Administrator

Administrator

Sunday, 29 April 2018 00:00

አፍታ ለማለፊያዎቻችን

       የሥነ-ጥበብን ውስጥ ውስጡን ለመመርመርና ለማድነቅ ይቅርና ላይ ላዩንም ለመነካካት ቸልታ ከሚያሳይ ማኅበረሰብ የፈለቁት የሃገራችን ሠዓልያንና የሥነ-ጥበብ ማኅበረሰቡ፣ለሠፊው የኢትዮጵያ ሕዝብ “ባርጤዛ” ሆነው ቆይተዋል። ሆኖም ሠዓሊውና የሥነ-ጥበብ ማኅበረሰቡ ይህ ተቃርኖ መኖሩን ፈጽሞ የማያውቅ እስኪመስል ለሙያው ባለው ልባዊ ፍቅርና ጽናት፣ ድንበሮቹን እየገፋ፣ ጭላንጭል ለውጦችን የሚያይበት ጊዜ እየመጣ ይመስላል፡፡ እዚህ ላይ በተለይ መንግስት ለሥነ-ጥበብ ያለው ጥልቅ ዝንጋዔ መቼ ሊሻሻል እንደሚችል ግምትም ሆነ መላምት ለማስቀመጥ አዳጋች ነው፡፡ እንዲህ ድንግዝግዝ ባለ ሁኔታ ስለ ሥነ-ጥበብ ማሰብና ማለም ደግሞ የጥበብ ልግስና ነውና ደስ ያሰኛል፡፡ ከላይ የጠቀስኩት ተቃርኖን የሚቃረን መልክ ባለው ገጽ ደግሞ የሃገር ባለ ውለታ የሆኑ አያሌ ሠዓልያን የሚገኙባት ሃገር ውስጥ መኖራችን የሚያስገርም ነው፡፡ ይህ ተለቅ ሲል ደግሞ እነዚህ የሃገር ባለ ውለታ የሆኑ ሠዓልያንን ያፈራ ታላቅና አንጋፋ ት/ቤትን እናገኛለን፡፡ ይህ ት/ቤት እንደ ተቋም በመንግስት ቢተዳደርም፣ ሕልውናው የተመሰረተውና የጸናው ግን ለሙያው ፍቅርና ቦታ ባላቸው ታላላቅ ሠዓልያን መስዋዕትነት ነው። ይሄ ደግሞ ማንኛውንም ኢትዮጵያዊ እንደ ዜጋ የሚያኮራ፣ መንፈስና ነብስን የሚያጠግብ እንዲሁም የሕሊና ምቾት የሚሰጥ ነው፡፡ የዚህ አጭር ጽሁፍ ዓላማ በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ አለ የሥነ-ጥበብና ዲዛይን ት/ቤት ውስጥ ለረዥም ዘመናት ያስተማሩትንና በቅርቡ ያረፉትን ቀራጺ ታደሰ በላይነህን በጣም በጥቂቱ ለማውሳት ነው፡፡
ቀራጺ ታደሰ በላይነህ ባጋጠማቸው ሕመም ለሶስት ወራት ህክምና ሲከታተሉ የነበሩ ሲሆን መጋቢት 29 ቀን 2010 ዓ.ም እስኪያርፉ ድረስ በት/ቤቱ ለሃምሳ ዓመታት በመምህርነት አገልግለዋል። እነዚህ ሃምሳ አመታት የማስተማር ብቻ ሳይሆን ሃገራችን የሥነ-ጥበብ ሙያተኞችን እንድታገኝ የማስቻል ኃላፊነትንም የሚጨምር ነበር፡፡ ለአስተዋጽኦዋቸው የሚመጥን ብሔራዊ እውቅና ባይቸራቸውም ባለፈው ሃሙስ በት/ቤቱ የመታሰቢያ ዝግጅት ተሰናድቶ የተዘከሩ ሲሆን ያስተምሩበት የነበረው አንዱ ስቱዲዮም በስማቸው ተሰይሟል፡፡
በቀድሞ ስያሜው የአዲስ አበባ ሥነ-ጥበብ ት/ቤት በመባል የሚታወቀው ይህ ተቋም የተመሰረተው ከስድሳ ዓመት በፊት ሲሆን ቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ በልደታቸው ቀን ሐምሌ 16 ቀን 1950 ዓ.ም ነበር መርቀው የከፈቱት፡፡ የትምህርት ቤቱ መስራች አሁን በስማቸው የሚጠራው ሠዓሊ አለ ፈለገሰላም ሕሩይ ሲሆኑ ትምህርት ቤቱ ተማሪዎችን ማስመረቅ ብቻ ሳይሆን ከተመረቁም በኋላ ወደ ውጪ ሃገራት በመላክ፣ ተምረው ሲመለሱም በትምህርት ቤቱ በመምህርነት እንዲቀጥሉ እድል መክፈት ችሏል፡፡ በዚህ እድል ተጠቃሚ ሆነው ወደ ቀድሞ ሶቭየት ሕብረት በማቅናት ትምህርታቸውን በLeningrad Repin Academy of Art ኪነ-ቅርጽ ያጠኑትና ወደ ሃገር ተመልሰውም በትምህርት ቤቱ ማስተማር ከጀመሩት ቀደምት መምህራን አንደኛው ታደሰ በላይነህ ናቸው፡፡
ጋሽ ታደሰ በላይነህ ከመምህርነታቸው ባሻገር በሙያቸው የተለያዩ ግልጋሎቶችን አበርክተዋል። በአዲስ አበባና በተለያዩ ክፍለ ሃገራት በሚገኙ አብያተ ክርስቲያናት ቅርጾችን የሰሩ ሲሆን በጎላ ሚካኤልና በየካ ሚካኤል የሰሯቸው ተጠቃሾች ናቸው፡፡ በዩጎዝላቪያ FORMA VIVA በተሰኘው የዓለም ቅርጻ-ቅርጽ አዋቂዎች ድርጅት ባደረጉት ተሳትፎና በቆይታቸው በሰሩት ስራም የዲፕሎማ ሽልማት ተበርክቶላቸዋል፡፡
በአለ የሥነ-ጥበብና ዲዛይን ት/ቤት ከ1983 እስከ 1989 የኃላፊነት ቆይታቸውም፤ ትምህርት ቤቱን በዳይሬክተርነት የመሩ ሲሆን ተቋማዊ የኔነት እንደነበራቸውም በመታሰቢያቸው ላይ በሰፊው ተወስቷል፡፡ ለትምህርት ቤቱ ተማሪዎችና መምህራን የመማሪያና የመስሪያ ስቱዲዮዎችን በማስገንባት ት/ቤቱ ወደ ከፍተኛ የትምህርት ተቋምነት እንዲሸጋገር የተጀመረውን ትግል አጠናክረው በመቀጠል አዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲን እንዲቀላቀል ከፍተኛውን ድርሻ እንደተወጡ ተባባሪ ፕሮፌሰር በቀለ መኮንን ገልጸዋል፡፡  
በሌላ በኩልም ጋሽ ታደሰ በላይነህ፤ የእንጦጦ ቴክኒክና ሙያ ኮሌጅ ሲቋቋም፣ ምስረታውን በማገዝና አስፈላጊውን ሙያዊ ድጋፋቸውን በመቸራቸው የሚወሱ ታላቅ የሃገር ባለውለታ ናቸው፡፡ ጋሽ ታደሰ በላይነህ ካጠኗቸውና በአደባባይ ላይ ሊቀመጡ ከሚገቡ ቅርጾች መካከል የአጼ ቴዎድሮስ ኪነ-ቅርጽ እንደሚገኝበት የጠቆሙት ረዳት ፕሮፌሰር አበባው አያሌው፤ በከተማችን ስለሚገኙና በውጭ  ዜጎች ስለተሰሩት ኪነ-ቅርጾች መሰረት ያለውና የተብራራ እውቀት እንደነበራቸውም  አውስተዋል፡፡
ይህች አፍታ እንደ ቀራጺና መምህር ጋሽ ታደሰ በላይነህ ያሉ ባለውለታዎቻችንን ለመዘከር እጅግ ቁንጽል ብትሆንም ጊዜና እርጋታው ተገኝቶ የሥነ-ጥበብ ታሪካችንን ለማጥናትና ለመሰነድ፤ የሥነ-ጥበብ ፍቅርና አክብሮት የሚኖረው ትውልድ ለመፍጠር የሚያስችሉ ጥረቶች በመንግስትና ሌሎች አጋዥ የማኅበረሰብ ክፍሎች እስኪጎለብቱ፣ማለፊያ የሆኑ ሥነ-ጥበባዊ ማንነቶችን ማውሳቱ ተገቢ ነው፡፡

Sunday, 29 April 2018 00:00

ድማሚት (1+1=3)

