Administrator

Administrator

Saturday, 06 January 2018 12:56

“የፖለቲካ ጅዝብትና”!?

 “--ኦክሲሞሮን…ግን ቃሉ እንደሚገልፀው የማይመጣጠኑ… አንድ ላይ ሊሰባሰቡ በማይችሉ ነገሮች መሀል የሚደረግ ጋብቻ ነው፡፡… የእብድና የጤነኛ ጋብቻ እንደማለት፡፡… እብድ መንግስት፣ ጤነኛ ህዝብን ቢያስተዳድር እንደማለት፡፡ ወይንም ባል ሞቶ ሳለ፣ ሚስቱ በመቅበር ፋንታ አብራው ስትኖር… አይነት፡፡--”

   አርዕስቱ ራሱ ፓራዶክስ ነው አይደል? ፓራዶክስ እንኳን አይደለም፤ ኦክሲሞሮን ነው። “oxymoron” ከሁለት ሃሳቦች ጥምረት የተሰራ ነው፡፡ Oxy (sharp), moron (foolish) “አያዋ” (Pardoxe) ከሁለት የሚመጣጠኑ የሃሳብ ተፎካካሪዎች ጥምረት የሚገኝ የአቻ ጋብቻ ውጤት ነው፡፡ የተመጣጣኞች ጋብቻ እንቆቅልሽ ይባላል። እንቆቅልሽ እድገት ነው፡፡ አዎንታዊ ድምር ነው፡፡ ማንኛውም አይነት የሰው ልጅ መረዳት፣ የተለያዩ የሚመስሉ የሀሳብ አቻዎችን አቻችሎ ከማስማማት ይወለዳል፡፡ እንቆቅልሹን መጀመሪያ አቀራርቦ ለማጋጠም ሲሞክር ግጭት ይፈጠራል፡፡ ግጭቱ ያስደነግጠዋል፡፡ ደንግጦ በአንዱና በሌላው መሀል እየለዋወጠ ያያል፡፡ ያመነታል፡፡ “ማመንታት” የሚለው ቃል ራሱ… መንታ መንገድ ላይ ቆሞ የመመዘንን ሂደት የሚያሳይ ነው፡፡ እንቆቅልሽ የማመንታትን ጥበብ የማስተማሪያ ዘዴ ነው፡፡
ይሄ ከላይ ለማሳየት የጣርኩት ሁሉ ጤነኛውን የሁለት ተመጣጣኝ ነገሮችን የጋብቻ ሂደት ነው። ፖለቲካ ህዝብን የማስተዳደሪያ ዘዴ ነው። የማስተዳደሪያ አቅም ወይንም ጥበብ ያለው… መተዳደር የሚፈልገውን የሚመራበት መንገድ ነው። ይኼ እንቆቅልሽ ነው፡፡ ተመጣጣኝ አስተዳዳሪና ተመጣጣኝ ህዝብ ሲገናኙ እንቆቅልሽ ይሰምራል፡፡ ዘመንና ታሪክ ከዚህ ተመጣጣኝ እንቆቅልሽ ውስጥ ይወለዳል፡፡ አስተዳዳሪው ህዝብን ይመስላል… የህዝብን ችግር እንደ ራሱ ችግር አድርጎ ይፈታል፡፡ ህዝብም አስተዳዳሪውን እንደኔ ሆነህልኛልና…በዙፋኑ ላይ ቆይልኝ ይለዋል። ህዝብን ግለሰብ (አስተዳዳሪ)፣ ግለሰብን ህዝብ ማድረጉ ነው እንቆቅልሹ፡፡ እንቆቅልሹ፤ ተግባቦቱ ከሰመረ “አያዋ” መሆኑ ይቀራል፡፡ “አዎ-አዎ” ሆኖ አንድና ያው መስሎ ይደመራል፡፡
ኦክሲሞሮን…ግን ቃሉ እንደሚገልፀው የማይመጣጠኑ… አንድ ላይ ሊሰባሰቡ በማይችሉ ነገሮች መሀል የሚደረግ ጋብቻ ነው፡፡… የእብድና የጤነኛ ጋብቻ እንደማለት፡፡… እብድ መንግስት፣ ጤነኛ ህዝብን ቢያስተዳድር እንደማለት፡፡ ወይንም ባል ሞቶ ሳለ፣ ሚስቱ በመቅበር ፋንታ አብራው ስትኖር… አይነት፡፡
ከዚህ በፊት እንዳልኩት፣ ለጥበብ ወይንም ለመለኮታዊ ውበት ባለሟልነት ሲል፣ ከተራው ሰው አመለካከቱና አኗኗሩ የሚለይን ሰው እኔ ጀዝባ ብዬ ነው የምጠራው፡፡ የብትህውና ህይወት በጥበብ ምክኒያት የመረጠ ማለት ነው፡፡ በሀይማኖታዊ ወይንም በሳይንሳዊ አንፃር ሳይሆን በጥበብ ውስጥ እውነት የሚፈልግ ሰው ነው ጀዝባ ለኔ፡፡ ሌሎች ደግሞ በሱስ ምክኒያት… ወይንም ለመረጠው ሱስ ሲል መደበኛ ህይወቱን የጣለ ሰውን ጀዝባ ብለው ይጠሩታል፡፡ አንዳንድ ጊዜ ለጥበብ ብሎ የሚኖር ሰውም ከጥበብ ህይወቱ ጋር ስለሚመሳሰል ለሰስ ብሎ የሚኖረውን ሰው ባህሪ፣ ከጥበብ ግቡ ጋር አብሮ ሲያራምድ ይታያል፡፡ ግን ቅድሚያ የሚሰጠው ጥበቡን እንደሆነ በስራው ይገልፀዋል፡፡
