Administrator

Administrator

 አሜሪካዊቷ የፖፕ ሙዚቃ አቀንቃኝ ማዶና፣ ከማላዊ በማደጎ ወስዳ እያሳደገቺው የሚገኘው የ12 አመቱ ታዳጊ ዴቬድ ባንዳ፤ ወደፊት የአገሪቱ ፕሬዚዳንት እንደሚሆን ያላትን ጽኑ እምነት መግለጧ ተዘግቧል፡፡
ከምታሳድጋቸው ስድስት የማደጎ ህጻናት መካከል አንዱ የሆነው ማላዊው ዴቪድ ባንዳ፣ እጅግ የሰላ አስተሳሰብና የአእምሮ ብቃት የተላበሰ ታዳጊ እንደሆነ ከሰሞኑ በትዊተር ድረገጽዋ ላይ በጻፈቺው ጽሁፍ የጠቆመቺው ማዶና፤ ለወደፊት እድሜው ሲገፋ አገሪቱን በብቃት የሚመራ ታላቅ ሰው እንደሚሆን በጽኑ አምናለሁ ማለቷን ቢቢሲ ዘግቧል፡፡
ዴቪድ ባንዳን ጨምሮ ከማላዊ አራት ህጻናትን በማደጎ ወስዳ እያሳደገች እንደምትገኝ የጠቆመው የቢቢሲ ዘገባ፤ ከ12 አመታት በፊት ባቋቋመቺው ሬዚንግ ማላዊ የተሰኘ ግብረ ሰናይ ድርጅት አማካይነት የተለያዩ ድጋፎችን እያደረገች እንደምትገኝም አውስቷል፡፡
የአገሪቱ መንግስት ከ5 አመታት በፊት ማዶና በአለም አደባባይ ለአገራችን የምታበረክተውን አስተዋጽኦ ከሚገባው በላይ አጋንና በመናገር ላይ ናት በሚል ወንጅሏት እንደነበርም ዘገባው አስታውሷል፡፡

 በደራሲ አንድነት ሀይሉ የተዘጋጀው “ቋንቋ እውቀት አይደለም” የተሰኘ መፅሐፍ ሰሞኑን ለንባብ በቃ፡፡ ደራሲው፤ “ሁሉም ሰው ውስጥ ሁሉም ቋንቋ አለህ ቋንቋ አለህ ቋንቋ እውቀት አይደለም፤ እውቀት ግን ቋንቋ ነው፡፡ ቋንቋ ሀገር አይደለም፤ ግን እውቀት ግን ሀገር ነው” ይላል- ደራሲው በመፅሐፉ፡፡
በዚህ መፅሐፍ ውስጥ ከተነሱ አያሌ ርዕሰ ጉዳዮች መካከል”የብሄር ጭቆና ምንድ ነው ብሄርስ ምንድ ነው?”፣ “ቱሪዝምና ቋንቋ”፣ “ትምሀርትና ቋንቋ የሚሉት ይገኙበታል፡፡ በ151 ገፆች የተቀነበበው መፅሐፍ በ50 ብር ለገበያ ቀርቧል፡፡

  የ“ወይዘሪት ምድረ ቀደምት” የቁንጅና ውድድር ይደረጋል

   የኢትዮጵያ ብሔር ብሔረሰቦች እርስ በእርስ ይበልጥ ይተዋወቁበታል የተባለለትና አዲሱ የኢትዮጵያ ቱሪዝም መለያ የሆነውን “ምድረ ቀደምት”ን ለማስተዋወቅ ያለመው “ኢትዮ አፍሪካ ካርኒቫል” በግንቦት ወር የመጀመሪያው ሳምንት ላይ እንደሚካሄድ ተገለፀ፡፡
 የኢትዮጵያ የባህልና ቱሪዝም ሚኒስቴር፣ አዲስ አበባ ባህልና ቱሪዝም ቢሮና የኢትዮጵያ ቱሪዝም ድርጅት፣ ከዘጠኙ ክልሎች እንዲሁም ከአይጂ ኢንተርቴይመንትና ከብርሀን ኤቨንት ኦርጋናይዘር ጋር በጋራ በሚያካሂዱት በዚህ ካርኒቫል የ”ምድረ ቀደምት” ሞዴል ሆና በዓለም ብራንዱን የምታስተዋውቅ አምባሳደር ለመምረጥ “የወይዘሪት ምድረ ቀደምት” የቁንጅና ውድድር እንደሚካሄድ ታውቋል፡፡ ክልሎች ለመጨረሻ ዙር ያለፉ አምስት አምስት አሸናፊዎችን ወደ አዲስ አበባ በመላክ የሚያወዳድሩ ሲሆን አሸናፊዋ “ወ/ሪት ምድረ ቀደምት” ሆና እንደምትሾምና ፖስተሯ ተሰርቶ ለአለም እንደምትተዋወቅ፣አዘጋጆቹ ከትላንት በስቲያ ረፋድ ላይ በባህልና ቱሪዝም ሚኒስቴር በሰጡት ጋዜጣዊ መግለጫ ጠቁመዋል፡፡
በዚህ የካርኒቫል ሳምንት “ምድረ ቀደምት አገር ኢትዮጵያ በመወለዴ እኮራለሁ” በሚል መሪ ቃል፣ምድረ ቀደምት ሎጎ የታተመበት ቲ-ሸርት የለበሱ 10 ሺህ ያህል ሰዎች የእግር ጉዞ እንደሚያደርጉም ተገልጿል፡፡ ለሶስት ቀናት የሚቆይ ባዛርና ኤግዚቢሽንም የካርኒቫሉ አንዱ አካል እንደሚሆን የተነገረ ሲሆን በዚህ ባዛር ላይ ብሔር ብሔረሰቦች ምርታቸውን፣ ባህላዊ ምግባቸውን፣ አልባሳትና የንግድ ሥራቸው ለእይታ የሚያበቁበትና ልምድ የሚለዋወጡበት እንደሚሆንም ታውቋል። የመንገድ ላይ ትርኢትን በሚያካትተው በዚህ ካርቪናል፤የተለያዩ ብሔር ብሔረሰቦች ዳንሶቻቸውንና ባህላዊ ጭፈራዎቻቸውን ለተመልካች ያቀርባሉ ተብሏል፡፡ በዚህ የጎዳና ላይ ትርኢት ሥራቸውን እንዲያቀርቡ ሌሎች የአፍሪካ አገራትም እንደሚጋበዙ የተገለፀ ሲሆን በስፔይን አገር በየዓመቱ የሚካሄደው “ሮቶቶም” የተባለው የሬጌ ፌስቲቫል ወደ ኢትዮጵያ መጥቶ፣በምሽቱ በሚያቀርበው የሬጌ ኮንሰርት  ካርኒቫሉ እንደሚዘጋ ለማወቅ ተችሏል፡፡

   (ከሣህለ ሥላሴ ብርሃነ ማርያም)
          ርዕስ፡- መልህቅ
          ደራሲ፡- ዘነበ ወላ
        የሕትመት ዘመን፡- 2010 ዓ.ም
        የትረካ ሥፍራዎች፡ - ምጽዋ ፥ አስመራ ፥ አሰብ ፥ እና አዲስ አበባ በጨረፍታ
        የገጽ ብዛት፡- 448
        ዋጋ፡- 150 ብር