 የአንዳንድ መጽሐፍ አርዕስቶች ለየት ማለት ቀልብ ይስባል፡፡ ይኼ አንዱ ነው ብዬ አምናለሁ፡፡ የሽፋኑ አርእስት በአሀዝም በፊደልም ‹‹አንድ ሲደመር አንድ እኩል ይሆናል ሶስት›› ነው የሚለው፡፡ ONE PLUS ONE EQUALS THREE. ጸሐፊው DAVE TROTT ስለ መጽሐፉ ፋይዳ በመግቢያ ገጹ ላይ ያሰፈረው አጭር ማስታወሻም...
which is the point of this book.
under the old system 1+1=2
 under the new system 1+1=3
በነባሩ ስሌት ውጤቱ ሁለት የነበረው፤ በአዲሱ አተያይ/ቀመር ሦስት ሲሆን እንደ ማለት፡፡
 1. HERD THINKING - መንገኝነት
ከጥቂት ዓመታት በፊት አፍሪቃ (ኮንጎ) ውስጥ ለማረፍ ያኮበኮበ አይሮፕላን በድንገት ተከሰከሰ፡፡ አንድ ተሳፋሪ ብቻ ተርፎ ወደ ሆስፒታል ሲወሰድ፣ ሌሎቹ ሀያ ተሳፋሪዎችና ሁለቱ አብራሪዎች ህይወታቸው አለፈ፡፡ አይሮፕላኑ ዘመናዊና በቴክኒክ አቋሙ የተሟላ፣አብራሪዎቹ በቂ ልምድና ብቃት ያላቸው፣ የአየር ንብረት ሁኔታው ለበረራ በጣም አመቺ ስለነበር የአደጋውን መንስኤ ለማወቅ በጣም አስቸገረ። በመጨረሻም ተርፎ ሆስፒታል የገባውን ሰው መጠየቅ ግድ ሆነ፡፡
ሰውየው ሲመሰክርም፤ ከተሳፋሪዎቹ መካከል አንዱ በድብቅ ትንሽዬ አዞ ይዞ ገብቶ ነበር፡፡አይሮፕላኑ ለማረፍ ሲያዘቀዝቅ አዞው ከነበረበት ቦርሳ ወጣ፡፡ ተሳፋሪዎቹ ሲያዩት በፍርሀት እየተንደረደሩ ወደ አብራሪዎቹ አቅጣጫ መነባበር ያዙ፡፡ ካፒቴኑ ባሉበት እንዲቆዩ ትእዛዝ ቢሰጥም ሰሚ አጣ፡፡ አይሮፕላኑ አፍንጫውን ቁልቁል ወደ መሬት ባደረገበት በዚያ ቅጽበት፤ ተሳፋሪዎቹ ሁሉ ባንድ ላይ ተሰባስበው ወደፊት ስለመጡ ሚዛኑን ስቶ ክፉኛ ባፍጢሙ ተከሰከሰ፡፡
ሚጢጢው አዞ በማንም ላይ አደጋ ለማድረስ የማይችል ገና ለአቅመ አዞነት ያልደረሰ መሆኑን ለማስተዋል ፋታ የወሰደ አልነበረም፡፡ የችግሩ ዋንኛ መንስኤም ይኸው ነበር - ከተሳፋሪዎቹ መካከል አንዳቸውም በተለየ መንገድ ማሰብ አለመቻላቸው፡፡ አንዱ ያደረገውን ኮርጆ ሌላውም ስለቀጠለበት ለከፋ አደጋ ተጋለጡ፡፡
በአለም ላይ ለሚከሰቱ የመከራና ሰቃይ፣ ጦርነት፣ ሽብር፣ ጅምላ ጭፍጨፋ . . .ወዘተ መነሻ ፍርሀት የሚፈጥራቸው አጉል ውሳኔዎች ናቸው፡፡ መላው ዜጋ ብቻውን እንደተተወ፣ባይተዋርነት፣ የመገለል ስሜት ሲያድርበት፤ከሌላ እንደሱ በፍርሀት ቆፈን ውስጥ ካለ ዜጋ ጋር መሆንን ምርጫው ያደርጋል፡፡ ፍርሀት አመክንዮን፡እንዴትና ለምን ብሎ መጠየቅን፣ምክንያታዊነትንና ማመዛዘንን ሁሉ ነጥቆ በስሜታዊነት ይነዳል፡፡ ለዚህም ነው ጥርስን ነከስ ሀሞትን ዋጥ ማድረግን የሚጠይቀው ውሳኔ በቁርጥ ቀን ላይ ግድ ይላል መባሉ፡፡ ከመንጋው መካከል ነጠል ብሎ በግል በራስ መወስን ለመቻል፡፡
ባለቅኔው  እንዲል...
ከሰው መንጋ እንገንጠል
ላንዳፍታ እንኳ እንገለል
በእፎይታ ጥላ እንጠለል... እንዲል ባለቅኔው
2. MOTIVATION - ማፋፋም
ቢል ሻንክሊ የሊቨርፑል ቡድንን ተጫዋቾች በከፍተኛ የአሸናፊነት መንፈስ ቅስቀሳ በማድረግ ከሁለተኛ ዲቪዚዮን አውጥቶ ወደ አንደኛ ዲቪዚዮን ወሰደው፡፡ አሁንም እያነሳሳ የዲቪዚዮኑ አሸናፊ አደረጋቸው፡፡ በእንግሊዝ ውስጥ ምርጥ ቡድን እንዲሆኑ አራገባቸው - ሆኑ፡፡ ቀጥሎም በአውሮጳ ዙሪያ ግጥሚያ በማድረግ ድል እንዲቀዳጁ አቀጣጠላቸው - ድል በድል ሆኑ፡፡ በ1965 የጀርመን አሸናፊ ከነበረው EC Cologne ቡድን ጋር ተጋጠሙ፡፡ ኮሎኝ ውስጥ አሸነፉ፡፡በመልስ ጨዋታውም ራሳቸው ሜዳ ላይ እንዲሁ፡፡ እናም በመጨረሻው ወሳኝ ግጥሚያ ከሁለቱም ሜዳ ውጪ ሮተርዳም ውስጥ ፍልሚያ የሚሰኝ ግጥሚያ አድርገው፣ በተጨማሪ ሰአት አሸነፉ እና ስማቸው ገነነ፡፡ ቡድኑም ወደ ኢንግላንድ ተመለሰ፡፡ ከሦስት ቀናት በኋላ ከቼልሲጋ ግጥሚያ ይጠብቃቸዋል፡፡
ተጫዋቾቹ መልበሻ ክፍል ውስጥ በድካም ዛል ብለው እንደተቀመጡ ሻንክሊ ገብቶ ፊት ለፊታቸው ቆሞ ትክ ብሎ አያቸው፡፡ እውነትም ድካም ይነበብባቸዋል፡፡ እናም እንዲህ አላቸው፡- ‹‹ልጆች መናገር ያልነበረብኝ ቢሆንም መደበቅ ደሞ አልችልምና ልንገራችሁ...›› አለና ወደ ኪሱ ገብቶ በደማቅ ወረቀት ላይ የታተመ ጽሑፍ አውጥቶ እያሳያቸው፣ ‹‹ይኼ ቼልሲዎች ስለ ናንነተ አሳትመው ያሰራጩት ነው፡፡ እናም ባለፈው ጨዋታችሁ ትንቅንቅ ስታደርጉ አቅማችሁን ሁሉ ስላሟጠጣችሁ ዛሬ በዝረራ እንደሚያሸንፏችሁ ጉራ ነፍተው የጻፉት ነው፡፡ እና እንዴት ነው እንዳሉትም ደክማችኋል እንዴ!››
በተጫዋቾቹ መሀል መጀመሪያ ቅሬታ ከዚያም የመጠቃት መንፈስ፣ ከዚያም እንደ ግስላ እመር አመር እያሉ በእልህ ይጎፈሉ ጀመር፡፡ ጨዋታውን እንደለመዱት በድል ካጠናቀቁት በኋላ፤ ሻንክሊ ወደ ቼልሲ አሰልጣኝ ሄዶ ሰላምታ ሲሰጠው አሰልጣኙ ቶሚ ዶቼቲ በጣም ተገርሞ፤ ‹‹ከዚያ የሮተርዳም ግጥሚያ በኋላ ልጆችህ በምን ተአምር እንዲህ አይነት ብቃት ይዘው ሊገኙ ቻሉ!›› ሲል ጠየቀው። ሻንክሊ ‹‹ይህን ስላስነበብኳቸው ነው›› ብሎ ያቺን ደማቅ ወረቀት አውጥቶ ሰጠው፡፡ ቶሚ ወረቀቱን አይቶ ‹‹ይኼ የምን እንቶ ፈንቶ ነው!›› ብሎ ጮኸ፡፡ ወረቀቷ በሌላ በማንም እጅ ያልነበረችና ልጆቹን አቀባብሎ ለመተኮስ ራሱ ሻንክሊ ያዘጋጃት አንዲት ኮፒ ብቻ ነበረችና፡፡ አለ አይደል በቃ ትንሽ ለመቆስቆስ፡፡
3. MIND BLOWING - እፎይታ
 በ1866 አሜሪካ የnitroglycerineን ፍንዳታ ጥቅም ላይ በማዋል ተራራና ቋጥኞችን ነድሎ የውስጥ ለውስጥ መንገዶች ለመስራትና መላ አህጉሩን ለማገናኘት ቋምጠው ነበር። ጉዳዩ ቢሳካ ለነዳጅ ፍለጋና ማእድን ቁፋሮ የሚባክነውን በመቶ የሚቆጠሩ ሰራተኞችን ጉልበትም ቆጣቢ ነው ተብሎ ነበር፡፡ ችግሩ nitroglycerine ፈሳሽ ስለነበር እርሱን ለማጓጓዝ በተደረጉ ሙከራዎች የብዙዎች ህይወት ተቀጠፈ። በመርከብና የተለያዩ ስፍራዎች ካለቁት ሰዎች በተጨማሪ ድንገተኛ ፍንዳታው ከተከሰተበት ግማሽ ማይል ርቀው ባሉ መኖሪያ ቤቶች 3ኛ ፎቅ ደርሶ መስኮት በመገነጣጠል የአንድ ሰው ክንድ እስከመጉመድና በመንገድ ላይ ተፈነጣጥረው የተገኙ የሰው ጀርባ አጥንት ዜናዎች መነጋገሪያ ሆኑ፡፡
ከሁለት አመት በፊት በ1864  በዚሁ የፍንዳታ ጦስ ታናሽ ወንድሙን ያጣ ሰው ነበረ - አልፍሬድ ኖቤል፡፡ ኖቤል ሳይንቲስት እና ጦርነት የማይወድ (Scientist and Pacifist) ሰው ነበረ፡፡ እናም nitroglycerineን በቀላሉ ለመያዝና ለማጓጓዝ የሚያስችል ፈጠራ ፈጠረ፡፡የፈጠራውንም ስም Dynamite (ድማሚት) ብሎ ሰየመው፡፡ ጥሩ ማሸጊያም ስለሰራለት የሚፈለገው ቦታ ደርሶ እስኪፈነዳ ድረስ ምንም ጉዳት እንዳያመጣ በማድረጉ የብዙዎችን ህይወት ታደገ። በዚያም እጅግ ብዙ ገቢ ለማግኘት ቻለ፡፡ እንደ አንድ ጦርነትን እንደሚጸየፍ Pacifist ሰውም የተሻለች ዓለም በመፍጠር ረገድ አቅሙ የፈቀደውን እገዛ ማድረጉ ተሰማው፡፡ ታላቅ ወንድሙ ታምሞ እስኪሞት ድረስ፡፡
አንድ የፈረንሳይ ጋዜጣ ዜናውን አወጫብሮ የወንድሙን ሞት ራሱ አልፍሬድ ኖቤል እንደሞተ አድርጎ ዘገበው፡፡ አርእስተ ዜናው እንዲህ ነበር የሚለው፡- ...‹‹ነጋዴው ኖቤል ሞተ››
ኖቤል ክው ብሎ ደነገጠ፡፡
ጋዜጣው ሀተታውን ሲቀጥልም፡- ‹‹የሰው ልጆችን ከመቼውም ጊዜ በበለጠ በፍጥነት እንዲሞቱ መንገድ የቀየሰ ሰው›› ይላል፡፡ ኖቤል ማመን አቃተው፡፡
እርሱ ስለ ራሱ የሚያስበው የነበረው እውነት፤ ድማሚትን በመፍጠሩ የሌሎችን ሕይወት የታደገ ግብረ ሰናይ ሰው መሆኑን ነበር፡፡ በዓለም ገሀድ እውነት ዓይን ሲታይ ግን ዳይናማይትን መፍጠር በጭራቅ እንዲመሰል አድርጎት ኖሯል ለካንስ!
ስለዬህም ኖቤል በጋዜጣ ላይ ከተገለፀበት መልኩ በተለየ በሌላ መልካም ስም ይታወስ ዘንድ በጽኑ ፈለገ፡፡ እናም የኖቤል ሽልማት የተሰኘውን የሽልማት ድርጅት አቋቋመ፡፡
በየዓመቱ በሳይንስ፣ ኬሚስትሪ፣ ህክምና፣ ሥነ ጽሑፍና ልዩ የዓለም የሰላም ኖቤል ሽልማት ተሸላሚ በሚል ዘርፍ ሽልማቱ መሰጠት ተጀመረ፡፡ ይኸውም ሽልማት ዛሬ በዓለም ላይ ያሉ ሳይንቲስቶች፣ የሀገር መሪዎችና ልዕለ ሰብእናዎች ሁሉ የሚጓጉለት ሽልማት ለመሆን በቃ፡፡
እናም ኖቤል የሚለው ስም አሁን እርሱ በፈለገው መንገድ የሚታወስ ለመሆን በቃ፡፡ የሞት ነጋዴው በሚለው አጉል መጠሪያ ሳይሆን በዓለም ላይ ካሉ ሽልማቶች ሁሉ ላቅ ባለውና የግብረ ሰናይነት መገለጫ በሆነው ስሙ- የኖቤል ሽልማት፡፡ እፎይ፡፡

 የታዋቂው ማህበራዊ ድረገጽ ፌስቡክ የመጀመሪያው ሩብ አመት አጠቃላይ ገቢ ካለፈው አመት ተመሳሳይ ጊዜ በግማሽ ያህል መጨመሩን የዘገበው አልጀዚራ፤ ፌስቡክ ባለፉት ሶስት ወራት ብቻ 11.96 ቢሊዮን ዶላር ገቢ ማግኘቱን ገልጧል።
ተቀማጭነቱን በካሊፎርኒያ ያደረገው ፌስቡክ ምንም እንኳን በመረጃ ቅሌት ቀውስ ውስጥ ቢሆንም ገቢውና የተጠቃሚዎቹ ቁጥር መጨመሩንና የተጠቃሚዎቹ ቁጥር ባለፉት ሶስት ወራት በ13 በመቶ በማደግ፣ 2.2 ቢሊዮን መድረሱን ባለፈው ረቡዕ ባወጣው መግለጫ አስታውቋል፡፡
በተመሳሳይ ዜናም የደቡብ ኮርያው ሳምሰንግ ኤሌክትሮኒክስ ለተከታታይ አራት ሩብ አመታት ክብረወሰን ያስመዘገበበትን ትርፍ ማግኘቱ የተዘገበ ሲሆን ባለፉት ሶስት ወራት ብቻ 10.8 ቢሊዮን ዶላር ትርፍ እንዳገኘ ተነግሯል፡፡
ሳምሰንግ በሚሞሪ ቺፕስና በጋላክሲ ኤስ 9 ስማርት ፎን ምርቶቹ ላይ ያለው የገበያ ፍላጎት ማደጉ ከፍተኛውን ትርፍ እንዲያገኝ አስችሎታል መባሉን የዘገበው ቴክ ግሎባል፤ 73 በመቶ የሚሆነውን ትርፍ ያገኘው ከሚሞሪ ቺፕስ ሽያጭ መሆኑንም አመልክቷል፡፡

የሳኡዲ አረቢያ መንግስት ባለፉት 4 ወራት ጊዜ ውስጥ ብቻ 48 ሰዎችን አንገታቸውን በመቅላት መግደሉን አለማቀፉ የሰብዓዊ መብቶች ተሟጋች ተቋም ሂውማን ራይትስ ዎች ማስታወቁን ዘ ጋርዲያን ዘግቧል፡፡
ሳኡዲ አረቢያ አንገት በመቅላት ብዙ ሰዎችን በመግደል በቀዳሚነት ከሚጠቀሱ የአለማችን አገራት አንዷ ናት ያለው ተቋሙ፤ በአገሪቱ መንግስት በ2018 የፈረንጆች አመት የመጀመሪያዎቹ አራት ወራት፣ አንገታቸው ተቀልቶ ከተገደሉ ሰዎች መካከል አብዛኞቹ የከፋ ወንጀል ያልፈጸሙ መሆናቸው እርምጃውን ኢ-ፍትሃዊ  ያደርገዋል ብሏል፡፡
በአገሪቱ ባለፈው አመት ብቻ 150 ያህል ሰዎች ጭካኔ በተሞላበት ሁኔታ አንገታቸውን ተቀልተው መገደላቸውንና እ.ኤ.አ ከ2014 መጀመሪያ አንስቶ ባለው ጊዜ ውስጥ በ600 ያህል ሰዎች ላይ የአንገት መቀላት ፍርድ ተፈጻሚ መሆኑን ያስታወሰው ተቋሙ፤ ከ30 በመቶ በላይ የሚሆኑትም ቅጣቱ የተጣለባቸው ከአደንዛዥ ዕጾች ዝውውር ጋር በተያያዘ ተከስሰው መሆኑን አመልክቷል፡፡
የሳኡዲው ልኡል ሞሃመድ ቢን ሳልማን በቅርቡ ከታይም መጽሄት ጋር ባደረጉት ቃለ ምልልስ፤ አገሪቱ ከነፍስ ማጥፋት ወንጀል በስተቀር በሌሎች ክሶች የሚሰጡ የሞት ፍርዶችን ወደ እድሜ ልክ እስራት ዝቅ የማድረግ ሃሳብ እንዳለ መናገራቸውን ዘ ጋርዲያን ዘግቧል፡፡

 በሰሜን ኮርያ እጅግ ግዙፉ እንደሆነ የሚነገርለትና ላለፉት 12  አመታት በአገልግሎት ላይ የቆየው የኒውክሌር ሙከራ ጣቢያ፤ አብዛኛው ክፍል በተደጋጋሚ ፍንዳታዎች በደረሰበት ጉዳት ሳቢያ መደርመሱና አገልግሎት የማይሰጥበት ደረጃ ላይ መድረሱ ተዘግቧል፡፡
ከአቅሙ በላይ በሆነ መልኩ ተደጋጋሚና በርካታ የኒውክሌር ሙከራ ፍንዳታዎችን ያስተናገደው ግዙፉ የሰሜን ኮርያ የሙከራ ጣቢያ፣ በከፋ ሁኔታ የተጎዳ ሲሆን ምናልባትም ቀጣይ ሙከራዎች ከተደረጉበት የኒውክሌር ጨረሮችን ሊያሾልክና አደጋ ሊያደርስ እንደሚችል አረጋግጠናል ሲሉ ቻይናውያን ተመራማሪዎች ባለፈው ረቡዕ ይፋ ባደረጉት የጥናት ሪፖርት ማስታወቃቸውን ዘ ኢንዲፔንደንት ዘግቧል፡፡
ፑንጌሪ በተባለው የአገሪቱ ሰሜን ምስራቃዊ ተራራማ ስፍራ ላይ የሚገኘው ግዙፉ የኒውክሌር ሙከራ ጣቢያ፣ ፕሬዚዳንት ኪም ጁንግ ኡን እ.ኤ.አ ከ2006 ወዲህ ያደረጓቸውን ስድስት የኒውክሌር ሙከራዎች በሙሉ ማስተናገዱን ያስታወሰው ዘገባው፤ የቻይና ሳይንስና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ተመራማሪዎችም ጣቢያው በመደርመሱ ሳቢያ ከአሁን በኋላ አገልግሎት ላይሰጥ እንደሚችል አረጋግጠናል ማለታቸውን አመልክቷል፡፡
የኒውክሌር ሙከራ ጣቢያው በሃይለኛ ፍንዳታዎችና በተደጋጋሚ የመሬት መንቀጥቀጦች በመመታቱ ክፉኛ መጎዳቱን የዩኒቨርሲቲው ተመራማሪዎች በጥናት ማረጋገጣቸውን የጠቆመው ዘገባው፤ የአገሪቱ ፕሬዚዳንት ይህንን ግዙፍ የኒውክሌር ሙከራ ጣቢያ እንደሚዘጉ፣ የኒውክሌር ጦር መሳሪያዎችንና የባላስቲክ ሚሳኤል ሙከራዎችን እንደሚያስቆሙ ከሰሞኑ ማስታወቃቸውንም አስታውሷል፡፡

 (የሙያ ባልደረቦቹ ምን ይላሉ?)