አስቡት፤ ይኼ ጥበበኛ ጥበብን የሚፈጥረው ወይንም ለመፍጠር የሚሞክረው የፖለቲካ ስልጣን ላይ ተቀምጦ ቢሆንና የፈጠራው ውጤቶች ህዝቦቹ ቢሆኑ፡፡ …ዛሬ አንዱን ገፀ ባህርይ ይፈጥረዋል፡፡…ሲፈልግ የፈጠረውን ገፀ ባህርይ ከእነ ወረቀቱ ጨማዶ ሊጥለው ይችላል፡፡ ወይ መፃፍ የጀመረውን ነገር በደንብ ሳያጠና ሊሆን ይችላል መፃፍ የሚጀምረው፡፡ ጀምሮ ሊተወው ይችላል፡፡ ዛሬ የጀመረውን ትቶ  ነገም ከነገ ወዲያም ሊጀምር ይችላል፡፡… እንደ ጀዝባ ጥበበኛነቱ፣ ይሄንን ሁሉ ሊያደርግ ይችላል፡፡ ግን ችግሩ ገፀባህሪዎቹና ድርሰቶቹ በተጨባጭ ህይወት የሚኖሩ…ህልውና ያላችሁ መሆናቸው ነው፡፡…
… ምናልባት ፖለቲከኛው የሙሉ ጊዜ ጀዝባና የጥበብ ሰው ለመሆን ይሆናል የተፈጠረው። ምናልባት የተፈጠረበትን ምክኒያት ሳያውቅ ሊሆን ይችላል ፖለቲካ ውስጥ የገባው፡፡… ወይንም በፖለቲካ (ተጨባጭ) እና ጥበብ (ምናባዊው) መሀል ብዙ ልዩነት አይታየው ይሆናል፡፡… መድረክ ላይ አሻንጉሊቶችን በክር አማካኝነት የሚያስደንሱ አርቲስቶች አሉ፡፡…. በክር አንጠልጥሎ የሚያስደንሳቸው ስጋ ለባሽ ሰዎች ከሆኑ ግን  sharp…ይሆን የነበረው ጥበብ… ወደ አሰቃቂ ክፋት ተለውጧል፡፡ ኦክሲሞሮን ተፈጥሯል… የጭካኔ ፈጠራ ሆኗል፡፡ “Kind cruelness”…
በአሻንጉሊቶቹ ላይ በክር እንጠልጥሎ እየጣለና እያነሳ ሲቀልድባቸው…ተመልካች ስለ ሰዎች እየመሰለ እንደሆነ ይገባቸዋል፡፡… በምሳሌው ግን ያስተምራቸዋል እንጂ ምሳሌውን እነሱ አድርጎ አይጫወትባቸውም፡፡
ጀዝባው በራሱ ህይወት ሊጫወት ይችላል። ስለሚሰራው ጥበብ ለማጥናት ሲል የራሱን ህይወት የመጫወቻ ሜዳ አድርጎ፣ ራሱን ከጥበቡ አሳንሶ ችላ ሊል ይችላል፡፡ ፖለቲከኛውም እንደ ትክክለኛ አስተዳዳሪ ራሱን ዝቅ አድርጎ፣ የህዝቡን አገልግሎቶች ከፍ ለማድረግ ሲሞክር ትክክለኛ የህዝብ መሪ ነው፡፡ ፖለቲከኛው ጀዝባ የሚሆነው ራሱን ከፍ አድርጎ ህዝቡን ሲንቅ ነው። “ፐርፐዙን” ሲተው ጀዘበ ይባላል፡፡… ህዝቡን በማስተዳደር ፈንታ ራሱን በህዝቡ ፈንታ ወይንም ጫንቃ የሚያስተዳድር ከሆነ… ለፖለቲከኛነት ሚናው ጀዝቧል፡፡ … ዓላማውን ክዷል፡፡ ሰይጣን ጀዝባ ነው፡፡ የመልአክነት ስራውን ወደ መልዕክት አዛቢነት ስለቀየረ፡፡
ዋናው ነገርዬው የሚመዘነው ከሚናው (Purpose) አንፃር ነው፡፡ የመጠቀ ወይም የዘቀጠ የሚለው መለኪያ የሚመጣው ለመጫወት ከመረጠው ሚናው አንፃር ነው፡፡ ፖለቲከኛነት ህዝብን ማስተዳደር ነው፡፡ ህዝብን ማስተዳደር ካልቻለ ለምን እንዳልቻለ መታወቅ ይኖርበታል።… አቅም አንሶት ከሆነ አቅም ላለው ሚናውን አሳልፎ መስጠት አለበት፡፡ ስራዬን የመሥራት አቅም የለኝም፤ መስራት ለሚችልም ግን አሳልፌ መስጠት አልፈልግም ካለ…ይኼኔ የፖለቲካ ጀዝባ ሆኗል። …መስራትም ሆነ ሌሎች እንዲሰሩ መፍቀድ ያልቻለውን ሚና፤ “ሥልጣን” ብሎ ይጠራዋል፡፡ ሥልጣኑ ያለው ስራውን መስራት ላይ አይደለም፡፡ ስራውን  ለመስራት አቅም የለውም፡፡ ግን ስራውን አላሰራ ያለው አቅም ማነስ፣ ሌሎች እንዳይሰሩ ወይም ለወደፊትም መስራት እንዳይሞክሩ አድርጎ የመሰባበር ታላቅ አቅም አለው፡፡ ስንፍናውን በዘላቂነት ለማስቀጠል ጎበዝ ነው፡፡ ጉብዝናው ያለው ግን ያለ ቦታው ነው፡፡ ጀዝባ ማለት ይኼ ነው… በፖለቲካ አንፃር ሳየው “Sharp loser” አይነት ነው፡፡ “ብቆጣም እመታሻለሁ….ብትቆጭም እመታሻለሁ” የሚለውን የአሰራር ዘዴ ተጠቅሞ ጀዝባነቱን ብቃት አስመስሎ ማቅረብ፡፡ ግን ይኼ ጅዝብትና ስልጣን ላይ ያለው ሰው ዘንድ ወይም አጋሮቹ ጋር ብቻ ተወስኖ አይቀርም፡፡