    ይህ መጽሐፍ ልብ ወለድ ነው እንዳንል ጥናት ላይ እንደተመሰረተ ጽሁፍ ዋቢ መጻህፍት ታክለውበታል፤ ያውም በአማርኛና በእንግሊዝኛ የተጻፉ በርካታ መጻሕፍትና ሌሎችም ምንጮች። በሌላ በኩል እውነተኛ ታሪክ ነው እንዳንል አቀራረቡ የታሪክ ሳይሆን የልብ ወለድ ድርሰት የአጻጻፍ ዘዴን ነው የተከተለው፡፡ ታዲያ የድርሰቱ ዓይነት ምንድነው ብለን እንመድበው? ምናልባት ከደራሲው ዘነበ ወላ ጋር በመስማማት፣ በልብ ወለድ መልክ የቀረበ እውነተኛ ሁነት ነው ብንል አያስኬድም ይሆን?
ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ከተለመደው የልብ ወለድ አጻጻፍ ዘዴ ወጣ ያሉ ፥ የቤተ ሙከራ ዓይነት ጽሑፎች ብቅ ብቅ ማለት መጀመራቸውን እንገነዘባለን፡፡ ልብ ወለዶች ናቸው እንዳንል አጽመ ታሪክ የሌላቸው፤ በውቅር (“ፕሎት”) ወይም በምክንያትና ውጤት ላይ ያልተመሰረቱ፤ ላይ በላይ እንደ አሸዋ በተከመሩ ሁነቶች ላይ ብቻ የተገነቡ ጽሑፎች ከአንድም ሁለት በላይ መከሰታቸው ተስተውሏል፡፡ “መልህቅ” ከእነዚህ አፈንጋጭ መሰል ጽሑፎች አንዱ ይሁን ወይም አይሁን በእርግጠኝነት ለመናገር ያዳግታል፡፡
ለማንኛውም ይዘቱ በደርግ ዘመን (ሥርዓቱ ተንኮታኩቶ ከመውደቁ ቀደም ባሉት ሁለት ዓመታት) በአስራ አምስቱ ዓመታት ውስጥ በኢትዮጵያ ባህር ኃይል አካባቢ የነበረውን የሕይወት ሁኔታ አጉልቶ የሚያሳይ መጽሐፍ ነው፡፡ በባህር ኃይሉ የነበሩት የጦር መርከቦች ዓይነት፤ የባህረኞቹ (የአዛዦቹና የታዛዦቹ) የሕይወት ዘይቤ፤ የዕለት ተዕለት የተግባር እንቅስቃሴአቸው፤ የቅኝታቸው ጉዞና መልስ፤ የባህሩ መናወጥና መልሶ መርጋት፤ በተለይ በጉዞ ላይ የሚደርሱ ፈተናዎች፤ የየዕለቱ ምግብና መጠጥ፤ አልፎ አልፎ የሚከናወኑት የመዝናኛ ዝግጅቶች፤ የባህረኞች (በተለይም የወጣቶቹ) የወሲብና የፍቅር ሕይወት፤ የአብዮቱ ዘመን ይፈጥረው የነበረው ፍርሃትና ጭንቀት፤ አንዳንድ ባህረኞች ሥርዓቱን መሸከም አቅቷቸው ወደ ባዕድ አገር ለመሰደድ የሚያደርጉት ሙከራ፤ የተፈጥሮ አስደናቂ ክስተቶች፤ በተለይም የአንዳንድ አሳዎች፥ የየብስ ተንፏቃቂ ነፍሳትና አእዋፍ አስገራሚ የሥጋ ተራክቦና የሚከተለው የሕይወት ሕልፈት፤ የአሳዎች ዝርያዎች ዓይነትና ባህርያቸው፤ በአጠቃላይ በባህርና በየብስ የባህረኞችና የሌሎች ፍጡራን ሕይወት ምን እንደሚመስል ፍንትው አድርጎ የሚያሳይ መጽሐፍ ነው - “መልህቅ”፡፡
ዘነበ ወላ በዚህ መጽሐፉ ከቀድሞዎቹ ሦስት መፅሐፎቹ (ህይወት በባህር ውስጥ ፥ ማስታወሻ ፥ እና ልጅነት) በበለጠ ደረጃ ጥንካሬ ያሳየው በገለጻ ኃይሉ ነው ብንል ሞጋች የሚነሳ አይመስለኝም፡፡ ዋቢ እንዲሆን ቀጥሎ ያለውን እንመልከት፤
“ወደ ራስ ዱሜራ ስንቀዝፍ ቀይ ባህር እንደ ራስ ዳሽን ተራራ ይከመራል፡፡ ጀልባችን ባህሩን በርቅሳው ለማለፍ ትጥራለች፡፡ ባህሩ አፍታም ሳይቆይ እንደሊማሊሞ ገደል ይናድና ቁልቁል ወደ መቀመቅ ጅው እንላለን፡፡ ከላይ ውሃ እንለብሳለን፤ ከስር ውሃ መቀመቅ ውስጥ እንሰጥማለን…” (ገጽ 10)
ተጨማሪ ምሳሌ ቢያስፈልግም እነሆ፤
“7,000 የፈረስ ጉልበት የሚያመነጨው የጀልባዋ ሞተር እንደ አንዳች ያጓራል፡፡ ማዕበሉን ሰንጥቆ ለማለፍ የጀልባዋ መቅዘፊያዎች እንደ አንዳች ይሽከረከራሉ፡፡ ባህሩ ተበርግዶ እልም ያለ ገደል ይፈጥራል፡፡ ጀልባዋን ሙሉ በሙሉ ይውጣትና መልሶ ተጉመጥምጦ እንደተፋት ሁሉ ባህሩ ደረት ላይ ትገኛለች፡፡ ቀይ ባህር ካለው ጥልቀትና ስፋት አኳያ 118 ቶን የሚከብደው የጀልባዋ አካል የቡሽን ያህል አትከብደውም፡፡ ከማዶ እንደ ጥቀርሻ የጠቆረ የባህር አካል ተንደርድሮ መጥቶ ይላተመዋል። እሷም እንደ ሰይፍ ሰንጥቃው ወደፊት ትመነጨቃለች፡፡ አንዳች ዓይነት የቁጣ፥ የመዓት ድምጽ በድፍን ባህሩ ላይ ያስተጋባል” (ገጽ 104)
የመጽሐፉ ባለታሪኮች በርካታ ናቸው። በይበልጥ ጎልተው የሚታዩት ግን ከወንዶቹ መሐከል ያሬድ ሐጎስ፥ ስንታየሁ፥ በብዙ ቦታ ባናየውም ሊረሳ የማይቻለው ሌናተናንት አሸናፊ ዋቅጅራ (የጀልባ 202 አዛዥ)፤ ከሴቶች መሐከል ደሞ ገነት አስገዶም፥ ዓወት ግርማይ ፥ እና ኮማሪቷ አበባ አድማሱ ይገኙባቸዋል፡፡ እነዚህ የመጽሐፉ ባለታሪኮች በገሐዱ ዓለም የነበሩ ይሁኑ ወይ ደሞ የፈጠራ ገጸ ባህሪያት ይሁኑ አንባቢው ለይቶ ለማወቅ ከቶም አይቻለውም፡፡ ነገር ግን የፈጠራ ታሪክ ገጸ ባህሪያት ከሆኑ በገሐዱ ዓለም ሞዴል እንዳላቸው ሊያጠራጥር አይችልም፤ ታሪኩ በእውነተኛ ሁነት ላይ የተመሰረተ ነው ስለተባለ፡፡
ለመሆኑ የመጽሐፉ ዓላማ ምንድነው? የገጸ ባህርያቱን ስሞች ስናጤን እያንዳንዳቸው ከየት ብሔረሰብ እንደፈለቁ ይጠቁሙናል፡፡ ከሁለት የተለያዩ ብሔረሰቦች የተፈጠሩም አሉ። ነገር ግን ሁሉም ለማለት ይቻላል እንደ ውሁድ ኢትዮጵያውያን ይተያያሉ እንጂ የብሔረሰብ ማንነታቸውን ከቁም ነገር ሲያስገቡ አናይም፡፡ ትንሽ ያፈነገጠ አመለካከት ያላቸው ቢኖሩ ከሰሜን ጫፍ በኩል ያሉት ብቻ ናቸው፡፡
በትረካው መጨረሻ አካባቢ ሌፍተናንት አሸናፊ ወደ ሱማሌ ከመኮብለሉ በፊት የፈጸመው ድርጊት አንባቢውን ግራ ያጋባዋል፡፡ መርከበኞቹ ከመርከቡ ዘልለው ወርደው ባህር ውስጥ እንዲገቡ ያዝዛቸዋል። እነሱም በዋና ነፍሳቸውን ለማዳን ሲጥሩ ይታያሉ፡ የሞቱት ሞተው የተቀሩት ይተርፋሉ፡፡ ግን የሌተናንት አሸናፊ ድርጊት ምን ትርጉም አለው? እነዚህ መርከበኞች በእሱ ስር ሆነው የሚያገለግሉ ናቸው፡፡ በደል ሰርተውበት እንደሆነ የተነገረ ነገር የለም፡፡ ነገር ግን ለከፋ አደጋ አጋልጧቸው መኮብለሉ ትርጉሙ ምንድን ነው? ነገሩ እንቆቅልሽ ይሆንብናል፡፡
የእነዚህ መርከበኞች ዕጣ ፈንታ ይህ ብቻ ቢሆን ኖሮ ቢያሳዝንም “መቼስ ምን ይደረጋል!” ተብሎ ሊታለፍ ይችል ነበር፡፡ ነገር ግን በዚህ ጦስ ምክንያት ባልፈጸሙት ወንጀል ተከስሰው ለፍርድ ሲቀርቡ እናያለን፡፡ እነሱ የአዛዣቸው ሰለባ ከመሆን በስተቀር አንዳችም የፈጸሙት ወንጀል የለም፤ ያሬድ ሀጎስ ቀደም ብሎ ለመሰደድ ያደረገው ያልተሳካ ሙከራ እንዳለ ሆኖ፣ ታዲያ ለምንድነው ለፍርድ የቀረቡት? ምክንያቱን ለመረዳት አሁንም ከመጽሐፉ መጥቀስ ግድ ይላል፤
“የኢትዮጵያ አብዮተኞችም እንዲሁ ራሳቸውን ከወንጀል ለማጽዳት ባለፉት አስራ አምስት ዓመታት የቀጠለውን የጦስ ፍየል መስዋዕት የማድረግና ማርከሻውን መፈክር አሰምቶ የማለፍ ልምድ፤ ዛሬ የጦስ ፍየል አራጁ የነገ ተረኛ እየሆነ ሞትን በቅብብሎሽ አኖሩት፡፡ ይህ የጦስ ፍየል ከምድር ጦር ፥ ከአየር ኃይል ፥ ከባህር ኃይል ፥ ከሲቪሉ ሕብረተሰብ እየታደነ የአብዮታዊያኑን ጦስና ጥንቡሳስ ይዞ ይገደልና በሟች ሬሳ ላይ መፈክር ይሰማል፡፡ ዛሬም ያሬድና ጓደኞቹ ባልሰሩት ወንጀል እንደ ወንጀለኛ ታፍነው ደህንነት ቢሮ በመገኘታቸው የጦስ ፍየል ሊያደርጓቸው መወሰኑ ወለል ብሎ ታየው፡፡” (ገጽ 440)
ስለ አስራ ሰባቱ ዓመታት የጨለማ ዘመን በርካታ ልብ ወለዶችና ኢ - ልብ ወለድ መጻሕፍት ከዚህ ቀደም ተጽፈዋል፤ የበዓሉ ግርማ “ኦሮማይ”፥ የአማኑኤል ሐዲስ “አስተኳሹ”፥ የባቢሌ ቶላ “የትውልድ ዕልቂት” (አውግቸው ተረፈ እንደተረጎመው) እና ሌሎችንም ለመጥቀስ ይቻላል። “መልህቅ” ከእነዚህ አንዱ መሆኑ ነው፡፡ የአብዮቱ ዘመን ታሪክ በእነዚህ ብቻ ሊወሰን የሚችልም አይደለም፡፡ አሳታሚ በማጣት በየጠረጴዛው ኪስ ውስጥ ተዘግቶባቸው የሚኖሩ ልብ ወለዶችና ኢ - ልብወለድ መጻሕፍት እንዳሉ በቀላሉ መገመት ይቻላል፡፡ ከድርጊቶቹ አስከፊነት የተነሳ ዛሬ ብቻ ሳይሆን ወደፊት ከአምሳና መቶ አመታት በኋላም በታሪካዊ ልብ ወለድ መልክ ሌሎች በርካታ መጻሕፍት እንደሚዘጋጁ ለመገመት ነቢይ መሆን አያሻውም፡፡     

