Administrator

Administrator

 • ህዝቡ ወደ ጎዳና የወጣው ነፃነትን ፍለጋ እንጂ ኢህአዴግን ለማደስ አይደለም
   • የሰብአዊ መብት ጥሰት የሚፈጸመው በፖሊሶች ሳይሆን በሥርአቱ ነው
   • ትግሉ ዳር እስኪደርስ በውጭ ሃገር እኖራለሁ ብዬ አላስብም

     ለ6ዓመታት ከታሰረ በኋላ በቅርቡ ከእስር የተለቀቀው ጋዜጠኛ እስክንድር ነጋ፤ ከሰሞኑ የዓለማቀፉ የሰብአዊ መብት ተሟጋች ድርጅት አምነስቲ ኢንተርናሽናል 50ኛ ዓመት የምስረታ በዓል ላይ በክብር እንግድነት ለመገኘት ወደ ኔዘርላንድ ተጉዟል፡፡ ጋዜጠኛው የተጀመረው ትግል ዳር ሳይደርስ በውጭ አገር የመኖር ሃሳብ እንደሌለው ጠቁሟል፡፡ ከጉዞው በፊት የአዲስ አድማስ ጋዜጠኛ አለማየሁ አንበሴ፣ ጋዜጠኛ እስክንድር ነጋን አግኝቶ ያነጋገረው ሲሆን አዲሱ ጠቅላይ ሚኒስትር ከህዝብ ጋር እያደረጉ ስላሉት ውይይት፣ ከጠ/ሚኒስትሩ ስለሚጠብቀው ጉልህ ለውጦች፣ ከተቃዋሚዎች ጋር መደረግ አለበት ብሎ ስለሚያምነው ድርድርና ሌሎችም ጉዳዮች አስተያየቱን ሰንዝሯል፡፡ እነሆ፡-



    ከእስር ከተፈታህ በኋላ ወደተለያዩ የአገሪቱ አካባቢዎች ተጉዘሃል፡፡ የጉዞው ዓላማ ምን ነበር?
በየአካባቢው እየተጋበዝን ነበር የምንሄደው። ነገር ግን ጉዞዎቹ በሚስጥር ነበር የሚደረጉት፡፡ ምክንያቱም የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ላይ ነን፡፡ ነገር ግን ደሙን አፍሶ ከእስር ያስፈታን ህዝብ በመሆኑ  በየአካባቢው እየሄድን ምስጋና ማቅረብ ነበረብን፡፡   
በተዘዋወርክባቸው አካባቢዎች በህዝቡ ላይ ያስተዋልከው ስሜት ምንድን ነው?
ህዝብ የለውጥ እንቅስቃሴ ውስጥ ነው ያለው፡፡ ሁሉን አቀፍ ለውጥ ያስፈልጋል የሚል ስሜት ይንጸባረቃል፡፡ አሁን በኢህአዴግ ውስጥ የተደረገው ሽግሽግ በቂ አይደለም፤ ወደ ስር ነቀል ዲሞክራሲያዊ ሽግግር ልንሄድ ይገባል የሚል ስሜት እንዳለ ነው የተረዳሁት፡፡
ለህዝቡ የለውጥ ጥያቄ፣ የአዲሱ ጠ/ሚኒስትር መመረጥ ምን አስተዋጽኦ ይኖረዋል?
ለለውጦች ተጨማሪ መንገድ ይከፍታል ብዬ ተስፋ አደርጋለሁ፡፡ ዓለማቀፍ ማህበረሰቡን ለማነጋገርም እድሉን አግኝቼ ነበር፡፡ እነሱም ለውጥ ሊመጣ ይችላል የሚል ግምት እንዳላቸው ተረድቻለሁ፡፡ በዲፕሎማቶቹ ዘንድ ጠ/ሚኒስትሩ የለውጥ ፍላጎት አላቸው የሚል እምነት ነው የሚንጸባረቀው፡፡ ባለፉት ንግግሮቻቸው ጥሩ ነገር ሰምተናል፤ ግን በወልቃይት ጉዳይ ህዝብን ቅር ያሰኘ ነገር ተናግረዋል፡፡ ከዚህ አንጻር  በንግግራቸው ላይ ጥንቃቄ ማድረግ ያለባቸው ይመስለኛል፡፡
ከጠቅላይ ሚኒስትሩ የሚጠበቁ ጉልህ ለውጦች ምንድን ናቸው?
ከጠቅላይ ሚኒስትሩ የሚጠበቀው ለቀጣዩ ምርጫ ምቹ ሁኔታ መፍጠር ብቻ አይደለም፤ሁለት አበይት ነገሮች አሉ፡፡ በመጀመሪያ የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁን ማንሳት ነው፡፡ ከዚያም አዋጁ ከተጣለ በኋላ የታሰሩ ግለሰቦችን ያለ ቅድመ ሁኔታ መፍታት ነው፡፡ ሁለተኛ ሃገሪቱን ወደ ሰላማዊ ሽግግር ማስገባት ነው፡፡ ለዚህ ደግሞ ሁሉን አቀፍ ድርድር ማድረግ ያስፈልጋል፡፡ ሁሉን አቀፍ ድርድር ሲባል፤ በህጋዊም ሆነ ከዚያ ውጪ ባሉ መድረኮች ያሉ ተቃዋሚ የፖለቲካ ድርጅቶችን የሚያካትት የድርድር ጉባኤ መጥራት ነው፡፡ ህጋዊ ባልሆነ መንገድ የሚታገሉ ሶስት ድርጅቶችን፡- “ኦነግ”፣ “ግንቦት 7” እና “ኦብነግ”ን ማካተት አለበት ድርድሩ፡፡ በደቡብ አፍሪካ ለውጥ የመጣው በገዥው ናሽናል ፓርቲና በኤኤንሲ መካከል ድርድር ከተካሄደ በኋላ ነው። ኢትዮጵያ ውስጥም ለውጥ ሊመጣ የሚችለው በሽብርተኝነት በተፈረጁ ድርጅቶችና በኢህአዴግ መካከል ድርድር ሲካሄድ ነው፡፡ ይሄ ካልተደረገ ህዝብ የሚፈልገው ለውጥ መጥቷል ማለት አይቻልም፡፡ ከሁለት ዓመት በኋላ ለሚደረገው ምርጫ፣ የፖለቲካ ምህዳሩን ለማመቻቸትም ይሄ ወሳኝ ነው፡፡ ምርጫው ገና ሩቅ ነው፡፡ ቅድሚያ ሊሰጠው የሚገባው ግን ከእነዚህ ኃይሎች ጋር ለሚደረገው ድርድር ነው፡፡  
ምን አይነት ድርድር ነው  መንግስት ማድረግ ያለበት?  
በዚህ ረገድ ምሳሌ የምትሆነን ደቡብ አፍሪካ ነች፡፡ ደቡብ አፍሪካ ያደረገችው ሰላማዊ ዲሞክራሲያዊ ሽግግር በድርድር የመጣ ነው። ይሄ ድርድር ውጤት ካመጣ በኋላ ለዓለም ሞዴል ሆኗል፡፡ በደቡብ አሜሪካ፣ በእስያ ሃገራት ተሞክሮ ውጤታማ ሆኗል፡፡ በአፍሪካም በተለያዩ ሀገራት ውጤት አምጥቷል፡፡ በኢትዮጵያም ውጤታማ እንደሚሆን ምንም ጥርጥር የለውም፡፡ የተሞከረ ሞዴል እያለ ሌላ ለማፍለቅ መጨነቅ የለብንም። ዋናው ነገር ያለ ቅድመ ሁኔታ ሁሉንም ወገን በድርድር መድረክ ማሳተፍ ነው፡፡ የዚህ ድርድር ውጤት ምንም ነገር ሊሆን ይችላል፡፡ በብዙ ሃገራት ይህ ዓይነቱ ድርድር በሽግግር መንግስት ይደመደማል፡፡ የሽግግር መንግስት ማለት ደግሞ የሚያስፈራ ነገር አይደለም፡፡ በቀላሉ የተለያዩ ድምፆችን የሚወክሉ አካላት የተሳተፉበት መንግስት ማለት ነው፡፡ ለምሳሌ በካቢኔ ውስጥ “ግንቦት 7”፣ “ኦነግ”፣ “መድረክ”፣ “ሰማያዊ ፓርቲ”ን ወዘተ ማሳተፍ ማለት ነው፡፡ በብዙ አገሮች የተደረገው ይሄ ነው፡፡ ድርድሩ ሲካሄድ ምናልባት እንደ ደቡብ አፍሪካ በዝግ ሊሆን ይችላል፡፡ ሁሉም ፓርቲዎች ግን የሰጥቶ መቀበልን መርህ መከተል ይኖርባቸዋል፡፡  
በዚህ ሂደት ውስጥ ከተቃዋሚዎች ምን ይጠበቃል?
በመጀመሪያ ነገር ከኢህአዴግ ብዙ ነገር ይጠበቃል፡፡ ከተቃዋሚዎች ደግሞ ግማሽ መንገድ መምጣት ይጠበቃል፡፡ ህዝቡ በተቃዋሚዎች ላይም ጫና ማድረግ ያስፈልገዋል። አሁን የሚደረገው  ድርድር የፖለቲካ ነጥብ ማስመዝገቢያ ሳይሆን የሃገር መታደጊያ ነው መሆን ያለበት፡፡ ተቃዋሚዎች ድርድሩ እንዲሳካ በኢህአዴግ የቀረበውን ጥሪ በፀጋ መቀበል  አለባቸው፡፡ ይህን እንዲቀበሉ ከሞራል መሪዎችና ከህዝቡ ግፊት ሊደረግ ይገባል። ድርጅቶች ጥቅማቸው ሊነካ እንደሚችል ጭምር አምነው ነው ወደ ድርድሩ መግባት ያለባቸው፡፡
ዶ/ር አብይ በኢህአዴግ ላይ ለውጥ ያመጣሉ አያመጡም የሚለው ጉዳይ አነጋጋሪ ሆኖ ቀጥሏል። ጠ/ሚኒስትሩ የሚፈለገውን ለውጥ ማምጣት ይችላሉ ብለህ ታምናለህ?
አዎ! ሶቪየት ህብረትን በኮሚኒስት ፓርቲው ውስጥ ሆኖ ወደ ለውጥ ያስገባው ሚኻኤል ጎርባቾቭ ነው፡፡ የአፓርታይድ ዋነኛ ባለቤት በነበረው የደቡብ አፍሪካው ናሽናል ፓርቲ ውስጥም ዴክለርክ ነው ለውጥ ያመጣው። የእነዚህን ሰዎች የመሪነት ክህሎት እስከ ዛሬ የምናደንቀው እኮ የድርጅታቸውን አስተሳሰብ ቀይረው ወደሚፈለገው ለውጥ ስለመሩት ነው፡፡
ዶ/ር አብይም በተመሳሳይ በፓርቲያቸው ውስጥ የሚገጥማቸውን ተቃውሞ አሸንፈው ዲሞክራሲን እውን በማድረግ ድርጅታቸውን ወደ ህዝቡ የለውጥ ፍላጎት እንዲያስገቡ ነው የምንጠብቀው። የአመራር ክህሎታቸው የሚፈተነው በዚህ ነው። ይሄን ማድረግ ካልቻሉ ታሪክ የጣለባቸውን ኃላፊነት መወጣት አልቻሉም ማለት ነው፡፡
ጠ/ሚኒስትሩ ሰፊ ተቀባይነት ካስገኘላቸው ጉዳይ አንዱ ኢትዮጵያዊነትን ማቀንቀናቸው ነው። ኢትዮጵያዊነትንና የብሔር ማንነትን ሚዛን አስጠብቆ ለመጓዝ አያስቸግራቸውም…?
ኢትዮጵያዊነት ውስጥ ብሔር ብሔረሰቦች እንዳሉ የምንክድበት ዘመን ላይ አይደለንም። እኚህ ሰው ኢትዮጵያዊነትን ሲያነሱ፣ ብሔር ብሔረሰቦችን ይክዳሉ ማለት አይደለም፡፡ በተመሳሳይ ብሔር ብሔረሰቦችን ሲያነሱም፣ ኢትዮጵያዊነትን ይክዳሉ ማለት አይደለም፡፡ ኢትዮጵያዊነትንም የብሔር ማንነትንም ሚዛናዊ አድርጎ የመሄድ ጉዳይ ነው። ሁለቱንም ይዞ መሄድ ችግር የለውም፡፡ ጎን ለጎን መሄድ የሚችሉ ናቸው፡፡ ይሄ ደግሞ ኢትዮጵያ ውስጥ ብቻ ሳይሆን በሌሎችም ሀገር ያለ ነው፡፡ ህንድ ውስጥ ህንዳዊነት አለ፤ የአካባቢ ማንነቶች ደግሞ አሉ፡፡ ጎረቤት ኬንያም ተመሳሳይ ነው፡፡ በብሔረሰቦችና በኢትዮጵያዊነት መሃል ያለውን ቀመር አጣጥሞ የመሄዱ ጉዳይ ነው ዋናው፡፡
