Administrator

Administrator

አንድ በወታደሮች ካምፕ የመዝናኛ ክበብ ዙሪያ የተፃፈ ሐተታ የሚከተለውን ቀልድ ነጥቧል፡፡
ከዕለታት አንድ ቀን በአንድ የመኮንኖች ክበብ ውስጥ ከተራ ወታደር እስከ ጄኔራሎች ድረስ እየተዝናኑ ሳሉ፣ የዕንቆቅልሽ መሰል ጥያቄና መልስ ተጀመረ፡፡
የጨዋታ መሪው፤
“ለመሆኑ ወሲብ (የአልጋ ላይ ግንኙነት) ስንት ፐርሰንቱ ፍቅር ነው? ስንት ፐርሰንቱስ ሥራ ነው?” ሲል ጠየቀ፡፡
መኮንኖቹ እንደየ ማዕረግ ደረጃቸው ይመልሱ ጀመር፡-
ጄኔራሉ:- “ዘጠና ከመቶው ፍቅር፣ አሥር ከመቶው ሥራ ነው” አሉ፡፡
ኮሎኔሉ፡- “በእኔ ግምት ሰማኒያ ከመቶው ፍቅር ነው፡፡ ሃያ ከመቶው ሥራ ነው፡፡” አሉ፡፡
ሻለቃው ቀጠሉ፡- “ለእኔ እንደሚሰማኝ ደግሞ ወሲብ ሰላሳ በመቶው ሥራ፤ ሰባ በመቶው ፍቅር ነው”
ሻምበሉ ደግሞ፤
“እኔ በበኩሌ አርባ በመቶው ሥራ ነው እላለሁ፡፡ ስልሳ በመቶው ግን ፍቅር ነው፡፡”
መቶ አለቃው ጥቂት ስሌት ሠርተው፤
“እኔ ደግሞ ወሲብ ሃምሳ በመቶው ፍቅር፣ ሃምሳ በመቶው ሥራ ነው እላለሁ”
አለ፡፡
ሃምሳ አለቃው ተነሳና፣
“የእኔ ከሁላችሁም ይለያል፡፡ ወሲብ አርባ በመቶው ፍቅር፤ ስልሳ በመቶው ሥራ ነው” አለ፡፡
አሥር አለቃው፤
“ሰላሳ በመቶው ፍቅር ነው፡፡ ሰባ በመቶ ደግሞ ሥራ ነው” አለ፡፡
ይሄኔ ተራ ወታደሩ እጁን አወጣ፡፡
ዕድል ተሰጠው፡፡
“እኔ ከሁላችሁም አልስማማም፤ ለእኔ ወሲብ መቶ በመቶ ፍቅር ነው” አለ፡፡
ጄኔራሉም፣ ኮሎኔሉም፣ ሻለቃውም አጉረመረሙ፡፡
“እኮ ምክንያትህን አስረዳና?” አሉት፡፡
ተራ ወታደሩም፤
“ጌቶቼ፤ ወሲብ ሥራ ቢኖርበት ኖሮ ለእኛ ትተውልን ነበር!”
* * *
አስተሳሰባችን የልምዳችን፣ የትምህርታችን የተፈጥሮአችን ተገዢ ነው፡፡ ልምዳችን የቅርብ የሩቁን የማስተዋልና በትውስታችን ቋት ውስጥ የማኖር ውጤት መዳፍ ሥር ያለ ነው፡፡ ትምህርታችን ትምህርት የሚሆነው ወደ ዕውቀት መለወጥ ሲጀመር ነው! ዕውቀታችን ወደ የብልህ-ጥበብ (wisdom) የሚለወጠው አንድም በዕድሜ፣ አንድም የሚዛናዊ አመለካከት ባለቤት ስንሆን ነው! ሚዛናዊነት የጎረኝነት (Positionality) ተቃራኒ ነው፡፡ የወገናዊነት ፀር ነው! ወገናዊነት የኢ-ፍትሐዊነት መቆፍቆፊያ ሰንኮፍ ነው፡፡ ኢ-ፍትሐዊነት ከማናቸውም ህገ-ወጥ ድርጊት ጋር፤ አንዱን-ሲነኩት-ሌላው ይወድቃል ዓይነት ግንኙነት አለው፡፡ (Domino-effect እንደሚባለው፡፡) ለችግሮች የምንሰጠው አጣዳፊ መፍትሔዎች ወዴት ያደርሱናል? ብሎ መጠየቅ ትልቅ መላ ነው፡፡ “የፊተኛውን ባልሽን በምን ቀበርሽው- በሻሽ፤ ለምን- የኋላኛው እንዳይሸሽ” የሚለውን ማውጠንጠን አለብን፡፡ በየለውጡ ውስጥ የአንድ የአገራችንን ገጣሚ ስንኞች ሥራዬ ብሎ ማዳመጥ ጠቃሚ ነው፡-
“ዘመንና ዘመን እየተባረረ
ከምሮ እየናደ፣ ንዶ እየከመረ
ይሄው ጅምሩ አልቆ፣ ማለቂያው ጀመረ
ጀመረ”
መውጫ መውረጂያችን በሥጋት የታጠረ ከሆነ፤ ከመረጋጋት ጋር እንራራቃለን፡፡ ያለ ሥጋት የምንጓዘው ለህሊናችን ታማኝ የሆንን እንደሆነ ነው! በስሜታዊነት ምንም ዓይነት ድርጊት መፈፀም የለብንም፡፡ ፅንፈኛ ሆነንም ማሰብ የለብንም፡፡ ከሁሉም በላይ ግን አሉታዊነትን
(Negativism) በፍፁምነት ማስወገድ አለብን፡፡ ለረዥም ጊዜ ሰቅዞ የያዘንን ሁሉ፣ በተቃውሞ በጋራ ከመጠርነፍ ዕምነት የግድ መላቀቅ ይኖርብናል፡፡ ነጋዴውን ሌባ ነው ብሎ አስቦ መጀመር፣ ባለሙያውን ከእኛ ጋር ካልሆነ ባለሙያ አይደለም ብሎ ማሰብ፣ ሰውን አላግባብ መፈረጅ፤ የእኔ ቦይ ውስጥ ካልፈሰስ የተሳሳተ ሰው ነው ብሎ መገምገም… እኒህና እኒህን መሰል አካሄዶች ሁሉ ከፀፀት አያፋቱንም!
ዛሬም ነገረ-ሥራችንን እንመርምር፡፡ ማህበረሰብ ለአመክንዮ እንጂ ለመላምት/ለግምት መጋለጡ ደግ አይደለም፡፡ ግለሰባዊ፣ ተቋማዊ አሊያም ፓርቲያዊ ግልፅነት (Transparency) ወደድንም ጠላንም አስፈላጊ ነው! አለበለዚያ ዳፍንተኝነት (Obscurantism) ይወርረናል፡፡ ህብረተሰብ የሀገሪቱ አካሄድ ውሉ እንዳይጠፋበት ማድረግ ያለበት አመራሩ ነው፡፡ አመራር ተመሪውን አይከተልም፡፡ ያ ከሆነ ጭራዊ እንቅስቃሴ ወይም የድሃራይ እንቅስቃሴ ውስጥ ይገባል- Tailist movement እንዲል መጽሐፍ፡፡ ደራሲ በተደራሲ ከተመራ፣ ገጣሚው በአጨብጫቢ-ታዳሚ ከተመራ፣ ዋናው ባለሙያ በበታቹ ተፅዕኖ ውስጥ ከወደቀ፣ መሪው በተመሪው እጅ ከተያዘ የመንተብ- decadence አንድ ድረጃ ነው! ከዚህ ተከትሎ ምርጫ ማጣት ይመጣል፡፡ የሚፈልገው ነገር ሁሉ ጭጋግ ውስጥ ይወድቅና አጥርቶ ማየት ይሳነናል፡፡ የቱን ልያዝ ዓይነት ድንግዝግዝ ውስጥ እንጨፈቃለን፡፡
ያኔ ነው እንግዲህ “ከሞትና ከህይወት የቱ ይሻልሃል?” ቢባል ሲያስብ ዘገየ፤ የሚለው ተረት ጎልቶ የሚነበበው! ከዚህ ይሰውረን!!

 

በፖለቲካ ጉዳዮች ላይ በተለያዩ የመገናኛ ብዙኃንና በማህበራዊ ሚዲያዎች ላይ አስተያየት በመስጠትና የሰሉ ሂሳዊ ጽሁፎችን በማቅረብ የሚታወቁት የአምቦ ዩኒቨርሲቲ ወሊሶ ካምፓስ መምህር የሆኑት አቶ ስዩም ተሾመ ሰሞኑን መታሰራቸው ታውቋል፡፡
የዩኒቨርሲቲ መምህሩና ጦማሪው አቶ ስዩም ተሾመ የመታሰራቸው ጉዳይ ከትናንት በስቲያ በማህበራዊ ሚዲያዎች የተነገረ ሲሆን ስለ ሁኔታው ለማወቅ ወደ ቅርብ ወዳጃቸው በመደወል መታሰራቸውን ለማረጋገጥ ተችሏል፡፡
የፖለቲካ ተንታኙ አቶ ስዩም ተሾመ፤ ሐሙስ ጠዋት 4 ሰዓት ገደማ ወሊሶ ከሚገኘው መኖሪያ ቤታቸው በፀጥታ ኃይሎች መወሰዳቸው የታወቀ ሲሆን ምንጮች በኮማንድ ፖስቱ ሳይታሰሩ እንዳልቀረ ቢገምቱም ለማረጋገጥ ግን አልተቻለም፡፡
በመንግስት ላይ ጠንካራ ትችቶችን በድፍረት በመሰንዘር የሚታወቁት የዩኒቨርሲቲ መምህሩ አቶ ስዩም ተሾመ፤በተለይ ካለፉት ሦስት ዓመታት ወዲህ ከአገሪቱ የፖለቲካ ቀውስ ጋር በተያያዘ ትንተናዎችና የመፍትሄ ሃሳቦች በመስጠት ትኩረት ስበው ቆይተዋል፡፡

ኢትዮጵያ እ.ኤ.አ እስከ 2025 ለማሳካት ለያዘችው ሁሉንም ዜጋ የኤሌክትሪክ ኃይል ተጠቃሚ የማድረግ እቅድ የሚውል የ375 ሚሊዮን ዶላር ብድር ከዓለም ባንክ ማግኘቷ ታውቋል፡፡
ከዓለም ባንክ ሰሞኑን የተገኘው የገንዘብ ብድር በተለይ በቀጣዮቹ 5 ዓመታት ውስጥ ለአንድ ሚሊዮን የገጠር ነዋሪዎች የኤሌክትሪክ ኃይል ለማቅረብ ለተያዘው እቅድ አጋዥ ይሆናል ተብሏል። በአጠቃላይ የ5 ዓመቱ ፕሮጀክት 1.5 ቢሊዮን ዶላር ወጪ እንደሚጠይቅም ታውቋል፡፡
ኢትዮጵያ ከፍተኛ የታዳሽ ኃይል የማምረት አቅም እንዳላት በመግለጫው የተጠቆመ ሲሆን ፕሮጀክቱም በቁርጠኝነት ከተሰራ ስኬታማ ይሆናል ተብሏል፡፡
ሀገሪቱ ካላት ሃይድሮ ኤሌክትሪክ አቅም ባሻገር ከፀሐይ፣ ከንፋስና ከጂኦተርሚናል ኃይል የማመንጨት ከፍተኛ አቅም እንዳላት የዓለም ባንክ ሪፖርት ጠቁሟል፡፡
የኢትዮጵያ መንግስት ባለፉት 10 ዓመታት ውጤታማ የኤሌክትሪክ ማዳረስ ፕሮግራም ዘርግቶ በሀገሪቱ የሚገኙ ከተሞችንና መንደሮችን ተጠቃሚ እያደረገ መሆኑም ተመልክቷል- በመግለጫው፡፡

ከግንባር ቀደም ዓለም አቀፍ ገንዘብ አስተላላፊ ድርጅቶች አንዱ የሆነው ዎርልድ ሬሚት፣ ኒውዮርክ የሚገኙ 9 ሺህ ኢትዮጵያውያን ዲያስፖራዎች በፈጣንና ዝቅተኛ ዋጋ ገንዘብ ወደ ኢትዮጵያ እንዲልኩ ማድረጉን አስታወቀ፡፡
ድርጅቱ ለዝግጅት ክፍላችን በላከው መግለጫ፣ ጊዜ ውድ በሆነበት የአሜሪካ (የውጭ አገር) ኑሮ፣ ደንበኞች ወደ አንድ ተቋም (ባንክ ወይም ገንዘብ አስተላላፊ ድርጅቶች) በአካል መሄድ ሳይኖርባቸው በማንኛውም ቦታና ሰዓት፣ የድርጅቱን ድረ - ገፅ ወይም ሞባይል ስልካቸውን በመጠቀም ወደ ኢትዮጵያ ገንዘብ መላክ ይችላሉ ብሏል፡፡
ዎርልድ ሬሚት በኒውዮርክ ግዛት የሚኖሩትን ጨምሮ ከ50 በላይ በሚሆኑ አገራት የሚኖሩና የሚሰሩ ኢትዮጵያውያን ዜቶች የሚልኩትን ገንዘብ፣ እዚህ ያሉ ገንዘቡ የተላከላቸው ሰዎች በመላ አገሪቷ ከሚገኙ የአንበሳ ኢንተርናሽናል ባንክ ቅርንጫፎች እንዲወስዱ ከባንኩ ጋር መዋዋሉን ገልጿል፡፡
የገንዘብ አስተላላፊው ድርጅት የምስራቅ አፍሪካ ኃላፊ ሻሮን ኪንያንጁይ፣ በዎርልድ ሬሚት በኩል ወደ ኢትዮጵያ የሚደረጉ የገንዘብ ዝውውሮች ከፍተኛ ዕድገት እያሳዩ መሆኑን መመልከታቸውን ጠቅሰው፣ የኢትዮጵያ ዲያስፖራዎችም ሆኑ ተቀባዮቹ ከዎርልድ ሬሚት ጥራት ያለው አገልግሎት እያገኙ መሆኑን ማረጋገጣችንን እንቀጥላለን፡፡ ኒውዩርክን ያካተተ አገልግሎት መጀመርና የአንበሳ ኢንተርናሽናል ባንክ ወደ መረባችን መግባት ወደ ኢትዮጵያ ሃዋላ ለሚልኩ ሰዎች መልካም ዜና ነው ብለዋል፡፡
በወጣት ሶማሊያዊ ኢንተርፕረነር እስማኤል አህመድ እ.ኤ.አ በ2010 የተመሰረተው ዎርልድ ሬሚት ወደ ኢትዮጵያ ገንዘብ መላክ የጀመረው በተመሰረተ በዓመቱ በ2011 እንደሆነ የጠቀሰው መግለጫው፣ ኒውዮርክ በመጨመሩ አሜሪካ የዎርልድ ሬሚት ትልቁ የገንዘብ መላኪያ ገበያ እንደምትሆንና ኩባንያው በ2017 ከአሜሪካ የሚላከው ገንዘብ 200 ፐርሰንት ዕድገት ማሳቱን አመልክቷል፡፡ ዎርልድ ሬሚት ከFacebook, spotify, Netfliy እና Slack እንዲሁም ቀዳሚ ኢንቨስተሮች ከሆኑት Accel እና TCV 200 ሚሊዮን ዶላር ማግነቱን ገልጿል፡፡ ዋና መ/ቤቱ በለንደን ሲሆን የአሜሪካ ዋና መ/ቤት በዴንቨር፣ ክልላዊ ቢሮዎች ደግሞ በካናዳ፣ በደቡብ አፍሪካ፣ በፊሊፕንስ፣ በጃፓን፣ በአውስትራሊያና ኒውዝላንድ እንዳሉት መግለጫው አመልክቷል፡፡