    ከየካቲት 9 ቀን 2010 ዓ.ም ጀምሮ ለሚቀጥሉት 6 ወራት በአገሪቱ ላይ የተጣለውን የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ዓለም አቀፉ ማህበረሰብና የምዕራብ መንግስታት፣በጥርጣሬና በስጋት ነው የተቀበሉት፡፡ የአሜሪካ መንግስትና የአውሮፓ ህብረትም፤አስቸኳይ ጊዜ አዋጁን አስመልክቶ ያወጡት መግለጫ ከወትሮው የተለየ ነው፡፡  
አዋጁን በፅኑ የተቃወመው የአሜሪካ መንግስት በኤምባሲው በኩል ባወጣው መግለጫ፤ “የኢትዮጵያ መንግስት በተለይ በመሰብሰብና ሀሳብን በነፃነት በመግለጽ መብት ላይ ገደብ የሚጥለውን የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ማወጁ፣ከቅርብ ጊዜ ወዲህ የተፈጠረውን ሁሉን አሳታፊ የሆነ የለውጥ መነሳሳት የሚያቀጭጭ፣ ይሰፋል ተብሎ በተስፋ የሚጠበቀውን የፖለቲካ ምህዳርም የበለጠ የሚያጠብ ነው” ብሏል፡፡   
 “የተፈጠሩት ሁከቶችና ብጥብጦች የሰው ህይወትን እየቀጠፉ እንደሆኑና በዚህም መንግስት ጭንቀት ውስጥ መግባቱን እንገነዘባለን” ያለው ኤምባሲው፤“ሆኖም ለዚህ አይነቱ ችግር መፍትሄው  መብትን መገደብ ሳይሆን የበለጠ ነፃነትን መፍቀድ ነው” ብሏል -የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁን መውጣት አጥብቆ እንደሚቃወመው በመግለጽ፡፡
የአውሮፓ ህብረት በበኩሉ፤መንግስት የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ማወጁ እየተካሄደ ያለውን የፖለቲካ ማሻሻያ በእጅጉ የሚጎዳ ነው ብሏል - በመግለጫው፡፡  
“አዋጁ መልካሙን ጅምር ሊያጠፋው ይችላል፤ከተቻለ የአጭር ጊዜያት ቆይታ ይኑረው” ሲልም ለመንግስት ምክር ለግሷል - ህብረቱ፡፡  
አዋጁ በሚተገበርባቸው ጊዜያት መሰረታዊ የሰብአዊ መብቶች እንዲከበሩና መሰረታዊ መብቶች እንዲረጋገጡ የአውሮፓ ህብረት የጠየቀ ሲሆን ለሀገሪቱ ሁነኛ የፖለቲካ መፍትሄ ሊሆን የሚችለው ከተቃዋሚዎችና ከሀገሪቱ የፖለቲካ ተዋናዮች ጋር የሚደረግ  ውይይት ነው ተብሏል፡፡
በኢትዮጵያ የኔዘርላንድ አምባሳደር ቤንት ቫን በሰጡት አስተያየት፤አዋጁ የሰብአዊ መብቶችን እንዳይገድብ ስጋት አለን ብለዋል፡፡ የአዋጁ የቆይታ ጊዜ ማጠር የሚችልበት ሁኔታም መመቻቸት እንዳለበት ጠቁመዋል፡፡
“ጠቅላይ ሚኒስትሩ ስልጣን ለመልቀቅ መወሰናቸው በበጎ የሚታይ ቢሆንም የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ የዜጎችን የመናገር፣ የመሰብሰብና ሃሳብን የመግለፅ መብቶች የሚገድብ በመሆኑ ያሳስበኛል” ያለው ደግሞ የእንግሊዝ መንግስት ነው፡፡  
አዋጁ ለአጭር ጊዜ ብቻ ይተገበራል የሚል ተስፋ አለኝ ያለው የእንግሊዝ መንግስት፤ “በዚህ ጊዜ ውስጥም ቢሆን መንግስት መሰረታዊ የዜጎችን ሰብአዊ መብቶች ያከብራል የሚል እምነት አለን” ብሏል፡፡ “በአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ ወቅትም ሰዎችን በጅምላ ማሰርና ኢንተርኔትን ማቋረጥ ሊተገበር አይገባም” ሲል አሳስቧል - የእንግሊዝ መንግስት የአፍሪካ ጉዳዮች ሚኒስቴር ባወጣው መግለጫ፡፡
“የኢትዮጵያ መንግስት ሰላማዊ፣ ፈጣንና ግልፅነት በተሞላው መንገድ የለውጥ ሂደቱን ለማስቀጠል አዲሱን ጠቅላይ ሚኒስትር ይመርጣል ብለን ተስፋ እናደርጋለን” ያለው መግለጫው፤ “ስለ ወዳጅነታችንም ለኢትዮጵያውያን እርዳታችን አይለይም” ብሏል፡፡
በሌላ በኩል ከተለያዩ የዓለም ሀገራት አምባሳደሮች ጋር በአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ ላይ ሰሞኑን ውይይት ያደረጉት የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ ዶ/ር ወርቅነህ ገበየሁ፤”አዋጁ ሀገሪቱ የገጠማትን የሰላምና መረጋጋት ችግር ለመፍታት የተዘጋጀ ነው፣ ተግባራዊ ከተደረገ ወዲህም የሀገሪቱ ሁኔታ መሻሻል አሳይቷል” በማለት የአዋጁን ጠቀሜታ ለዲፕሎማቶቹ አስረድተዋል፡፡   