የሚንቀውን ሰው አስተዳዳሪ አድርጎ በተደጋጋሚ የሚመርጥ ህዝብም የዛው በሽታ ተጠቂ ነው፡፡ የጅዝብትና፡፡ ህዝቡ “የዝንብ ጠንጋራን የሚያውቅ” ሆኖ ግን የሚያዋጣውን ፖለቲካ የማያውቅ ከሆነ ጀዝባ ነው፡፡ እውቀቱ ያለው የማይመለከተው ነገር ላይ በመሆኑ፡፡ ህልውናውን በቀጥታ የሚመለከተውን ነገር ትቶ፣ “የዝንብ ጠንጋራን” በመለየት ከተጠመደ፣ ህዝብም ጀዝባ ፖለቲከኛ ነው፡፡… ማን የማን የሥራ ውጤት እንደሆነም ለማወቅ አዳጋች ይሆናል፡፡
ባለፈው “ENN” ተብሎ በሚጠራው ቴሌቪዥን ላይ  አንድ ማስታወቂያ ሲነገር  ጆሮዬ ጥልቅ አለ። “በ…ወዘተ… ወዘተ.. ስልክ ቁጥር መሪዎቻችሁን በቀጥታ ስልክ አግኝታችሁ ማነጋገር የምትችሉበት ፕሮግራም….” ምናምን ይላል ጥቅል መልዕክቱ፡፡ ይኼ ራሱ ኦክሲሞሮን ነው፡፡…. መንግስትና ህዝብ…. በቀጥታ መስመር ስላልተገናኙ ነው ያልተዋወቁት ለማለት ነው፡፡ …በአካል ላይ ጭንቅላትንና አካልን በስልክ  ለማወያየት እንደመሞከር ነው፡፡ ደም ስር…ስጋ አጥንት…እና በሚጫወቱት ሚና መግባባት ያልቻሉ ነገሮችን በቀጭኑ ሽቦ… “አንድ አድማጭ መስመር ላይ ገብቷል” እየተባባሉ ሊነጋገሩ። ግን አልሳቅሁም፡፡ ሳቅ የእንቆቅልሽን አዲስነት የሚያበስር የማወቅ ሂደት ነው፡፡… የማይመስል ሀሳብ ሲደጋገም…ያበሽቃል፡፡ መበሻሸቅ ነው የያዙት። …ጥሩ የአስማት በትረ ስልጣን የያዘ መሪ እንደ ሙሴ የችግርን ባህር ከፍሎ ህዝቡን ያሻግራል። …የፖለቲካ ጀዝባ እጅ ላይ ግን አስማታዊው ህዝብን የማስተዳደሪያ ስልጣን ጓሮን እንኳን አፅድቶ ወደማይጠርግ ያለቀ መጥረጊያ ይለወጥበታል፡፡ ስልጣኑም በእጁ ውስጥ የእሱን ባህሪ ተላብሶ ይጀዝባል፡፡ ሁለት “trivial planes” በሚያደርጉት ሰበቃ “The absolute” ፕሌን ላይ የሚደረስ ይመስላቸዋል፡፡ የሚደርሱት ግን “tragic plane” ላይ ነው፡፡
ዮናስ፤ እግዚአብሔር የሰጠውን መልእክት ወደ ነነዌ ሰዎች ሄዶ የማስተላለፍ ተልዕኮ ይቅርብኝ … ተራው ህይወቴ ይሻለኛል ብሎ አልሰማም አለ። … አልሰማ ያለው ችግር ገፍቶ መጣና ዓሳ ነባሪ ሆድ ውስጥ ጨመረው፡፡ በዓሳ ነባሪው ሆድ ውስጥ ቀናትን ቆይቶ ሲተፋ ግን እንደ ቀድሞው ችላ ባይ አልሆነም፡፡ …  የዓሳ ነባሪው የሆድ እቃ ጨለማ፣ የእግዚአብሔር ነብይ አድርጎ ነው ያወጣው። ተራው ህይወት (Trivial plane) በፈተና መስዋዕትነት (Tragic plane) ውስጥ ሲያልፍ … አልፎ በህይወት ከተረፈ፣ ከተራነት ጅዝብትናው ወጥቶ ተልዕኮውን ወደ መገንዘብ … ከሰውነት በላይ ከፍ ብሎ ወደተቀመጠው ማዕረግ ከፍ ወደ ማለት ይጠጋ ይሆናል፡፡
ይሄ ህዝባችን በብዙ ጨለማ ውስጥ አልፏል ይላሉ የታሪክ ዘገባዎች፡፡ … ታዲያ ከዛ ሁሉ የዓሳ ነባሪ ሆድ የተተፋ ህዝብ፣ እንዴ መልሶ እዛው ተራነት ውስጥ እየተመላለሰ ይታሻል፡፡ … ምናልባት ህዝቡ እንደ ዮናስ በተለያዩ የፖለቲካ ጀዝቦች ብልጠት ለአሳ ነባሪ ሲሰጥ ኖረ እንጂ አስተዳዳሪዎቹ ይሄ እጣ ፈንታ ገጥሟቸው አያውቅ ይሆናል፡፡ … የህዝብ አካል ያልሆነ ፖለቲከኛ ወይንም አስተዳዳሪ … አሊያም ብልጣብልጥ የሚባል ዝርያ አለ እንዴ? ..