    ድምፃዊ ታምራት ደስታ ከሻሸመኔ አለፍ ብሎ በሚገኘውና የሃዋሳ አጎራባች በሆነው ጥቁር ውሃ በ1971 ዓ.ም ተወለደ፡፡ ዕድሜው ለትምህርት እንደደረሰ በአካባቢው ትምህርቱን የተከታተለው ታምራት ደስታ፤ በ1990ዎቹ መጀመሪያ ላይ ወደ ሙዚቃው ኢንዱስትሪ በመቀላቀል “ሀኪሜ ነሽ” የተሰኘውን የመጀመሪያ አልበሙን ለአድማጭ ጆሮ በማድረስ ከፍተኛ  ተወዳጅነትን ተቀዳጅቷል፡፡
ከዚያም የ“አንለያይም”፣ “ካንቺ አይበልጥም” እና “ከዚያ ሰፈር” የተሰኙ ተወዳጅ አልበሞችን ያወጣ ሲሆን አምስተኛ አልበሙን በማገባደድ ላይ ሳለ ነው ሞት በድንገት የቀደመው፡፡ ከድምፃዊነት ባሻገር የግጥምና ዜማ ደራሲ የሆነው ታምራት፤ የአምስት ልጆች አባት ሲሆን ሦስቱ ልጆቹ እዚሁ፣ ሁለቱ ደግሞ በጣሊያን እንደሚኖሩ ለማወቅ ተችሏል፡፡ አርቲስቱ ባለፈው ረቡዕ ድንገት ባጋጠመው ህመም፣ ለህክምና በራሱ መኪና ከቤቱ ወጥቶ ሳይመለስ ቀርቷል፡፡ ወዳጆቹ እንደሚሉት፤ በአንድ የግል ክሊኒክ መርፌ በተወጋ በ30 ደቂቃ ውስጥ ነው ህይወቱ ያለፈው፡፡
ከትናንት በስቲያ ከቀኑ 9፡00 ሰዓትም በቅድስት ሥላሴ ካቴድራል የተፈፀመ ሲሆን በቀብር ስነ ሥርዓቱ ላይ በርካታ የሙያ አጋሮቹ፣ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ዶ/ር ገበየሁ ወርቅነህ፣ ቴዲ አፍሮ፣ አረጋኸኝ ወራሽ፣ ነዋይ ደበበ፣ ቀመር የሱፍ፣ ደረጀ ደገፋው እንዲሁም አድናቂዎቹ፣ ቤተሰቦቹና የቅርብ ጓደኞቹ ተገኝተዋል፡፡
የአዲስ አድማስ ጋዜጠኛ ናፍቆት ዮሴፍ፤ በድምፃዊው ድንገተኛ አሟሟት ዙሪያ የሙያ አጋሮቹን አስተያየት አሰባስባ እንደሚከተለው አጠናቅራዋለች፡፡

     “ታምራት ከተረጋጉ ጥቂት ድምፃዊያን አንዱ ነበር”
(ድምፃዊ ደረጀ ደገፋው)
ከታምራት ደስታ ጋር የረጅም ጊዜ ትውውቅ ነው ያለን፡፡ በተለይ “አንለያይም” የሚለውን አልበሙን ከሰራ በኋላ ከጥበቡ ወርቅዬ ጋር አሜሪካ መጥተው ነበረ፡፡ ሳልለያቸው ነበር የማስተናግዳቸው፡፡ ከዚያን ጊዜ ጀምሮ አድናቂው ሆንኩኝ፡፡ ከዚያ በኋላ በተለያየ አጋጣሚ መገናኘትና ጓደኝነታችንን ማጠናከር ጀመርን፡፡ የሚገርምሽ የዛሬ 10 ቀን፣ ገርጂ መብራት ኃይል የሚባል አካባቢ አብረን ቁርስ በልተናል (ረጅም ለቅሶ)፡፡ ዛሬ (የቀብሩ ዕለት ማለት ነው) ከሰዓት በኋላ የሙዚቃ ሥራ ለመስራትና በዚያውም ለመነጋገር ቀጠሮ ነበረን (አሁንም ለቅሶ ..) እውነቴን ነው በጣም አዝኛለሁ፡፡
ባህሪውን በተመለከተ ከተረጋጉ ዘፋኞች አንዱ ነው፡፡ አንዳንዶች እንደኔ “ታዋቂ ነኝ” በሚል፣ ልታይ ልታይ የሚሉ አሉ፡፡ ታምራት አንገቱን የደፋና እጅግ ሥነ ሥርዓት የተላበሰ ልጅ ነው፡፡ ማሪያምን ነው የምልሽ … የሱን ፀባይ ሳይ እሱን ባደረገኝ ሁሉ እላለሁ። የተረጋጋ፣ ልታይ ልታይ የማይል፣ ሰዎች ሙዚቃ እንዲሰሩ የሚገፋፋና ዜማ ካልሰራሁላችሁ ብሎ የሚለምን ነው፡፡ የዛሬው ቀጠሯችን ለእኔ ግጥምና ዜማ ሊሰራልኝ ነበር፡፡ ገርጂ ስቴዲዮ ያለው ወንድምአገኝ አሰፋ የተባለ አቀናባሪ አለ፡፡ የታሜ የቅርብ ጓደኛ ነው፡፡ ትላንት ደወለልኝና የታሜን ሞት ነገረኝ፡፡ “ምን አይነት ቀልድ ነው? እንዴት በዚህ ይቀለዳል? ለምን ታሟርታለህ” ብዬ ስልኩን ዘጋሁት፡፡ እንደገና ደወለና፤ “ለማመን ይከብዳል አይደል?!” አለኝ፡፡ እሱም ያለቅስ ነበር፤ እኔም እንደዛው፡፡ ሰው መኪና እያሽከረከረ ሄዶ፣ እንዴት በሳጥን ይመለሳል? የመጠየቂያ ሁለትና ሶስት ቀንኮ አለ (ረጅም ለቅሶ…) ሆስፒታል ደርሶ ቢሆን፣ የመዳን እድል ይኖረው ነበር፡፡ በአጠቃላይ የታሜ ነገር እጅግ ልብ ይነካል፡፡ ለሙዚቃው ዘርፍም ትልቅ ጎደሎ ነው፡፡ ከህይወት ታሪኩ ስሰማ አምስት ልጆች አሉት፡፡ እናቱም በህይወት አሉ፡፡ ልጆቹ እንዳይለያዩ፤ እንዳይቸገሩ … የበኩላችንን ማድረግ ይኖርብናል። ለታምራት ልጆች፣ ለመላ ቤተሰቡ፣ ለአድናቂዎቹና ለወዳጅ ዘመዶቹ መፅናናትን እመኛለሁ፡፡

ለዛሬ 9፡00 ሰዓት የቀጠረኝ እንድቀብረው ይሆን እላለሁ”
(አርቲስት ካሌብ አርአያሥላሴ)
ከታምራት ጋር የረጅም ጊዜ ወዳጅነት ነው ያለኝ። ድሮ የምሽት ክበብ ነበረኝ፤ እዛ ሲመጣ ከነበረን ደንበኝነት ጀምሮ ነው የምንተዋወቀው፡፡ እሱ እነ ጎሳዬንና ሌሎችንም ይዞ ሲመጣ ቤቱ ይሞቃል፤ በጣም ደስ ይለኝ ነበር፡፡ ታምራት የምሬን ነው የምልሽ … የፈጣሪ ስራ ሆነ እንጂ በዚህ ሰዓት ሞት አይገባውም ነበር፡፡ ሞት ለማንኛችንም የማይቀር ቢሆንም እንደ ቀልድ ከቤቱ ወጥቶ መቅረት የሚገባው ልጅ አልነበረም፡፡ በጣም አዝኛለሁ፤ መቀበል አቅቶኛል። ታሜ ዛሬ በህይወት ካጠገባችን ስለራቀ አይደለም፤ እጅግ የዋህ፣ ደግና ሩህሩህ ሰው ነበር፡፡ ሰው ካልሄደ ወይ ካልሞቱ አይመሰገንም ይባላል፡፡
ከታሜ ጋር እሁድ ጠዋት አብረን ቁርስ በልተን ነበር፡፡ ባልደራስ አካባቢ ቁርስ ስንበላ በርካታ የአካባቢው ህዝብ አይቶን ነበር፡፡ ሞተ ሲባል ብዙ ሰዎች እየደወሉ፤ “በቀደም አብራችሁ አልነበራችሁ? … ምን ሆነ? እውነት ነው?” እያሉ ጠይቀውኛል፡፡ ዛሬ 9 ሰዓት ላይ ቀጠሮ ነበረን፡፡ የቡና አስጨፋሪው አዳነና ሌሎች ለዛሬ ስንቀጣጠር ሰምተዋል፡፡ ዛሬ የተቀበረው 9 ሰዓት ላይ ነው፡፡ “ለዛሬ የቀጠረኝ እንድቀብረው ይሆን” እላለሁ፡፡ በጣም ያሳዝናል፡፡
ታሜ እናት ማለት ነው፡፡ በመዝናናትና በጨዋታ መሃል እንኳን ገብቶ ምክር የሚሰጥና የሚያበረታታ፣ በቁም ነገር የተሞላ ሰው ነው፡፡ ደግ ነው፡፡ በእድልም በልምድም ከሱ የሚበልጡ ግን የሚያከብሩት አርቲስቶች አሉ፡፡ እሱ ወረድ ብሎ ከእኛ ጋር ነው ጊዜ የሚያሳልፈው፡፡ እኛ ያልነውን ሁሉ ይሰማል። የሚዝናናው እንኳ አነስ ያለ ቤት ነው፡፡ በትህትና የተሞላ ሰው ነበር፡፡ ምን ዋጋ አለው፤ ድንገት ተነጠቅን።
ለዛሬ የተቀጣጠርነው ለእኔ የሚሆን ስራ እንዳለውና አንዳንድ ነገር ሊያደርግለኝ ፈልጌ ነው። ነገር ግን ምን እንዳሰበልኝ እንኳን ሳላውቅ ነው ያጣሁት። ፈጣሪ ለልጆቹ፣ ለቤተሰቡ፣ ለአድናቂዎቹና ለእኛም ለጓደኞቹ መፅናናትን ይስጠን እላለሁ፡፡
በቀጣይ ለልጆቹ እንክብካቤ በማድረግ፣ ለቁም ነገር ልናበቃቸው ይገባናል፡፡ በዚህ ላይ ሁሉም ቢያስብበት መልካም ነው፡፡ ልጆቹ ስለ ምንም ሳይጨነቁ ትምህርታቸውን መማር፣ ለቁም ነገር መብቃት አለባቸው፡፡ በተለይ አረጋኸኝ ወራሽ የማስተባበርና የማቀናጀት ተሰጥኦና ነፍስ ስላለው፣ እርሱ በዋናነት ኃላፊነቱን ወስዶ ለልጆቹ ዘላቂ የሆነ ነገር ቢደረግ እላለሁ፡፡
“እንደ ቀልድ መርፌ እየተወጉ ህይወታቸውን የሚያጡ ሰዎች ጉዳይ ትኩረት ያሻዋል”
(አርቲስት ንዋይ ደበበ)
ከሁሉ በፊት ለኢትዮጵያ ህዝብና ለቤተሰቦቹ መፅናናት እመኛለሁ፡፡ አየሽ ልጁ በጣም ተወዳጅ ነው። በጣም ትልቅ ተሰጥኦ ያለውና እጅግ የምናከብረው ልጅ ነው፡፡ ዜማ ያወጣል፣ ግጥም ይፅፋል፣ በድምፁ ይጫወታል፡፡ ይህ ደግሞ በእኔና በእርሱ መካከል የባህሪ ውርርስ ይፈጥራል፡፡ እጅግ ከማከብርለት ነገር መካከል ዋናው የፈጠራ ሰው … መሆኑ ነው፡፡ ሁለተኛው ደግነቱ ለጉድ ነው። ልጁ የዋህ ነው፤ ሩህሩህ ነው፡፡ የታምራትን ደግነት፣ ትዕግስት፣ ፀባይና ሥነ - ሥርዓት ይሄ ነው ብሎ መናገር አይቻልም፡፡ ሰላማዊ ነው፣ ፍቅር ፈላጊ። ከጓደኞቹ ጋር አብሮ መብላትና ጊዜ ማሳለፍ ይወዳል። ለዚህ ነው እንደምታይው፣ ሰው ሁሉ አልቅሶ የማይበቃው፡፡
የወላይታን አንድ የልማት መዝሙር አብረን ሰርተናል፡፡ በወላይታ ልማት ማህር (ወ.ል.ማ) ማለት ነው፡፡  ለመሆኑ የድምፁን ቃና ሰምተሽዋል? በጣም ማር ማር የሚል፣ የማይጠገብ ልጅ ነበር፡፡ እንግዲህ እግዚአብሔር ለመንግስተ ሰማያት ያብቃው፤ ለቤተሰቡና ለወዳጆቹ መፅናናትን እመኛለሁ፡፡
በመጨረሻ በአፅንኦት መናገር የምፈልገው፤ ለመሆኑ ስንት ሰዎች ናቸው እንደዚህ መርፌ እየተወጉ የሚሞቱት የሚለውን ነው፡፡ የዚህ ልጅ ጉዳይ ጎልቶ የወጣው ታዋቂ ስለሆነ ነው፡፡ የህክምና ስህተት ተፈጥሯል አልተፈጠረም የሚለውን ሙያዬ ስላልሆነ የማውቀው ነገር የለም፤ ነገር ግን መኪናውን እያሽከረከረ ወጣ፤ መርፌ ተወጋ፤ በ30 ደቂቃ ውስጥ ህይወቱ አለፈ፡፡ በመኪና ወጥቶ በሳጥን ሲመለሽ ትንሽ አይከብድም? እስኪ ንገሪኝ … ቅር አያሰኝም ወይ? (በከፍተኛ ብስጭትና ቁጭት) እርግጥ የምርመራ ውጤቱ በቀጣይ ይፋ ይሆናል፤ ግን መንግስት ይሄን ጉዳይ በከፍተኛ ሁኔታ ተከታትሎ አንድ ነገር ላይ መድረስ አለበት፡፡ ሌላውም እየሄደ በደቂቃ ልዩነት ህይወቱን ማጣት የለበትም፡፡ ከፍተኛ ክትትልና ማጣራት መደረግ አለበት፡፡
ልጆቹን በሚመለከት እኛ አለን፤ የኪነ ጥበቡ ማህበረሰብ አላቸው፡፡ በተለይ አሁን ላይ በከፍተኛ ደረጃ በማህበር እየተደራጀን ነው ያለነው፤ እግዚአብሔር ፈቃዱ ከሆነ ወደፊት እንደዚህ ወጣት የሙያ አጋሮቻችን ድንገት ሲቀጠፉ፣ ቤተሰባቸውን እንዴት ማገዝ እንዳለብን እንመክራለን፤ እንተገጋገዛለን።
“ታሜ ለጥበብ የተፈጠረ ሰው ነው”
(አርቲስት ታደለ ገመቹ)
ከታሜ ጋር ከ18 ዓመት በላይ የዘለቀና የጠበቀ ጓደኝነት አለን፡፡ ሞቱን የሰማሁት ማመን በሚያቅተን መልኩ ነበር፡፡ የሱ ዜና እረፍት በሶሻል ሚዲያ ላይ ወጥቶ፣ ለእኔ እጅግ በርካታ ስልክ ይደወልልኝ ነበር። እኔ ደግሞ ስቱዲዮ ውስጥ ሆኜ ስልክ መመለስ አልቻልኩም፡፡ ከዚያ ወጥቼ ስሰማ ማመን ነው ያቃተኝ፡፡ ሰው ጋር ከመወደሌ በፊት ለተወሰነ ጊዜ ግራ ገብቶኝ፣ ደንዝዤ ነበር፡፡ ትንሽ ቆይቼ ነው እንቅስቃሴ የጀመርኩት፡፡ አረጋኸኝ ጋ ደውዬ፤ እውነት መሆኑን ሲነግረኝ፣ እንዴት ቤቱ እንደደረስኩም አላውቅም፣ በርሬ መጣሁ፡፡
እንደነገርኩሽ ከ18 ኣመት በፊት ተዋወቅን፣ ከዚያ በኋላ አብረን ብዙ ነገር አሳልፈናል፡፡ እንግዲህ ትውውቃችን እኔም እሱም አልበም ከማውጣታችን በፊት፣ ክለብ ውስጥ ስንሰራ ነው፡፡ ስለ ታሜ ብዙ ነገር ተብሏል፡፡
ዋናው ነገር ታሜ ለጥበብ የተፈጠረ ልዩ ሰው ነው፡፡ ለጓደኞቹና ለሰው ሁሉ ያለው ፍቅርና አመለካከት ልዩ ነው፡፡ በአጠቃላይ የጥሩ ሰው መመዘኛና መለኪያ ነው፡፡ ይህ አባባሌ “ሰው ሲሞት ነው የሚመሰገነው” በሚለው ባይወሰድብኝ ደስ ይለኛል፡፡ ታሜ ለሰው የሚኖር፣ ትሁትና ሽቁጥቁጥ፣ በጣም ጨዋ ልጅ ነው፡፡ ፈጣሪ ነፍሱን ለገነት ያብቃት ነው የምለው፡፡

