Administrator

Administrator

ሁለት አንበሶች እኔ እገዛ፣ እኔ እገዛ ተጣሉ! አሉ፡፡ አንዱ፤ ዕድሜዬ ረዥም ነውና ለመግዛት የኔ ነው የሚፈቅደው ባይ ነው፡፡
ሌላው፤ “ባያት በቅድመ - አያቴ ስለተመረቅሁ - ገዥው እኔ ነኝ” አለ፡፡
“እንግዲያው ይለይልን” ሆነ፤ የመጨረሺያው መፍትሄ፡፡ ይሄ ሁሉ ሲሆን ጥንቸል ባቅራቢያው ሆና ትታዘባለች፡፡
ክፉ ትግል ገጠሙ፡፡ ብዙ ፍልሚያ ካካሄዱ በኋላ ሁለቱም ደክመው መሬት ላይ ተዘረሩ፡፡ Ending infatigue እንደሚባለው ነው፡፡ ጥንቸል ውጤቱን ስትጠባበቅ ቆይታ ሁለቱም አቅም አጥተው መውደቃቸውን አየች፡፡ ይሄኔ በኩራትና በእብሪት፣ በዙሪያቸው ተቀምጣ ሰው፣ ባለፈ ባገደመ ቁጥር፤
“ትልቅና ጉልበተኛ መሆን ሳይሆን ብልሃተኛ መሆን ነው የድል ሚስጥሩ” እያለች ማስረዳቷን ቀጠለች፡፡
ከጥቂት ጊዜ በኋላ ግን አንደኛው አንበሳ ከተኛበት ነቃ፡፡ ይሄኔ ጥንቸል፤
“እርስዎ እንደሚነሱ አውቄ አካባቢውን ስጠብቅ እስካሁን ቆይቻለሁ፡፡ እንግዲህ በሰላም ከነቁ ብሄድ ይሻላል፡፡” አለች፡፡
አንበሳም፤ ቀጨም አድርጎ ያዛትና፤ “ለሰዎች ሁሉ፤ ብልሃት የሌላቸው አንበሶች ይወድቃሉ ስትይ የሰማሁ መሰለኝ፡፡ ለዚያም ዋጋ ትከፍይበታለሽ፡፡ በኛ ደክሞ መውደቅ አንቺ ዝና ልትገዢ መጣርሽ ምን እንደሚያስከፍል ማወቅ አለብሽ!” አላት
ጥንቸልም፤
“በእንቅልፍ ልብዎ መሆን አለበት የሚያወሩኝ” አለች፡፡
አንበሳም፤
“አይ ጥንቸል! በእንቅልፍ ልቤም’ኮ ልቤ የራሴ ነው!” ብሎ አድቅቆ ደቁሶ በላት!
*        *      *
ጊዜ አመቸኝ ብሎ መፎከር ውጤቱ አደገኛ ነው፡፡ ጊዜ ሰጠኝ ብሎ ዝና ለማፍራት መሞከር በመጨረሻ ዋጋ ያስከፍላል፡፡ ዝና መቼ መጠቂያ እንደሚሆን ስለማይታወቅ ብርቱ ጥንቃቄ ይጠይቃል፡፡ አንዲት ያልታወቀች ገጣሚ፤
“ዝናኮ እንደንብ ነው
ዜማ አለው
እሾክ አለው
እግዚኦ ለሰማያቱ ያለህ፣
ለካ ክንፍም አለው!” ብላለች፡፡
የዝና ክንፍ የት እንደሚያደርሰን አይታወቅም፡፡ ለጊዜው የሚያደንቀን ህዝብም መቼ ጀርባውን እንደሚያዞርብን አይታወቅም፡፡ ዝና ጥንቃቄ የሚያስፈልገው ለዚህ ነው! ዛሬ የገነንን ይመስለናል፡፡ ነገ ግን ስንወድቅ ምሳሩን እኛው ላይ እንደሚሰነዝር አንርሳ፡፡ ቂሙን የማይረሳ ህዝብ፣ መቼም ይሁን መቼ፣ ለሰራነው ዋጋ ሳያስከፍለን አይቀርም፡፡ ለጊዜው ቢያቀረቅርም ቀኑ ሲመሽብን፣ ታሪክን ጠቅሶ ቁጭቱን ይወጣል፡፡ ሁሉም የጊዜ ጉዳይ ነው፤ ይለናል፡፡ ስለዚህ ዛሬውኑ መናዘዝ፣ ዛሬውኑ ህዝብን ይቅር በለኝ ማለት የመዳኛችን አንዱ መንገድ ነው! ውጊያውን እንጂ ጦርነቱን እንዳላሸነፍን እንወቅ! (Won the battle but not the war) ጦርነቱ ያለው ህዝብ ልቦና ውስጥ ነውና! “የጀርመን ግንብ ቢፈርስም፤ ህዝቡ ጭንቅላት ውስጥ አልፈረሰም” የሚባለው ለዚህ ነው! አሁንም ደግመን ደጋግመን፣ ለህዝቡ ምን ደግ ነገር ሰርተናል? ብለን እንጠይቅ፡፡ የወደፊት ዕድሜያችን የሚለካው በዚያ ነው፡፡
የነገ ህይወታችንን የሚወስኑት ዛሬ የምናያቸው ምልክቶች ናቸው፡፡ የሰው ምሬት የት ደርሷል? ኢኮኖሚያችን የህዝብን በልቶ ማደር ያገናዘበነውን? ተጠይቀው ያልተመለሱት የፖለቲካ ጥያቄዎች፣ ዛሬም እንደተንጠለጠሉ ናቸው? ወይስ ተመልሰውልናል? ዲሞክራሲው እየተዳከመ ነው እየጠነከረ የመጣው? ፍትሐችን ሚዛኑን በመጠበቅ ረገድ ወገናዊ ነው አይደለም? “እናቱ የሞተችበትም ገበያ የሄደችበትም እኩል ያለቅሳሉ”፤ የሚባልበት አገር አሁንም አለን? ወይስ ሁኔታው ተለውጧል? እስረኞችን መፍታት አንድ ይበል የሚሰኝ እርምጃ ነው፡፡ በቀጣይ የተሻለ ሁኔታ እንጠብቃለን፡፡ ሌሎች የማይታሰሩበትን ሁኔታ መፍጠር ወሳኝ ሂደት ነው፡፡ ያማረ ሁኔታ ይፈጠር ዘንድ ሁላችንም መረባረብ ይኖርብናል፡፡ ያም ሆኖ መጪውን ችግር የሚጠቁሙ ሂደቶችን እናስተውል፡፡ Coming events cast their shadows ይላሉ ፀሐፍት፡፡ መጪው ጊዜ ዛሬ ላይ ጥላውን ይጥላል፤ እንደማለት ነው፡፡ ነገን ዛሬ እንጠንቀቅ፡፡ አለበለዚያ “በመስከረም የሚቆስል በሰኔ ያሳክከዋል” የተባለው ተረት ዕውን ይሆናል፡፡ እናስብ! እናስብ! ደጋግመን እናስብ!