 ከዕለታት አንድ ቀን አንድ እረኛ በጎቹን እየጠበቀ ሳለ፣ አንድ ሀሳብ መጣለትና ከፍ ወዳለው ኮረብታ ወጣ፡፡
ከዚያም፤ “ተኩላ! ተኩላ! በጎቻችንን ሊጨርስ መጥቷል፡፡ ቶሎ ድረሱ!” ሲል ለመንደሩ ህዝብ ጮኸ፡፡
መንደሬው ጦር ያለው ጦሩን፣ ቆንጨራ ያለው ቆንጨራውን፣ ዱላ የያዘ ዱላውን ይዞ እየሮጠ ኮረብታውን ወጥቶ ወደ ግጦሹ ሜዳ ሄደ፡፡
“የታለ፣ ተኩላው?” ብለው ጠየቁት፡፡
“ተኩላውማ ወደ እናንተ ስጮህ ሰምቶ ሸሸ!” አላቸው፡፡
መንደሬዎቹ አመለጠን ብለው እየተናደዱ ተመለሱ፡፡
ከአንድ ሳምንት በኋላ ያ እረኛ እንደገና ወደ ኮረብታው ይመጣል፡፡
ከዚያም፤
“ተኩላ! ተኩላ! ያ ተኩላ በጎቻችንን ሊበላ መጥቷል፡፡ ድረሱልኝ!” አለ፡፡
መንደርተኞቹ፤
“ዛሬስ አያመልጠንም! በታችም በላይም መውጫ መግቢያውን እንዝጋበት፤ የትም አይጠፋም!” እያሉ በግሪሳ መጡ!”
እግጦሹ ሜዳ ሲደርሱ፤
“የታለ ተኩላው? ዛሬ አንምረውም!” አሉና ጠየቁት፤ እረኛውን፡፡
እረኛውም፤
“አይ ዛሬ እንኳን ማ ለችግሬ እንደሚደርስ፣ ማ እንደማይመጣ፣ ማ ለበጎቹ እንደሚጨነቅ፣ ማ እንደማይጨነቅ፣ ለመለየት ብዬ ነው እንጂ ተኩላው አልመጣም! አለና መለሰ፡፡
መንደርተኞቹ፤ እየተናደዱና በእረኛው እያማረሩ ወደየቤታቸው ተመለሱ፡፡
በሶስተኛው ሳምንት በእርግጥም ተኩላው መጣ!
እረኛው እየሮጠ፣ እያለከለከ ወደ ተራራው ወጣ፡፡
“ተኩላ! ተኩላ! ዛሬ የምሩ ተኩላ መጥቷል፡፡ በጎቻችሁ እንዳይበሉ በነብስ ድረሱ!” አለ፡፡ ማን ይስማው? ማንም ሰው ሳይመጣ ቀረ! ተኩላው በነፃነት የሚችለውን ያህል በግ ቅርጥፍ አድርጎ በላና ሄደ፡፡
*        *      *
“ዋዛ ፈዛዛ ልብ አያስገዛ” የሚባለው ለዚህ ነው፡፡ ውሸት ሆነው ሲደጋገሙ ዕውነት የሚመስሉ፣ ወይም የሚሆኑ አያሌ ነገሮች አሉ፡፡ በእርግጥ ደግሞ የሂትለር ዋና ፀሐፊ ጎብልስ፤ “አንድን ውሸት ደጋግሞ በመናገር ወይም በማስነገር ዕውነት ለማድረግ ይቻላል” የሚለውንም አንዘነጋም! ህብረተሰብ በእጅጉ ባልነቃበት አገር፤ ውሸትን ዕውነት ለማስመሰልም ሆነ ዕውነትን ውሸት ለማስመሰል መሞከር አያስገርምም! ፖለቲካ ብዙ የማስመሰል ጥበብ አለበት፡፡ ሀሳዊውን ፖለቲከኛ ከሀቀኛው መለየት የህዝብ ኃላፊነት ነው! በዘልማድ “እገሌ ክፉኛ ይቦተለካል” ማለት፤ ሸፋጭ ነው፣ ቀጣፊ ነው ማለት ነው፡፡ ምናልባት Politics is a dirty game የተባለው ለዚህ ሳይሆን አይቀርም፡፡ በእርግጥም ፖለቲካ አስቀያሚ ጨዋታ ነው፡፡ በፖለቲካ ይሉኝታ የለም። ያም ሆኖ በፖለቲካው በዚህ መንገድ ብሄድ ያዋጣኛል አያዋጣኝም ብሎ መጠየቅ፤ የብልህ እርምጃ ነው፡፡ ትላንት ያሉትን ሽምጥጥ አድርጎ መካድ ፖለቲካ ነው፡፡
ፖለቲካ ለሱ መፈጠርን ይጠይቃል፡፡ ምሁር ወይም የሙያ ሰው ለፖለቲካ አይሆንም፤ የሚባለው ከዚህ መሰረታዊ የፖለቲካ ባህሪ በመነሳት ነው፡፡ ዞሮ ዞሮ ግን በየትኛውም የፖለቲካ ጎራ እንሰለፍ፣ የሀገርና የህዝብን ጥቅም ለማስጠበቅ መቆም የሀቀኛ ፖለቲከኛ ተግባር መሆን አለበት፡፡
ከፖለቲከኝነት ጋር ሳይነጣጠል እጅ ለእጅ ተያይዞ የሚጓዝ አንድ አባዜ አለ - ሙስና! ይህ አባዜ በተለይ በአፍሪካ መሪዎች ዘንድ እንደ ማተብ የሚጠለቅ፣ እንደ ዳዊት የሚደገም የዕለት የሰርክ ፀሎት ነው! “የዕለት እንጀራዬን አታሳጣኝ” ወደ “የዕለት ሙስናዬን አታሳጣኝ” ተለውጧል! “ሲሾም ያልበላ ሲሻር ይቆጨዋል” የሚለው ተረት፤ የባለስልጣኑ መሪ - መፈክር ሆኗል፡፡
በሙስና የተሰራው ህንፃ አፍ ቢኖረው ስንቱን ባጋለጠ ነበር፡፡ የታጠረም ሆነ ያልታጠረ አጥር አፍ ቢኖረው፣ ስንቱን ጉድ ባደረገ ነበር፡፡ ወገናዊነት መናገር ቢችል ኖሮ፣ ስንቱን ግፍ ባስረዳን ነበር፡፡ ዲሞክራሲ አፍ ቢኖረው ኖሮ፣ ስንቱን ሀሳዊ ዲሞክራት አፉን ባስዘጋ ነበር፡፡ ፍትህ ርትዕ አንቀፅ መጥቀስ ቢችል ኖሮ፣ ስንቱን ኢ-ፍትሐዊ ድርጊት ባደባባይ ባጋለጠ ነበር፡፡ ሀገራችን ገና ብዙ መንገድ ይጠብቃታል። ማደግ ያለበት መለወጥ ያለበት፣ መቀልበስ ያለበት አያሌ ጉዳይ ይጠብቃታል፡፡ ይህን መፈፀም ያለባቸው ከየጎራው ያሉ አካላት በሙሉ ፈቃደኝነትና ቆራጥነት ዝግጁ መሆን አለባቸው፡፡ አፋቸው ሌላ ልባቸው ሌላ የሚያስብ ከሆነ ግን “ጅብ፤ ጥጃ ጠብቅ” ቢባል፤ “ቢጠፋብኝስ?” አለ፤ እንደተባለው ይሆናል!  

  • አሁን የሚያስፈልገን የአስቸኳይ ጊዜ አንድነትና ፍቅር ነው
      • ማረሚያ ቤት መታረሚያ ቦታ እንጂ መሰቃያ መሆን የለበትም
      • የጋዜጠኝነት ሙያ እዚህ የደረሰው በጋዜጠኛው ብርታት ነው
      • የሽብርን አስከፊነት እኛ ኢትዮጵያውያን አሳምረን እናውቀዋለን

     ከሰሞኑ ከእስር ከተፈቱት ግለሰቦች መካከል አንዱ የሆነው ጋዜጠኛ ውብሸት ታዬ፤ለ7 ዓመት በእስር ቤት በነበረው ቆይታ፣ በጋዜጠኝነት ሙያው፣ በሀገሪቱ ፖለቲካዊ ሁኔታና ተያያዥ ጉዳዮች ዙሪያ ከአዲስ አድማስ ጋዜጠኛ አለማየሁ አንበሴ ጋር ተከታዩን ቃለ ምልልስ አድርጓል፡፡