 • ህዝቡ ወደ ጎዳና የወጣው ነፃነትን ፍለጋ እንጂ ኢህአዴግን ለማደስ አይደለም
   • የሰብአዊ መብት ጥሰት የሚፈጸመው በፖሊሶች ሳይሆን በሥርአቱ ነው
   • ትግሉ ዳር እስኪደርስ በውጭ ሃገር እኖራለሁ ብዬ አላስብም

     ለ6ዓመታት ከታሰረ በኋላ በቅርቡ ከእስር የተለቀቀው ጋዜጠኛ እስክንድር ነጋ፤ ከሰሞኑ የዓለማቀፉ የሰብአዊ መብት ተሟጋች ድርጅት አምነስቲ ኢንተርናሽናል 50ኛ ዓመት የምስረታ በዓል ላይ በክብር እንግድነት ለመገኘት ወደ ኔዘርላንድ ተጉዟል፡፡ ጋዜጠኛው የተጀመረው ትግል ዳር ሳይደርስ በውጭ አገር የመኖር ሃሳብ እንደሌለው ጠቁሟል፡፡ ከጉዞው በፊት የአዲስ አድማስ ጋዜጠኛ አለማየሁ አንበሴ፣ ጋዜጠኛ እስክንድር ነጋን አግኝቶ ያነጋገረው ሲሆን አዲሱ ጠቅላይ ሚኒስትር ከህዝብ ጋር እያደረጉ ስላሉት ውይይት፣ ከጠ/ሚኒስትሩ ስለሚጠብቀው ጉልህ ለውጦች፣ ከተቃዋሚዎች ጋር መደረግ አለበት ብሎ ስለሚያምነው ድርድርና ሌሎችም ጉዳዮች አስተያየቱን ሰንዝሯል፡፡ እነሆ፡-



    ከእስር ከተፈታህ በኋላ ወደተለያዩ የአገሪቱ አካባቢዎች ተጉዘሃል፡፡ የጉዞው ዓላማ ምን ነበር?
በየአካባቢው እየተጋበዝን ነበር የምንሄደው። ነገር ግን ጉዞዎቹ በሚስጥር ነበር የሚደረጉት፡፡ ምክንያቱም የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ላይ ነን፡፡ ነገር ግን ደሙን አፍሶ ከእስር ያስፈታን ህዝብ በመሆኑ  በየአካባቢው እየሄድን ምስጋና ማቅረብ ነበረብን፡፡   
በተዘዋወርክባቸው አካባቢዎች በህዝቡ ላይ ያስተዋልከው ስሜት ምንድን ነው?
ህዝብ የለውጥ እንቅስቃሴ ውስጥ ነው ያለው፡፡ ሁሉን አቀፍ ለውጥ ያስፈልጋል የሚል ስሜት ይንጸባረቃል፡፡ አሁን በኢህአዴግ ውስጥ የተደረገው ሽግሽግ በቂ አይደለም፤ ወደ ስር ነቀል ዲሞክራሲያዊ ሽግግር ልንሄድ ይገባል የሚል ስሜት እንዳለ ነው የተረዳሁት፡፡
ለህዝቡ የለውጥ ጥያቄ፣ የአዲሱ ጠ/ሚኒስትር መመረጥ ምን አስተዋጽኦ ይኖረዋል?
ለለውጦች ተጨማሪ መንገድ ይከፍታል ብዬ ተስፋ አደርጋለሁ፡፡ ዓለማቀፍ ማህበረሰቡን ለማነጋገርም እድሉን አግኝቼ ነበር፡፡ እነሱም ለውጥ ሊመጣ ይችላል የሚል ግምት እንዳላቸው ተረድቻለሁ፡፡ በዲፕሎማቶቹ ዘንድ ጠ/ሚኒስትሩ የለውጥ ፍላጎት አላቸው የሚል እምነት ነው የሚንጸባረቀው፡፡ ባለፉት ንግግሮቻቸው ጥሩ ነገር ሰምተናል፤ ግን በወልቃይት ጉዳይ ህዝብን ቅር ያሰኘ ነገር ተናግረዋል፡፡ ከዚህ አንጻር  በንግግራቸው ላይ ጥንቃቄ ማድረግ ያለባቸው ይመስለኛል፡፡
ከጠቅላይ ሚኒስትሩ የሚጠበቁ ጉልህ ለውጦች ምንድን ናቸው?
ከጠቅላይ ሚኒስትሩ የሚጠበቀው ለቀጣዩ ምርጫ ምቹ ሁኔታ መፍጠር ብቻ አይደለም፤ሁለት አበይት ነገሮች አሉ፡፡ በመጀመሪያ የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁን ማንሳት ነው፡፡ ከዚያም አዋጁ ከተጣለ በኋላ የታሰሩ ግለሰቦችን ያለ ቅድመ ሁኔታ መፍታት ነው፡፡ ሁለተኛ ሃገሪቱን ወደ ሰላማዊ ሽግግር ማስገባት ነው፡፡ ለዚህ ደግሞ ሁሉን አቀፍ ድርድር ማድረግ ያስፈልጋል፡፡ ሁሉን አቀፍ ድርድር ሲባል፤ በህጋዊም ሆነ ከዚያ ውጪ ባሉ መድረኮች ያሉ ተቃዋሚ የፖለቲካ ድርጅቶችን የሚያካትት የድርድር ጉባኤ መጥራት ነው፡፡ ህጋዊ ባልሆነ መንገድ የሚታገሉ ሶስት ድርጅቶችን፡- “ኦነግ”፣ “ግንቦት 7” እና “ኦብነግ”ን ማካተት አለበት ድርድሩ፡፡ በደቡብ አፍሪካ ለውጥ የመጣው በገዥው ናሽናል ፓርቲና በኤኤንሲ መካከል ድርድር ከተካሄደ በኋላ ነው። ኢትዮጵያ ውስጥም ለውጥ ሊመጣ የሚችለው በሽብርተኝነት በተፈረጁ ድርጅቶችና በኢህአዴግ መካከል ድርድር ሲካሄድ ነው፡፡ ይሄ ካልተደረገ ህዝብ የሚፈልገው ለውጥ መጥቷል ማለት አይቻልም፡፡ ከሁለት ዓመት በኋላ ለሚደረገው ምርጫ፣ የፖለቲካ ምህዳሩን ለማመቻቸትም ይሄ ወሳኝ ነው፡፡ ምርጫው ገና ሩቅ ነው፡፡ ቅድሚያ ሊሰጠው የሚገባው ግን ከእነዚህ ኃይሎች ጋር ለሚደረገው ድርድር ነው፡፡  
ምን አይነት ድርድር ነው  መንግስት ማድረግ ያለበት?  
በዚህ ረገድ ምሳሌ የምትሆነን ደቡብ አፍሪካ ነች፡፡ ደቡብ አፍሪካ ያደረገችው ሰላማዊ ዲሞክራሲያዊ ሽግግር በድርድር የመጣ ነው። ይሄ ድርድር ውጤት ካመጣ በኋላ ለዓለም ሞዴል ሆኗል፡፡ በደቡብ አሜሪካ፣ በእስያ ሃገራት ተሞክሮ ውጤታማ ሆኗል፡፡ በአፍሪካም በተለያዩ ሀገራት ውጤት አምጥቷል፡፡ በኢትዮጵያም ውጤታማ እንደሚሆን ምንም ጥርጥር የለውም፡፡ የተሞከረ ሞዴል እያለ ሌላ ለማፍለቅ መጨነቅ የለብንም። ዋናው ነገር ያለ ቅድመ ሁኔታ ሁሉንም ወገን በድርድር መድረክ ማሳተፍ ነው፡፡ የዚህ ድርድር ውጤት ምንም ነገር ሊሆን ይችላል፡፡ በብዙ ሃገራት ይህ ዓይነቱ ድርድር በሽግግር መንግስት ይደመደማል፡፡ የሽግግር መንግስት ማለት ደግሞ የሚያስፈራ ነገር አይደለም፡፡ በቀላሉ የተለያዩ ድምፆችን የሚወክሉ አካላት የተሳተፉበት መንግስት ማለት ነው፡፡ ለምሳሌ በካቢኔ ውስጥ “ግንቦት 7”፣ “ኦነግ”፣ “መድረክ”፣ “ሰማያዊ ፓርቲ”ን ወዘተ ማሳተፍ ማለት ነው፡፡ በብዙ አገሮች የተደረገው ይሄ ነው፡፡ ድርድሩ ሲካሄድ ምናልባት እንደ ደቡብ አፍሪካ በዝግ ሊሆን ይችላል፡፡ ሁሉም ፓርቲዎች ግን የሰጥቶ መቀበልን መርህ መከተል ይኖርባቸዋል፡፡  
በዚህ ሂደት ውስጥ ከተቃዋሚዎች ምን ይጠበቃል?
በመጀመሪያ ነገር ከኢህአዴግ ብዙ ነገር ይጠበቃል፡፡ ከተቃዋሚዎች ደግሞ ግማሽ መንገድ መምጣት ይጠበቃል፡፡ ህዝቡ በተቃዋሚዎች ላይም ጫና ማድረግ ያስፈልገዋል። አሁን የሚደረገው  ድርድር የፖለቲካ ነጥብ ማስመዝገቢያ ሳይሆን የሃገር መታደጊያ ነው መሆን ያለበት፡፡ ተቃዋሚዎች ድርድሩ እንዲሳካ በኢህአዴግ የቀረበውን ጥሪ በፀጋ መቀበል  አለባቸው፡፡ ይህን እንዲቀበሉ ከሞራል መሪዎችና ከህዝቡ ግፊት ሊደረግ ይገባል። ድርጅቶች ጥቅማቸው ሊነካ እንደሚችል ጭምር አምነው ነው ወደ ድርድሩ መግባት ያለባቸው፡፡
ዶ/ር አብይ በኢህአዴግ ላይ ለውጥ ያመጣሉ አያመጡም የሚለው ጉዳይ አነጋጋሪ ሆኖ ቀጥሏል። ጠ/ሚኒስትሩ የሚፈለገውን ለውጥ ማምጣት ይችላሉ ብለህ ታምናለህ?
አዎ! ሶቪየት ህብረትን በኮሚኒስት ፓርቲው ውስጥ ሆኖ ወደ ለውጥ ያስገባው ሚኻኤል ጎርባቾቭ ነው፡፡ የአፓርታይድ ዋነኛ ባለቤት በነበረው የደቡብ አፍሪካው ናሽናል ፓርቲ ውስጥም ዴክለርክ ነው ለውጥ ያመጣው። የእነዚህን ሰዎች የመሪነት ክህሎት እስከ ዛሬ የምናደንቀው እኮ የድርጅታቸውን አስተሳሰብ ቀይረው ወደሚፈለገው ለውጥ ስለመሩት ነው፡፡
ዶ/ር አብይም በተመሳሳይ በፓርቲያቸው ውስጥ የሚገጥማቸውን ተቃውሞ አሸንፈው ዲሞክራሲን እውን በማድረግ ድርጅታቸውን ወደ ህዝቡ የለውጥ ፍላጎት እንዲያስገቡ ነው የምንጠብቀው። የአመራር ክህሎታቸው የሚፈተነው በዚህ ነው። ይሄን ማድረግ ካልቻሉ ታሪክ የጣለባቸውን ኃላፊነት መወጣት አልቻሉም ማለት ነው፡፡
ጠ/ሚኒስትሩ ሰፊ ተቀባይነት ካስገኘላቸው ጉዳይ አንዱ ኢትዮጵያዊነትን ማቀንቀናቸው ነው። ኢትዮጵያዊነትንና የብሔር ማንነትን ሚዛን አስጠብቆ ለመጓዝ አያስቸግራቸውም…?
ኢትዮጵያዊነት ውስጥ ብሔር ብሔረሰቦች እንዳሉ የምንክድበት ዘመን ላይ አይደለንም። እኚህ ሰው ኢትዮጵያዊነትን ሲያነሱ፣ ብሔር ብሔረሰቦችን ይክዳሉ ማለት አይደለም፡፡ በተመሳሳይ ብሔር ብሔረሰቦችን ሲያነሱም፣ ኢትዮጵያዊነትን ይክዳሉ ማለት አይደለም፡፡ ኢትዮጵያዊነትንም የብሔር ማንነትንም ሚዛናዊ አድርጎ የመሄድ ጉዳይ ነው። ሁለቱንም ይዞ መሄድ ችግር የለውም፡፡ ጎን ለጎን መሄድ የሚችሉ ናቸው፡፡ ይሄ ደግሞ ኢትዮጵያ ውስጥ ብቻ ሳይሆን በሌሎችም ሀገር ያለ ነው፡፡ ህንድ ውስጥ ህንዳዊነት አለ፤ የአካባቢ ማንነቶች ደግሞ አሉ፡፡ ጎረቤት ኬንያም ተመሳሳይ ነው፡፡ በብሔረሰቦችና በኢትዮጵያዊነት መሃል ያለውን ቀመር አጣጥሞ የመሄዱ ጉዳይ ነው ዋናው፡፡