“የእስረኞች መለቀቅ በበጎ የሚታይ ነው፤ አስቸኳይ ጊዜ አዋጁ ግን አሳሳቢ ነው” - የተመድ ሰብአዊ መብት ኮሚሽን

በሁከትና ብጥብጥ የተሳተፉ ግለሰቦችን በቁጥጥር ስር እያዋለ መሆኑን የገለጸው ኮማንድ ፖስቱ፤ በሀገሪቱ አሁን የሚደረገው ተቃውሞ የቀለም አብዮት መልክ እየያዘ መምጣቱንና የመንግስት ስልጣን በሃይል ለመያዝ የመፈለግ አዝማሚያ እንዳለው አስታውቋል፡፡
ከሰኞ የካቲት 26 እስከ ረቡዕ የካቲት 28 በኦሮሚያ በተለይ ከአዲስ አበባ አምቦ ነቀምት ባለው አቅጣጫ እንዲሁም ከአዲስ አበባ ወሊሶ ጅማ መስመር፣ የንግድና የትራንስፖርት እንቅስቃሴዎች ተዘግተው መሰንበታቸውን የኮማንድ ፖስቱ ሴክሬተሪያትና የመከላከያ ሚኒስትሩ አቶ ሲራጅ ፈርጌሳ ጠቁመው፤ በአድማ የሰነበቱ ከተሞች ከረቡዕ አንስቶ በአብዛኛው ወደ መደበኛ እንቅስቃሴያቸው መመለሳቸውን ገልጸዋል፡፡
የንግድና የትራንስፖርት አድማ በተደረጉባቸው የኦሮሚያ ከተሞች በተሽከርካሪዎች ላይ ጉዳት መድረሱንና ፋብሪካ መቃጠሉን የጠቆመው ኮማንድ ፖስቱ፤ በ17 የፀጥታ ኃይሎችም ላይ ጉዳት ደርሶባቸዋል ብሏል፡፡ በሌላ በኩል፣ የአሜሪካ ድምፅ ሬዲዮ፣ የሆስፒታልና የዓይን እማኞችን ጠቅሶ ባቀረበው ዘገባ፤ ከአድማና ተቃውሞው ጋር ተያይዞ በተለያዩ ከተሞች 6 ሰዎች መገደላቸውን ጠቁሟል፡፡ ኮማንድ ፖስቱ በዚህ ጉዳይ ላይ ምንም ያለው ነገር የለም፡፡
በሰሞኑ የሀገሪቱ የፀጥታ ጉዳይ ላይ ለመገናኛ ብዙኃን መግለጫ የሰጡት የኮማንድ ፖስቱ ሴክሬቴሪያት አቶ ሲራጅ ፈርጌሳ፤ በህዝብ የተመረጠን መንግስት በኃይል ለመጣል የሚደረግ እንቅስቃሴ መኖሩን ገልጸው፣ እንቅስቃሴውም የቀለም አብዮት መልክ እየያዘ መሆኑን አስታውቀዋል፡፡
በዚህ እንቅስቃሴ አራት ተሽከርካሪዎች መቃጠላቸውን፣ 10 ያህል ተሽከርካሪዎች መጎዳታቸውን የተናገሩት አቶ ሲራጅ፤ የቀበሌና ወረዳ ጽ/ቤቶች እንደተቃጠሉም ገልፀዋል፡፡ የንብረት ዘረፋና ከጸጥታ ሃይሎች ላይ መሳሪያ የመቀማት ሙከራ መደረጉ የተጠቆመ ሲሆን በጸጥታ ሃይሎች ላይ ጉዳት እንደደረሰባቸውም ተነግሯል፡፡ ህብረተሰቡ መንግስት ተዳክሟል በሚል የሚናፈሰውን አሉባልታ ማመን እንደሌለበት የገለጹት አቶ ሲራጅ ፈርጌሳ፤ መንግስት እንዳሁኑም ተጠናክሮ አያውቅም ሲሉ አስገንዝበዋል፡፡
የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ፣ መንግስት የፖለቲካ ምህዳሩን ለማስፋት ያግዛል በሚል የጀመረውን የፖለቲካ እስረኞችን የመፍታት እርምጃ እንደማይገታ ያስታወቁት አቶ ሲራጅ፤ በሌላ በኩል ኮማንድ ፖስቱ ከህብረተሰቡ የሚደርሱትን ጥቆማዎች መሰረት በማድረግ እንዲሁም በሁከትና ብጥብጥ ተሳትፈዋል ብሎ የጠረጠራቸውን ግለሰቦች በቁጥጥር ስር ማዋሉን ገልጸዋል፡፡ ሆኖም በቁጥጥር ሥር የዋሉት ከየት አካባቢና ምን ያህል እንደሆኑ አልጠቀሱም፡፡
በንግድና ትራንስፖርት የማቆም አድማ ላይ የሰነበቱት አብዛኞቹ የኦሮሚያ ከተሞች ከትላንት በስቲያ ሐሙስ ጀምሮ ወደ መደበኛ እንቅስቃሴያቸው መመለሳቸውን ለማወቅ የተቻለ ሲሆን በቡራዩና አዳማ አካባቢ ደግሞ በአድማው የተሳተፉ ነጋዴዎች “ህግ አላከበራችሁም” በሚል ንግድ ቤቶቻቸው እንደታሸጉባቸው ታውቋል፡፡ በተመሳሳይ በወልቂጤ ከተማ ሲካሄድ የነበረው አድማ ቆሞ ከሐሙስ ጀምሮ መደበኛ እንቅስቃሴ መቀጠሉን ምንጮች ጠቁመዋል፡፡
ይህ በዚህ እንዳለ በአዲስ አበባ የሚገኘው የአሜሪካ ኤምባሲ ባለፈው ሰኞ የካቲት 26 ቀን 2010 ዓ.ም ባወጣው የጉዞ ማስጠንቀቂያው፤ ዜጎቹ ከአዲስ አበባ ውጪ እንዳይጓዙ ያሳሰበ ሲሆን ከአዲስ አበባ ወጣ ብለው በሚገኙ ከተሞች የትራንስፖርትና የንግድ እንቅስቃሴዎች መቆማቸውንም አስታውቆ ነበር፡፡
በሌላ በኩል የተባበሩት መንግስታት የሰብአዊ መብት ኮሚሽን ኮሚሽነር ዞይር ራድ አል ሁሴን ባለፈው ረቡዕ በተካሄደው 37ኛው የኮሚሽኑ መደበኛ ስብሰባ፤ የዓለም ሀገራት የሰብአዊ መብት አያያዝ ሁኔታን በቃኙበት ሪፖርታቸው፤ ኢትዮጵያ በቅርቡ ከ7 ሺህ በላይ እስረኞችን መልቀቋ በበጎ የሚታይ ተቀባይነት ያለው እርምጃ መሆኑን ጠቁመው፤ የታወጀው የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ግን አሳሳቢ ነው ብለዋል፡፡
ፖለቲካዊ ማሻሻያዎችና ለውጥ ውጤታማ ሊሆን የሚችለው በእውነተኛና ሁሉን ያሳተፈ ውይይትና የፖለቲካ ሂደት ነው ብሏል - የኮሚሽኑ ሪፖርት፡፡
መንግሥትም በቅርቡ በተፈፀሚ የዜጎች ግድያ ላይ ተሳታፊ የሆኑ አካላትን አጣርቶ ለህግ እንዲያቀርብ ኮሚሽነሩ ጠይቀዋል በሪፖርታቸው፡፡

አሜሪካ- በአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ፣ ሩሲያ- በኒውክሌር ማብልያ፣ አረብ ኤምሬትስ- በወደብ አጠቃቀም አተኩረዋል ባሳለፍነው ሳምንት አዲስ አበባ የሦስት አገራት የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሮችን ተቀብላ አስተናግዳለች። የተባበሩት አረብ ኤምሬት፣ የአሜሪካና የሩሲያ የውጭ ጉዳይ ሚኒስተሮች፡፡ ሳምንቱ በኢትዮጵያ የዲፕሎማሲ ታሪክ ውስጥ ትልቅ ስፍራ ያለው ነው ብለዋል- የውጭ ጉዳይ ሚ/ሩ ዶ/ር ወርቅነህ ገበየሁ። ሚኒስትሮቹ በኢትዮጵያ ጉብኝታቸው በንግድ፣ በኢንቬስትመንት፣ በፀጥታና ደህንነት ጉዳዩ ላይ ከኢትዮጵያ አቻቸው ጋር የተነጋገሩ ሲሆን በኢትዮጵያ ስላለው ወቅታዊ ፖለቲካዊ ሁኔታ ላይ መወያየታቸውም ታውቋል፡፡ የተባበሩት አረብ ኢምሬት የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ሼክ አብዱላህ ቢን ዛይድ አል ናህያን፤ በንግድና ኢንቨስትመንት፣ በወደብ አጠቃቀምና እንዲሁም በሰራተኞች አያያዝና ልውውጥ ላይ ሲነጋገሩ፣ የአሜሪካው የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ሬክስ ቲለርሰን በዋናነት በፀጥታና ደህንነት፣ በወቅታዊ የኢትዮጵያ ፖለቲካ ጉዳይ እንዲሁም የሩሲያ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ሰርጌ ላቭሮቭ በኒውክሌር ግንባታ፣ በኢንቨስትመንት መወያየታቸው ተጠቁሟል፡፡ ረቡዕ አመሻሽ ላይ አዲስ አበባ የገቡት የአሜሪካው የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ሬክስ ቲለርሠን የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ እንደሚያሳስባቸውና መንግስት የቆይታ ጊዜውን ያሣጥረዋል የሚል ተስፋ እንዳላቸው ተናግረዋል፡፡ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ዶ/ር ወርቅነህ ገበየሁ በበኩላቸው፤ ከቲለርሠን ጋር በቀጠናዊ ፀጥታና ሠላም፣ በኢኮኖሚና ኢንቨስትመንት ትብብር እንዲሁም በኢትዮጵያ እየተካሄደ ባለው ፖለቲካዊ ማሻሻያዎች ላይ መነጋገራቸውን ገልፀዋል፡፡ የሠው ህይወት እየቀጠፈ ባለው የፀጥታ ችግር ተነጋግረናል ያሉት ቴለርሠን፤ የዜጎች መብትን ከመገደብ ይልቅ የበለጠ የሚረጋገጥበት ሁኔታ መፈጠር አለበት ብለዋል፡፡ በኢትዮጵያ እየተደረገ ያለው የጠቅላይ ሚኒስትር የስልጣን ሽግግርን እንደግፈዋለን ያሉት የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ፤ ሠላማዊ የስልጣን ሽግግር በለጋነት ለሚገኘው የሃገሪቱ ዲሞክራሲ ጠቃሚ ነው ብለዋል፡፡ በሃገሪቱ ለሁለተኛ ጊዜ የተጣለው የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ መንግስታቸው በእጅጉ እንደሚያሣስበው የጠቀሡት ቲለርሠን፤ አሣሣቢ የሚያደርገውም በመሠረታዊ የሠብአዊ መብቶች ላይ ገደብ ስለሚያበጅ መሆኑን ጠቁመዋል፡፡ ከውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ወርቅነህ ገበየሁ ጋር ባደረጉት ውይይት ላይም የሠብአዊ መብቶች መከበር እንዳለባቸው፣ የህግና ስርአት መከበር አስፈላጊ ቢሆንም የፀጥታ ሃይሎች የሃይል እርምጃዎችን ከመውሠድ እንዲቆጠቡ ተነጋግረናል ብለዋል-ቲለርሰን፡፡ በሃገሪቱ ሠላምና መረጋጋት ለማምጣት ፖለቲካዊ ማሻሻያዎች አስፈላጊ መሆናቸውን እንዲሁም፣ ገደቦችን ከማበጀት ይልቅ ከሁሉም ባለድርሻዎች ጋር የሚደረግ ፖለቲካዊ ውይይት ጠቃሚ መሆኑን መነጋገራቸውንም አስታውቀዋል። ዜጎችም ለዲሞክራሲ መረጋገጥ የሚደረገው ጥረት ሂደትን የሚጠይቅ መሆኑን በመገንዘብ፣ አመፅ ብቻውን መፍትሄ እንደማይሆን በመረዳት፣ በሃገሪቱ የተሻለውን ለማምጣት በሚደረገው ጥረት ውስጥ የድርሻቸውን እንዲወጡ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ ጥሪ አቅርበዋል፡፡ “ሃገሪቱ ያለችበትን አስቸጋሪ ሁኔታ እንረዳለን” ያሉት ቲለርሠን “ዜጎች ሠላማዊ በሆነ መንገድ ጥያቄያቸውን ማቅረብ አለባቸው፤ መንግስትም መብትን ከመገደብ ይልቅ የበለጠ ማስፋት ነው ያለበት” ብለዋል፡፡ የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ ቆይታም እንደሚያጥር ተስፋ አደርጋለሁ ያሉት ቲለርሠን፤ “በቆይታው ወቅትም በዜጎች ላይ የሠብአዊ መብት ጥሠት ሊያስከትል ይችላል” የሚለውን ስጋት በሚያስወግድ ሁኔታ ሊተገበር እንደሚገባው ገልፀዋል፡፡ አሜሪካ በኢትዮጵያ የሚደረገውን ዲሞክራሲን የማሣደግ ሒደትም እንደምትደግፍ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ አስታውቀዋል፡፡ በዚህ ወቅት በኢትዮጵያ ጉብኝት ለማድረግ ለምን መረጡ? የሚል ጥያቄ ከጋዜጠኛ የቀረበላቸው ቲለርሠን፤ የኢትዮጵያና የአሜሪካ ግንኙነት 100 ዓመታትን የዘለቀ መሆኑን፣ በአሁኑ ወቅትም በተለይ በአካባቢ የፀጥታ ጉዳይ ኢትዮጵያ አጋር መሆኗን በመጥቀስ፣ በኢትዮጵያ ያለውን ለጋ ዲሞክራሲ ማገዝ በሚቻልበት ሁኔታ ላይ ለመነጋገር ነው ብለዋል፡፡ በቆይታቸውም በዲሞክራሲ ጉዳይ፣ በፀጥታና ደህንነት፣ በኢኮኖሚያዊና ኢንቨስትመንት ግንኙነት ዙሪያ በሠፊው መነጋገራቸውንም አስታውቀዋል፡፡ ኢትዮጵያ በደቡብ ሱዳን፣ በሶማሊያ ወታደሮቿን በሠላም አስከባሪነት በመላክ ለቀጠናው ሠላምና ደህንነት የምታበረክተውን አስተዋፅኦ እንዲሁም ስደተኞችን ተቀብላ ማስተናገዷ ከፍተኛ ዋጋ የሚሠጠው መሆኑን ቲለርሠን በመግለጫቸው አውስተዋል፡፡ በሣምንቱ መጀመሪያ ላይ ወደ ኢትዮጵያ የመጡት የዩናይትድ አረብ ኢምሬት የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር፤ በዋናነት በሁለቱ ሃገራት መካከል ለወደፊቱ በሚኖረው የንግድና ኢንቨስትመንት ግንኙነት እንዲሁም ኢትዮጵያውያን የቤት ሠራተኞች ወደ ሃገሪቱ አቅንተው ደህንነታቸው ተጠብቆ በሚሠሩበት ሁኔታ ላይ መነጋገራቸውና መስማማታቸውን የውጭ ጉዳይ ቃል አቀባይ አቶ መለስ አለም አስታውቀዋል፡፡ በተመሣሣይ ከወራት በፊት የጉብኝት ፕሮግራም የተያዘላቸው የሩሲያው የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ሠርጌ ላቭሮቭም በሳምንቱ መጨረሻ ላይ ጉብኝት አድርገዋል፡፡ በጉብኝታቸው ወቅትም ሩሲያ ለሰላማዊ አገልግሎት የሚውል የኒውክሌር ማብላያ ጣቢያ በኢትዮጵያ ለመገንባት የተስማሙ ሲሆን ሩሲያ ለኢትዮጵያ የ163 ሚሊዮን ዶላር እዳ ስረዛ ማድረጓም ታውቋል፡፡ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ ዶ/ር ወርቅነህ ገበየሁ፤ የተባበሩት አረብ ኤምሬት፣ የአሜሪካ እና የሩሲያ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሮችን ጉብኝት አስመልክቶ በሰጡት መግለጫ ሳምንቱ በኢትዮጵያ የዲፕሎማሲ ታሪክ ውስጥ ትልቅ ስፍራ ያለው ነው ብለዋል፡፡ የሩሲያና የአሜሪካ አምባሳደሮች በአንድ ሆቴል ማደራቸውን ጠቁመው፤ በተመሳሳይ ጊዜ ወደ ኢትዮጵያ የመምጣታቸውም ጉዳይ “የተለየ ምስጢር የለውም፤ የአጋጣሚ ጉዳይ ነው” ብለዋል። ከተባበሩት አረብ ኤምሬት የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ጋር በተደረገ ውይይት፤ የሶማሊያን ሉአላዊነት በማይነካ መልኩ ኢትዮጵያ በበርበራ ወደብ ላይ የ17 በመቶ ድርሻ ኖሯት፣ ከተባበሩት አረብ ኤምሬት ጋር ለመጠቀም ስምምነት ላይ መደረሱን ዶ/ር ወርቅነህ አስታውቀዋል፡፡ “የአሜሪካው የውጭ ጉዳይ ሚኒስትርም በዋናነት ስለ ሀገራችን ወቅታዊ ሁኔታ ሊጠይቁ አይደለም የመጡት፤ መደበኛ ዲፕሎማሲውን የማጠናከር ስራ ሊሰሩ ነው ጉብኝት ያደረጉት” ያሉት ዶ/ር ወርቅነህ፤ ከሩሲያ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ጋር በተደረገው ውይይትም የሀገራቱን ግንኙነት ይበልጥ በማጠናከር ጉዳይ እንዲሁም ኒውክሌርን ለሰላማዊ ጉዳይ በማዋል ጉዳይ ላይ መወያየታቸውን አስረድተዋል፡፡

