Administrator

Administrator

    ከሳምንታት በፊት በጠባቂያቸው 119 ላፕቶፖችን የተዘረፉት የቀድሞው የዚምባቡዌ ፕሬዚዳንት ሮበርት ሙጋቤ፤ አሁን ደግሞ ጉሹንጎ ሆልዲንግስ በተባለው ተቋማቸው ተቀጥሮ በሚሰራ የሂሳብ ባለሙያ 10 ሺህ ዶላር ያህል መዘረፋቸውን አፍሪካን ኒውስ ድረገጽ ዘግቧል፡፡
ፒተር ቢሂቢ የተባለውና ዝርፊያውን ፈጽሟል የተባለው የድርጅቱ ሰራተኛ፣ በፖሊስ ቁጥጥር ስር ውሎ ባለፈው ሳምንት ፍርድ ቤት መቅረቡን የጠቆመው ዘገባው፤ በ100 ዶላር ዋስትና የተለቀቀው ግለሰቡ በመጪዎቹ ሳምንታት ተገቢው የፍርድ ውሳኔ ይተላለፍበታል ተብሎ እንደሚጠበቅም አመልክቷል፡፡
ይህ የዝርፊያ ወንጀል ከተፈጸመ ከቀናት በፊትም ጠባቂያቸው የነበረ አንድ የአገሪቱ ወታደር ከሮበርት ሙጋቤ 119 ላፕቶፕ ኮምፒውተሮችን በመዝረፍ መሰወሩንና በፖሊስ ቁጥጥር ስር መዋሉን ያስታወሰው ዘገባው፤ ተጠርጣሪው ግን “ላፕቶፖቹን ሙጋቤ ናቸው በስጦታ መልክ የሰጡኝ” ሲል መከራከሩንና ከሰሞኑም እርግጥም ሰጥተውት እንደሆነ ራሳቸው ሙጋቤ ምስክርነት ይሰጣሉ ተብሎ እንደሚጠበቅ ተጠቁሟል።

 የታንዛኒያ መንግስት 900 ዶላር በመክፈል የጡመራ ፈቃድ ሳያወጡ ሲሰሩ ያገኛቸውን ጦማሪዎች፤ የ2 ሺህ 200 ዶላር እና የ1 አመት እስር ቅጣት እንደሚያስተላልፍባቸው ከሰሞኑ ማስታወቁን ሲኤንኤን ዘግቧል፡፡
የአገሪቱ መንግስት ባለፈው መጋቢት ወር በስራ ላይ ባዋለው አዲስ የድረገጽ ይዘት መመሪያ መሰረት፣ ተመዝግበው ከሚመለከተው አካል ፈቃድ ያላገኙ ጦማሪዎች፤ ከዛሬ ጀምሮ በህገወጥ መንገድ ሲሰሩ ከተገኙ የተጠቀሰው እርምጃ እንደሚወሰድባቸው ማስጠንቀቁን ዘገባው ገልጧል፡፡
ጦማሪያኑ አብረዋቸው የሚሰሩ ባለአክስዮኖችን፣ ካፒታላቸውን፣ ዜግነታቸውን፣ የሙያ ብቃታቸውን፣ የታክስ የምስክር ወረቀታቸውንና የመሳሰሉትን መረጃዎች ለሚመለከተው አካል እንዲያስመዘግቡና 900 ዶላር ከፍለው ፈቃድ ማግኘት እንዳለባቸው የሚያስገድደው መመሪያው፤ ሃሳብን በነጻነት የመግለጽ መብትን የሚጥስ፣ ኢ-ፍትሃዊ እርምጃ በሚል በአገሪቱ ጦማርያንና አክቲቪስቶች መተቸቱንም ዘገባው አመልክቷል፡፡