 • የገዢዎች አፈና ሲቆም የህዝቦች ግንኙነት ይጠናከራል
      • አጀንዳችን የኢትዮጵያን አንድነት ማምጣት ነው
      • በአጠቃላይ የዘር ፖለቲካው አላንቀሳቅስ ብሎናል

     ሰሞኑን አረና ትግራይ ለፍትህና ለሉአላዊነት፣ የማዕከላዊ ኮሚቴ ስብሰባውን አድርጎ፣ የሀገሪቱን ወቅታዊ ሁኔታ የገመገመበትን መግለጫ አውጥቷል፡፡ ለመሆኑ መግለጫው ስለ ሀገሪቱ ወቅታዊ ሁኔታ ምን ይላል? በትግራይ ክልላዊ መንግስት የተደረገውን የአመራር ለውጥስ እንዴት ያየዋል? በእነዚህና ሌሎች ወቅታዊ የፖለቲካ ጉዳዮች ዙሪያ የአዲስ አድማስ ጋዜጠኛ አለማየሁ አንበሴ፣ ከፓርቲው ሊቀ መንበር አቶ አብርሃ
ደስታ ጋር ተከታዩን አጭር ቃለ ምልልስ አድርጓል፡፡ እነሆ፡-


    ፓርቲያችሁ የሀገሪቱን ወቅታዊ ሁኔታ እንዴት ነው የገመገመው?
አንደኛ፣ በሀገሪቱ የፖለቲካ ቀውስ የመኖሩን ጉዳይ ነው የገመገምነው፡፡ የፖለቲካ ቀውሱ ደግሞ በኢህአዴግ አፈና ምክንያት የተፈጠረ ነው፡፡ አሁን የህዝብ አልገዛም ባይነት አለ፡፡ በሌላ በኩል ደግሞ የኢህአዴግ ህዝብን መምራትና ማስተዳደር አለመቻል እየታየ ነው፡፡ ይሄ ነገር በአግባቡ ካልተመራ ወደባሰ ፖለቲካዊ ቀውስ ሊመራን ስለሚችል፣ ምን ማድረግ አለብን በሚለው ጉዳይ ላይ ተወያይተናል፡፡ ሀገሪቱን ለማዳን፣ ቀውሱን ለመፍታት ምን መደረግ አለበት በሚለው ላይ ሰፊ ውይይት አድርገናል፡፡
ታዲያ በውይይታችሁ ምን ላይ ደረሳችሁ…?
እንግዲህ ኢህአዴግ ለሀገሪቱ ችግር መፍትሄ ከማምጣት ይልቅ አባባሽ ሁኔታዎችን እየፈጠረ በመሆኑ፣ እኛ ከሌሎች ኢትዮጵያውያን ጋር በመሆን፣ የሀገር አንድነት ማምጣት እንደሚገባንና የእርስ በእርስ ግጭት እንዲቆም ሁሉም ህዝብ እንደ አንድ ህዝብ በጋራ እንዲታገል መጣር  አለብን ብለናል። በሌላ በኩል በኢትዮጵያ አንድነት ከሚያምኑ፣ የኢትዮጵያ መፃኢ እድል ከሚያሳስባቸው የፖለቲካ ድርጅቶች ጋር ትብብር በመፍጠር፣ አንድ ላይ መስራት እንዳለብን ተስማምተናል፡፡ በትግራይ አካባቢ ህዝብን ፖለቲካ ማስተማርና ማደረጃት እንደሚገባን፣ ከምንም በላይ የኢትዮጵያን አንድነት ማስጠበቅ እንዳለብን አቅጣጫ አስቀምጠናል፡፡
ከሰሞኑ ተፈፅመዋል የተባሉ ብሄር ተኮር ጥቃቶችን  እንዴት ተመለከታችሁት? መፍትሄውስ ምንድን ነው?
እርግጥ ነው የትግራይ ተወላጆች ጥቃት ደርሶባቸዋል፤ ግን ይሄ የሆነው በህውሓት ምክንያት ነው፡፡ ስለዚህ መፍትሄው፣ ከህዝቡ ጋር ሆኖ ህውሓትን መታገል ነው ብለን ገምግመናል። ሁሉም የሚስተካከለው የተቀናጀ ትግል ሲደረግ ብቻ ነው።
በቅርቡ በትግራይ ክልል የተደረገው የአመራር ለውጥ ምን ውጤት ያመጣል ትላላችሁ?
የህዝብ ጥያቄ በአመራር ለውጥ ብቻ አይመለስም፡፡ ህውሓት ህውሓት ነው፤ ሰዎቹም የህውሓት አባሎች ናቸው፡፡ ስለዚህ እኛ ከዚህ የአመራር ለውጥ፣ ብዙም ውጤት አንጠብቅም፡፡ ህዝቡ የፈለገውን እንዲመርጥ መፍቀድ አለባቸው  ብለን እናምናለን፡፡ አሁን በኦሮሚያ እየተደረገ  ያለው ጥሩ ነገር ነው፡፡ በህውሓትም እነሱ መርተው ለውጥ ማምጣት እንደማይችሉ አውቀው፣ የለውጥ ኃይል እንዲመጣ መንገዱን መክፈት ነው ያለባቸው። እንደ ቀድሞ ጨቁኖ መግዛት የማይቻልበት ደረጃ ላይ እየተደረሰ በመሆኑ ወይ ተገደው ይለወጣሉ ወይ እነሱ ራሳቸው በለውጡ ይሄዳሉ፡፡
