርሱ በችግሩ ጊዜ ከእኔ እንደማይወስድ፣ ልጅህን ላሳክምልህ ነው” የሚለኝ፡፡ ሆኖም እንደ እኔ ባጋጣሚ ሳይሆን፣ የሚፈልገውን ላሟላለት ነው ልጄን የወለድኩት፡፡ ደሜ የፈሰሰውም ለእርሱ ነው፡፡ የአራት ሰው ደም ነው የወሰድኩት፡፡ በዛ ላይ ቆንጆ ልጅ ነው፡፡ እንደምወደው እያወቀ፣ ሌሊት ሌሊት በህልሜ ከእርሱ ጋር እንደማድር እያወቀ፣ ባለቤቴን ከቤቱ እንዳስቀመጠ ሳላውቅ…፡፡ እሷ እሱ ቤት ሆና እንድትከሰኝ አመቻችቷል፡፡ እኔ ሳላዉቅ፡፡ እኔ ከጥቁር አንበሳ ሆስፒታል ወጥቼ እያገገምኩ፣ ጠበቃ የሆነ አንድ ጓደኛ ነበረኝ፡፡ “አራዳ ፍርድ ቤት ባለቤትህ ስትመላለስ ነበር” አለኝ፡፡ ቅርብ ስለሆነ ሄድኩ፡፡ ቦርዱ ላይ ሳየዉ ከሳኛለች፡፡ ወደ ላይ ስወጣ፣ “ጥቁር አንበሳ ሆስፒታል ነው ያለው፡፡ እና ጉዳቱ የጭንቅላት ነው ይህን መስጠት የለብሽም፤” … ከብዙ ድራማ በሁዋላ ወደ መዝገብ ቤት ተመለሰ፡፡ “ለምን እኔ አልጠይቃትም” ብዬ ትዳር እኮ ማቆየት እንጂ አደጋው፣ ለማፍረስ ምንም እኮ ችግር የለውም፡፡ ትዳሩ ደበረኝ ብሎ እኮ ማፍረስም ይቻላል። እንኳን ይህ ሁሉ ምክንያት እያለኝ” እኔም በዛው ቀን የፍታህ ብሄር ክስ ይዤላት መጣሁ፡፡ እኔም ስለማልስራ አንቺም ስለማትሰሪ ፍርድ ቤቱ “ይህ ያንቺ፣ ይህ የእኔ” እስኪለን ድረስ አብረን እንኑር፤ ተባብለን አብረን መኖር ጀመርን፡፡ ማድረግ ያልነበረብኝ ነገር ነው … እስከ መጋቢት 29/2010 ድረስ፡፡ ወይ አንሰለጥን፣ ወይም ደግሞ…፡፡
ወደ ፍርድ ቤት ከመሄዳችሁ በፊት ችግራችሁን በሽምግልና ለመፍታት አልሞከራችሁም?
እኔ ከአስራ አምስት  ጊዜ በላይ ሽምግልና ሞክሬአለሁ። እነ ዶክተር እዝራ፣ እነ አየለ እምሩ፣ እነ ብርሃኔ ዘርው፣ እነ ሽመልስ አበራ ጆሮ…፡፡ እኔ እርሷን አልከሰስኳትም፡፡ ክስዋን የሰጠችው ለፖሊስ ነው፡፡ እኔ ታምሜ ምንም አላይም፡፡ ከዛ ወደ መዝገብ ቤት ተመለሰ፡፡ ደግሞ እኮ ይነገራል፡፡ እኔ ሄጄ ባየው ጊዜ በጣም ነው የተናደድኩት፡፡ ደግሞ ወዲያውኑ ነው የወሰንኩት፡፡ ሰው ከጠላቱ ጋር አይኖርም፡፡ እሷም ያሰበችው ይኖራል፡፡ እንዲህ በቀላሉ ትዳር የሚያስፈታ ነገር ምን አለ? እኔን ጨካኝ አድርገው የሳሉ ሰዎች ይኖራሉ፡፡ ምንም የማላውቀው ነገር  ስላለ ነው፡፡ ድርጅት ነበረን፣ እኔ ስተኛ አብሮ ተኛ፡፡ ሠራተኞች ነበሩ፤ እየነቃሁ ስመጣ ግን በሙሉ ተበትነዋል፡፡ ምን አለ አሁን ተቀምጦ ሂሳብ ከመስራት፤ እንደ ባለትዳር የማታስተዳድረው ድርጅቱን?... በጣም አሳዛኝ ነው፡፡ ሽምግልናው ሰልችቶኛል፡፡  ቃል ተጠብቆ፣ ይህን ያሉኝን አላደርግም ብሎ አይሆንም፡፡ ቂም አንድ ቀን እስኪያስተምራት መጠበቅ ነው፡፡
ፍቺ ከጠየቅህ በኋላ ከአንዴም ሁለት ጊዜ ፍርድ ቤት ያልቀረብክበት ምክንያት ምንድን ነው?
ይህን ህጻን ልጅም ይመልሰዋል፡፡ በውክልና፣ እራሴን ሆኖ ሚከራከር ጠበቃ ጉዳዩን ሰጥቻለሁ፡፡ እኔ አልናገርም። ዳኛዋን እንደ እርሷዋ በእንባ ለመብላት ነው እንዴ? ሳልናገር ተቀምጬ፣ ዳኛዋን ትክክለኛ ፍትህ እንዳትሰጥ አላደርጋትም። ለፍትህ መዛባት ሲሉ፣ የማይደረግ ነገር የለም።  ናፈቅኳት እንዴ?... ይህ የምትለውን ስታጣ ግራ ገብቷት ነው፡፡
ሰኔ 26 ለተያዘው ቀጠሮስ ትቀርባለህ?
እንዳልኩሽ ነው፡፡ ግን ጠበቃዬ በህመም ወይም በሌላ ነገር ከቀረ፣ እኔ ሄጄ በፅሁፍ የምጠየቀውን ልመልስ እችላለሁ፡፡ የከበደኝን “ጠበቃዬን ላማክርና እርሱ ይመልስላችኋል” ልል እችላለሁ፡፡ እኔ በፅሁፍ ይመለስ ወይም አይመለስ አላነበብኩም፡፡
በአሁኑ ሰዓት ባለቤትህና ልጆችህ በምን ሁኔታ ላይ እንዳሉ ታውቃለህ?
የእርሷን መኖሪያ አላውቅም፣ ልጆቼን ብታሳየኝም ጥሩ ነበር፡፡ አዲስ አበባ ነች ስላት ሌላ ሀገር ትሄዳለች፡፡ የአንተ ልጆች አይደሉም ነው የምትለኝ፡፡ ርካሽ ዝና ከእኔ ትወስዳለች እንጂ ልጆቼን አታሳየኝም፡፡ ለምሳሌ እስከ 17,000 ብር ይከራይ ነበር ቤቱ፡፡ ባለፈው እዚህ ጋዜጣ ላይ፣ ሰብራ ገባሁበት ያለችው፡፡ የኪራዩ ውልም እኔ ዘንድ አለ፡፡ እኔ ታምሜአለሁ፡፡ ነገርን ከማፋፋም ተቆጥባ፣ ሰብራ ከምትገባ እህቴ ሙሉ ውክልና አላት፡፡ እሷ አከራይታው መኖር አትችልም ነበር?... ወይስ የእኔን ስም ካላጠፋሁት ነው?... ስንቱ የተጣላ እየታረቀ፣ ፍርድ ቤት ንብረት አከፋፍሎ፣ ሰማኒያችንን እስኪቀደው ድረስ ለምን ሰላም ማጣት ያስፈልጋል? … እህቴ ለእርሷ እንጂ ለእኔ አድልታ አታውቅም። ግልፅ ናት፡፡ ሰከን ብላ ማሰብ አለባት፡፡ መካሪዎች ምንም ሊያደርጉላት አይችሉም፡፡ በባለፈው ጋዜጣ ላይ የመካሪ ቃላት ተሞልታ እንደ መጣች ግልፅ ነበር፡፡ ሁሉንም ስድብ ባለቤት ባለቤቱን እያወቅኩት ነበር፣ ይቺ የእገሌ ናት…ወዘተ።  ...አዶኒ ይስማዕከ፣ እና መልእክተ ይስማዕከ ብዬ ለልጆቼ ስም አውጥቼ ነበር፡፡ ሳልጠራችሁ ቀረሁ እንጂ፡፡ እነሱን ግን “ልጆችህም የአንተ አይደሉም” ብላለች፡፡ … አዲስ የእናቶችና የህፃናት ሆስፒታል ሂዱና አረጋግጡ (ከቀበና ገባ ብሎ ነው ያለው)… “Baby Tsega Andarge” የሚል ነው ስሙ፡፡ እኔ አባታቸው ቆሜ ነው ያዋለድኳቸው፡፡ የሚያስፈልገውን ነገር አደርጋለሁ ለልጆቼ፡፡ ልጆቼ ሲታመሙም፣ ትኩሳት ሲኖራቸውም ወስጄ አሳክማለሁ፡፡ እስከ ዛሬም ድረስ ያው በእኔ ስም አይጠሩም፡፡ ወደ ሶስት አመት ሊሆነው ነው፡፡ እኔ ግን አንገቴን ደፍቼ ነበር የማሳክመው፡፡ በጣም ነውሩን የሚያውቁት ብልህ ሴቶች ናቸው፡፡ አባታቸውን በመጠየቅ ሲያድጉ፣ መከራዋን የሚያበሏት እሷን፡፡ በጥቅሉ…  በሌላ ነገር ቢያስጠረጥራትም፣ እኔ ግን ልጆቼን ማንም አይነጥቀኝም፡፡  
የሚላስ የሚቀመስ በሌለበትና ለመኖሪያ በማይመች ቤት ውስጥ እንዳለች ነው የነገረችን …