     በሽብር ወንጀል ተጠርጥረህ የታሰርክበት አጋጣሚ እንዴት  ነበር?
የታሰርኩት ሰኔ 12 ቀን 2003 ዓ.ም ነው። ሁኔታዎች በጣም እየተወሳሰቡ የመጡበት ወቅት ነበር፡፡ ምናልባት በወቅቱ እፅፋቸው በነበሩ መጣጥፎች  ላይ በስፋት ፀረ ሽብር ህጉን እተች ነበር፡፡ ፀረ ሽብር ህጉ በጣም ከባድ መሆኑንና አሳሳቢ መሆኑን ለማመላከት የአቅሜን እጥር ነበር። ፖለቲካዊ ሁኔታዎች ደግሞ እየተካረሩ የመጡበት ሁኔታም ነበር፡፡ በዚህ ምክንያት እንዲሁ የሆነ ነገር ሊፈጠር እንደሚችል እገምት ነበር፡፡ በኋላ ሰኔ 12 ቀን የጋዜጣ ኤዲቶሪያል ስብሰባ ነበረኝ፡፡ ወደ ቢሮ ስሄድ ብዙ ሰዎች ይከተሉኝ ነበር፡፡ በወቅቱ የሆነ ችግር እንዳለ ገምቼ፣ እኔም ሁኔታውን በጥንቃቄ እከታተል  ነበር፡፡ በኋላ ወደ ኢንተርኔት ካፌ ገባሁና ሊሲፒጂኤ እና ለጋዜጠኛ ማህበራት ስለ ሁኔታው በኢ-ሜይል አሳወቅሁኝ፡፡ የጠረጠርኩት አልቀረም፣ እዚያው ኢንተርኔት ቤት እያለሁ፣ ብዙ የፌደራል ፖሊስ አባላትና ተሽከርካሪዎች መጥተው ያዙኝ፡፡ በወቅቱ በሁኔታው ተገርሜ ነበር፡፡ ምናልባት ሄሊኮፕተር ነው የቀረው እንጂ የተሽከርካሪና የፖሊሶችን ብዛት ላየ፣ አንድ በእጁ ብዕርና ወረቀት የያዘን ጋዜጠኛ ለመያዝ አይመስልም፡፡ እኔ በህይወቴ መሳሪያ የሚባል ነገር ነክቼ አላውቅም፡፡ ግን ሁኔታውን ለተመለከተ፣ መሳሪያ የያዝኩ ነበር  የሚመስለው። በኋላም ቤቴ ተፈተሸ፡፡ በሽብር ተጠርጥረህ ነው ተባልኩ፡፡ ይሄን ሲሉኝ፣ ቀልድ ነበር የመሰለኝ፤ በኋላ ቤቴ ተፈትሾ፣ ከ4 በማያንሱ ፌስታሎች፣ ወረቀቶችና የተለያዩ መንፈሳዊ ፊልሞች እንዲሁም ካሴቶች በሙሉ ተወሰዱ፡፡ እኔ ቤት ውስጥ ከመዝሙርና ከመንፈሳዊ ፊልሞች ውጪ ምንም የለም፡፡ እነሱም በኋላ ይሄን ሲረዱ፣ የወሰዱትን በሙሉ ለባለቤቴ መልሰውላታል፡፡  ይሄን የቤት ውስጥ ብርበራ ሲያደርጉ፣ እስከ ዛሬ ከህሊናዬ የማይጠፋው፣ ሁለት እጆቼ በካቴና ታስረው፣ ልጄ ሊጠመጠምብኝ እየሮጠ ሲመጣ፣ በድንገት እጄ ላይ ያለውን ሰንሰለት አይቶ፣ የደነገጠው ድንጋጤና መሸማቀቅ ነው፡፡ ልጄ በወቅቱ ፊቴን አያይም ነበር። ገና 2 ዓመቱ ነበር፡፡ ነገር ግን እጄን ነበር አተኩሮ ያይ የነበረው፡፡ ይሄ እስከ ዛሬ አዕምሮዬ ውስጥ የፈጠረው መጥፎ ጠባሳ አለ፡፡ ልጄ “ፍትህ”፤ በልጅነቱ ሳቂታና ተጫዋች ነበር፡፡ አሁን ግን  ዝምተኛና ብዙ የማይናገር ሆኖ ነው ያገኘሁት፡፡ እኔን ለመጠየቅ ሲመላለስም በዝምታ ይመለከተኛል  እንጂ ብዙ አያናግረኝም ነበር፡፡
ማዕከላዊ ከገባህ በኋላ የምርመራ ሂደቱ ምን ይመስል ነበር?
ማዕከላዊ በነበረው ምርመራ ሁሉም ነገር ከመጀመሪያው ነው የሚጀመረው፡፡ አስበሃል ወይ? እያሉ ነው የሚጠይቁት፡፡ እነሱ አስቧል ብለው ለያዙት ሰው እንኳ በቂ መረጃና ማስረጃ የላቸውም። እኔ ለውጭ ሚዲያዎች ስሰራ ሙያዬን ጠብቄ ነበር፡፡ አሁንም ቢሆን ለ8 ወራት ተጠልፈዋል የተባሉትን የስልክ ንግግሮች ለየትኛውም በጉዳዩ ላይ ጥናት ለሚሰራ አካል ለመስጠት ዝግጁ ነኝ፡፡ መደበኛ የመረጃ ልውውጥ፣ ንግግሮችን ነው ሳደርግ  የነበረው፡፡ እነሱ መረጃ አምጣ እያሉ ድብደባ ፈፅመውብኛል፡፡ ብርሃን በሌለውና ሙቀት በሌለው ቤት ውስጥ ለ90 ቀናት እንድቆይ ተደርጌአለሁ፡፡ የኔ እንደውም በምርመራ ሂደት ዓይናቸውን ካጡት፣ የመራቢያ አካላቸውን ከተጎዱት የተሻለ ነው ማለት እችላለሁ፡፡ እርግጥ ነው በድብደባ ብዛት ጆሮዬ ለረጅም ጊዜያት ደም ይፈሰው ነበር፡፡ ከዚያ በተረፈ ስነ ልቦናን የሚጎዱ፣ በብሄር ማንነት ላይ ያተኮሩ ዘለፋዎች ነበሩ፡፡ እኔ የማውቀው ሰው መሆኔን ነው፤ ግን ዘለፋው አዕምሮ ይጎዳ ነበር፡፡ ፍርድ ቤቱ እንግዲህ በኋላ ላይ የሰጠውን ፍርድ ሰጥቷል፡፡
በአንተ የክስ ክርክር ላይ “ኦፕሬሽን” የሚል ቃል እንደ ማስረጃ ቀርቦ ነበር፡፡ እስቲ ስለሱ ንገረን?
ጉዳዩ እንግዲህ አባታችን ታመው እኛ ጋ መጥተው ነበር፡፡ ሃገር ውስጥ ያለሁት ወንድ የቤተሰባችን አባል እኔ ብቻ ስለነበርኩ፣ ህክምናቸውን የምከታተለው እኔ ነበርኩ፡፡ በወቅቱ እሳቸው ኦፕራሲዮን ተደርገው ከውጪ ወንድሜ ይደውልልኝና፤ ”አባታችን እንዴት ናቸው?” ይለኛል። እኔም፤ “አይ አሁን በቃ አታስብ፣ ኦፕሬሽኑን አድርጓል” አልኩት፡፡ ይሄ ቃል የሆነ ኦፕሬሽን ነው ተብሎ ነው፣ የምርመራው አካል ሆኖ የቀረበው፡፡ ሁኔታው ይሄን ይመስላል፡፡ አባታችንም እኔ እስር ቤት ሆኜ፣ ህይወታቸው አልፏል፡፡ ሌሎችም በጣም የተዛቡ ጉዳዮች ነበሩ፡፡ ለዚህ ነው በጉዳዩ ላይ ጥናት ማድረግ ለሚፈልግ መረጃ መስጠት እችላለሁ ያልኩት፡፡ ሌሎች እንደ ማስረጃ የቀረቡብኝ ፅሁፎች ደግሞ አምኜባቸው፣ ሃሳቤን ይገልፁልኛል ብዬ የፃፍኳቸው፣ የምወዳቸው ፅሁፎች ናቸው፡፡ በወቅቱ ምንም ማድረግ ስለማይቻል፣ ፍ/ቤቱ በኛ ላይ ያሳለፈውን ውሳኔ በአክብሮት ተቀብለነዋል፡፡
በወቅቱ የ14 ዓመት እስራት  ይፈረድብኛል ብለህ ጠብቀህ ነበር?
መሬት ላይ ያለውን ሃቅ እንገምግም ከተባለ፣ ሊከሰስ ይገባል ብባል እንኳ መከሰስ የነበረብኝ በሚዲያ አዋጁ መሰረት ነበር፡፡ በመረጃ ልውውጡ ወቅት ሀገሪቱን የሚጎዳ ነገር ተፈጽሟል ከተባለ እንኳ በሚዲያ አዋጁ ነበር ሊታይ የሚገባው። ነገሩን ለጥጠው በሽብር አዋጁ ነው የከሰሱኝ። የሽብርን አስከፊነት እኛ ኢትዮጵያውያን እናውቀዋለን፡፡ በሃይማኖትና በግብረ ገብ ተቀርፀን፣ በእዝነት እንድናድግ ሆነን ነው እኛ ኢትዮጵያውያን ቤተሰቦችን የሚያሳድጉን፡፡ ይሄ ስነ ልቦና ለሽብር ያውም በገዛ ሀገር ላይ ሽብር ለመፈጸም በእጅጉ ሩቅ ነው፡፡ እኔም በወቅቱ በሽብር ተከሰሃል ስባል፣ ከፍተኛ ቅጣት ነው የጠበቅሁት፡፡ እርግጥ አንድም ምስክር አልቀረበብኝም ነበር፡፡ ተከላከል ስባልም ተከላክያለሁ፡፡ ግን ያው 14 ዓመት እስራት ተፈረደ። ፍርዱ ሲሰጥ አስገርሞኛል እንጂ አላስደነገጠኝም ነበር፡፡
የማረሚያ ቤት ቆይታህስ ምን ይመስላል?
እንግዲህ ማረሚያ ቤት የቆየሁት ለ7 አመታት ያህል ነው፡፡ በማረሚያ ቤት መቆየት ብዙ ነገር ለማሰላሰል፣ የጥሞና ጊዜ ለማግኘት ይረዳል። መከራዎች፣ እንግልቶችና መገፋቶች መልካም ነገር ነው የሚያወጡት፡፡ ወተት ሲናጥ ነው ቅቤ የሚወጣው፤ አበባ ሲረግፍ ነው ዛፍ ፍሬ ማፍራት የሚጀምረው፡፡ የማረሚያ ቤት ቆይታዬን በዚህ ነው የምገልፀው፡፡ አብዛኛውን ጊዜዬን ዝዋይ ነው ያሳለፍኩት፡፡ በወቅቱ ጉዳያችን በመላው ህዝብ ዘንድ ትኩረት ማግኘቱ፣ ብዙ ወገን ከጎናችን መቆሙን ስንሰማ፣ የዓለም አቀፍ ማህበረሰብ ስለኛ እየተሟገተ መሆኑን ስንረዳ ተስፋችን ይለመልም ነበር፡፡ በአሉታዊ ጎኑ ደግሞ ምናልባት እኔ ጠንካራ ባለቤት ስላለችኝ ቤተሰቤ እንደነበረ ጠበቀኝ እንጂ በርካታ ቤተሰብ በዚህ ምክንያት ፈርሷል፡፡ እኔም ወላጅ አባቴን ማገዝ ስችል በመታሰሬ ሳላግዘው አጥቼዋለሁ፡፡
በማረሚያ ቤት ህክምና አናገኝም ነበር። በአንድ ወቅት እንደውም የኩላሊት ጠጠር ያመኝ ስለነበር እንድታከም ወደ ሆስፒታል ሪፈር ተፅፎልኝ፣ በማረሚያ ቤት ኃላፊዎች ተከልክያለሁ። ብዙ አስነዋሪ ነገሮች አሉ፡፡ በማረሚያ ቤት የብዙ ሰዎችን መከራ መመልከት ይቻላል፡፡ ድብደባዎች ይፈፀማሉ፡፡ እውነቱን ለመናገር የሚሰማ አካል ካለ፣ ይሄ መመርመር አለበት፡፡ በርካታ ኢትዮጵያውያን በዘፈቀደ የሚቀጠቀጡበት ቦታ እስር ቤት ነው። ማረሚያ ቤት ማለት እኮ መታረሚያ ቦታ እንጂ መሰቃያ መሆን የለበትም፡፡ በድብደባ ብዛት የሞቱ ሰዎች አሉ፡፡ እኔ በመፅሐፌ በዝርዝር ፅፌዋለሁ፡፡ ግን የኢትዮጵያ ሰብአዊ መብት ኮሚሽን የተባለው ተቋም፣ ይሄን እንኳ ለማጣራት ጥረት ሲያደርግ አንመለከተውም፡፡ ራሳቸውን አጥፍተው ሞቱ የሚባሉ የኦነግ ተከሳሹን ኢ/ር ካሳሁን ጨመዳን ጨምሮ በርካቶች አሉ፡፡ ለምን ይሄ ጉዳይ አይጣራም? መጣራት አለበት፡፡ እኔ በብዛት ከእነ ጀነራል አሳምነው ፅጌ ጋር ከሌሎች እስረኞች ተገልለን ነው ታስረን የቆየነው፡፡ ቤተ ክርስቲያን መሄድ አንችልም፣ የካፌ አገልግሎት አናገኝም። ከሌሎች እስረኞች ጋር እንድንገናኝ አይፈለግም ነበር፡፡
ለምንድን ነው እንደዚያ የሚደረገው?