ከሰሞኑ “ትግራይን መገንጠል” የሚል ነገር በአንዳንድ ወገኖች፣ በማህበራዊ ሚዲያ ተነስቷል። ይሄን ጉዳይ ፓርቲያችሁ እንዴት ይመለከተዋል?
አረና በኢትዮጵያ አንድነት የሚያምን ፓርቲ ነው፤ ትግራይ የኢትዮጵያ መሰረት ነው ብለን ነው የምናስበው፡፡ ትግራይ ከሚለው ስም በፊት ኢትዮጵያ ብሎ ነው የትግራይ ህዝብ የሚያምነው፡፡ ይሄ ሃሳብ  በተለያዩ አካባቢዎች ከሚደርሱ ብሔር ተኮር  ጥቃቶች የተነሳ የመጣ ነው፡፡ ተገፋሁ የሚል አካል ይሄን ማንሳቱ የሚገርም ባይሆንም ጊዜያዊ ስሜት መሆኑ ግን አያጠያይቅም፡፡ የትግራይ ህዝብ በኢትዮጵያዊ አንድነቱ ፅኑ መሰረት አለው። ወደ መገንጠል ወይም ሌላ አማራጭ የሚሄድ አይደለም። ይሄ ሃሳብ የመከፋት ስሜት መኖሩን የሚጠቁም እንጂ የትግራይ ህዝብን አቋም የሚገልፅ አይደለም፡፡ የኛም እምነት የኢትዮጵያ አንድነት ነው። አጀንዳችንም የኢትዮጵያን አንድነት ማምጣት ነው፡፡
ከዚህ ቀደም አንድ ጠንካራ ሃገራዊ ፓርቲ የመፍጠር ዓላማ  እንዳላችሁ ጠቁማችሁ ነበር፡፡ ይህ ሃሳብ ከምን ላይ ደረሰ?
እርግጥ ነው እቅድ አውጥተን ነበር፡፡ ነገር ግን አልተሳካም፡፡ ከፓርቲዎች ጋር ለመቀራረብ ያደረግነው ጥረት ውጤት አላመጣም፡፡ አጋጣሚ ሆኖ ፖለቲካው ወደ ብሄር ፖለቲካ ገባ፡፡ ሁሉም በብሄር ማሰብ ጀመረ፡፡ በዚህ የተነሳ ዕቅዱን መተግበር አስቸጋሪ ሆነብን፡፡ ኢትዮጵያዊነት የሚለው ነገር ብዙ ትኩረት ባለማግኘቱ፣ ውጤታማ መሆን አልቻልንም፡፡ ነገር ግን አሁንም እንቅስቃሴው አልቆመም፤ ሆኖም  ይሄን እኛ ብቻ ልናደርገው አንችልም፡፡ ሌሎች ፓርቲዎችም ይሄን ሃሳብ ይዘው መንቀሳቀስ እስኪጀምሩ ድረስ ክልላዊ ፓርቲ ሆነን እንቀጥላለን፡፡
አሁን አረና እያደረገ ያለው ፖለቲካዊ  እንቅስቃሴ ምን ይመስላል?
አሁን ጠንካራ እንቅስቃሴ እያደረግን አይደለም። ያላደረግንባቸው ምክንያቶች ደግሞ በርካታ ናቸው። አንዱ የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ ነበር፡፡ በሌላ በኩል፣ ህውሓት በኛ ላይ የሚነዛው ፕሮፓጋንዳ አላንቀሳቅስ ብሎናል፡፡ በኢትዮጵያዊነት ጉዳይ ላይ ስንንቀሳቀስ፣ ህውሓት፣ “እነዚህ ስለ ትግራይ ህዝብ ጥቃት አያስቡም” ይለናል፡፡ ለትግራይ ህዝብ መቆርቆር ስናሳይ ደግሞ በአንዳንድ ወገኖች “ፀረ ኢትዮጵያ” እንባላለን፡፡ ይሄ ለፖለቲካዊ እንቅስቃሴያችን ከፍተኛ  እንቅፋት ሆኖብናል፡፡ በአጠቃላይ የዘር ፖለቲካው አላንቀሳቅስ ብሎናል፡፡
በሌላ በኩል ግን የትግራይ ህዝብ፣ የፖለቲካ ለውጥ በመፈለግ ሰፊ እንቅስቃሴ እያደረገ ነው፡፡ አሁን ደጋፊና ለውጥ ፈላጊ ህዝብ ስላለ፣ አረና በጥሩ ሁኔታ ላይ ይገኛል ማለት ይቻላል፡፡ አሁን የብሄር ፖለቲካው የበላይነት ስለያዘ፣ ለጊዜው ህዝብን ስለ ኢትዮጵያ አንድነት እየሰበክን ነው መንቀሳቀስ የምንፈልገው፡፡ አጀንዳው ከባድ ቢሆንብንም በኢትዮጵያ አንድነት ተስፋ አለን፡፡ በህዝቦች መካከል እየተፈጠረ ያለው ችግርም የገዥዎች የአፈና ውጤት ነው ብለን እናምናለን፡፡ ይሄ አፈና ሲቆም የህዝቦች ግንኙነት ይጠናከራል የሚል እምነት አለን፡፡