ጠ/ሚኒስትሩ በአገሪቱ የተለያዩ አካባቢዎች የሚያደርጓቸው ንግግሮች ፖለቲካዊ ችግሮችን ለመፍታት ጠቀሜታ አላቸው ብለህ ታምናለህ?
ጠቀሜታ አላቸው፡፡ ነገር ግን በጥያቄና መልስ ወቅት ጥንቃቄ ማድረግ አለባቸው፡፡ ለምሳሌ በወልቃይት ጥያቄ ላይ የሰጡት ምላሽ ጥሩ አልነበረም፡፡ የወልቃይት ጥያቄ የዲሞክራሲ ነው እንጂ የልማት ተብሎ ሊታለፍ የሚችል አይደለም። የአንድን ህዝብ ዲሞክራሲ የሚጋፋ ነገር እንዳይናገሩ ጥንቃቄ ማድረግ አለባቸው፡፡ በሌላ በኩል ንግግሮቻቸው ወደ ተግባር እስካልተለወጡ ድረስ ትርጉም አልባ ነው የሚሆኑት፡፡ በእርግጥ ሰውየው የለውጥ ፍላጎት እንዳላቸው የመጡበት መንገድም ያሳያል፡፡ በከፍተኛ ፍላጎት ወደ ስልጣን መምጣታቸው በራሱ የለውጥ ፍላጎት እንዳላቸው ያመላክታል፡፡ የኦህዴድን አቋም የኢህአዴግ ማድረግ ከቻሉ ደግሞ ለውጡ ሁሉን አቀፍ ሊሆን ይችላል፡፡
በተረፈ አሁን የጫጉላ ጊዜ ላይ ናቸው፡፡ ግን ይሄን የጫጉላ ጊዜ ተጠቅመው የሚፈለገውን ነገር ማምጣት ካልቻሉ ህዝብ በድጋሚ ወደ ጎዳና የማይወጣበት ምክንያት የለም፡፡ ይሄን ጉዳይ በቅጡ ሊያስቡበት ይገባል፡፡ ጠ/ሚኒስትሩ፤ “የኢትዮጵያ ጎርባቾቭ” ወይም “የኢትዮጵያ ዴክለርክ” እንዲሆኑ ነው የምንፈልገው፡፡ በአጭር ጊዜ ውስጥ ሁሉን አቀፍ ድርድር የማይጠሩ ከሆነ፣ የዲሞክራሲ ጥያቄው ወደ ጎዳና ሊወጣ ይችላል፡፡ ይሄ በሌሎች ሃገሮችም ያየነው ልምድ ነው፡፡ ህዝቡ በኢህአዴግ የስልጣን ሽግሽግ ረክቶ አይቀመጥም፡፡ ሥር ነቀል ዲሞክራሲያዊ ለውጥ ይፈልጋል፣ ነፃነቱን መቀዳጀት ይሻል፡፡ ህዝቡ ወደ ጎዳና የወጣው ነፃነትን ፍለጋ እንጂ ኢህአዴግን ለማደስ አይደለም፡፡ በኢህአዴግ ውስጥ የተፈጠረውን የስልጣን ሽግሽግ በፀጋ የተቀበለው ነፃነት ለማምጣት መሸጋገሪያ ይሆናል በሚል ነው፡፡ የነፃነት አመለካከት ያላቸው ግለሰቦች ወደ ስልጣን መጥተዋል ብሎ ነው የተቀበለው፡፡ ስለዚህ ተግባራዊ እንቅስቃሴ ይጠይቃል፡፡
ለረዥም ጊዜ የውዝግብና የግጭት መነሻ ሆኖ የዘለቀው የወልቃይት ጉዳይ እንዴት መፈታት አለበት ትላለህ?
የወልቃይት ጥያቄ በመሰረታዊነት የዲሞክራሲ ጥያቄ ነው፡፡ ችግሩ ሊፈታ የሚችለው በአካባቢው ህዝብ ፈቃድ ብቻ ነው፡፡ ህዝብ ነው መወሰን ያለበት፡፡ በህዝበ ውሳኔ እልባት ማግኘት አለበት፡፡ በመሰረታዊነት የሃገሪቱ የዲሞክራሲ ጥያቄ ሲመለስ የአካባቢው ህዝብ ጥያቄም መልስ ያገኛል፡፡ ህዝቡ የወልቃይትን ጉዳይ “እኛ ሳንጠየቅ ሌሎች ናቸው በኛ ላይ የወሰኑት፣አሁን ራሳችን መወሰን አለብን” እያለ ነው፡፡ ይሄም ህገ መንግስቱ ያረጋገጠው መብታችን ነው ይላል፡፡ የህዝቡን ጥያቄ  ጠቅላይ ሚኒስትሩ በሚገባ ሊያዳምጡ ይገባል። የወልቃይት ዲሞክራሲያዊ መብት ተነካ ማለት አጠቃላይ የሃገሪቱ ህዝብ መብት ተነካ ማለት ነው፡፡ ስለዚህ ጥያቄው አጠቃላይ ሃገራዊ የዲሞክራሲ ጥያቄ አካል ነው፡፡
ባለፈው ሳምንት የአሜሪካ ኮንግረስ ያጸደቀው HR 128፣ በኢትዮጵያ ላይ በተግባር የሚያሳድረው  ተፅዕኖ ምንድን ነው?
 ወደ ደቡብ አፍሪካ ጉዳይ እንደገና ልመለስና ኔልሰን ማንዴላ ከእስር ሲለቀቁ፣ ሽብርተኛ የተባለው ኤኤንሲ ፍረጃው ተነስቶለት ወደ ሃገር ውስጥ ገብቶ፣ ቢሮ ከፍቶ መንቀሳቀስ ጀመረ። ይሄኔ የምዕራቡ አለም ሰዎች፣ “በቃ ደቡብ አፍሪካ ውስጥ የሚፈለገው ለውጥ መጥቷል፤ ፖለቲከኞች ተፈተዋል፤ ኤንኤንሲም ሽብርተኛ የሚለው ፍረጃ ተነስቶለት ወደ ሃገር ውስጥ ገብቶ እየተንቀሳቀሰ ነው፤ ስለዚህ በደቡብ አፍሪካ ላይ ተጥሎ የነበረው ማዕቀብ መነሳት አለበት” የሚል እንቅስቃሴ ጀመሩ፡፡ በዚህ ሃሳብ ላይ ኤኤንሲ እና ኔልሰን ማንዴላ ተጠየቁ፡፡ ምላሻቸው ግን ፈፅሞ ማዕቀቡ መነሳት የለበትም የሚል ነበር፡፡ “ገና ጅማሮ ላይ ነው ያለነው፤ ይሄ ማዕቀብ ጅማሮ ላይ እያለን የሚነሳ ከሆነ ሊቀለበስ ይችላል፡፡ ወደ ለውጥ ሂደቱ ያስገባን ማዕቀቡ ነው፤ ነገሮች ገና ሳይበስሉ የሚነሳ ከሆነ ወደ ቀድሞ ሁኔታ የማንመለስበት አስተማማኝ ነገር የለም፡፡ ከተቀለበሰ በኋላ እንደገና ማዕቀብ ለመጣል ረዥም ጊዜ ይፈጃል። ስለዚህ ማዕቀቡ መነሳት የለበትም” ሲሉ ተከራክረው ነበር፡፡ ክርክራቸውም ተቀባይነት አግኝቶ ማዕቀቡ  ቆይቷል፡፡ ወደ ኢትዮጵያ ሁኔታ ስንመጣ “ኢትዮጵያ ወደ ለውጥ እየገባች ነው፤ HR 128 ለማጽደቅ ጊዜው አይደለም” የሚል ክርክር ተነስቷል፡፡ ግን የለውጥ ጅማሮው ዳር መድረስ አለበት፡፡ ጅማሮው ዳር እንዲደርስ ደግሞ HR 128 ያስፈልጋል፡፡ የውሳኔ ሃሳቡ ጠቀሜታ ከዚህ አኳያ ነው፡፡
በመንግስት ላይ ተፅዕኖ የሚፈጥረው በምን መንገድ ነው?
በHR 128 ውስጥ አንድ አንቀፅ አለ፡፡ የሰብአዊ መብት ጥሰት የፈፀሙ ባለስልጣናት ወደ አሜሪካ እንዳይገቡ ማዕቀብ ይጥላል፡፡ አንዱ ጠቀሜታ ይሄ ነው፡፡ በመንግስት በኩል እውነተኛ ለውጥ ሳይሆን ጥገናዊ ለውጥ ብቻ የሚደረግ ከሆነ የሰብአዊ መብት ጥሰቱ መቀጠሉ አይቀርም። ከዚህ አንፃር HR 128 እውነተኛ ለውጥ እውን እስኪሆን ድረስ ጠቃሚ ይሆናል፡፡ ይህ የሚደረገው አሁን በኢህአዴግ ውስጥ የተፈጠረውን ለውጥ በመቃወም አይደለም። እንደውም ለውጡ በቂ አይደለም፤ አጠናክሩ ለማለት ነው፡፡ በኢህአዴግ ውስጥ መለወጥ ይገባናል ለሚለው ድምፅም አጋዥ ነው ብዬ አምናለሁ፡፡ ተጨባጭ ለውጥ ከሌለ ኢህአዴግ ከህዝብ ብቻ አይደለም የሚነጠለው። ከ27 ዓመት በኋላ ከዓለማቀፉ ማህበረሰብም ይነጠላል ማለት ነው፡፡ ይህ የመነጠል አደጋ ከፊት ለፊቱ ተጋርጧል፡፡ በአንድ ወቅት የዚምባቡዌው ሙጋቤ ከዓለማቀፉ ማህበረሰብ እንደተነጠሉት ማለት ነው፡፡
የማዕከላዊ ምርመራ ቢሮ መዘጋት የሰብአዊ መብት ጥሰትን ለመከላከል ፋይዳ ይኖረዋል ብለህ ታምናለህ?
በነገራችን ላይ ማዕከላዊ ለኔ ሌላኛው ቤቴ ነው። ከጥፊ ጀምሮ ተገልብጦ እስከ መገረፍ የሚደርስ የሰብአዊ መብት ጥሰት ተፈፅሞብኛል፡፡ ይህን የፈጸሙብኝ ፖሊሶቹ አይደሉም፤ ሥርአቱ ነው፡፡  የሰብአዊ መብት ጥሰት የሚፈፅመው ስርአቱ እንጂ እንደኛ ሰው የሆኑት ፖሊሶች አይደሉም፡፡ ከዚህ አንፃር ማዕከላዊን በመዝጋት ብቻ የሰብአዊ መብት ጥሰትን ማስቆም አይቻልም፡፡ ከምንጩ ለማድረቅ ከተፈለገ ስርአቱን ነው መለወጥ ያለብን፡፡ የሰብአዊ መብት ጥሰቶችን ከምንጫቸው የሚያደርቀው የዲሞክራሲያዊ ስርአት መመሥረት ብቻ ነው። ለፖሊሶች ስልጠና መስጠትና ማዕከላዊን መዝጋት ብቻውን መፍትሄ አይሆንም፡፡ የሰብአዊ መብት ጥሰት የአምባገነናዊ ስርአት ባህሪ ውጤት ነው፡፡ አምባገነናዊ ስርአት እስካለ ድረስ ግድያ፣ እስራት፣ የሃሰት ክስ አለ፡፡ ስለዚህ ከምንጩ ነው ማድረቅ ያለብን፡፡ ምናልባት የማዕከላዊ መዘጋት ኢህአዴግ ለውጥ እንደሚያመጣ   ምልክት ከሆነ እሰየው ነው።
ዛሬ ወደ ውጪ አገር ትበራለህ፡፡ እዚያው የመቅረት ሃሳብ አለህ ወይስ ትመለሳለህ?
እኔ ልቅር ብልም ባለቤቴ እዚያ አታስቀምጠኝም። ህዝብን ከድተህ እኔ ጋር አትቀመጥም ብላ ነው የምታባርረኝ፡፡ ዲሞክራሲያዊ ስርአት እስክናገኝና ትግሉ ዳር እስኪደርስ ድረስ ውጭ ሃገር እኖራለሁ ብዬ አላስብም፡፡ የተነሳንበት፣ የታሰርንበት ዓላማ ከዳር መድረስ አለበት፡፡ የሚቻል ነው ብዬ ስለማምን እስከ መጨረሻው ድረስ እታገላለሁ፡፡ ይሄ ደግሞ የኔ ብቻ ሳይሆን የቤተሰቤም አቋም ነው፡፡