    ኤችአይቪ ቫይረስ በሚያስከትለው የአቅም መዳከም የተነሳ በመውለድ እድሜ ላይ ያሉ ሴቶችን ጤንነት የሚፈታተንና እንዲሁም ቫይረሱ ወደ ቤተሰብ የመተላለፍ እድሉን ስለሚጨምር ወደ ፊት ልጅ ለመውለድ የሚኖራትን ፍላጎት ሊፈታተነው ይችላል፡፡ ስለዚህም ያልተፈለገ እርግዝና መከላከያ መጠቀም ያልተፈለገ እርግዝናን ከመከላከሉም ባሻገር ቫይረሱ ከእናት ወደልጅ የሚኖ ረውን መተላለፍ ይቀንሳል፡፡
ከላይ የተጠቀሰው እውነታ ከአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ጤና ሳይንስ ኮሌጅ ንጹህ አዲስና ዶ/ር እስክንድር ከበደ ካደረጉት ጥናት የተወሰደ ነው፡፡ ጥናቱ የተደረገው በአዲስ አበባ ጥቁር አንበሳ፤ ጋንዲ መታሰቢያ ሆስፒታል እና ዘውዲቱ መታሰቢያ ሆስፒታል በእርግዝና ወቅት ክትትል ከሚደረግበት ክሊኒክ ነው፡፡ በሶስቱ ሆስፒታሎች በአመት እስከ 12.000/አስራ ሁለት ሺህ እናቶች የሚወልዱ ሲሆን ጥናቱ የተደረገውም April-August/2016/ ድረስ ነው፡፡
የኤችአይቪ ቫይረስ በደማቸው ውስጥ ያለ ሴቶች እርግዝናን በእቅድ ወይንም በፕላን እንዲያ ደርጉ የሚመክረውን ጥናት ለማድረግ በጥናቱ የተካተቱ ሴቶች በሙሉ ቫይረሱ ያለባቸው ሲሆኑ በተጠቀሱት ሆስፒታሎች የእርግዝና ክትትል በማድረግ ላይ የነበሩ ናቸው፡፡ በእርግጥ ቫይረሱ በደማቸው ቢኖርም በምጥ ላይ የነበሩ ወይንም ጽንስ በማቋረጥ ላይ የነበሩ እና የተረ ገዘው ልጅ ሞት የገጠማቸውን እናቶች ጥናቱ አላካተተም፡፡ በጥናቱ የተካተቱት እናቶች 183/ሲሆኑ በተለይም 173/እናቶች 94% የሚሆኑት ለጥናቱ ጠቃሚ መረጃን በመስጠት ተሳትፈዋል፡፡   
ሰውነት ሕመምን እንዲቋቋም የሚያስችለውን አቅም የሚፈታተነው ኤችአይቪ ቫይረስ ከሰሀራ በታች ባሉ የአፍሪካ አገራት ከፍተኛውን የስርጭት ቁጥር የያዘ ሲሆን ከዚህም ሴቶች 58% የሚሆነውን በቫይረሱ የመያዝ ድርሻ ይይዛሉ፡፡ የኤችአይቪ ስርጭት በህጻናቱም በኩል ከሰሀራ በታች ባሉ የአፍሪካ አገራት ከፍ ያለ ቁጥር የተመዘገበበት ሲሆን በአለም በአመት በአዲስ በቫ ይረሱ ከሚያዙት 98% የሚሆኑት በዚሁ ክልል የሚኖሩ ናቸው፡፡
እርግዝናን በእቅድ መፈፀም በተለይም በደማቸው ውስጥ የኤችአይቪ ቫይረስ ላለባቸው ሴቶች እጅግ አስፈላጊ ከሚሆንበት ምክንያት አንዱ ቫይረሱ ከእናት ወደልጅ እንዳይተላለፍ ለማድረግ ሲሆን ከፕላን ውጭ የሚደረገው ግን በጣም አደገኛና የተጸነሱትን ልጆችም ከቫይረሱ ለመጠበቅ የማያስችል የተሳሳተ አካሄድ ነው፡፡
ያልተፈለገ እርግዝናን መከላከያ ዘዴን መጠቀም አቅምን ያገናዘበና ኤችአይቪ ከእናት ወደ ልጅ እንዳይተላለፍ ለማድረግ እንዲሁም የእናቶችን እና የህጻናቱን ጤንነት እና ሕይወትን ለመጠበቅ የሚያስችል አስተማማኝ ዘዴ ነው፡፡ ኮንዶምን መጠቀም ኢንፌክሽንን ከመተላለፍ የሚያግድ ጠቃሚው መንገድ ነው፡፡
አንዳንድ መረጃዎች እንደሚጠቁሙት ከሰሀራ በታች ባሉ የአፍሪካ አገራት /20-43% የሚሆኑ ቫይረሱ በደማቸው ያለ እናቶች ብቻ የቤተሰብ እቅድ ዘዴን የሚጠቀሙ መሆኑ ተረጋግጦ አል፡፡ በተደረገው ጥናት ውጤት መሰረትም 14/ሚሊየን/አስራ አራት ሚሊየን የሚሆኑ ያልታ ቀዱ እርግዝናዎች በየአመቱ ከሰሀራ በታች ባሉ የአፍሪካ አገራት ይከሰታሉ፡፡ ከዚህ ጋር በተያ ያዘ በተደረገው ዳሰሳ የተገኘው ምላሽ እንደሚያሳየው ከሆነ ያገቡ እና የተማሩ እንዲሁም በከ ተማ የሚኖሩ ቫይረሱ በደማቸው የሚገኝ ሴቶች በተሻለ ያልተፈለገ እርግዝናን መከላከል የሚያ ደርጉ ሲሆን በተቃራኒው ደግሞ ሴቶቹ በራሳቸው ሕይወት መወሰን የማይችሉ ፤ ዝቅተኛ የኑሮ ደረጃ (ድህነት) ያላቸው ፤ዝቅተኛ የሆነ የቤተሰብ እቅድ ዘዴ አገልግሎት ካለ እና የቤተሰብ ቁጥራቸው ከፍ እንዲል የሚፈልጉ ከሆነ ችግሩን ለማስወገድ ጥረት የማያሳዩ ናቸው፡፡
እንደውጭው አቆጣጠር በ2011/በተደረገው ጥናት በአዲስ አበባ 43.3% የሚሆኑ ቫይረሱ በደ ማቸው ያለ እናቶች ልጅ እንዲኖራቸው የሚፈልጉ ሲሆን በጥናቱ ከታቀፉት ውስጥ 71.5% የሚሆኑት በቅርብ እንደሚወልዱ ተናግረዋል፡፡ መልስ ከሰጡት 26.8% የሚሆኑት ጥናቱ በሚ ካሄድበት ወቅት እርጉዝ የነበሩ ናቸው፡፡
በኢትዮጵያ በተደረገው ጥናት እንደታየው ከሆነ ሴቶች በምርመራ ቫይረሱ በደማቸው ውስጥ መኖሩ ሲነገራቸው ወዲያውኑ ልጅ እንዳይኖራቸው የሚወስኑ ብዙ ሲሆኑ በኬንያ ደግሞ አብዛ ኞቹ ማለትም 87% የሚሆኑት ቫይረሱ በደማቸው የሚገኝ እናቶች ቫይረሱ ከእናት ወደልጅ እንዳይተላለፍ የሚያስችለውን ፕሮግራም በፈቃደኝነት እንደሚሳተፉና ወደፊትም ያልተፈለገ እርግዝናን ለመከላከል የቤተሰብ እቅድ ዘዴን ለመጠቀም ዝግጁ መሆናቸውን ስላሳዩ በዚህም ወደ 59% የሚደርስ ያልተፈለገ እርግዝናን ለመከላከል ፈቃደኝነት እና ተግባር ታይቶ አል፡፡
በኢትዮጵያ በጥቁር አንበሳ ሆስፒታልና በጋንዲ ሆስፒታል በውጭው አቆጣጠር በ2013/ በተደ ረገው ጥናት የታየው ያልተፈለገ እርግዝና ቫይረሱ በደማቸው ባለባቸው ሴቶች 56.3% ሲሆን ቫይረሱ በደማቸው የሌለባቸው ሴቶች ግን 29.5% ማለትም በግማሽ ያህል የቀነሰ ነበር፡፡
አስፈ ላጊውን መከላከያ ያለማግኘት ምክንያት ተደርገው የሚወሰዱት፤
በጉዳዩ ዙሪያ ማለትም ስለመከ ላከያዎቹ አገልግሎት ትንሽ ወይ ንም ጭርሱኑ እውቀት አለመኖር፤
አገልግሎቱን ለማግኘት አለመቻል ፤
በኤችአይቪ እና በቤተሰብ እቅድ ዘዴ አገልግሎት መካከል ቅንጅት አለመኖር፤
የአድሎና መገለል ፍራቻ የመሳሰሉት ናቸው፡፡
ቫይረሱ በደማቸው የሚገኝ እናቶች ኮንዶምን ስላለመጠቀም የሰጡት መልስ የሚከተለውን ይመስላል፡፡
እኔ እርጉዝ ነኝ፡፡ ስለዚህ ኮንዶም መጠቀም አያስፈልገኝም፡፡
ባለቤቴ በኮንዶም መጠቀም የሚባለውን ነገር በፍጹም አይደግፈውም፡፡አይወድም፡፡
ፍቅረኛዬ ወይንም በወሲብ የምገናኘው ሰው እኔ ቫይረሱ በደሜ ውስጥ እንዳለ አያውቅም።
በኮንዶም ወሲብን መፈጸም ስሜትን ስለሚቀንስ አላደርገውም፡፡
ምክንያቱ ባይገባኝም አልወደውም፡፡
ሌሎች፡-
ኤችአይቪ ኤይድስ ከእናት ወደልጅ እንዳይተላለፍ ከሚረዱ መንገዶች አንዱ ያልተፈለገ እርግ ዝናን መከላከል ወይንም ተገቢውን የጊዜ እርቀት በመጠቀም ልጆችን ማፍራት እንዲሁም ምን ያህል ልጅ በቤተሰብ መወለድ አለበት የሚለውን መወሰን ነው፡፡
ለዚህ ጽሁፍ መነሻ የሆነው ጥናት እንደሚያሳየው ከሆነ በጥናቱ ከተካተቱት በደማቸው ኤችአይቪ ቫይረስ የሚገኝባቸው ሴቶች መካከል እርግዝናቸው የታቀደ መሆኑን ያረጋገጡት 113/ሲሆኑ 60/ዎቹ ግን ካለእቅድ ማርገዛቸውን ተናግረዋል፡፡ ስለባለቤቶቻቸው ኤች አይቪ መረጃ ሲመልሱም 83/የሚሆኑት ቫይረሱ በባላቸው ደም ውስጥ እንዳለ ሲመሰክሩ 34/የሚ ሆኑት ደግሞ ነጸ መሆኑን ተናግረዋል፡፡ ነገር ግን 56/የሚሆኑት ሴቶች ባላቸው ኤችአይቪ ቫይረስ በደሙ ውስጥ ይኑር አይኑር የሚያውቁት ነገር የለም፡፡
ያልተፈለገ እርግዝናን መከላከል ከሚያስችሉ መከላከያዎች በተለይም ቫይረሱ ያለባቸው ሰዎች ቢጠቀሙ የሚመከረው ኮንዶም ነው፡፡ ይህንን በተመለከተም ቫይረሱ በደምሽ ውስጥ መኖሩ ከታወቀ በሁዋላ ኮንዶም መጠቀም ጀምረሻል ወይ ለሚለው ጥያቄ አልጠቀምም ያሉ /71/ሲሆኑ አንዳንድ ጊዜ ያሉ /55/ናቸው፡፡ በተከታታይ እጠቀማለሁ ያሉ ግን /47/ያህል ናቸው፡፡ ኮንዶምን በእርግዝናው ወቅት ትጠቀማላችሁ ወይ ለሚለው ደግሞ አዎን የሚል ምላሽ የሰጡ /45/ ሲሆኑ አልጠቀምም ያሉት ግን 126/ናቸው፡፡
ባጠቃላይም በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ያሉ የጽንስና ማህጸን ሕክምና ባለሙያዎች ባደረጉት ጥናት መሰረት ከተገኘው ውጤት በመነሳት የደረሱበት ድምዳሜ ከቫይረሱ ነጻ የሆነ ትውልድን ለማፍራት እንዲ ቻል፤ ቫይረሱ በደማቸው ያለ ሴቶች በተገቢው መንገድ ያልተፈለገ እርግዝናን መከላከል እንዲ ችሉ ፤እንዲሁም የኢንፌክሽን መተላለፍ እንዳይኖር ተገቢው ድጋፍና ክትትል እንዲሁም ምክርና አገልግሎት መስጠት ያስፈልጋል፡፡     