...ተዉት በቃ! ...መልሱ ተከሰተልኝ፡፡ ህዝቡ ከድሮም እስከ አሁን በአስተዳዳሪዎቹ ሆድ እቃ ውስጥ ነው ያለው፡፡ የፖለቲካ ጀዝባዎቹ ናቸው ዓሳ ነባሪዎቹ፡፡ እየተቀባበሉ ይዋዋጡታል እንጂ ተፍተውት አያውቅም፡፡ ታዲያ ይሄ ህዝብ ከጨለማው ተሞክሮው (Tragic plane) ትምህርት ወስዶ ወደተሻለ የፍፁማዊነት ጎዳና  እንዴት ያምራ? …አንድ ጨለማ ሲመሽ ሌላ ጨለማ እየነጋበት፣ አፍሪካን የምታክል የዓሳ ነባሪ ሆድ ውስጥ እስረኛ ሆኖ ቀርቷል፡፡
…አልፎ አልፎ ዓሳ ነባሪው አፉን ገርበብ አድርጎ ሲከፍት፣ ሊተፋው ይመስለውና የተስፋ ህልም ያያል፡፡ “I see light at the end of tunnel, I think this time around we are  going to emerge into the light, into the clear--” ብሎ ይመኛል፡፡ … በዓሳ ነባሪው አፍ ግን የተስፈ ህልምና ወደ ጨለማው ተውጦ የሚቀላቀል አባል ብቻ ነው የሚጨመረው፡፡
…ተስፋ ያስቆርጣል፡፡ መፍረድም ይከብዳል። …በጨለማ ውስጥ ሆነው ጀዝቦቹ እርስ በራስ ይወነጃጀላሉ፡፡ “በቀጥታ የስልክ መስመር” ተነጋግረን ችግራችንን እንቅረፍ ይባባላሉ፡፡ … ችግራቸውን እንዲህ በቀላል እንደማይፈቱ እያወቁ፣ እንዳላወቁ ---- ገልባጭ መኪና ሙሉ መፈክርና ፕሮፓጋንዳ፣ አንዱ የጨለማ ፍጡር በሌላኛው ጀርባ ላይ ወስዶ ይደፋል፡፡ … “ገላጋይ መስሎ አጥቂ” ይሆናል፡፡ መአት አይነት “ኦክሲሞሮን” እያዳቀለ ያራባል፡፡ የጅዝብትና እና የመደንዘዝ ውጤት ነው፡፡

    ጥንት፣ ዛሬ እየፈረሰ ባለው ማዕከላዊ ምርመራ ድርጅት እሥር ቤት ውስጥ የተለያዩ ሰዎች ታስረው ይመጡ ነበር፡፡ የገና ሰሞን ከታሠሩት ውስጥ ጥቂቶቹን ዛሬ እንይ፡፡ ተረት ይምሰሉ እንጂ ዕውነተኛ ባህሪያት ናቸው፡፡ በበዓል ማሠር የተለመደ ነበር!
ሁለት ዕብዶች ነበሩ፡፡ አንደኛው ፒያሳ ደጎል አደባባይ እየዞረ፡-
“ጓድ ሊቀመንበር መንግሥቱ ሃ/ማርያም ሀቀኛ ኮሙኒስት ናቸው!
ጓድ ሊቀመንበር መንግሥቱ ሃ/ማርያም ሀቀኛ ኮሙኒስት ናቸው!”
እያለ ቀኑን ሙሉ አደባባዩን ሲዞረው ውሎ፤ ወደ ማታ ላይ ሲቪል የለበሱ ሰዎች አሥረው ወደ ማዕከላዊ ያመጡታል፡፡
“ጥፋቴ ምንድን ነው?” ሲል መርማሪውን ይጠይቃል፡፡
መርማሪውም፤
“ይህንን፤ ዓለም ያወቀውን ዕውነት የምትደጋግመው ነገር ቢኖርህ ነው!”
“ምን ዓይነት ነገር?”
“በውስጠ-ሚሥጥር “ሀቀኛ ኮሙኒስት አይደሉም” ብለህ ህዝቡን ለመቀስቀስ ነው! ነቅተንብሃል” ብሎ “አንዱ ክፍል አስገቡት” በማለት አዘዘ፡፡
ሁለተኛው ዕብድ የመጣው ደግሞ በአንድ የቀበሌ ስብሰባ ላይ፤
“መንግሥት እስከ መቼ ነው ጊዜያዊ ወታደራዊ ደርግ የሚባለው? ለምን ቋሚ አናደርገውም?” ብሎ በጠየቀው መሠረት፣ ህዝቡ በዚሁ ጉዳይ ሲጨቃጨቅ በመዋሉ፤ ህዝብን ለአመፅ የሚቀሰቅስ ፀረ-አብዮት ተግባር ነው” ተብሎ ነው፡፡
ሁለቱ ዕብዶች ዳማ ይጫወታሉ፡፡ አንደኛው ሌላኛውን በልቶት አንዲት ጠጠር ብቻ ቀርታዋለች፡፡ ያቺን ጠጠር በንጉሥም፣ በወታደርም መብላት ይችላል፡፡
ተሸናፊው፤ እየደጋገመ፤
“በወታደር አልበላም፡፡ በንጉሥ እንድትበላኝ ትገደዳለህ” ይለዋል፡፡
አሸናፊው ዕብድ፤
“የእኔ ወንድም፤ አንዴ ሞት ከተፈረደብህ፣ በቺቺ ግደሉኝ፣ በክላሽ ግደሉኝ፣ በሽጉጥ ግደሉኝ እያልክ ምን ያጨቃጭቅሃል?” አለው፡፡
ሌላኛው፤
“አሄሄ ሌላ ሸውድ! የንጉሥ አገዳደልና የወታደር አገዳደል አንድ መሰለህ? ንጉሥ፤ አንድ አንተን ብቻ ገሎ እፎይ ብሎ ይተኛል፡፡ ወታደር ግን አንድ አንተን ብቻ ገድሎ ዝም አይልም፡፡ ቂም ይይዙብኛል ብሎ ዘመድ አዝማድህን ሁሉ ይፈጃል፡፡ ለዚህ ነው በንጉሥ እንድትበላኝ ትገደዳለህ የምልህ!”