 • “ኮማንድ ፖስቱ የተለጠጠ ሥልጣን ተሰጥቶታል”
    
   ለ6 ወር የሚተገበረው የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ በህዝብ ተወካዮች ም/ቤት በ2/3ኛ ድምፅ የፀደቀ ሲሆን የአዋጁን ድንጋጌዎች ተላልፎ የተገኘ እስከ 5 ዓመት በሚደርስ እስራት ይቀጣል ተብሏል፡፡
የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ በ346 ድጋፍ፣በ88 ተቃውሞና በ7 ድምጸ ተአቅቦ ጸድቋል ተብሎ ነበር፡፡ ሆኖም በኋላ ላይ በተሰጠው መግለጫ፤አዋጁ በ395 የድጋፍ ድምጽ ጸድቋል በሚል ተስተካክሏል፡፡
የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁን የተቃወሙት በአብዛኛው የኦሮሚያ ክልል ተመራጭ የፓርላማ አባላት መሆናቸውም ታውቋል፡፡
ጠቅላይ አቃቤ ህግ አቶ ጌታቸው አምባዬ፤ የአዋጁን አስፈላጊነት ባብራሩበት ንግግራቸው፤ በዋናነት አዋጁ ትኩረት ያደረገው የፀጥታ ችግሮችን ከመሰረቱ ማድረቅ ላይ ነው ብለዋል፡፡ ግጭቶች ከጊዜ ወደ ጊዜ እየተባባሱ አድማሳቸው እየሰፋ መጥቷል ያሉት አቶ ጌታቸው፤ የዜጎች የመንቀሳቀስ መብት፣ በፈለጉበት ቦታ ተዘዋውሮ የመኖርና ሃብት አፍርቶ የመጠቀም መብትን የሚገድቡ እንቅስቃሴዎች ተበራክተዋል፣ አሳሳቢ ደረጃም ደርሰዋል ብለዋል፡፡
አሁን እየተከሰቱ ያሉ ሁከቶች ኃይል የተቀላቀለበት የሰው ህይወት የሚቀጠፍበት፤ ብሄርን መነሻ በማድረግ ዜጎችንም የሚያፈናቅል ሆኗል ተብሏል። በሌላ በኩል በከተሞች ህገ ወጥ የመሬት ወረራዎች መበራከታቸውንም አቶ ጌታቸው ጠቁመዋል፡፡
አዋጁም እነዚህን ችግሮች ከምንጩ ለማድረቅ ታቅዶ የተዘጋጀ ነው ብለዋል፡፡ ለዚህም ሲባል ከዚህ ቀደም ከነበረው የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ በተለየ ሁኔታ በዋናነት የሚተኮረው የሁከት ጠንሳሾችና አቃጆች ላይ ይሆናል ተብሏል፡፡
ሌላው አዋጁ በዋናነት ትኩረት የሚያደርገው የተፈናቀሉ ወገኖችን ወደ ነበሩበት ለመመለስ የሚደረግን ጥረት ማገዝ ላይ ይሆናል ያሉት አቶ ጌታቸው፤ ህዝባዊ አገልግሎት በሚሰጥባቸው የስፖርት ማዘውተሪያ ስታዲየሞችና የሃይማኖት ተቋማት የመሳሰሉት አካባቢ የሚፈጠሩ ሁከቶችን መቆጣጠር ላይ ትኩረት ይደረጋል ብለዋል፡፡
ህገ ወጥ የመሬት ወረራንና ግንባታን እንዲሁም የኢንቨስተሮችን መሬት በህገ ወጥ መንገድ መውሰድን መከላከል ላይ አዋጁ ያተኩራል ተብሏል፡፡
በአዋጁ ማብራሪያ ላይ አስተያየትና ጥያቄ ያቀረቡ በርካታ የምክር ቤት አባላት፤ በተለይ በአዋጁ አፈፃፀም ላይ በየደረጃው ያሉ የክልል የአስተዳደር አካላት ድርሻ ሊኖራቸው ይገባል ያሉ ሲሆን በተለያዩ አንቀፆች ላይም ማሻሻያዎችን ጠይቀዋል፡፡
የምስራቅ ወለጋ ዞን የፓርላማ ተመራጭ ባቀረቡት አስተያየት፤ በነቀምት ከተማ ተከስቶ ከነበረው ግጭትና ተቃውሞ ጋር ተያይዞ የዞኑ ም/አስተዳዳሪና የነቀምት ከተማ ከንቲባ መታሰራቸውን በመጥቀስ፤ በዚህ አዋጅ አስተዳደሮች ሰለባ ከመሆን ይልቅ አብረው መስራት ቢችሉ የተሻለ ነው ብለዋል፡፡
አንድ አባልም አዋጁ ለ6 ወር ከሚፀና ወደ 3 እና 4 ወር ዝቅ ቢል የሚል አስተያየት ሰንዝረዋል፡፡
የሰብአዊ መብት ጥሰቶችን ከመስጋት አንፃር አዋጁ በህዝቡ ተቀባይነት ላያገኝ ይችላል የሚል ስጋት እንዳላቸው የገለፁ አንድ የምክር ቤት አባል “ማንኛውም የመገናኛ ዘዴ ሊቋረጥ ይችላል” የሚለው ድንጋጌም በመገናኛ ብዙኃን ህልውና ላይ ችግር ሊፈጥር ይችላል የሚል ስጋት ተፈጥሯል” ብለዋል፡፡
እኚሁ የምክር ቤቱ አባል፤ ህገ ወጥ የመሬት ወረራ የተመለከቱ ጉዳዮች በመደበኛ ህግ ሊታዩ ይችላል የሚል ሃሳብ አቅርበዋል፡፡
“ኮማንድ ፖስቱ የተለጠጠ ሥልጣን ነው የተሰጠው” ያሉ ሌላው የምክር ቤት አባል በበኩላቸው፤ “ኮማንድ ፖስት ከመሬት ጋር ምን አገናኘው?” ሲሉ ጠይቀዋል፡፡ በህዝባችን ላይ ስጋት የፈጠረው የተለጠጡ መብቶች ለኮማንድ ፖስቱ መሰጠቱ ነው ሲሉ አክለዋል፡፡
ከምክር ቤቱ አባላት ለተነሱት ጥያቄዎች ምላሽና ማብራሪያ የሰጡት ጠቅላይ አቃቤ ህጉ፤ በአሁኑ ወቅት ሁከትና ብጥብጥ እየተጠራ ያለው በማህበራዊ ሚዲያ መሆኑን በመጥቀስ፤ መገናኛ ዘዴዎችን መቆጣጠር የሚያስችል ሁኔታ ለኮማንድ ፖስቱ ካልተፈቀደ የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ ትርጉም አይኖረውም ብለዋል፡፡
ከመሬት ጋር በተያያዘ በመደበኛ ህግ፣ ህገ ወጥ የመሬት ወረራን የክልልና የፌደራል አስተዳደሮች ማስቆም ባለመቻላቸው በአዋጁ መካተቱን የጠቀሱት አቶ ጌታቸው፣ “ህግና ስርዓት የለም በሚል መሬት የሚወረርበትና ህገ ወጥ ግንባታ የሚከናወንበት ሁኔታ ተፈጥሯል” ብለዋል፡፡
“የኢንቨስተሮች መሬትን መቀማትም በህግና በስርአት መሆን አለበት ከዚህ ውጪ ያለ እርምጃ በቸልታ አይታለፍም” ብለዋል - ጠቅላይ አቃቤ ህጉ፡፡
አዋጁ፤ “የወንጀል ተጠያቂነትን” ባስቀመጠበት አንቀፁ፤ “መደበኛ ህግ የተመለከተው እንደተጠበቀ ሆኖ በዚህ አዋጅ የተመለከቱ ከአስቸኳይ ጊዜ እርምጃዎችና መተባበር ጋር የተያያዙ ግዴታዎችን ተላልፎ የተገኘ ማንኛውም ሰው እስከ አምስት ዓመት በሚደርስ ፅኑ እስራት ይቀጣል” ይላል፡፡   


=========

ከጋዜጣው አዘጋጅ፡-  በፓርላማ የተገኘው የአዲስ አድማስ ጋዜጠኛ፤አዋጁ በ346 የድጋፍ ድምጽ መጽደቁን የዘገበ ሲሆን በኋላ ላይ የፓርላማው ኮሙኒኬሽን ዳይሬክተር የድጋፍ ድምጹ 395 ነው በሚል ማስተካከያ መስጠታቸው ይታወቃል፡፡ ሆኖም በጋዜጣው ላይ 390 የድጋፍ ድምጽ የሚል የቁጥር ስህተት ተፈጥሯል፡፡ ለዚህም ውድ አንባቢያንን ይቅርታ ልንጠይቅ እንወዳለን፡፡
 



  

 · አድዋን በዘመኑ ፖለቲካ መቃኘት ታላቅ የታሪክ በደል መፈጸም ነው
  · ጀግኖች አባቶቻችን ጣሊያንን ያሸነፉት በጦር በጎራዴ አይደለም
  · ኢትዮጵያ ከተፈጠረች ጀምሮ በነፃነት የቆየች ሃገር ነች
  · ከ40 በላይ በአድዋ ላይ የተፃፉ መፅሐፍትን ይዘን ነው የሄድነው
  · “መታወቂያዬ ላይ ብሔሬ ከሚፃፍ፣ የደም ዓይነቴ ቢፃፍ ይሻለኛል”
  · ታሪክ ማለት ዛሬ ያለችው ኢትዮጵያ ብቻ አይደለችም