ሰብራ የገባችበት ቤት ነው? በህግ ያስጠይቃታል፡፡ በቁጥጥር ስር ያዋለችው ሆቴል፣ ያው ከእንጀራ እናቱዋና ከአባቱዋ ቤት አጠገብ ነው፡፡ እኔ እኮ በፍትሀ ብሄር ነው የከሰስኩዋት፡፡ ፍርድ የእርሷ ነው ካለ፣ የእርሱዋ ነው አይደለም; … “እግዚአብሔር ሲያሸነፍህ፣ ራስህን ነው ቀድሞ ስህተት የሚያሰራህ” …የንግድ ቤት ነው፡፡ “መስተዋቱ ያንፀባርቅብኛል፣ መስተዋቱ ረበሸኝ” ብላለች፡፡ ሆቴል ነበረ። እኔ እንኳ ለመኖሪያ ቤት ተመኝቸው አላውቅም፡፡ ከባንክም ባለፈው ዓመት ተበድረንበታል፡፡ እኔ አዲስ አበባ ውስጥ ከከተማ እርቄ ተከራይቼ እኖራለሁ፡፡ እሷ ደግሞ ተከራይቶ ለባንኩ በሚከፈልበት ቤት ውስጥ ትኖራለች፡፡ እስከ 17,000 ብር ድረስ ይከራያል፡፡ የአንተ አይደሉም የምትለኝ ልጆቼ፣ በዚህ ያድጉበት ነበር፡፡ ይህ ሆኖ እያለ፣ ለልጆቼ ክፈል ትላለች፡፡ ብዙ የተከራየ እቃ ያለበት ነው፡፡ ነገ ለሚነሳው ጥያቄ መልሷ ምን ይሆን; ጥበቃውንም አባራዋለች፡፡ “እዛ ግድም አትድረስ ተብያለሁና፣ እኔ ለህይወቴ አደገኛ ነው” ብሎናል፡፡
ዋና መንገድ ላይ ያለ እና ለሆቴል ሲባል ነው የተሰራው እንጂ ለመኖሪያ አይደለም፡፡  መልእክቱ እሱን ለእኔ ስጠኝ እኮ ነው - የባለፈው ጋዜጣ ላይ የወጣው፡፡
1ኛ. እኔ ታምሜ እያለሁ ድርጅቴን ዘጋችው- ወደ ሶስት መቶ ሺህ ብር የቤት ኪራይ እያለበት፡፡
2ኛ. ቤት ሰብራ ገባችበት- የሚከራየውንና ለልጆቼም ለእኔም የሚያኖረንን፡፡
3ኛ.ከዚህ በፊት የወሰደችው 110,000 ብር አለ፡፡ ምስክሮች አሉ፡፡
4ኛ. በኢትዮጵያ ውስጥ የሚገኙትን የባንክ አካውንቴን አሳግዳብኛለች፡፡ ይህ ራሱ በቂ ነው ለእሷ ላለመክፈሌ፡፡ በየትኛውም ባንክ ያለህ፣ ይስማዕከ ብለህ ግባማ አንድ ጊዜ ታግዷል አለህ? ..በቃ፡፡
ይህ ጭራሽ ምቀኝነት፣ ካልሆነ በቀር፣ ባለፀጋዋ ነው በእንባ አባብላ የነገረቻችሁ፡፡ እውነቱ ይውጣና ለልጆቼ እንጂ ለራሴ ምንም አልፈልግም፡፡ እኔ ከዳንኩ ከዜሮ ጀምሬ እጥራለሁ። አብረን ባንኖርም፣ የልጆቼ እናት ለማኝ ሆና እኔ እንቅልፍ የሚወስደው አዕምሮ የለኝም፡፡ ለዚህ ሁሉ ምክንያቱ ራሷ በመክሰሱዋና አብረን ስንት ወራት ስንኖር አለመናገሩዋ ነው፡፡ የቤቱ ጉዳይ ግን እየተከራየ ለባንክ ተከፍሎ ቢሆን ጥሩ ነው፡፡ አለበዚያ ነገ ደግሞ ሊሸጠው እንዳይመጣ፡፡ እኔ ታምሜአለሁ። በአስማት የምሰራ ይመስለዋል ሰው? እሱ “የኦጋዴን ድመቶች” ላይ ብቻ ነው ያለው፡፡ እኔ ደግሞ ደሙን በብድር ነው የወሰድኩት፡፡ የአራት ሰው ደም ተቀብያለሁ ማለቴ ነው፡፡  
መጨረሻ አካባቢ ትኖሩበት ከነበረው ባሻ ወልዴ ችሎት የጋራ መኖሪያ በሌለችበት ቤት ቀይረህ መሰወርህንና የማተሚያ ማሽኖችን ማሸሸህን ተናግራለች፡፡ እውነቱ ምንድን ነው?
በመጀመሪያ ፋሲካ ሲደርስ፣ “አንተ ካልሄድክ ወደ ሀዋሳ እኔ እሄዳለሁ” አለችኝ፡፡ መናገር አልችልም፣ አብረን ሄድን ሀዋሳ። አዲስ አበባ ሳለሁ የሚደውሉልኝን በነጋታው አገኘቻቸው። በሴት እንባዋ አደረቀቻቸው፡፡ (ፈፅሜ ካላዘንኩ እኔ እንባዬ አይመጣም)፡፡ ብዙዎቹ ደነገጡ፡፡ በእኔም ላይ አዘኑ፡፡ የእኔን መልስ ሳይሰሙ ማለት ነው፡፡ አንዳንዶቹ መደወል የጀመሩት አዲስ አድማስ ጋዜጣን ካነበቡ በኋላ ነው፡፡ ለእኔ እኮ እንደዚህ ነበር ያለችኝ፡፡ አሁን እሱን ገልብጣ ጋዜጣ ላይ አወጣቸው፡፡ የስራዋን ይስጣት፡፡ አስገድዶ ወሰደኝ ማለት ምን ማለት ነው; እኔ እኮ ግማሽ ጭንቅላቴ ባዶ ነው፡፡ ጠጠር ቢያገኘኝ እሞታለሁ። ውጪ አገር ቀዶ ጥገና የሚካሄደውም ለእርሱ ነው፡፡ የእኔን በሽታ ለማረጋገጥ ሆስፒታሎቹ ሁሉ ክፍት ናቸው፡፡ ጥቁር አንበሳ ለአይኔ በምኒልክ ሆስፒታል እንዲሰራ ሪፈር ፅፎ ነበር፡፡ የዓይኔ ቀዶ ጥገና ለሚጥለኝ በሽታ የምወስደውን ለሁለት ዓመት በቀን ሶስት ጊዜ፣ ማደንዣውን በመፍራት፣ ሌሎች ይደረጉ በሚል የምኒልክ ሆስፒታል ሌሎች እስኪደረጉ እየጠበቀ ነው፡፡
ሀ) አስቸኩዋይ የጭንቅላት ቀዶ ጥገና (Cranioplasy)
ለ) ለሚጥል በሽታ ጭንቅላት ውስጥ የሚወጣ (Eplepsy)
ሐ) የመናገር ልምምድ (Speech Therapy)
መ) የማገገምያ ህክምና (Rehablitation)
ይህ እውነት ለመሆኑ ጥቁር አንበሳ ሆስፒታል፣ ማንም ሰው ሄዶ ማረጋገጥ ይችላል፡፡ በተጨማሪም ለእኔ ማስረጃ ተሰጥቶኛል፡፡ ሁሉን ነገር ይዤ በተጠየኩት ቦታ ሁሉ እቀርባለሁ። …የጥቁር አንበሳ ሆስፒታልን ማስረጃ ማጣጣል ግን፣ በህግም ያስጠይቃል፡፡
እግዚአብሔር ልቦና ይስጣት፡፡ አንድ ሳምንት ብለምናት ወደ አዲስ አበባ አልሄድም አለች፡፡ እንዲያውም የሚጥል በሽታዬ ተነስቶ ጣለኝ፡፡ ቤታችንም ኪራዩ እየደረሰ ነው ወር በገባ በ16 ነው የቤት ኪራይ የምንከፍለው፡፡ የሦሥት ወር ነው 22,500 ብር ይህን ገንዘብ መክፈል አልችልም፡፡ በዚህ ጭንቀት ላይ እያለሁ፣ “ሀዋሳ ቤተሰቦቿ ጋር ሆና “ልብሴን ላኩልኝ፣ እኔ አልመጣም። የህፃናቶቹንም አንድም ሳታስቀሩ” ብላ ለእህቴ ደወለች። ጠበቃዬን ወዲያው አማከርኩ፡፡ የእለት ስለሆነ ትውሰድ አለኝ፡፡ ከአጎትዋ ጋር ናርዶስ የምትባል የአክስቷ ልጅ መጣች። መኪናው ሞላ ብለው አንዳንድ እቃ አስቀሩ፡፡ ከዛ ይመለሱ ከሆነ ቢሮ አስቀምጪላቸው አልኩዋት፤ ለእህቴ ነገርኩዋት፡፡ ከዚህ በኋላ እኔ ልጆቼን አሳድግበታለሁ ብዬ እንጂ ለእኔማ ምን ይሰራልኛል ብዬ ቤቱን ለቅቄአለሁ፡፡ በፍጹም የሱዋን እቃም አልነካሁም፡፡ ፖሊስ ይዤ ነው እቃውን ያወጣሁት፡፡  ይህን ነገር አታሎኝ መጣ ምናምን ያለችው ይህንን ነው፡፡ የሚገርመው ነገር፣ የእኔ ግማሽ ጭንቅላቴ በህመሙ ምክንያት ታውኳል፡፡ “እኔ አልመጣም” ብላ አታሎኝ ነው የምትለው? በእጅ በእግሬ ገብታ /እባክህ/ ብላ ቤተሰቦቹዋ ጋር ለወሰድኳት! እንዴት እኔ ከፈታኋት ሚስቴ ጋር አቲካራ እገጥማለሁ? እንደለመደችው ታሳስረኝ እንዴ? አንድ ነገር ብናገራት ስልኳ ላይ እኮ የፖሊስ ስልክ አለ፡፡ በአምስት ደቂቃ ውስጥ ነው የምታሳስረኝ፡፡
የሚጥል በሽታ ከመኪና አደጋው ጋር ካጋጠመኝ ወዲህ ጊዜ፤ “ልጄን በፍፁም ቆመህ እንዳትታቀፈው፡፡…ምን እንደ ህጻን ትንተባተብብኛለህ? ... ይህ ያልከው ነገር፣ አስተርጓሚ ይፈልጋል… ወዘተ” ትለኛለች በእናቴ ፊት፣ በእህቴ ፊት፡፡ ቢያንስ ህዝብ ይወቅውልኝ፡፡ ኧረ ብዙ ነው፡፡
ለህክምናህ አራት መቶ ሺህ ዶላር ያስፈልጋል። መባሉና መናገር ያለመቻልህ ጉዳይ እያነጋገረ ነው። ባለቤትህን ጨምሮ ሌሎችም መናገር ይችላል የሚል አስተያየት ይሰጣሉ። ለህክምና የተጠቀሰውን ያህል ገንዘብ እንደሚያስፈልግህና በትትክክል መናገር እንደማትችል የሚያረጋግጥ የሀኪም ማስረጃ አለህ?