 በአንድ አገር በጀግንነት የተደነቀ አንድ ተወዳጅ ሰው ነበር፡፡ በመንደሩ ያሉት ሰዎች ሁሉ ስለ አንበሳነቱ ሲያወሩ አድረው፣ ሲያወሩ ቢውሉ፤ አይሰለቻቸውም፤ አይደክማቸውም፡፡
አንድ ቀን ሽፍቶች በመንደሩ ዙሪያ ለወረራ እየተዘጋጁ ነው የሚል መረጃ መጣ፡፡ አገሬው ተረበሸ፡፡ የአገር ሽማግሌዎች ተሰበሰቡና ምን እናድርግ ተባባሉ፡-
አንደኛው - “በየቤታችን ያለንን ጦርም ይሁን ገጀራ እናሰባስብና በክፍል በክፍል ሆነን እንግጠማቸው” አሉ።
ሁለተኛው - “የለም እኛ ያንን እስክናደርግ ጊዜ አይሰጡንም፡፡ ስለዚህ ፈጥነን የጎበዝ አለቆች አንድ ሶስት መርጠን፣ አካባቢያቸውን እናጥቃ” አሉ፡፡
ሦስተኛው፡- “የለም እንደዚያ እንዳናደርግ ስልት ይጎድለናል፡፡ ስለዚህ ዋና የጎበዝ አለቃችን አድርገን ጀግናችንን እንምረጥና ሄደን እንንገረው፡፡ እሱ በሚሰጠን ትዕዛዝ እንንቀሳቀስ” አሉ፡፡
በሦስተኛው የአገር ሽማግሌ ሃሳብ፣ ሁሉም ተስማሙ እና ወደ ጀግናው ቤት ሄዱ፡፡
ጀግናው - “እንዴት አመሻችሁ? ዛሬ ምን እግር ጣላችሁ?” ሲል ጠየቀ፡፡
የሽማግሌዎቹ ተወካይ፤
“ጀግናችን ሆይ!
እንደምታውቀው ወይም እንደሰማኸው፤ ወራሪዎች ወደ መንደራችን እየገሰገሱ ነው፡፡ እኛ ደግሞ በቅጡ አልተዘጋጀንም፡፡ ፈጥኖ ጋሻ መከታ ይሆነናል ብለን የመረጥነው ሰው አንተን ነው፡፡ እሺ ካልከን በመረጥከው ዘዴ፣ ይሄን ይሄን አድርጉ በለን፡፡ ያዘዝከንን እንፈፅማለን” አሉ፡፡
ጀግናው - “ይሄ ቀላል ነገር ነው፡፡ እኔ ከናንተ ቃል አልወጣም፡፡ ዛሬውኑ ዝግጅት እጀምራለሁ፡፡ እናንተ የሽፍቶቹን መረጃ እያሰባሰባችሁ ትልኩልኛላችሁ”
ሽማግሌዎቹ በአንድ ድምፅ፤
“አምላክ ውለታህን ይክፈልህ፡፡ ፈጣሪ ያንተን ዓይነት ጀግና አያሳጣን! አጣዳፊ መረጃዎችን እያደራጀን፣ መልዕክተኛ እንልክብሃለን” ብለው አመስግነው ወጡ፡፡
የሽፍቶቹ መንደሪቱን መክበብ ወሬ፣ እየገነነ መጣ፡፡ ሽማግሌዎቹ ፍርሃት፣ ሽብርና ጭንቀት ከሰዓት ሰዓት እየወጠራቸው መጣ፡፡ የመንደሩ ሰው በየደቂቃው ‹ኧረ አንድ ነገር ይደረግ› ይላቸዋል፡፡ ውጥረት በውጥረት ሆነ መንደሩ፡፡
ሽማግሌዎቹ በየሰዓቱ፤
“ምነው ዝም አልክ?”
“ምነው ባንተ ተማምነን ጉድ አደረከን?”
“ኧረ እየገቡ ነው ይባላል?”
…እያሉ አጣዳፊ መልዕክቶችን ያዥጎደጉዱለታል፡፡
ጀግናው የሰበሰባቸውን መሳሪያዎች ይወለውላል፡፡ እየፈታ ይገጥማል፡፡ ዝናሩን በጥይት ይሞላል፡፡ ጠመንጃዎች በመልክ በመልክ ይኮለኩላል፡፡ ገምባሌና የጦር ልብስ ያዘጋጃል፡፡
ሽማግሌዎቹ ትዕግስታቸው አልቆ ሲሮጡ መጡ፡፡
“ህዝቡ እኛን ወጥሮ ሊገለን ነው፡፡ የመጨረሻውን ቃል ንገረንና ይሄን ትዕዛዝ ይዘን እንሂድ፡፡ ሽፍታውኮ ደጃፋችን ላይ እያፏጨ ነው?”
ጀግናው የመለሰው አንድ ነገር ብቻ ነው፤
“ጌቶቼ፣ ሞቼ ልጠብቀው እንዴ?! ለመሆኑ እናንተስ እኔን ብቻ ነው የምትጠብቁት? ህዝቡን አታደራጁትም?” አለ፡፡
*   *   *
ያለ ዝግጅት፣ ያለ ድርጅት፣ ያለ ስነ አዕምሯዊ ብቃት፣ ያለ ልበ ሙሉነት፣ የትም አይደረስም፡፡ “አንድ አይነድ አንድ አይፈርድ” የሚለውን የአበው አነጋገር አንዘንጋ፡፡ ከሁሉም አስቀድሞ ማህበረሰባዊ የአዕምሮ ዝግጅት፣ የአዕምሮ ስክነት ያስፈልጋል፡፡ ቀጥሎ በየግል የየራስ ኃላፊነትን መወጣትን ይጠይቃል፡፡ “እኔስ ምን እያደረኩ ነው? ገደሉን ለመሙላት ምን ጠጠር ልጣል?! ምን ሀሳብ ላዋጣ?” ማለት እጅግ ተገቢ ነገር ነው፡፡ ከቶውንም “እናቴን ያገባ ሁሉም አባቴ ነው” ከሚል አመለካከት መላቀቅም ለመጠነ - ሰፊ አስተሳሰብ አጋዥ ግብዓት ነው፡፡
“ለጌሾው ወቀጣ ማንም ሰው አልመጣ
ለመጠጡ ጊዜ ከየጎሬው ወጣ”
የሚለውን ጥንታዊ አባባል እንደ ትዝብት መነፅር እናስቀምጠው፡፡ ህብረ - ሱታፌ ወሳኝ ነገር ነው። “አይሆኑም” ብለን ቃል የገባንላቸው ጉዳዮች የማይሆኑት ስለተመኘናቸው አይደለም፡፡ ከእነ ችግራቸው በተግባር ልናስተናግዳቸው ስንችል ነው፡፡ ቀጥሎ ሁነኛ ከባቤ አየር (conduvive atmosphere) ሲኖር ነው። ይሄን ከባቤ አየር እኛም ተጨምረን ልንፈጥረው ስንችል ነው፡፡ “ሁለት ያለው አንዱን ለሌለው ይስጥ” እያሉ ሲያስተምሩ ያረፈዱት ሰባኪ”፤ ሚስታቸው ለተቸገሩ ሰዎች ልብሳቸውን ሰጥታ ጠበቀቻቸው፡፡ ተናደው “ለምን አደረግሽ?” ቢሏት፣ “እርሶ ባስተማሩት መሰረት ነው”፤ አሁንም ሰባኪው ብስጭት ብለው፤ “እኔ ስጡ አልኩ እንጂ ልስጥ አልኩ እንዴ?!” አሉ፤ አሉ፡፡ የምንለውን ሁሉ እራሳችንን ውስጡ አድርገን እናስብ! ሁሉም የሀገር ጉዳይ፣ የሁላችንም ጉዳይ ነው፤ እንበል!
በለውጥ ጉዟችን ላይ ዕውቀትን እየገነባን እንሂድ፡፡ እያወቅን ስንሄድ እያወቅንበት እንራመዳለን፡፡ በአንድ እጅ አይጨበጨብም፤ ይሏል፡፡ እንደ አገሩ ችግር ጥልቀት ግን በሁለትም ላይቻል ይችላል፡፡ ስለዚህም መጠነ ሰፊ የመተባበርር የማስተባበር፣ የማደራጀትና የመደራጀት ሥነ - ልቦና ያስፈልጋል፡፡ “መነሳትና ሳይነሱ እንነሳ ማለት ይለያያሉ” ይላሉ ሩማኒያውያን፡፡ ተነሱ አትበል፤ ራስህ ተነስ፤ እንደማለት ነው፡፡
ድክመቶቻችን ብዙ መሆናቸውን ካወቅን፣ አያሌ አመታት ተቆጥረዋል፡፡ ስንወተውት፣ ስናሳስብ፣ ወይ የሚለን አጣን፣ የሰሚ ያለህ ስንል ወቅቶች አልፈዋል፡፡ የዓለም የጤና ቀን፣ የዓለም የመረጃ ቀን፣ የዓለም የፕሬስ ቀን … የዓለም፣ የዓለም …  የዓለም … ባልን ቁጥር ጉዳዩን በዓለም አኳያ እናወጋለን፤ ጉዳዬ ነው እንለዋለን፡፡ ጣጣው የሚመጣው የእኛስ ቀን አለን ወይ? ያልን ዕለት ነው፡፡ የእኛ ቀን እንዲኖር እኛ ልባዊ ህልውና ያስፈልገናል። ፍቅራችን፣ አንድነታችን፣ ዝማሬያችን፣ ሐዘናችን ቃናው መቀራረብ አለበት፡፡ ጥረታችን መቀራረብ አለበት፡፡ ተስፋችን መዛመድ አለበት!
ከሁሉም ይበልጥ አሳሳቢ ከሆኑት ችግሮቻችን አንዱና ጉልሁ መናናቃችን ነው፡፡ በንቀት ምክንያት ማንም ማንንም ለማዳመጥ ፈቃደኝነት አጥቷል፡፡ ፖለቲካዊ ንቀት፣ ኢኮኖሚያዊ ንቀት፣ ትምህርታዊ ንቀት ከቦናል፡፡ “እሱን አናውቀውም እንዴ?” ብለን ጀምረን … “የእሱን ነገር አታንሳብኝ” ጋ ለመድረስ አፍታ አይፈጅብንም፡፡ የሀገራችን ፖለቲካዊ አመለካከት እመርታ ያስፈልገዋል፡፡ አለበለዚያ “አሁን እዚችም ሆድ ውስጥ እህል አለ?” አለች በቆሎ፤ ጤፍን አይታ፤ ከሚለው ተረት አንወጣም!  