  25 ወጣቶች የተሳተፉበትን የዘንድሮ “ጉዞ አድዋ” የመራው ታዋቂው የፊልም ባለሙያ ያሬድ ሹመቴ፤47 ቀናት ስለፈጀው “ጉዞ አድዋ”፤ ከኢትዮጵያዊነትና የአንድነት ስሜት ጋር ያለውን ቁርኝት፣ጀግኖች አባቶቻችን ጣሊያንን የተዋጉት በጦር በጎራዴ አለመሆኑን --- ወዘተ ከአዲስ አድማስ ጋዜጠኛ አለማየሁ አንበሴ ጋር ባለፈው ረቡዕ ባደረገው የስልክ ቃለ ምልልስ አብራርቷል፡፡ መንግስት የአድዋ በዓልን በፖለቲካ ቅኝት ውስጥ አስገብቶ ለመዘከር ከሞከረ ታላቀ የታሪክ በደል መፈጸም መሆኑንም ይናገራል - ያሬድ ሹመቴ፡፡ ሌሎችም ጉዳዮች ተነስተዋል፡፡ እነሆ፡-

   የዘንድሮ “ጉዞ አድዋ” ምን ይመስላል?
ጉዞው ዘንድሮ ለ5ኛ ጊዜ የተደረገ ነው፡፡ በዚህ ጉዞ የተሳተፉት ደግሞ 25 ተጓዦች ናቸው፡፡ 21 ወንዶችና 4 ሴቶች ናቸው የተሳተፉት፡፡ ጉዟው በአጠቃላይ 47 ቀናትን ፈጅቶብናል፡፡ የአድዋ ታሪክ የተሰራባቸውን ቦታዎች በሙሉ ተጉዘንባቸዋል፡፡ አባገሪማ ማሪያም፣ ሸዊቶና ሰሎዳ ይጠቀሳሉ፡፡
በጉዞ ላይ የሕብረተሰቡ አቀባበልስ እንዴት ነው?
በአጠቃላይ 1060 ኪ.ሜትር የሸፈነ ጉዞ ነው። ከአዲስ አበባ ከወጣን ጀምሮ በየቦታው በጣም አስደሳች አቀባበል ነው የተደረገልን፡፡ የህዝቡ ስሜት የተለየ ነበር፡፡ ዘንድሮ ደግሞ ለየት የሚያደርገው፣ በኢትዮጵያዊነት አሰባሳቢ ሃሳብ ውስጥ የአድዋ ድል፣ እንደ መፍትሄ እየተቆጠረ ነው፡፡ ብዙ ቦታ ላይ የአንድነት ስሜትን የመናፈቅና አንድነቱን ወደ ኋላ ሄዶ የመመኘት ነገር አስተውለናል፡፡ በብዙ ሰዎች ላይ እንዳየነው፤በአቀባበሉ ወቅት ዝም ብሎ መቀበል ብቻ ሳይሆን ከወትሮው በተለየ ሁኔታ አንድነትን በመናፈቅ የተደረገ ነው፡፡
ወደፊት ይህን ጉዞ አስፍቶ የመቀጠል እቅድ አላችሁ?
እኛ ከ5 ዓመት በፊት የጀመርነው በ5 ሰው ነበር፡፡ አሁን 25 ሰው ደርሰናል፡፡ በ5 ዓመት ውስጥ የተጓዡ መጠን በ5 እጥፍ አድጓል፡፡ በቀጣይ እያሳደግነው ከሄድን፣ አድዋን የሚያህል ግዝፈት ያለው ህዝብ የሚሳተፍበት እንደሚሆን ጥርጥር የለውም፡፡ ዋናው እኛ የምንፈልገው ነገር፣ አድዋ ጥልቀቱን ዝም ብሎ በስሜት ብቻ የሚረዱት ሳይሆን በዕውቀት ሲረዱት የበለጠ ጥልቀት ያለው ሆኖ ይገኛል፡፡ ፍቅር ደግሞ ከስሜት ይልቅ በዕውቀት ሲሆን የበለጠ የጠለቀ ይሆናል፡፡ ከዚህ አንፃር እኛ ከእግር ጉዞው በመለስ፣ በየሄድንበት ቦታ ስናርፍ፣ ንባብ ላይ ትኩረት እናደርጋለን፡፡ ታሪክ ማወቅ ላይ ነው ትኩረታችን፡፡ ከ40 በላይ በአድዋ ላይ የተፃፉ መፅሐፍትን ይዘን ነው የሄድነው፡፡ በየቦታው እያጣቀስን ነው ታሪክን የምንረዳው፡፡ ከዚህ ቀደም ንባቡን የማነበው እኔ ነበርኩ፤ ዘንድሮ ተስፋዬ ሞላ የተባለ ተጓዥ፣ በአንባቢነት አገልግሏል፡፡
በዚህ መንገድ እያነበብን 122 ወደ ኋላ፣ 1060 ወደፊት እየገሰገስን ነው ጉዟችንን ያጠናቀቅነው። አድዋን እስከ ዛሬ በስሜት ብቻ ስለምንረዳው፣ ብዙ የተዛቡ ምስሎችን በአዕምሮአችን ቀርፀናል። ለምሳሌ በጦር በጎራዴ አባቶቻችን እንደተዋጉ ነው ሁሉም የሚናገረው፡፡ አድዋን ያሸነፍነው ግን በጦርና በጎራዴ አይደለም፡፡ ከጣሊያን ጋር የሚገዳደር መሳሪያ ይዘን ነው፡፡ በጦር በጎራዴ የሚለው ታሪክ አድዋን አይገልፀውም፡፡ አድዋ ላይ ጠንካራ ዝግጅት አድርገን የተሰለፍነው፡፡ ለምሳሌ እኛ በጦርነቱ የተጠቀምነው መድፍ፣ ከፈረንሳይ የተገዛ 4500 ሜትር መተኮስ የሚችል ሲሆን ጣሊያን በአንፃሩ ይዞት የነበረው መድፍ 3800 ሜትር ርቀት የሚተኩስ ነበር፡፡ ስለዚህ ጣሊያኖች የያዙትን ምሽግ በተለይ እንዳየሱስ ላይ የነበረውን ውጊያ በቀላሉ መምታት ተችሎ ነበር፡፡
ጣሊያኖችን በጦር ዝግጅትና በኃይል አሰላለፍ ጭምር በልጠናቸው ነበር የሄድነው፤ እነሱ በንቀት ነበር የተመለከቱን፡፡ አረመኔ፣ ያልተማረ፣ ንቃተ ህሊና የሌለው ህዝብ ብለው፣ምኒልክን በቀፎ ይዘን እንመለሳለን በማለት በንቀት ነበር የተመለከቱት። እኛ ደግሞ አክብደን፣ በቂ ዝግጅት አድርገንበት ነው የገጠምናቸው፡፡ ከ100 ሺ በላይ የተሰለፈ ጦር፣ ሁሉም የነፍስ ወከፍ መሳሪያ ነበረው፡፡ በአተኳኮስ ሥርአትም ቢሆን አዝማቻቸው ጀነራል ባራቴሪ የመሰከረው ነው፡፡ “ኢትዮጵያውያን ተዋጊዎች፤ ሁለት ወታደር በአንድ ጥይት የሚገድል ሰራዊት ነው  የነበራቸው፤ እኛ ግን ዝም ብለን ነበር የምናባክነው” ብሏል፤ ባራቴሪ፡፡ እነዚህን ታሪኮች ሚዲያውም ቢሆን አርቆ ማቅረብ መቻል አለበት፡፡ ጎራዴ የሚጠቀሙት ጠላት ቀረብ ሲል ጥይት ላለማባከን በሚደረግ ፍልሚያ ላይ ነበር፡፡ አባቶቻችን ዝም ብለው አይደለም የዘመቱ፤በበቂ ዝግጅትና እውቀት  ነው፣ ጦርነቱን በድል የተወጡት፡፡
የአድዋ ድል ላንተ ምንድን ነው?  
እንደሚታወቀው ማዘጋጃ ቤት የልደት ሰርተፊኬት ይሰጠናል፡፡ ይሄኛው ድል ደግሞ የኢትዮጵያዊነት ማህተም የተረጋገጠበት፣ ኢትዮጵያዊነት የሚለው ቁመና ገዝፎ እንዲታይ፣ አካል ኖሮት እንዲጨበጥ ያስቻለ ነው፡፡ የኢትዮጵያዊነት ማረጋገጫ ደግሞ አድዋ ነው። ግዝፈት ያለው ታሪክ እንጥራ ብንል፣ ትልቁ የታሪካችን ማህተም አድዋ ነው፡፡
የአድዋ ድል፣ የግዝፈቱን ያህል ትኩረትና ክብር አግኝቷል ብለህ ታስባለህ?
ለአድዋ ታሪክ ትኩረት ተሰጥቷል ብዬ አላምንም፡፡ ግን ትንንሽ ፍንጮች እየታዩ ነው። አሁንም ቢሆን ግን በተለያየ መንገድ ድሉን የፖለቲካ አሽከር ለማድረግ ነው የሚሞክረው። በዘመኑ የፖለቲካ ምህዳር ውስጥ አድዋን ለመቃኘት መሞከር ትልቅ የታሪክ በደል ነው፡፡ ብሔር ብሔረሰቦች በሚል ቅኝት አድዋን ልንዘክር ስንሞክር፤ አንድ ህዝብ ተብሎ የተቀመጠን፣ የኢትዮጵያ ህዝብ ከፋፍሎ ማስቀመጥ ነው፡፡ ይሄ ያኔ የነበረውን ታሪክ አይወክልም፡፡ አሁን መንግስት የፖለቲካ አቅጣጫ አስይዞ ሊጠቀምበት እንደፈለገ ነው የሚታየው፡፡ ይሄ ደግሞ በትክክል የአድዋን ድል የሚመጥን አይደለም፡፡ መንግስት ድሉን ሊይዘው የሚገባው ከፖለቲካ ነፃ በሆነ፣ ለአሁን ብቻ ሳይሆን ለትውልድ በሚጠቅም መንገድ ነው፡፡ ለኛ ብቻ ሳይሆን ለዓለምም ብርሃን ሊሆን በሚችል መንገድ አድዋን ለመዘከር ቢሞከር መልካም ነው ብዬ አስባለሁ፡፡
 ለምሳሌ የአባይን ጉዳይ ብንመለከት ቀደም ሲል የኢትዮጵያ ህዝብ በሙሉ በግጥሙም በዘፈኑም በእንጉርጉሮውም ይዞ ነው የኖረው፡፡ አሁን ግን “አባይ” ፖለቲካ ሆኗል፡፡ አሁን አባይ የሚል ቃል ከተፈጠረ ፖለቲካ ነው፡፡ የመንግስት የፖለቲካ ቃል ሆኖ እንዲቀር ነው የተደረገው፡፡ አድዋም የዚህ እጣ እንዳይደርሰው ያሰጋኛል፡፡ መንግስት የያዘበት አካሄድ፣ ወደዚያ እንዳያመራ ያሰጋኛል፡፡ መንግስት አድዋን ለመዘከር ሲያስብ፣ ወደ ራሱ ስቦ ሳይሆን፣ ወደ እውነተኛ ታሪኩ ራሱ ተስቦ መሆን አለበት፡፡ እርግጥ አሁን እኛም ከባህልና ቱሪዝም ሚኒስቴር ድጋፍ እያገኘን ነው፡፡ በተለይ ዶ/ር ሂሩት ወ/ማሪያም ወደ ሚኒስትርነቱ ከመጡ በኋላ ምሁራን ታሪኩን የሚመጥን ጉዳይ እንዲያቀርቡ በተለይ በሙዚየም ግንባታ ላይ ትክክለኛ ታሪኩን የሚመጥን ነገር ለመስራት የሚደረገውን ጥረት ማድነቅ ያስፈልጋል። ይህ የሚኒስቴር መስሪያ ቤቱ ስራ ግን በኋላ ቅኝቱ ተለውጦ ወደ ፖለቲካ ቅኝት እንዳይገባ፣ ከወዲሁ ምሁራን ሚናቸውን ሊወጡ ይገባል፡፡ ዝም ብሎ “የተጀመረውን ልማት ለማስቀጠል የአድዋ ድልን ..” የሚል መግለጫ ማውጣቱ ልክ ያልሆነ ነገር ነው፡፡ የአድዋ ድል የአባቶቻችን የጀግንነት ስራ በመሆኑ፤ “እንኳን ደስ ያለን፤ በአባቶቻችን እንኮራለን” ነው ሊባል የሚገባው፡፡ ወደ ራስ ቅኝት ማምጣት ብሔራዊ ስሜት አይፈጥርም፡፡ የዋህ ባለቅኔ ከወርቁ ይጀምራል ይባላል፡፡ መንግስት እንደዚያ አይነት አካሄድ አለው፡፡ ታሪኮች በራሳቸው ቆመው መዘከር ነው ያለባቸው፡፡ ከራስ ጋር እያገናኙ ፖለቲካዊ ቅኝት ለማስያዝ መሞከር ስህተት ነው፡፡
የአድዋ ድል ተገቢውን ክብር ያለማግኘቱ፣ ያጎደለብን ነገር ያለ ይመስልሃል?
በሚገባ አጉድሎብናል፡፡ አድዋ ብቻ ሳይሆን የአምስቱ ዓመት የአርበኝነት ታሪክም ራሱን የቻለ የኢትዮጵያውያን ትልቅ ተጋድሎ ነው፡፡ ይሄ ብቻ አይደለም፡፡ የደርግ ነገር እንዳይነሳ ተዳፍኖ ቀረ እንጂ ኢትዮጵያውያን በሶማሌ ወረራ ያደረጉት ተጋድሎ እንዴት ይዘነጋል፡፡ ስንት የጀግንነት መስዋዕትነት የተከፈለበት አይደለም እንዴ?! ያውም ሀገርን በወረረ ኃይል ላይ “ህፃናት አምባ” የሚባል ማዕከል የተቋቋመው፣ የጦር ተጎጂ ወላጆች ህፃናትን ማሳደጊያ ነበር፡፡ የፖለቲካ ነገር ሆኖ ፈረሰ እንጂ ህያው ምስክር የነበረ ነው፡፡ ታሪክ ማለት ዛሬ ያለችው ኢትዮጵያ ብቻ አይደለችም፡፡ በዚህ ረገድ ደርግ ትንሽም ቢሆን አድዋንም ሆነ ሌሎች የታሪክ ተጋድሎዎችን ለማንሳት ይሞክር ነበር፡፡ ከኢህአዴግ በኋላ ግን ህዝቡ ታሪክ ጠባቂ ባይሆን ኖሮ፣ አድዋ እንደውም የተሸነፍንበት ታሪክ ሆኖም ሊፃፍ ይችል ነበር፡፡
እንደምናውቀው በዚህች ሀገር ብሄራዊ መግባባት ያስፈልጋል ሲባል ነበር፡፡ መንግስት፤ ሃሳቡን አልቀበልም፤ ማን የተጣላ አለና ነው ብሔራዊ መግባባት የምትሉት ሲል ነበር፡፡ ዛሬ ራሱ የብሄራዊ መግባባት አጀንዳ  አራማጅ ሆኗል። ዋናውና ትልቁ ነገር፤ አንድ ህዝብ የሆነን፣ በህገ መንግስት ሳይቀር “ህዝቦች” እየተባለ እየተጠራ፣ በልዩነት ላይ ብቻ ብዙ ርቀት ከተሰራ በኋላ እንደገና የተበተነውን ለመስፈት መሞከር ማለት፣ የቡቱቶ ቀሚስ በመርፌ እንደ መጥቀም ነው፡፡ ኢትዮጵያ ውስጥ እስካሁን ልዩነት ላይ ያተኮረ ስራ ተሰርቷል። አሁን ይሄን ዝም ብሎ ለመስፋት ከመሞከር በመጀመሪያ እስካሁን የነበረው ነገር ልክ አይደለም ብሎ ማመን ያስፈልጋል፡፡ ዛሬም የአንድነትና የህብረት ስሜት ላይ ያተኮሩ በርካታ እድሎች አሉን፡፡ ነገስታቱን ለመኮነን ሲባል ጨቋኝና በዳይ አድርጎ በማቅረብ ህዝቡን ካጣላን በኋላ፣ ታሪክን እንዴት ማክበር ይቻላል? አንድን ንጉስ ታሪኩን አጥላልቶ፣ በሱ ዘመን የተሰራን ታላቅ ታሪክ እንዴት የማክበር ሞራል ይኖራል? ይሄ ስህተት መሰራቱን  ማመን ያስፈልጋል፡፡
በነገስታቱ ዘመን፣ ዛሬ የምንኮራባቸው፣እነ አክሱም ጎንደር፣ ላሊበላ የመሳሰሉት ተሰርተዋል። በዘመነ መሳፍንት ጊዜ ግን ህዝቡን ምናልባት ጦረኝነት ከማስተማር የዘለለ ለታሪክ የሚቀመጥ ነገር አልተሰራም። ምናልባት ህዝቡን፣ ለአድዋ የጦርነት ባህል ያለማመደው፣ ዘመነ መሳፍንት ሊሆን ይችላል፡፡ በተረፈ ግን መቧደንና መለያየት፣ በታሪካችን ውስጥ አውዳሚ ሆኖ ከማለፍ ውጭ ያመጣልን በጎ ነገር የለም፡፡
 በአሁን ጊዜ በህዝቡ ውስጥ ህብረትና አንድነት ጠፍቶ፣ ልዩነትና መከፋፈል ነግሷል እየተባለ ነው፡፡ አንተ ምን ትላለህ?
ይሄን በምሳሌ ልናገር፡- ሰይጣን፤ “እኔ ነኝ አምላካችሁ” ባለ ጊዜ፣ ”አይደለም አምላካችን እግዚአብሔር” ነው ያሉት፣ ከእነ ቅዱስ ሚካኤል ጎን የተሰለፉት መላዕክት ሲሆኑ፣ “ልክ ነህ አንተ ነህ አምላካችን” ያሉት ደግሞ ከሳጥናኤል ወገን ተሰልፈው ነበር፤ መሃል ላይ ደግሞ መናፍስቶች አሉ፡፡ እነዚህ መናፍስቶች አቋም አልነበራቸውም። ብዙ የመናፍስት ባህሪ ያላቸውን ግለሰቦች ዛሬም እናያለን፡፡
አሁን አብዛኛው ሰው፣ ዘመኑ በፈጠረው የንግግር ዘይቤ ውስጥ ራሱን የሚያስቀምጥ ነው። በግልፅ እናውራ ከተባለ፤ የኢትዮጵያዊነት አስተሳሰብ የሞተ ነበር የሚመስለው፡፡ በሌላ በኩል የአንድነት አመለካከቶች ደብዝዘዋል ተብሎ ተሰግቶ ነበር፡፡ የኦሮሚያው ፕሬዚዳንት ለማ መገርሳ ስለ ኢትዮጵያዊነት አንድነት ሲናገሩ፣ ህዝቡ ተቀበላቸው። ይሄ የህዝባችንን ትክክለኛ ቁመና ያሳየናል፡፡ ጥግ መያዝ፣ የፍርሃት ውጤት ነው፡፡ የዘረኝነት ሃሳብ የሚመጣውም ከፍርሃት ነው፡፡ ፍርሃት በሰፊው ተሰብኳል፤”እነ እከሌ ሊበሉህ ነው፣ እነ እከሌ አጥፍተውህ ነበር” በሚል የተፈበረከ፣ የህብረት ፀር የሆነ ፍርሃት ነው የተፈጠረው፡፡ እምነት ማጣትና መጠራጠር፣ መፍራትን ይወልዳል፤ፍርሃት ደግሞ ዘረኝነትን ይወልዳል፡፡ አሁን ይሄ እየተቀየረ፣ በፍርሃት ወደ ጠባብ ቡድናቸው ገብተው የነበሩ፣ አንድነቱ ሲሰበክ፣ ወደ ፊት እየወጡ ነው፡፡ አሁን ተስፋ ሰጪ ጊዜ ላይ እንዳለን ይሰማኛል፡፡ መንግስትም ይሄን የሰውን የህብረት፣ የፍቅር፣ የአንድነት፣ የሰላም ፍላጎት የተረዳው ይመስለኛል፡፡ በተቃራኒው ደግሞ አሁንም የተፈበረከ ጥላቻ ላይ የሚተጉ አሉ። አሁን የአንድነትና የህብረት መንፈስ ጠፍቷል ከተባለ፣ የጠፋው አስቀድሞ በተሰራው ስራ ምክንያት ነው፡፡ ይሄ ትውልድ ከሊቅ እስከ ደቂቅ በተለይም በመሪነት ቦታ ላይ ያሉ ሰዎች፤ በህብረትና በአንድነት ላይ መስራት አለባቸው፡፡
ከመታወቂያህ ላይ “ብሔር” የሚለውን ለማስጠፋት ሙከራ ስታደርግ ነበር፡፡ ጉዳይህ ምን ላይ ደረሰ?
እኔ በመታወቂያዬ ላይ ብሔር የሚል ነገር እንዳይሰፍር ስጠይቅ ሁለት ነገሮችን አስቤ ነው። ብሄር የሌለበት መታወቂያ ከሰጡኝ ለመያዝ፣ ካልሰጡኝ ግን መታወቂያ የሚባል ነገር ላለመያዝ አስቤ ነው የተንቀሳቀስኩት፡፡ ስለዚህ አሁን እኔ የቀበሌ መታወቂያ የለኝም፡፡ በፓስፖርት ነው የምንቀሳቀሰው፡፡ የራሴን እርምጃ ወስጃለሁ ማለት ነው፡፡
በሌላ በኩል፤ እኔ ይቅርታ ይደረግልኝና አዲስ አበባ ባለቤቷ ማን እንደሆነ የማይታወቅ ግራ የምትገባኝ ከተማ ናት፡፡ ማን እንደሚመራት የማይታወቅ፣ ማን ለጥያቄህ መልስ እንደሚጥ የማይታወቅባት? እኔ በበኩሌ፤ የአዲስ አበባ ህዝብ ጥያቄ ገብቶት ለማስተዳደር የተቀመጠ ሰው አለ ብዬ አላምንም፡፡ የአዲስ አበባ ህዝብ የዘረኝነት ጥያቄ የለውም፡፡ አብዛኛው የአዲስ አበባ ህዝብ ኢትዮጵያዊ ነኝ፣ በኢትዮጵያዊነቴ እወቁኝ ነው የሚለው፡፡ ያንን መልስ ከመስጠት ይልቅ ህዝቡን ወደ ክፍፍል የሚወስድ ስራ ነው የሚሰራው። በገባሁባቸው ቢሮዎች ያስተዋልኩት ነገር፣ የበላይ ሰው የሚባለውን ለማወቅ አስቸጋሪ ነው። መልስ ማግኘት አስቸጋሪ ነው፡፡ ምናልባት ከዚህ የአድዋ ጉዞ በኋላ ከንቲባው ቢሮ ሄጄ፣ መልስ ለማግኘት እሞክራለሁ፡፡ እስካሁን የሄድኩባቸው ብዙ መንገዶች፣ እስከ ፌደራል ድረስ ውጤት አላስገኘልኝም፡፡
የመጨረሻ ጥያቄዬን ለከንቲባው ለማቅረብ ተዘጋጅቻለሁ፡፡ መልስ የማላገኝበት ምክንያት ይኖራል ብዬ አልገምትም፡፡ ምክንያቱም እኛ አዲስ አበባ ላይ ያነሳነው ጥያቄ፤ ኦሮሚያ ላይ ምላሽ አግኝቷል። ኦሮሚያ ላይ የኦሮሚያ ክልል ነዋሪነት እንጂ ብሄርን የሚጠቅስ መታወቂያ መስጠት አቁመዋል፡፡ አቶ ለማ መገርሳ ራሳቸው፣ ይሄን ነገር ሲናገሩ ሰምቻቸዋለሁ፡፡ ከቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል ጋር የህዝብ ለህዝብ ዝግጅት በነበረበት ወቅት፣ ራሳቸው አቶ ለማ መገርሳ፤ብሄርን መታወቂያ ላይ መፃፍ እንደቀረ ይፋ አድርገዋል፡፡ ይሄ ኦሮሚያ ላይ ምላሽ ያገኘ ጉዳይ አዲስ አበባ ላይ ምላሽ የማያገኝበት ምክንያት አይኖርም፡፡ እኔ መታወቂያዬ ላይ ብሔሬን ከሚፅፉ፣ የደም ዓይነቴን ቢፅፉ ይሻለኛል፡፡ ምክኒያቱም ቢያንስ መንገድ ላይ አደጋ ደርሶብኝ ደም ቢያስፈልገኝ፣ በደም ልገሳ ለመዳን ይረዳኛል፡፡