  በደራሲ መካሻ አበራ የተፃፈው “መንግሥትና የግለሰብ ነፃነት” መፅሀፍ ገበያ ላይ ዋለ፡፡ መፅሐፉ በዋናነት የብአዴን ጽ/ቤት ኃላፊ በሆኑት አቶ አለምነው መኮንን የተፃፈው “ፖለቲካ፣ ኢኮኖሚና የኢትዮጵያ ህዳሴ” ለተሰኘው መጽሀፍ ምላሽ የሚሰጥ ነው ተብሏል፡፡ በአምስት ዋና ዋና ምዕራፎች የተከፋፈለው መፅሃፉ በሪበራል ዴሞክራሲና ገበያ አክራሪነት፣ በምዕራባዊያን የገበያ አክራሪነትና ሊበራል ዴሞክራሲ የቀረበውን ትችት በተመለከተ አጠቃላይ እይታና በበርካታ ጉዳዮች ዙሪያ የሚያጠነጥን ነው፡፡ በ240 ገፅ የተመጠነው መፅሀፉ በ65 ብር እየተሸጠ ነው፡፡

• የዳግማዊ አፄ ቴዎድሮስ ፋውንዴሽን ለማቋቋም ስምምነት ላይ ደርሰናል
  • ቅርሶችን ከውጭ አገራት የማስመለስ ከፍተኛ መነቃቃት ተፈጥሯል
  • እንግሊዞች የመቅደላ አምባ ሙዚየም ግንባታን ማገዝ አለባቸው

    የዳግማዊ አፄ ቴዎድሮስ 150ኛ ዓመት ዝክረ  በዓል “መስዋዕትነት ለብሔራዊ ኩራት” በሚል መሪ ቃል ከሚያዝያ 2-8 ቀን 2010 ዓ.ም በጎንደር፣ ደብረታቦርና መቅደላ በተለያዩ ዝግጅቶች ተከብሯል፡፡ ባለፈው ሰኞም በአዲስ አበባ ጌትፋም ሆቴል የመዝጊያ ሥነ ሥርዓቱ በደመቀ ሁኔታ የተከናወነ ሲሆን በዝግጅቱ ላይም የባህልና ቱሪዝም ሚኒስትር ዶ/ር ሂሩት ወ/ማሪያም፣ ፕ/ር እንድሪያስ እሸቴ፣ ፕ/ር ባህሩ ዘውዴ፣ ፕ/ር ማሞ ሙጨ፣ የጎንደር ዩኒቨርሲቲ ፕሬዚዳንት ዶ/ር ደሳለኝ መንገሻ፣ የአማራ ክልል ባህልና ቱሪዝም ቢሮ ኃላፊ ዶ/ር ሂሩት ካሣው እንዲሁም ጥሪ የተደረገላቸው አርቲስቶችና የዳግማዊ አፄ ቴዎድሮስ ቤተሰቦች ተገኝተዋል፡፡
ከአፄ ቴዎድሮስ 150ኛ ዓመት ዝክረ በዓል ዝግጅት ምን ውጤት ተገኘ? በክብረ በዓሉ ላይ የተመሰረተው ጊዜያዊ የቅርስ አስመላሽ ኮሚቴ ዓላማ ምንድን ነው? ሳይገነባ ከ10 ዓመት በላይ የቆየው የመቅደላ አምባ ሙዚየም ዕጣ ፈንታ ምንድን ነው? አደጋ የተጋረጠባቸውን ላሊበላና ጣና ሐይቅን ማነው የሚታደጋቸው?---የአዲስ አድማስ ጋዜጠኛ ናፍቆት ዮሴፍ፤ ከባህልና ቱሪዝም  ሚኒስትሯ ዶ/ር ሂሩት ወ/ማሪያም ጋር በእነዚህና ሌሎች የቱሪዝም ዘርፍ ጉዳዮች ተከታዩን ቃለ ምልልስ  አድርጋለች፡፡