*      *      *
በሀገራችን ታሪክ እሥር ቤት ረዥም ዕድሜ ካላቸው ፍሬ ጉዳዮች አንዱ ነው፡፡ የማዕከላዊ ምርመራ ድርጅት እሥር ቤት ደግሞ በዓይነቱ ለየት ያለ ነው፡፡ ከፖሊስ ጣቢያ፣ ከቀበሌና ከፍተኛ እንዲሁም ከደርግ ጽ/ቤት እሥር ቤቶች ይልቅ ልዩ ባህሪ ያለው የማዕከላዊ ምርመራ ድርጅት እሥር ቤት ነው፡፡ በአፍ-እላፊ (መንግሥትንና መሪን በመስደብ) በእግር- እላፊ (በእግር ድንበር ተሻግሮ መሄድ) በእጅ እላፊ (በስርቆት)፣ በልብ- እላፊ (ያሰበ ይቀጣል የሚለውን ህግ በመድፈር)… ብዙ እላፊዎች አሉ፡፡ የእላፊ ወንጀሎች በፖለቲካ ከመታሠር፣ በአረንጓዴው ዘመቻ  (በምርት ዘመቻ) ከመታሠር፣ በነብስ ግድያ፣ ጫካ ገብቶ እስከ መታገል ከሚፈጠሩ እስሮች ይለያሉ፡፡ ማዕከላዊ፤ ሰውና ዕድሜን አይመርጥም፡፡ ለፆታና ቀለም አያደላም፡፡ ማዕረግ አይለይም- ከየማዕረጉ ያሥራል። ዕብድም ከተገኘ ይታሠራል፡፡
በዚህ ምክንያት አንዳንድ ተሳላቂዎች፣ ዲሞክራሲያዊ እሥር ቤት ነው ይሉታል! ሌላው ባህሪው “የአደራ እሥረኛ” የሚባሉ እሥረኞችን ማጎሩ ነው፡፡ ማንም እማይነካቸው፣ ያስቀመጣቸው ሰው (ባለሥልጣን) ብቻ፤ ፈቅዶ ወዶ በቃኝ ሲል የሚያስወጣቸው፣ እሥረኞች ናቸው፡፡ በምድር የሰጠሁህን በሰማይ እቀበልሃለሁ ብሎ ነው ማለት ነው፡፡ የገዛ አባላቱ እገዛ መሥሪያ ቤታቸው ማዕከላዊ፤ ባለ ተራ ሲሆኑ የሚታሠሩም አሉ፡፡ የደርግ ኢሰፓአኮ ሥር ያሉ ድርጅቶች የመኢሶን፣ የወዝሊግ፣ የማሌሪድ፣ የሰደድ፣ የኢጭአት ሰዎችም ታስረውበታል፡፡ ማዕከላዊ ሁሉን ጎራሽ ነው፡፡ ለማንም አይተኛም፡፡ ኢትዮጵያ የእሥር ቤትም፣ የእስረኛም፣ ድሃ ሆና አታውቅም፡፡
ከወንጀል ጋር በተያያዘ ሲታሰብ፣ እሥር ቤት መቼም አላስፈላጊ የሆነበት ጊዜ የለም፡፡ ችግሩ የሚመጣው አላግባብ መታሠር ሲመጣ ነው፡፡ በግርፊያ ካላመንክ ወዮልህ መባል ሲከሰት ነው፡፡ የዘገየ ፍርድ ከአለመፈረድ አንድ ነው በሚባልበት ዓለማችን፤ ፍርድ ቤት ሳይቀርቡ፣ ያለ አንዳች ውሳኔ ጨለማ ቤት ሆኖ ዓመታትን መቁጠር ሲኖር ነው ዘግናኝ የሚሆነው፡፡ ዐይንን ተጨፍኖ “ቤርሙዳ” ሲገባ ነው ፍፁም ሰቅጣጭ የሚሆነው፡፡ ለመሆኑ የገራፊዎች የሥራ ልምድ ሌላ ሥራ ለመያዝ ይረዳቸው ይሆን?! ወይስ ወደ ሌላ እሥር ቤት ይዘዋወራሉ፡፡ የሰራተኛ ማስተዳደሪያ መሥሪያ ቤት ሕግ አያውቃቸውም ማለት አይቻልም፡፡ ወይም አንዳንዴ ይቻላል! ዓመት በዓል ሲመጣ ለእስረኞች ምህረት ማድረግ በየመንግሥታቱ የተለመደ ይመስላል፡፡ ቤተሰብም መቼም ተስፋ ማድረጉ አይቀርምና ይጠብቃል! በዛሬውም የክርስቶስ ልደት ዋዜማ የምሕረት ተስፋ ማግኘቱ፣ የአያሌ ቤተሰቦችን ተስፋ ማለምለሙ፣ ደስታን መፍጠሩ አይቀሬ ነው፡፡ ማዕከላዊ ሙዚየም ይሆናል የሚለውም ቃል ሲተገበር፣ የማዕከላዊን ውስጣዊ ገፅታ እንደ ጎብኚ የማየት ዕድሉን ህዝብ ማግኘቱ አንድ ፍሬ ነገር ነው! ጥሩ ጅማሬ ነው፡፡ አዝማሚያውን ማስፋፋት ነው። ብዙ ገናዎች፣ መውሊዶች እና ሌሎች በዓላት፤ መልካም ዜና ያመጡልን ዘንድ ተስፋ እናድርግ!!
“ጊዜ የሥልጣን እጅ ነው” የሚለን ሎሬት ፀጋዬ ገ/መድህን፤ ሁሉ ነገር በራሱ ጊዜ እንደሚመጣ አስረጅ ማቅረቡ ነው! መልካም ድርጊት የምንፈፅመው ሲጨንቀንና ሲጠበን መሆን የለበትም፡፡ ቀናነት ውስጣችን ሁሌም መኖር አለበት፡፡ ስንቸገር ብቻ ደግ የምንሆን ከሆነ ግን አጉል ተስፋን ነው የምንሰብከው፡፡ በቅሎ የጠፋበት የተሰቀለ ኮርቻ ገልጦ አየ ማለት ይሆናል፡፡ መልካም ገና!!