 የኦሮሞ ህዝብ ዴሞክራሲያዊ ድርጅት (ኦህዴድ) ማዕከላዊ ኮሚቴ የካቲት 15/2010 ባካሄደዉ ስብሰባ የአመራር ሽግሽግ ማድረጉ ይታወሳል፡፡ በዚህም መሰረት ክቡር ዶ/ር አቢይ አህመድ የድርጅቱ ሊቀመንበር፣ ክቡር አቶ ለማ መገርሳ ደግሞ ምክትል ሊቀመንበር ሆነዉ እንዲያገለግሉ ወስኗል፡፡ ይህን ዉሳኔ በማስመልከት ክቡር አቶ ለማ መገርሳ ከኦ.ቢ.ኤን ጋር ቆይታ አድርገዋል፡፡ ክቡር አቶ ለማ መገርሳ ከኦ.ቢ.ኤን ጋር ያደረጉትን ቃለ ምልልስ ወደ አማርኛ ተተርጉሞ እንዲቀርብላችሁ በተደጋጋሚ ባቀረባችሁት ጥያቄ መሰረት ቃለ ምልልሱን ተርጉመን እንደሚከተለዉ አቅርበንላችኋል፡፡ መልካም ንባብ፡፡

    ‘የኦህዴድ ማዕከላዊ ኮሚቴ ባካሄደው ስብሰባ፤ የድርጅታችን አሰራር መሠረት በማድረግ የአመራሮችን ሁኔታ አስመልክቶ አንዳንድ አቅጣጫዎችን በማስቀመጥ ውሳኔዎችን አስተላልፏል፡፡
በአሁኑ ወቅት በሃገራችን ከተፈጠረው ሁኔታ በመነሳት፤ ድርጅታችን የሕዝባችንን ጥያቄ ከመመለስ አንፃር እስካሁን የሄደዉ አካሄድ ምን እንደሚምስል እና ትግሉን ብስለትና ቀጣይነት ባለው መንገድ እንዴት መምራት ይችላል በሚል መንፈስ መልሰን መላልሰን ስንመለከተው ነበር፡፡
በዚህ አካሄድም ግልጽ የሆነ ነገር ተፈጥሯል። ሕዝባችን እንደክልል ራሱን በራሱ ማስተዳደርና የኢኮኖሚ ተጠቃሚ እንዲሆን ከመፈለጉ የተነሳ ጥያቄዎችን ሲያነሳ ነበር፡፡ በሌላ መልኩም በፌደራል ደረጃ የሃላፊነት ድርሻ በመወሰድና በወሰደውም ልክ የአመራርነት ድርሻ እንዲኖረው ጥያቄ ነበረው፡፡ ይህ ጥያቄ ደግሞ የሕዝባችን ብቻ ሳይሆን የድርጅታችንም ጥያቄ ነበር፡፡ በክልልም ሆነ በፌዴራል ደረጃ የአመራርነት ሚናችንን በተገቢዉ መንገድ በመወጣት ለህዝባቸን ጥያቄ ተገቢዉን ምላሽ መስጠት እንዳለብን እናምናለን። ይህንን ከግብ ማድረስ ይገባናል፡፡ ለስኬታማነቱም ከሕዝባችን ጋር በመሆን ረዥም የትግል ጉዞ በማድረግ እዚህ ደርሰናል፡፡ ይህ ማለት ግን ትግሉ በዚህ አበቃ ማለት አይደለም፡፡ ትልቁ ትግል ከፊታችን ያለው ነው። ከዚህ በመነሳትም በፌዴራል መንግስት ውስጥ የአመራርነት ሚና በብቃት መወጣት አለብን ስንል ክልላችንን በመዘንጋት መሆን የለበትም፡፡
እዚህ ላይ ማሰብ ያለብን አብይ ጉዳይ ሃላፊነትን መቀበል አለብን ብለን ማሰብ ብቻ ሳይሆን በታሪክ አጋጣሚ ያገኘነውን ዕድል፣ እንዴት አድርገን ልንሰራበት እንደምንችል በማጤን፣ በበሰለ አካሄድ የወደፊቱን ግብ ማየት ነው እንጂ ሀላፊነትን መቀበል ብቻውን በቂ አይሆንም፡፡ ጉዳዩን ስትራቴጂያዊ በሆነ መንገድ ማጤን አስፈላጊ ነው፡፡ የተሰጠንን ዕድል በአግባቡ ካልተጠቀምንበትም መውደቅ ሊመጣ ይችላል፡፡ ይህ ደግሞ በሕዝባችን ላይ የሚያመጣው ተጽዕኖ ቀላል አይሆንም፤ በመሆኑም ጉዳዩን በሰከነ መንፈስ በማየት ልንሰራ ይገባል፡፡ ሕዝባችን በፌዴራል መንግስት ተገቢዉን የሃላፊነት ድርሻ ማግኘት አለብን ብሎ ሲጠይቅ ጥያቄው የሞራል ጥያቄ ነው፡፡ ድርጅቱም በዚህ ጥያቄ ተገቢነት ያምናል። በፌዴራል ደረጃ የሚቀመጠው አመራር ለኦሮሞ ሕዝብ የተለየ የኢኮኖሚ ተጠቃሚነትን ያመጣል ብለን አናስብም፡፡ አንድ ሰው ከመካከላችን በመውጣት ሀገሪቱን መምራት ይችላል ብንል እንኳ፤ የሀገሪቱን ብሔር ብሔረሰቦች በእኩልነትና በፍትሐዊነት ይመራል፡፡ የታገልነውም ለዚህ ነው፡፡ የኦሮሞን ሕዝብ ወክሎ እንደመቀመጡ መጠንም የኢትዮጵያን ሕዝብ ክብርና ጥቅም በማስጠበቅ፣ እኩልነት በሀገሪቱ እንዲሰፍንና ፍትሐዊነት እንዲረጋገጥ መስራት አለበት፡፡
በሌላ በኩል የኦሮሞን ክብር ማስጠበቅ የምንችለው፣ ሰርቀን ለሕዝባችን በማምጣት ሳይሆን ለፍትሐዊነትና ለእውነት የምንስራ መሆናችንን፣ በተሰጠን ዕድል ሰርተን በማሳየት ብቻ ነዉ፡፡
በቀጣይነት የሚነሳው የኢኮኖሚ ተጠቃሚነት ጥያቄ ነው፡፡ ይህ የሕዝብ ጥያቄ እንዴት መመለስ እንዳለበት ማዕከላዊ ኮሚቴው በግልጽና በጥልቀት በመወያየትና በመደማመጥ፣ ከኢኮኖሚ ተጠቃሚነት አንፃር ያለዉ ችግር እንዴት መፈታት እንዳለበት ሲመለከት ቆይቷል። ይህን ችግር ለመፍታት የአመራሩ ድርሻ ቁልፍ መሆኑ ተሰምሮበታል። ከዚህ በመነሳት እንደ አመራር ያለንን ፑል በመጠቀም፣ ከምንጊዜውም በላይ በአንድ ልብና ሃሳብ ጠንክረን team spirit (collective leadership ፈጥረን) በመንቀሳቀስ ላይ እንገኛለን።
ከግብ የምናደርሰው የህዝባችንን ጥያቄ ስለሆነ፣ በክልል ያለውን አመራራችንን እንዴት እናስቀጥል፣ በፌዴራል ደረጃ ያለንን ተልዕኮስ እንዴት ከግብ እናድርስ የሚለውን ሃሳብ አፅንኦት ሰጥተን ተመልክተነዋል፡፡ በፌዴራል ደረጃ ያለውን ብቻ በማየት በክልል ያለውን ጉዳይ የምናንጠባጥብ ከሆነ ውድቀት ማስከተሉ አይቀርም፡፡ አንድ ሰው አይደለም፤ ሀያ ሰው በፌዴራል ደረጃ ወንበር ቢያገኝ፤ የኦሮሞ ሕዝብ ጥያቄ መልስ አግኝቷል ማለት አይደለም፡፡ ስለሆነም በሁለቱም አቅጣጫ ተመልክተን አንድም ክልላችንና ሕዝባችን ያሉባቸውን ችግሮች ያለ ማንም ጣልቃ ገብነትና ንክኪ፣ ራስችንን ችለን ማስተዳደር መቻል ትልቅ ድል ነው፡፡
በተለይ የኢኮኖሚ ጥያቄን በመለከተ፤ ድርጅታችንን በማጠናከርና የመንግስት መዋቅርን በመገንባት ላይ አትኩረን ከሰራን፣ ከምን ጊዜውም በላይ ልንጠቀምበት እንችላለን፡፡ ዋናው ትኩረት ኦሮሚያ ላይ መስራት ነው። የስልጣናችን ምንጭ ሕዝባችን ስለሆነ ወደፊትም ወደ ፌዴራል ሄደን የምንሰራው ሥራ በግለሰብ የሚሰራ ስላልሆነ፣ ይህ ሕዝብ ዕውቅና እስካልሰጠውና እሰካልደገፈው ሁለት ሰውም ይሁን ሀያ ሰው ሄዶ ውጤታማ ሊሆን አይችልም፡፡ ይህንን ደግሞ ማምጣት የምንችለው በቤታችን ውስጥ የምንፈልገውን ነገር መስራት ስንችል ነው፡፡ በነፃነት ጠንክረን ኦሮሚያ ውስጥ ስንሰራ፣ የሕዝባችንን ችግር መፍታት እንችላለን። በተለያየ መልኩ እንቅፋት እየኖነብን፣ መሮጥ የምንችለውን ያህል እንዳንሮጥ የገደበን ነገር ቢኖርም፤ አሁን ባለን አቅም መሮጥ የሚያስችለን ነገር አለን ብለን እናምናለን፡፡ ስለዚህ ጠንካራ አመራር በክልላችን ሊኖረን ይገባል፡፡ ብዙ በጅምር ተንጠልጥለው ያሉ የኢኮኖሚ ተጠቃሚነትና ሕዝባችንን አንድ የማድረግ ስራዎች ይቀሩናል፡፡
የመንግስትና የድርጅት አደረጃጀት ጠንካራና ለሕዝቡ የሚቆረቆር መሆን አለበት። ይህንን ድርጅት ለማጠናከር የተለያዩ ትግሎችንና እርምጃዎችን እየወሰድን እዚህ ደርሰናል፡፡ ነገር ግን አሁንም ጠንካራ ሆኖ የወጣ አይደለም፡፡ አሁንም በተለየ መንገድ ማጠንከር ያስፈልጋል። ዝም ብለን በሩን ክፍት አድርገን፣ ሁላችንም፣ የምንሄድ ከሆነ ተያይዘን እንወድቃለን። አሁን ባለበት በአንድ ልብና ሃሳብ ጠንክረን ከሰራን ከላይ የምንሰራው ስራም ዉጤታማ ይሆናል፣ ረዥም መንገድም ይጓዛል፣ በመንገድም አይቀርም፡፡ ይሄንን የሚያስተጓጉል የሚሞክር ሊኖር ይችል ይሆናል፤ በሕዝብና በጠንካራ ድርጅት ከተደገፈ ግን ምንም አይሆንም፤ ስለሆነም በኦሮሚያ ላይ የሚሰራው ስራ ወሳኝ ነው፡፡ ስለዚህ ጠንካራ የሆነ አመራር ኦሮሚያ ላይ ሊኖረን ይገባል፡፡ ልክ እንደ እግር ኳስ ጨዋታ ማን የት ቢጫወት የበለጠ ውጤት ያመጣል አንደሚባለው ማየት አለብን፡፡ ከዚህ በመነሳት ካለን የአመራር ፑል፣ ማንን የትና እንዴት ብናዘጋጅ ይሻላል ብለን አንዱን በማንሳትና ሌላውን በመተው ሳይሆን በአንድ ሃሳብና በቡድን፣ ለአንድ ግብ ብንስራ ተያይዘን ረዥም መንገድ መጓዝ እንችላለን። ሕዝባችን ከእኛ የሚጠብቀውንም ነገር ከግብ ማድረስ እንችላለን።
ከዚህም በመነሳት የህዝባችንን ፍላጎት ከግብ ለማድረስ በሚያስችለን መልኩ አንድ አንድ ማስተካከያዎችን አድርገናል፡፡ ያደረግነው ማስተካከያ በፌዴራል ደረጃ የኦህዴድ ሚና የጎላ እንደሚሆን ሙሉ እምነት አለን፡፡ ድርጅቱ በፌዴራል አመራርነት ዉስጥ በሚገባ ሚናውን እንዲወጣ ስንታገል ነበር፤እየታገልንም ነው፥ ለወደፊትም እንታገላለን፡፡ይሄም ጥያቄ ዉስጥ አይገባም፡፡ የሚሆነዉም ዲሞክራቲክ በሆነ መልክ ነው፡፡ እንዲህ ስናደርግ ደግሞ ማን የት ቢተካ የበለጠ ዉጤታማ እንሆናለን በማለት አይተናል። በሌላ በኩል እንደ መስፈርት የሚነሱ አንድ አንድ ጉዳዮች ከወዲሁ በተሟላ መልክ እንድናደራጅ ትኩረት ሰጥተን ተወያይተን ወስነናል፡፡ አንድ አንድ ለውጥም አድርገናል፤ ለምሳሌ ማናችንም ከማናችን በልጠን አይደለም፤ ነገር ግን ማን የት ቢሆን በይበልጥ ዉጤት ማምጣት ይችላል? እና የድርጅቱን አላማ ከግብ ማድረስ ይችላል በማለት አይተናል፡፡