  ከእንግሊዝ አምባሳደር ጋር በእስረኞችና በሀገሪቱ የፖለቲካ ጉዳይ ላይ ተወያይተዋል

    በቅርቡ ከእስር የተለቀቁት ዶ/ር መረራ ጉዲና፣ ወደ መደበኛ የፓርቲ ሥራቸው ለመመለስ መወሰናቸውን የገለጹ ሲሆን በኢትዮጵያ የእንግሊዝ አምባሳደር ከሆኑት ሱዛን ሞርሄድ ጋር መወያየታቸውም ታውቋል፡፡
በኢትዮጵያ የእንግሊዝ ኤምባሲ ባወጣው መረጃ፤ አምባሳደሯ በወቅቱ የሀገሪቱ ጉዳይ ላይ ከዶ/ር መረራ ጉዲና ጋር መወያየታቸውን ጠቁሟል። ውይይቱን በተመለከተ ለአዲስ አድማስ ያብራሩት ዶ/ር መረራ፤ ስለ ማረሚያ ቤቶች የእስረኞች አያያዝ፣ ስለ ወቅቱ የሀገሪቱ ሁኔታና ወደፊት ሊሆን ስለሚገባው ጉዳይ ከአምባሳደሯ ጋር በስፋት መነጋገራቸውን ገልጸዋል፡፡ በተለይ ህብረተሰቡ በመንግስት ላይ ያለውን ተቃውሞ የሰው ህይወት መቅጠፍን የሚያስከትል ግጭት ሳይፈጠር፣ በሰላማዊ መንገድ በሚያሰማበት ሁኔታ ላይ በትኩረት ተወያይተናል ብለዋል - ዶ/ር መረራ።
በተመሳሳይ ከሁለት ሳምንት በፊት በኢትዮጵያ የጀርመን አምባሳደር ከሆኑት አምባሳደር ቫግ ነር ጋር መወያየታቸውን  መዘገባችን  ይታወሳል፡፡
ከእስር በተለቀቁ ወቅት በፖለቲካ ትግላቸው ይቀጥሉ እንደሆነ አለመወሰናቸውን የተናገሩት ዶ/ር መረራ፤ በአሁኑ ወቅት በኦሮሞ ፌደራሊስት ኮንግረስ (ኦፌኮ) የሊቀ መንበርነት ሥራቸው ለመቀጠል መወሰናቸውን ለአዲስ አድማስ አስታውቀዋል፡፡
በሌላ በኩል፣ ዶ/ር መረራ ጉዲና፣ ከአደአ በርጋ ህዝብ በቀረበላቸው ጥሪ መሰረት፣ ከትናንት በስቲያ ሐሙስ ወደ አካባቢው በተጓዙበት ወቅት በመቶ ሺዎች የሚቆጠሩ የአካባቢው ነዋሪዎች ከፍተኛ የአድናቆት አቀባበል እንዳደረጉላቸው የኦፌኮ ም/ሊቀመንበር አቶ ሙላቱ ገመቹ ለአዲስ አድማስ ጠቁመዋል፡፡   
በተመሳሳይ ዶ/ር መረራ፣ ከሁለት ሳምንት በፊት በአምቦ ከተማ፣ተቀራራቢ ቁጥር ያለው ህዝብ ደማቅ   አቀባበል እንዳደረገላቸው ይታወቃል፡፡

  53 ኢትዮጵያውያን ከሞዛምቢክ እስር ቤት ወጥተዋል

    የኬንያ መንግስት በህገ ወጥ መንገድ ወደ ግዛቴ ገብተዋል ያላቸውን 29 ኢትዮጵያውያን፣ ከትናንት በስቲያ ሐሙስ ጠዋት ያሰረ ሲሆን በሌላ በኩል፣ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር፣ በሞዛምቢክ በህገ ወጥ መንገድ ድንበር አቋርጠዋል ተብለው የታሰሩ 53 ኢትዮጵያውያንን ማስፈታቱን  አስታውቋል፡፡
ፓስፖርትና አስፈላጊ የጉዞ ሰነዶች ሳይኖራቸው፣ ከሞያሌ በጭነት መኪና በመጓጓዝ ላይ ሳሉ ሩዋራካ በተሰኘች የኬንያ ግዛት ውስጥ በቁጥጥር ስር የዋሉት 29 ኢትዮጵያውያን፣ አላማቸው ወደ ደቡብ አፍሪካ መሻገር እንደነበር  የኬንያው ዘ ስታንዳርድ ጋዜጣ  ዘግቧል፡፡ ኢትዮጵያውያኑ በፖሊስ ቁጥጥር ስር በዋሉበት ወቅት የተሻለ ስራ ፍለጋ ከሀገራቸው መሰደዳቸውን መናገራቸውን የጠቆመው ዘገባው፤ በእስረኞች ማቆያ እንዲገቡ ተደርጎም፣ ተጨማሪ ምርመራ እየተደረገባቸው መሆኑን አመልክቷል፡፡
ከኢትዮጵያውያኑ በተጨማሪ የመኪናው አሽከርካሪ በቁጥጥር ስር ዋለ ሲሆን የኬላ ጠባቂ ፖሊስ ላይም ምርመራ እየተካሄደ ነው ተብሏል፡፡ ኢትዮጵያውያኑ ፍ/ቤት ከቀረቡ፣ በህገ ወጥ መንገድ የሀገሪቱን ግዛት በማቋረጥ ወንጀል ተከሰው፣ እስከ 1 ዓመት የሚደርስ እስራት ሊፈረድባቸው እንደሚችል ታውቋል፡፡  
በሌላ በኩል፣ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር፣ በተመሳሳይ የሞዛምቢክን ድንበር በህገ ወጥ መንገድ አቋርጠው ደቡብ አፍሪካ ሊገቡ ሲሉ በሞዛምቢክ ፖሊስ ተይዘው ታስረው የነበሩ 53 ኢትዮጵያውያንን፣ ከፍተኛ ድርድር በማድረግ ማስመለሱን አስታውቋል፡፡ ከወራት በፊትም በተመሳሳይ፣ በዛምቢያ እስር ቤት የነበሩ 150 ኢትዮጵያውያንን በማስፈታት፣ ወደ ሀገር ቤት እንዲመለሱ ማድረጉን ሚኒስቴሩ መግለፁ ይታወሳል፡፡    