   የዳግማዊ አፄ ቴዎድሮስ 150ኛ ዓመት ዝክረ በዓል፣ ለሳምንት ገደማ ከጎንደር እስከ አዲስ አበባ፣ በተለያዩ ዝግጅቶች ተከብሯል፡፡ ከዚህ ክብረ በዓል ምን ውጤት ተገኘ?
ይህ ዝክረ በዓል ትልቅና ታሪካዊ ነው ብሎ በሙሉ ልብ መናገር ይቻላል፡፡ በዚህ የአፄ ቴዎድሮስ 150ኛ ዓመት ዝክረ በዓል ላይ ብዙ ዝግጅቶች ተከናውነዋል። ከአጼው የትውልድ ቦታ ራሳቸውን በክብር እስከ ሰዉበት መቅደላ ድረስ ታሪካዊ አሻራቸውን ያኖሩባቸው ቦታዎች ተጎብኝተዋል፡፡ የመዝጊያ ሥነ ስርዓቱም በአዲስ አበባ ጌትፋም ሆቴል በደመቀ ሁኔታ ተከናውኗል። እንግዲህ ምን ውጤት ተገኘ ለተባለው፣ አፄው በዘመናቸው ከሰነቋቸው ራዕዮች የአሁኑ ትውልድ ምን መማር ይችላል፣ የእርሳቸው ትሩፋቶች ምንድን ናቸው፣ አገርን ከማልማት፣ ከማዘመንና አንድ ከማድረግ አኳያ ህልማቸው ምን ነበር ወዘተ--የሚሉትን ለመፈተሽ ያስቻለ ሁነት ነበር ማለት ይቻላል። ከአፄው ስኬት ብቻ ሳይሆን ከውድቀታቸውም፣ ከውጭም ከውስጥም ከገጠሟቸው ፈተናዎች ምን እንማራለን? የህልማቸው ጫፍ ላይ እንዳይደርሱ ፈተና የሆነባቸው ምን ነበር? የሚሉትን እንድናይ፣ የአሁኑ ትውልድም ትምህርት እንዲቀስም ትልቅ አጋጣሚ ፈጥሯል፡፡ ሌላው ደግሞ በየቀኑ በንጉሱ ህይወት ላይ የሚያጠነጥኑ፣ ጥልቅ ምርምር የተደረገባቸው የጥናት ጽሁፎች በትላልቅ የአገር ውስጥና የውጭ ምሁራን እየቀረቡ፣ ስንማርና ዕውቀታችንን ስናሰፋ ነው የቆየነው፡፡
በጎንደር ዩኒቨርሲቲ ሳይንስ አምባም ሆነ በአዲስ አበባ፤ በውጭ የሚገኙና እየተመለሱ ያሉ ቅርሶቻችንን፣ የልዑል አለማየሁን ፎቶግራፍ፣ የአፄውን የክብርና የንግስና ጌጣጌጦች እንዲሁም ዲፕሎማሲያዊ ግንኙነት ያደረጉባቸው ደብዳቤዎችን ያካተተ የፎቶግራፍ አውደ ርዕይ ለእይታ ቀርቦ ነበር፡፡ ከዚህም ብዙ እውቀት መቅሰም ተችሏል፡፡ ጋዜጠኞች የአፄው ዱካዎች ያረፉባቸው ታሪካዊ መዳረሻዎችን ጎብኝተው በየሚዲያዎቻቸው በማስተላለፍ፣ ለማህበረሰቡ ትልቅ መነቃቃትና ግንዛቤ ፈጥረዋል፡፡ እነዚህ ሁሉ እንግዲህ የዚህ ዝክረ በዓል ትሩፋቶች ናቸው፡፡
በሌላ በኩል እነዚህን ታሪክ የተሰራባቸውን ቦታዎች በሚገባ አልምተን፣ እንዴት የቱሪስት መዳረሻ ማድረግ እንደምንችል አቅጣጫ ያሳየና ትልቅ ትምህርት የተወሰደበት ነው፡፡ ጠቅለል ስናደርገው፤ ስለ አፄ ቴዎድሮስ ያለን እውቀት ሰፍቷል፤ የምንወስደውን ትምህርት ለይተን ከቱሪዝም ጋር አቀናጅተን ምን መጠቀም እንችላለን የሚለውን ተገንዝበናል፣ የአፄ ቴዎድሮስ ፋውንዴሽን እንዲቋቋም ሀሳብ ቀርቦ፣ በደብረ ታቦር ለማቋቋም ስምምነት ላይ ደርሰናል። መቅደላ ላይ ደግሞ ሙዚየም ለማቋቋም ተስማምተናል፡፡
በዚህ ዝክረ በዓል ላይ ከኢትዮጵያ ተዘርፈው በእንግሊዝ ሙዚየሞች የሚገኙ ቅርሶችን የማስመለስ ጉዳይ ትልቅ ትኩረት የተሰጠው ይመስላል---  
እውነት ነው፣ጉዳዩ ትልቅ ትኩረት ተሰጥቶታል። እንደሚታወቀው አፄው መጨረሻ ላይ ራሳቸውን ሲሰዉ፣ እንግሊዞች ልጃቸውን ወስደዋል፤ ሽሩባቸውን ከራሳቸው ላይ ገፍፈው ወስደዋል፣ ልብሶቻቸውን ሳይቀር ቆራርጠው ተቀራምተውታል፡፡ በግምጃ ቤታቸው ያጠራቀሟቸው የአገራችን የእጅ ጥበብ ውጤት የሆኑ በርካታ አይነት ቅርሶችንም (የፅሁፍ፣ ጌጣጌጦች፣ አልባሳት፣ ታቦታት፣ ዘውዶችና ሌሎች በርካታ ሀብቶች) ዘርፈዋል፡፡ ከ200 በላይ በሚሆኑ በቅሎዎችና ከ20 በላይ በሆኑ ዝሆኖች ጭነው ነው የወሰዱት፡፡
እንደውም በእንግሊዝ አገር ያሉ ቅርሶቻችን እስከ 2 ቢሊዮን ፓውንድ እንደሚያወጡ ይነገራል….
እውነት ነው፤ ከዚያም በላይ ናቸው፡፡ በነገራችን ላይ የተዘረፉትን ቅርሶች አይነትና መጠን ስንመለከት፤ አፄ ቴዎድሮስ በዚያ ቦታ ላይ ቤተ መፅሐፍትና ሙዚየም የማቋቋም ሀሳብ ነበራቸው ለማለት ያስችላል፡፡ ይህን የሚያመላክት ጥልቅና አሳማኝ ጥናትም ዛሬ በዚሁ መድረክ ላይ ሲቀርብ ተመልክተሻል፡፡ ምክንያቱም እሳቸው ከውጭ ማለትም ከአውሮፓና ሌሎች አገራት ጋር በፈጠሩት ዲፕሎማሲያዊ ግንኙነት፣ ስለ ቤተ-መፃሕፍትና ስለ ሙዚየም ጥሩ ግንዛቤ ነበራቸው።  መቅደላ ላይ በብዛት የነበሩት ቅርሶችም ከመላ አገሪቱ የሰበሰቧቸው ነበሩ፡፡ የቅርሶቹ በአንድ ቦታ ላይ መገኘት፣ ለዘራፊዎቹ ምቹ ሁኔታን  ፈጥሮላቸዋል፡፡
እነዚህ ከአገራችን የተዘረፉ ሀብቶችን በማስመለስ ረገድ በህግና በዲፕሎማሲ ምን ስራዎች መሰራት አለባቸው፣ በዚህ እንቅስቃሴ ውስጥ የሚሳተፉ ባለድርሻ አካላት እነማን ናቸው፣ ምሁሩ አርቲስቱ፣ ሚዲያው፣ ባህልና ቱሪዝም፣ የውጭ ጉዳይ መስሪያ ቤት--ምን ምን የቤት ስራዎች ይውሰዱ፣ ምን አይነት ስልቶችስ ይቀየሱ --- የሚሉ በርካታ ምክረ ሃሳቦች ቀርበዋል፡፡ በአገር አቀፍ ደረጃም ከፍተኛ መነቃቃት ተፈጥሯል፡፡ ከዚህ ባሻገር ጠንካራ ቅርስ አስመላሽ ብሔራዊ ኮሚቴ ለማቋቋም ጊዜያዊ አስተባባሪ ኮሚቴ ተመስርቷል፡፡ ስለዚህ እጅግ የተዋጣለት፣ ብዙ ውጤት የተገኘበት ሁነት ነው፡፡ ይህን ኢንሺየቲቭ የወሰደውን ጎንደር ዩኒቨርሲቲንና በዚህ ክብረ በዓል ላይ አሻራቸውን ያሳረፉ ዩኒቨርሲቲዎችን፣ የባህልና ቱሪዝም ቢሮ ጽ/ቤቶችን እንዲሁም ተሳታፊ ድርጅቶችንና ግለሰቦችን ለማመስገን እወዳለሁ፡፡
የእንግሊዝ መንግሥት ቅርሶቻችንን በረጅም ጊዜ ውሰት ለኢትዮጵያ ለመስጠት ጥያቄ ቢያቀርብም  የኢትዮጵያ መንግሥት “ሰው ንብረቱን ይወስዳል እንጂ አይዋስም” በሚል ጥያቄውን ውድቅ ማድረጉ ተነግሯል፡፡ “ብልጥ ልጅ የያዘውን ይዞ ያለቅሳል” እንዲሉ፣ቅርሶቹን በውሰት ተቀብሎ ሙሉ ለሙሉ ለማስመለስ ጥረት ማድረግ አይሻልም ነበር?
በነገራችን ላይ የእንግሊዝ መንግሥት አቀረበ የተባለው ጥያቄ  በቀጥታ ለእኛ አልቀረበልንም። ለባህልና ቱሪዝም ሚኒስቴርም ሆነ ለሌላ የትኛውም የመንግሥት አካል “ቅርሱን ለረጅም ጊዜ ተውሳችሁ ውሰዱ” የሚል ጥያቄ በቃልም በፅሁፍም አልመጣልንም፡፡ እኛም የሰማነው “ዘ ጋርዲያን” ከተባለ ጋዜጣና ከሌሎች የእንግሊዝ ሚዲያዎች  ነው፡፡ እኛን የጠየቀንም ያማከረንም የለም፡፡ የእንግሊዝ መንግስት ከምን ተነስቶ ሀሳቡን እንዳነሳው የምናውቀው ነገር ስለሌለ መልስ ለመስጠት፣ ለመቀበልም ሆነ ሌሎች አማራጮችን ለማየት አልተንቀሳቀስንም፡፡ እርግጥ እኛ እንደ መንግስት ሀብታችን ይመለስልን የሚል ጥያቄ አቅርበናል፡፡ በ2007 ዓ.ም ይህ ጥያቄ በርዕሰ ብሔሩ ፊርማ ተልኳል፡፡ ግን መልስ አልሰጡም፤ እኛም በተለያየ መንገድ ጥያቄ ማቅረባችንን ቀጥለናል፡፡
እርስዎ ሚኒስቴር መሥሪያ ቤቱን መምራት ከጀመሩ በኋላ ተሳክቶልኛል ብለው የሚጠቅሱት ሥራ ወይም ፕሮጀክት ካለ ቢነግሩኝ?
ገና እኮ ነው! ይሄ አልቋል፣ አሳክቸዋለሁ ልልሽ አልችልም፡፡ ነገር ግን በዚህም በዚያም የሚታየው ጅምር ሁሉ ተስፋ ሰጪ ነው፡፡ በነገራችን ላይ ስኬት ሂደት ነው፡፡ ለምሳሌ ዛሬ እኛ የምናመቻቸው፣ የምንቀይሰው ነገር እውን የሚሆነው፣ ከኛ ቀጥሎ በሚመጡት መሪዎች ሊሆን ይችላል፡፡ ለዚህ ነው ሂደት ነው የምልሽ። ተስፋ ሰጪ ነገሮች እየሰራን ነው፤ ያንን ነዳጅ ጨምረን ፍጥነታችንን አሳድገን ወደፊት መሄድ ነው፡፡ አገራችን የረጅም ጊዜ ታሪክ፣ ስልጣኔና ቅርስ ባለቤት እንደመሆኗ፣ ይህችን ትልቅ አገር አጉልቶ ታሪኳን፣ ስልጣኔዋንና ቅርሷን ለማሳየት በርካታ ስራ መሰራት አለበት፡፡ ለዚህ ደግሞ ብዙ ርብርብ ይጠይቃል፡፡ አመለካከትን መቀየር፣ ቅርስንና ሀብትን ወደ ብሔራዊ ጠቀሜታ መለወጥ ያስፈልጋል፡፡
እርስዎ ከተሾሙ በኋላ ሁለት ጊዜ የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ታውጇል፡፡ ይህ ደግሞ በዋናነት እርስዎ የሚመሩትን የቱሪዝም ዘርፍ የሚጎዳ ነው፡፡ በአገሪቱ ላይ ተፈጥሮ የነበረው የሰላም መታወክና አለመረጋጋት በቱሪዝም ላይ ያሳደረው ተጽዕኖ ምን ያህል ነው?
ቱሪዝም እንደሚታወቀው በመጀመሪያ ደረጃ የሚፈልገው ሰላምና መረጋጋትን ነው፡፡ ይሄ ግልፅ ነው። አንድ ቱሪስት ከአንድ አገር ወደ ሌላ አገር ለመዘዋወር መጀመሪያ የሚጠይቀውና የሚያጠናው የሚሄድበትን አገር ደህንነት፣ ሰላምና መረጋጋት ነው፡፡ ከዚህ አንፃር እኛም አገር ተፅዕኖ ማሳረፉ የሚካድ አይደለም፡፡ በተለይ ደግሞ አንዳንድ አገሮች የሚያወጧቸው የጉዞ መረጃዎች የተጋነኑ መሆናቸው፣ ዘርፉ ላይ ተፅዕኖ ማሳረፉ ምንም ጥያቄ የለውም፡፡
ሆኖም እነ እስራኤልን ብትመልከቺ፣ በየቀኑ ቦንብ እየፈነዳ ውሎ የሚያድርበት አገር ነው። ግብፅና ሌሎችም አገራት እንደዛው ናቸው፡፡ በዓለም ላይ ሙሉ በሙሉ ወይም መቶ ፐርሰንት መረጋጋት አለ ማለት አይቻልም፡፡ ግን እስራኤልም ሆነ ሌላው አገር ቱሪስት እንደ ጉድ ይጎርፋል፡፡ ነገር ግን ኢትዮጵያ ውስጥ ትንሽ ኮሽ ሲል የሚጋነን ነገር  አለው፡፡ የሆነ ሆኖ የአገሪቱን ገፅታ ለመመለስ በተደረጉ የተለያዩ ጥረቶች፣የቱሪስት ፍሰት የተፈራውን ያህል አልቀነሰም ማለት ይቻላል፡፡
በአሁኑ ወቅት እመጣለሁ ብሎ ጉዞ የሰረዘ ቱሪስት የለም፡፡ ሰሜን ተራሮች ብትሄጂ ቱሪስት በብዛት አለ። ሌሎች የቱሪስት መዳረሻዎችም ላይ እንዲሁ፡፡ ነገር ግን አሁንም ጠንክረን መስራት ይኖርብናል፡፡ ከዚህም በኋላ የቱሪስቶች መምጣትና መቅረት፣ በምንሰራው ሥራ የሚወሰን ነው የሚሆነው፡፡ ከዚህ አኳያ የተለያዩ ስራዎች እየሰራን ነው፡፡ አሁን አገሪቱ የተረጋጋ ሁኔታ ላይ ነው ያለችው፡፡ ለየትኛውም ቱሪስት የስጋት ምንጭ የሆነ ነገር የለም፤ግን አሁንም ከዚህ በተሻለ መስራት አለብን፡፡
በላሊበላና በጣና ሀይቅ ላይ ትልቅ አደጋ መጋረጡ ቢታወቅም፣ እነዚህን ቅርሶች ለመታደግ መንግሥት በተለይም እርስዎ የሚመሩት መሥሪያ ቤት ዳተኝነት አሳይቷል የሚል ወቀሳ ይሰነዘራል፡፡ የእርስዎ ምላሽ ምንድን ነው?
ምንም ዳተኝነት የለም፤ ማድረግ ያለብንን ሁሉ እያደረግን ነው፡፡ አገራችን የበርካታ ተፈጥሯዊና ሰው ሰራሽ ሀብቶች ባለቤት እንደ መሆኗ፣ ቅርሶቿ ፈተና ይገጥማቸዋል፡፡ ይሄ በየትኛውም ዓለም ያለ ነገር ነው፡፡ ሁሉም ነገር ዘላለማዊ አይደለም፡፡ ከዚህ አኳያ ላሊበላን ያየን እንደሆነ፣ ረጅም እድሜ ያለው ጥንታዊ፣ከአንድ አለት የተፈለፈለ፣ አለቱም በቀላሉ የሚፈረካከስና ውስብስብ አርክቴክቸራል አሻራ ያረፈበት ትልቅ የአብያተ ክርስቲያናት ቅርስ ነው፡፡ እንግዲህ ቅርሱ ከእድሜውም ባሻገር በዝናብና በፀሐይ የተለያዩ ጉዳቶች ደርሶበታል፡፡ በተጨማሪም ከዚህ በፊት የተደረጉ የጥገና ስራዎች ለምሳሌ፡- ጥላው (ሼዱ) ተፅዕኖ አሳድሮበታል የሚል ከፍተኛ ስጋት አለ፡፡
እርስዎ  ቦታው ድረስ ሄደው ችግሩን  አይተውታል?
ኦው… በጣም ብዙ ጊዜ! በነገራችን ላይ እዚህ መስሪያ ቤት እንደተመደብኩ መጀመሪያ የሄድኩትም ላሊበላ ነው፡፡ ከስጋቱ አኳያ አንድ አጥኚ ቡድን አቋቁመን፣ ጥናት አካሂዶ ውጤቱን ሰጥቶናል፡፡ የጥናቱ ውጤት የሚያሳየውም ችግሩ አስጊ መሆኑን ነው፡፡ ስለሆነም ችግሩን ለመቅረፍ የባህልና ቱሪዝም ሚኒስቴር እንዲሁም የቅርስ ጥናትና ጥበቃ ባለስልጣን በርካታ ሥራዎችን እየሰሩ ነው፡፡  
ለምሳሌ ሊጠቅሱልኝ ይችላሉ---?
አንደኛ ከዩኔስኮና ይህንን ሼድ ከሰራው ኩባንያ ጋር ተገናኝተን በመነጋገር፣ባለፉት ሶስት አራት ቀናት አንድ ቡድን መጥቶ ላሊበላን እያየው ይገኛል፡፡ አሁን ነገ (ሰኞ ነው ቃለ ምልልሱ የተደረገው) ከእኛ ጋር ስብሰባ አላቸው። እነዚህ ባለሙያዎች ችግሩ በትክክል ምን ደረጃ ላይ እንዳለ ይነግሩናል፡፡ የባለሙያዎች ቡድኑ ከጣሊያንና ከዩኔስኮ የተውጣጡ ናቸው። እነሱ የሚሉትን እንሰማለን፡፡ የእኛ ባለሙያዎችም ያጠኑት አለ። እነሱም እይታቸውን ይገልፁልናል፡፡ ዞሮ ዞሮ እኛ ሪስክ አንወስድም፤ትንሽም ቢሆን የሚያሰጋን ነገር ካለው እንደ መንግስት ሼዱ እንዲነሳ ነው የምንፈልገው።
ላሊበላን ለመታደግ ከፍተኛ ገንዘብ ያስፈልጋል ተብሏል፡፡ ይሄን ገንዘብ ከየት ለማግኘት ነው ያቀዳችሁት?
እንዳልሺው እጅግ ብዙ ገንዘብ ያስፈልጋል፡፡ ምን ያህል ነው ለሚለው የተለያየ ግምት አለ፤ ግን ገና ዝርዝሩ አልተሰራም፡፡ ዞሮ ዞሮ በሚኒስቴር መስሪያ ቤታችን ወይም በቅርስ ጥናትና ጥበቃ ባለስልጣን አቅምና በጀት የሚሰራ አይደለም፡፡ ሀገራዊ ንቅናቄ ተፈጥሮ፣ ሀብት መሰብሰብ አለበት። ይህንን ጉዳይ በተመለከተ ከጠቅላይ ሚኒስትር ቢሮ ጋር ተነጋግረናል። በተለይ ከምክትል ጠ/ሚኒስትሩ ጋር ረጅም ውይይት አድርገን፣ ጥናቱን ያቀረብንላቸው ሲሆን አንድ አገራዊ ኮሚቴ እንደሚቋቋምና የላሊበላ ጉዳይ ብሔራዊ አጀንዳ እንደሚሆን ተወስኗል፡፡ በተለይ ከቱሪዝም ዘርፉ ጥቅም የሚያገኙ አካላት በሙሉ፡- ቤተ ክህነት፣ ቱር ኦፕሬተሮች፣ አየር መንገድና ሆቴሎች እንዲሁም ሁሉም ኢትዮጵያውያን እንዲረባረቡና የበኩላቸውን እንዲወጡ፣ የፌደራልም ሆነ የክልል መንግስታትም ተባብረው የሚያስፈልገውን ሀብት በማሰባሰብ ስጋቱ እንዲቀረፍ ለማድረግ ስምምነት ላይ ደርሰናል። በቅርቡ ይህንን ብሔራዊ አጀንዳ አድርገን ለህዝቡ እናስተዋውቃለን፡፡
የጣናም ጉዳይ ከላሊበላ በባሰ መልኩ ትልቅ ፈተና ነው፡፡ እንደሚታወቀው ዩኒቨርሲቲዎቻችን ምርምር እያካሄዱ ነው፡፡ እንዴት አድርገን መጤውን አረም እናስወግዳለን የሚለውን ጥያቄ ለመመለስና በእውቀት ላይ የተመሰረተ እርምጃ ለመውሰድ የሚያስችል ስራ እየተሰራ ነው፡፡
የውጭ አገራት የወሰዱብንን በርካታ ቅርሶች ለማስመለስ እየጣርን ነው፡፡ ነገር ግን  አፄ ቴዎድሮስ ከተወለዱበት እስከ ተሰዉበት ባሉት ታሪካዊ ቦታዎች ላይ የሚገኙት ቅርሶች ሙዚየም የላቸውም፡፡ አጼው በነገሱባት የዳናሞራዋ ደራስጌ ማርያም እጅግ ውድ ታሪካዊ ቅርሶች አልባሌ ቦታ ላይ ነው የሚገኙት፡፡ እዚህ ያሉት ቅርሶች በአግባቡ የሚቀመጡበት ሳያገኙ  ከውጭ የሚመጡትን የት ልናደርጋቸው ነው---?
እርግጥ ነው እስካሁን ብዙ ሙዚየም አልገነባንም። በርካታ ሙዚየሞች ያስፈልጉናል፡፡ እጅግ በርካታ ልናሳየው የምንችለው ሀብት አለ፡፡ ስለዚህ ሙዚየሞች በብዛት መገንባት አለባቸው። ሙዚየም የሚገነባው ደግሞ በመንግሥት ብቻ አይደለም፡፡ የሃይማኖት ተቋማት፣ ከፍተኛ የትምህርት ተቋማት ሙዚየም መገንባት አለባቸው፡፡ ለምሳሌ አዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ትልቅ ኤትኖግራፊክ ሙዚየም አለው፡፡ ግለሰቦችም ሆኑ መንግሥት ሙዚየሞችን መገንባት አለባቸው። የክልልም የፌደራልም ተቋማት ሙዚየም መገንባት ይገባቸዋል፡፡
ሆኖም  የውጭዎቹ ቅርሶች ይመለሱልን እንጂ የምናስቀምጥበት አናጣም፡፡ በነገራችን ላይ በየቦታው የተጀማመሩ የሙዚየም ፕሮጀክቶች አሉ፡፡ ለምሳሌ የመቅደላ አምባ ሙዚየም በሀሳብ ደረጃ ቀርቧል፤ ያንን ተረባርቦ መገንባት ያስፈልጋል፡፡ እንግሊዞችም እንደ ካሣ፣ ይህን ግንባታ ማገዝ አለባቸው፡፡ በግንባታ ብቻም ሳይሆን ባለሙያን በማሰልጠን ሊያግዙን ይገባል። እንግሊዞች ብቻ ሳይሆኑ ሌሎች የእኛን ቅርሶች ወስደው ሲጠቀሙ የነበሩም ሆነ እየተጠቀሙ ያሉ አገራት ድጋፍ ማድረግ አለባቸው፡፡ እኛም ትኩረት ሰጥተን በጀት መድበን፣ ከህዝቡም አሰባስበን፣ በርካታ ሙዚየሞችን መገንባት አለብን፡፡ ይህ እንዳልኩት የሁሉንም ርብርብ ይጠይቃል፡፡  