 የበሬ ዋጋ ከዓምናው በእጅጉ አሻቅቧል

   በዘንድሮው የገና በዓል ገበያ የተለያዩ አካባቢዎችን የዳሰስን ሲሆን በተለምዶ ሾላ የሚባለውና ከኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት አጠገብ በሚገኘው ገበያ ዶሮዎች እንደየ መጠናቸው ከ210 ብር እስከ 350 ብር እየተሸጡ ይገኛሉ፡፡ አይብ በኪሎ 120 ብር፣ ቅቤ ከ180 እስከ 250 ብር የሚሸጥ ሲሆን የሀበሻም የፈረጅም እንቁላል አንዱ በ4 ብር ሂሳብ  ይገኛል፡፡
ከዚሁ ገበያ ከፍ ብሎ በሚገኘው ሰሜን ማዘጋጃ፣በግ ከ2000 እስከ 4200 ብር ባለው ዋጋ  እየተሸጠ ነው፡፡ በሰሜን ማዘጋጃ አካባቢ በሚገኙ ወፍጮ ቤቶች ያነጋገርናቸው የእህል ነጋዴዎች፣ 1ኛ ደረጃ ማኛ ጤፍ በኪሎ 29 ብር፣ ሰርገኛ 23 ብር እንደሚሸጥና ክክ ምስር በኪሎ 53 ብር፣ ድፍን ምስር 28 ብር እንደሚሸጥ ገልጸውልናል፡፡    ፒያሳ አትክልት ተራ ባደረግነው ቅኝት፣ ሰሞኑን 9 እና 10 ብር ይሸጥ የነበረው ሽንኩርት ለበዓሉ እንደየ ደረጃው ከ12 እስከ 16 ብር እየተሸጠ ሲሆን ነጭ ሽንኩርት በኪሎ ከ45-50 ብር፣ ዝንጅብል 80 ብር፣ ቲማቲም ከ8-10 ብር፣ ቃሪያ በኪሎ 28 ብር ይሸጣል፡፡ በተለያዩ ባልትና ቤቶች ተዘዋውረን እንዳየነው፤ የተፈጨ በርበሬ በኪሎ  140 ብር፣ ኮሮሪማ 120 ብር፣ ዝንጅብል 80 ብር እየተሸጠ ይገኛል፡፡
በመገናኛ ሾላ ገበያ፣ በሬ ከ14ሺ- 20ሺ ብር በሚደርስ ዋጋ የሚገኝ ሲሆን ዶሮ ከ180 ብር እስከ 400 ብር እየተሸጠ ይገኛል፡፡ በዚሁ ገበያ ቀይ ሽንኩርት 16 ብር፣ ነጭ ሽንኩርት 55 ብር፣ ድንች በኪሎ 8 ብር የሚሸጥ ሲሆን የሀበሻ ቀይ ሽንኩርት በኪሎ 25 ብር እየተሸጠ ነው፡፡
በአቃቂ ቄራ ገበያ የበሬ ዋጋ ከባለፈው ዓመት በእጅጉ ማሻቀቡን ነጋዴዎች የገለጹልን ሲሆን የበግና የፍየል ዋጋ እምብዛም ጭማሪ አላሳየም፡፡ ባለፈው ዓመት ለገና በዓል የበሬ ዋጋ ከ7 ሺህ እስከ 22 ሺህ ብር እንደነበር ያስታወሱት ነጋዴዎች፤ በዘንድሮ በዓል ትንሹ 12 ሺ ብር፣ መካከለኛው 25 ሺ እንዲሁም ትልቁ 38 ሺ ብር ዋጋ ማውጣቱን ለአዲስ አድማስ አስረድተዋል፡፡
የበግ ዋጋ ላይ እምብዛም ለውጥ አለመኖሩን ለማወቅ የቻልን ሲሆን ከ1700 ብር እስከ 3500 ብር ሲሸጥ ሰንብቷል፡፡ የበግም ሆነ የበሬ ዋጋ በበአሉ ዋዜማ (ዛሬ ማለት ነው) ሊያሻቅብ እንደሚችል ነጋዴዎች ነግረውናል፡፡ የበሬ ዋጋ ከወትሮው ለምን አሻቀበ ስንል የጠየቅናቸው ነጋዴዎች፤ በስፋት ከብቶች በተለይ በኦሮሚያ ክልል ወደ ማደለቢያ በረቶች እየገቡ ተቀልበው ወደ ውጪ ኤክስፖርት እየተደረጉ በመሆኑ በቀላሉ ከገጠር ወደ ከተማ አምጥቶ መሸጥ ባለመቻሉ መሆኑን አስታውቀዋል፡፡ መጪው ጊዜ የሰርግ ወራት መሆኑም በበሬ ዋጋ ላይ ጭማሪ ማስከተሉን ነጋዴዎቹ  ጠቁመዋል፡፡
ይህ በእንዲህ እንዳለ ከገና በዓል ጋር የተያያዙ እንደ ገና ዛፍ ያሉትን ዋጋም በተለያዩ መደብሮች የቃኘን ሲሆን ፒያሳ፣ ቦሌ፣ አዲሱ ገበያ እና ሜክሲኮ አካባቢ የገና ዛፍ በ180 ብር የሚገኘውን ያህል 200 ሺ ብር የሚሸጥም አይተናል፡፡ ቀይ የገና የወንዶች ኮፍያ 200 ብር፣ ጫፉ ላይ እና ዙሪያው ነጭ  የገና የሴት ኮፍያ ከ40 እስከ 60 ብር፣ ፖስት ካርዶች ደግሞ እንደ ዓይነታቸው ከ10 እስከ 35 ብር እንደሚሸጡ ለማረጋገጥ ችለናል፡፡
 መልካም የገና በዓል ይሁንላችሁ!!  