  እኔ ቀድሜ የተረጎምኩትን “The power of Now” የተሰኘ መጽሐፍ ተርጉመው፣ የ100 ሺህ ብር ኪሣራ አድርሠውብኛል ያሉት ተርጓሚ በፍ/ቤት የ194 ሺ ብር ካሣ እንዲከፈላቸው ተወሠነ፡፡
ከሳሽ ደራሲና ተርጓሚ አፈወርቅ በቀለ ለፌደራል ከፍተኛ ፍ/ቤት ፍትሃ ብሄር ችሎት ሚያዚያ 13 ቀን 2007 ዓ.ም ባቀረቡት የክስ አቤቱታ፤ በኤክርሃቶ ቶል፣ “The power of Now” በሚል የተፃፈውን መፅሐፍ “የአሁንነት ሃይል” በሚል ወደ አማርኛ ተርጉመው ለአንባቢያን ማቅረባቸውን ይሁን አንጂ እሳቸው በማያውቁትና ፍቃዳቸው ሳይጠየቅ አቶ ብስራት እውነቱ የተባሉ ደራሲ “የአሁኑ ሃይልነት” በሚል ርዕስ ወደ አማርኛ ቋንቋ በመመለስ ኪሣራና ጉዳት እንዳደረሰባቸው ጠቁመዋል፡፡
በዚህ የክስ አቤቱታ፤ አቶ መኮንን ፋንታሁን መፅሃፉን እንዲተረጉም በማድረግና በአሣታሚነት እንዲሁም ፋር ኢስት ትሬዲን ኃላ/የተ/የግ/ማህበር ደግሞ በአታሚነትና በመሸጥ፣ ከፍተኛ ጥቅም ማግኘታቸውና ጉዳት አድራሽ መሆናቸው ተመልክቷል፡፡
ተከሳሾች በቀረበባቸው ክስ፣ የራሳቸውን መልስ ለፍ/ቤት ያቀረቡ ሲሆን አንደኛ ተከሣሽ የሆኑት አቶ ብስራት እውነቱ፤ የመፅሃፍ ባለመብትና ደራሲ ሄክሃርት ቶል እንጂ ከሣሽ አይደሉም ስለዚህ የፈጠራ ባለመብት አይደሉም፤ የሚል መልስ የሠጡ ሲሆን ሁለተኛ ተከሳሽ በበኩላቸው፤ ከሣሽ ራሳቸው የዋና ደራሲውን ፈቃድ ሣያገኙ ነው የተረጎሙት፤ በዚህም የመፅሃፍ ባለመብት ሆነው ክስ ማቅረብ አይችሉም የሚል ምላሽ ሰጥተዋል፡፡ 3ኛ ተከሳሽ (ማተሚያ ቤቱ በበኩሉ፤ እኔ ስራዬን የመፅሐፉን ይዘት ማንበብ ሣይሆን ማተም ብቻ ነው የሚል ምላሽ ሠጥተዋል፡፡
ከሣሽ በበኩላቸው፤ በፍሬ ጉዳይ ላይ ባቀረቡት መከራከሪያ፤ የትርጉም ስራ እራሱን የቻለ ፈጠራ በመሆኑ በቅጅና ተዛማጅ አዋጅ ቁጥር 410/96 መሠረት ጥበቃ አለው፤ ሲሉ አንቀፅ ጠቅሠው ተከራክረዋል፡፡
የግራ ቀኙን ክርክር የመረመረው ፍ/ቤቱ፤ ከሣሽ “መፅሃፉን እኔ ስለተረጎምኩት ሌላ ሠው ሊተረጉመው አይችልም” ብለው አንቀፅ በመጥቀስ ያቀረቡትን መከራከሪያ ተቀባይነት እንደሌለው፤ ነገር ግን ተከሣሾችም ከሳሽ መፅሀፉን በመጀመሪያ መተርጎማቸውን ማመናቸውንና ይዘቱም ተመሣሣይነት እንዳለው ከግምት በማስገባት፣ በጉዳዩ ላይ ውሣኔ ሠጥቷል፡፡
ፍ/ቤቱ ባሣለፈው ውሣኔ፣ 1ኛ እና 2ኛ ተከሣሽ ጥፋተኛ በመሆናቸው፣ በከሳሽ ደራሲና ተርጓሚ አፈወርቅ በቀለ ላይ ላደረሡት ቁሣዊ ጉዳት 94 ሺህ አንድ መቶ አርባ ብር (94,140) እንዲሁም በከሳሽ ላይ ለደረሰው የሞራል ጉዳት ብር አንድ መቶ ሺህ (1000,000) በድምሩ አንድ መቶ ዘጠና አራት ሺህ አንድ መቶ አርባ ብር (194,140) ብር እንዲከፍሉ ወስኗል፡፡ 3ኛ ተከሳሽ (ማተሚያ ቤቱ) በከሳሽ ላይ ላደረሠው ቁሣዊም ሆኖ ሞራላዊ ጉዳት ሃላፊነት የለባቸውም ብሏል - ፍ/ቤቱ፡፡