ያው እኛን ለመጉዳት ነው፡፡ የማግለል ስራ ነው የሚሰራው፡፡ ስለ ምግቡ እንኳ ባናነሳው ነው የሚሻለው፡፡፡ እንጀራውና ወጡ ከምን እንደሚሰራ እንኳ አናውቅም፡፡ በጣም አቅምን የሚያዳክም ምግብ ነው፡፡ በአብዛኛው ያለ ምግብ ነው የኖርነው ማለት ይቻላል፡፡
እዚያው እስር ቤት ሆነህ ሁለት መፅሐፍትን አሳትመሃል፡፡ እንዴት ነው የተሳካልህ?
የሰው ልጅ አካሉ ቢታሰርም አዕምሮው ማሰብ አያቆምም፡፡ በተቻለኝ አቅም ተደብቄ ነበር የምፅፈው፡፡ የምፅፋቸውን ደግሞ ፖሊሶች የማያገኙት ቦታ እደብቃለሁ፡፡ አወጣጡ የራሱ መንገድ አለው፡፡ ያን መንገድ አሁን መግለፁ ብዙም አስፈላጊ አይሆንም፡፡ ሌሎችም ያንን መንገድ ሊጠቀሙ ይችላሉ፡፡ በዚህ መልኩ ነው፣ መፅሐፎቼ ወጥተው የታተሙት፡፡
በማረሚያ ቤት ሳለህ፣ አብዛኛውን ጊዜህን እንዴት ነበር የምታሳልፈው?
በብዛት መፅሐፍት አነባለሁ፡፡ በሳምንት አንድ ቀን ወደ ቤተ መፅሐፍት በጥበቃ ታጅበን እንሄዳለን፤ 5 ደቂቃ ይሰጠናል፡፡ በ5 ደቂቃ ውስጥ አንድ የምንፈልገውን መፅሐፍ መርጠን፣ ተመልሰን እንገባለን፡፡ ከዚያ ውጪ የምንፈልጋቸውን መጽሐፍት፣ ከውጪ በተለያየ መንገድ እናስገባለን። ሌላው ስፖርት በብዛት እንሰራለን፤ የፀሎት ጊዜም አለን፤ ስለተለያዩ ጉዳዮችም እንወያያለን፡፡ እስር ቤቶች የኢትዮጵያ ብሄር ብሄረሰቦች መገኛ ናቸው። ከሁሉም ጋር እንወያያለን፡፡ እነዚህን በመሳሰሉ ነገሮች ነበር  ጊዜያችንን የምናሳልፈው፡፡
የትኞቹን  ሚዲያዎች ትከታተሉ ነበር?
ያው ኢቲቪ አለ፡፡ ጋዜጦች አይገቡም፡፡ በመጨረሻ አካባቢ ደግሞ የኦሮሚያ ብሮድካስቲንግ ኔትወርክ (OBN) እንዲቋረጥ ተደርጓል፡፡ በተለያየ መንገድ ግን መረጃዎችን ለማግኘት እንሞክር ነበር። እነ ኦሮማይን የመሳሰሉ መጻህፍት እኮ መግባት አይችሉም፡፡ ምናልባት ማስገባት የሚቻለው የተረት መጻህፍት ይመስለኛል፡፡  
እስር ቤት ሆነህ ሁለት ዓለማቀፍ ሽልማቶችን አግኝተሃል፡፡ በሽልማቶቹ ምን ነበር የተሰማህ?
እንግዲህ አንደኛው ሂውማን ራይትስ ዎች ያበረከተልኝ ሽልማት ሲሆን ሁለተኛው የሲኤንኤን መልቲ ቾይዝ አፍሪካ ዓመታዊ ሽልማት ላይ “የዓመቱ ጋዜጠኛ” በሚል የተሸለምኩት ነው፡፡ እነዚህ ሽልማቶች እኔ ከሌላው የበለጠ ስለሰራሁ የተሰጡኝ አይመስለኝም፡፡ ሽልማቶቹ ተምሳሌታዊ ናቸው፡፡ ሌላው አለም እየተከታተለን እንደሆነ ለማሳየት የተደረጉ ሽልማቶች ይመስሉኛል፡፡ ሽልማት ይሰጥ ከተባለ ኢትዮጵያ ውስጥ 30 እና 40 ዓመት በጋዜጠኝነት የሰሩ የምናከብራቸው ጋዜጠኞች አሉ፡፡ እኔ በጋዜጠኝነት የቆየሁት ለ10 ዓመት ነው፡፡ ግን ሽልማቶቹን በአክብሮት እቀበላቸዋለሁ፡፡ ለኔ ከሁሉም በላይ ሽልማቴ፣ የኔን ጉዳይ ሲከታተሉ የነበሩ ሰዎች የሚለግሱኝ ፍቅር ነበር፡፡ አስታውሳለሁ፣ በፊት ቢሮዬ እየመጡ፣ ጋዜጣ በነፃ የምሰጣቸው አንድ ጡረተኛ ሽማግሌ ነበሩ፡፡ እሳቸው ለባለቤቴ 20 ብር ሰጥተዋት፣ “ሙዝ ገዝተሽለት ሂጂ” ያሏት ነገር፣ ዛሬም ከህሊናዬ አልወጣም፡፡ ከዚህ የሚበልጥ ሽልማት ለኔ የለም፡፡
በይቅርታ ለመፈታት ያመለከትክበት አጋጣሚ እንደነበር ሰምቼአለሁ፡፡ በእርግጥ ይቅርታ ጠይቀህ ተከልክለሃል?
ሁላችንም እንደምናስታውሰው፤ ሁለቱ ስዊድናውያን ጋዜጠኞች፣ ርዕዮት ዓለሙና እኔን በወቅቱ የኢትዮጵያ ጋዜጠኞች ህብረት ፕሬዚዳንት የነበረው አቶ አንተነህ አብርሃም፣ የአለማቀፍ የጋዜጠኝነት ህብረት ተወካይና ሌሎች ሰዎች መጥተው አነጋገሩን፡፡ እኛ እንድትፈቱ ነው የምንፈልገው፣ መንግስት ሊፈታችሁ ይፈልጋል። ለምን ነገሮችን እዚህ ጋ አንቋጭም የሚል ሃሳብ አቀረቡ፤ ሁለቱ ስዊድናዊያንና እኔ ይሄን ተቀብለን የይቅርታውን ሰነድ ሞላን፡፡ የቀድሞው ጠ/ሚኒስትር አቶ መለስ፣ ”የጥቁርና ነጭ ደም አይለያይም” ብለው ነበር፤ በኋላ ግን ነጮቹን በመፍታት እኔን በማቆየት እንደሚለያይ አሳይተውናል፡፡ ነጮቹን ወዲያው ለቀቋቸው፣ እኛን አቆዩን፡፡ አሁን ግን “ይቅርታ አድርገንላችኋል፣ ትቀበላላችሁ አትቀበሉም” የሚል አማራጭ ነው ያቀረቡልን፡፡ እንቀበለዋለን ብለን ወጥተናል፡፡
በዚህ መንገድ ከእስር  እፈታለሁ የሚል ግምት ነበረህ?
መቼ እና እንዴት የሚለውን መገመት ባልችልም በመሃል እንደምፈታ ተስፋ አደርግ ነበር፡፡ በኛ ጉዳይ ተመሳሳይ ፍርድ የተፈረደባቸው ሲፈቱ ሳይ፣ ተስፋ አደርግ ነበር፡፡ በነገራችን ላይ የኢትዮጵያ ሁኔታ ተገማች አይደለም፡፡ ተገማች አለመሆኑ ደግሞ በጣም አደገኛ ነው፡፡ ስለዚህ ይሄን አይነት የአፈታት መንገድ አልገመትኩም፡፡
በእስር ላይ ሆናችሁ ሀገሪቱ ባለፉት 3 ዓመታት ያሳለፈችውን ፖለቲካዊ ቀውስ በተመለከተ ምን ያህል መረጃ ታገኙ ነበር?
መረጃዎችን በደንብ እንከታተል ነበር፡፡ በተለያየ አማራጭ እያንዳንዷን ነገር እናገኝ ነበር፡፡ ከፖሊሶችም ቢሆን መረጃ የምናገኝበት አጋጣሚ ይኖራል፡፡
እንደ ጋዜጠኝነትህ፣ የሀገራችንን የጋዜጠኝነት ሙያ እንዴት ትገልፀዋለህ?
 የኢትዮጵያ የጋዜጠኝነት ሙያ በብዙ ጎታች ነገሮች ወደ ኋላ እየተጎተተ፣ ጥርሱን ነክሶ ወደፊት ለመግፋት የሚሞክር ነው፡፡ የሀገሪቱ የጋዜጠኝነት ሙያ እዚህ የደረሰው፣ አሰሪ ሁኔታዎች በመኖራቸው ሳይሆን በጋዜጠኛው ብርታት ነው፡፡ ሁሉም ጋዜጠኞች ብዙ ይጥራሉ፡፡ የግሉ ሚዲያ ደግሞ በመከራ ውስጥ ያለ ነው፤ ይሄን ተቋቁሞ ወደፊት ለመግፋት የሚውተረተር ነው፡፡ በጥቅሉ ኢትዮጵያ ውስጥ ያለን ጋዜጠኞች፣ ምስኪን ጋዜጠኞች ነን፡፡ በብዙ ፈተና እና ትግል ውስጥ ነው የምናልፈው። እኔ ለምሳሌ በሙያዬ ስንቀሳቀስ፣ ከ5 ጊዜያት በላይ ታስሬያለሁ፣ ታግቻለሁ፡፡ ሂደቱ እጅግ ፈታኝና በምስቅልቅሎሽ የተሞላ ነው፡፡ ወደ ኋላ በሚጎትቱ አሰራሮች፣ ደንቦችና ስልታዊ ደባዎች የተጠፈረ የሙያ መስክ ቢኖር ጋዜጠኝነት ነው፡፡ እስካሁን ያለፍንበት ሂደት የመገፋፋት ነበር፡፡ ከዚህ በኋላ የሚኖረውን ሂደት አላውቅም፡፡ የተሻለ ነገር እንዲመጣ ተስፋ አደርጋለሁ፡፡
አሁን ሀገሪቱ ያለችበትን ፖለቲካዊ ሁኔታ እንዴት ትገልጸዋለህ?
አሁን ብዙ የሚያስጨንቁ ነገሮች አሉ፡፡ ጫፍ ላይ ነው ያለነው፡፡ ሃይማኖታዊ በዓል ሲያከብሩ ሰዎች እየሞቱ ነው፡፡ ብዙ ምስቅልቅል ነገሮችን እንመለከታለን፡፡ በነዚህ መሃል ደግሞ የነበሩ ብዙ ነገሮች አሉ፡፡ የኢትዮጵያ ህዝብ አሁን ነፃነት፣ ዲሞክራሲ ፈልጓል፡፡ አሁን  የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ሳይሆን አስቸኳይ ውይይት ነበር የሚያስፈልገን። የአስቸኳይ ጊዜ አንድነት፣ ፍቅር ነው የሚያስፈልገን። ሰራዊት ማሰማራት ሳያስፈልግ፣ ሁሉንም ነገር በፍቅር ማስተካከል ይቻላል፡፡ እውነተኛ የሀገር ሽማግሌዎች ስራቸውን መስራት አለባቸው፡፡ ኢህአዴግ በአውራ ጣቱ ቆሞ ሳይሆን ቁጭ ብሎ ነው መወያየት ያለበት፡፡ ዶ/ር መረራ እንዳሉት፤ ሁለቱም ወገኖች መቀራረብ አለባቸው። መፍትሄው ያለው ሁለቱም ጋ ነው፡፡ ነገር ግን ፈለግንም አልፈለግንም ከእንግዲህ ዲሞክራሲ ኢትዮጵያ ላይ ማበቡ አይቀርም፡፡ የዲሞክራሲ ፀሐይ መውጣቱ አይቀርም፡፡ ይሄ የብሄር ማንነት ላይ የሚደርስ ጥቃት መቆም አለበት፡፡ በነገራችን ላይ እኔ ዝዋይ እያለሁ፣ ማረሚያ ቤት ድረስ እየመጡ የሚጠይቁኝ አደይ፣ ትርሃስ የሚባሉ እናቶች ነበሩ፡፡ ከልባቸው ጠይቀውኝ፣ መርቀውኝ ነበር የሚሄዱት፡፡ እኛን እነዚህ የፍቅር እናቶች ናቸው ዘር ሳይለዩ ያሳደጉን። ወንበር ላይ የተቀመጡ ሰዎች በሰሩት ስህተት፣ ሌሎች መጎዳታቸው ተገቢ አይደለም፡፡ እዚህ ላይ ቆም ብሎ ማሰብ ያስፈልጋል፡፡ ይሄ የለውጥ ጊዜ ስለሆነ፣ ሁሉንም ነገር ቆም ብሎ ማሰብ የግድ ይላል፡፡  
የወደፊት እቅድህ ምንድን ነው?
እኔ በጋዜጠኝነት ሙያዬ የተሻለ ነገር ለማድረግ ነው የምጥረው፡፡ አንድ ሰው ባዳበረው ሙያ ነው መጓዝ ያለበት፡፡ አንድን በባህር ውስጥ የለመደ ዓሳ፣ በሰማይ ብረር ብንለው አይሆንም፡፡ የኔም እንደዚያው ነው፡፡ በጋዜጠኝነት ሙያዬ ቀጥዬ፣ አስተዋፅኦ ማበርከት እፈልጋለሁ፡፡
በተረፈ ከጎኔ የቆሙ የሰው ዘሮችን በሙሉ ማመስገን እፈልጋለሁ፡፡ ኢትዮጵያውያን ወገኖቼን ከልቤ አመሰግናለሁ፡፡ ሀገራችን ኢትዮጵያንም እግዚአብሔር እንዲባርካት፣ እንዲጠብቃት፣ ያጣነውን መደማመጥ እንዲሰጠን እመኛለሁ፡፡     