በመጀመሪያ ለህዝብ ብለው በመቆርቆራቸው ደስ ይላል፡፡ ነገር ግን ይህን ራሳቸውም ያድርጉት፡፡ እኔ ህዝቤን ያስተማርኩ ሰው ግን እስከ ወዲያኛው ያሳዝናል፡፡ “የኦጋዴን ድመቶ”ን ስፅፍ እንኳ በመጀመሪያ ታስሬ፣ ተገርፌአለሁ፡፡ ለእኔ ከትርፉ ላይ ሰላሳ አምስት ከመቶ ነው የሚደርሰኝ፡፡ ግን ካልፃፍኩት አይኖርም ነበር፡፡ ከእኔ ውጪ ደግሞ ለማንም አልተሰጠምና አይፅፈውም፡፡ ነገር ግን እኔ የረካሁት አሁን በዘመነ አቢይ ነዳጅ ተገኘ ስባል ነው፡፡ በገንዘብ ማንም ኢትዮጵያዊ ደራሲ አይጠቀምም፡፡  ዶ/ር አቢይ እኔን ያስበኛል ብዬ አስባለሁ። ነገር ግን እኔ አንድ ልብ ወለድ ብፅፍ፣ የማንንም እጅ አላይም ነበር፡፡ በአሉ ግርማም አሳክሙኝ ቢል አንድ ቀን አሰብኩ። በእኔ ግምት ማንም አያሳክመውም  እላለሁ፡፡ ጠፋ ጠፋ ሲባል ጊዜ እንጂ ያሁኑን ያህል ዝነኛ እንደማይሆን እጠራጠራለሁ። ለእኔ ድንቁ መፅሐፍ አደፍርስ ነውና፡፡ ምን ማለቴ ነው? … መጋቢት 29/2010 ዓ.ም ሚስቴን አብሬአት የነበርኩት፡፡ ለ3 ወራት አይታመምም ያለው ማነው?... እንኳን እንደዚህ እንድሞት በጋዜጣችሁም በፌስ ቡክም ያለ ስሜ ስም ሰጥታ ህዝቡን ግራ ስታጋባው?... ሌሎች እኔን ለአንድ ቀን እንኳ አይተውኝ አያቁም። ሌሎችም የዘወትር ጠላቶቼ ናቸው። ጠላት አያሳጣን ነው፡፡ ወያኔን ያህል ጠላት ባይኖር ኖሮ፣ እኔ እኮ 13 መፅሀፍ አልፅፍም ነበር፡፡ እንኩዋን ለሁለቱ ብቻ፣ እንኩዋ እስከዛሬ 10 ወር ሞላኝ። አስቸኩዋይ የጭንቅላት ቀዶ ጥገና (Cranioplasy)፣ ለሚጥለኝ በሽታ ጭንቅላት ውስጥ የሚወጣ (Eplepsy)… እንኳ አልሳካልኝ ብሎ ነው፡፡  ግን የማያይዝልሽን (Attach) ሁሉንም እንዲያዩ ብታደርጊልኝ ጥሩ ነበር (የዶክተሮችን የምስክር ወረቀት)፡፡
ሌላው … አራት መቶ ሺህ ዶላር ብሎ የጠየቀኝም የለም። አዲስ አበባ ውስጥ እንኳ ህክምና ይለያያል፡፡ የኮሪያ ሆስፒታል እና የጥቁር አንበሳ እንኳ በገፍ ይለያያል፡፡ ስለዚህ እንዲያውም እስከ አምስት መቶ ሺህ ዶላርም ያለ የህክምና ሆስፒታል አለ። ይህን የኢንተርኔት አገልግሎትን በውል የሚያውቅ ሰው ይመልከተው፡፡ 400ሺ ብር ነው ያለችው? … “እንዲያውም ለሕዝብ ብላ አሳግደዋለች፡፡” ለካ፡፡ እኔ የህዝብ ጠላት ነኝ ለካ። ጥሩ ነው፡፡ ይህ ቀን ያልፍና ወይም ይገድለኝና እንተዛዘባለን፡፡  
ልጆችህን ለመጨረሻ ጊዜ ያየሀቸው መቼ ነው?
መጋቢት 29/2010 ዓ.ም፡፡ ከዚያ በኋላ ልታሳየኝ አልፈለገችም፡፡ ስልኬን አደለም በቃሉዋ…በሰይፉ ሾው ላይ አገር ያወቀው ነው፡፡
አፍሪ ሄልዝ ያመቻቸለትን ህክምና አልተቀበለም የሚል ነገር ተሰምቷል፡፡ በዚህ ላይ ምን ምላሽ አለህ?
አንድ የሚያቋቁሙት ቻናል  አላቸው መሰለኝ፡፡ የእኔ የጤና ጉዳይ አላሳሰባቸውም፡፡  ደግሞ ቃላቸውን አጥፈዋል፡፡ ለቻናላቸው ርካሽ ዝና ፈላጊዎች በመሆናቸው … አሁን ስናየው በእያንዳንዱ ስብሰባ ላይ ቃላቸውን ማጠፋቸው አስደንቆናል። እኔ ልሙት ተውኝ፡፡ አንዳንድ ሰዎች ግን ቃላችሁን አትጠፉ፡፡ ቃል ክቡር ነው፡፡ አምላክ እኮ መፍጠሪያው የነበረ ነው፡፡

 አንድ የቱርኮች ተረት እንዲህ ይላል፡፡ ከዕለታት አንድ ቀን፤ አንድ ዛፍ ጥላ ሥር ተቀምጠው እናትና ልጅ ይወያያሉ፡፡


ልጅ:- እማዬ?
እናት:- ወዬ
ልጅ:- ስንት አባቶች ናቸው ያሉኝ?
እናት:- ሰባት ናቸው
ልጅ:- መቼ መቼ አገባሻቸው?
እናት:-የመጀመሪያውን ሰኞ ለታ
ልጅ:- ሁለተኛውንስ?
እናት:- ማክሰኞ
ልጅ:- ሦስተኛውንስ?
እናት- ዕሮብ ለታ
ልጅ:-አራተኛውንስ?
እናት:-ሐሙስ ለታ
ልጅ:-አምስተኛውንስ?
እናት:-ዓርብ ለታ?
ልጅ:- ስድስተኛውንስ?
እናት:-ቅዳሜ ለታ
ልጅ:- ሰባተኛውንስ?
እናት:- እሑድ ለታ
ልጅ:- እማዬ ትንሽ አልቸኮልሽም?
እናት:- ምን ይደረግ፤ ጊዜው ነው
ልጅ:- የመጀመሪያውን አባቴን ለምን ፈታሽው?
እናት፡- ሁለተኛውን ላገባ
ልጅ፡- ሁለተኛውንስ ለምን ፈታሽው?
እናት፡- ሦስተኛውን ላገባ
ልጅ፡- ሦስተኛውንስ?
እናት- አራተኛውን ላገባ
ልጅ- እሺ አራተኛውንስ?
እናት፡- አምስተኛውን ላገባ
ልጅ- አምስተኛውንስ?
እናት- ስድስተኛውን ላገባ
ልጅ- ስድስተኛውን ለምን ፈታሽው?
እናት- የመጨረሻውን ላገባ
ልጅ፡- አልተጣደፍሺም እማዬ?
እናት- ጊዜው የፈቀደው ነው
ልጅ- ከመጨረሻው ጋር ለምን ቆየሽ/ ታዲያ?
እናት፡- የመጀመሪያውን እስካገኝ
ልጅ፡- ብታገኚው ልታገቢው?
እናት፡- አዎን!
ልጅ፡- ዞረሽ ዞረሽ ያው እዚያው ተመለስሽኮ? ያው ባልሽ አይደለም እንዴ?
እናት፡- አይ ያው አይደለም
እናት፡- እንዴት?
እናት፡- እሱ ያው ባል አይደለም፡፡ እኔም ያቺው ሚስት አይደለሁም
ልጅ፡- እንዴት አስረጂኝ!!
እናት፡- አየህ ልጄ፤ አሁን እሱ ፊት ሆኖ፣ ያለ ሚስት የመኖር ልምድ ያለው ባል ሆኗል፡፡ ተለውጧል፡፡ እኔ ደሞ አሁን ብዙ ባሎች የማግባት ልምድ ያላት ሚስት ሆኛለሁ፡፡ ተለውጫለሁ፡፡ ጊዜ የማይለውጠው ማንም የለም! ዋናው ይሄንን ማሰብና ከስህተት መማርና መገንዘብ መቻል ነው!
*    *    *
ጊዜ የለውጥ መዘውር ነው! ሁኔታዎች አይለወጡም ብሎ መዘናጋት የመጨረሻ የዋህነት ነው፡፡ የሰው ልጅ ጭንቅላት ውስን መሆኑን የምናውቀው፤ አይሆንም ያልነው ሲሆን፣ ይሆናል ያልነው ሲሆን፣ ነው። ሁሉም ነገር የራሱ ዘመን አለው!
“አይመጣምን ትተሸ ይመጣልን ጨምሪበት” የሚለው የአበው አባባል፤ ሁልጊዜ በቀጥታ የምናስበውን ብቻ እንደ መጨረሻ መደምደሚያ አለመውሰድና ትንሽ ቀዳዳ መተው፣ “ያ ባይሆንስ ምን አደርጋለሁ”? ብሎ ለሀሳብ መንሸራሸሪያ ቦታ ማስቀመጥ ተገቢ መሆኑን የሚያፀኸይልን ነው፡፡ በፖለቲካ ህይወታችን ውስጥ በተለይ ጊዜንና ከሱ ጋር የሚመጣውን ለውጥ ማስላት ተገቢ ነው፡፡ ማቀድ የጊዜ ተገዢ ነው፡፡ ማናቸውንም ዕቅድ ዳር ማድረሳችንን ማረጋገጥ ዋናው የመንቀሳቀሻችን አውታር መሆኑን ልብ ማለት አለብን፡፡ ዕቅዳችንን፣ መመሪያችንን፣ መሪ ፍልስፍናችንን ለህዝብ አበክሮ ማሳወቅ፣ ማንቃትና የራሴ ብሎ አምኖ እንዲጨብጠው ማድረግ ወሳኝ ነው፡፡ ቀጥሎ እንግዲህ፤ የጨበጠውን አስተምህሮት እንደምን በተግባር በሥራ ላይ ያውለዋል? የሚያደርገውንስ እነማን ይመሩታል? ያርቁታል? ይመክሩበታል? የሚለውን በቅጡ ማውጠንጠን ይገባል፡፡
ጊዜን ካጤንን፣ ጊዜ ሊያመጣና ላያመጣ የሚችላቸውን እሳቤዎች ከመረመርን፤ መንገዱ አልጋ በአልጋ አለመሆኑን፣ በየደረጃው የየራሱን መስዋዕትነት መጠየቁን፣ እናስተውላለን፡፡ መገንዘብ ያለብን፤ እንቅፋት ሁሌም ይኖራል፡፡ ዋናው ፍሬ ተግባር ግን የመጣውን ክፉ ሁሉ ተጋትሮና ተጋፍጦ ለማለፍ ስነ ልቡናዊም፣ ፖለቲካዊም ማህበራዊም ዝግጁነት ምንጊዜም መኖር እንዳለበት ማሰብ ላይ ነው፡፡ ካፊያ ዝናብ ሲታይ ከመደናገጥ ይልቅ፣ የተዘጋጀሁት ለዶፍ ዝናብ እኮ ነው፤ ብሎ የሚያስብ ልብ ማንገብ ነው፡፡ ትዕግሥትን፣ ጥንካሬንና ኢ-ስሜታዊነትን እንደ ዕለት ፀሎት ማዘውተር ነው፡፡
እስከ ዛሬ በሀገራችን ለውጥን የሚያመጣው የግራ ፅንፉ ወይም የቀኝ ፅንፍ ወገን ነው የሚል ቀኖናዊ ዕምነት ነበር፡፡ በዚሁ እሳቤ ሳቢያ በማህል ያለውን ሰፊ ህብረተሰብ ከጉዳይ አንፅፈውም ነበር፡፡ ሁሌም ወይ ጥቁር ወይ ነጭ ወገን እንጂ፤ የመካከሉን ግራጫ ክፍል “እህ?” ብለን አናደምጠውም ነበር! ከሰፊው የህብረተሰብ ክፍል የሚገኘው ሰፊ አስተሳሰብ፣ እውቀት፣ ምክር፣ ማስገንዘቢያና “እስቲ ረጋ በሉ” የሚል ማሳሰቢያ፣ ነገሬ አንለውም ነበር፡፡ ዛሬ መካከለኛው ሜዳ ላይ የታደመውን ባህር ህዝብ “ምን ታስባለህ?” የምንልበት ሰዓት መጣ!! ይሄ የለውጥ ደወል፣ የደወል ሰዓት ነው፡፡ እኛም ከደራሲው ሄሚንግዌይ ጋር “For whom the bell tolls?” (ደወሉ የተደወለው ለማን ነው?) እንደማለት ማለት አለብን!