 “--ለአውጉስጢን ታላቅ ክብር ያለው ጥበብ ሃይማኖት ነው፤ የዕውቀቶች ኹሉ መዳረሻ ለሃይማኖት ማገልገል መቻል ነው፤ ፍልስፍና
ከተፈጥሮ ጋር የተናበበችና በምክንያት የምትመራ ስለኾነች ለክርስትና ሃይማኖት መልካም አገልጋይ መኾን ትችላለች፡፡--”

    መግቢያ
ቅኔ ከፍልስፍና ጋር ባለው ግንኙነት ዙሪያ የምናደርገውን ምርመራ በግሪክ ፈላስፎች ዙሪያ ተሽከርክረን፣ ባለፈው ሣምንት የአርስቶትልን ክርከር ዐይተን ነበር ያቆምነው፤ ለዛሬው የቅዱስ አውጉስጢን (St. Augustine) ዕይታ እንቃኛለን፡፡
ቅ. አውጉስጢን የተወለደውና የተማረው በሰሜን አፍሪቃ ነው፤ የኖረበት ዘመን እ.ኤ.አ ከ354- 430 ዓ.ም ነው፡፡ ክርስቲያን ሳይኾን በፊት በሚላን እና በካርቴጅ አስተማሪ እና የት/ቤቶቹ ቀዳሚ ሊቀመንበር ነበር፤ ክርስትናን ከተቀበለ በኋላ ግን ወደ ሰሜን አፍሪቃ ተመልሶ የመኖኮሳት ማኅበርን መሠረተ፡፡ ከዚያም ክህነት ተቀብሎ በሂጶ ጳጳስ ኾነ፡፡ ቅ. አውጉስጢን በተለየ የሚታወቅበት ሥራው የእግዚአብሔር መናገሻ (The City of God) በሚለው መጽሐፉ ነው፡፡
ሊቁ አውጉስጢን ቀድሞ ባለቅኔ ነበር፤ እንዳውም በቅኔው ተወዳድሮ በማሸነፍ እሰከ መሸለም ደርሶ እነደነበር ይነገራል፤ ኋላ ግን ክርስቲያን ሲኾን ያ ኹሉ መውደስ ለባዕድ አምልኮ የሚቀርብ መኾኑን ተረዳ። ስለዚህ ቅኔን ገሸሽ በማድረግ ወደ ማራከስ ዞረ፤ ፍልስፍናንም የክርስትና ሃይማኖት ገረድ አድርጎ በመቅጠር፣ የፕሌቶ የቅኔና የፍልስፍና ንትርክን ቀይሮ፣ በቅኔና በሃይማኖት መካከል የሚደረግ ‹የእኔ እበልጥ እኔ እበልጥ›  ፉክክር አድርጎ ሞገተ፡፡
በአውጉስጢን ላይ ተፅእኖ ያሳደሩ ሦስት ሰዎች አሉ፡- ፕሌቶ፣ ፕሎጢኑስ (Plotinus) እና ማርቆስ ቫሮ (Marcus Varro) ናቸው፡፡ ፕሌቶ ቅኔን በቅጅ ቅጅነትና በተረትነት በመፈረጁ ‹አደገኛ› የሚል ‹ታፔላ› ለጥፎቦታል፤ አውጉስጢንም እንደ ፕሌቶ ቀድሞ የባዕድ አምልኮን አወዳሽ ባለቅኔ ስለነበር፤ ክርስቲያን ከኾነ በኋላ ቅኔን በማንከዋሰስ ከፕሌቶ ጋር ተስማማ፤ በዚህ የተነሣም የፕሌቶ አወዳሽ ለመኾን በቃ፡፡ የThe City of God የሚለው መጽሐፉ የመጀመሪያ ክፍልም ለፕሌቶ ውደሳ ያሽጎደጎደበት ነው፡፡ አውጉስጢን ለፕሌቶ ውዳሴውን በማሽጎድጎድ የቸረው ቅኔን በቅጅ ቅጅነትና በተረትነት አወራርዶ ስላቃለለ እና በአደጋነት ስለፈረጀ ነው፡፡
ሌላው የፕሌቶ አስተምህሮ ፕላቶናዊያንን አስገኝቷል፤ አውጉስጢን ወደ ክርስትና ሲቀየር ሰብዕናውንና አስተሳሰቡን የቀየሩትና ተጽዕኖ ያደረጉበት እነዚህ ፕላቶኒያውያን ሲኾኑ በተለይ ፕሎጢኑስ እና ቫሮ ግንባር ቀደሞቹ ናቸው። የእነዚህ ሐሳቢያን ተፅእኖም በአውጉስጢን የፈጠራና የአስተውሎት ችሎታ እየተሽከረከረ ወደ የቅኔ እና የሃይማኖት ፉክክር አድርሶታል፡፡
የፕሎጢኑስ ተፅእኖ
አውጉስጢን መጀመሪያ ከክርስትና ጋር ሲገናኝ ‹በመጀመሪያ ቃል ነበር፤ ቃልም በእግዚአብሔር ዘንድ ነበር፤ ቃልም እግዚአብሔር ነው› የሚለው የዮሐንስ ወንጌል ጥቅስ፣ በፕሎጢኑስና በደቀ መዝሙሩ ፖርፊሪ (Porphyry) እየተተረጎመ ተብራርቶ አገኘው። ቃል ደግሞ በፅርዕ (በግሪክ) ሎጎስ ስለሚባል የቃልም ትርጉም አመክንዮ (ምክንያተ ነገር) ማለት መኾኑን ተረዳ፤ የምክንያት ትስስርም ከቅኔ የበለጠ ከሰማያዊ ፍልስፍና ጋር እንደኾነ በማየትም በምክንያት ለምትመራው ፍልስፍና የበለጠ ክብር ሰጠ፡፡
ፕሎጢኑስ የፈላስፎችና የባለቅኔዎች ሥራ በከፍተኛው የማሰላሰል ደረጃ ላይ ሊገናኝ (ሊገጣጠም) ይችላል ይላል፤ ልዩነቱን የሚፈጥረው ማሰላሰልን በዕውቀት (በሥልጠና) የመደገፍ ኹኔታ ስለኾነ ለባለቅኔዎች፣ ለሙዚቀኞችና ለሌሎች የአርት ሰዎች ፊት ለፊት ከሚታየው ክስተት ባለፈ ያለውን መስተጋብር እንዲያስተውሉ፤ እዚያ ማዶ (ከአካባቢያቸው ባለፈ) ያለውን ራዕይ እንዲይዙ ይመክራል፡፡
ስለ ተረት በጥልቅ አስተውሎቱ ፕሌቶን ራሱ ‹የተረት ጸሐፊ ነው› ብሎ ይሞግታል፡- ፕሎጢኑስ፤ ይህ የፕሌቶ ተረትም በማስደነቅ ምሥጢር ይዞ የየትኛውንም አስተሳሰብ ጥልቀትና ስፋት ለመመርመር መነሻ ይኾናል፤ ይህንንም ማወቅና መረዳት የምንችለው ዘይቤያዊ ስልቶችን (በማመሳሰል፣ በማነጻጸር፣ በመወከል፣…) በመጠቀም መኾኑን ሞግቷል፡፡
ፍልስፍናዊ አሰላስሎትም ባለቅኔውን የቅኔን የተፈጥሮ ገላጭነትና ተፈጥሮ የምትፈልገውን መያዝ እንዳለበት እንዲገነዘብ ያደርገዋል ይለናል። ስለዚህ  ቅኔ (አርት) እንደ ፕሌቶ ተፈጥሮን አስመስሎ መቅዳት ብቻ ሳይኾን ከተፈጥሮ ምንጭ ፈልቆ መፍሰስም በመኾኑ፣ ቅኔ ራሱ የህልው (እውን) ነገር ተፈጥሮን መረዳት እስከቻልነው ድረስ መግለጫና መመርመሪያ ጥበብ መኾኑን ሞግቷል፡፡ በሙግቱም ተፈጥሮ በከፍተኛው ደረጃ እውን ነገርን እንድንረዳ የምታደርገው ተፈጥሯዊ ፍሰቱን ጠብቃ እንደኾነው፤ የአርትን (የቅኔን) ምንነትም በተመሳሳይ መልኩ መረዳት ይገባናል ይላል፡፡
ለፕሎጢኑስ  እውነት በቁስ አካል፣ በነፍስ፣ በአእምሮና በአሐድነት ላይ ያርፋል፤ በዚህም የምትገኝ እውነትም ከመልካምነት ጋር የተዋሐደች ናት፡፡ አሐድነት የኹሉም ምንነት መሠረት ነው፤ አእምሮ ደግሞ የመኾን ኑባሬ እውንነት ነው፡፡ ነፍስም በኹለት ትከፈላለች፡- የዓለም (የኹሉም) ነፍስ  እና የግለሰቦች (ዝርዝር) ነፍስ በሚል፤ እሷም የአካላችን (የሥጋችን) አንቀሳቃሽ ኃይል ናት፤ አካላችን ደግሞ የቁስ አካል ሥሪት ነው፤ ቁስ አካልም ከኹሉም ሥር የሚገኝ ያዥ (ንጣፍ) ነው በማለት ይተነትናል፡፡
በዚያም ላይ ‹እሺ የሕይወት ከፍታው ምንድን ነው?› ብሎ ይጠይቅና  መልሱን ‹አእምሮ› በማለት ይሰጣል፤ አእምሮ እኛን ወደፊት የሚገፋፋንን (የሚያንቀሳቅሰንን) የሰዎችን ነፍስ ጠባያትና የእግዚአብሔርን ሕሊና ጠባያት አዋሕዶ መያዙን ይሞግታል፤ ስለኾነም በከፍተኛ ሕይወት የሚገኝ ትልቁ ሥጦታ የሶቅራጥስ እሰጥ አገባ ነው ይለናል። በዚህ ሥጦታ ነፍስ ኹሉንም ነገር ትመረምራለች፣ ሕሊናም ከአድማሱ ወዲያ ያለውን ኑባሬ ሳይቀር ጠልቆ ያያል፤ ከኹሉም ግን ምርጡ የፍልስፍና ክፍል የእሰጥ አገባ ስልት ነው ይለናል፡- ፕሎጢኑስ።
‹እንዴት ግን በዚህ መልክ ጥልቅ የኾነውን የከፍታ ዕውቀት ገንዘብ ማድረግ ይቻላል?› ሲባል፤ መልሱ በዘይቤ ወይም በምሳሌ ስልት አእምሯችን እየተምዘገዘገ፣ የምሥጢረ ፍጥረትንና የግብረ-ገብን ከፍታን መጥቆና ሰርጎ በመግባት የኑባሬ ምሥጢር፣ የጥልቀት መዳረሻ፣ የንፅሕና ጥግ፣ የኹሉም ነገር መሠረት፣… የኾነውን ነገር መመርመር/መፈተሽ ይችላል ይለናል፡፡  
ደረጃ አውጥቶ ሲያስቀምጥም፤ የከፍታውን ጫፍ መልካምነት አድርጎ ዝቃጩን ሥፍራ ደግሞ ቁስ አካል ያደርገዋል፤ መልካምነት ከመጠበብም የሚበልጥና የኹሉም ነገር ከፍታ ነው ይላል። የፍልስፍና እና የቅኔ መደነቅም ከቁስ አካል ጋር ተያይዞ ከሚገኝ ውበት ጋር ከኾነ ይጠፋል፤ በመልካምነት ተውህቦ ከኾነ ግን ይዘልቃል የሚል ክርክር ነበረው፡- ከታች ወደ መልካምነት ጫፍ ሲያወጣ፡፡ ስለኾነም ቅኔ ከተውህቦ፣ ከዜማና ከጥበብ ንድፍ ይጀምራል፤ ይኽም ቅኔ ከዝቅተኛው ወደ ከፍተኛው ዕይታ መምጠቅ እንዳለበት ይከራከራል፡፡ በአጠቃላይ ግን የፕሎጢኑስ ትልቁ ተፅእኖው፤ አውጉስጢን ወደ ክርስትና እንዲመለስና ፍልስፍናን የሃይማኖት ገረድ ለማድረግ ማስቻሉ ነው፡፡
ማርቆስ ቫሮ
የፕሌቶ ተፅእኖ ብቻ ሳይኾን ቫሮም ያደረገው የአማልክት ምደባም ለአውጉስጢን ትልቅ ግብዓት ኾኖታል፡፡ ቫሮ የሚታወቀው አማልክትን በየግብራቸው መሠረት በመከፋፈል ነው፤ በዚህም 20 (12 ወንዶች እና 8 ሴቶች) አማልክትን ለይቶ አቅርቧል። እነዚህን አማልክትም በሦስት ምደባዎች ጠቅልሎ አስቀምጧቸዋል፡- የሥነ-ተረት፣ የሲቪልና የተፈጥሮ አማልክት በሚል፡፡ የሥነ ተረት አማልክት ከባለቅኔዎች ሥራ ጋር ሲያያዙ፣ የሲቪል ደግሞ ከከተማ ሕዝብ ተግባራት ጋር የተያያዙ ናቸው፤ በሰው ሠራሽ ድርጊቶች (ለምሳሌ በትያትር) ይገለጻሉ፤ የተፈጥሮ አማልክት ደግሞ ከፈላስፎች ተግባራት ጋር የተቆራኙ ሲኾኑ በተፈጥሮ ጠባይ የሚገለጹ ናቸው በሚል ተከራክሯል፡፡
የሰው ሠራሽ ነገሮች የሚገለጹት በአርት ሥራ ሲኾን ከእውነት በጣም የራቁ ወይም ሐሰተኞች ናቸው፤ ቀጥታ ከተፈጥሮ ጋር የሚገናኙት ግን ለእውነትነት በጣም የቀረቡ ናቸው ይላል፡፡ ሰው ደግሞ ከሐሰት ይልቅ እውነትን መምረጥ ስላለበት የተፈጥሮን ጥበብ የሚያጠናው ፍልስፍና ከቅኔ የበለጠ ክብር ሊሠጠው ይገባል ይለናል፤ ስለዚህ በተረትነት ከተፈረጀው ከቅኔ ይልቅ ከተፈጥሮ የሚቀዳው ፍልስፍና የተሻለ እውነት ያለው ነው፡- ለአውጉስጢን፡፡  
ኾኖም አውጉስጢን ቅኔ ስለ አማልክት ተረት በጥልቀት የሚያወራ የሐሳብ ቤት በመኾኑ ይስማማል፤ ግን ደግሞ ሐሰተኛ አማልክትን እንጂ እውነተኛ አምላክን አይገልጽም ባይ ነው፡፡ የዚህን ምክንያት አውጉስጢን ሲገልጽ፤ ቅኔ የሚያቀነቅነው የምድራዊና ሰው ሠራሽ አማልክትን ተግባራት ስለኾነ እና ባለቅኔዎች የሚቀኙት በጋኔን መንፈስ እየተመሩ ስለኾነ፣ ከእውነተኛው አምላክ ጋር አይገናኙም፡፡ ለአውጉስጢን ከተፈጥሮ አማልክት ጋር ስለሚገናኝ ፍልስፍና ለእውነት ከሌሎች የበለጠ ቅርብ ነው፤ አንዱን አምላክ ከሌላው ለመለየትም ትልቅ ሚና ይጫወታል፤ ምድራዊ አማልክቱ ግን እርስ በራሳቸው ስለማይስማሙ ምድራዊ ፍልስፍና እውነተኛውን አምላክ ለማወቅ አያስችልም፤ ትክክለኛው አምላክ የመጨረሻው እውነት መኾን አለበት፤ ይህም የተገለጸው በክርስትና ሃይማኖት ነው ይላል፤ ለእሱ ክርስቲያን የሰማያዊት ከተማ ባለርስት ነው፡፡
የምድራዊ ከተማ ለሐሰተኛ አማልክት ሲያገለግል፣ ሰማያዊ ከተማ ደግሞ የእውነተኛው አምላክ መገለጫ ነው፤ ሐሰተኛ አምላክ በባለቅኔዎች ሲገለጽ እውነተኛው ደግሞ በነቢያት ይገለጻል። የምድራዊ ፈላስፎች ለባለቅኔዎች ምላሽ ሲሰጡ የክርስትና ፈላስፎች ደግሞ ለነቢያት ትንቢት መልስ ይሰጣሉ፤ የምድራዊ ከተማ ፍልስፍናንም ይገነዘባሉ፤ ምክንያቱም እውነተኛው እግዚአብሔር የሚናገረው በነቢያት ነውና ብሎ ሞግቷል፡፡ እውነተኛው አምላክም ኹሉንም ነገር የሠራ፣ የእውነት ገላጭና ደስታን ሰጪ (አዳይ) ስለኾነ ‹እውነተኛ ፈላስፋ የእግዚአብሔር አፍቃሪ ነው› የሚል ክርክር አቅርቧል፡፡ ኾኖም እውነተኛው አምላክም ለዓለሙ የተገለጸው በፈላስፎች፣ በባለቅኔዎች ወይም በሲቪል ሰዎች ሳይኾን በኢየሱስ ክርስቶስ ነው የሚል መደምደሚያ ላይ ደርሷል፡፡
በአጠቃላይ
ለአውጉስጢን ታላቅ ክብር ያለው ጥበብ ሃይማኖት ነው፤ የዕውቀቶች ኹሉ መዳረሻ ለሃይማኖት ማገልገል መቻል ነው፤ ፍልስፍና ከተፈጥሮ ጋር የተናበበችና በምክንያት የምትመራ ስለኾነች ለክርስትና ሃይማኖት መልካም አገልጋይ መኾን ትችላለች፡፡ የሥነ ተረት ሥነ መለኮት ግን የባለቅኔዎች የባዕድ አምልኮ ማቀንቀኛ ስለኾነ ከክርስትና ሃይማኖት ጋር አይስማማም፤ ይህም የቅኔን ፉክክር እንደ ፕሌቶ ከፍልስፍና ጋር ሳይኾን ከሃይማኖት ጋር በማድረግ የክርክሩን ዓይነት ቀይሮታል፡፡ አውጉስጢን በዚህ በሥነ-ተረት አስተሳሰቡ በተለይ ከአርስቶትል ጋር አይስማማም፤ ምክንያቱም አርስቶትል ቅኔን በተረትነት አይነቅፍም፤ የተረትን አስፈላጊነትም ይሞግታል። በአጠቃላይ ግን አውጉስጢን ቅኔን ለጣኦት መወድስ የምታወረድ፣ ፍልስፍናንም የሃይማኖት ገረድ አድርጎ ተከራክሯል።
ፍልስፍናም የሥነ መለኮት ዕውቀት አገልጋይ በመሆኗ፣ ቅኔን ከፍልስፍና መለየት/አለመየቱ ዋና ጉዳይ መኾን የለበትም፤ ይልቁንስ ቅኔ የሥነ ተረት መተረኪያ ስለኾነ፣ በውስጡ ያለው የቋንቋ ስህተት ብቻ ሳይኾን የጋኔን (የሠይጣን) መነጋገሪያ ቋንቋ መሆኑም ዋናው ችግር ነው፤ ይኽም ማለት ቅኔ የሥነ ተረት እምነት (አማልክት) መተረኪያ ነው፡፡
 እሱ እንዳለው ከኾነ፡-
የተፈጥሮ ፈላስፎች ሕዝብን ለመጥቀም ይጽፋሉ፤ ባለ ቅኔዎች ደግሞ ሕዝቡን ለማስደሰት ይቀኛሉ፤ ስለዚኽ የባለቅኔዎቹ ትረካዎች ሕዝቦቹና አማልክቱ የሚደሰቱባቸው የእግዚአብሔር ወገን የኾኑ ሰዎች ሊከተሏቸው የማይገቡ የአማልክቱ ወንጀሎች መኾን አለባቸው፡፡ ስለዚኽ ባለቅኔዎች ከማስደሰት ያለፈ ጥቅም የላቸውም፤ የአማልክቱን ትክክልነት ለመተረትና ለሕዝቡ ክብር ለማስገኘት ይጽፋሉና፡፡
በመኾኑም ለአውጉስጢን ቅኔ መጻፍ እጅግ ዝቅተኛ ጠቀሜታ ሲኖረው፣ ለሃይማኖት የሚጠቅም ፍልስፍና መጻፍ ደግሞ በተቃራኒው ከፍተኛ ጠቀሜታ ይኖረዋል፤ ምክንያቱም ፍልስፍና የሥነ መለኮት ዕውቀት መገልገያ በመኾን ከፍተኛ አገልግሎት ይሠጣልና፤ ቅኔን ግን የአምልኮተ ጣዖት (የባዕድ አምልኮ) ማቀንቀኛ የተረት አካል በማድረግ ይደመድማል፡፡ በመሆኑም ለአውጉስጢን በቅኔና በፍልስፍና መካከል ያለው አለመጣጣም ከፍተኛ ነው፤ በተለይም ፍልስፍና የሃይማኖት አገልጋይ በመኾኗ ፉክክሩን በቅኔና በሃይማኖት መካከል አድርጎ ያጦዘዋል፤ ከእነ ፕሌቶ የሚለየውም የፍልስፍናን ለሥነ መለኮት መመርመሪያ መኾን በማግዘፍ ወይም ለሃይማኖት ከኹሉም የበለጠ ቦታ በማቀዳጀት ነው፡፡