 በፕሬስ ነጻነት አፈና ሰ/ ኮርያና ኤርትራ አለማችንን ይመራሉ

    የአለማችን አገራትን የፕሬስ ነጻነት አጠቃላይ ሁኔታ በመገምገም በየአመቱ ደረጃ የሚሰጠው ሪፖርተርስ ዊዛውት ቦርደርስ፣ ከሰሞኑም የ2018 አመት የአገራትን ደረጃ ይፋ ያደረገ ሲሆን፣ ኢትዮጵያ በፕሬስ ነጻነት ከ180 የአለማችን አገራት 150ኛ ደረጃን መያዟን አመልክቷል፡፡
በኢትዮጵያ የፕሬስ ነጻነት አፈናዎች ላይ ይህ ነው የሚባል መሻሻል አልታየም ያለው የተቋሙ ሪፖርት፣ በአገሪቱ ኢንተርኔትና ማህበራዊ ድረገጾች በተደጋጋሚ እንደሚዘጉ፣ የመገናኛ ብዙሃንን ለማፈን በጋዜጠኞች ላይ ጥቃቶች፣ ያለአግባብ እስርና ክስ  እንደሚፈጸም አመልክቷል፡፡
የጸረ-ሽብር ህጉ ከጸደቀበት ጊዜ ጀምሮ ጋዜጠኞችን ለማጥቃት በጥቅም ላይ ሲውል እንደነበር፣ ከሽብር ጋር በተያያዘ የተከሰሱ ጋዜጠኞች የረጅም ጊዜ እስር እንደሚፈረድባቸውና ለተራዘመ ጊዜ ፍርድ ቤት ሳይቀርቡ በእስር እንደሚቆዩም ገልጧል፡፡ የአገሪቱ መንግስት የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁን በመጠቀም የሰላ ሂስ በማቅረብ የሚታወቁ ጋዜጠኞችን ሊያስርና ህብረተሰቡ አንዳንድ መገናኛ ብዙሃንን እንዳይከታተል ሊከለክል ይችላል ሲልም ተቋሙ በሪፖርቱ አመልክቷል፡፡
በዘንድሮው አለማቀፍ የፕሬስ ነጻነት ሁኔታ አመልካች ሪፖርት መሰረት፣ በፕሬስ ነጻነት አፈና ከአለማችን አገራት ሰሜን ኮርያ ቀዳሚነቱን ስትይዝ ኤርትራና ቱርኬሚኒስታን በሁለተኛና በሶስተኛነት እንደሚከተሉ አስታውቋል፡፡
የ2018 የፈረንጆች አመት አለማቀፍ የፕሬስ ነጻነት ሁኔታ አመልካች ሪፖርት እንደሚለው የፕሬስ ነጻነት በአለማቀፍ ደረጃ አምና ከነበረበት ዘንድሮ ወደከፋ ሁኔታ የገባ ሲሆን፣ በርካታ የአለማችን አገራት ጋዜጠኞችም የተለያዩ አፈናዎችና ጥቃቶች ደርሶባቸዋል፡፡
በአፍሪካ ለጋዜጠኞች ምቹና የተሸለ የፕሬስ ነጻነት ያለባት አገር ጋና ናት ያለው ተቋሙ፣ ጋና በአለማችን አገራት የፕሬስ ነጻነት ደረጃ 23ኛ ላይ መቀመጧንና፣ ናሚቢያ 26ኛ ደቡብ አፍሪካ 28 ደረጃን መያዛቸውን አመልክቷል፡፡
የስካንዲኒቪያን አገሮች ዘንድሮም መልካም የፕሬስ ነጻነት በማስፈን በቀዳሚነት የተቀመጡ ሲሆን፣ አምና በፕሬስ ነጻነት ቀዳሚዋ የአለማችን አገር የነበረቺው የኖርዌይ ጋዜጠኞች ዘንድሮም ከተቀረው አለም አገራት በሙሉ በነጻነት እንዲሰሩ ተፈቀደላቸው ዕድለኞች ናቸው ተብሏል፡፡ ስዊድንና ኔዘርላንድስም በፕሬስ ነጻነት ከአለማችን አገራት ሁለተኛና ሶስተኛ ደረጃን ይዘዋል፡፡
ተቋሙ በ180 የአለማችን አገራት የፕሬስ ሁኔታ ላይ የሰራውን ጥናት መሰረት አድርጎ ባለፈው ረቡዕ ይፋ ባደረገው መረጃ እንዳለው፣ ከአለማችን አገራት የፕሬስ ነጻነትን በከፍተኛ ሁኔታ ያሻሻለቺው ቀዳሚዋ አገር ጋምቢያ ስትሆን፣ የፕሬስ ነጻነት ሁኔታቸው ከአምናው በከፍተኛ ሁኔታ የከፋባቸው አገራት በአንጻሩ ማልታ፣ ሞሪታኒያ እና ቼክ ሪፐብሊክ ናቸው፡፡

 “ሃገር ለዋጭ ሐሳቦች ከምሁራኑ ሊፈልቁ ይገባል”

    ከጊዜ ወደ ጊዜ እየተስፋፋ የመጣውን ጎሠኝነትና ብሔርተኝነት ከሃገራዊ ማንነት ጋር ማስታረቅ የሚቻልበትን የመፍትሄ ሐሳብ እንዲያፈላልጉ ጠቅላይ ሚኒስትር ዶ/ር ዐቢይ አሕመድ ለምሁራን ጥሪ አቀረቡ፡፡ የአገሪቱ ፖለቲካዊ ችግሮች የተወሳሰቡ በመሆናቸው ችግሮቹን አገናዝቦ መውጫ መንገድ የሚያሳይ ምሁር ያስፈልገናል፤ ብለዋል፡፡
ጠቅላይ ሚኒስትሩ ባለፈው ሳምንት የባሕር ዳር ቆይታቸው፤ በዐውደ ጥናት ላይ የነበሩ የባህር ዳር ዩኒቨርሲቲ መምህራንን ያነጋገሩ ሲሆን፤ ምሁራኑ ለሀገሪቱ ፖለቲካዊ ችግሮች መፍትሄ የሚሆኑ የምርምር ሥራዎችን እንዲያቀርቡ ጠይቀዋል፡፡ አገር ለዋጭ ሐሳቦች ከምሁራኑ ይፈልጋሉ ሲሉም ተናግረዋል፡፡
ምሁራኑ በሀገሪቱ እየተስፋፋ ስለመጣው የብሔርተኝነት ጉዳይ ጥናት እንዲያደርጉ ያሳሰቡት ጠቅላይ ሚኒስትሩ፤ “መንግሥት ከምሁራኑ ጋር እስካልተመካከረ ድረስ ከገባንበት ችግር ልንወጣ አንችልም፤” ብለዋል፡፡ የብሔር ማንነትና ኢትዮጵያዊ ማንነት የሚታረቁባቸው የመፍትሔ ሐሳቦች ከምሁራኑ እንዲፈልቅም ጠይቀዋል፡፡

 ከሀገረ ስብከቱ ሥራ አስኪያጅ ጋር አለኝ ያሉት ግንኙነት ትኩረት ስቧል
   ሥራ አስኪያጁ፣ ለሠራተኛ ቅጥር 100ሺሕ ብር ጉቦ መቀበላቸው ታወቀ

     በአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት የደብረ ምጥማቅ ሰዓሊተ ምሕረት ቅድስት ማርያም ካቴድራል፣ ከሀብት ምዝበራና ብክነት እንዲሁም ከሥርዐተ ቤተ ክርስቲያን ጥሰት ጋራ በተያያዘ ማኅበረ ምእመናኑ በአስተዳደር ሓላፊዎች ላይ ያቀረቡትን አቤቱታ ለማጣራትና ወራት ያስቆጠረውን አስተዳደራዊ ችግር ለመፍታት፣ ከብሔራዊ መረጃና ደኅንነት መምሪያ ተልኬያለሁ ያሉ ግለሰብን ፖሊስ አስሮ እየመረመረ ነው፡፡
በካቴድራሉ የተፈጠረው ችግር ከአቅሙ በላይ እንደኾነ በመግለጽ ለመፍትሔው ትብብር እንዲደረግለት፣ የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት ለብሔራዊ መረጃና ደኅንነት መምሪያ የፖሊቲካ ጉዳዮች ጽ/ቤት የጻፈውን ደብዳቤ በመያዝና በሕገ ወጥ መታወቂያ ተጠቅመው ራሳቸውን የመሥሪያ ቤቱ ባልደረባ በማስመሰል፣ የማጣራት ሒደቱን አስቀጥላለሁ በማለት የተንቀሳቀሱ ሲኾን፤ አኳኋናቸው በተጠራጠሩ የአጥቢያው ማኅበረ ምእመናን ዐቢይ ኮሚቴ አባላት ጥቆማ በፖሊስ ቁጥጥር ሥር ውለዋል፡፡
ኃይለ ኢየሱስ ተፈራ የተባሉት እኚሁ ግለሰብ፣ መጋቢት 19 ቀን 2010 ዓ.ም. ወደ ካቴድራሉ አምርተው ከአጥቢያው ማኅበረ ምእመናን ዐቢይ ኮሚቴ ጋራ በተገናኙበት ወቅት፣ ከብሔራዊ መረጃና ደኅንነት መምጣታቸውን ገልጸው እንደተዋወቋቸው የጠቀሱ ምንጮች፤ የካቴድራሉን አስተዳደራዊ ችግር የማጣራት ሒደት በእርሳቸው አማካይነት እንዲቀጥል የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት ፍላጎት እንደኾነና ለዚህም ደብዳቤ እንደደረሳቸው ለኮሚቴው ማስታወቃቸውን ተናግረዋል፡፡
በዕለቱ በተደረገው ስብሰባ፣ ቀደም ሲል የተጀመረው የማጣራት ሒደት የተስተጓጎለበትን ምክንያት ኮሚቴው ያስረዳ ሲኾን፣ በምክክርና በሰላማዊ መንገድ በአስቸኳይ እንዲፈታ ፍላጎት እንዳለው ገልጿል፡፡ ለዚህም፣ አቤቱታ የቀረበባቸውና በሕዝብ የታገዱት የአስተዳደር ሓላፊዎች በአካል ተገኝተው ከማስመርመር የዘለለ ተግባር ማከናወን እንደማይችሉ እንዲሁም ሀገረ ስብከቱ በአዲስ መልክ ከሚመድባቸው አጣሪዎችና ‘ደኅንነት ነኝ’ ካሉት ግለሰብ በተጨማሪ፥ ከጠቅላይ ቤተ ክህነት፣ ከአዲስ አበባ ፖሊስ ኮሚሽን፣ ከቦሌ ክፍለ ከተማ አስተዳደር ጽ/ቤትና ፖሊስ መምሪያ፣ ከቦሌ ክፍለ ከተማ የወረዳ 07 አስተዳደር ጽ/ቤትና ስድስት የአጥቢያው ምእመናን ተወካዮች እንደሚሳተፉ የጋራ ስምምነት ተደርሶ እንደነበር ተጠቁሟል፡፡
በበነጋው መጋቢት 20 ቀን 2010 ዓ.ም.፣ የካቴድራሉ የአስተዳደር ሓላፊዎች ፈጽመውታል የተባለውን የሀብት ምዝበራና ብክነት እንዲሁም የሥርዐተ ቤተ ክርስቲያን ጥሰት የሚገልጹና ምእመናን በየመግቢያ በሮች ላይ የሰቀሏቸውን ባነሮች እንዲያነሡ ማድረግን በተመለከተ ግለሰቡ ባስያዙት አጀንዳ፣ ከዐቢይ ኮሚቴው ጋራ ተወያይተዋል፡፡ ባነሮቹ ተፈላጊውን መልእክት በማስተላለፋቸው በሚመለከተው መንግሥታዊ መሥሪያ ቤት እንዲነሡ መታዘዙን ግለሰቡ በቅድመ ኹኔታ መልክ ቢገልጹም፤ ባነሮቹ እንደተሰቀሉ እንዲቆዩ የተደረገው፣ ሀገረ ስብከቱ ማጣራት እንደሚጀምር ቃል ከገባ በኋላ ጥር 18 ቀን በፍ/ቤት የሁከት ይወገድልኝ ክሥ በመመሥረቱ እንደኾነ በኮሚቴው አባላት ተነግሯቸዋል፡፡ ከአንድ ሺሕ በላይ የካቴድራሉ ምእመናን የሀገረ ስብከቱን አካሔድ በመቃወም፣ የካቲት 2 ቀን ለቋሚ ሲኖዶስ አቤቱታ አቅርበው አምስት አባላት ያሉት አጣሪ ልኡክ ቢመደብም ሒደቱ በአስቸኳይ ተፈጻሚ ባለመኾኑ ወርዶ የተቀመጠው ባነር ተመልሶ መሰቀሉን አስረድተዋቸዋል፡፡
በዚሁ ዕለት በግለሰቡ ላይ የተመለከቱት ኹኔታ ከብሔራዊ መረጃና ደኅንነት መ/ቤት መምጣታቸውን እንዲጠራጠሩ እንዳደረጋቸው የተናገሩት የኮሚቴው ምንጮች፤ ካቴድራሉ ለሚገኝበት የቦሌ ክ/ከተማ አስተዳደር የጸጥታ አካል ስለጉዳዩ በመጠቆም፣“ደኅንነት ነኝ” የሚሉት አቶ ኃይለ ኢየሱስ ተፈራ በክትትል ውስጥ እንዲገቡ ማድረጋቸውን ገልጸዋል፡፡ መጋቢት 21 ቀን፣ ግለሰቡ ባስያዙት ቀጠሮ መሠረት፣ የሀገረ ስብከቱ ሥራ አስኪያጅ መ/ር ጎይትኦም ያይኑና ሁለት የአስተዳደር ጉባኤ አባላት ከዐቢይ ኮሚቴው ጋራ በጽ/ቤቱ ተገናኝተው ስለማጣራት ሒደቱ አፈጻጸም በተነጋገሩበትም ወቅት ክትትሉ ቀጥሎ እንደነበር ጠቁመዋል፡፡ የማጣራት ሒደቱን ለመጀመር ስምምነት በተደረሰበትና ግለሰቡ በካቴድራሉ ቅጽር በተገኙበት መጋቢት 25 ቀን፣ አስቀድሞ መረጃው ደርሷቸው ሲከታተሏቸው በቆዩ የፖሊስና የጸጥታ አካላት ያለምንም ውዝግብ በቁጥጥር ሥር እንዲውሉ መደረጋቸው ታውቋል፡፡
ግለሰቡ በቁጥጥር ሥር ሲውሉ፣ ከብሔራዊ መረጃና ደኅንነት መ/ቤት ተልከው ስለመምጣታቸው የሚያረጋግጥ ትክክለኛ ማስረጃ ማቅረብ እንዳልቻሉና ደርሶኛል ካሉት የሀገረ ስብከቱ ደብዳቤ ጋር በተያያዘ ሥራ አስኪያጁን መ/ር ጎይትኦም ያይኑን የተመለከተም ምርመራ እየተካሔደባቸው መኾኑን ለማወቅ ተችሏል።
በአ/አበባ ሀ/ስብከት ሥራ አስኪያጅ መ/ር ጎይትኦም ያይኑ ቲተርና ፊርማ ወጪ በተደረገውና ለብሔራዊ መረጃና ደኅንነት መምሪያ የፖሊቲካ ጉዳዮች ጽ/ቤት በተጻፈው የትብብር መጠየቂያ ደብዳቤ፣ ግለሰቡ በካቴድራሉ ተገኝተው ስለጉዳዩ አጭር ሪፖርት እንዲያቀርቡ የሚያዝ ምሪት ተሰጥቶበታል። የመሥሪያ ቤቱን ትብብር በደብዳቤ መጠየቃቸውን ለቦሌ ክፍለ ከተማ ፖሊስ መምሪያ በጽሑፍ በሰጡት ምላሽ ያረጋገጡት ሥራ አስኪያጁ በበኩላቸው፤ የካቴድራሉን ሰላም ለመመለስ ከመጣር ውጪ፣ ግለሰቡን እንደማያውቋቸው፣ ደብዳቤውንና በአባሪነት የተያያዘውን 35 ገጽ ሰነድም ለግለሰቡ እንዳልሰጧቸው ገልጸዋል፡፡