አንድ ነገር ግን ልብ እንበል፡- የብዙሃኑን ፍላጎትና ሀሳብ አበጥሮና አንጥሮ፣ መላ መላ የሚያበጅ ንቁ ተግባራዊ ቡድን (Conscious Action Group) መፍጠር ያሻናል፡፡
ይህ ቡድን ፍፁም አድራጊ- ፈጣሪ ሳይሆን አሳቢና አመቻቺ ኃይል፣ ማለት ነው!
አንድን መሪ፤ የአገሬው ሰዎች፤
“የአገራችን የኢትዮጵያ አብዮት (ለውጥ) ቅመሙ የወጣለት ቡና (decaffeinated) ዓይነት ሆኗል የሚባለውን እንዴት ያዩታል?” ብለው ጠየቁት፡፡
መሪውም፤
“እኔ እንኳን የማየው፤ ቅመሙ የወጣለት ቡና አድርጌ ሳይሆን፤ እየበሰለ በመሄድ ላይ ያለ ወይን አድርጌ ነው (a fermenting wine)” ብሎ ነበር፡፡
ይሄ መልካም መርህ ነው፡፡ ምንጊዜም እየመረቀነ፣ እየጣፈጠ፣ እያማረ የሚቀጥል ለውጥ እንጂ አንድ ጊዜ ፈልቶ፣ በአፍታ ፈንድቶ ሁሉን ደረማምሶ፣ ሥር-ነቀል እና “በእነእገሌ መቃብር ላይ ቆመናል!” የሚያሰኝ አሊያም መፈንቅለ- መንግሥታዊ ክሳቴ አያሻም፡፡ አበው፤ “ፈልተህ ከምትገነፍል፣ እያደር ብሰል!” የሚሉት ይሄንኑ ነው፡፡ የጀመርነውን ሰላም ያብስልልን!!

“ልጆቹ ይመጣል እያሉ በየቀኑ በጉጉት ይጠብቁታል” - (ፕ/ር በየነ ጴጥሮስ)

   በኢትዮ ኤርትራ ጦርነት ወቅት በኤርትራ ጦር ከተማረኩ በኋላ አድራሻቸው የጠፋው የኢትዮጵያ አየር ሃይል ባልደረባ ኮሎኔል በዛብህ ጴጥሮስን የማፈላለግ ስራ መንግስት እንዲያከናውን ቤተሠቦችና ኢትዮጵያውያን እየጠየቁ ነው፡፡
ከሠሞኑ በተለያዩ ከተሞች በተካሄዱ የድጋፍ ሠልፎች ላይ ከተንፀባረቁ መልዕክቶች አንዱ፤ “ባለ ከፍተኛ ጀብዱው ኮሎኔል በዛብህ ጴጥሮስን የኤርትራ መንግስት የት እንዳደረሠው መጠየቅ አለበት፤” የሚል ነው፡፡
የኢትዮጵያ እና የኤርትራ የ17 ዓመታት ፍጥጫ አብቅቶ ሰሞኑን ዲፕሎማሲያዊ ግንኙነት መጀመሩን ተከትሎ፣ በኮሎኔሉ የትውልድ አካባቢ ሆሳዕና ላይ ለጠ/ሚኒስትር ዐቢይ አህመድ በተደረገ የድጋፍ ሰልፍ ላይ፤ “የጀግናው ኮሎኔል በዛብህ ጴጥሮስ ይመለስልን ጥያቄ፣ በጠቅላይ ሚኒስትር ዶ/ር ዐቢይ አህመድ ምላሽ ያገኛል!” የሚሉ መፈክሮች በሰልፈኞች ተስተጋብተዋል፡፡
አዲስ አድማስ ያነጋገራቸው የኮሎኔል በዛብህ ጴጥሮስ ታላቅ ወንድም፣ አንጋፋው ፖለቲከኛ ፕ/ር በየነ ጴጥሮስ በሰጡት አስተያት፤ “የህዝቡ ጥያቄ የቤተሠቦቹም ጥያቄ ነው፤ መንግስት የወንድማችንን ጉዳይ በትኩረት እንዲይዘው እንፈልጋለን፤” ብለዋል፡፡
እስካሁን ኮሎኔሉን ለማስመለስ የኢትዮጵያ መንግስት ያደረገው ጥረት እንደሌለ አረጋግጠናል፣ ያሉት ፕ/ር በየነ፤ በግላቸው በተዘዋዋሪ መንገድ ለማፈላለግ ሙከራ አድርገው እንደነበረ ጠቁመው፤ “በዚህ ጉዳይ የኢትዮጵያ መንግስት እንጂ እናንተን አይመለከታችሁም፤” ተብለው ጉዳዩን በእንጥልጥል እንደተዉት ተናግረዋል፡፡
“ከኢትዮጵያ መንግስት ስለ ኮሎኔሉ ጥያቄ አልቀረበልንም፤ ፍቱልንም ሆነ መረጃ ስጡን ያለን የለም፤” ተብዬ ነበር ያሉት ፕ/ር በየነ፤ ቤተሠቦቹ በህይወት መኖሩንና አለመኖሩን እንኳ ማረጋገጫ ማግኘት ተስኗቸው፣ ለስነ ልቦና ቀውስ መዳረጋቸውን ገልፀዋል፡፡
“ልጆቹ በየቀኑ ይመጣል እያሉ በጉጉት ይጠብቁታል፤” ያሉት ፕ/ር በየነ፤ መላ ቤተሰቡም ቁርጥ ያለ መረጃ ባለማግኘቱ፣ በጉጉት ከመጠበቅ ወደ ኋላ አላለም፤ ብለዋል፡፡ በአልጀርሱ ስምምነት መሠረት፤ የምርኮኛ ልውውጥ ይደረጋል ያሉት ፕ/ር በየነ፤ በጦርነቱ ተማርከው የነበሩ ኤርትራውያን ሲለቀቁ፣ የኛ ወገኖች አልተለቀቁም፣ ኮሎኔሉም በዚህ ምክንያት አድራሻው ሳይታወቅ ቀርቷል፤ ብለዋል፡፡
“ህዝቡ የሚያቀርበው ጥያቄ የቤተሰቦቹም ነው፤ ጠቅላይ ሚኒስትር ዶ/ር ዐቢይ አህመድ ጉዳዩን እንደ አንድ አጀንዳ እንዲይዙት እንፈልጋለን፤ ኮ/ል በዛብህ የቤተሰቦቹ ብቻ ሳይሆን የሃገር ጀግና ነው፤” ብለዋል ፕ/ር በየነ፡፡
የኮ/ል በዛብህ ጴጥሮስ ጉዳይ በቅርቡ ምላሽ ያገኛል፤ የሚል እምነት እንዳላቸውም ፕሮፌሰሩ ለአዲስ አድማስ አስታውቀዋል፡፡
ኮሎኔል በዛብህ ጴጥሮስ፤ ከደርግ መንግስት ጀምሮ የኢትዮጵያ አየር ሃይል የተዋጊ ጀት አብራሪ የነበሩ ሲሆን፣ በሶማልያ ወረራና በኢትዮ ኤርትራ ጦርነት ወቅት በፈፀሟቸው ጀብዱዎች ዝናቸው የናኘ መሆኑ ይታወቃል፡፡

- የአገልጋዮችን ሥነ ምግባርና የምእመናንን ጥያቄዎች ይመለከታል
   - የሀገረ ስብከቱ ሥራ አስኪያጅ ተነስተው አዲስ ተመድበዋል

   በኢ/ኦ/ተ/ቤተ ክርስቲያን የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት ካህናትና ሠራተኞች፣ ቅዱስ ፓትርያርኩ፣ በሀገረ ስብከቱ አሠራሮችና የምእመናን አቤቱታዎች ጉዳይ ላይ ሰብስበው እንዲያነጋግሯቸው ጠየቁ፡፡
ካህናቱ ባለፈው ረቡዕ ለፓትርያርኩ በጻፉት ደብዳቤ፣ ቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን በራሷ የውስጥ አስተዳደራዊ ችግር ምክንያት፣ ክብሯና ልዕልናዋ እየተዳከመ፣ ተደማጭነቷና ተጽዕኖ ፈጣሪነቷ እየቀነሰ ነው፤ ብለዋል፡፡
የቤተ ክርስቲያኒቱን የቀደመ ስም ለመመለስና መንፈሳዊ ተልእኮዋን በአግባቡ እንድትወጣ ለማስቻል፣ የአስተዳደር ችግሮቿን መፍታት ወሳኝ መኾኑን የጠቀሱት ካህናቱ፤ በአጠቃላይ በቤተ ክርስቲያኒቱ ወቅታዊ ችግሮች ላይ፣ ከቅዱስ ፓትርያርኩ እና ከቅዱስ ሲኖዶሱ ጋራ መወያየት እንፈልጋለን፤ ብለዋል፡፡
በዋናነትም በአገልጋዮች ሥነ ምግባር፣ በሠራተኞች የሥራ ላይ መብቶች እንዲሁም በሕዝበ ክርስቲያኑ መንፈሳዊና አስተዳደራዊ ጥያቄዎች ላይ መነጋገር እንደሚፈልጉ አመልክተዋል - ካህናቱ፡፡
ቤተ ክርስቲያኒቱ በአገልጋዮች አስከፊ የሥነ ምግባር ብልሽት ምክንያት ክብሯን እያጣች ነው፤ ያሉት ካህናቱ፤ ይህን ችግር ለማረም ጥልቅ ውይይትና በመዋቅራዊ ለውጥ የተደገፉ የለውጥ እርምጃዎችን እንሻለን፤ ብለዋል፡፡
የሀገረ ስብከቱ የዋና ክፍሎች ሐላፊዎች በሙሉ እንዲነሡና የጥቅም መረቦቻቸው ተለይተው በሕግ እንዲፈተሽ የጠየቁት ካህናቱ፤ ከግለሰቦች መነሣት ባሻገር ሥርዓታዊ መፍትሔን መሠረት ባደረገና የቤተ ክርስቲያኒቱን ክብርና ሃይማኖታዊ ተልእኮ በሚመጥን ደረጃ፣ ከዘረኝነትና ጥቅመኝነት የጸዳ ሥር ነቀል የአስተዳደር መዋቅር፣ አደረጃጀትና አሠራር እንደ አዲስ እንዲዘረጋ ጠይቀዋል፡፡