 በአንድ አገር በአንዲት መንደር ውስጥ ብቻውን የሚኖር አንድ ሰዓሊ ነበር፡፡
በመንደሩ ውስጥ አንድ ሐይቅ አለ፡፡ ሐይቁ ሰዓሊው ከሚኖርበት ቤት ጥቂት ራቅ ይላል፡፡
ያ ሰዓሊ ታላላቅ የተባሉ ስዕሎችን ይሰራና ወደ ተለያዩ የዓለም ክፍሎች ይልካል፡፡ በዚህም ታላቅ ስምና ዝናን ያተርፋል፡፡ ይህ ሁሉ ሲሆን ግን የእሱ መንደር ሰው ስለሱ ምንም የሚያውቀው ነገር የለም። እሱ ከማንም አይገጥምም፡፡ ቤቱ ስቱዲዮው ነው፡፡ ከቤቱ ከወጣ ወደ ሐይቁ ሄዶ ቁጭ ብሎ ተፈጥሮን ሲያደንቅ ይውላል፡፡
በዚህ ዓይነት ህይወቱን ሲገፋ ኖሮ፣ አንድ ቀን ታመመ፡፡ ብዙ ማቅቆ ማቅቆ ሞተ፡፡
የዓለም የዜና ማሰራጫ አውታሮች በጠቅላላ የሚያወሩት ስለዚያ ታላቅ ሰዓሊ ሆነ፡፡ የማታ ማታ የመንደሩ ሰው፤ የአገሩ ታላቅ ሰዓሊ መሆኑንና በዓለም ላይ ስመ ጥር ሰው መሆኑን አወቀ፡፡ ስለዚህ በስሙ አንድ ማስታወሻ ማቆም ያስፈልገናል ተባለና መመካከር ጀመሩ፡፡
አንደኛው - ይህ ታላቅ ሰዓሊ ጠባዩ ምን መሳይ ነበረ? በትክክል ገፅታውን ያስተዋለ ሰው አለ?
ሁለተኛው - አመለካከቱስ? ፍልስፍናውስ? ትምህርቱስ ምንድን ነበር?
ሦስተኛው - ይሄንን ለማወቅ ያስቸግራል፡፡ ምክንያቱም ማንም አናግሮት የሚያውቅ ሰው የለም፡፡ ስዕሉን እንኳን ዓይተንለት አናውቅም፡፡ ስለዚህ ማንን ጠይቀን መረጃ እናግኝ?
አንደኛው - ማንንም ልንጠይቅ አንችልም፡፡ የሚሻለው ሁልጊዜ ይሄድበት የነበረውን ሐይቅ ሄደን መጠየቅ ነው፡፡
ሁሉም ወደ ሐይቁ ሄዱ፡፡ ከዚያም፤
“ሐይቅ ሆይ! ታላቁ ሰዓሊያችን አርፏል፡፡ እኛ አንድ መታሰቢያ ልናቆምለት አስበናል፡፡ ሆኖም መልኩን እንኳን በቅጡ ማስታወስ የሚችል ሰው ጠፋ፡፡ ስለዚህ ያ ሰዓሊ ምን መሳይ እንደነበር እንድትነግረን ነው ወደ አንተ የመጣነው!”
ሐይቁዉም፤
“አመጣጣችሁ መልካም ነው፡፡ ሆኖም ብዙ የምረዳችሁ አይመስለኝም፡፡ ምክንያቱም እናንተ፤ ሰውን በህይወቱ እያለ ከማክበር ይልቅ ሲሞት ክብር የምትሰጡ ሰዎች ናችሁ፡፡ እኔም ብሆን በመጣ ቁጥር ዐይን ዐይኑን ሳይ ነው የከረምኩት፡፡ ስለዚህ ዐይኑ ብርሃን እንዳለው ብቻ ነው የማውቀው፡፡”
*   *   *
ብርሃናማ ሰዎቻችንን ለማወቅ የውጪ ሰው እስኪነግረን አንጠብቅ፡፡ እኛው ብርሃናማ ሰዎቻችንን እንወቅ፡፡ ከየትኛውም ጠባብነት፣ ከየትኛውም ትምክህተኝነት እንለያይ፡፡ የምስራቅንና ምዕራብ ጀርመንን ይከፍል የነበረው “ታላቁ” ግምብ፤ ዛሬም ጀርመናውያን አዕምሮ ውስጥ አለ ይባላል፡፡ ግምብን በአካል ማፍረስ ብቻ ሳይሆን አገርን የሚያድነው፤ አንድያውን ከአዕምሮ መሰረዝ ነው! ምናልባትም ሥር ነቀል ለውጥ (Radical Transformation) የሚመጣው አላስፈላጊ ጉዳዮችን ከናካቴው ከዕሳቤ በመገላገል ነው! አለበለዚያ “እንደቀንድ - አውጣ ሰንኮፈን፣ እንጭጭ ህሊና ያወጡ” እንዳለው ሎሬት ፀጋዬ፤ በየጊዜው እንጭጭ ህሊና መቀፍቀፍ ይሆናል ዕጣ-ፈንታችን፡፡ ይህን ልብ እንበል፡፡
ሌላው ጉዳያችን፤ ልዩነት ለዘለዓለም ይኑር (viva la difference!) የሚለውን ከልብ መቀበል ነው፡፡ ሆኖም ልዩነት ያለ ጥንቃቄና ያለ ዕውቀት ኪሳራ ነው፡፡ አምላክ አንድ ያደረጋቸውን መለያየት አይቻልም እንደሚባል ሁሉ፤ የለያያቸውንም ማዋሃድ አይቻልም፤ ማለትም ያስኬዳል፡፡ በሁለቱም አባባሎች ውስጥ የኃይል እርምጃ (Coercive measure) እንዳይኖር መጠንቀቅ ነው ዋናው፡፡ የጠረጴዛ ውይይት የሚፈታውን ችግር ጦር ሰብቆ፣ ዘገር ነቅንቆ ካልሆነ፣ አይሆንም ማለት ከግብዝነት የማይተናነስ ጀብደኝነት ነው፡፡ በአንፃሩ በምንም ዓይነት ዘይትና ውሃ መሆኑ የታወቀን ነገር፣ በንግግር ካልፈታሁ ማለት፤
“Poet! Don’t go far a word
When what you all need is a sword
Bile, not the veil, in the war field!”
(“አንት ባለቅኔ ሆይ!
እጦር ሜዳ ገብቶ ጎራዴ ለሚሻው
መፍትሔው ወኔ ነው፣ ቅኔ አይደለም ቋንቋው!
ሀሞትህ ነው እንጂ የሙሽራ ልብስህ
ከባሩድ መካከል፣ ከቶም አያድንህ!”
… እንደማለት ነው፡፡ ሁሉም ነገር አግባብ ባለው ቦታና ሰዓት መደረግ አለበት፡፡ የሹመትና ሥልጣን ሽግግር፤ የለውጥ ዝግጁነትን የሚያስከትል ከሆነ ብቻ ነው፤ ለውጥ የሚገኘው፤ ስለሆነም አመለካከትን መለወጥ ላይ መሰራት አለበት!
ገጣሚው፡-
“በቀን ሦስት ጊዜ እንበላለን ብለን
አንዱም ባንዴ አቃተን!”
እንዳለው እንዳይሆንብን፤ በምግብ ራስን ለመቻል መትጋት ተቀዳሚ መሆን አለበት፡፡ ሁሉን ቢናገሩት ሆድ ባዶ ይቀራልንም መቼም ቢሆን አንዘንጋ!
ሥልጣን የሁልጊዜ ይዞታ አይደለም፡፡ ርስተ - ጉልትም አይደለም፡፡ ወሳኙ ነገር ከህዝብ ጋር እየመከሩ፣ ዘለቄታው ምን ይሁን? የሚረከበንን እንዴት እንምረጥ? እንዴት እንቅረፅ? እኔ እንዴት እዘልቃለሁ ሳይሆን አገር እንዴት ትዘልቃለች? ከትላንት የተሻለች ኢትዮጵያን እንዴት እናምጣት? ማለት ያባት ነው! ምንጣፉን ከእግራችን ሥር የሚጎትቱ ባላንጦች እንዳሉ አንርሳ! ማደግ የሚቻለው የዕድገት ግብአቶችን በትክክል፣ በትክክለኛው ቦታ፣ በትክክለኛው ሰዓት በመጠቀም ነው፡፡ የዚህ ሁሉ መጎናፀፊያው፤ ዕውቀትንና መረጃን መሰረት በማድረግ፣ ዘላቂነትን፤ ረዥም ዕድሜን፤ ከዘለዓለማዊነት ባለማምታታት ነው፡፡
(Not mistaking longevity for eternity)
ዋና ጉዳይ፤ “ሥልጣን ዘለዓለማዊ ቢሆን ኖሮ አንተ ጋ አይደርስም ነበር!” የሚለው የአረቦች ተረት ትርጉም የሚኖረው እዚህ ላይ ነው! ልብና ልቦና ይስጠን!


          “--አካልን በሚጨቁነው በዚህ ሥልጣኔ ውስጥ ይበልጥ ተጎጅዎች ደግሞ በተፈጥሮ ከአካል ጋር ጥብቅ የሆነ ሥነ
ልቦናዊና ስሜታዊ ትስስር ያላቸው ሴቶች ናቸው፡፡ አካልና ስሜትን የሚጨቁን ሥልጣኔ፣ ‹‹የስሜት ምንጭ ናቸው›› ብሎ
የሚፈርጃቸውን ሴቶች የመጨቆኑ ነገር አይቀሬ ነው፡፡ በዚህም ሴቶች ለዘመናት ቂም ይዘው ኖረዋል፡፡--”

           መንፈሳዊነትን በማወደስ ከጥንት ጀምሮ እጅግ በጣም ብዙ ነገር ተብሏል፡፡ እስኪ ዛሬ ደግሞ የመንፈሳዊነት ሌላኛውን ገፅታ እናንሳ፤ መንፈሳዊነት በተሞገሰ ቁጥር ስለሚንኳሰሰው የሰው ልጅ ‹‹አካል›› እናውራ፡፡ በመሆኑም በዚህ ፅሁፍ ውስጥ በባህል፣ በሥነምግባር፣ በኪነ ጥበብ፣ በምሁርነትና በመንፈሳዊነት ስም ‹‹አካል›› ላይ ስለሚደርሰው ዘርፈ ብዙ ጥቃት እናነሳለን።
ይሄንን ፅሁፍ በማዘጋጅበት ወቅት አንድ ልብን በጣም የሚያራራ (በያሬድ ‹‹አራራይ›› ዜማ የተሰራ) መዝሙር ከርቀት ይሰማኛል፡፡ መዝሙሩ ‹‹ከንቱ ነኝ! የከንቱ ከንቱ ነኝ!!›› ይላል፡፡ በዚህ አምስት ቃላትን በያዘ አንድ ዓረፍተ ነገር ውስጥ ‹‹ከንቱ›› የሚለው ቃል ሦስት ጊዜ ተደጋግሟል፡፡ በመቶኛ ስናሰላው 60 ፐርሰንት መሆኑ ነው፡፡ ‹‹ከንቱ›› የሚለው ቃል በአንድ ዓረፍተ ነገር ውስጥ እንደዚህ ታጭቆ ጥቅም ላይ የዋለው ደግሞ ዓለማዊ ህይወትን ለማንቋሸሽና አካልን (የለበስነውን ሥጋ) ለማውገዝ ነው፡፡
በሰው ልጅ ሥልጣኔ ውስጥ ለዘመናት የሰውን ልጅ መከራና ሸክም ከተሸከሙ እንስሳት ውስጥ ዋነኛዋ አህያ ናት፡፡ የሰው ልጅ የሥራ መሳሪያዎቹን ማሻሻል አቅቶት በደነቆረበት ዘመናት ሁሉ የእሱን ድንቁርና የተሸከመችለት አህያ ናት፡፡ አህያ የሰውን ልጅ ድንቁርናውን ብቻ አይደለም የተሸከመችለት፣ ይልቅስ ከድንቁርናው የሚመነጨውን ጭካኔውን ጭምር እንጂ። ድንቁርና ላይ የተመሰረተ ጭካኔ ደግሞ አረመኔነቱ መኖርን ሁሉ ያስመርራል፡፡ አህያ ይሄንን ሁሉ የሰውን ልጅ ዕዳ ተሸክማ ኖራለች፡፡
ከአህያ በላይ የሰውን ልጅ ጭካኔ የተሸከመ አንድ ነገር አለ - እሱም አካል ነው፤ የለበስነው ሥጋ!! አህያ የሰውን ልጅ ጭካኔ ብትሸከም ሳሯን ግጣ፣ ውሃዋን ጠጥታ ነው፡፡ ከስድብ ጋር ዱላ ቢያርፍባት ዱላው እንጂ ስድቡ አይሰማትም፡፡ አካል ግን የእነዚህ ሁሉ ተጠቂ ነው፡፡ ‹‹አካል የመንፈሳዊ ህይወት ፀር ነው›› እየተባለ በርሃብ እንዲጠወልግ፣ በውሃ ጥም እንዲንገበገብ፣ በፍትወት እንዲቃጠል፣ በስድብ እንዲዋረድ ይደረጋል፤ ‹‹ከንቱ ነህ፣ የከንቱ ከንቱ ነህ!!›› ይባላል፡፡
‹‹ከመንፈሳውያኑ አንዱ…›› ይላሉ ፕ/ር ጌታቸው ኃይሌም፤ ‹‹ደቂቀ እስጢፋኖስ›› በተባለው መፅሐፋቸው ውስጥ በገፅ 33፣
ከመንፈሳውያኑ አንዱ ስለ ፅድቅ የውሃ ጥም ሲያቃጥለው በፅዋ ቀዝቃዛ ውሃ ይሞላና ከፊቱ ያስቀምጣል፤ አእምሮቱ ይባሱኑ ያቃጥለዋል። “ለምን እንዲህ ታደርጋለህ?” ቢሉት፣ “ዋጋዬ በእግዚአብሔር ዘንድ እንዲበዛልኝ በስቃዬ ላይ ስቃይ መጨመሬ ነው፤” አላቸው፡፡