ሀገረ ስብከቱን በበላይነት የሚመሩት ብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርክ አቡነ ማትያስ፤ ባለፈው ሳምንት ኃሙስ ከቀትር በኋላ፣ የካቴድራሉን ወቅታዊ ኹኔታ በተመለከተ በጽ/ቤታቸው ተቀብለው ላነጋገሯቸው የማኅበረ ምእመናኑ ዐቢይ ኮሚቴ አባላት፣ ሥራ አስኪያጁ እና “ደኅንነት ነኝ” ባዩ ግለሰብ አላቸው ስለሚባለው ግንኙነት ማንሣታቸው ተጠቅሷል፡፡“የሁለቱን ግንኙነት ነጥብ በነጥብ ዘርዝረን ለቅዱስነታቸው አስረድተናቸዋል፤” ብለዋል የኮሚቴው አባላት፡፡ ፓትርያርኩም፤ “ደኅንነት ነኝ የሚለው ግለሰብ አሳስቶት ነው ወይስ አምኖበት?” በማለት እንደጠየቋቸውና “ኾን ብለው ተማክረው እንዳደረጉትና ኹሉንም ነገር መ/ር ጎይትኦም እንደሚያውቅ፤ ጉዳዩም በሕግ እንደተያዘና እኛም ፍትሕ እንደምንሻ ገልጸንላቸዋል፤” ብለዋል፡፡
ሀገረ ስብከቱ የመሠረተባቸውን ክሥ፣ የመጀመሪያ ደረጃ ፍ/ቤት ውድቅ ቢያደርገውም፣ የጠየቀው ይግባኝ እንዲቋረጥ ትእዛዝ እንዲሰጡላቸውና ቋሚ ሲኖዶሱ የመደባቸው ልኡካን ማጣራቱን እንዲጀምሩ በአጽንኦት ያመለከቱት የዐቢይ ኮሚቴው አባላት፤ ሒደቱ በመዘግየቱ ከላይ ለተጠቀሱት ዐይነት ትንኮሳዎች እየዳረጋቸው መኾኑን ለፓትርያርኩ አስረድተዋል፡፡ የካቴድራሉ አስተዳደር ሓላፊዎች በሕዝቡ ተቃውሞ ከተባረሩበት ታኅሣሥ 20 ቀን 2010 ዓ.ም. ጀምሮ ሰላሙ ተጠብቆ ዓመታዊና ወርኃዊ በዓላት መከበራቸውን፤ የውስጥ አገልግሎቱና ስብከተ ወንጌሉም ያለአንዳች እንከን እየተከናወነ እንደኾነም ነግረዋቸዋል፡፡ በሦስት ክብረ በዓላት በሙዳየ ምጽዋት የተሰበሰበው ገንዘብ፣ የሀገረ ስብከቱና የክፍለ ከተማ ቤተ ክህነቱ ተወካዮች በተገኙበት የተቆጠረበትን ቃለ ጉባኤና የባንክ ሰነዱን አሳይተዋቸዋል፡፡
“የአስተዳደር ሓላፊዎቹ እያሉ በሁለት የባንክ ሒሳቦች የነበረውን የገንዘብ መጠንና ከእነርሱ በኋላ 1ነጥብ2 ሚሊዮን ብር የሁለት ወራት የካህናት ውዝፍ ደመወዝ ተከፍሎም ከ7 ሚሊዮን ብር በላይ ተቀማጭ እንደሚገኝ በመጥቀስ ቤተ ክርስቲያናችንን እየጠበቅን እንዳለ አስረድተናቸዋል፤”ብለዋል የኮሚቴው አባላት፡፡
ኮሚቴው ባቀረበው የሥራ ክንውን መደሰታቸውን የገለጹት ፓትርያርኩ፣ “ቢሮዎቹን ባታሽጉ ኖሮ አትንከራተቱም ነበር፤ እግዚአብሔር በሚያውቀው እንዲጣራ እፈልጋለሁ፤ ለዚህም ወዲያው መርቼበት ነበር፤” ማለታቸውን የዐቢይ ኮሚቴው ምንጮች ተናግረዋል፡፡ በሀገረ ስብከቱ የተመሠረተውን ክሥ በተመለከተም፣ ጉዳዩ በፍ/ቤት በመያዙ ውሳኔውን እየጠበቁ እንደኾነ ያስታወቁት አቡነ ማትያስ፤ “ለቤተ ክርስቲያን ሲባል ነው የተከሰሣችሁት፤ የፍ/ቤቱ ጉዳይ አይቆምም፤” እንዳሏቸው ተገልጿል፡፡ ከውሳኔው በፊት ተተኪ አስተዳዳሪ መመደብ የማይመልሱት ችግር ውስጥ እንደሚከታቸው ፓትርያርኩ ቢጠቁሙም፣ “ስላለው ነገር ልመካከርበትና እነግራችኋለሁ፤” በማለት የዐቢይ ኮሚቴውን አባላት በቡራኬ እንዳሰናበቷቸው ምንጮቹ አክለው ተናግረዋል፡፡
ደኅንነት ነኝ ባዩን ግለሰብ በቁጥጥር ሥር አውሎ በተለይ በደብዳቤው በተሰጠው ምሪት ላይ ያተኮረ የቴክኒክ ምርምራ እያካሔደ ያለው የቦሌ ክፍለ ከተማ ፖሊስ፤ ተጠርጣሪውን ሁለት ጊዜ ፍ/ቤት አቅርቦ ተጨማሪ የምርመራ ጊዜ ቀጠሮ እንደጠየቀባቸውና ለሦስተኛ ጊዜም የፊታችን ሚያዝያ 25 ቀን ፍ/ቤት እንደሚቀርቡ ታውቋል፡፡ በተያያዘ ዜና፣ በአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት የደብረ ገሊላ ቅዱስ ዐማኑኤል ካቴድራል የትሩፋት(ነፃ) አገልጋይ የኾኑ ዲያቆን፣ ወደ ቢሮ ሥራ ለመመደብ በሚል ለሥራ አስኪያጁ መ/ር ጎይትኦም ያይኑ 100ሺሕ ብር ጉቦ መስጠታቸውን፣ ከግለሰቡ የተገኘው ማስረጃ አጋለጠ፡፡ ፈቀደ ተስፍዬ የተባሉት አገልጋዩ፣ በአንድ የግል ባንክ በተከፈተ የሥራ አስኪያጁ የቁጠባ ሒሳብ፣ ባለፈው ዓመት ሐምሌ 4 ቀን 2009 ዓ.ም. ገንዘቡን እንዳስገቡ፣የገቢ ማዘዣ ሰነዱ(Cash Deposit Voucher) ያረጋግጣል፡፡
በአካውንቲንግ ሞያ በብድርና ቁጠባ ተቋም እንደሠሩና በካቴድራሉ ከ15 ዓመታት ያላነሰ በደጀ ጠኚነት በዲቁና እንዳገለገሉ የሚናገሩት ግለሰቡ፤ ምደባ የጠየቁበት የቢሮ ሥራ፣ ሒሳብ ሹምነት እንደኾነ ተጠቁሟል፡፡ ኾኖም እጅ መንሻ የሰጡበትና በአንድ ከፍተኛ የካቴድራሉ ሓላፊ አማካይነት ለማስፈጸም የሞከሩትን ምደባ በመካከላቸው በተፈጠረ አለመግባባት ምክንያት ባለማግኘታቸው፣ ገንዘባቸውን ባለፈው ማክሰኞ በሓላፊው አማካይነት ማስመለሳቸው ታውቋል፡፡
በአጥቢያ አብያተ ክርስቲያናት የሠራተኞች ቅጥር የሚፈጸመው ጥያቄው በአድባራት ሲቀርብ፣ በሀገረ ስብከቱ እንደኾነና አሠራሩም የቅጥር ኮሚቴ በማዋቀርና ማስታወቂያ በማውጣት በውድድር እንደሚፈጸም፣ ባለፈው መጋቢት አጋማሽ ከአዲስ አድማስ ጋራ ቃለ ምልልስ ያደረጉት ሥራ አስኪያጁ መ/ር ጎይትኦም ያይኑ መግለጻቸው ይታወሳል፡፡ ከአሠራሩ ውጭ የሠራተኛ ቅጥር “አልፎ አልፎ የሚፈጸመው” በአድባራቱ እንደኾነና ከአቤቱታ አቅራቢዎች ጋር አለመግባባት የሚፈጠርበት አንድ መንሥኤ እንደኾነም መናገራቸው አይዘነጋም፡፡
ሥራ አስኪያጁ ይህን ይበሉ እንጅ፣ ከደብረ ገሊላ ቅዱስ ዐማኑኤል ካቴድራል ነፃ አገልጋይ ቅጥር ጋር በተያያዘ አስተያየት የሰጡ ምንጮች፤ “ከአጥቢያ አብያተ ክርስቲያናት እስከ ሀገረ ስብከቱ ሹማምንት ድረስ በተለይ ለጽ/ቤት ሓላፊዎች ቅጥርና ዝውውር የተዘረጋውን የሙስና ሰንሰለትና የሚያካብቱትን ሕገ ወጥ ሀብት የሚያረጋግጥ ነው፤” ብለዋል፡፡ የማስረጃ ሰነዱ ለብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርኩ መድረሱን ያመለከቱት ምንጮቹ፤ በሰነዱ ትክክለኛነትና ሌሎች ተያያዥ ጉዳዮች ላይ ማጣራቱ እንደተጠናቀቀ አስተዳደራዊና ሕጋዊ ርምጃ ይወሰዳል ተብሎ ይጠበቃል፤ ብለዋል፡፡