ከ150 ባላነሱ የአድባራት አስተዳዳሪዎች፣ ጸሐፊዎች፣ ካህናትና ልዩ ልዩ ሠራተኞች ፊርማ የተደገፈው ይኸው ጥያቄ፣ ባለፈው ሳምንት ረቡዕ በተካሔደው የቋሚ ሲኖዶስ ሳምንታዊ ስብሰባ ላይ በንባብ እንደተሰማና ሀገረ ስብከቱን በበላይነት በሚመሩት በፓትርያርኩ በኩል ምላሽ እንደሚሰጥበት በቅዱስ ሲኖዶስ ጽ/ቤት ተገልጾልናል፤ ብለዋል - ካህናቱ፡፡
በተደጋጋሚ ከሀገረ ስብከቱ ካህናትና ሠራተኞች፣ አቤቱታ የቀረበባቸውና ከሥራ አስኪያጅነታቸው ባለፈው ሳምንት ዐርብ፣ በፓትርያርኩ የታገዱት የሀገረ ስብከቱ ሥራ አስኪያጅ መ/ር ጎይትኦም ያይኑ ከሓላፊነታቸው ተነሥተው፣ በምትካቸው መ/ር ይቅር ባይ እንዳለ ባለፈው ረቡዕ መመደባቸው ታውቋል፡፡
የሀገረ ስብከቱ ካህናትና ሠራተኞች፣ በመጪው ሰኞ ለአዲሱ ሥራ አስኪያጅ ከሚያደርጉላቸው አቀባበል በኋላ፣ ጽ/ቤቱን ጨምሮ የ7ቱ ክፍላተ ከተማ ቤተ ክህነትንና የአጥቢያ አብያተ ክርስቲያናት አገልጋዮችን ያሳተፈ ተከታታይ ውይይት ይደረጋል ተብሎ ይጠበቃል፡፡

 በሰምና ወርቅ ሚዲያና ኢንተርቴይንመንት በየወሩ የሚካሄደው “ሰምና ወርቅ የኪነ ጥበብ ምሽት” የፊታችን ሐሙስ ከቀኑ 11፡00 ጀምሮ ፓኖራማ ሆቴል አጠገብ በሚገኘው ቫምዳስ የመዝናኛ ማዕከል ይካሄዳል፡፡
በዚህ ምሽት ላይ ሙአዘ ጥበባት ዳንኤል ክብረት፣ የጠብታ አምቡላንስ ባለቤት አቶ ክብረት አበበ፣ አርቲስቶቹ ተስፋዬ ማሞ፣ ሀረገወይን አሰፋ፣ ፍቃዱ ከበደ፣ አዜብ ወርቁ፣ ገጣሚ መቅደስ ጀምበሩ፣ መምህርት ዕፀገነት አበበ፣ ገጣሚዎቹ ብሩክ ሚፍታህ፣ ምኒልክ ብርሃኑና ሌሎችም በመሶብ ባህላዊ ባንድ ታጅበው ሥራዎቻቸውን እንደሚያቀርቡ የፕሮግራሙ አዘጋጅ ጋዜጠኛ ጌታቸው ዓለሙ ገልጿል፡፡

 በኢቢኤስ ቴሌቪዥን “ቴክ ቶክ” በተሰኘው ሾው አስገራሚ የቴክኖሎጂ ውጤቶችን በማስተዋወቅና በመተንተን የሚታወቀው የሰለሞን ካሳ “ግርምተ ሳይቴክ” መፅሐፍ ከትንት በስቲያ ከምሽቱ 12፡00 ጀምሮ በሸራተን ሆቴል ላሊበላ አዳራሽ ተመረቀ፡፡
መፅሐፉ ለኢትዮጵያውን እንዲያገለግል በአማርኛ የተፃፈ ሲሆን፤ የምረቃው ሥነ ስርዓት በሳይንስና ቴክኖሎጂ ሚኒስቴር የተዘጋጀውን የአይሲቲ ኤክስፖ ኢትዮጵያ 2010 የአይሲቲ ሳምንት ምክንያት በማድረግ የተዘጋጀ እንደሆነና በምረቃ ሥነ ስርዓቱ ላይ የሚኒስትሩ የስራ ኃላፊዎች፣ በዘርፉ የተሰማሩ ባለሙያዎችና ተጋባዥ እንግዶች እንደተገኙም ታውቋል፡፡ 


ባለፈው ቅዳሜ ሰኔ 16 ቀን 2010 ዓ.ም ወደ ጠ/ሚኒስትርነት ሥልጣን ከመጡ ሦስት ወራት ያስቆጠሩትን ዶ/ር
ዐቢይ አህመድን ለመደገፍ በተዘጋጀው ሰላማዊ ሰልፍ ላይ የደረሰውን የቦንብ ጥቃት ለማጣራት፣ አሜሪካ፣ የኤፍቢአይ
ባለሙያዎችን ወደ አዲስ አበባ እንደምትልክ አስታወቀች፡፡
ከቦንብ ጥቃቱ ጋር በተያያዘ ከ30 በላይ ተጠርጣሪዎች በፖሊስ ቁጥጥር ሥር መዋላቸው የተገለጸ ሲሆን እነዚህ
ተጠርጣሪዎች በነገው ዕለት ፍርድ ቤት ይቀርባሉ ተብሏል፡፡
አንድ የአሜሪካ ከፍተኛ ባለሥልጣን እንዳረጋገጡት፤ የአሜሪካ የፌደራል ምርመራ ቢሮ (ኤፍቢአይ) ባለሙያዎች
በአዲስ አበባ የደረሰውን የቦንብ ጥቃት ይመረምራሉ፡፡
በዕለቱ ከደረሰው የቦንብ ጥቃት ጋር በተያያዘ፣ የአዲስ አበባ ፖሊስ ኮሚሽን ምክትል ኮሚሽነር ግርማ ካሣ
እንዲሁም የአዲስ አበባ የብሔራዊ መረጃና ደህንነት አስተባባሪ አቶ ተጋሩ ጎሃድባ ጨምሮ፣ ከ30 በላይ
ተጠርጣሪዎች በፖሊስ ቁጥጥር ሥር ሆነው፣ ምርመራ እየተካሄደባቸው መሆኑ ታውቋል፡፡
ባለፈው ቅዳሜ በመስቀል አደባባይ ጠ/ሚኒስትሩ ከተቀመጡበት መድረክ በግምት በ40 ሜትር ርቀት ላይ በፈነዳው
ቦንብ 165 ሰዎች ላይ ጉዳት የደረሰ ሲሆን ሁለቱ በህክምና ላይ እያሉ ህይወታቸው አልፏል፡፡ 15 ያህሉ
ለከፍተኛ ጉዳት መዳረጋቸው የታወቀ ሲሆን ለአካል ጉዳት ከተዳረጉት መካከል በዲላ ዩኒቨርሲቲ ስፔሻላይዝድ
ሆስፒታል ሃኪም የሆኑት ዶ/ር መኮንን ብርሃኑ በአደጋው አንድ እግራቸውን ማጣታቸውን ምንጮች ጠቁመዋል፡፡
አብዛኞቹ ተጎጂዎች እግራቸው፣ እጃቸውና ጭንቅላታቸው አካባቢ መጎዳታቸውን የህክምና ባለሙያዎች የገለጹ ሲሆን 3
ሰዎች እግራቸው መቆረጡም ታውቋል፡፡
ከዚሁ ጋር በተያያዘ ጠ/ሚኒስትሩ በቦንብ ጥቃቱ ህይወታቸው ያለፈውን ሁለት ወጣት ቤተሰቦች በስልክ
አጽናንተዋል፡፡ በጥቃቱ ህይወታቸውን ያጡት የወላይታ ሶዶ ተወላጁ፣ የ28 ዓመቱ  ወጣት ዮሴፍ አያሌው እና
የምዕራብ ወለጋ ጊምቢ ተወላጁ፣ የ25 ዓመቱ ጉሳ ጋዲሳ መሆናቸው ታውቋል፡፡
የአዲስ አድማስ ዝግጅት ክፍል፤ በቦንብ ጥቃቱ ለደረሰው ሞትና የአካል ጉዳት የተሰማውን ጥልቅ ሃዘን
እየገለጸ፣ለተጎጂ ቤተሰቦችና ለመላው የኢትዮጵያ ህዝብ መጽናናትን ይመኛል፡፡

 የሙዚቃ መምህርና ሃያሲ ሰርፀ ፍሬ ስብሃት፣ ከሰኔ 7 ቀን 2010 ዓ.ም ጀምሮ የኢትዮጵያ ቱሪዝም ድርጅት ም/ዋና ዳይሬክተር ሆኖ እንዲያገለግል፣ በጠ/ሚኒስትር ዶ/ር አብይ አህመድ ተመርጦ ተሹሟል፡፡ አሁን ለተሾመበት ቦታ ሲመረጥ ምን ተሰማው? በቱሪዝም ድርጅት ምን ሊሰራ አቅዶ ይሆን? በሚሉትና በተያያዥ ጉዳዮች ዙሪያ፣ከአዲስ አድማስ ጋዜጠኛ ናፍቆት ዮሴፍ ጋር ተከታዩን አጭር ቆይታ አድርጓል፡፡

   እስቲ ስለ አዲሱ ሹመት የተሰማህን ንገረኝ …
እኔ እንግዲህ እስካሁን በኪነ ጥበቡ ውስጥ የመጣሁበትና የታወቅኩበት መንገድ አለ፡፡ አሁን ደግሞ ድንገተኛም ቢሆን፣ ከአገሪቱ አጠቃላይ የለውጥ መንፈስ ጋር አብሮ በሚታይ መልኩ፣ የሙያና የእውቀት ሰዎችን ወደ አመራር ማምጣት የታመነበት ይመስለኛል። እኔም በዚህ ውስጥ በመታሰቤና በመመረጤ እጅግ በጣም ነው ደስ ያለኝ፡፡ አሁን የተሾምኩበት የኢትዮጵያ ቱሪዝም ድርጅት፣ከአምስት ዓመታት በፊት፣ በቱሪዝም ዘርፍ ይታይ የነበሩ ችግሮች በትልቅ አቅም የተቋቋመ ድርጅት ነው፡፡ ትልቅ ስራ እንዲሰራ በትልቅ ፍላጎትም ጭምር ነው የተቋቋመው። ቱሪዝም ደግሞ ጥበቡን፣ ባህሉን፣ የተፈጥሮ ሃብቱን----እነዚህን ሁሉ ለዓለም አቀፍ እውቂያ የሚያበቃ ትልቅ የኢኮኖሚ ዘርፍ ነው፡፡ ይህ እንግዲህ ሁሉን በአንድ የሚያስተሳስር ነው፡፡ ጥበቡን ብንሰራ ስልጣኔውን ብንሰራ፣ ሌላውንም ብናቀናጅ፣ ሁሉም እይታ ይፈልጋል፡፡ መታየት ብቻ ሳይሆን ኢኮኖሚው ውስጥም ቀጥታ ጣልቃ ገብቶ ሚና መጫወት አለበት፡፡
ስለዚህ የተሾምክበት ቦታ ከፍተኛ ኃላፊነትና ትጋት የሚጠበቅበት ይመስለኛል…
እጅግ በጣም ከፍተኛ ኃላፊነት ነው፤በአገር ቁምነገር ደረጃ ትልቅ ኃላፊነት ላይ እንድሰራ ነው የተመረጥኩት።
ሹመቱ ከጠቅላይ ሚኒስትሩ ፅ/ቤት የመጣ ይመስለኛል?