ጠ/ሚኒስትሩ በአገሪቱ የተለያዩ አካባቢዎች የሚያደርጓቸው ንግግሮች ፖለቲካዊ ችግሮችን ለመፍታት ጠቀሜታ አላቸው ብለህ ታምናለህ?
ጠቀሜታ አላቸው፡፡ ነገር ግን በጥያቄና መልስ ወቅት ጥንቃቄ ማድረግ አለባቸው፡፡ ለምሳሌ በወልቃይት ጥያቄ ላይ የሰጡት ምላሽ ጥሩ አልነበረም፡፡ የወልቃይት ጥያቄ የዲሞክራሲ ነው እንጂ የልማት ተብሎ ሊታለፍ የሚችል አይደለም። የአንድን ህዝብ ዲሞክራሲ የሚጋፋ ነገር እንዳይናገሩ ጥንቃቄ ማድረግ አለባቸው፡፡ በሌላ በኩል ንግግሮቻቸው ወደ ተግባር እስካልተለወጡ ድረስ ትርጉም አልባ ነው የሚሆኑት፡፡ በእርግጥ ሰውየው የለውጥ ፍላጎት እንዳላቸው የመጡበት መንገድም ያሳያል፡፡ በከፍተኛ ፍላጎት ወደ ስልጣን መምጣታቸው በራሱ የለውጥ ፍላጎት እንዳላቸው ያመላክታል፡፡ የኦህዴድን አቋም የኢህአዴግ ማድረግ ከቻሉ ደግሞ ለውጡ ሁሉን አቀፍ ሊሆን ይችላል፡፡
በተረፈ አሁን የጫጉላ ጊዜ ላይ ናቸው፡፡ ግን ይሄን የጫጉላ ጊዜ ተጠቅመው የሚፈለገውን ነገር ማምጣት ካልቻሉ ህዝብ በድጋሚ ወደ ጎዳና የማይወጣበት ምክንያት የለም፡፡ ይሄን ጉዳይ በቅጡ ሊያስቡበት ይገባል፡፡ ጠ/ሚኒስትሩ፤ “የኢትዮጵያ ጎርባቾቭ” ወይም “የኢትዮጵያ ዴክለርክ” እንዲሆኑ ነው የምንፈልገው፡፡ በአጭር ጊዜ ውስጥ ሁሉን አቀፍ ድርድር የማይጠሩ ከሆነ፣ የዲሞክራሲ ጥያቄው ወደ ጎዳና ሊወጣ ይችላል፡፡ ይሄ በሌሎች ሃገሮችም ያየነው ልምድ ነው፡፡ ህዝቡ በኢህአዴግ የስልጣን ሽግሽግ ረክቶ አይቀመጥም፡፡ ሥር ነቀል ዲሞክራሲያዊ ለውጥ ይፈልጋል፣ ነፃነቱን መቀዳጀት ይሻል፡፡ ህዝቡ ወደ ጎዳና የወጣው ነፃነትን ፍለጋ እንጂ ኢህአዴግን ለማደስ አይደለም፡፡ በኢህአዴግ ውስጥ የተፈጠረውን የስልጣን ሽግሽግ በፀጋ የተቀበለው ነፃነት ለማምጣት መሸጋገሪያ ይሆናል በሚል ነው፡፡ የነፃነት አመለካከት ያላቸው ግለሰቦች ወደ ስልጣን መጥተዋል ብሎ ነው የተቀበለው፡፡ ስለዚህ ተግባራዊ እንቅስቃሴ ይጠይቃል፡፡
ለረዥም ጊዜ የውዝግብና የግጭት መነሻ ሆኖ የዘለቀው የወልቃይት ጉዳይ እንዴት መፈታት አለበት ትላለህ?
የወልቃይት ጥያቄ በመሰረታዊነት የዲሞክራሲ ጥያቄ ነው፡፡ ችግሩ ሊፈታ የሚችለው በአካባቢው ህዝብ ፈቃድ ብቻ ነው፡፡ ህዝብ ነው መወሰን ያለበት፡፡ በህዝበ ውሳኔ እልባት ማግኘት አለበት፡፡ በመሰረታዊነት የሃገሪቱ የዲሞክራሲ ጥያቄ ሲመለስ የአካባቢው ህዝብ ጥያቄም መልስ ያገኛል፡፡ ህዝቡ የወልቃይትን ጉዳይ “እኛ ሳንጠየቅ ሌሎች ናቸው በኛ ላይ የወሰኑት፣አሁን ራሳችን መወሰን አለብን” እያለ ነው፡፡ ይሄም ህገ መንግስቱ ያረጋገጠው መብታችን ነው ይላል፡፡ የህዝቡን ጥያቄ  ጠቅላይ ሚኒስትሩ በሚገባ ሊያዳምጡ ይገባል። የወልቃይት ዲሞክራሲያዊ መብት ተነካ ማለት አጠቃላይ የሃገሪቱ ህዝብ መብት ተነካ ማለት ነው፡፡ ስለዚህ ጥያቄው አጠቃላይ ሃገራዊ የዲሞክራሲ ጥያቄ አካል ነው፡፡
ባለፈው ሳምንት የአሜሪካ ኮንግረስ ያጸደቀው HR 128፣ በኢትዮጵያ ላይ በተግባር የሚያሳድረው  ተፅዕኖ ምንድን ነው?
 ወደ ደቡብ አፍሪካ ጉዳይ እንደገና ልመለስና ኔልሰን ማንዴላ ከእስር ሲለቀቁ፣ ሽብርተኛ የተባለው ኤኤንሲ ፍረጃው ተነስቶለት ወደ ሃገር ውስጥ ገብቶ፣ ቢሮ ከፍቶ መንቀሳቀስ ጀመረ። ይሄኔ የምዕራቡ አለም ሰዎች፣ “በቃ ደቡብ አፍሪካ ውስጥ የሚፈለገው ለውጥ መጥቷል፤ ፖለቲከኞች ተፈተዋል፤ ኤንኤንሲም ሽብርተኛ የሚለው ፍረጃ ተነስቶለት ወደ ሃገር ውስጥ ገብቶ እየተንቀሳቀሰ ነው፤ ስለዚህ በደቡብ አፍሪካ ላይ ተጥሎ የነበረው ማዕቀብ መነሳት አለበት” የሚል እንቅስቃሴ ጀመሩ፡፡ በዚህ ሃሳብ ላይ ኤኤንሲ እና ኔልሰን ማንዴላ ተጠየቁ፡፡ ምላሻቸው ግን ፈፅሞ ማዕቀቡ መነሳት የለበትም የሚል ነበር፡፡ “ገና ጅማሮ ላይ ነው ያለነው፤ ይሄ ማዕቀብ ጅማሮ ላይ እያለን የሚነሳ ከሆነ ሊቀለበስ ይችላል፡፡ ወደ ለውጥ ሂደቱ ያስገባን ማዕቀቡ ነው፤ ነገሮች ገና ሳይበስሉ የሚነሳ ከሆነ ወደ ቀድሞ ሁኔታ የማንመለስበት አስተማማኝ ነገር የለም፡፡ ከተቀለበሰ በኋላ እንደገና ማዕቀብ ለመጣል ረዥም ጊዜ ይፈጃል። ስለዚህ ማዕቀቡ መነሳት የለበትም” ሲሉ ተከራክረው ነበር፡፡ ክርክራቸውም ተቀባይነት አግኝቶ ማዕቀቡ  ቆይቷል፡፡ ወደ ኢትዮጵያ ሁኔታ ስንመጣ “ኢትዮጵያ ወደ ለውጥ እየገባች ነው፤ HR 128 ለማጽደቅ ጊዜው አይደለም” የሚል ክርክር ተነስቷል፡፡ ግን የለውጥ ጅማሮው ዳር መድረስ አለበት፡፡ ጅማሮው ዳር እንዲደርስ ደግሞ HR 128 ያስፈልጋል፡፡ የውሳኔ ሃሳቡ ጠቀሜታ ከዚህ አኳያ ነው፡፡
በመንግስት ላይ ተፅዕኖ የሚፈጥረው በምን መንገድ ነው?
በHR 128 ውስጥ አንድ አንቀፅ አለ፡፡ የሰብአዊ መብት ጥሰት የፈፀሙ ባለስልጣናት ወደ አሜሪካ እንዳይገቡ ማዕቀብ ይጥላል፡፡ አንዱ ጠቀሜታ ይሄ ነው፡፡ በመንግስት በኩል እውነተኛ ለውጥ ሳይሆን ጥገናዊ ለውጥ ብቻ የሚደረግ ከሆነ የሰብአዊ መብት ጥሰቱ መቀጠሉ አይቀርም። ከዚህ አንፃር HR 128 እውነተኛ ለውጥ እውን እስኪሆን ድረስ ጠቃሚ ይሆናል፡፡ ይህ የሚደረገው አሁን በኢህአዴግ ውስጥ የተፈጠረውን ለውጥ በመቃወም አይደለም። እንደውም ለውጡ በቂ አይደለም፤ አጠናክሩ ለማለት ነው፡፡ በኢህአዴግ ውስጥ መለወጥ ይገባናል ለሚለው ድምፅም አጋዥ ነው ብዬ አምናለሁ፡፡ ተጨባጭ ለውጥ ከሌለ ኢህአዴግ ከህዝብ ብቻ አይደለም የሚነጠለው። ከ27 ዓመት በኋላ ከዓለማቀፉ ማህበረሰብም ይነጠላል ማለት ነው፡፡ ይህ የመነጠል አደጋ ከፊት ለፊቱ ተጋርጧል፡፡ በአንድ ወቅት የዚምባቡዌው ሙጋቤ ከዓለማቀፉ ማህበረሰብ እንደተነጠሉት ማለት ነው፡፡
የማዕከላዊ ምርመራ ቢሮ መዘጋት የሰብአዊ መብት ጥሰትን ለመከላከል ፋይዳ ይኖረዋል ብለህ ታምናለህ?
በነገራችን ላይ ማዕከላዊ ለኔ ሌላኛው ቤቴ ነው። ከጥፊ ጀምሮ ተገልብጦ እስከ መገረፍ የሚደርስ የሰብአዊ መብት ጥሰት ተፈፅሞብኛል፡፡ ይህን የፈጸሙብኝ ፖሊሶቹ አይደሉም፤ ሥርአቱ ነው፡፡  የሰብአዊ መብት ጥሰት የሚፈፅመው ስርአቱ እንጂ እንደኛ ሰው የሆኑት ፖሊሶች አይደሉም፡፡ ከዚህ አንፃር ማዕከላዊን በመዝጋት ብቻ የሰብአዊ መብት ጥሰትን ማስቆም አይቻልም፡፡ ከምንጩ ለማድረቅ ከተፈለገ ስርአቱን ነው መለወጥ ያለብን፡፡ የሰብአዊ መብት ጥሰቶችን ከምንጫቸው የሚያደርቀው የዲሞክራሲያዊ ስርአት መመሥረት ብቻ ነው። ለፖሊሶች ስልጠና መስጠትና ማዕከላዊን መዝጋት ብቻውን መፍትሄ አይሆንም፡፡ የሰብአዊ መብት ጥሰት የአምባገነናዊ ስርአት ባህሪ ውጤት ነው፡፡ አምባገነናዊ ስርአት እስካለ ድረስ ግድያ፣ እስራት፣ የሃሰት ክስ አለ፡፡ ስለዚህ ከምንጩ ነው ማድረቅ ያለብን፡፡ ምናልባት የማዕከላዊ መዘጋት ኢህአዴግ ለውጥ እንደሚያመጣ   ምልክት ከሆነ እሰየው ነው።
ዛሬ ወደ ውጪ አገር ትበራለህ፡፡ እዚያው የመቅረት ሃሳብ አለህ ወይስ ትመለሳለህ?
እኔ ልቅር ብልም ባለቤቴ እዚያ አታስቀምጠኝም። ህዝብን ከድተህ እኔ ጋር አትቀመጥም ብላ ነው የምታባርረኝ፡፡ ዲሞክራሲያዊ ስርአት እስክናገኝና ትግሉ ዳር እስኪደርስ ድረስ ውጭ ሃገር እኖራለሁ ብዬ አላስብም፡፡ የተነሳንበት፣ የታሰርንበት ዓላማ ከዳር መድረስ አለበት፡፡ የሚቻል ነው ብዬ ስለማምን እስከ መጨረሻው ድረስ እታገላለሁ፡፡ ይሄ ደግሞ የኔ ብቻ ሳይሆን የቤተሰቤም አቋም ነው፡፡