    የተባበሩት መንግስታት ድርጅት የህጻናት መርጃ ድርጅት ዩኒሴፍ በኦሮሚያና ሶማሌ ክልሎች በተቀሰቀሱ ግጭቶች ከመኖሪያ ቀያቸው የተፈናቀሉ 84 ሺህ 659 የሚገመቱ በአንደኛ ደረጃ ትምህርት የዕድሜ ክልል ውስጥ የሚገኙ ህጻናት ምንም አይነት የትምህርት አገልግሎት እያገኙ እንዳልሆነ አስታውቋል፡፡ ዩኒሴፍ ትናንት የሰጠውን መግለጫ ጠቅሶ አናዶሉ ኤጀንሲ እንደዘገበው፣ በሁለቱ ክልሎች የተከሰቱ ግጭቶች 14 ሺህ ያህል ህጻናትን ከወላጆቻቸው ጋር እንዲለያዩ ምክንያት ሆነዋል ተብሎ ይገመታል፡፡
በሁለቱም ክልሎች 120 ሺህ የሚገመቱ ዕድሜያቸው ከአምስት አመት በታች የሆናቸው ህጸናት እንዲሁም 20 ሺህ ነፍሰ ጡርና ጡት የሚያጠቡ እናቶች የአሰቸኳይ የንጥረምግብ አገልግሎቶች ድጋፍ ያስፈልጋቸዋል ያለው ዘገባው፣ ዕድሜያቸው ለትምህርት የደረሱትን ህጻናት የአንደኛ ደረጃ ትምህርት እንዲያገኙ ለማስቻል 2.9 ሚሊዮን ዶላር ያህል እንደሚያስፈልግ ዩኒሴፍ ማስታወቁን አመልክቷል፡፡

ደንበኞች ባሉበት ሆነው የአየር መንገዱን ሙሉ አገልግሎት ማግኘት ያስችላቸዋል

    የኢትዮጵያ አየር መንገድ ደንበኞቹ ባሉበት ቦታ ሆነው የአየር መንገዱን የተለያዩ አገልግሎቶችን ማግኘት የሚችሉበትን የተንቀሳቃሽ ስልክ መተግበሪያ (አፕሊኬሽን) ተግባራዊ ማድረጉን አስታውቋል፡፡
ይህ የመረጃ መተግበሪያ (አፕሊኬሽን) ደንበኞች ተንቀሳቃሽ ስልካቸውን በመጠቀም የበረራ ቲኬት መቁረጥ፣ ክፍያ መፈፀምና የበረራ ወንበር ቁጥር ባሉበት ቦታ ሆነው ለመምረጥ የሚያስችላቸው ነው ተብሏል፡፡
የገንዘብ ክፍያም በሞባይል ባንኪንግ አሊያም በኢንተርኔት መፈፀም ይቻላል ተብሏል። መተግበሪያው በጎግል ፕሌይ እና በአፕስቶር እንደሚገኝና ማንኛውም ሰው ዳውንሎድ አድርጎ የአገልግሎቱ ተጠቃሚ መሆን እንደሚችል አየር መንገዱ ለሀገር ውስጥ ጋዜጠኞች በሰጠው መግለጫው አስታውቋል፡፡
ደንበኞች ከአማርኛ ቋንቋ በተጨማሪ በእንግሊዝኛ፣ ፈረንሳይኛ፣ ጀርመንኛ፣ አረብኛና ሌሎች የውጭ ሃገር ቋንቋዎች አገልግሎቱን ማግኘት እንደሚችሉ ታውቋል፡፡ ይህ መተግበሪያ በአየር መንገዱ የኢንፎርሜሽን ቴክኖሎጂ ባለሙያዎች መሰራቱ የተገለፀ ሲሆን አገልግሎቱ ለደንበኞች ምቹና ቀልጣፋ አገልግሎት መስጠት እንደሚያስችል የአየር መንገዱ ዋና ሥራ አስፈፃሚ አቶ ተወልደ ገ/ማርያም ገልፀዋል፡፡

     ሱዳን ከኢትዮጵያ ጋር በባቡር መስመር የመገናኘት እቅድ እንዳላትና ከካርቱም ኢትዮጵያ ድንበር የሚደርስ የባቡር መስመር በቅርቡ መገንባት እንደምትጀምር የሱዳኑ ፕሬዚዳንት ኦማር አልበሽር አስታውቀዋል፡፡
ፕሬዚዳንቱ ከትናንት በስቲያ ከካርቱም ወደ ሌላኛዋ የሱዳን ከተማ ኤልገዚራ የተገነባውን የባቡር መስመር መርቀው ስራ ባስጀመሩበት ወቅት ደቡብ ሱዳን፣ ኢትዮጵያና ሱዳንን የሚያገናኝ ረጅም የባቡር መስመር ሃገራቸው እንደምትገነባ ተናግረዋል፡፡  
ወደ ኢትዮጵያ የሚገነባው የባቡር መስመር የራሷ ወደብ ለሌላት ኢትዮጵያ በእጅጉ ጠቃሚ መሆኑንና ወደ ደቡብ ሱዳን የሚዘረጋው መስመርም በተለይ ከኬንያና ከኡጋንዳ ጋር የሚያገናኝ በመሆኑ በምስራቅ አፍሪካ ማህበረሰቦች መካከል መቀራረብና የንግድ ቅልጥፍናን ይፈጥራል ብለዋል- ፕሬዚዳንቱ፡፡
አሜሪካ በሱዳን ላይ ጥላው የነበረውን ማዕቀብ ካነሳች በኋላ ባለፉት ሁለት ዓመታት የሃገሪቱ ኢኮኖሚ በከፍተኛ ደረጃ መነቃቃት መጀመሩን የዘገበው ሱዳን ትሪቡን፤ አዳዲስ የባቡር መስመሮችን እየገነባች ከመሆኑ በተጨማሪ አሮጌዎቹንም እየጠገነች ስራ እያስጀመረች መሆኑን ገልጿል፡፡
በሌላ በኩል የኢትዮ-ጅቡቲ ስታንዳርድ ጌጅ የባቡር መስመር ከታህሳስ 25 ቀን 2010 ዓ.ም አንስቶ የመንገደኞች የባቡር ትራንስፖርት አገልግሎት መስጠት የጀመረ ሲሆን በ4 ቢሊዮን ዶላር ወጪ የተገነባው የባቡር መስመሩ፣ የመንገደኞችና የጭነት ትራንስፖርት ዋጋም ወጥቶለታል፡፡    
ለእቃ ማመላለሻ ባቡር ለአንድ ቶን በኪሎ ሜትር 1 ብር ከ75 ሳንቲም ሲሆን ለመንገደኞች ማጓጓዣ ከለቡ ተነስቶ ጅቡቲ ለመድረስ በወንበር ተቀምጠው ለሚሄዱ 503 ብር፣ በመኝታ ክፍሎች ተጠቅመው ለሚጓጓዙ እንደየ ደረጃው 671፣922 እና 1,006ብር ዋጋ ተተምኗል፡፡
ከለቡ ወደ ድሬደዋ ለመሄድ በወንበር 308 ብር እንዲሁም በአልጋ ለሚጓዙ እንደ አልጋው ደረጃ 410፣ 564 እና 616 ብር ተተምኗል፡፡ በልዩ መኝታ ክፍሎች ከለቡ ተነስተው ጅቡቲ ለሚጓዙ 1,258 ብር እና 1,341 ብር ዋጋ እንደወጣለት ታውቋል፡፡   

ዓለማችን ሊጠናቀቅ የቀናት ዕድሜ በቀረው የፈረንጆች ዓመት 2017፣ እጅግ በርካታ ክስተቶችን አስተናግዳለች፡፡ ባለፉት 12 ወራት ዓለማችን ያስተናገደቻቸውን ዋና ዋና ክስተቶች በተመለከተ የተለያዩ መገናኛ ብዙኃን ከሰሞኑ ለንባብ ካበቋቸው አበይት መረጃዎች መካከል ጥቂቶቹን መርጠን እነሆ ብለናል!