ትክክል ነው፡፡ ደብዳቤው የኢትዮጵያ ፌደራላዊ ዴሞክራሲያዊ ሪፐብሊክ፣ የጠቅላይ ሚኒስትር ጽ/ቤት፣ በሚኒስትሮች ምክር ቤት ደንብ ቁጥር 294/2005 አንቀፅ 11 ንዑስ አንቀፅ ሁለት መሰረት፤ ከሰኔ 7 ቀን 2010 ዓ.ም ጀምሮ፣ የኢትዮጵያ ቱሪዝም ድርጅት ዋና ዳይሬክተር ሆነው እንዲያገለግሉ የተሾሙ መሆኑን አስታውቃለሁ የሚልና በጠቅላይ ሚኒስትሩ ሥምና ፊርማ የወጣ የሹመት ደብዳቤ ነው የደረሰኝ፡፡
ሹመቱ አንተም እንዳልከው ድንገተኛ ቢሆንም በባህል ዘርፎች አንዱና ዋነኛው በሆነው በሙዚቃ ውስጥ ስትሰራ ቆይተሃል፤ አሁንስ ምን ለመስራት አቀድክ?
እንግዲህ በቀጥታም ባይሆን የሙዚቀኞች ማህበርን ስመራ በነበረበት ጊዜ፣ ቀጥታ እንገናኝ የነበረው ከባህልና ቱሪዝም ሚኒስቴር ጋር ነበር፡፡ ቀጥታ ተጠሪነቱም ለእኛ ባህልና ቱሪዝም ሚኒስቴር ነበር፡፡ በዛን ጊዜ ያሉትን ነገሮች በማወቅ፣ እንደው እነዚህ ነገሮች እንዲህ ቢሆኑ እንዲህ ቢደረጉ እያልኩ ሳውጠነጥናቸው የነበሩ ነገሮች ነበሩ፡፡
እስኪ ምን አይነት ሃሳቦች ነበሩ?
ለምሳሌ በስትራክቸር ደረጃ፤ ባህሉን፣ስነ ጥበቡንና ቱሪዝሙን የነጠለ፣ትልቅ መዋቅር ያስፈልጋል። እያንዳንዳቸው በተናጠል ሰዎች እንዲረዷቸው እንዲደረጉና ተቋማዊ ጥንካሬ ኖሯቸው፣ ነገር ግን በጎንዮሽ ግንኙነት ኖሯቸው፣ ተናብበው እንዲሰሩ ቢደረግ፣ የሚል ትልቅ ምኞትና ፍላጎት ነበረኝ፡፡ በዚህ ምክንያት መነጣጠላቸው፣ከዚህ ቀደም ለአንዱ ትኩረት ሲሰጥ፣ ለአንዱ ትኩረት ሲዳከም ሌላውም እንደዚህ አትኩሮት ሲነፍገው ሁሌ የምናስተውለው ችግር ነበር፡፡ አሁን ግን እነዚያ አዕምሮዬ ላይ የነበሩትን ሀሳቦች ተግባራዊ ለማድረግ፣ በቢሮ ውስጥ በሌሎች ኤክስፐርቶች የነበሩ፣ በደንብ ተጠንተው፣ አዲስ የሆነና ጥበቡን ያካተተ ትልቅ እይታና አሰራር መፍጠር ይቻላል፡፡
ልማታዊውንም ሆነ ፕሮሞሽናል ጎኑን፣ ሁለቱንም በጥሩ ሁኔታ ማስኬድ የሚቻልበት መንገድ አለ የሚለው እምነት፣ በውስጤ ስላደረ፣ እሱን እያጠናሁና እየተዘጋጀሁ ነው ያለሁት፡፡ ከቆዩ ልምዶችም ብዙ የምማራቸው ነገሮች ይኖራሉ፡፡ ከዚህ ቀደም ታዋቂ የሆኑና እድሜ ልካቸውን ቱሪዝም ላይ የሰሩ ባለሙያዎች ያሉበት ቤት እንደመሆኑ፣ እነሱ  ያጋጠሟቸው ችግሮች፣ እሱን ለመፍታት ያጠኗቸው ጥናቶች እውን የሚሆኑበትን ትልቅ መስመር መፍጠርና ያንን ምቹ ሁኔታ ለእነሱ ማመቻቸትና ይሄም ያለ ምንም ገደብ እስከ ላይ መዋቅር ድረስ አሰራሩ ምቹ የሚሆንበትን መንገድ ለማመቻቸት ዝግጁ ነኝ፡፡ እንግዲህ እስኪ እንሄድበታለን፡፡
ባለፈው ሳምንት ጠቅላይ ሚኒስትሩ፤ ለብሔራዊ ቴአትር፣ ረ/ፕሮፌሰር ነብዩ ባዬን፣ ለብሔራዊ ባህል ማዕከል አቶ ተስፋዬ ሽመልስን መሾማቸው ይታወሳል። ከነዚህ ተቋማት ጋርም ሆነ ከተሾሙት ዳይሬክተሮች ጋር ቀጥታ ግንኙነት ያለው ቦታ ላይ እንደ መሾምህ ወደፊት በትብብር ምን ለመስራት እያሰብክ ነው?
እንግዲህ ለእነዚህ ተቋማት ትክክለኛ ባለሞያዎች የመሾማቸውን ጥቅም ልንገርሽ፡፡ እስከ ዛሬ ድረስ በቱሪዝም ዘርፍ ሲታዩ የነበሩት የተፈጥሮ ሀብቶች፣ የቀደምት ስልጣኔ ውጤት የሆኑ ቅርሶችና ቁሳቁሶች ብቻ ነበሩ፡፡ አሁን ግን የክዋኔ ጥበቦች (ፐርፎርሚንግ አርትስ) የምንላቸው የቱሪዝሙ አካል ናቸው፡፡ የፈጠራ ስራዎችና ከተማ ውስጥ የሚካሄዱ ትልልቅ ሁነቶችን ሁሉ ሳያዩ፣ ቱሪስቶች ቀጥታ ወደ አክሱም ላሊበላ ነው የሚሄዱት፡፡ እነዚህን ሁነቶችና የክዋኔ ጥበቦች፣ ከቱሪስቱ ጋር የኢኮኖሚ ቀጥታ ግንኙነት ከፈጠርንላቸው፣ ጥበቦች የኢኮኖሚ ምንጭ ይሆናሉ። ከዚያም በላይ በጣም አድገው የመስራትና በጣም ውድና የተከበሩ የመሆን እድላቸው ይሰፋል። ጥበበኛውም ያድጋል፡፡ ጥበቡንና ከተማዋን ሁሉ ለእይታና ለጉብኝት የተመቻቸ ቦታ የማድረግ አጋጣሚው ይፈጠራል፡፡
እነዚህ እውን ሲሆኑ የቱሪስቱን የቆይታ ጊዜም የሚያራዝሙት ይመስለኛል …
ትክክል ነሽ! ቱሪስቶች ለምሳሌ ሂልተን ያርፉና በጠዋት ተነስተው፣ በአውሮፕላን ወደ አክሱምና ወደ ላሊበላ ነው የሚሄዱት፡፡ እዚህ እንዲቆዩ የሚያደርግ ነገር ስላልፈጠርንላቸው አይቆዩም፡፡ ነገር ግን ቀደም ብዬ እንደነገርኩሽ፣ እነዚህን ጥበቦች በደንብ ከሰራንባቸው ይቆያሉ፡፡ አርቶቹ የሚሰሩባቸው ቦታዎች፣ አርቲስቶቹም በየጊዜው ስራ ይኖራቸዋል። ጥበበኞችም አገርም የኢኮኖሚ  ተጠቃሚ ይሆናሉ። ይህንን ሁሌም ከብሔራዊ ቴአትርና ከብሔራዊ የባህል ማዕከል ጋር በማገናኘት ጥሩ ስራ ይሰራል የሚል እምነት አለኝ፡፡ ለዚህ ደግሞ ከፍተኛ የቱሪስት ፍሰትን መፍጠር አለብን፡፡ ለዚህ ደግሞ ሶስቱ ተቋማት በቅንጅት ትልቅ ሥራ መስራት ይችላሉ የሚል እምነት አለኝ፡፡
ከጠቅላይ ሚኒስትር ዶ/ር አብይ ጋር ከዚህ ቀደም ተገናኝታችሁ ታውቃላችሁ?