  በኢትዮጵያ የተፈጠረው አለመረጋጋትና የሠላም እጦት እንዳሳሰበው የጠቆመው የአፍሪካ ህብረት፤ ሁሉም ኢትዮጵያውያንና መንግስት ለሠላምና መረጋጋት ቅድሚያ እንዲሰጡ ጥሪ አቅርቧል፡፡
የህብረቱ የወቅቱ ሊቀመንበር ሙሣ መሃመት ፋኪ ከትናንት በስቲያ ለመገናኛ ብዙሃን ባሠራጩት መግለጫ፤ ሁሉም የኢትዮጵያ ፖለቲካ ተዋንያን ሠላምና መረጋጋትን ከሚነሣ ድርጊት መታቀብ አለባቸው ብለዋል፡፡
“መንግስትና የሃገሪቱ ህዝብ ችግሩን በመግባባት እንደሚፈቱት እምነት አለኝ” ያሉት ሊቀ መንበሩ፤ መንግስት የፖለቲካ ምህዳሩን ለማስፋት ቃል መግባቱንም ህብረቱ በአዎንታ እንደሚቀበለው አስታውቀዋል፡፡
“የኢትዮጵያ መረጋጋት ለህዝቧ፣ ለቀጠናውና ለመላው አፍሪካ በእጀጉ አስፈላጊ ነው” ያሉት ሙሣ ፋኪ፤ መንግስትና ሁሉም የሃገሪቱ ባለድርሻዎች በሃላፊነት ስሜት እንዲንቀሣቀሱ አሳስበዋል፡፡