በዚህም መሰረት ዶ/ር አብይ የድርጅቱ ሊቀመንበር ሆኖ እንዲሰራ እኔ ደግሞ ምክትል ሆኜ እንድሰራ ወስነናል፡፡ ይሄን ስናደርግ ለህዝባችን ግልፅ ሊሆን የሚገባው ምንም ነገር ተፈጥሮ አይደለም። ነገር ግን የህዝባችንን ፍላጎት ከግብ ለማድረስ የተጠቀምንበት ስልት እንጂ፡፡ ይሄ የፖለቲካ ጉዳይ ነው፤ እድር አይደለም ወይም ማህበር አይደለም። ፖለቲካ ደግሞ በሁሉ አቅጣጫ መመልከትን ይጠይቃል፡፡ የህዝብ ፍላጎትን ያማከለና የድርጅቱን ዓላማ ከግብ ያደርሳል ብለን ያሰብነውን ሁሉ አድርገናል፡፡ በዚህ ዕይታ ነው ይሄን ማስተካከያ ያደረግነው፡፡ እንደዚህ ሲሆን አንድና ሁለት ሰው ማዘጋጀት ሳይሆን ወደ ፌዴራል አመራር የሚሄድ አካል በቡድን እንዲሰራ በማሰብ ጭምር ነው። ለፌዴራል የሚሄድ አካል እንዴት መሰራት እንዳለበት፤ ምን መስራት እንዳለበት ግንዛቤ በመያዝ፣ ይሄን ማስተካከያ አድርገናል፡፡ በክልል የሚቀረው አካል ምን መስራት እንዳለበት አንድ ሁለት ብለን አስቀምጠናል። ሁለቱም አካላት ደግሞ በመደማመጥ፤ በመተጋገዝ ይሰራሉ ብሎ ድርጅቱ አምኖበት፣ ማዕከላዊ ኮሚቴው ቀጣዩን ስራ በማጤን ወስኗል፡፡
ይህ ማለት ድርጅቱን ስመራው እንደቆየሁት አሁንም እመራለሁ፤ ሌሎቹም እንዲሁ፡፡ በጅምር ተንጠልጥሎ ያሉ የቤት ሥራዎች አሉን፡፡ ተንጠልጥሎ ያለ ሥራን ትቶ መሄድ ደግሞ የራሱ የሆነ ተፅእኖ ይኖረዋል፡፡ ስለዚህ እንደ እኛ ሃሳብ ጅምር ስራዎችን በክልሉ እየገነባን ባለነው ቲም/ቡድን/ በርትተን ብንሰራ ይበልጥ የተሳካ ይሆናል። ወደ ፌዴራል የሚሄደው ቡድን በዚህ ደረጃ የህዝባችንን ፍላጎት ያስከብራል፡፡ ይሄንን ስናደርግ በስልጣን ስሌት የምናየው ከሆነ፤ አንዱ ወንበር ካንዱ ይበልጣል፡፡ ይሄ ደግሞ በታሪክ ሲገጥመን ለመቀበል ማናችንም ትልቅ ጉጉት ይኖረናል፡፡ ነገር ግን እንደ ግለሰብ ወንበር በመመኘት ብቻ ህዝባችን ዋጋ የከፈለበትን ጉዳይ ከግብ እናደርሳለን ብለን ማሰብ አይቻልም። በይበልጥ የት ሆነን ብንሰራ፣ ህዝቤ ዋጋ የከፈለበትን ከግብ አደርሳለሁ ብሎ በማሰብ እንጂ፡፡ ለእኔ ትልቁ ስኬት ዋጋ ከፍለን እዚህ ያደረስነዉን ትግልና በኦሮሚያ የተጀመረውን ሁሉን አቀፍ ትግል ከግብ ማድረስ ሲቻል ነው፡፡ የተለያዩ ጫናዎችና ሙሉ ትኩረታችንን የሚበትኑ ጉዳዮች ከቆሙ፣ በሙሉ ኃይል ዛሬ ላይ ከምናደርገው ሩጫ በሁለትና ሶስት እጥፍ ማፍጠን እንችላለን፡፡ ሌት ተቀን ሙሉ ኃይላችንን በመጠቀም በኦሮሚያ የጎላ ለዉጦች እናመጣለን ብዬ አምናለሁ፡፡
በሀገራች ደረጃ ያለዉን ቸግር ለመፍታት በምናደርገዉ እንቅስቃሴ፣ በክልል ያለውን ችግር በመሰረቱ ካልፈታን፣ እንደ መዋጮ አስር ሰውና ከዚያ በላይ ወደ ፌዴራል አመራር በመላክ ቀጣይነት ያለዉ መፍትሄ ልናመጣ አንችልም። መጀመሪያ ክልላችን መሰረቱ የጠነከረ መሆን ይገባዋል፤ በሁለት እግሩ መቆም ይኖርበታል፤ ካሁን በኋላ የሚሆነው ጠንካራ ትግል ነው፡ ዝም ብለን ለአጭር ጊዜ ኃላፊነት ወስደን መመለስ ከሆነ፣ ማንም ሰው የፈለገበት ቦታ መሄድ ይችላል፡፡ ነገር ግን የተገኘውን ዕድል ዘላቂ ለማድረግ አስበንበት፣ እስትራቲጂክ በሆነ መንገድ መስራት ይኖርብናል። በተለይ በክልል ደረጃ ፍፃሜ ሳያገኙ የቆዩ የቤት ስራዎችን ሙሉ ማድረግ አስፈላጊ ነው፡፡ ሙሉ አድርገን ማናችንም በፈለግን ቦታ፤ ደረጃ መስራት እንችላለን፡፡ በክልል ደረጃ ተጨባጭ ለዉጥ ካመጣን፣ ጠይቀን ሳይሆን ተጠይቀን መስራት እንችላለን ብዬ ተስፋ አደርጋለሁ፡፡ አሁን ብዙ የቤት ስራ አለብን፤ ድርጅታችንን ጠንካራ ድርጅት ማድረግ አለብን፤ በጣም ብዙ ነገር ማስተካከል አለብን፡፡ በራሱ የሚተማመን፣ ቀን ከሌሊት ሰርቶ ስር-ነቀል ለውጥ የሚያስገኝ ጠንካራ ክልላዊ መንግስት መፍጠር ይጠበቅብናል፡፡ አሁን ባለዉ ተጨባጭ ሁኔታ የህዝባችንን የሞራልና ኢኮኖሚ ጥያቄ የመመለስ አቅም በቂ አይደለም፡፡ የኢኮኖሚ ጥያቄ መመለስ ይኖርብናል፡፡ በኦሮሚያ ያለን የሰው ሀብት፣ የተፈጥሮ ሀብት በማቀናጀት ለውጥ ማምጣት አለብን። ለዚህ ደግሞ አሁን ባሰብነው መንገድ ከሰራን ረጅም መንገድ ያስኬደናል ብለን ስለምናምን፣ በአንድ አቋም መፅናት ነዉ ያለብን፡፡
መርሳት የሌብን ነገር ቢኖር፣ በአንዳንድ አሉታዊ ንክኪዎች አንተ እንዲህ አድርግ፣ አንተ ደግሞ እንዲህ ሁን ብሎ ዛሬ በሚታየዉ መልኩ የምንሰራ ከሆነ ህዝባችንን አሳፍረናል፤ የፈሰሰዉን ደም ዋጋ አሳጥተናል ማለት ነዉ። ስለዚህ በዚህ አንሰራም። ለህዝባችን ቃል በገባነዉ መሠረት እንጂ፡፡ ዛሬም ነገም ቃላችንን አንሸራርፍም፡፡ የምንሰራዉም ማንንም በመስማት ሳይሆን ህዝባችንን በመስማት ይሆናል፡፡ ይህ አቋም አይሸራረፍም፡፡ እዚህ ያደረስነዉን ወደኋላ የሚመልስ የለም፡፡ ዋናዉ ጉዳይ ግን ሁሉም ነገር በብልኃት፣ ዲሞክራቲክና በተደራጀ መንገድ መሆን አለበት፡፡ ከአሁን በኋላ በተናጠል የሚሰራ አመራር የለም፡፡ ሁሉም በቡድን መንፈስ ነዉ የሚሰራዉ፡፡ በዚህ መልክ ተግባብተን እየሠራን ነዉ፤ በዚህ አጋጣሚ ደግሞ ይበልጥ አጠንክረን በአንድ ሀሳብ፣ በአንድ አቋም፣ በአንድ እይታ ተቀናጅቶ የሚሠራ አመራር መሆን አለብን። በዚህ መልኩ ኮሚቴያችን አምኖኝ ተቀብሎኛል። የኦሮሚያ ካቢኔዎች እንዲሁ በዚሁ መልክ ሀሳቡን ተቀብሏል፤ ይህን ደግሞ ማጠናከር ነዉ፡፡ አመራሩን ማብቃት አለብን፡፡ አንድ ሰዉ አንድ ሰዉ ነዉ፤ ጠንካራ አመራር ማፍራት አለብን፤ በምኞት ብቻ አላማችንን ማሳካት አይቻልም፤ ወደ ተግባር መቀየርና የትም ቦታ ሆነን መገኘት አለብን፡ በልጠን መገኘት አለብን፣ ዛሬ እዚህ ካልተሰራ ከየትም ሊመጣ አይችልም፡፡ ትልቅ ዕድል እጃችን ላይ ነው። ትልቅ እድል ነው፤ ለኛ ውድቀት አይደለም፡፡ ልንጠቀምበት ይገባል። እስከ ዛሬ ለህዝባችን ትልቅ ውጤት አስገኝተናል ብለን እናምናለን፡፡ ጠንክረን ሰርተን ከኦሮሚያ አልፈን ህዝባችን የተናቀበትን፣ ሌላን ማስተዳደር ይቅርና እራሱን እንደማያስተዳድር ተደርጎ የነበረውን የመቶ ዓመት ጥያቄን አልፈን፣ ዛሬ የሀገራችን ህዝቦች ኦሮሞ ያስተዳድረናል የሚልበት ደረጃ ላይ ደርሰናል፡፡ እንዲሁ አልመጣም በሥራ እንጂ፤ ታሪክ ተቀይሯል ከመቶ ሃምሳ ዓመት በላይ የነበረብንን እድፍ ታጥበናል፡፡ በዚህ ደረጃ የኦሮሞ ታጋዮች በጋራ ትግል እዚህ ደርሰናል፡፡ቀጥሎም እንደዚያዉ ነው መሆን የምንመኘው፣ እውን ሆነን ምኞቱን ማረጋገጥ ያለብን የቤት ሥራ ነው፡፡
እኔ ዛሬ ብወድቅ ብቻዬን አልወደቅኩም፤ ህዝብን አከትለን ስለሆነ የምንቀመጥበት መቀመጫ የህዝባችን ማንነት እንጂ የግላችን አይደለም፡፡ የእኔ መውደቅ መድከም ለዚህ ህዝብ የሚያመጣዉ ተጽእኖ አለ፡፡ ስለዚህ በጥንቃቄ መስራት ያስፈልጋል፡፡ በመደጋገፍና በመተጋገዝ መስራት ያስፈልጋል፡፡ በተገኘው ዕድል መጠቀም እንጂ ወዲያ ወዲህ የምናይበት ጊዜ አይደለም። ማፈራረስ አይደለም የሚንፈልገዉ፤ መተቻቸት አይደለም የሚፈለግብን፤ በየትም በኩል የህዝባችንን ምኞትና ጥቅም ማስጠበቅ ነው፡፡ ይሄንም ከግብ ለማድረስ የሰራንበት ጉዳይ ስለሆነ ህዝባችን በዚህ በኩል ልረዳን ይገባል፡፡
የወሰነዉ ዉሳኔ የሌላ አካል ጫና አለበት ብሎ ለሚጠራጠር ማንም ሰው ግልፅ ሊሆን የሚገባው፣ በማንም ጫናና ተፅዕኖ አልሰራንም። ግልጽ ሊሆንለት ይገባል፡፡ እኔ መገፋት ያለበትን ገፍቼ፤ ማድረግ ያለብኝን አድርጌ፣ ዛሬ ላይ ደርሼ በማንኛውም አካል ግፊት የምወስን ከሆነ ይሄን ህዝብን መናቅ ይሆናል። የህዝቡንም ትግል ዋጋ ማሳጣት ነው፡፡ በፍጹም አናደርግም፡፡ መታወቅ ያለበት ጉዳይ ነገሮችን በፖለቲካ አይን መመልከት ነው፡፡ በቅድሚያ ማየት ያለብን፣ እኛ የምንፈልገው ቤታችንን ማድዳት ነው፤ ራሳችንን ነፃ ማድረግ ነው፤ ሌላ ነገር የለም፡፡
ይሄን በአጽንኦት መመለከት ይኖርብናል፡፡ ለኔ የማንም ሰው ግፊት/ ጫና/ አይደለም፤ ለህዝቤ ብሠራ ይበልጥ ውጤት ማምጣት እችላለሁ ብዬ አምናለሁ፡፡ ዛሬም ነገም የጀመርነው ወደ ኋላ ሊንሸራተት ይችላል፤ የህዝብ ትግል ወደ ኋላ ይቀለበሳል ብዬ አይደለም፤ ነገር ግን መስተካከል ያለባቸው ብዙ ነገሮች አሉ፡፡