ዶ/ር አብይ የሳይንስና ቴክኖሎጂ ሚኒስትር በነበሩበት ወቅት በቅጅ መብት ምክንያት ቀጥታ ጉዳያችን ከሚኒስቴሩ ጋር ይገናኝ ስለነበር፣ እዛ ተገናኝተን እናውቃለን፤ ነገር ግን ያ የተገናኘንበት አጋጣሚ የእኔን ብቸኛ ሚና የሚያሳይ አልነበረም፡፡ በወቅቱ ከተለያዩ የኪነ ጥበብ የሙያ ማህበራት አባላት ጋር ነበር የሄድነው፡፡ እነ ድምፃዊ ፀጋዬ እሸቱ ነበሩ፡፡ የኦዲዮ ቪዥዋል አሳታሚዎች ማህበር ሰዎችም ነበሩ፡፡ ሌሎችም አብረውን ነበሩ፡፡ ከዛ ውጭ በተለየ አጋጣሚ የተገናኘንበት ጊዜ የለም፡፡
ጠቅላይ ሚኒስትሩ በየዘርፉ ለቦታው ይመጥናሉ ያሉ የዕውቀት ሰዎችን እየሾሙ ነው፡፡ ይሄን እንዴት ታየዋለህ?
ትክክል ነው! እኔን ለምሳሌ ከሁለትና ከሶስት ዓመት በፊት ሹመት ቢሰጥህ ትቀበል ነበር ወይ ብትይኝ፣ በፍፁም አልቀበልም፡፡ አሁን የተቀበልኩት የአጠቃላይ የአገሪቱን የለውጥ መንፈስ በማየት ነው፡፡ ከዛ በፊት ያለውን ወንበሩን ምን አይነት እንደሆነ አውቀዋለሁ፤ አሰራርና አካሄዱንም በደንብ ስለማውቀው አልቀበልም ነበር፡፡ አሁን የተሰጠኝን ኃላፊነት ለመወጣት እጥራለሁ። የለውጡ አካል በመሆኔ በጣም ደስ ብሎኛል፡፡

 ከዕለታት አንድ ቀን፣ ኢትዮ-ኤርትሪያ ጦርነት ሊጀመር ሰሞን፤ አንድ ክስተት ላይ ተመርኩዞ በዚህ ጋዜጣ፣ ተረት መሰል ትርክት አቅርበን ነበር፡፡ አንዳንድ ዕውነት እጅግ ሲቆይ ተረት ይመስላል፡፡ ዕውነትና ተረት አንዳንዴ በጣም ከመቀራረባቸው የተነሳ አንዱ አንዱን ተክቶ የሁኔታዎች መግለጫ፣ አሊያም የሂደቶች አንዳች መተንተኛ ይሆናል፡፡ እንግዲህ ያኔ የሚከተለውን ፅፈን ነበር፡፡
እነሆ ዛሬ፤
“ጊዜ በጊዜ ቀለበት
ሰተት …” ሆነና ደግመን እናየው ዘንድ ወቅቱን ጠብቆ ፋይዳው ፍንትው አለ፡፡
ከዕለታት አንድ ቀን በትግራይ ክልል ለስራ ጉዳይ ሄደን ሳለን፤ ዋና ዋና ጉዳያችንን ፈፃፅመን ስናበቃ፤ ወደ ማታ ግድም ትንሽ ዘና የማለት ፍላጎት አድሮብን፣ ከአንድ ቡና ቤት ወደ ሌላ እየተዘዋወርን ስንጫወት፤ ስናወጋና ጭፈራ ስናይ እያመሸን ሳለን፤ በአንደኛው መዝናኛ ቦታ የኤርትራ ዘፋኝ የሚጫወተው ዘፈን ይዘፈናል፡፡ ሰው በየነሸጠው ቅፅበት እየተነሳ ይጨፍራል፡፡ ይደነክራል፡፡ የደከመው ይቀመጣል፡፡ ሌላው በራሱ ጊዜ ይነሳል፡፡
በአጋጣሚ ከእኛ ከአዲሳቤዎቹ እንግዶች አጠገብ የተቀመጡ የዚያው ክልል ሰው፣ ጎምቱ አዛውንት ናቸው፤ ነሸጣቸውና ብቻቸውን ተነስተው ያስነኩት ጀመር - ጭፈራውን፡፡ እስኪበቃቸው ተወዛውዘው መጥተው አጠገባችን ተቀመጡ፡፡
የገረመንን አንድ አንድ ጥያቄዎች ከሰላምታ በኋላ እያነሳን መጨዋወት ቀጠልን፡፡
“እንግዳ ትመስላላችሁ?” አሉ፡፡
“አዎን ከአዲሳባ ነን፡፡ ደሴ አድረን ነው ወደዚህ የመጣን”
“ለሥራ ነው፣ አገር ለማየት? የመጣችሁት?”
“ለሥራ ነው፡፡ ሆኖም ሥራችንን ስናገባድድ፣ አገር ማየታችን አይቀርም መቼም ….
እርስዎ መቼም የዚሁ አገር ሰው መሆንዎ አያጠራጥርም”
“አዎ እዚሁ ነኝ፡፡”
“አሁን ተነስተው ሲጨፍሩ ገርሞን ነበር የምናይዎት”
“በስተ እርጅና እንዴት ይጨፍራል ብላችሁ ነው?”
“ኧረ አይደለም”
“ታዲያ ምንድን ነው ያስገረማችሁ?”
“በሀገራችን እንደምንሰማው ከኤርትራ ጋር ጦርነት ውስጥ ልንገባ አሥራ አንደኛው ሰዓት ላይ ደርሰናል ነው የሚባለው”
“አዎን”፤ አሉ አቦይ ሳያመነቱ፡፡
“ይሄ አሁን ሙዚቃው የሚጫወተው ዘፈን ደግሞ ኤርትራዊ ዘፋኝ የሚዘፍነው፤ የኤርትራዊ ዜማ ቅኝት ነው፡፡”
“እንዴታ?!”
“እንዴት ሊሆን ይችላል? ባሁኑ ሰዓት እንዴት ሊዘፈን ቻለ? እርሶስ እንደምን ይደንሱበታል!”
አቦይ፤ አልተደናገጡም፡፡ ግር ማለትም አልታየባቸውም፡፡
“አያችሁ ልጆቼ! አዲሳባ ሆናችሁ ስለ ኤርትራና ኢትዮጵያ ድንበር ጦርነት የሰማችሁት ሁሉ ዕውነት ነው፡፡ ጦርነቱ አይቀሬ ነው፡፡ ደም መፋሰስ ይኖራል፡፡ ከሁለቱም ወገን ሰው ያልቃል፡፡ ጥንት የነበረው አብሮ መኖር ሁሉ ይቀራል!
ግን አንድ ፅኑ ዕውነት ልንገራችሁ፡፡ በኤርትራና በትግራይ (በኢትዮጵያ) ድንበር መካከል፣ በሥራቅና ምዕራብ ጀርመን መሀል እንደነበረው ዓይነት ታላቅ ግንብ ቢገነባ እንኳን፤ ለካሴት መቀባበያ የምትሆን አንዲት መስኮት ትኖራለች!!” አሉና “ተነሱ እንጫወት እባካችሁ!” ብለው “ደርብ!” አሉ፡፡ ጭፈራው በጣም ያምርባቸዋል፡፡
*   *   *
ያቺ የአቦይ መስኮት የባህል በር ናት፡፡ የታሪክ በር ናት፡፡ የልብ ለልብ መተሳሰቢያ ምት ናት! የህዝብ መተናፈሻ ናት!! ከሥጋ ዝምድና፣ እስከ ጋብቻ፣ በጉርብትና ቡና ከመጠራራት እስከ ጠቅላይ አብሮ መኖር ድረስ በዚያች መስኮት ታሪካዊ ቅብብሎሹ ይቀጥላል፡፡ ትላንት ነበረ፣ ዛሬም አለ፡፡ ነገም ይኖራል!! እንደ ዛሬ በራሱ ጊዜ መስኮቱ ሰፊ በር፣ ሰፊው በር ደግሞ ዋናው “ከተም በሪ” ይሆናል፡፡ ብሎ ማን ያስባል? ወይም ደግሞ ግንቡ እንደ ጀርመኑ ግንብ እስከናካቴው ይፈራርስ ይሆናል፡፡ ከዚያም የምናስተውለውን ወለል ያለ ሰፊ እይታ እናስብ፡፡ ገላጣውን የአንድነት አውላላ ሜዳ (ፈረንጆቹ WIDER VISTA የሚሉትን ዓይነት) እንደምን በፍቅር አንቀልባ ጠቅልለን እንደምንይዘው ከርቀት እንይ፡፡
ዛሬ! ጊዜው በራሱ ጊዜ ወገግ ያለ ይመስላል፡፡ እኛስ?
“ጊዜ በራሱ ጊዜ ወገግ
ጭፍግ የራሱን ጭጋግ ጥርግ
ዕድሜ በራሱ ሰዓት ፈገግ! …
እንል ይሆን ቀን ሳንሸሽግ?!
የት ድረስ ነው የምኞት ድግ?
የት ድረስ ነው የተስፋስ ጥግ?...”
ዛሬ! የይቅርታ መስኮት አንድ ፀጋ ነው፡፡ የህገ መንግሥት ሥርዓትና መልክ መያዝ ሌላ መስኮት ነው፡፡ የንቃተ - ህሊናችን ማደግ፣ የትጋታችን መቀስቀስ፣ የተስፋችን ማበብ ዋና በር ነው! ከሁሉም በላይ ግን ዜጋን የማፈን፣ የመሸሸግ፣ የውስጥ ውስጡን መመሳጠር፣ የእስር ቤት አሰቃቂ ህይወት፣ የሸፋፍነህ ግዛ ኢ-ፍትሐዊ ግፍ፣ የነጋዴ ቢሮክራቶች ፖለቲካ - ኢኮኖሚያዊ ምዝበራ፣ የመንግሥት መጨቆኛ መሳሪያዎች ቁልፉ ፍሬ ነገር ነው! የቅርቡ የኢትዮጵያ የሥርዓት እርምት፣ ሽግሽግ፣ ሽግግርና እድሳት አዲስ ሂደት፤ ህዝበ - ሱታፌን የሚጠይቅ፣ ኢትዮጵያ የሁላችንም አገር መሆኗን በአንድ አፍ፣ በአንድ ልብና በአንድ አቅም፣ አንድም ሦስትም ነን በሚሰኝ ብልሃትና ጥበብ-ተስፈኛ፣ አዎንታዊ እና ልበ - ሙሉ አገር ለዋጮች የምንሆንበት ይመስለናል፡፡
ዛሬ!