 “የወጣው መስፈርት አንድን ግለሰብ ታሳቢ ያደረገ ነው”
       “በ4 ወር እንኳን አንድ ድርጅት በምስራቅ አፍሪካ ያሉም ቢተባበሩ ሥራው አያልቅም”

   የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ቁጠባ ቤቶች ልማት ኢንተርፕራይዝ ጥር 1 ቀን 2010 ዓ.ም በአዲስ አበባ በሦስት ሳይቶች የሚገኙ 40/60 ቤቶችን የአሉሙኒየም በርና መስኮት ከነመስታወቱና ከነሙሉ ገጠማ ስራው እንዲሰራለት ያወጣው የ1 ቢሊዮን ብር ጨረታ ሠነድ ቅሬታ አስነስቷል፡፡
በጨረታው ሠነድ ላይ የወጣው መስፈርት ለአንድ ድርጅት የወገነ፣ የወቅቱን የምንዛሬ እጥረት ያላገናዘበና በአጠቃላይ ሌሎች ተፎካካሪ ድርጅቶችን ከጨዋታ ውጭ የሚያደርግ ነው ሲሉ  በአልሙኒየም አስመጭነትና ሥራ ላይ የተሰማሩ ድርጅቶች ቅሬታቸውን ለአዲስ አድማስ ገልፀዋል፡፡
ለአንድ ግለሰብ እንዲመች ሆኖ የተሰናዳው የጨረታ ሠነድ እንኳን በ4 ወር በ4 ዓመት በአንድ ድርጅት ተሰርቶ  ሊያልቅ ቀርቶ በምስራቅ አፍሪካ ያሉ በአልሙኒየም ሥራ ላይ የተሰማሩ ድርጅቶች ቢተባበሩ እንኳን ሥራው እንደማያልቅ ቅሬታ አቅራቢዎቹ ጨምረው ገልፀዋል፡፡
ኢንተርፕራይዙ ባወጣው የጨረታ ሠነድ ተጫራች ድርጅቶች የአልሙኒየም ክምችት (ስቶክ) እንዲኖራቸውና ከኢትዮጵያ ደረጃ መዳቢዎች የተሰጠ የብቃት ማረጋገጫ እንዲያቀርቡ መጠየቁን የገለፁት ድርጅቶቹ ባለው የውጭ ምንዛሪ እጥረት ድርጅቶች ቶሎ ቶሎ እቃውን እያስገቡ ማከማቸት እንደማይችሉ፣ አንድ ዕቃ ታዝዞ እስኪገባ የሚፈጀውን ጊዜ ግምት ውስጥ ሳያስገቡ ሠነዱን በዚህ መልኩ ማዘጋጀታቸው አንድን ድርጅት ለመጥቀም ሆን ብሎ የተሰራ ሴራ ነው ሲሉ ያማርራሉ፡፡
ከደረጃ መዳቢዎች የተሰጠ ሠርተፍኬት አቅርቡ መባሉን በተመለከተም፤ “እኛ እቃውን ከውጭ የምናስመጣ እንደመሆናችን ከኢትዮጵያ ደረጃ መዳቢዎች የሚሰጠን ሠርተፍኬት እንደሌለ ይታወቃል” ያሉት ቅሬታ አቅራቢዎቹ፤ ከውጭ አገር የሚሰጥ ተመጣጣኝ ሠርተፍኬት እንዲያቀርቡ አለመጠየቃቸውም ሆን ተብሎ ተፎካካሪዎችን ከጨዋታ ውጭ ለማድረግ የተሰራ በመሆኑ ሠነዱን ቢገዙም በጨረታው እንደማይሳተፉ ለአዲስ አድማስ ገልፀዋል፡፡
የጨረታው ሠነድ አንድ ድርጅትን ለመጥቀም ታስቦ ለመውጣቱ ምን ማረጋገጫ አላችሁ በሚል ከአዲስ አድማስ ለተነሳው ጥያቄ፣ ቅሬታ አቅራቢዎቹ ሲመልሱ፣  ታሳቢ የተደረገው ድርጅት ከውጭ በሚመጣ አልሙኒየም ተረፈ ምርት ሪሳይክል እያደረገ የሚያመርት በመሆኑ ክምችትም የኢትዮጵያ ደረጃ መዳቢዎች ሠርተፍኬትም እንዳለው ይታወቃል በአጠቃላይ የታዘዘው የአልሙኒየም አይነትና ቀለም ሳይቀር ለዚሁ ድርጅት የታሰበ ነው ብለዋል፡፡
ከዚህ ቀደምም ከአምስት ዓመታት በፊት በክራውንና በሰንጋ ተራ ለተገነቡ ቤቶች ተመሳሳይ የ1 ቢሊዮን ብር ጨረታ ወጥቶ ይሄው ድርጅት ማሸነፉንና እስከ ቅርብ ጊዜ ድረስ ያላጠናቀቀው ሥራ እንደነበር ገልፀው፤ ጭራሽ እነዚህን ቤቶች በአራት ወር (በ120 ቀናት) አንድ ድርጅት በጥራትና በፍጥነት ያጠናቅቃል ማለት ዘበት ነው ብለዋል፡፡
የቁጠባ ቤቶች ልማት ኢንተርፕራይዝ በአራት ወር አልሙኒየም በሮች ከነመስታወታቸው ተገጥመው እንዲጠናቀቁለት ጨረታ ያወጣባቸው ሦስት ሳይቶች ሲሆኑ፤ እነዚህም ሳይት አንድ ቦሌ ቡልቡላ የሚገኝ ሲሆን፤ በዚህ ሳይት 15 ባለ 15 ወለል (G+15)  ቤቶች፣ በሳይት ሁለት ቦሌ በሻሌ 22 ባለ 15 (G+15)፣  15 ባለ 13 ወለል (G+13)፣ 21 ባለ 9 ወለል (G+9) ቤቶች፣ በሳይት ሦስት ደግሞ ቦሌ አያት፡- 16 ባለ 15 ወለል (G+15)፣   34 ባለ 13 ወለል (G+13)፣ 10 ባለ 8 ወለል (G+8) ቤቶች ሲሆኑ እነዚህን ብሎኮች በ120 ቀናት የአልሙኒየም በር ከነመስታወቱ ለመግጠም አልሙኒየሙ በካሬ ተባዝቶ፣ ለ120 ቀናት ሲካፈል ድርጅቱ በቀን 3637 ካሬ ሜትር አልሙኒየም መስራት እንዳለበት የገለፁት ቅሬታ አቅራቢዎቹ፤ ይህ በህልምም በእውንም የማይታሰብ መሆኑን ተናግረዋል፡፡ አሁን ባለው ሁኔታ አንድ ጠንካራ የሚባል ድርጅት በቀን ከ30 ካ.ሜ በላይ አልሙኒየም ቆርጦ አስተካክሎ፣ መስታወት ገጥሞና ሠርቶ ማጠናቀቅ እንደማይችል የጠቆሙት ቅሬታ አቅራቢዎቹ፤ ይሄ በቤት ችግር እየተሰቃየ መቶ ፐርሰንት ከፍሎ በጉጉት ለሚጠብቀው ህዝብ ተጨማሪ መዘግየትን እንደሚፈጥር ገልፀው፤ ኢንተርፕራይዙ እነዚህን ሕገ-ወጥ አሰራሮች በጥሞና ተመልክቶ፣ የጨረታ ሠነዱን እንዲያስተካክል ጠይቀዋል፡፡ ምላሽ የማይሰጣቸው ከሆነም መብታቸውን በህግ እንደሚያስከብሩ ቅሬታ አቅራቢዎቹ ገልፀዋል፡፡  
የቁጠባ ቤቶች ልማት ኢንተርፕራይዝ ኃላፊዎች በጉዳዩ ዙሪያ ምላሽ እንዲሰጡን ላለፉት ሁለት ሳምንታት በተደጋጋሚ ቢሮአቸው ብንመላለስም ኃላፊነት ወስዶ ምላሽ የሚሰጥ ባለመገኘቱ የኢንተርፕራይዙን ሀሳብ ማካተት አልቻልንም፡፡

በጦርነትና የግጭት ቀጠናዎች ውስጥ አደገኛና አስቸጋሪ ህይወት እየገፉ የሚገኙ የአለማችን ህጻናት ቁጥር በከፍተኛ ሁኔታ በማደግ ከ357 ሚሊዮን በላይ መድረሱን ሴቭ ዘ ችልድረን ከትናንት በስቲያ ባወጣው ዓለማቀፍ ሪፖርት ማስታወቁ ተዘግቧል፡፡
በጦርነትና በግጭት ቀጠናዎች ውስጥ ከሚገኙት የአለማችን ህጻናት፣ ግማሽ ያህሉ ወይም 165 ሚሊዮን የሚደርሱት ከፍተኛ ግጭት በሚከሰቱባቸው አካባቢዎች ውስጥ እንደሚኖሩ የጠቆመው ሪፖርቱ፤ የመካከለኛው ምስራቅ አገራት ህጻናት ለዚህ ችግር በመጋለጥ ረገድ ቀዳሚነቱን እንደሚይዙና አፍሪካውያን ህጻናት እንደሚከተሉ በመግለጽ፣ በመካከለኛው ምስራቅ አገራት ከሚኖሩ አምስት ህጻናት፣ ሁለቱ ግጭት ወይም ጦርነት በሚከናወንበት አካባቢ በ50 ኪሎ ሜትሮች ርቀት ውስጥ እንደሚኖሩ አመልክቷል፡፡
በርካታ ህጻናት በጦርነትና በግጭት ቀጠናዎች ውስጥ እንደሚገኙባቸውና ለህጻናት እጅግ አደገኛ ናቸው ተብለው በሪፖርቱ ከተጠቀሱት የአለማችን አገራት መካከል ሶሪያ ቀዳሚነቱን ስትይዝ፣ አፍጋኒስታንና ሶማሊያ በተከታታይነት ተቀምጠዋል፡፡
በህጻናት ላይ የሚፈጸሙ ግድያዎችና የማቁሰል ጥቃቶች ከጊዜ ወደ ጊዜ እየተበራከቱ እንደመጡ የዘገበው ዘ ኢንዴፔንደንት፤ የተባበሩት መንግስታት በማስረጃ አስደግፎ የሚመዘግባቸው መሰል ጥቃቶች ቁጥር ባለፉት ሰባት አመታት ውስጥ በ3 እጥፍ ማደጉንም አስታውሷል፡፡
በግጭቶችና በጦርነቶች ሳቢያ ከመኖሪያ አካባቢያቸው እየተፈናቀሉ ለተለያዩ ስቃዮችና እንግልቶች የሚዳረጉ የአለማችን ህጻናት ቁጥር እያሻቀበ እንደሚገኝ የጠቆመው ዘገባው፤ ከ65 ሚሊዮን በላይ የዓለማችን ህጻናት ምንም አይነት ቋሚ የመኖሪያ ቤት እንደሌላቸው አመልክቷል፡፡