“ነፍሳችን እንድትድን ሥጋችንን እንጣላት”
የመንፈሳዊነት ማግኛ መንገዳችን በጣም አስገራሚ ነው፡፡ ግብፃዊው አባ እንጦንስ፤ መንፈሳዊ ህይወት የቆመበትን ዋነኛ ምሰሶ ሲያስረዱ እንዲህ ይላሉ፡-
‹‹ከልብ ስንራብ፣ ስንጠማ፣ ስንራቆት፣ ስናዝን፣ በጣር ላይ ስንሆን ለእግዚአብሔር የተገባን እንሆናለን። እግዚአብሔርን እንድናገኘው ሐዘንን እናስቀድማት፣ ነፍሳችን እንድትድን ሥጋችንን እንጣላት፡፡››
በዚህ ሥልጣኔ ውስጥ ‹‹መንፈሳዊነት ያለ አካላዊ ስቃይ አይገኝም›› የሚል ቅቡል የሆነ አስተሳሰብ አለ፡፡ እውነት ታዋቂ የሚሆነው፣ እሴት የሚገኘው፣ መንፈሳዊነት የሚዳብረው በአካላዊ ስቃይ እንደሆነ ሁሉም ተቀብለውታል፡፡ በዚህም አካላዊ ስቃይ ማህበረሰብንና መንፈሳዊ ተቋማትን የማደራጃ መርህ ሆኗል፡፡ ባህል፣ ሥነምግባርና መንፈሳዊነት አካልን በማሰቃየት የሚገኙ ነገሮች ሆነዋል፡፡  
አካል ላይ የሚወርደው ይህ ጭካኔ፣ ውግዘትና ውርደት ደግሞ በረጅሙ የሁዳዴ ፆም ላይ ጠንከር ይላል። ሁዳዴ ከሊቅ እስከ ደቂቅ አካልን የሚያወግዙበት ወር ነው፡፡ አካልን ለማዋረድና ለማዳከም የቀን መቁጠሪያ ላይ ቀጠሮ ይያዝለታል። ምስኪን አካል!!
በጣም የሚያሳዝነው ደግሞ ከዘርዓያዕቆብና ከወልደ ህይወት ሌላ ለአካል ጠበቃ የቆመ አንድም ኢትዮጵያዊ ምሁር እስከ ዛሬ ድረስ አለማግኘታችን ነው። ዘርዓያዕቆብ ለአካል ጠበቃ ሆኖ መገኘቱ ለኢትዮጵያ ፍልስፍና መነሻ ሆኗል፡፡
በጥንት ግሪካውያን ፍልስፍና የተጀመረው እግዜርን ልክ እንደ ሰው አድርጎ የሚያስተምረውን የነሆሜርን ተረት በመቃወም ነው። በኢትዮጵያ ፍልስፍና የተጀመረው ደግሞ በመንፈሳዊነት ስም አካል ላይ የሚደርሰውን ጥቃት በመቃወም ነው። ይሄንንም ጥቃት ለመከላከል በነዘርዓያዕቆብ በኩል የቀረበው የመፍትሔ ሐሳብ፤ የነፍስንና የሥጋን ቅራኔ መፍታት ነው። በመሆኑም የኢትዮጵያ ፍልስፍና ይሄንን ቅራኔ የማስታረቅ ፕሮጀክት ነው።
መንፈሳዊ ተቋማት አካል ላይ ብዙ ዓይነት ጥቃት ቢያደርሱም ለአካል ጥብቅና የሚቆም ግን አንድም ተቋም የለም፡፡ የሰብዓዊ መብት ተሟጋቾች አካልን ከሌላ ወገን ከሚመጣ አካላዊ ጥቃት የሚከላከሉ ተቋማት ቢሆኑም፣ በመንፈሳዊ ተቋማት በኩል ለሚመጣ አካላዊ ጥቃት ግን ጥብቅና አይቆሙም፡፡
ይህ ዓለም የአካል ነው፡፡ እግዚአብሔር የራሱን እስትንፋስ አካል (ሥጋ) ካለበሳት በኋላ (አዳም ከሆነ በኋላ) እንድትኖር የላካት ወደ ምድር ነው። በመሆኑም ምድር የአካል መኖሪያ ነች፡፡ ይበልጥ የሚያሳዝነውም አካል በራሱ መኖሪያ ላይ መገፋቱና መዋረዱ ነው። አካል በራሱ ዓለም ላይ በደስታና በፈንጠዝያ መኖር ሲገባው፣ ሥነ ምግባርንና መንፈሳዊነትን ውለድ እየተባለ እንዲሰቃይ ይደረጋል፡፡
በምድር ላይ ስደተኛው ሥጋ ሳይሆን ነፍስ ነች፡፡ በመሆኑም፣ በምድር ላይ ይበልጥ መብትና ተሰሚነት ሊኖረው የሚገባው አካል እንጂ ነፍስ አይደለችም፡፡ በዚህ ምድር ላይ ነፍስ ነች እንጂ ለአካል መታዘዝ ያለባት፣ አካል አይደለም ለነፍስ መታዘዝ ያለበት፡፡ በመሆኑም፣ ስደተኛውን ከቀደምት ነዋሪው የበለጠ መብትና ክብር የሰጠው የሰው ልጅ አስተሳሰብ ኢ-ፍትሐዊ ነው፡፡ እናም በዚህ ኢ-ፍትሐዊነት ውስጥ ስደተኛዋ ነፍስ፣ አካል የሚሰቃይበትን ሲዖል በምድር ላይ ፈጥራለች፡፡ አካል በራሱ ዓለም ላይ እየተሰቃየ ነው፡፡
ይበልጥ የሚያናድደው ደግሞ የእግዜሩ ነው። ገነትን ለአዳምና ለሄዋን በአካል እንዲኖሩበት ከእግዜር የተሰጣቸው ሉዓላዊ ስፍራቸው ነው። እግዜሩ ገነትን በአካል እንዲኖሩበት ከሰጣቸው በኋላ ተደብቆ መከታተልን ምን አመጣው? እግዜር የሰጣቸውን ስፍራ እንደፈለጉ በአካል እንዲኖሩበት ማድረግ ሲገባው፣ ስደተኛዋን ነፍስ በአካላቸው ላይ ሾሞባቸው ሄደ፡፡ ከዚያም አካላቸውን ሲኖሩ ለቅጣት መጣ፡፡
እናም እግዜሩ ሳይቀር ያለ ስፍራው መጥቶ አካልን በራሱ ዓለም ላይ ይቀጣዋል። ‹‹ደም ይፍሰስሽ››፣ ‹‹ምጥሽ ይብዛ›› የሚለው ሄዋን ላይ የተጣለው አካላዊ ቅጣት፣ እግዜር በራሷ በሔዋን ዓለም ላይ መጥቶ የጣለው ኢ-ፍትሀዊ ቅጣት ነው፡፡ ኢ-ፍትሃዊነቱ አልበቃ ብሎት ጭራሽ እንዲፀፀቱም አደረገ፡፡
ይበልጥ የሚያናድደውም ይሄ ‹‹ፀፀት›› የሚባለው ነገር ነው። እግዜሩ በሉዓላዊ መኖሪያቸው ላይ መጥቶ የራሱን እንደራሴ (ነፍስን) በአካላቸው ላይ መሾሙና አዳምና ሄዋን ላይ ያደረሰው አካላዊ ቅጣት አልበቃ ብሎት፣ ጭራሽ ‹‹ፀፀት›› የሚባል ዘላለማዊ የህሊና ስብራት፣ በሉዓላዊው አካላቸው ላይ አትሞባቸው ሄደ። ሉዓላዊ መብታቸው መደፈሩ ሳያንስ ‹‹ፀፀት›› የሚባል ዘላለማዊ (ከልጅ ወደ ልጅ የሚተላለፍ) የህሊና ስብራት ተሸካሚ ተደረጉ። ምስኪን ሔዋን!!
አካል፣ ይሄንን ስቃዩን የሚያቃልሉለት ምሁራን ሊኖሩት ሲገባ፣ ዓለም እስከ ዛሬ ድረስ ያፈራቻቸው ምሁራን ግን ጭራሽ በተቃራኒው ስቃዩን ደግፈው የሚፅፉትን ነው፡፡ ምሁራዊ ሽፋን እየሰጡ አካልን ከሚያስጠቁ ሰዎች ውስጥ ግንባር ቀደሙ ደግሞ ዚግመንድ ፍሮይድ ነው፡፡ ‹‹ይህ ስልጣኔ አካላዊ ስሜትን በመጨቆን የተገነባ ነው፤ ያለ አካላዊ ጭቆና፣ ሥልጣኔን ማምጣት አይቻልም›› የሚለው የፍሮይድ አስተሳሰብ፤ አካልን ማሰቃየት ለሚፈልጉና ‹‹የከንቱ ከንቱ ነህ›› እያሉ ለሚያዋርዱት ሰዎች ምሁራዊ ከለላ ይሰጣል፡፡
ይህ ዓለም፣ “ስሜታችንን ሳንጨቁን ስልጣኔን ማምጣት አንችልም” (Non-repressive civilization is impossible) በሚል በእንደዚህ አይነት ትእቢት በተወጠረ መርህ ላይ የተመሰረተ ነው፡፡ በዚህ ትምክህታዊ መርህ ታዲያ ኒቸ እንደሚለው፡-
‹‹ደስታና ድሎትን የምትጠየፍ ፕላኔት፣ ከስሜቱ የተገነጠለና ከተፈጥሮ ስርዓትም ያፈነገጠ፣ ከማህበራዊ ህይወትም ተገልሎ በብቸኝነት የሚሰቃይ፣ ምድራዊ ሕይወትን አምርሮ የሚጠላ፣ ከስቃይ ውስጥም ደስታንና ተስፋን የሚፈልግ ከንቱ የሆነ ማህበረሰብንና ዓለምን ፈጥረናል፡፡››
እስከ ዛሬ ድረስ ዓለም ካፈራቻቸው ምሁራን ውስጥ ለአካል ጥብቅና በመቆም ፍሬድሪክ ኒቸን የሚያክል የለም፡፡ የኒቸ አብዛኛዎቹ ሥራዎቹ ለአካል ጥብቅና የሚቆሙና አካል ላይ የሚሰነዘረውን ምሁራዊና ማህበረሰባዊ ጥቃት የሚያጋልጡ ናቸው፡፡ ከመንፈሳዊ ተቋማት በኩል አካል ላይ የሚሰነዘረው ጥቃት ፊት ለፊት የሚታይ ቢሆንም፤ በኪነ ጥበብ፣ በፍልስፍናና በፖለቲካ አማካኝነት የሚሰነዘረው ጥቃት ግን ስውር ነው፡፡ ኒቸን ከታላቁ ጀርመናዊ የሙዚቃ ቀማሪ ዋግነር ጋር ያጣላውም ይሄው ነበር -  ‹‹በሙዚቃ ውስጥ ብሕትውናን እያሞገስክ አካል ላይ ጥቃት ትሰነዝራለህ›› በሚል፡፡
ኒቸ፣ ‹‹በፍልስፍና ውስጥ ተደብቀው አካልን ያንቋሽሻሉ›› በማለት ከሚከሳቸው ምሁራን ውስጥ ግንባር ቀደሞቹ ፕሌቶና ካንት ናቸው፡፡ ካንት ‹‹የዚህ ዓለም ነገር ‹‹በህወስታችን›› መታወቅ አይችልም›› የሚለው አባባሉ ፀረ - አካል አቋሙን አሳብቆበታል፡፡
ፕሌቶ ለአካል ያለው ጥላቻ ደግሞ ጭራሽ የባሰ ነው፡፡ የፕሌቶ መሰረታዊ ችግር የሚነሳው ከዲበ አካላዊ (ሜታፊዚካል) ፍልስፍናው ነው፡፡ ገና ከመነሻው፣ ዓለምን ‹‹መለኮታዊና ቁሳዊ›› ብሎ ለሁለት መክፈል ሲጀምር ነው አካል ላይ ጥቃት ለመሰንዘር ቆርጦ መነሳቱን ያሳየው። ‹‹በስሜት ህዋሳቶቻችን ተጭበርብረናል››፣ ‹‹ስጋዊ ፍላጎታችንን ከተከተልን አረመኔ እንሆናለን››፣ ‹‹ምድራዊ ሐብትን በሚመኙ ሰዎች ከተመራን እንነቅዛለን›› የሚለው የፕሌቶ ሥነ ዕውቀታዊ (epistemological)፣ ሥነ ምግባራዊና ፖለቲካዊ አስተምህሮው በሙሉ አካልን በማጥላላት ላይ የተመሰረተ ነው፡፡
በመንፈሳዊ ተቋማቱ፣ በኪነ ጥበቡ፣ በፍልስፍናው፣ በፖለቲካው፣ በባህሉ ... በኩል አካል ላይ የሚሰነዘረውን እንደዚህ ዓይነቱን ሁሉን አቀፍ ጥቃት የተመለከተው ኒቸ፤በስተመጨረሻ ‹‹አጠቃላይ ስልጣኔያችን የሰውን ልጅ በማስቃየት የተገነባ (Masochistic civilization) ነው፤›› ወደሚል መደምደሚያ እንዲሄድ አድርጎታል፡፡
“በማሰቃየት” ብቻ ቢሆን ኖሮ ጥሩ ነበር፤ ምክንያቱም የሰው ልጅ በተፈጥሮው ደስታን ፈላጊ ስለሆነ የሚያሰቃየውን ነገር አሽቀንጥሮ ይጥለው ነበር፡፡ ችግሩ ግን ማሰቃየት ውስጥ “ፈቃደኝነትን” እና “ተስፋን” ማስገባታቸው ነው፡፡
ምንም እንኳ አካል ሰብዓዊ ተሟጋች ባይኖረውም አንድ ሁነኛ ጠበቃ ግን አለው - የህመም ስሜት። አካል ጥቃት ሲደርስበት በደሉን የሚያስተጋባለት በህመም ስሜት በኩል ነው። ህመም አካልን የሚከላከለው ሰውየው ላይ ስቃይ በማምጣት ነው። ሆኖም ግን የመንፈሳዊ ተቋማት ‹‹ስቃይ›› የሚባለውን የአካል ተሟጋች የሚያሽመደምዱበት አንድ ዘዴ ዘየዱ- “መታገስና ተስፋ ማድረግ” የሚል፤ ለሚመጣው ዘላለማዊ ህይወት ሲባል አካላዊ ስቃይን መቻልና መታገስ።
ሰው ስቃይን በማስወገድ አካሉን ነፃ እንዳያወጣ፤በዚህ መልኩ ስቃዩን በተስፋ መረዙበት፤ “ይሄንን ስቃይና መከራ ከታገስክ ማርና ወተት ከምታፈልቀው ሰማያዊ መንግስት ውስጥ የዘላለም ህይወት ይኖርኻል፤ እንደ መላዕክትም እያሸበሸብክና አምላክህን እያመሰገንክ በደስታ ትኖራለህ፤” የሚል ተስፋ ሰጡት፡፡ እናም ለዚህ ሰማያዊ ተስፋ ሲል ራሱን በፈቃደኛነት ማሰቃየትን ተያይዞታል፡፡ ለሰብዓዊ መብት ተሟጋቾችም ያስቸገራቸው ነገር ይሄ ‹‹በፈቃደኝነት ራስን ማሰቃየት›› የሚባለው ነገር ነው::
አካልን በሚጨቁነው በዚህ ሥልጣኔ ውስጥ ይበልጥ ተጎጅዎች ደግሞ በተፈጥሮ ከአካል ጋር  ጥብቅ የሆነ ሥነ ልቦናዊና ስሜታዊ ትስስር ያላቸው ሴቶች ናቸው፡፡ አካልና ስሜትን የሚጨቁን ሥልጣኔ፣ ‹‹የስሜት ምንጭ ናቸው›› ብሎ የሚፈርጃቸውን ሴቶች የመጨቆኑ ነገር አይቀሬ ነው፡፡ በዚህም ሴቶች ለዘመናት ቂም ይዘው ኖረዋል፡፡
ታዲያ ሴቶች በነፃነታቸው ማግስት ያደረጉት ነገር፣ “ያለ አካልና ስሜት ጭቆና ሞራላዊና መንፈሳዊ ዕድገትን ማምጣት አይቻልም፤” የሚለውን የዚህን ሥልጣኔ መርህ፣ ስሜታቸው ላይ ትኩረት በማድረግ፣ አካላቸውን በማስዋብና ወሲብ ቀስቃሽ ልብሶችን በመልበስ መቃወም ነው፡፡
የፍሮይድ ተንታኝ የሆኑት ኤርክ ፍሮምና ማርኩዘም፤ ሴቶች አካላቸውን የደስታና የውበት ምንጭ አድርጎ በመሳል አዲስ ዓይነት ማህበራዊ አስተሳሰብ እያመጡ እንደሆነ እንዲህ በማለት ያስረዳሉ፣
‹‹አሁን ያለው ማህበረሰብ የሚመራበት መርህ፤ ፍሮይዳዊውን አስተሳሰብ የሚፃረር ነው፡፡ ይሄም አዲስ ማህበረሰብ አካልን የሚያየው የሞራልና የመንፈሳዊ እድገቱ ፀር አድርጎ ሳይሆን እንዲያውም ወደ ደስታና ነፃነት የሚወስድ ሃይል አድርጎ ነው፤ ይሄም የሚያመላክተው እስከ ዛሬ ድረስ በአካልና በስሜት ጭቆና ላይ የተመሰረተው ማህበረሰብ መሰረቱ እየፈራረሰ መሆኑን ነው፡፡››
እናም አዲሱ ማህበረሰብ አካልን የደስታ፣ የውበትና የነፃነት ምንጭ አድርጎ በመመልከቱ ውስጥ ‹‹መንፈሳዊነት ያለ አካላዊ ስቃይ አይገኝም›› የሚለውን የቀድሞውን መንፈሳዊ ሥልጣኔ እየተሰናበተ ነው፡፡ ኦሾም ‹‹ሴቷ ይበልጥ ደስተኛ፣ ውብና ጤነኛ እንድትሆን ይበልጥ አካሏ ላይ ትኩረት ማድረግ አለባት፤ የልስላሴና የአደጋ ተጋላጭነትን የመጨረሻ ከፍታ እየነካች ይበልጥ ስስ፣ ይበልጥ ለስላሳ፣ ይበልጥ ቆንጆ መሆን አለባት!!›› ይላል፡፡
ከአዘጋጁ፡- (ጸሃፊው ‹‹የኢትዮጵያ ፍልስፍና›› መፅሐፍ ደራሲ ነው)