  በደራሲ መካሻ አበራ የተፃፈው “መንግሥትና የግለሰብ ነፃነት” መፅሀፍ ገበያ ላይ ዋለ፡፡ መፅሐፉ በዋናነት የብአዴን ጽ/ቤት ኃላፊ በሆኑት አቶ አለምነው መኮንን የተፃፈው “ፖለቲካ፣ ኢኮኖሚና የኢትዮጵያ ህዳሴ” ለተሰኘው መጽሀፍ ምላሽ የሚሰጥ ነው ተብሏል፡፡ በአምስት ዋና ዋና ምዕራፎች የተከፋፈለው መፅሃፉ በሪበራል ዴሞክራሲና ገበያ አክራሪነት፣ በምዕራባዊያን የገበያ አክራሪነትና ሊበራል ዴሞክራሲ የቀረበውን ትችት በተመለከተ አጠቃላይ እይታና በበርካታ ጉዳዮች ዙሪያ የሚያጠነጥን ነው፡፡ በ240 ገፅ የተመጠነው መፅሀፉ በ65 ብር እየተሸጠ ነው፡፡

• የዳግማዊ አፄ ቴዎድሮስ ፋውንዴሽን ለማቋቋም ስምምነት ላይ ደርሰናል
  • ቅርሶችን ከውጭ አገራት የማስመለስ ከፍተኛ መነቃቃት ተፈጥሯል
  • እንግሊዞች የመቅደላ አምባ ሙዚየም ግንባታን ማገዝ አለባቸው

    የዳግማዊ አፄ ቴዎድሮስ 150ኛ ዓመት ዝክረ  በዓል “መስዋዕትነት ለብሔራዊ ኩራት” በሚል መሪ ቃል ከሚያዝያ 2-8 ቀን 2010 ዓ.ም በጎንደር፣ ደብረታቦርና መቅደላ በተለያዩ ዝግጅቶች ተከብሯል፡፡ ባለፈው ሰኞም በአዲስ አበባ ጌትፋም ሆቴል የመዝጊያ ሥነ ሥርዓቱ በደመቀ ሁኔታ የተከናወነ ሲሆን በዝግጅቱ ላይም የባህልና ቱሪዝም ሚኒስትር ዶ/ር ሂሩት ወ/ማሪያም፣ ፕ/ር እንድሪያስ እሸቴ፣ ፕ/ር ባህሩ ዘውዴ፣ ፕ/ር ማሞ ሙጨ፣ የጎንደር ዩኒቨርሲቲ ፕሬዚዳንት ዶ/ር ደሳለኝ መንገሻ፣ የአማራ ክልል ባህልና ቱሪዝም ቢሮ ኃላፊ ዶ/ር ሂሩት ካሣው እንዲሁም ጥሪ የተደረገላቸው አርቲስቶችና የዳግማዊ አፄ ቴዎድሮስ ቤተሰቦች ተገኝተዋል፡፡
ከአፄ ቴዎድሮስ 150ኛ ዓመት ዝክረ በዓል ዝግጅት ምን ውጤት ተገኘ? በክብረ በዓሉ ላይ የተመሰረተው ጊዜያዊ የቅርስ አስመላሽ ኮሚቴ ዓላማ ምንድን ነው? ሳይገነባ ከ10 ዓመት በላይ የቆየው የመቅደላ አምባ ሙዚየም ዕጣ ፈንታ ምንድን ነው? አደጋ የተጋረጠባቸውን ላሊበላና ጣና ሐይቅን ማነው የሚታደጋቸው?---የአዲስ አድማስ ጋዜጠኛ ናፍቆት ዮሴፍ፤ ከባህልና ቱሪዝም  ሚኒስትሯ ዶ/ር ሂሩት ወ/ማሪያም ጋር በእነዚህና ሌሎች የቱሪዝም ዘርፍ ጉዳዮች ተከታዩን ቃለ ምልልስ  አድርጋለች፡፡