             “የበላይ ባለስልጣናት በፈፀሙት ወንጀል እኛ ዋጋ እየከፈልን ነው”
            
      ባለፈው ሐምሌ ወር በተካሄደው የፀረ ሙስና ዘመቻና በተለያዩ ጊዜያት በልዩ ልዩ የሙስና ወንጀሎች ተከሰው ጉዳያቸው በፍ/ቤት እየታየ የሚገኘው 152 ተከሳሾች፤ ፍትህ ይሰጠን የሚል አቤቱታቸውን ለጠቅላይ ሚኒስትሩ አቀረቡ፡፡
ጉዳያቸው በፍ/ቤት ቀጠሮ ላይ የሚገኘው እነዚህ የሙስና ወንጀል ተከሳሾች፤ ለጠቅላይ ሚኒስትር ዶ/ር አብይ አህመድ እንዲቀርብላቸው የላኩት የ152 እስረኞችን ፊርማ ያካተተ የአቤቱታ፤ ደብዳቤ ሲሆን ለጠቅላይ ሚኒስትሩ እንዲደርስ በፌደራል ማረሚያ ቤቶች አስተዳደር ለፍትህ ዳይሬክቶሬት ዳይሬክተር ተመርቶላቸዋል፡፡
ተከሳሾቹ፤ በዚህ አቤቱታቸው ላይ እንደገለፁት፤ የሙስና ወንጀል ሳንፈፅም ለፖለቲካ ፍጆታ ሲባል የታሰርን ሰዎች በመሆናችን ጠቅላይ ሚኒስትሩ ከሌሎች ከሚመለከታቸው አካላት ጋር በመሆን ፍትህ እንድናገኝ ሊያደርጉን ይገባል ብለዋል፡፡ “ትልልቆቹና ዋንኞቹ አሳዎች በሰሩት ሙስና እኛ ዋጋ ከፋይ ልንሆን አይገባም” ያሉት እነዚሁ ተከሳሾች፤ “አብዛኛዎችን የራሳችን የሆነ ምንም ነገር የሌለን በኪራይ ቤት የምንኖርና በወንጀል ሥራ ውስጥ ተሳትፎ ያላደረግን ሰዎች ነን” ብለዋል፡፡ አቤቱታ አቅራቢዎቹ ዘመቻው የፖለቲካ መሆኑን ጠቁመው፤ ያለበቂ ማስረጃ ክስ ቀርቦባቸው ያለአግባብ እየተሰቃዩ መሆኑን በአቤቱታቸው ላይ ገልፀዋል፡፡ ፍርድ ቤቶች ያለ ተፅዕኖ በነፃነት ፍትህ እየሰጡን አይደለም ያሉት አቤቱታ አቅራቢዎቹ “ያለ ስራችን እጅግ አሳፋሪና ሞራላችንን የሚነካ ሙሰኞች የሚል ስም ተሰጥቶን በእስር እየተሰቃየን እንገኛለን፡፡ ስለዚህም ፍ/ቤቱ ነፃ ሆኖ የሚገባንን ፍትህ ይሰጠን ዘንድ እንጠይቃለን” ብለዋል፡፡
እነዚሁ አቤቱታ አቅራቢዎች በአቤቱታቸው ላይ እንደገለፁት፤ “አቃቤ ህግ ያለፍርድ ቤት ትዕዛዝ አወጣሁ በሚላቸውና ትክክለኛውን የፍትህ ሂደት ባልጠበቁ የተለያዩ ማስረጃዎች ማቅረብ ሰበብ የማይገባንን ዋጋ እየከፈልን በመሆኑ ጠቅላይ ሚኒስትሩ ከሚመለከታቸው አካላት ጋር በመሆኑን ለአቤቱታችን አፋጣኝ ምላሽ ይሰጡን ዘንድ እንጠይቃለን” ሲሉ ተማፅነዋል፡፡


             “ለመለወጥ የተዘጋጀ አዲስ አመራር ነው የገጠመኝ”

    የተባበሩት መንግስታት የሰብአዊ መብት ኮሚሽን ከፍተኛ ኮሚሽነር ዛይድ አል ሁሴን፤ በኢትዮጵያ በነበራቸው የሦስት ቀናት ጉብኝት ከእስር ከተፈቱ ፖለቲከኞች፣ ጋዜጠኞችና ሲቪል ማህበራት አመራሮች እንዲሁም አባ ገዳዎች ጋር በአገሪቱ የሰብአዊ መብት አያያዝ ላይ መነጋገራቸው ታውቋል፡፡
ከፍተኛ ኮሚሽነሩ ከእስር ከተፈቱ ተቃዋሚ ፖለቲከኞች፣ጋዜጠኞች፣ጦማሪያን፣የዋልድባ መነኮሳትና ከሙስሊሙ መፍትሄ አፈላላጊ ኮሚቴ አባላት ጋር  ባደረጉት ውይይት፣ በእስር ቤቶች ውስጥ ስለሚፈጸሙ የመብት ጥሰቶች ተነግሯቸዋል፡፡ በውይይቱ ላይ ተሳታፊ የነበረው  ጋዜጠኛ እና የሰብአዊ መብት ተሟጋቹ እስክንድር ነጋ፤በኢትዮጵያ ውስጥ የሚፈፀሙ የሰብአዊ መብት ጥሰቶች አሰቃቂ እንደሆኑ ኮሚሽነሩ መረዳታቸውን  ጠቁሟል፡፡ ኮሚሽነሩ በሀገሪቱ ስለሚፈጸሙ የሰብአዊ መብት ጥሰቶች ብቻ ሳይሆን  በቀጣይ እንዴት ጥሰቶቹን ማስቀረት ይቻላል በሚለውም ላይ ከተሳታፊዎች ጋር እንደመከሩ ለማወቅ ተችሏል፡፡
በሀገሪቱ የሚፈፀሙ የሰብአዊ መብት ጥሰቶች ከምንጫቸው ሊደርቁ የሚችሉት ጠ/ሚኒስትር ስለተቀየረ ወይም አዲስ ካቢኔ ስለተቋቋመ አሊያም ማዕከላዊ ስለተዘጋ ሳይሆን በአጠቃላይ ዲሞክራሲያዊ ስርአት ሲረጋገጥ መሆኑን  መግባባት ላይ መደረሱን የውይይቱ ተሳታፊዎች ለአዲስ አድማስ ገልፀዋል፡፡
“በተቃውሞ ላይ በመሳተፋቸውና መንግስት ላይ ከሰነዘሩት ትችት ጋር በተያያዘ ታስረው የነበሩ ጦማርያንን ጨምሮ በርካታ ቁጥር ያላቸው ተቃዋሚ ፖለቲከኞችና ሌሎችም ከእስር መለቀቃቸውን እንደሚያደንቁ የገለጹት ዛይድ አል ሁሴን፤በዚህ ጉብኝታቸውም ከጥቂቶቹ ጋር በግል ለመነጋገር ዕድል ማግኘታቸውንም ጠቁመዋል፡፡  
በኦሮሚያ ከክልሉ ባለሥልጣናትና አባ ገዳዎች ጋር ተገናኝተው መነጋገራቸውን የገለጹት ከፍተኛ ኮሚሽነሩ፤ከክልሉ ባለሥልጣናትና አባ ገዳዎች ጋር የተደረገውን ይህን የመጀመሪያ ግንኙነት መንግስት በማመቻቸቱ ምስጋና አቅርበዋል፡፡ አባ ገዳዎች በክልሉ ያልተመጣጠነ ሃይል በመጠቀም በዜጎች ላይ ግድያ የፈጸሙ ወገኖች ተጣርተው፣ ለህግ እንዲቀርቡና የሁሉም ኢትዮጵያውያን ሰብአዊ መብቶች እንዲከበር መጠየቃቸውንም የጠቀሱት ኮሚሽነሩ፤በክልሉ ለረዥም ዘመን የዘለቀውን የሰብአዊ መብት ችግሮች ከአዲሱ አመራር ጋር በመሥራት እንፈታዋለን ብለው ተስፋ እንደሚያደርጉ  ገልጸውልኛል ብለዋል፡፡ ከጠ/ሚኒስትር ዐቢይ ጋር በአገሪቱ የሰብአዊ መብት አያያዝ ጉዳይ ላይ ያደረጉት ውይይትም ውጤታማና ተስፋ ሰጪ ነው ብለዋል- ኮሚሽነር ዛይድ አል ሁሴን፡፡
የተባበሩት መንግስታት የሰብአዊ መብት ኮሚሽን ቢሮም፣ በኦሮሚያና አማራ ክልሎች  የተፈጸሙ የሰብአዊ መብት ጥሰቶችን መመርመር እንደሚፈልግ ያስታወቁት ከፍተኛ ኮሚሽነሩ፤ይህም የሰብአዊ መብት አያያዝን የተሻለ ለመገምገም፣መንግስት የዲሞክራሲ ምህዳሩን ለማስፋትና  ለሰብአዊ መብት ጥሰቶች ተጠያቂነትን ለማስፈን በሚያደርጋቸው ጥረቶች ለማገዝ የሚያስችል ይሆናል፡፡” ብለዋል፡፡
በተመሳሳይ ኮሚሽነሩ ከውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ዶ/ር ወርቅነህ ገበየሁ፣ ከኢትዮጵያ ሰብአዊ መብቶች ኮሚሽን ኮሚሽነር ዶ/ር አዲሱ ገብረ እግዚአብሄር እንዲሁም ከጠ/ሚኒስትር ዶ/ር አብይ አህመድ ጋር በሀገሪቱ የሰብአዊ መብቶች ይዞታ ላይ የመከሩ ሲሆን የተባበሩት መንግስታት ድርጅት የሰብአዊ መብት ኮሚሽን የምስራቅ እና ደቡብ አፍሪካ 17 አገሮችን የሚሸፍን ፅ/ቤቱን በአዲስ አበባ ለመክፈት ከኢትዮጵያ መንግስት ጋር  ስምምነት ተፈርሟል፡፡
የተመድ የሰብአዊ መብት ኮሚሽን ከፍተኛ ኮሚሽነሩ ዛይድ አል ሁሴን፣ የኢትዮጵያ ጉብኝታቸውን አጠናቅቀው  ለውጭ መገናኛ ብዙኃን በሰጡት መግለጫ፤”በኢትዮጵያ ለመለወጥ የተዘጋጀ አዲስ አመራር ነው የገጠመኝ” ብለዋል፡፡