ዛሬ ወጥተን ለመታየታችን እኔ በግሌ የሰራሁት ልዩ ሥራ አለ ብዬ አላስብም፡፡ ለዚህ ክብር ያበቃን ይሄ ህዝብ ነው፡፡ እኔ በግሌ ከማንም በልጬ አይደለም፡፡ በዚህ ህዝብ ተማምነን ደግሞ ማድረግ የሚገባንን ነገር ያለ ፍራቻና መሸማቀቅ አድርገነዋል፡፡ የተማመነው በእነርሱ ነው፡፡ ክብርና ሞገስ ያጎናፀፈንንና ዕውቅና የሰጠንን ህዝብ ተማምነን ነው የሰራነው፡፡ ነገም በዚህ እይታ ነው የምንሰራው ዛሬም ቢሆን ይህን ህዝብ ለማዋረድ ብለን አይደለም፤ በቅድሚያ ግን ቤታችን ውስጥ ያላፀዳነው ነገር አለ፡፡ ያልሰራነው ነገር አለ። እሱን አልጨረስንም፤ ይህንን መዘንጋት የለብንም፤ ዛሬም ተንኮልና ሴራ አይሰራብንም ብለን የምናስብ ከሆነ ተሳስተናል፡፡ አቅማችንን ማጎልበት ይቀረናል። አንድነታችንን ማጠናከር ይቀረናል፡፡ ጠንካራ ለህዝብ የሚሰራና ህዝባዊ ድጋፍ ያለው ድርጅት ለመገንባት ልንሰራ ይገባል፡፡ ኦህዴድን እንደ አዲስ ልንሰራው ይገባል ስንል፣ ይህንን ድርጅት ማንም ሊሰራው አይገባም ማለታችን ነዉ፡፡ እንደ ጀመርኩት እኔም መሥራት ይገባኛል ብዬ አስባለሁ። አብሮኝ ከሚሰራ ኃይልና አመራር ጋር መሥራት ይገባኛል ብዬ አስባለሁ። ይሄ ክልል፤ ክልል ብቻ አይደለም፤ ትልቅ ሐገር ነው፡፡ በዚህ ክልል ትልቅ ሀብት አለ። ግን አልሰራንበትም፡፡ ይህቺን ሀገር ለመለወጥ ኦሮሚያን መቀየር አለብን ብለን ነበር፡፡ እሱን ልንሰራ ይገባል፡፡ ለዚህ ደግሞ አቅማችን ሊበታተን አይገባም፡፡ ስለሆነም እዚህ ያለውን መሥራት ይገባናል። ለእኔ ህዝቤ ያንን መመኘቱ ክብር ነው፡ ክብርን ያጎናፀፈኝ ነው፡፡ ስለዚህ እኔም ይህን ክብር ሳይሸራረፍ ለማስጠበቅ፣ ትናንትና ህይወቴን ሰጥቼ እንደሰራሁት ሁሉ ነገም ለእሱ እሰራለሁ፡፡ ለእሱ ስሰራለትም የት ቦታ ውጤታማ እንሆናለን በሚለው አግባብ እኔም ሆንኩኝ ድርጅቴ አይተን ፈፅመናል። ስለሆነም አንዳንድ ነገሮች በዕድል እጃችን ይግቡ እንጂ በመሃከላችንና በጓዳችን ማስተካከል የሚገቡን አንዳንድ ነገሮች አሉ፡፡ ይህ ማለት ለማ ነገ ወደ ታሰበው ቦታ የመምጣት ዕድሉ ተዘጋ ማለት አይደለም፡፡ በጓዳችንና በቀዬአችን ያለውን ነገር ሁሉ አስተካክለን ከጨረስን፣ ሳንወድ የግድ መንገዱ አጭር ይሆናል፤ የሚል ግምት አለኝ፡፡
አይደለም በኦሮሚያ በዚህች ሀገር በየትኛውም ደረጃ ሰርተንም ሆነ መርተን ለውጥ ማምጣት እንችላለን፡፡ በሀገሪቱ GDP ውስጥ የክልሉ ድርሻ ወሳኝ ነው፡፡ እውነት ይህችን ሀገር መቀየር ከተፈለገ፣ በክልሉ ላይ ነው መሰራት ያለበት፡፡ ይሁን እንጂ እኛ ሀገሪቱን መቀየር አይደለም፣ የድሀውን ህዝብና ኦሮሞ ኑሮ መቀየር አይቻልንም፡፡ ዛሬም ለም መሬት ላይ ተቀምጦ፣ እየተራበና እየተጠማ ያለ ህዝብ አለን፡፡ መጀመሪያ እሱን መቀየር አለብን፤ ይህንን ከቀየርን ለወደፊትም ጊዜ አለ፡፡ ነገ በየትኛውም ቦታ ለማም ይምጣ ገመቹ፣ እሱ ምንም አይደለም፣ መንገድ ብቻ ይከፈት፤ መጀመሪያ እሱን እንቀይር፤ መንገድ ተከፍቶ የተሟላ አቅም ኖሮን፣ አንድነት ኖሮን ይህንን መጎናፀፍ የሚያስችለን አቅም ካለ፤ አይደለም ዛሬ ነገም ማንም በቀጣይነት ሊመጣበት ይችላል፡፡ ይህንን ልንዘነጋው አይገባም ስለሆነም በዚህ ደረጃ ልንሰራ ይገባል፤ አንድ ሰው አንድ ነው። አንድ ሰው ድርሻ የለውም ማለት አይደለም። ነገሮችን በመለወጥ ውስጥ ድርሻ አለው፡፡ ነገር ግን አንድ ሰው፤ ያዉ አንድ ሰው ነው:: ከልብ የሚሰራ፣ ትልቅ ኃይል ከሥሩ ማደራጀት አለበት። በየትኛውም ጊዜ በማንኛውም ሰአት በሚመጣ ንፋስ የማይናወጥ ሰው ሊኖረን ይገባል እንጂ በግል ቢንጠላጠል ረዥም መንገድ መሄድ አይችልም፡፡
ስለዚህ ይሄን አውቀን ጠንክረን መስራት ይገባናል። ይህን ሁሉ እናደርጋለን ስንል ለኦሮሞ ብቻ ሳይሆን ለመላው ሀገሪቱ ብሔሮች ብሔረሰቦችና ህዝቦች ነው፡፡ እኛ በየትኛውም ደረጃ ኦሮሞ የአመራርነት ድርሻ ወስዶ ይምራ ስንል የኦሮሞ የበላይነት እንዲመጣ አይደለም፤ የብሔሮች ብሔረሰቦችና ሕዝቦች እኩልነት እንዲረጋገጥ ነው። ይህች ሀገር ሰላም አግኝታ ቀጣይ ሆና እንድትኖር ነው ኦሮሞ እየታገለ ያለው፡፡ ይህም ከግብ እንዲደርስ ከየአቅጣጫዉ በማየት መስራት ይጠይቀናል። ይህ ነው ግባችን፡፡ ለዚህ ደግሞ በየትኛውም ቦታ ይሁን ወደ ጨዋታው እስከገባን ድረስ የተሻለ የሚጫወትበት ቦታ ላይ መጫወት ነው፡፡ ለምሳሌ ወደ ፌደራል የምንልካቸው ሰዎች፤ ብቻቸውን ምንም መሥራት አይችሉም። ዕድላቸውን የሚወስነው እኛ የምንሠራው ሥራ ነው፡፡ በሀሳብ እንደ ምሰሶ ካልደገፍናቸዉ፣ ቅርንጫፍ ሆነው ነዉ የሚቀሩት፡፡ እናም ምሶሶ እና ግንድ ላይ እንስራ። ግንዱ ጠንካራ ከሆነ፣ ቅርንጫፉ የትም መሄድ አይችልም፤ በዚህ ላይ በብስለት ልንሰራ ይገባል። ወደ ኃላ ማለት የለብንም ብለን ነው እነጂ የሚገባበት ቦታ ገብተን ለመስራት ማናችንም የምናቅማማበት ጊዜ ላይ አይደለንም፡፡ ከዚህ ወደ ኋላ አንልም፤ ይህ ሲሆን ግን እኔ በግሌ ብቻዬን ወደፊት ወጥቼ፣ ሁሉንም ነገር አሳካለሁ ማለት አይደለም ፡፡ እንደ አመራር መሥራት የሚችሉትንም ማብቃት አለብኝ። ሌሎች ለነገ አመራርነት ብቁ የሆኑ፤ ፖለቲካው ገብቷቸው ሊሰሩበት የሚችሉ ቆራጥ፤ ተቆርቋሪ፤ ልባም፤ ሙሉ ዕውቀትና ክህሎት ያላቸውን አምጥቶ በማለማመድ መሥራት ትልቅ ጥበብና አመራርነት ይጠይቃል፡፡ እንዲህ እየሠራን ነው የመጣነው፡፡
እኔም በግሌ ዛሬ የዚህች ሀገር አመራር ብሆን፤ ማንም ያላገኘውን ዕድል እንዳገኘሁ ይሰማኛል። ይቅርና በኢትዮጵያ በአሜሪካ ውስጥ ሰው ለስልጣንና ለወንበር ብሎ ነው ይገዳደል የነበረው። ለግል ስም ከሆነ ማንም ያላገኘውን ዕድል ነው ያገኘሁት፡፡ ነገር ግን እኔ የምኖረዉ ለግል ስሜ ሳይሆን ለህዝቤ ነው፡፡ ለህዝቤ ደግሞ መሥራት በምችለው ቦታ ላይ ነው መሥራት ያለብኝ፡፡ ምክንያቱም ክብር፤ ሞገስና ፍቅር አጎናፅፎ ለዚህ ያበቃኝ የለማ የግል ብቃትና ችሎታ አይደለም፤ይህ ህዝብ ነው፡፡ የት ጋር ብሰራ ነው ዉጤት ላመጣ የምችለው የሚለውን አስቤ ከማንኛውም ነገር ነፃ በመሆን መሥራት አለብኝ፡፡ በሥልጣን ዕይታ ካየነው ማንም ሰው ያላገኘውን ዕድል ነው ያገኘሁት፡፡ ቢሆንም ባይሆንም ዛሬ መቀበል ነው የሚገባኝ፡፡ እሱ ሳይሆን ግን እኔ የግል ክብር የለኝም። ክብሬ ከህዝቤ ጋር ነው፡፡ ይሄ ህዝብ ክብር ሲያገኝ ነው፣ እኔም አብሬ የምክብረው፡፡ በዚህ መልኩ ነው እየሰራን ያለነው፡፡ በዚህ ረገድ ህዝባችን ምንም ጥርጣሬ ሊገባው አይገባም፡፡ ድርጅታችን የሚወስነው ውሳኔ ባለን እዉቀት፣ አቅማችን በፈቀደውና በተረዳነው መንገድ ሁሉ፣ ይህንን ህዝብ በሚጠቅም መንገድ ነው እየሰራን ያለነው፡፡ እዚህ ደረጃ ላይ ከደረስን በኋላ ሌላ አካል ፈርተዉ፣ በሌላ ትእዛዝ ይሰራሉ ብሎ የሚያስብ ሰው ካለ ሞኝ ነው፡፡ ኦህዴድ እዚህ ደረጃ ላይ ከደረሰ በኋላ ታዞ የሚሰራ ከሆነ ሞኝ ነው ማለት ነዉ፡፡ ለራሱ ይጠፋል እንጂ ይህን ህዝብ ማጥፋት አይችልም፡፡ የዚህን ህዝብ ትግልም ሊያጨልም አይችልም፡፡ የህዝባቸንን ትግል አናጠፋውም፤ ይበልጥ ጎልቶ እንዲታይ መሥራትና በበሳል መንገድ ነው መጓዝ ያለብን፡፡
ባለፉት ዓመታት ሲሰሩ የነበሩ ነገሮች ምንድናቸው? ከላይ ያለው ንፋስ ምን ይመስላል? በዚህ ውስጥ በምን ወቅት ነው ለውጥ ማምጣት የምንችለው? የሚሉትን በሰከነ መንገድ ማየት አስፈላጊ ነው፡፡ በዚህ መልኩ ተረጋግተን በማየት ነው ውሳኔ ላይ የደረስነው፡፡ በመሆኑም ህዝባችን፣ የድርጅታችን አባላትና የመንግስት መዋቅርም ጥርጣሬ ሊገባቸው አይገባም፡፡ ይህ ስኬታማ እንዲሆን ተረዳድተን መሥራት ይገባናል፡፡ ትናንት በጋራ የጀመርነውን ትግል ከግብ ለማድረስ አውቀን በመግባባት ከፊታችን ለሚጠብቀን ትግል ዝግጁ ልንሆን ይገባል፡፡ እዚህ ውሳኔ ላይ የደረስነው ለህዝባችን ጥቅም በማስብ እንጂ ሌላ ጉዳይ ኑሮን አይደለም፡፡ ለግለሰብ ወንበርና ጥቅም ተብሎ ሳይሆን ለህዝብ ጥቅም መሆኑ ሊታወቅ ይገባል፡፡
ገለቶማ!
በክልሉ መ/ኮ/ጉ/ፅ/ቤት ኃላፊ አቶ አዲሱ አረጋ የተረጎሙት
“ይህቺን አገር ለመለወት ኦሮሚያን መቀየር አለብን”