   የዳግማዊ አፄ ቴዎድሮስ 150ኛ ዓመት ዝክረ በዓል፣ ለሳምንት ገደማ ከጎንደር እስከ አዲስ አበባ፣ በተለያዩ ዝግጅቶች ተከብሯል፡፡ ከዚህ ክብረ በዓል ምን ውጤት ተገኘ?
ይህ ዝክረ በዓል ትልቅና ታሪካዊ ነው ብሎ በሙሉ ልብ መናገር ይቻላል፡፡ በዚህ የአፄ ቴዎድሮስ 150ኛ ዓመት ዝክረ በዓል ላይ ብዙ ዝግጅቶች ተከናውነዋል። ከአጼው የትውልድ ቦታ ራሳቸውን በክብር እስከ ሰዉበት መቅደላ ድረስ ታሪካዊ አሻራቸውን ያኖሩባቸው ቦታዎች ተጎብኝተዋል፡፡ የመዝጊያ ሥነ ስርዓቱም በአዲስ አበባ ጌትፋም ሆቴል በደመቀ ሁኔታ ተከናውኗል። እንግዲህ ምን ውጤት ተገኘ ለተባለው፣ አፄው በዘመናቸው ከሰነቋቸው ራዕዮች የአሁኑ ትውልድ ምን መማር ይችላል፣ የእርሳቸው ትሩፋቶች ምንድን ናቸው፣ አገርን ከማልማት፣ ከማዘመንና አንድ ከማድረግ አኳያ ህልማቸው ምን ነበር ወዘተ--የሚሉትን ለመፈተሽ ያስቻለ ሁነት ነበር ማለት ይቻላል። ከአፄው ስኬት ብቻ ሳይሆን ከውድቀታቸውም፣ ከውጭም ከውስጥም ከገጠሟቸው ፈተናዎች ምን እንማራለን? የህልማቸው ጫፍ ላይ እንዳይደርሱ ፈተና የሆነባቸው ምን ነበር? የሚሉትን እንድናይ፣ የአሁኑ ትውልድም ትምህርት እንዲቀስም ትልቅ አጋጣሚ ፈጥሯል፡፡ ሌላው ደግሞ በየቀኑ በንጉሱ ህይወት ላይ የሚያጠነጥኑ፣ ጥልቅ ምርምር የተደረገባቸው የጥናት ጽሁፎች በትላልቅ የአገር ውስጥና የውጭ ምሁራን እየቀረቡ፣ ስንማርና ዕውቀታችንን ስናሰፋ ነው የቆየነው፡፡
በጎንደር ዩኒቨርሲቲ ሳይንስ አምባም ሆነ በአዲስ አበባ፤ በውጭ የሚገኙና እየተመለሱ ያሉ ቅርሶቻችንን፣ የልዑል አለማየሁን ፎቶግራፍ፣ የአፄውን የክብርና የንግስና ጌጣጌጦች እንዲሁም ዲፕሎማሲያዊ ግንኙነት ያደረጉባቸው ደብዳቤዎችን ያካተተ የፎቶግራፍ አውደ ርዕይ ለእይታ ቀርቦ ነበር፡፡ ከዚህም ብዙ እውቀት መቅሰም ተችሏል፡፡ ጋዜጠኞች የአፄው ዱካዎች ያረፉባቸው ታሪካዊ መዳረሻዎችን ጎብኝተው በየሚዲያዎቻቸው በማስተላለፍ፣ ለማህበረሰቡ ትልቅ መነቃቃትና ግንዛቤ ፈጥረዋል፡፡ እነዚህ ሁሉ እንግዲህ የዚህ ዝክረ በዓል ትሩፋቶች ናቸው፡፡
በሌላ በኩል እነዚህን ታሪክ የተሰራባቸውን ቦታዎች በሚገባ አልምተን፣ እንዴት የቱሪስት መዳረሻ ማድረግ እንደምንችል አቅጣጫ ያሳየና ትልቅ ትምህርት የተወሰደበት ነው፡፡ ጠቅለል ስናደርገው፤ ስለ አፄ ቴዎድሮስ ያለን እውቀት ሰፍቷል፤ የምንወስደውን ትምህርት ለይተን ከቱሪዝም ጋር አቀናጅተን ምን መጠቀም እንችላለን የሚለውን ተገንዝበናል፣ የአፄ ቴዎድሮስ ፋውንዴሽን እንዲቋቋም ሀሳብ ቀርቦ፣ በደብረ ታቦር ለማቋቋም ስምምነት ላይ ደርሰናል። መቅደላ ላይ ደግሞ ሙዚየም ለማቋቋም ተስማምተናል፡፡
በዚህ ዝክረ በዓል ላይ ከኢትዮጵያ ተዘርፈው በእንግሊዝ ሙዚየሞች የሚገኙ ቅርሶችን የማስመለስ ጉዳይ ትልቅ ትኩረት የተሰጠው ይመስላል---  
እውነት ነው፣ጉዳዩ ትልቅ ትኩረት ተሰጥቶታል። እንደሚታወቀው አፄው መጨረሻ ላይ ራሳቸውን ሲሰዉ፣ እንግሊዞች ልጃቸውን ወስደዋል፤ ሽሩባቸውን ከራሳቸው ላይ ገፍፈው ወስደዋል፣ ልብሶቻቸውን ሳይቀር ቆራርጠው ተቀራምተውታል፡፡ በግምጃ ቤታቸው ያጠራቀሟቸው የአገራችን የእጅ ጥበብ ውጤት የሆኑ በርካታ አይነት ቅርሶችንም (የፅሁፍ፣ ጌጣጌጦች፣ አልባሳት፣ ታቦታት፣ ዘውዶችና ሌሎች በርካታ ሀብቶች) ዘርፈዋል፡፡ ከ200 በላይ በሚሆኑ በቅሎዎችና ከ20 በላይ በሆኑ ዝሆኖች ጭነው ነው የወሰዱት፡፡
እንደውም በእንግሊዝ አገር ያሉ ቅርሶቻችን እስከ 2 ቢሊዮን ፓውንድ እንደሚያወጡ ይነገራል….
እውነት ነው፤ ከዚያም በላይ ናቸው፡፡ በነገራችን ላይ የተዘረፉትን ቅርሶች አይነትና መጠን ስንመለከት፤ አፄ ቴዎድሮስ በዚያ ቦታ ላይ ቤተ መፅሐፍትና ሙዚየም የማቋቋም ሀሳብ ነበራቸው ለማለት ያስችላል፡፡ ይህን የሚያመላክት ጥልቅና አሳማኝ ጥናትም ዛሬ በዚሁ መድረክ ላይ ሲቀርብ ተመልክተሻል፡፡ ምክንያቱም እሳቸው ከውጭ ማለትም ከአውሮፓና ሌሎች አገራት ጋር በፈጠሩት ዲፕሎማሲያዊ ግንኙነት፣ ስለ ቤተ-መፃሕፍትና ስለ ሙዚየም ጥሩ ግንዛቤ ነበራቸው።  መቅደላ ላይ በብዛት የነበሩት ቅርሶችም ከመላ አገሪቱ የሰበሰቧቸው ነበሩ፡፡ የቅርሶቹ በአንድ ቦታ ላይ መገኘት፣ ለዘራፊዎቹ ምቹ ሁኔታን  ፈጥሮላቸዋል፡፡
እነዚህ ከአገራችን የተዘረፉ ሀብቶችን በማስመለስ ረገድ በህግና በዲፕሎማሲ ምን ስራዎች መሰራት አለባቸው፣ በዚህ እንቅስቃሴ ውስጥ የሚሳተፉ ባለድርሻ አካላት እነማን ናቸው፣ ምሁሩ አርቲስቱ፣ ሚዲያው፣ ባህልና ቱሪዝም፣ የውጭ ጉዳይ መስሪያ ቤት--ምን ምን የቤት ስራዎች ይውሰዱ፣ ምን አይነት ስልቶችስ ይቀየሱ --- የሚሉ በርካታ ምክረ ሃሳቦች ቀርበዋል፡፡ በአገር አቀፍ ደረጃም ከፍተኛ መነቃቃት ተፈጥሯል፡፡ ከዚህ ባሻገር ጠንካራ ቅርስ አስመላሽ ብሔራዊ ኮሚቴ ለማቋቋም ጊዜያዊ አስተባባሪ ኮሚቴ ተመስርቷል፡፡ ስለዚህ እጅግ የተዋጣለት፣ ብዙ ውጤት የተገኘበት ሁነት ነው፡፡ ይህን ኢንሺየቲቭ የወሰደውን ጎንደር ዩኒቨርሲቲንና በዚህ ክብረ በዓል ላይ አሻራቸውን ያሳረፉ ዩኒቨርሲቲዎችን፣ የባህልና ቱሪዝም ቢሮ ጽ/ቤቶችን እንዲሁም ተሳታፊ ድርጅቶችንና ግለሰቦችን ለማመስገን እወዳለሁ፡፡
የእንግሊዝ መንግሥት ቅርሶቻችንን በረጅም ጊዜ ውሰት ለኢትዮጵያ ለመስጠት ጥያቄ ቢያቀርብም  የኢትዮጵያ መንግሥት “ሰው ንብረቱን ይወስዳል እንጂ አይዋስም” በሚል ጥያቄውን ውድቅ ማድረጉ ተነግሯል፡፡ “ብልጥ ልጅ የያዘውን ይዞ ያለቅሳል” እንዲሉ፣ቅርሶቹን በውሰት ተቀብሎ ሙሉ ለሙሉ ለማስመለስ ጥረት ማድረግ አይሻልም ነበር?
በነገራችን ላይ የእንግሊዝ መንግሥት አቀረበ የተባለው ጥያቄ  በቀጥታ ለእኛ አልቀረበልንም። ለባህልና ቱሪዝም ሚኒስቴርም ሆነ ለሌላ የትኛውም የመንግሥት አካል “ቅርሱን ለረጅም ጊዜ ተውሳችሁ ውሰዱ” የሚል ጥያቄ በቃልም በፅሁፍም አልመጣልንም፡፡ እኛም የሰማነው “ዘ ጋርዲያን” ከተባለ ጋዜጣና ከሌሎች የእንግሊዝ ሚዲያዎች  ነው፡፡ እኛን የጠየቀንም ያማከረንም የለም፡፡ የእንግሊዝ መንግስት ከምን ተነስቶ ሀሳቡን እንዳነሳው የምናውቀው ነገር ስለሌለ መልስ ለመስጠት፣ ለመቀበልም ሆነ ሌሎች አማራጮችን ለማየት አልተንቀሳቀስንም፡፡ እርግጥ እኛ እንደ መንግስት ሀብታችን ይመለስልን የሚል ጥያቄ አቅርበናል፡፡ በ2007 ዓ.ም ይህ ጥያቄ በርዕሰ ብሔሩ ፊርማ ተልኳል፡፡ ግን መልስ አልሰጡም፤ እኛም በተለያየ መንገድ ጥያቄ ማቅረባችንን ቀጥለናል፡፡
እርስዎ ሚኒስቴር መሥሪያ ቤቱን መምራት ከጀመሩ በኋላ ተሳክቶልኛል ብለው የሚጠቅሱት ሥራ ወይም ፕሮጀክት ካለ ቢነግሩኝ?
ገና እኮ ነው! ይሄ አልቋል፣ አሳክቸዋለሁ ልልሽ አልችልም፡፡ ነገር ግን በዚህም በዚያም የሚታየው ጅምር ሁሉ ተስፋ ሰጪ ነው፡፡ በነገራችን ላይ ስኬት ሂደት ነው፡፡ ለምሳሌ ዛሬ እኛ የምናመቻቸው፣ የምንቀይሰው ነገር እውን የሚሆነው፣ ከኛ ቀጥሎ በሚመጡት መሪዎች ሊሆን ይችላል፡፡ ለዚህ ነው ሂደት ነው የምልሽ። ተስፋ ሰጪ ነገሮች እየሰራን ነው፤ ያንን ነዳጅ ጨምረን ፍጥነታችንን አሳድገን ወደፊት መሄድ ነው፡፡ አገራችን የረጅም ጊዜ ታሪክ፣ ስልጣኔና ቅርስ ባለቤት እንደመሆኗ፣ ይህችን ትልቅ አገር አጉልቶ ታሪኳን፣ ስልጣኔዋንና ቅርሷን ለማሳየት በርካታ ስራ መሰራት አለበት፡፡ ለዚህ ደግሞ ብዙ ርብርብ ይጠይቃል፡፡ አመለካከትን መቀየር፣ ቅርስንና ሀብትን ወደ ብሔራዊ ጠቀሜታ መለወጥ ያስፈልጋል፡፡
እርስዎ ከተሾሙ በኋላ ሁለት ጊዜ የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ታውጇል፡፡ ይህ ደግሞ በዋናነት እርስዎ የሚመሩትን የቱሪዝም ዘርፍ የሚጎዳ ነው፡፡ በአገሪቱ ላይ ተፈጥሮ የነበረው የሰላም መታወክና አለመረጋጋት በቱሪዝም ላይ ያሳደረው ተጽዕኖ ምን ያህል ነው?
ቱሪዝም እንደሚታወቀው በመጀመሪያ ደረጃ የሚፈልገው ሰላምና መረጋጋትን ነው፡፡ ይሄ ግልፅ ነው። አንድ ቱሪስት ከአንድ አገር ወደ ሌላ አገር ለመዘዋወር መጀመሪያ የሚጠይቀውና የሚያጠናው የሚሄድበትን አገር ደህንነት፣ ሰላምና መረጋጋት ነው፡፡ ከዚህ አንፃር እኛም አገር ተፅዕኖ ማሳረፉ የሚካድ አይደለም፡፡ በተለይ ደግሞ አንዳንድ አገሮች የሚያወጧቸው የጉዞ መረጃዎች የተጋነኑ መሆናቸው፣ ዘርፉ ላይ ተፅዕኖ ማሳረፉ ምንም ጥያቄ የለውም፡፡
ሆኖም እነ እስራኤልን ብትመልከቺ፣ በየቀኑ ቦንብ እየፈነዳ ውሎ የሚያድርበት አገር ነው። ግብፅና ሌሎችም አገራት እንደዛው ናቸው፡፡ በዓለም ላይ ሙሉ በሙሉ ወይም መቶ ፐርሰንት መረጋጋት አለ ማለት አይቻልም፡፡ ግን እስራኤልም ሆነ ሌላው አገር ቱሪስት እንደ ጉድ ይጎርፋል፡፡ ነገር ግን ኢትዮጵያ ውስጥ ትንሽ ኮሽ ሲል የሚጋነን ነገር  አለው፡፡ የሆነ ሆኖ የአገሪቱን ገፅታ ለመመለስ በተደረጉ የተለያዩ ጥረቶች፣የቱሪስት ፍሰት የተፈራውን ያህል አልቀነሰም ማለት ይቻላል፡፡
በአሁኑ ወቅት እመጣለሁ ብሎ ጉዞ የሰረዘ ቱሪስት የለም፡፡ ሰሜን ተራሮች ብትሄጂ ቱሪስት በብዛት አለ። ሌሎች የቱሪስት መዳረሻዎችም ላይ እንዲሁ፡፡ ነገር ግን አሁንም ጠንክረን መስራት ይኖርብናል፡፡ ከዚህም በኋላ የቱሪስቶች መምጣትና መቅረት፣ በምንሰራው ሥራ የሚወሰን ነው የሚሆነው፡፡ ከዚህ አኳያ የተለያዩ ስራዎች እየሰራን ነው፡፡ አሁን አገሪቱ የተረጋጋ ሁኔታ ላይ ነው ያለችው፡፡ ለየትኛውም ቱሪስት የስጋት ምንጭ የሆነ ነገር የለም፤ግን አሁንም ከዚህ በተሻለ መስራት አለብን፡፡
በላሊበላና በጣና ሀይቅ ላይ ትልቅ አደጋ መጋረጡ ቢታወቅም፣ እነዚህን ቅርሶች ለመታደግ መንግሥት በተለይም እርስዎ የሚመሩት መሥሪያ ቤት ዳተኝነት አሳይቷል የሚል ወቀሳ ይሰነዘራል፡፡ የእርስዎ ምላሽ ምንድን ነው?
ምንም ዳተኝነት የለም፤ ማድረግ ያለብንን ሁሉ እያደረግን ነው፡፡ አገራችን የበርካታ ተፈጥሯዊና ሰው ሰራሽ ሀብቶች ባለቤት እንደ መሆኗ፣ ቅርሶቿ ፈተና ይገጥማቸዋል፡፡ ይሄ በየትኛውም ዓለም ያለ ነገር ነው፡፡ ሁሉም ነገር ዘላለማዊ አይደለም፡፡ ከዚህ አኳያ ላሊበላን ያየን እንደሆነ፣ ረጅም እድሜ ያለው ጥንታዊ፣ከአንድ አለት የተፈለፈለ፣ አለቱም በቀላሉ የሚፈረካከስና ውስብስብ አርክቴክቸራል አሻራ ያረፈበት ትልቅ የአብያተ ክርስቲያናት ቅርስ ነው፡፡ እንግዲህ ቅርሱ ከእድሜውም ባሻገር በዝናብና በፀሐይ የተለያዩ ጉዳቶች ደርሶበታል፡፡ በተጨማሪም ከዚህ በፊት የተደረጉ የጥገና ስራዎች ለምሳሌ፡- ጥላው (ሼዱ) ተፅዕኖ አሳድሮበታል የሚል ከፍተኛ ስጋት አለ፡፡
እርስዎ  ቦታው ድረስ ሄደው ችግሩን  አይተውታል?
ኦው… በጣም ብዙ ጊዜ! በነገራችን ላይ እዚህ መስሪያ ቤት እንደተመደብኩ መጀመሪያ የሄድኩትም ላሊበላ ነው፡፡ ከስጋቱ አኳያ አንድ አጥኚ ቡድን አቋቁመን፣ ጥናት አካሂዶ ውጤቱን ሰጥቶናል፡፡ የጥናቱ ውጤት የሚያሳየውም ችግሩ አስጊ መሆኑን ነው፡፡ ስለሆነም ችግሩን ለመቅረፍ የባህልና ቱሪዝም ሚኒስቴር እንዲሁም የቅርስ ጥናትና ጥበቃ ባለስልጣን በርካታ ሥራዎችን እየሰሩ ነው፡፡  
ለምሳሌ ሊጠቅሱልኝ ይችላሉ---?
አንደኛ ከዩኔስኮና ይህንን ሼድ ከሰራው ኩባንያ ጋር ተገናኝተን በመነጋገር፣ባለፉት ሶስት አራት ቀናት አንድ ቡድን መጥቶ ላሊበላን እያየው ይገኛል፡፡ አሁን ነገ (ሰኞ ነው ቃለ ምልልሱ የተደረገው) ከእኛ ጋር ስብሰባ አላቸው። እነዚህ ባለሙያዎች ችግሩ በትክክል ምን ደረጃ ላይ እንዳለ ይነግሩናል፡፡ የባለሙያዎች ቡድኑ ከጣሊያንና ከዩኔስኮ የተውጣጡ ናቸው። እነሱ የሚሉትን እንሰማለን፡፡ የእኛ ባለሙያዎችም ያጠኑት አለ። እነሱም እይታቸውን ይገልፁልናል፡፡ ዞሮ ዞሮ እኛ ሪስክ አንወስድም፤ትንሽም ቢሆን የሚያሰጋን ነገር ካለው እንደ መንግስት ሼዱ እንዲነሳ ነው የምንፈልገው።
ላሊበላን ለመታደግ ከፍተኛ ገንዘብ ያስፈልጋል ተብሏል፡፡ ይሄን ገንዘብ ከየት ለማግኘት ነው ያቀዳችሁት?
እንዳልሺው እጅግ ብዙ ገንዘብ ያስፈልጋል፡፡ ምን ያህል ነው ለሚለው የተለያየ ግምት አለ፤ ግን ገና ዝርዝሩ አልተሰራም፡፡ ዞሮ ዞሮ በሚኒስቴር መስሪያ ቤታችን ወይም በቅርስ ጥናትና ጥበቃ ባለስልጣን አቅምና በጀት የሚሰራ አይደለም፡፡ ሀገራዊ ንቅናቄ ተፈጥሮ፣ ሀብት መሰብሰብ አለበት። ይህንን ጉዳይ በተመለከተ ከጠቅላይ ሚኒስትር ቢሮ ጋር ተነጋግረናል። በተለይ ከምክትል ጠ/ሚኒስትሩ ጋር ረጅም ውይይት አድርገን፣ ጥናቱን ያቀረብንላቸው ሲሆን አንድ አገራዊ ኮሚቴ እንደሚቋቋምና የላሊበላ ጉዳይ ብሔራዊ አጀንዳ እንደሚሆን ተወስኗል፡፡ በተለይ ከቱሪዝም ዘርፉ ጥቅም የሚያገኙ አካላት በሙሉ፡- ቤተ ክህነት፣ ቱር ኦፕሬተሮች፣ አየር መንገድና ሆቴሎች እንዲሁም ሁሉም ኢትዮጵያውያን እንዲረባረቡና የበኩላቸውን እንዲወጡ፣ የፌደራልም ሆነ የክልል መንግስታትም ተባብረው የሚያስፈልገውን ሀብት በማሰባሰብ ስጋቱ እንዲቀረፍ ለማድረግ ስምምነት ላይ ደርሰናል። በቅርቡ ይህንን ብሔራዊ አጀንዳ አድርገን ለህዝቡ እናስተዋውቃለን፡፡
የጣናም ጉዳይ ከላሊበላ በባሰ መልኩ ትልቅ ፈተና ነው፡፡ እንደሚታወቀው ዩኒቨርሲቲዎቻችን ምርምር እያካሄዱ ነው፡፡ እንዴት አድርገን መጤውን አረም እናስወግዳለን የሚለውን ጥያቄ ለመመለስና በእውቀት ላይ የተመሰረተ እርምጃ ለመውሰድ የሚያስችል ስራ እየተሰራ ነው፡፡
የውጭ አገራት የወሰዱብንን በርካታ ቅርሶች ለማስመለስ እየጣርን ነው፡፡ ነገር ግን  አፄ ቴዎድሮስ ከተወለዱበት እስከ ተሰዉበት ባሉት ታሪካዊ ቦታዎች ላይ የሚገኙት ቅርሶች ሙዚየም የላቸውም፡፡ አጼው በነገሱባት የዳናሞራዋ ደራስጌ ማርያም እጅግ ውድ ታሪካዊ ቅርሶች አልባሌ ቦታ ላይ ነው የሚገኙት፡፡ እዚህ ያሉት ቅርሶች በአግባቡ የሚቀመጡበት ሳያገኙ  ከውጭ የሚመጡትን የት ልናደርጋቸው ነው---?
እርግጥ ነው እስካሁን ብዙ ሙዚየም አልገነባንም። በርካታ ሙዚየሞች ያስፈልጉናል፡፡ እጅግ በርካታ ልናሳየው የምንችለው ሀብት አለ፡፡ ስለዚህ ሙዚየሞች በብዛት መገንባት አለባቸው። ሙዚየም የሚገነባው ደግሞ በመንግሥት ብቻ አይደለም፡፡ የሃይማኖት ተቋማት፣ ከፍተኛ የትምህርት ተቋማት ሙዚየም መገንባት አለባቸው፡፡ ለምሳሌ አዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ትልቅ ኤትኖግራፊክ ሙዚየም አለው፡፡ ግለሰቦችም ሆኑ መንግሥት ሙዚየሞችን መገንባት አለባቸው። የክልልም የፌደራልም ተቋማት ሙዚየም መገንባት ይገባቸዋል፡፡
ሆኖም  የውጭዎቹ ቅርሶች ይመለሱልን እንጂ የምናስቀምጥበት አናጣም፡፡ በነገራችን ላይ በየቦታው የተጀማመሩ የሙዚየም ፕሮጀክቶች አሉ፡፡ ለምሳሌ የመቅደላ አምባ ሙዚየም በሀሳብ ደረጃ ቀርቧል፤ ያንን ተረባርቦ መገንባት ያስፈልጋል፡፡ እንግሊዞችም እንደ ካሣ፣ ይህን ግንባታ ማገዝ አለባቸው፡፡ በግንባታ ብቻም ሳይሆን ባለሙያን በማሰልጠን ሊያግዙን ይገባል። እንግሊዞች ብቻ ሳይሆኑ ሌሎች የእኛን ቅርሶች ወስደው ሲጠቀሙ የነበሩም ሆነ እየተጠቀሙ ያሉ አገራት ድጋፍ ማድረግ አለባቸው፡፡ እኛም ትኩረት ሰጥተን በጀት መድበን፣ ከህዝቡም አሰባስበን፣ በርካታ ሙዚየሞችን መገንባት አለብን፡፡ ይህ እንዳልኩት የሁሉንም ርብርብ ይጠይቃል፡፡  