 ደራሲ ከበደ ሚካኤል ከፃፏቸው አስገራሚ ተረቶች መካከል የሚከተለው ተረት ደጋግሞ ቢነገር እንኳ የማይሰለችና ትምህርታዊ ተምሳሌት ነው፡፡
አንድ ፈረሰኛ ወደ አንድ ከፍተኛ ተራራ ይጓዝ ነበር፡፡ ወደ ተራራው ወገብ ላይ ሲደርስ አንድ ምስኪንና አንድ እግሩ ሽባ የሆነ ሰው እንዳቅሙ ቋጥኙን እየቧጠጠ ለመውጣት ሲፍጨረጨር ያገኛል፡፡
ፈረሰኛው፤
ወዳጄ፤ ይህን የሚያህል ተራራ እንዲህ ተንፏቀህ የሚገፋ አይደለም፡፡ ስለዚህ እንደምንም ፈረሴ ላይ ላውጣህና አፈናጥጬ ዳገቱ ጫፍ ላይ ላድርስህ?
ሰውዬው፤
እግዚአብሔር የባረከህ ሰው ነህ! ግን ሥጋቴ እንዳላጣብብህ ነው፡፡ ለማፈናጠጥ ይበቃል ብለህ ነውን?
ፈረሰኛው፤
እንደምንም ተጣበን እንወጣዋለን እንጂ በዚህ ሁኔታ በፍፁም ጥዬህ ብሄድ ግፍ ይሆንብኛል፡፡ ሰው እንኳ ባይኖር ተራራውም ይታዘበኛል፡፡ ስለዚህ ና ውጣ ግዴለህም፡፡
ሰውዬው፤
ፈጣሪ ምስክሬ ነው፤ ለእኔ የተላክ ውድ አዳኝ መልዐክ ነህ፡፡ አምላክ ውለታህን ይክፈልህ!
ፈረሰኛው ተሸክሞ ፈረሱ ላይ አስቀመጠውና ተራራውን ተያያዙት፡፡ ጥቂት እንደሄዱ ግን፤
ሰውዬው
ወዳጄ፤ ቅድም እንደፈራሁት በጣም ተጣበናል፡፡ ብወርድልህ ይሻላል፡፡
ፈረሰኛው፤
እንደሱማ አይሆንም፡፡ ባይሆን የተወሰነውን ዳገት እኔ በእግሬ ልሞክረው፤ አንተ ፈረሱን ያዝ አለውና ፈረሱን ሰጥቶት ወረደ፡፡ ሰውየው እየጋለበ ዳገቱን እየወጣ እየራቀ ሄደ፡፡
ፈረሰኛው በእግሩ ዳገቱን ተያያዘው፡፡ ሆኖም ባለፈረሱ እየራቀ ሄደ፡፡ ፈረሰኛው ሥጋት እየገባው በተቻለው ፍጥነት ሊከተለውና ሊጠጋው ቢሞክርም ሰውዬው ፈረሱን ይብስ አፈጠነው፡፡
ፈረሰኛው መጣራት ጀመረ፡፡ ወይ የሚለው ግን አጣ፡፡ ሰውዬው ፈረሱን ይዞ ሊጠፋ መሆኑ ለፈረሰኛው ገባው፡፡
“አንተ ሰው፤ ግዴለም ፈረሱን ይዘኸው ትሄዳለህ፡፡ ግን አንድ ነገር ቆም ብለህ ስማኝ እባክህ፡፡ እንደማልደርስብህ ታውቃለህ፡፡ ጆሮህን ብቻ አውሰኝ?” ሲል ለመነው፡፡
ሰውዬው ርቀቱን በደንብ ካረጋገጠ በኋላ፤
“እሺ ምንድነው ልትነግረኝ የፈለከው?”
ፈረሰኛውም፤
“ወዳጄ፤ መቼም አንድ ቦታ ወርደህ ከሰው መቀላቀልህ አይቀርም፡፡ አደራህን ይሄን አሁን እኔን የሰራኸኝን ነገር ለማንም ሰው እንዳትነግር፡፡ አለበለዚያ ደግ የሚሰራ ሰው ይጠፋል!”
*   *   *
የሚያጪበጭቡልን፣ የሚያሞግሱን፣ የሚያወድሱን ሁሉ ደግ ላይሆኑ እንደሚችሉ አንርሳ! ሰዎች ለችግራቸው የደረሰላቸውን ሰው እንኳ ውለታውን መመለስ ቀርቶ ጭራሹን ተንኮል ሊሰሩበት፣ ግፍ ሊውሉበት ይችላሉ፡፡ ደግ የሚሰራ እንዳይጠፋ የሰራነውን ክፉ ነገር ለሰዎች ባንነግር መልካም ነው፡፡ አገራችን ኢትዮጵያ የብዙ ችግር ባለቤት ናት፡፡ የብዙ ፀጋም ባለቤት ናት፡፡ ከእነ ችግሮቹ ሀገሩን አሳቢ ብዙ ንቁ ዜጋ፣ ብዙ ልባም ሰው፣ ብዙ የተማረ፣ አስተዋይና አገር ሊለውጥ የሚችል አዋቂ አላት፡፡ እንዲህ ዓይነቱን ሰው በዲዮጋን ፋኖስም ቢሆን ፈልጎ ማግኘት ተገቢ ነው፡፡ ሰዓሊ ገ/ክርስቶስ ደስታ ብራውኒንግን ጠቅሶ እንደፃፈው፤
“… ደግሞም፤ ማወቅ ማለት፤
ከውጪ ያለውን ሄዶ ከመፈለግ
ከውስጥ የበራውን እንዲወጣ ማድረግ”
… ወቅታዊነት ያለው ጥበብ ነው፡፡
ሀገራችን የብዙ ካህናት፣ የአያሌ ጠቢባን፣ የበርካታ አበው ፈላስፎች አገር ሆና ሳለ፤ የትምህርት ሥርዓቷ እየተዳከመ፣ ምሁር ማፍራቷ እየተመናመነ መምጣቱ ቢያንስ ሊያስቆጨን የሚገባና አንገብጋቢ ጉዳይ መሆኑን መረዳት ይጠበቅብናል፡፡ የትምህርት ድክመት የሀገርን ድክመት የሚጠቁም ከባድ የመከራ ደወል ነው፡፡ ባለሙያ የምናፈራው ከዚህ የዕውቀት ማሳ ነው፡፡ “ኩሉ አመክሩ ወዝሰናየ እፅንዑ” (ሁሉንም ሞክሩ የተሻለውን አፅኑ) የሚለው የጥንቱ ዲግሪ ላይ የተፃፈው መልዕክት፤ ተምረን በየአቅጣጫው ጥረት ማድረግና አገርን የማሳደግ አደራ እንዳለብን ጠቋሚ ጥቅስ ነበር፡፡፡ አሁንም በነበር መቅረት ያለበት ሀሳብ አለመሆኑን ማስተዋል ይጠበቅብናል! መንገዱ መኖሩን እያየን አላየንም ማለት ሐጢያት ነው፡፡ መማር እየቻልን አለመማርም ሐጢያት ነው፡፡ ለሐጢያታችን ሥርየት የምናበጀው ዕውቀት ሲኖር ነው፡፡ አገር የምትድነው በአዋቂዎቿ የተከፈተ ዐይን ነው፡፡
“ይቺን ጨቅላ መጥሐፍ የምታነቡ ሁሉ
አደራ ስለኔ ማርያም ማርያም በሉ፡፡
ከሃያ ስድስቱ ወንዶች ፊደላት
አርግዣለሁና መዝገበ - ቃላት
ከሆዴ ያለውን የትምህርት ሽል
ያለጭንቅ እንድወልድ እንድገላገል!
ስንት እልፍ አበው ናቸው አርግዘው የሞቱ
ቀኝ እጃቸው አጥሮ ፊደል በማጣቱ
ለትምክህት አይደለም ይህን መናገሬ
ለማስቀናጠ እንጂ ሰነፉን ገበሬ!
ሐዋርያው ሲናገር ወደ ምዕመናኑ
ለምትበልጥ ፀጋ ይላል ቅኑ አስቀኑ”
በተባለባት አገር የትምህርት ደሀ ልትሆን አይገባም፡፡ መልሰን ራሳችንን ለመፍጠር መፍረምረም አለብን። ብልሃቱንና መላውን ካበጀን የማንወጣው ዳገት አይኖርም፡፡ እጅ ለእጅ ከተያያዝን፣ አዕምሮ ለአዕምሮ ከተናበብን፤ መሻሻል ግዴታችን ይሆናል፡፡
ሁሉንም አዳርሰን ስናበቃ እያንዳንዱን በተናጠልና በጥበብ ካቀድን፣ ለሀገር ቅጥ ቅጥ ማበጀት አያቅተንም። መልካም እንሰራለን ያልነው ሁሉ ላይሳካ ቢችልም፤ ለዛም መዘጋጀት አንድ መልካም ነገር ነው፡፡ ሁሉንም ሰው እናረካለን ብለን አናስብ፡፡ ፈረንጆቹ፤ “To satisfy all is to satisfy none” የሚሉት ወደው አይደለም - ዕውነትም “ሁሉንም ለማርካት መሞከር ማንንም አለማርካት ነው!”