   *ዋና ዳይሬክተሯን ተክተው ይሰራሉ ተብሏል

    የተባበሩት መንግስታት ድርጅት ዋና ጸሃፊ፣ በአለማቀፍ ተቋማት የረጀም አመታት የከፍተኛ አመራርነት ልምድ ያላቸውን ኢትዮጵያዊውን አቶ ደረጀ ወርዶፋን የተመድ የስነ-ህዝብ ፈንድ የፕሮግራም ምክትል ዋና ዳይሬክተር አድርገው መሾማቸውን ከትናንት በስቲያ አስታውቀዋል፡፡ ኢትዮጵያዊው፤በቅርቡ የስነ-ህዝብ ፈንድ ዋና ዳይሬክተር ሆነው የተሾሙትን የፓናማ ተወላጇን ናታንያ ካኔም ተክተው እንደሚሰሩም ነው የተገለጸው፡፡
በተለያዩ አለማቀፍና አህጉራዊ ተቋማት ውስጥ በከፍተኛ የስራ ሃላፊነቶች ላይ ከ28 አመታት በላይ የዘለቀ ስኬታማ አመራር በመስጠት የካበተ ልምድ ያላቸው ኢትዮጵያዊው አቶ ደረጀ፣ በተቋሙ ዋና ዳይሬክተር ሆነው በማገልገል ላይ ያሉትን ናታሊያ ካኔምን እንደሚተኩ ተመድ ባወጣው መግለጫ አመልክቷል፡፡ በአሁኑ ሰዓት በአለማቀፉ ኤስኦኤስ የህጻናት መንደር፣ የምስራቃዊና ደቡባዊ አፍሪካ አለማቀፍ ክልላዊ ዳይሬክተር የሆኑትና 4 ሺህ 500 ያህል ሰራተኞችን በስራቸው በማስተዳደር ላይ የሚገኙት አቶ ደረጀ፣ ብቃት ባለው አመራር በአስቸጋሪ ሁኔታዎች ውስጥ ፈተናዎችን በመቋቋም፣ በአብዛኛው አፍሪካን ተደራሽ ያደረጉ በርካታ ስራዎችን በስኬታማነት እንዳከናወኑ መግለጫው አስረድቷል፡፡
አቶ ደረጀ ከዚህ ቀደምም አሜሪካን ፍሬንድስ ሰርቪስ ኮሚቴ በተባለው ተቋም በክልላዊ ዳይሬክተርነት፣ በኡጋንዳ የኦክስፋም ሃላፊ፣ በሴቭ ዘ ችልድረን በምክትል የፕሮግራም ዳይሬክተርነትና በሌሎች ታላላቅ ተቋማት በከፍተኛ የስራ ሃላፊነቶች ላይ በማገልገል ብቃታቸውን ማስመስከራቸውን አስታውሷል፡፡
ኢትዮጵያዊው አቶ ደረጀ ከኦክስፎርድ ብሩከስ ዩኒቨርሲቲ በቢዝነስ አድሚኒስትሬሽን በማስተርስ፣ በለንደን ስኩል ኦፍ ኢኮኖሚክስ በሶሻል ፖሊሲ ኢን ዲቨሎፒንግ ካንትሪስ በማስተርስ መመረቃቸውንና፣ የመጀመሪያ ዲግሪያቸውንም በቢዝነስ ማኔጅመንት ከአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ማግኘታቸውን መግለጫው አክሎ ገልጧል፡፡  

  “አንቺም አባዎራ እኔም አባዎራ
                   ግራ ገባው ቤቱ በማ እንደሚመራ…”