 ከዕለታት አንድ ቀን፣ አንድ ነብሰ ገዳይ፣ ከአንድ ሟች ጋር ይጨቃጨቃል፡፡ በቀላል ጉዳይ ነው ጭቅጭቃቸው!
ገዳይ - “ሰማይ ከጠቆረ ይዘንባል” ይላል፡፡
ሟች - “ዳመና - ግላጭ ሲሆን ነው የሚዘንበው፡፡ ይሄ የውሸት ጥቁረት ነው” ይላል፡፡
ገዳይ - “የለም ይሄ የውሸት ጥቁረት አይደለም፡፡ እኔ አያቴ የነገሩኝ፤ ጥቁር ዳመና ስታይ በጊዜ ተሰብሰብ፡፡ ምክኒያቱም አንተም ጥቁር ስለሆንክ ቁጠኛ ነህ - ትዘንባለህ!”
ሟች - አያትህ፤ ዝም ብለው የልጃቸው ልጅ ስለሆንክ ሲያሞካሹህ ነው!
ገዳይ - “አንተ ማን ነህና ነው፣ ለአያቴ እንዲህ ያለ ግምት የምትገምተው? የት ታውቃቸዋለህ? ደደብ” ይላል፡፡
ሟች - “ደደብስ አንተ! ከስንት ዘመን በፊት ያረፉ አያትህን ንግግር ለዛሬ ይሰራል ብለህ ያሰብክ!”
ገዳይ - “ለዚህ ድፍረትህ ደህና ዋጋ ያስፈልግሃል - አንድ ጥይት!” ብሎ ሽጉጥ አውጥቶ፣ ግንባሩን ይለዋል፡፡
ሟች - ድፍት ይላል፡፡
የጥይቱን ጩኸት የሰማ አንድ ባላገር፣ ወደ ቦታው ሲመጣ፣ ሟችንና ገዳይን ያያል፡፡
ፖሊስ መጣ፡፡ ገዳይን ያዘው፡፡ ባላገሩን በምስክርነት ጠራው፡፡ ችሎት ፊት፣ ዳኛ ለምስክሩ ጥያቄ ያቀርባሉ፡-
“ያየኸውን ተናገር!”
ምስክር - “ሁኔታው ሲፈፀም ባቅራቢያው ነበርኩ”
ዳኛ - “ከዚያስ?”
ምስክር - “የጥይት ጩኸት ወደተሰማበት ሄድኩ፡፡ ሟች ግንባሩን ተመቶ ተዘርሯል፡፡ ገዳይ ባካባቢው በግዳይ ጥያለሁ መንፈስ ይንጎራደዳል! ገዳይ መሆኑ ያስታውቃል!”
ዳኛ - “ግን ተኩሶ ሲገድለው በዐይንህ በብረቱ አይተሃል?”
ምስክር ዝም ይላል፡፡
ዳኛ - “ስለዚህ ተኩስ ሰማህ እንጂ ሲተኩስና ሲመታው አላየህም፡፡”
ምስክር - “አዎን አላየሁም”
ዳኛ - “እንግዲያው ለምስክርነት አትበቃም!”
ምስክር፤ ከችሎቱ ወጥቶ ባለው ረዥም ኮሪደር እየሄደ፤
“አይ ዳኛ! አይ ፍርድ!” እያለ ሳቁን ይለቀዋል፡፡
ዳኛው ለህግ አስከባሪው፤ “አምጣልኝ ይሄን አጋሠሥ! ፍርድ ቤቱን ደፍሯል!”
ተጠርቶ ተመለሰ!
ምስክር - “ደሞ ለምን ተጠራሁ?”
ዳኛ - “ፍርድ ቤቱን በመድፈር ስለተከሰስክ ነው”
ምስክር - “ምን አድርጌ?”
ዳኛ - “በፍርድ በቱ በመሳለቅ ስለሳቅህ ነው!”
ምስክር - “ይሄን በምን አወቁ፤ ጌታዬ?”
ዳኛ - “እኔ ራሴ ሰምቼሃለሁ!”
ምስክር - “ስስቅ አይተዋል?”
ዳኛ - “አላየሁም”
ምስክር - “እንግዲያው እርሶም ለምስክርነት አይበቁም!”
ዳኛው አፈሩና አሰናበቱት!!
*      *     *
ሁኔታዎች ለፍርድ ሳይመቹ ሲቀሩ በራስ ላይ እንደ መተኮስ ያለ አደገኛ ችግር ውስጥ ይከትታሉ - ፈረንጆቹ እንደሚሉት፤
ቡመራንግ (boomerang) ይፈጠራል! አትፍረድ ይፈረድብሃል እንደተባለው ነው! ምንጊዜም፣ በተለይ አመራር ላይ ሆነን፣ የምንሰራቸው ስህተቶች፣ ከማንኛውም ዜጋ፣ ከፍ ባለ ደረጃ ተጠያቂዎች ያደርጉናል፡፡ ይህም በመሠረቱ የህሊና ተጠያቂነትን መደላድል ያደረገ ጠንካራ ዕውነታ ነው፡፡ በሥልጣን ላይ እያለን የምንሠራው ደግ ነገር፣ የስኬታችን ቁልፍ በመሆን እንደሚያስመሰግን ሁሉ፤ የምንሠራው መጥፎ ነገርም እንደ ጥቁር ጥላ በሄድንበት ቦታ ሁሉ እየተከተለ፣ የህሊና-ውጋት (guilt) እንደሚሆንብን አንርሳ! በሥልጣን ላይ ስንሆን ወደ እኛ የሚጠቁሙ ስህተት ፈላጊ ጣቶች አያሌ ናቸው፡፡ Fault-finder society እንደሚሉት ነው፡፡ ስለዚህም ራሳችንን ነጭ ወረቀት ላይ እንዳለ ነጥብ ቆጥረን፣ ከህዝብ ዐይን መሠወር እንደማንችል እናስብ! ያለፈው መንግሥት፤ “ከሠፊው ህዝብ እሰወራለሁ ብሎ ማሰብ፣ ግመል ሠርቆ እንደ ማጎንበስ ነው” ይል ነበር፡፡ አሊያም እንደ ሰጎኗ አልታየሁም ብሎ አንገትን አሸዋ ውስጥ መቅበር ይሆናል፡፡
አንድ ህዝብን ለመምራት ሥልጣን የያዘ ሹም፤ ከሁሉም በላይ ወቃሽና ከሳሹ ህሊናው ነው። ቀጣዩ ወቃሽና ከሳሽ የታሪክ መዝገብ ነው፡፡ ይህንን አስምሮ የማይጓዝ ባለሥልጣን፤ በማን-አለብኝ ይሞላል፡፡ ሁሉን ምንግዴ ይላል፡፡ ብሰርቅ፣ ብመዘብር፣ ህዝብን ብበድል፤ ወንበሬ እስካለ ድረስ የሚነካኝ የለም፤ ብሎ ይኩራራል፡፡ እንዲህ ያለው ሹም ውሎ አድሮ ከአምባገነንነት ሰፈር እንደማይወጣ ታሪክ ያሳየናል፡፡ መውጣት እንዳለ ሁሉ መውረድ እንዳለ ግን አሁንም ታሪክ በየዘመኑ ሲያሳየን ከርሟል፡፡ ያንን ልብ ማለት ከብዙ መዘዝ ያድናል፡፡ ሥልጣን ጣፋጭ ሰዓት እንዳለው ሁሉ፣ መራራ ቀንም አለው፡፡ የሥልጣን አሳሳች ባህሪ (intriguing nature) እስከ መጨረሻዋ የመውደቂያችን ደቂቃ የማንወድቅ መምሰሉ ነው፡፡ ይህን የተገነዘበ የፖለቲካ ሰው፣ በብልህነት እየታረመ ይጓዛል፡፡ እያንዳንዷን እርምጃውን በህዝብ ፍቅር ይለካል፡፡ በሀገር ጥቅም ይመዝናል፡፡ ከቶውንም የሥልጣን ዘመናችንን፣ በራስ በመተማመን ዘዴ መምራት፣ በሌሎች ላይ ተማምኖ ስህተት ላይ ከመውደቅ ያድናል፡፡ በሌሎች ሀብት መመካት፣ በሌሎች ጭንቅላት ማሰብ፣ በሌሎች ጥላ ስር ለመኖር መሞከር፣ ራሳችን ባላፈራነው ድል መኩራራት፣ የማታ ማታ ልጓሙን ሲስቡብን መላወሻ ማጣትን ያስከትላል፡፡ ይህን ቆም ብሎ አለመመርመርና የሌለንን አቅም ያለን ማስመሰል፤ አባዜው መቶ ከአምሳ ነው፡፡ “አውራ ዶሮ፤ በሰው ስጥ ሚስቱን ይጋብዛል” የሚለው ተረት ትርጉም የሚኖረው ይሄኔ ነው፡፡ ራስን ለኃላፊነት ማብቃትና በራስ መተማመንን የመሰለ ኃይል የለም!