 “--ለአውጉስጢን ታላቅ ክብር ያለው ጥበብ ሃይማኖት ነው፤ የዕውቀቶች ኹሉ መዳረሻ ለሃይማኖት ማገልገል መቻል ነው፤ ፍልስፍና
ከተፈጥሮ ጋር የተናበበችና በምክንያት የምትመራ ስለኾነች ለክርስትና ሃይማኖት መልካም አገልጋይ መኾን ትችላለች፡፡--”

    መግቢያ
ቅኔ ከፍልስፍና ጋር ባለው ግንኙነት ዙሪያ የምናደርገውን ምርመራ በግሪክ ፈላስፎች ዙሪያ ተሽከርክረን፣ ባለፈው ሣምንት የአርስቶትልን ክርከር ዐይተን ነበር ያቆምነው፤ ለዛሬው የቅዱስ አውጉስጢን (St. Augustine) ዕይታ እንቃኛለን፡፡
ቅ. አውጉስጢን የተወለደውና የተማረው በሰሜን አፍሪቃ ነው፤ የኖረበት ዘመን እ.ኤ.አ ከ354- 430 ዓ.ም ነው፡፡ ክርስቲያን ሳይኾን በፊት በሚላን እና በካርቴጅ አስተማሪ እና የት/ቤቶቹ ቀዳሚ ሊቀመንበር ነበር፤ ክርስትናን ከተቀበለ በኋላ ግን ወደ ሰሜን አፍሪቃ ተመልሶ የመኖኮሳት ማኅበርን መሠረተ፡፡ ከዚያም ክህነት ተቀብሎ በሂጶ ጳጳስ ኾነ፡፡ ቅ. አውጉስጢን በተለየ የሚታወቅበት ሥራው የእግዚአብሔር መናገሻ (The City of God) በሚለው መጽሐፉ ነው፡፡
ሊቁ አውጉስጢን ቀድሞ ባለቅኔ ነበር፤ እንዳውም በቅኔው ተወዳድሮ በማሸነፍ እሰከ መሸለም ደርሶ እነደነበር ይነገራል፤ ኋላ ግን ክርስቲያን ሲኾን ያ ኹሉ መውደስ ለባዕድ አምልኮ የሚቀርብ መኾኑን ተረዳ። ስለዚህ ቅኔን ገሸሽ በማድረግ ወደ ማራከስ ዞረ፤ ፍልስፍናንም የክርስትና ሃይማኖት ገረድ አድርጎ በመቅጠር፣ የፕሌቶ የቅኔና የፍልስፍና ንትርክን ቀይሮ፣ በቅኔና በሃይማኖት መካከል የሚደረግ ‹የእኔ እበልጥ እኔ እበልጥ›  ፉክክር አድርጎ ሞገተ፡፡
በአውጉስጢን ላይ ተፅእኖ ያሳደሩ ሦስት ሰዎች አሉ፡- ፕሌቶ፣ ፕሎጢኑስ (Plotinus) እና ማርቆስ ቫሮ (Marcus Varro) ናቸው፡፡ ፕሌቶ ቅኔን በቅጅ ቅጅነትና በተረትነት በመፈረጁ ‹አደገኛ› የሚል ‹ታፔላ› ለጥፎቦታል፤ አውጉስጢንም እንደ ፕሌቶ ቀድሞ የባዕድ አምልኮን አወዳሽ ባለቅኔ ስለነበር፤ ክርስቲያን ከኾነ በኋላ ቅኔን በማንከዋሰስ ከፕሌቶ ጋር ተስማማ፤ በዚህ የተነሣም የፕሌቶ አወዳሽ ለመኾን በቃ፡፡ የThe City of God የሚለው መጽሐፉ የመጀመሪያ ክፍልም ለፕሌቶ ውደሳ ያሽጎደጎደበት ነው፡፡ አውጉስጢን ለፕሌቶ ውዳሴውን በማሽጎድጎድ የቸረው ቅኔን በቅጅ ቅጅነትና በተረትነት አወራርዶ ስላቃለለ እና በአደጋነት ስለፈረጀ ነው፡፡
ሌላው የፕሌቶ አስተምህሮ ፕላቶናዊያንን አስገኝቷል፤ አውጉስጢን ወደ ክርስትና ሲቀየር ሰብዕናውንና አስተሳሰቡን የቀየሩትና ተጽዕኖ ያደረጉበት እነዚህ ፕላቶኒያውያን ሲኾኑ በተለይ ፕሎጢኑስ እና ቫሮ ግንባር ቀደሞቹ ናቸው። የእነዚህ ሐሳቢያን ተፅእኖም በአውጉስጢን የፈጠራና የአስተውሎት ችሎታ እየተሽከረከረ ወደ የቅኔ እና የሃይማኖት ፉክክር አድርሶታል፡፡
የፕሎጢኑስ ተፅእኖ
አውጉስጢን መጀመሪያ ከክርስትና ጋር ሲገናኝ ‹በመጀመሪያ ቃል ነበር፤ ቃልም በእግዚአብሔር ዘንድ ነበር፤ ቃልም እግዚአብሔር ነው› የሚለው የዮሐንስ ወንጌል ጥቅስ፣ በፕሎጢኑስና በደቀ መዝሙሩ ፖርፊሪ (Porphyry) እየተተረጎመ ተብራርቶ አገኘው። ቃል ደግሞ በፅርዕ (በግሪክ) ሎጎስ ስለሚባል የቃልም ትርጉም አመክንዮ (ምክንያተ ነገር) ማለት መኾኑን ተረዳ፤ የምክንያት ትስስርም ከቅኔ የበለጠ ከሰማያዊ ፍልስፍና ጋር እንደኾነ በማየትም በምክንያት ለምትመራው ፍልስፍና የበለጠ ክብር ሰጠ፡፡
ፕሎጢኑስ የፈላስፎችና የባለቅኔዎች ሥራ በከፍተኛው የማሰላሰል ደረጃ ላይ ሊገናኝ (ሊገጣጠም) ይችላል ይላል፤ ልዩነቱን የሚፈጥረው ማሰላሰልን በዕውቀት (በሥልጠና) የመደገፍ ኹኔታ ስለኾነ ለባለቅኔዎች፣ ለሙዚቀኞችና ለሌሎች የአርት ሰዎች ፊት ለፊት ከሚታየው ክስተት ባለፈ ያለውን መስተጋብር እንዲያስተውሉ፤ እዚያ ማዶ (ከአካባቢያቸው ባለፈ) ያለውን ራዕይ እንዲይዙ ይመክራል፡፡
ስለ ተረት በጥልቅ አስተውሎቱ ፕሌቶን ራሱ ‹የተረት ጸሐፊ ነው› ብሎ ይሞግታል፡- ፕሎጢኑስ፤ ይህ የፕሌቶ ተረትም በማስደነቅ ምሥጢር ይዞ የየትኛውንም አስተሳሰብ ጥልቀትና ስፋት ለመመርመር መነሻ ይኾናል፤ ይህንንም ማወቅና መረዳት የምንችለው ዘይቤያዊ ስልቶችን (በማመሳሰል፣ በማነጻጸር፣ በመወከል፣…) በመጠቀም መኾኑን ሞግቷል፡፡
ፍልስፍናዊ አሰላስሎትም ባለቅኔውን የቅኔን የተፈጥሮ ገላጭነትና ተፈጥሮ የምትፈልገውን መያዝ እንዳለበት እንዲገነዘብ ያደርገዋል ይለናል። ስለዚህ  ቅኔ (አርት) እንደ ፕሌቶ ተፈጥሮን አስመስሎ መቅዳት ብቻ ሳይኾን ከተፈጥሮ ምንጭ ፈልቆ መፍሰስም በመኾኑ፣ ቅኔ ራሱ የህልው (እውን) ነገር ተፈጥሮን መረዳት እስከቻልነው ድረስ መግለጫና መመርመሪያ ጥበብ መኾኑን ሞግቷል፡፡ በሙግቱም ተፈጥሮ በከፍተኛው ደረጃ እውን ነገርን እንድንረዳ የምታደርገው ተፈጥሯዊ ፍሰቱን ጠብቃ እንደኾነው፤ የአርትን (የቅኔን) ምንነትም በተመሳሳይ መልኩ መረዳት ይገባናል ይላል፡፡
ለፕሎጢኑስ  እውነት በቁስ አካል፣ በነፍስ፣ በአእምሮና በአሐድነት ላይ ያርፋል፤ በዚህም የምትገኝ እውነትም ከመልካምነት ጋር የተዋሐደች ናት፡፡ አሐድነት የኹሉም ምንነት መሠረት ነው፤ አእምሮ ደግሞ የመኾን ኑባሬ እውንነት ነው፡፡ ነፍስም በኹለት ትከፈላለች፡- የዓለም (የኹሉም) ነፍስ  እና የግለሰቦች (ዝርዝር) ነፍስ በሚል፤ እሷም የአካላችን (የሥጋችን) አንቀሳቃሽ ኃይል ናት፤ አካላችን ደግሞ የቁስ አካል ሥሪት ነው፤ ቁስ አካልም ከኹሉም ሥር የሚገኝ ያዥ (ንጣፍ) ነው በማለት ይተነትናል፡፡
በዚያም ላይ ‹እሺ የሕይወት ከፍታው ምንድን ነው?› ብሎ ይጠይቅና  መልሱን ‹አእምሮ› በማለት ይሰጣል፤ አእምሮ እኛን ወደፊት የሚገፋፋንን (የሚያንቀሳቅሰንን) የሰዎችን ነፍስ ጠባያትና የእግዚአብሔርን ሕሊና ጠባያት አዋሕዶ መያዙን ይሞግታል፤ ስለኾነም በከፍተኛ ሕይወት የሚገኝ ትልቁ ሥጦታ የሶቅራጥስ እሰጥ አገባ ነው ይለናል። በዚህ ሥጦታ ነፍስ ኹሉንም ነገር ትመረምራለች፣ ሕሊናም ከአድማሱ ወዲያ ያለውን ኑባሬ ሳይቀር ጠልቆ ያያል፤ ከኹሉም ግን ምርጡ የፍልስፍና ክፍል የእሰጥ አገባ ስልት ነው ይለናል፡- ፕሎጢኑስ።
‹እንዴት ግን በዚህ መልክ ጥልቅ የኾነውን የከፍታ ዕውቀት ገንዘብ ማድረግ ይቻላል?› ሲባል፤ መልሱ በዘይቤ ወይም በምሳሌ ስልት አእምሯችን እየተምዘገዘገ፣ የምሥጢረ ፍጥረትንና የግብረ-ገብን ከፍታን መጥቆና ሰርጎ በመግባት የኑባሬ ምሥጢር፣ የጥልቀት መዳረሻ፣ የንፅሕና ጥግ፣ የኹሉም ነገር መሠረት፣… የኾነውን ነገር መመርመር/መፈተሽ ይችላል ይለናል፡፡  
ደረጃ አውጥቶ ሲያስቀምጥም፤ የከፍታውን ጫፍ መልካምነት አድርጎ ዝቃጩን ሥፍራ ደግሞ ቁስ አካል ያደርገዋል፤ መልካምነት ከመጠበብም የሚበልጥና የኹሉም ነገር ከፍታ ነው ይላል። የፍልስፍና እና የቅኔ መደነቅም ከቁስ አካል ጋር ተያይዞ ከሚገኝ ውበት ጋር ከኾነ ይጠፋል፤ በመልካምነት ተውህቦ ከኾነ ግን ይዘልቃል የሚል ክርክር ነበረው፡- ከታች ወደ መልካምነት ጫፍ ሲያወጣ፡፡ ስለኾነም ቅኔ ከተውህቦ፣ ከዜማና ከጥበብ ንድፍ ይጀምራል፤ ይኽም ቅኔ ከዝቅተኛው ወደ ከፍተኛው ዕይታ መምጠቅ እንዳለበት ይከራከራል፡፡ በአጠቃላይ ግን የፕሎጢኑስ ትልቁ ተፅእኖው፤ አውጉስጢን ወደ ክርስትና እንዲመለስና ፍልስፍናን የሃይማኖት ገረድ ለማድረግ ማስቻሉ ነው፡፡
ማርቆስ ቫሮ
የፕሌቶ ተፅእኖ ብቻ ሳይኾን ቫሮም ያደረገው የአማልክት ምደባም ለአውጉስጢን ትልቅ ግብዓት ኾኖታል፡፡ ቫሮ የሚታወቀው አማልክትን በየግብራቸው መሠረት በመከፋፈል ነው፤ በዚህም 20 (12 ወንዶች እና 8 ሴቶች) አማልክትን ለይቶ አቅርቧል። እነዚህን አማልክትም በሦስት ምደባዎች ጠቅልሎ አስቀምጧቸዋል፡- የሥነ-ተረት፣ የሲቪልና የተፈጥሮ አማልክት በሚል፡፡ የሥነ ተረት አማልክት ከባለቅኔዎች ሥራ ጋር ሲያያዙ፣ የሲቪል ደግሞ ከከተማ ሕዝብ ተግባራት ጋር የተያያዙ ናቸው፤ በሰው ሠራሽ ድርጊቶች (ለምሳሌ በትያትር) ይገለጻሉ፤ የተፈጥሮ አማልክት ደግሞ ከፈላስፎች ተግባራት ጋር የተቆራኙ ሲኾኑ በተፈጥሮ ጠባይ የሚገለጹ ናቸው በሚል ተከራክሯል፡፡
የሰው ሠራሽ ነገሮች የሚገለጹት በአርት ሥራ ሲኾን ከእውነት በጣም የራቁ ወይም ሐሰተኞች ናቸው፤ ቀጥታ ከተፈጥሮ ጋር የሚገናኙት ግን ለእውነትነት በጣም የቀረቡ ናቸው ይላል፡፡ ሰው ደግሞ ከሐሰት ይልቅ እውነትን መምረጥ ስላለበት የተፈጥሮን ጥበብ የሚያጠናው ፍልስፍና ከቅኔ የበለጠ ክብር ሊሠጠው ይገባል ይለናል፤ ስለዚህ በተረትነት ከተፈረጀው ከቅኔ ይልቅ ከተፈጥሮ የሚቀዳው ፍልስፍና የተሻለ እውነት ያለው ነው፡- ለአውጉስጢን፡፡  
ኾኖም አውጉስጢን ቅኔ ስለ አማልክት ተረት በጥልቀት የሚያወራ የሐሳብ ቤት በመኾኑ ይስማማል፤ ግን ደግሞ ሐሰተኛ አማልክትን እንጂ እውነተኛ አምላክን አይገልጽም ባይ ነው፡፡ የዚህን ምክንያት አውጉስጢን ሲገልጽ፤ ቅኔ የሚያቀነቅነው የምድራዊና ሰው ሠራሽ አማልክትን ተግባራት ስለኾነ እና ባለቅኔዎች የሚቀኙት በጋኔን መንፈስ እየተመሩ ስለኾነ፣ ከእውነተኛው አምላክ ጋር አይገናኙም፡፡ ለአውጉስጢን ከተፈጥሮ አማልክት ጋር ስለሚገናኝ ፍልስፍና ለእውነት ከሌሎች የበለጠ ቅርብ ነው፤ አንዱን አምላክ ከሌላው ለመለየትም ትልቅ ሚና ይጫወታል፤ ምድራዊ አማልክቱ ግን እርስ በራሳቸው ስለማይስማሙ ምድራዊ ፍልስፍና እውነተኛውን አምላክ ለማወቅ አያስችልም፤ ትክክለኛው አምላክ የመጨረሻው እውነት መኾን አለበት፤ ይህም የተገለጸው በክርስትና ሃይማኖት ነው ይላል፤ ለእሱ ክርስቲያን የሰማያዊት ከተማ ባለርስት ነው፡፡
የምድራዊ ከተማ ለሐሰተኛ አማልክት ሲያገለግል፣ ሰማያዊ ከተማ ደግሞ የእውነተኛው አምላክ መገለጫ ነው፤ ሐሰተኛ አምላክ በባለቅኔዎች ሲገለጽ እውነተኛው ደግሞ በነቢያት ይገለጻል። የምድራዊ ፈላስፎች ለባለቅኔዎች ምላሽ ሲሰጡ የክርስትና ፈላስፎች ደግሞ ለነቢያት ትንቢት መልስ ይሰጣሉ፤ የምድራዊ ከተማ ፍልስፍናንም ይገነዘባሉ፤ ምክንያቱም እውነተኛው እግዚአብሔር የሚናገረው በነቢያት ነውና ብሎ ሞግቷል፡፡ እውነተኛው አምላክም ኹሉንም ነገር የሠራ፣ የእውነት ገላጭና ደስታን ሰጪ (አዳይ) ስለኾነ ‹እውነተኛ ፈላስፋ የእግዚአብሔር አፍቃሪ ነው› የሚል ክርክር አቅርቧል፡፡ ኾኖም እውነተኛው አምላክም ለዓለሙ የተገለጸው በፈላስፎች፣ በባለቅኔዎች ወይም በሲቪል ሰዎች ሳይኾን በኢየሱስ ክርስቶስ ነው የሚል መደምደሚያ ላይ ደርሷል፡፡
በአጠቃላይ
ለአውጉስጢን ታላቅ ክብር ያለው ጥበብ ሃይማኖት ነው፤ የዕውቀቶች ኹሉ መዳረሻ ለሃይማኖት ማገልገል መቻል ነው፤ ፍልስፍና ከተፈጥሮ ጋር የተናበበችና በምክንያት የምትመራ ስለኾነች ለክርስትና ሃይማኖት መልካም አገልጋይ መኾን ትችላለች፡፡ የሥነ ተረት ሥነ መለኮት ግን የባለቅኔዎች የባዕድ አምልኮ ማቀንቀኛ ስለኾነ ከክርስትና ሃይማኖት ጋር አይስማማም፤ ይህም የቅኔን ፉክክር እንደ ፕሌቶ ከፍልስፍና ጋር ሳይኾን ከሃይማኖት ጋር በማድረግ የክርክሩን ዓይነት ቀይሮታል፡፡ አውጉስጢን በዚህ በሥነ-ተረት አስተሳሰቡ በተለይ ከአርስቶትል ጋር አይስማማም፤ ምክንያቱም አርስቶትል ቅኔን በተረትነት አይነቅፍም፤ የተረትን አስፈላጊነትም ይሞግታል። በአጠቃላይ ግን አውጉስጢን ቅኔን ለጣኦት መወድስ የምታወረድ፣ ፍልስፍናንም የሃይማኖት ገረድ አድርጎ ተከራክሯል።
ፍልስፍናም የሥነ መለኮት ዕውቀት አገልጋይ በመሆኗ፣ ቅኔን ከፍልስፍና መለየት/አለመየቱ ዋና ጉዳይ መኾን የለበትም፤ ይልቁንስ ቅኔ የሥነ ተረት መተረኪያ ስለኾነ፣ በውስጡ ያለው የቋንቋ ስህተት ብቻ ሳይኾን የጋኔን (የሠይጣን) መነጋገሪያ ቋንቋ መሆኑም ዋናው ችግር ነው፤ ይኽም ማለት ቅኔ የሥነ ተረት እምነት (አማልክት) መተረኪያ ነው፡፡
 እሱ እንዳለው ከኾነ፡-
የተፈጥሮ ፈላስፎች ሕዝብን ለመጥቀም ይጽፋሉ፤ ባለ ቅኔዎች ደግሞ ሕዝቡን ለማስደሰት ይቀኛሉ፤ ስለዚኽ የባለቅኔዎቹ ትረካዎች ሕዝቦቹና አማልክቱ የሚደሰቱባቸው የእግዚአብሔር ወገን የኾኑ ሰዎች ሊከተሏቸው የማይገቡ የአማልክቱ ወንጀሎች መኾን አለባቸው፡፡ ስለዚኽ ባለቅኔዎች ከማስደሰት ያለፈ ጥቅም የላቸውም፤ የአማልክቱን ትክክልነት ለመተረትና ለሕዝቡ ክብር ለማስገኘት ይጽፋሉና፡፡
በመኾኑም ለአውጉስጢን ቅኔ መጻፍ እጅግ ዝቅተኛ ጠቀሜታ ሲኖረው፣ ለሃይማኖት የሚጠቅም ፍልስፍና መጻፍ ደግሞ በተቃራኒው ከፍተኛ ጠቀሜታ ይኖረዋል፤ ምክንያቱም ፍልስፍና የሥነ መለኮት ዕውቀት መገልገያ በመኾን ከፍተኛ አገልግሎት ይሠጣልና፤ ቅኔን ግን የአምልኮተ ጣዖት (የባዕድ አምልኮ) ማቀንቀኛ የተረት አካል በማድረግ ይደመድማል፡፡ በመሆኑም ለአውጉስጢን በቅኔና በፍልስፍና መካከል ያለው አለመጣጣም ከፍተኛ ነው፤ በተለይም ፍልስፍና የሃይማኖት አገልጋይ በመኾኗ ፉክክሩን በቅኔና በሃይማኖት መካከል አድርጎ ያጦዘዋል፤ ከእነ ፕሌቶ የሚለየውም የፍልስፍናን ለሥነ መለኮት መመርመሪያ መኾን በማግዘፍ ወይም ለሃይማኖት ከኹሉም የበለጠ ቦታ በማቀዳጀት ነው፡፡