 የስነተዋልዶ ጤና መበቶች በሰብዐዊ መብቶች ላይ የተመሰረቱ እና ለጾታ እና ለስነተዋልዶ የሚያገለግሉ መብቶች ናቸው፡፡ እነዚህ መብቶች በአራት የተለያዩ ክፍሎች የተጣመሪ ሲሆን፤ ለስነተዋልዶ ጤና መብቶች ስንጠቀምባቸው አንዳቸው ካንዳቸው ጋር ያላቸው ተዛዶ እጅጉን የጠበቀ ነው፡፡ እነሱ፤
የስነጾታ ጤና፤
የስነጾታ መብት
የስነተዋልዶ ጤና እና
የስነተዋልዶ መብት ናቸው። በስነጾታ፤ እና በስነተዋልዶ ጤና እና መብት ጥናት ውስጥ እነዚህን አራት ሃሳቦች ለያይተን የምንጠቀምባቸው ሲሆን አንዳቸው ከሌላኛው ጋር ያለው ዝምድና ግን እጅጉ ከፍተኛ ነው፡፡
የስነጾታ እና የስነተዋልዶ ጤና በአብዛኛው አንዱ ሌላኛውን እንደሚተኩ አድርገን የምንጠቀምባቸው አገላለጾ ሲሆኑ፤ የስነጾታ እና የስነተዋልዶ መብቶችንም እንዲሁ አንዱ ሌላውን የሚተካ ሃሳብ ተደርጎ መጠቀሙ የተለመደ ነው፡፡ አንዳንድ ጊዜ የስነተጾታ መብት በስነጾታ ጤና ውስጥ ተካቶ፤ አሊያ ግልባጩን ማግኘት የተለመደ ነው፡፡ የተለያዩ የቃላት አጠቃቀሞች በተለያዩ መንግስታዊ ባሆኑ ድርጅቶች መኖቸው ብቻ ሳይሆን፤ በአንድ መንግስታዊ ባሆነ ድርጅት ውስጥም የተለያየ የቃላት አጠቃቀም ይስተዋላል፡፡
በጉዳዩ ላይ ከሚሰሩ አለም አቀፍ የተረዐዶ ድርጅቶች መካከል የአለምአቀፍ የታቀደ ወላጅነት ፌደሬሽን፤ የአለምአቀፍ የስነጾታ ማህበር፤ እንዲሁም የአለም አቀፍ የኤች አይ ቪ አድስ ትብብር ይገኙበታል፡፡
የአለምአቀፌ የጤና ድርጅት የስነጾታ ጤናን እንዲህ ይተረጉመዋል- የስነጾታ ጤና ማለት ከጾታ ጋር በተገናኘ የአካላዊ የስነልቦናዊ እንዲሁም የማህበራዊ ደህንነትን ያመለክታል፡፡ ይህም በመልምነት እና በመከባበር ላይ የተሞላ አመለካከት ለስነጾታ፤ ለጾታዊ ግንኙነቶች እና በማናቸውም ሃይል የተሞላበት ድርጊት ላይ ያልተመረኮዘ የስነጾታ ግንኙነትን መፈለግ ያንንም ለመከነወን መቻልን ያመለክታል፡፡
ከሌሎች ከሶስቱ ጽንሰ ሃሳቦች በተለየ መልኩ የስነጾታ መብት በጾታዊ ግንኙነት መደሰት መቻልን እና ስሜትን በነጻነት መግለጽ መቻል ላይ ያተኩራል፡፡ ይህን መብት ለመታገል የሚደረገው ትግል ከሚደረግባቸው ተጨባጭ መሰረቶች አንዱ የአለምአቀፉ የስነጾታ መብት ማህበር የደነገገው ድንጋጌ ነው፡፡ በ14ኛው በአለምአቀፉ የስነጾታ ኮንግረስ ወቅት ማለትም በሆንግ ኮንግ እንደፈረንጆቹ አቆጣጠር በ1999 አ/ም በተካሄደው፤ ማህበሩ 14 ነጥቦች ያሉት የስነጾታ መብቶችን አውጥቶ አጸድቆ ነበር፡፡ በኋላ ላይ በመጋቢት 2014 ደግሞ ተጨማሪ 14 ነጥቦች አካቶ ስራ ላይ ውሏል። በስተመጨረሻ በጸደረገ ክለሳ አሁን የምንጠቀምባቸው 16 የስነጾታ መብቶች ላይ ስምምነት ላይ ተደርሷል፡፡
የእኩልት እና ከአድሎ ነጻ የመሆን መብት፤
የራስን መብት በራስ የመወሰን መብት
የህይወት፤ የነጻነት እንዲሁም የደህንነት መብት፤
ከሰብዐዊ ካልሆኑ ቅጣቶች ነጻ የመሆን መብት፤
ከማቸውም ጥቃትና አስገዳጅ ሁኔታዎች ነጻ የመሆን መብት፤
 የግለኝነት መብት
ሁኔታዊ የሚፈውደውን የተሻለ የጤና፤ የስነጾታ ጤና አገልግሎትን ጨምሮ የማግኘት፤ ድህንነቱ የተጠበቀ የስነጻታ እርካታን የማግኘት መብት
የሳይንሳዊ ግኝቶችን እና እነሱን ተከትሎ የሚመጡ የጤና አገልግሎት ውጤቶችና ጥቅሞቻቸውን የማግኘት መብት፤
መረጃን የማግኘት መብት
 ለትምህርት እና ለሁሉን አቀፍ የስነጾታ ትምህርት የማግኘት መብት
ትዳርን እና መሰል ግንኙነቶችን የመመስረት፤ ወይም በትክክለኛ መረጃ እና በእኩልነት ላይ በተሰረት መልኩ የማፍረስ መብት
ልጆችን ለማፍራት፤ የሚያፈሩበትን ጊዜ እና ቁጥሩን የመወሰን እና ያንንም ለማድረግ የሚያስችል መረጃን የማግኘት መብት፤
ሃሳብን በነጻነት የማንጸባቅ መብት፤
በማበር የመደራጀት እንዲሁም ሰላማዊ ስብሰባዎችን የማድረግ መብት
በፖለቲካና በማበራዊ እንቅስቃሴዎች ላይ የመሳተፍ መብት
ፍትህን፤ እና ይግባኝን የማግኘት መብት
የሚሉት ናቸው፡፡ እነዚህም ድንጋጌውች ቆይተው የዮጋካርታ ድንጋጌ ተብ ለሚጠራው እና በመጋቢት 2007 ለወጣው ድንጋጌ መሰረት ጥለዋል፡፡

  በሎሬት ፀጋዬ ገ/መድህን የአፄ ቴዎድሮስ ቴያትር ውስጥ ስለ አፄ ቴዎድሮስ መድፍ ስለ ሴቫስቶፖል የተነገረውና የተተወነው ታሪክ በጣም ደማቅ ነው፡፡
አፄ ቴዎድሮስ፤
“ሃያ ሺህ ጎበዝ መልምላችሁ መድፌን ሴቫስቶፖልን መቅደላ አፋፍ ድረስ አምጡልኝ” ብለው ባዘዙት መሰረት፣ መድፉ መጣላቸው፡፡
ያንን ቀጥ ያለ አቀበት፣ እጅግ ክብደት ያለውን መድፍ ይዞ መውጣት በዕውነትም ትልቅ ጉልበት የሚጠይቅ ነበር፡፡ ወደ ላይ ከወጣ በኋላ መልሶ ወደ ታች ይንሸራተታል፡፡ እንደገና ሽቅብ ይስቡታል፡፡ ደህና ወጥቶ ወጥቶ፣ መልሶ ቁልቁል ይወርዳል፡፡ ሽቅብ ይስቡታል፤ ቁልቁል ይሳባል፡፡ ለአገር አንድነት ሲሳብ፣ እስከ መጨረሻው ተደክሞበታል፡፡
በመከራ አፋፍ ድረስ ተጎትቶ መጥቶ፣ በመጨረሻ ደረሰና ተተኮሰ፡፡ ሆኖም የታሰበው ሳይሆን ያልታሰበው ተከሰተ!
እንደ ሎሬቱ አገላለፅ፤
“ሴቫስቶፖል መድፋችን የኋሊት ፈነዳ!”
ከዚህ በኋላ ነው እንግዲህ ቴዎድሮስ
“አየሽ አንቺ እማማ ኢትዮጵያ፣ አየሽ አንቺ እናት ዓለም ቃል የእምነት ዕዳ ነው እንጂ፤ የእናት የአባትኮ አይደለም!” ብለው ቃላቸውን የፈፀሙት!
“… እጅህን ስጥ አለኝ ፈረንጅ፣ እጅ ተይዞ ሊወሰድ … ምን እጅ አለው የእሳት ሰደድ … አያውቅም ክንዴ እንደሚያነድ!”
የሚሉት እንደ እሳት በሚንቀለቀል ወኔ ነው፡፡ ለሀገራቸው ህይወታቸውን የሰጡት ከዚህ ወዲያ ነው፡፡
“መቅደላ አፋፉ ላይ ጩኸት በረከተ
የሴቱን አናውቅም ወንድ አንድ ሰው ሞተ”
የተባለውና የተገጠመው ለዚህ ነበር፡፡
ገጣሚ መንግሥቱ ለማም በ“ባለካባና ባለዳባ” ቴያትራቸው ውስጥ “ቴዎድሮስ በህይወት ቢኖሩ ኖሮ ይሉታል” ብለው የሚያስቡትን እንዲህ ፅፈውታል፡-
“ቀማኛን መቀማት ከሌባ መስረቅ
ለማቅለል ከሆነ የድሆችን ጭንቅ
በእኔ ቤት ፅድቅ ነው አንድ ሰው ይሙት
አንድ መቶ ሺ ሰው ኪኖር በምፅዋት!”
ቀማኛን፣ ሙሰኛን መዋጋታቸው ነው፡፡ ድህነትን መፋለማቸው ነው፡፡ ለደሀ መቆማቸውን ማሳየታቸው ነው!!
*   *   *   *
የህዝብን አደራ መቀበልና ቃልን ማክበር፣ የመልካም መሪ የተቀደሰ ምግባር ነው፡፡ ራስን እስከ መስዋዕትነት ማዘጋጀትም በአርአያነት ተጠቃሽ የሆኑ ታላላቅ መሪዎች መልካም ተምሳሌት ነው፡፡ በተለይ እንደ እኛ አገር ያለች ድህነት ያቆራመዳት፣ አስተዳደር የራባት፣ ወገናዊነት ያጠጣባት፣ ዲሞክራሲ የተራቆተባት፤ ችግር ሲመጣ ብቻ ስብሰባና ግምገማ፣ ግርግርና መዋከብ የሚበዛባት፤ አገር ላይ ሹም መሆን አበሳው ብዙ ነው፡፡ ሥነ ልቦናዊም፣ ፖለቲካዊም፣ ማህበራዊም ዝግጅት በጣም አስፈላጊ ነው፡፡ ለዚህ ደግሞ የልዩ አጋዥ ተቋማት መኖር ግድ ነው፡፡ የሲቪክ ማህበራትን መፍጠርና ያሉትንም ማጠናከር ያሻል። ለሀገር የሚበጅ ሀሳብን በአማራጭ እንዲያቀርቡ መንገዱን መጥረግ የጥበብ መጀመሪያ ነው፡፡ ሀሳብን አለመገደብ ልዩ ልዩ የዕድገት አማራጮችን እናይ ዘንድ ያግዘናል፡፡ ምንም ቢሆን ምንም፣ ለተስፋ መቁረጥ ቦታ አለመስጠት የጥንካሬያችን መፍለቂያ ነው፡፡ እፊታችን የተደቀኑ እልህ አስጨራሽ እንቅፋቶች ሊኖሩ መቻላቸው የማይታበል ሀቅ ነው፡፡ ቀበቶን ጠበቅ አድርጎ በዙሪያችን ያሉ ሰዎችን አጠናክሮ፣ በሆደ - ሰፊነት መስመር የጋራ ቤታችን የሆነችውን ሀገራችንን ከትናንት ወደተሻለ ነገ ለማሸጋገር ጥረት እናድርግ፡፡ ልዩነት የለም ብለን አናስብ፡፡ ይልቁንም እናጠበዋለን ብለን እንመን! ሁሉም መንገድ ወደ ድል ያደርሰናል ብለን አንገበዝ፡፡
“ህዝብ ያላማከረ ንጉሥ፣ አለአንድ ዓመት አይነግሥ” የሚለውን የአበው ብሂል አንዘንጋ!
“እንግዲህ ንጉሡ ምን እራስ አላቸው
ሁሉ በየአቅጣጫው እያደሙባቸው” የሚለውንም አንርሳ፡፡
ገጣሚው፤
“እንግዲህ ወገኔ ዳሩን እወቅና
መካከሉን ዳኘው በጥበብ ያዝና
አይፈለፈልም ደረቁ ባቄላ
እሳት አይገባውም፣ ርሶ ካልተበላ
አለቀ እምንለው ሰው አላቂ አይሆንም
ተሳፋሪው እንጂ አሳፋሪ አይወርድም!” የሚለውንም አንዘንጋ!
ከሁሉም በላይ ግን ረግጠን የመጣነውን መንገድ ሳንረሳ፣ የመሄጃችንን አውራ ጎዳናውንና መጋቢ - መንገዱን እንለይ! እንደ ጥንቱ ሚሲዮናውያን የኋሊት የሚፈነዳ መድፍ ሊሰሩልን የሚመኙትን ታላላቅ መንግሥታት በዐይነ - ቁራኛ እንይ!! ደግ - አሳቢ ነው ያልነው መቼ ክፉ - አሳቢ እንደሚሆን አይታወቅምና በተጠንቀቅ መጠበቅ ብልህነት ነው፡፡ ዮሐንስ ቤል እንዳለው፤ የሀገራችን ደወል “ፍርሃት … ብልሃት … ብልሃት … ፍርሃት …” እንደሚል ማዳመጥ መታደል ነው! “ሽቅብ መሳብ፣ ቁልቁል መሳብ፤ ለአገር አንድነት ሲባል” የሚለው እሳቤ ግን መቼም የማይሞት ነው! እያንዳንዱ ድል የራሱን መስዋዕትነት ይጠይቃልና!!    

ንብ ኢንተርናሽናል ባንክ ለቀጣይ አምስት ዓመታት የሚያገለግለውን ስትራቴጂካዊ ዕቅድ ለማዘጋጀት “ኬፒኤምጂ ኢስት አፍሪካ ሊሚትድ ኩባንያ ጋር ባለፈው ረቡዕ ከሰዓት በኋላ ቦሌ ደንበል ህንፃ ላይ በሚገኘው የባንኩ ዋና መሥሪያ ቤት ተፈራረመ፡፡
የባንኩ የዲሬክተሮች ቦርድ፣ የሥራ አስፈፃሚዎችና የኬፒኤምጂ ተወካዮች በተገኙበት በተፈፀመው የውል ስምምነት ሥነ - ሥርዓት ላይ የባንኩ ፕሬዚንት አቶ ብሩክ ፎንጃ እና የኬፒኤምጂ ኢስት አፍሪካ ሊሚትድ ኩባንያ ዳይሬክተር ሚስተር ዴቪድ ሌሂ ፊርማውን ፈፅመዋል፡፡
ስትራቴጂክ እቅዱን ለማሰራት ባንኩ ጨረታ ካወጣ በኋላ ለመወዳደር ጨረታውን ከወሰዱት 23 ድርጅቶች መካከል ስምንቱ የአገር ውስጥ ኩባንያዎች መሆናቸውን በፊርማ ሥነ ሥርዓቱ የተገለፀ ሲሆን በተደረገው የቴክኒክ ምርመራ ኬፒኤምጂ ኢስት አፍሪካ ሊሚትድ የተሻለ ውጤት በማግኘት፣ ጨረታውን አሸንፎ ለስምምነት መብቃቱም በዕለቱ ተገልጿል፡፡
ስትራቴጂካዊ ዕቅዱ የባንኩን ድርጅታዊ አወቃቀር ከዘመኑ ጋር እንዲዘምን በማድረግ ለሰራተኛውም ሆነ ለተገልጋዩ የተቀላጠፈ አሰራርና አገልግሎት ለመስጠት ያስችላል ተብሎ እንደሚጠበቅ ተገልጿል፡፡
ንብ ኢንተርናሽናል ባንክ፤ በአሁኑ ወቅት 25 ቢሊዮን ብር ጠቅላላ ሀብት ያለው ሲሆን ተቀማጩ 20 ቢ. ብር፣ በብድር የተሰጠ 13 ቢ. ብር፣ እንደደረሰ ጠቁሟል፡፡ 209 ቅርንጫፎችና እንዲሁም ከ4 ሺህ በላይ ሰራተኞች ያሉትና ከቀዳሚ የግል ባንኮች አንዱ እንደሆነም ተገልጿል፡፡

Saturday, 07 April 2018 00:00

የከረመለታ!...

አረዱለት ጥጃ
ጋረዱለት ግምጃ፣
የከረመለታ…
ጎደ’ላሉት ጎታ
ከለከሉት ኩታ!
(መኮንን ተሾመ ቶሌራ - ዘ ገዳም ሰፈር)