   በኬንያ ከወራት በፊት በተካሄደው የድጋሚ ምርጫ ያሸነፉት ኡሁሩ ኬንያታ፤ በይፋ ቃለ መሃላ ፈጽመው አገሪቱን በፕሬዚዳንትነት መምራት ከጀመሩ ከወራት በኋላ፣ እነሆ ያልተጠበቀ ነገር ባለፈው ማክሰኞ በመዲናዋ ናይሮቢ ተከናወነ፡፡
ምርጫው ተጭበርብሯል ብለው ካስደገሙ በኋላ፣ ራሳቸውን ከውድድሩ ያገለሉት የተቃዋሚው ፓርቲ መሪ ራይላ ኦዲንጋ፤ ባለፈው ማክሰኞ ናይሮቢ በሚገኝ ፓርክ ውስጥ በሺህዎች የሚቆጠሩ ደጋፊዎቻቸውን ሰብስበው፣ “የታላቋ ኬንያ ሪፐብሊክ  ፕሬዚዳንት ነኝ” ሲሉ በማወጅ ቃለ መሃላ ፈጸሙ፡፡
የያዘውን ስልጣን በድንገት መነጠቁ ያስደነገጠውና ጉዳዩ ወደ ከፋ ግጭት እንዳያመራ ያሰጋው የኡሁሩ ኬንያታ መንግስት፤ የጎንዮሹ ቃለ መሃላ አገርን የሚያፈርስ፣ክፉ ድርጊት በመሆኑ እንዳይካሄድ ብሎ ቢያስጠነቅቅም፣ ራይላ ኦዲንጋ ግን ጆሮ ዳባ ልበስ ብለው፣ መጽሃፍ ቅዱሳቸውን ከፍ አድርገው ይዘው፣ መሪነታቸውን አወጁ። ሁለተኛ ፓርላማ ማቋቋማቸውንም በድፍረት ተናገሩ፡፡
ህጋዊው የኡሁሩ መንግስት. የኦዲንጋን የጎንዮሽ በዓለ ሲመት በቀጥታ ስርጭት ለህዝቡ ለማድረስ እየተዘጋጁ የነበሩትን ኬቲኤን፣ ኤንቲቪ እና ሲቲዝን ቲቪ የተባሉ ሶስት ታላላቅ የአገሪቱ የቴሌቪዥን ጣቢያዎችን ስርጭት አቋርጧል፡፡
የኡሁሩ መንግስት የቴሌቪዥን ጣቢያዎቹን መዝጋቱን ተከትሎ፣ ባለፈው ሃሙስ የአገሪቱ ከፍተኛ ፍርድ ቤት ችሎት ላይ ተሰይሞ ጉዳዩን ካጤነው በኋላ፣ ለ14 ቀናት ያህል በጉዳዩ ዙሪያ ቀጣይ ምርምራ አድርጎ እስከሚጨርስና የመጨረሻ ብይን እስኪሰጥ ድረስ፣ የመንግስት ውሳኔ ተሽሮ፣ የቴሌቪዥን ጣቢያዎቹ ስርጭታቸውን እንዲቀጥሉ ወስኗል፡፡
የኡሁሩ መንግስት ግን የፍርድ ቤቱን ውሳኔ አክብሮ፣ ጣቢያዎቹን ለመክፈት ፍላጎት አለማሳየቱን የዘገበው ቢቢሲ፤ የአዲሱ ፕሬዚዳንት ራይላ ኦዲንጋ ደጋፊዎችና ተቃዋሚ ፓርቲዎች እንዲሁም የአገሪቱ በርካታ ጋዜጠኞች፣ ሃሳብን በነጻነት የመግለጽ ህገ መንግስታዊ መብትን የሚጥስ ነው፣ በማለት የመንግስትን እርምጃ ማውገዛቸውን አመልክቷል፡፡
የኡሁሩ ኬንያታ መንግስት ለጉዳዩ ተገቢውን ትኩረት ሰጥቶ ሁነኛ ምላሽ እስካልሰጠ ድረስ፣ ኬንያ በቀጣዮቹ ቀናት ወደ ከፋ ብጥብጥና ቀውስ ልታመራ እንደምትችል የሚናገሩት የመብት ተሟጋቾች፤ ሁለቱም ሃይሎች አገሪቱን ወደ ጥፋት ከማምራት እንዲቆጠቡ ጥሪ ማቅረባቸውን ቢቢሲ ዘግቧል፡፡

ስራ ፈትተው ከሚቀለቡ 6 ሺህ ወታደሮች፣ የተወሰኑት በግድ እረፍት ይወጣሉ

   ፕሬዚዳንቱ ወጪን ለመቀነስ ሲሉ ለሰሞኑ የህብረቱ ስብሰባ፣ የግል አውሮፕላናቸውን ትተው፣ በመደበኛ አውሮፕላን ነበር የመጡት
ከፍተኛ የፋይናንስ እጥረት የገጠመው የናሚቢያ መንግስት፤ወጪን ለመቆጠብ በሚል ሚኒስትሮችን፣ ምክትል ሚኒስትሮችንና ከፍተኛ የመንግስት ተቋማት ሃላፊዎችን ጨምሮ ሁሉም የአገሪቱ ባለስልጣናት ወደ ውጭ አገራት እንዳይሄዱ መከልከሉን አልጀዚራ ዘግቧል፡፡
ማንኛውም የአገሪቱ ባለስልጣን ለስብሰባ፣ ለስልጠናና ለሌሎች ጉዳዮች ከአገሪቱ ውጭ የሚያስወጣው ጉዞ ካለ በአፋጣኝ እንዲሰርዝ መንግስት መመሪያ ማስተላለፉን የጠቆመው ዘገባው፤ የጉዞ ክልከላው ቢያንስ እስከ ወሩ መጨረሻ ተግባራዊ ሆኖ እንደሚቆይና ይራዘማል ተብሎ እንደሚጠበቅ አመልክቷል፡፡ በውጭ አገራት ጉዞ ሳቢያ ለባለስልጣናት ከፍተኛ ወጪ ማውጣት እንዲቆም ያሳሰቡት የአገሪቱ ፕሬዚዳንት ሀጌ ጌንቦ፤ በሰሞኑ የአፍሪካ ህብረት የመሪዎች ጉባኤ ላይ ለመሳተፍ ወደ አዲስ አበባ በመጡበት ወቅትም የግል አውሮፕላናቸውን ትተው፣ የህዝብ ማመላለሻ መደበኛ አውሮፕላን መጠቀማቸውን ዘገባው አስታውሷል፡፡
የናሚቢያ ኢኮኖሚ በአብዛኛው በማዕድን ኤክስፖርት ገቢ ላይ የተመሰረተ እንደሆነ የጠቆመው ዘገባው፤ የአለም አቀፍ ገበያ መቀዛቀዝ ኢኮኖሚዋን ክፉኛ እንደጎዳውና የፋይናንስ እጥረት የገጠመው የአገሪቱ መንግስት መሰል ወጪዎችን ለመቀነስ እርምጃ መውሰድ መጀመሩን አስረድቷል።
ስራ ፈትተው በጦር ካፕሞች ለሚኖሩ የጦር ሃይሉ አባላት ደመወዝ በአግባቡ መክፈልም ሆነ የእለት ምግብና ውሃን ጨምሮ የተለያየ ወጫቸውን መሸፈን ያቃተው የአገሪቱ መንግስት፣ ከሰሞኑ በሺህዎች የሚቆጠሩ ወታደሮቹን የአመት እረፍት ለማስወጣትና በእረፍት ላይ ለሚገኙትም ተመልሰው እንዳይመጡ መመሪያ ለመስጠት መወሰኑን ዘ ናሚቢያን የተባለው የአገሪቱ የግል ጋዜጣ ዘግቧል፡፡
የአገሪቱ መከላከያ ሚ/ር ለ2018 የበጀት አመት 5.6 ቢሊዮን የአገሪቱ ዶላር እንደተመደበለት ያስታወሰው ዘገባው፣ አገሪቱ 15 ሺህ ያህል ወታደሮች እንዳሏትና 6 ሺህ ያህሉ ስራ ፈትተው በጦር ካምፖች ውስጥ እንደሚኖሩ መነገሩንም አክሎ ገልጧል፡፡