እስቲ ከቁጣ፣ ከቂም፣ ከበቀል፣ ‹ከእኔ ብቻ ነኝ ልክ› እንውጣና እራሳችንን ከፍቅርና ከሰላም አቅል አቅጣጫ እንመልከት የምንልበት ቀን ነው! ያጣናቸውንና ያመለጡንን፣ ያልተጠቀምንባቸውን ቀና ነገሮች ሁሉ፣ በቁጭት ከመመንዘር ይልቅ፣ “ነገ የሚባል የማናውቀው ቀን እንይ” ብለን አሰልቺውን ህይወት፣ ከሻካራ ገፁ የምንነጥልበት የምናበለፅግበት ቀን መጥቷል፡፡ ትላንት የቆሰልነውና የደማንበት! “አሸነፍን አላሸነፍን” የተባባልንበት፡፡ በታሪክ፣ በባህል፣ በሃይማኖት አስተሳስሮን፣ አንጀታችን ገብቶ፣ አድሮ የማይሞተውን ፍቅራችንን የሚተካ፣ ዞሮ መግቢያና ማረፊያ አገራችንን የሚያኮራ፣ የማቴሪያልም ሆነ የአካላዊ ጥቅም ፍሬ አላገኘንበትም፡፡ ዋጋው የማይለካ (Priceless እንዲሉ) ነገር! ወንድማማችነታችን፣ ተዛምዶአችን፣ መጋባት መዋለዳችን፤ መግባባትና አብረን መሳቃችን፣ አብረን ማደጋችን፤ የማይበጠስ ማተባችን፣ መንፈሳዊ መቀንቻችን የሁልጊዜ ህልውናችን መሆኑን፣ ዛሬ ባንድ ልብና ልቦና አሳድረነዋል! አንድነት የጠራ ሀቃችን (Crystal Truth) መሆኑን፣ የማይሸራረፍ ህልውናችን መሆኑን፣ የማታ ማታም ቢሆን ነብሳችን ላይ መንቀሳችን ቀዳሚና ላዕላይ እሴታችንን ማስረገጣችንን እንድናሰምር አግዞናል! ለዚህና ስለዚህም ምስክርነት የሚሰጥ፣ ከእኛና ከእኛ ሌላ ማን አለ?
ሎሬት ፀጋዬ ገ/መድህን፤ በአንደኛው ተውኔቱ ውስጥ ስለ እሥር ቤት የነገረንን ዛሬ ብናስታውስ ደግ ነው፡፡ ባጭሩ ጃንሆይ ወህኒ ቤትን መርቀው ሲከፍቱ ያደረጉት ንግግር ነው፡-
“የአባታችን ርስተ - ጉልት የሆነውን ይህንን የሀገር ወህኒ ቤት መርቀን ስንከፍትላችሁ፤ እናንተም፤ በተለመደው ባህላችሁ፣ በመተሳሰብ እንድትተሳሰሩበት ነው!”
አንዳችን አንዳችንን ስናስር ኖረናል፡፡ በየታሪካችን ምዕራፍ እንደተቀመጠው፤ ጦር ሰብቀን፣ ዘገር ነቅንቀን፣ ደም ተፋሰን፣ ሬሳ ተቋጥረን፣ ድንበር ተቋርሰን፣ … የሁለንተናችን መገለጫ ሰውና የሰው ሰላም መሆኑን አናምንም ብለን፤ እንደ ጉልት ደንጊያ አንነቀነቅ ብለን፤ በጉድ አዋጅ እንደታጠርን ብዙ የደም ዘመን ገፋን! ዛሬስ ይብቃን! ዛሬ በሰፊ አዕምሮ ስናስተውለው፤ “ለዚሁ ነው በሬዬን ያረድኩት?” እንዳለው ሰውዬ መሆናችንን በትዝብት ተገነዘብን! ለልጆቻችን የምናወርሰው ፍቅርና ግብረገብነት የሌለን፣ ባዶ ልብና ባዶ ኪስ ነን! ታሪክ እያለን ታሪክ እንደሌለን የሆንንበትን ምክንያት መመርመር አለብን! ታሪክ ሰሪም፣ ታሪክ - ፀሐፊም ማጣት እርግማን ነው! ኦና ቤት ውስጥ የነግ ዕጣ - ፈንታውን ሳያውቅ እንደተቀመጠ እንስሳ ሆነን መኖራችን ደግሞ የከፋ እርግማን ነው!
“እራስን በራስ ማስተዳደር እስከ መገንጠል” (Regional autonomy upto and including cessation) የማለትን መርህ እያስታወስን፤ ወደ ኋላ እየሳቅን፣ ወደፊት ለመራመድ የምናስብበት ወቅት ይመስላል!
ዛሬ!
ጦርነት ኋላ ቀር ነው የሚለውን ሃሳብ እንደ “ማጨስ የፋራ ነው” እንደማለት ማስተዛዘብ ጀምረናል፡፡ ቤርቶልት ብሬሽት “ጀግና የማትወልድ አገር የታደለች ናት!” ያለንን መቀበል ላይ ነን፡፡
የደም ጀግንነት ይብቃን እንደማለት ነው፡፡ “የሰሜንን እህል፣ አልበላም እርሜ ነው ያጨደው መትረየስ፣ ያፈሰሰው ደም ነው!” ያልነውን የምር አረግነው እንደማለት ነው፡፡ ሁሉንም በዲሞክራሲ ገበታ ላይ ብንመካከረውስ? ማለት ስልጣኔ ነው! ወደ ሥልጣኔ ገበታ እኩል እጃችንን መሰንዘር መቻል መታደል ነው! ጥቂቶች የሚሞቁት ደመራ ሳይሆን ሁሉም ችቦ ችቦውን ይዞ “እዮሃ!” የሚልበት በዓል ዘንድ እየደረስን ነው፡፡
የትላንትናን ጥፋት በአንዲት በዛሬ ጀንበር እንሰርዘዋለን ማለት የዋህነት መሆኑን አላጣነውም! ይቅርታን መድፈር ብርቱ ጅማሮ ነው! እርቅ ኃያል ግለ - ሂስ ነው! ያማል ግን ያድናል! ዛሬም ለውጥ አዳጊ ሂደት እንጂ በቁርጥ ክፍያ የሚጨረስ የቀን ሥራ አይደለም! ስንል እንደኖርነው ሁሉ፣ ዛሬም Change is an incremental process- አዳጊ ሂደት ነው! የሁላችንም ድምፅ ወደሚሰማበት አገር ለመሄድ መንገድ መጀመር ነው ዲሞክራሲ፡፡ ዲሞክራሲን ያፈንነው እኛ ነንና፣ የምንፈታውም እኛው ነን! ያማረ ነገር ስናይ “ምነው የእኔ በሆነ” ማለት ሰብዓዊ ምኞት ነው፡፡ “ያ ያማረ ነገር ምነው የእኔ ብቻ በሆነ” ማለት ግን ገና ከጥንስሱ ጤና ያጣ ፍላጎትን ያዘለ ነው፡፡ ሁሉም ነገር፤ የተጣመመው ተቃንቶ፣ የተበላሸው ተስተካክሎ፣ ፀድቶ እንደነበረው እንዲሆን ለማድረግ መጣጣራችን መልካም ነው፡፡ ሆኖም ዛሬ ሌላ ጠዋት ነውና፣ ራሱን ትላንት ጠዋትን ካላገኘሁ ሞቼ እገኛለሁ አንበል፡፡ እንኳን ትላንት ጠዋት፣ ነገ ጠዋትም ሌላ ነው!
“ወዳጅና ወዳጅ፣ የተጣላ እንደሆን
መታረቁም አይቀር፣ እንደጥንቱም አይሆን!”
ተብሎ ሲነገር የኖረው Nothing remains the same; everything changes except the law of change (ምንም ነገር እንዳለ አይቆይም፡፡ ሁሉ ተለዋጭ ነው፣ ከለውጥ ህግ በስተቀር! እንደማለት ነው፡፡) ከዚህ ተነስተን በስንኝ ጥያቄ ብንቋጥር፤
ለሁሉም ጊዜ አለው ብሏል ሰለሞን
እጠይቀው ነበር በተገናኘን
 መገንጠል የሚሞት ምን ጊዜ እንደሆን?
በለውጥ ጎዳና ላይ የማስጠንቀቂያ ደወል አለ፡፡ እንዲሁም የህይወት ሂደት፡፡
“የአገራችን ፖለቲከኞች ዋና ችግር ማክረር ነው - ሁሉን ነገር ማጥበቅ! ስለዚህ ላላ ፈታ ማለት ያስፈልጋል፡፡ አይመስልህም?” ብሎ ቢጠይቀው፤
“መላላቱንም አታጥብቀው!” አለው፡፡ የጀመርነውን ተስፋ ያዝልቅልን!!  

ኦኤምኤን ቴሌቪዥን ዛሬ ከአዲስ አበባ ስርጭቱን ይጀምራል

    መንግስት አገልግሎት እንዳይሰጡ ዘግቷቸው የነበሩ 264 የተለያዩ ድረ-ገጾችና የጦማርያን ገጾችን በመክፈት አገልግሎት እንዲሰጡ ማድረጉን፣ የጠቅላይ ሚኒስትር ጽህፈት ቤት ሃላፊው አቶ ፍጹም አረጋ ትናንት በትዊተር ገጻቸው አስታውቀዋል፡፡
በአሜሪካ ፍቃዱን አግኝቶ የሚሰራጨው የኦሮሞ ሚዲያ ኔትዎርክ (OMN) ቴሌቪዥን፣ በዛሬው ዕለት ከአዲስ አበባ ሥርጭቱን እንደሚጀምር ታውቋል፡፡
ሃሳብን በነጻነት የመግለጽ መብትን ማረጋገጥ፣ ለሌሎች መብቶች መከበር መሰረታዊ ጉዳይ መሆኑን የገለጹት አቶ ፍጹም፤ በመስኩ የማሻሻያ እርምጃዎችን በመውሰድ ላይ የሚገኘው የጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አህመድ መንግስት፣ ተዘግተው የነበሩ ድረ-ገጾችን በመክፈት፣ አገልግሎት እንዲሰጡ ማድረጉን አመልክተዋል፡፡
ነጻ የመረጃ ፍሰት እንዲኖር ማድረግ፣ በአገሩ ጉዳይ ተሳታፊና ሃላፊነት የሚሰማው ዜጋ ለመፍጠር ቁልፍ ሚና ይጫወታል ያሉት አቶ ፍጹም፤ መንግስት የተዘጉ ድረገጾችን ከመክፈት በተጨማሪ የኢሳትና የኦኤምኤን የቴሌቪዥን ስርጭቶች በነጻነት እንዲታዩ መፍቀዱንም ገልጸዋል፡፡    
አሶሼትድ ፕሬስ በበኩሉ፤ መንግስት ዘግቷቸው የነበሩት ብዙዎቹ ድረ-ገጾች በአሜሪካና በሌሎች ውጭ አገራት የተከፈቱ እንደሆኑ በመጠቆም፣ በአገሪቱ ታስረው የነበሩ ከሞላ ጎደል ሁሉም ጋዜጠኞችና ጦማሪያን በአዲሱ የጠቅላይ ሚኒስትር አቢይ መንግስት ከእስር መለቀቃቸውንና መንግስትን በመተቸት በሚታወቁ አክቲቪስቶች ላይ ተመስርተው የነበሩ ክሶች መቋረጣቸውን ዘግቧል፡፡