  በየቀኑ 50 ሚሊዮን ሰዓታት ፌስቡክ ላይ ይጠፋሉ

    ታዋቂው የማህበራዊ ድረ-ገጽ ፌስቡክ፣ ባለፈው የፈረንጆች አመት 2017፣ የመጨረሻው ሩብ አመት፣ ሶስት ወራት ጊዜ ውስጥ የ4.3 ቢሊዮን ዶላር ትርፍ ማግኘቱንና ይህም ካለፈው የሩብ አመት ትርፍ፣ በ61 በመቶ ብልጫ እንዳለው ኩባንያው ባለፈው ረቡዕ ባወጣው መግለጫ አስታውቋል፡፡
የኩባንያውን መስራችና ዋና ስራ አስፈጻሚ ማርክ ዙክበርግን ጠቅሶ ዘ ኢንዲፔንደንት እንደዘገበው፤ ፌስቡክ በተጠቀሰው የሶስት ወራት ጊዜ ውስጥ በድምሩ 12.7 ቢሊዮን ዶላር ያገኘ ሲሆን፣ የወርሃዊ ተጠቃሚዎቹ ቁጥርም 2.13 ቢሊዮን ያህል ደርሷል። ፌስቡክን በሞባይል የሚጠቀሙ ደንበኞች ቁጥር ማደጉ በሩብ ዓመቱ ከፍተኛ ትርፍ እንዲያገኝ አስችሎታል ያለው ዘገባው፤ በየዕለቱ ፌስቡክን የሚጠቀሙ ደንበኞች ቁጥርም 1.4 ቢሊዮን መድረሱን አስረድቷል፡፡
ፌስቡክ የተጠቃሚዎቹን ጊዜ በከፍተኛ ደረጃ እየተሻማና ስራ እያስፈታ ነው በሚል የሚሰነዘርበትን ትችት በማጤን፣ በሩብ አመቱ ተጠቃሚዎች በየቀኑ ፌስቡክ ላይ የሚያጠፉትን ጊዜ በተወሰነ መልኩ ለመቀነስ የሚያስችል እርምጃ መውሰዱን የጠቆመው ዘገባው፤ በአንድ ቀን ውስጥ ተጠቃሚዎች በፌስቡክ ላይ የሚያጠፉትን አጠቃላይ ድምር ጊዜ ወደ 50 ሚሊዮን ሰዓታት ዝቅ ማድረጉን አስታውሷል፡፡
በአዲሱ የፈረንጆች አመት የዓለማችን የዲጂታል ማስታወቂያ ገበያ ውስጥ 266 ቢሊዮን ዶላር ያህል ገንዘብ ይንቀሳቀሳል ተብሎ እንደሚጠበቅ የጠቆመው ዘገባው፤ በዚህ ገበያ ውስጥ ፌስቡክ 18.4 በመቶ ያህል ድርሻ ይኖረዋል ተብሎ እንደሚገመት አመልክቷል፡፡

የሳኡዲ አረቢያ መንግስት የፓስፖርት ጉዳዮች ዳይሬክቶሬት፣ በ140 የተለያዩ ክፍት የስራ ቦታዎች ላይ ሴቶችን ቀጥሮ ለማሰራት ባወጣው ማስታወቂያ፤ ከ107,000 በላይ አመልካቾች መቅረባቸውን ኤንቢሲ ኒውስ ዘግቧል፡፡
በአውሮፕላን ማረፊያዎችና በድንበር አካባቢ መስሪያ ቤቶች መስራት ለሚፈልጉ ስራ ፈላጊዎች የወጣው የክፍት የስራ ቦታ ማስታወቂያ፤ በድረ ገጽ አማካይነት በተሰራጨ በአንድ ሳምንት ጊዜ ውስጥ ብቻ ከ107,000 በላይ አመልካቾች መቅረባቸው ያስደነገጠውና መስተንግዶው ከአቅሙ በላይ የሆነበት ዳይሬክቶሬቱ፤ በአፋጣኝ ማስታወቂያውን ማንሳቱን ዘገባው አመልክቷል፡፡
ክፍት የስራ ቦታ ማስታወቂያው ቢያንስ ሁለተኛ ደረጃን ያጠናቀቁና ከ25 እስከ 35 አመት በሚገኘው የእድሜ ክልል ውስጥ ያሉ አመልካቾችን ብቻ መጋበዙን የጠቆመው ዘገባው፤ በሳኡዲ አረቢያ የሴቶች ስራ አጥነት 33 በመቶ ላይ እንደሚገኝም አስታውሷል፡፡