የትራምፕ መምጣት
የፈረንጆች አመት 2017 አሃዱ ብሎ ሲጀምር፣ አለማችን ካስተናገደቻቸው ዋነኛ መነጋገሪያ ጉዳዮች መካከል የዶናልድ ትራምፕ በዓለ ሲመት አንዱ ነበር፡፡ ለወራት በዘለቀው የአሜሪካ ፕሬዚዳንታዊ ምርጫ የቅስቀሳ ዘመቻ ላይ “ሙስሊሞችን ከአገሬ አባርራለሁ” የሚለውን ጨምሮ በርካታ አወዛጋቢ ጉዳዮችን በአደባባይ ሲያስተጋቡ የከረሙት ትራምፕ፤ ዲሞክራቷን ተፎካካሪያቸው ሄላሪ ክሊንተንን አሸንፈው መንበረ ስልጣኑን ይረከባሉ ብሎ የጠበቃቸው ብዙ ሰው ባይኖርም፣ ድል ቀንቷቸው አለምን አስገርመዋል፡፡
በአመቱ የመጀመሪያ ወር ላይ በደማቅ በዓለ ሲመት፣ 45ኛው የአሜሪካ ፕሬዚዳንት የሆኑት ትራምፕ፤ አመቱን ሙሉ አለምን የሚያስገርሙና በአነጋጋሪነታቸው ጎልተው የወጡ እርምጃዎችን በመውሰድ ነበር ያሳለፉት፡፡
ሰብዓዊ ቀውሶች
በዓለማችን የከፋው የሰብዓዊ ቀውስ ሰለባ እንደሆነች አመቱን አገባድዳለች - በእርስ በእርስ ጦርነት የምትታመሰዋ የመን፡፡ ከ17 ሚሊዮን በላይ የመናውያን የሚልሱ የሚቀምሱት አጥተው አመቱን በርሃብ አልፈውታል፡፡ በአገሪቱ የተቀሰቀሰው የኮሎራ ወረርሽኝም 1 ሚሊዮን ያህል ዜጎችን ሲያጠቃ፣ ከ2 ሺህ በላይ የሚሆኑትን ደግሞ ለሞት ዳርጓል፡፡
የዓለም ባንክ ባወጣው አመታዊ ሪፖርት እንዳለው፤ ባለፉት 12 ወራት ውስጥ በ45 የአለማችን አገራት ውስጥ የሚገኙ 83 ሚሊዮን ያህል ዜጎች የርሃብ አደጋ ተጠቂና የአስቸኳይ የምግብ እርዳታ ፈላጊ ነበሩ፡፡ ይህ ቁጥር ከሁለት አመታት በፊት ከነበረው ጋር ሲነጻጸር፣ በ70 በመቶ ጭማሪ አሳይቷል ተብሏል፡፡
የተፈጥሮ አደጋ
የፈረንጆች አመት 2017 ከአፍሪካ እስከ አሜሪካ፣ ከእስያ እስከ ደቡብ አሜሪካ፣ በተለያዩ የአለማችን አገራት በርካታ ቁጥር ያላቸው የተፈጥሮ አደጋዎች የተከሰቱበትና ከፍተኛ ጥፋት ያደረሱበት ነበር፡፡ 2017 የካሊፎርኒያና የፖርቹጋልን ጨምሮ በርካታ የሰደድ እሳቶች የተከሰቱበት ዓመት ነበር፡፡ ከአሜሪካዎቹ ሃሪኬኖች እስከ አየርላንድ አውሎንፋሶች ድረስ እጅግ ከፍተኛ ጥፋት አስከትለዋል፡፡
ሰሜን ኮርያ
ሰሜን ኮርያ ከመቼውም ጊዜ በበለጠ ዘንድሮ በሚሳኤል ሙከራና በኒውክሌር ማስፋፋት የተጠመደችበት ሆኖ ነበር ያለፈው፡፡ የተባበሩት መንግስታት ድርጅት ማዕቀብም ሆነ የአሜሪካና የሌሎች አገራት ዛቻና ማስፈራሪያ ያልበገራት ሰሜን ኮርያ፤ ባለፉት 12 ወራት ውስጥ ከ12 ጊዜያት በላይ የባለስቲክ ሚሳኤል ሙከራዎችን አድርጋለች፡፡ ሰሜን ኮርያ ወሩ በገባ በሁለተኛው ሳምንት ወደ ጃፓን ባህር ባስወነጨፉት ሚሳኤል የተጀመረው የሚሳኤል ሙከራ፤ የአካባቢውን አገራት ብቻ ሳይሆን የተቀረውን አለምም ያስደነገጠና ስጋት ውስጥ ከትቶ ያለፈ ነበር፡፡
ሰሜን ኮርያና አሜሪካ፤ በቃላት ጦርነትና በፍጥጫ ነበር አመቱን ያገባደዱት፡፡ ትራምፕ እና ኪም ጁንግ ኡን አንዳቸው ሌላኛቸውን በቃላት ሲያዋርዱና ሲዘልፉ፣ ከአሁን አሁን ተታኮሱ በሚል አለምን ሲያስጨንቁ፣ አመቱን በቃላት ጦርነት አገባድደውታል፡፡
የሮሂንጋ ሙስሊሞች መከራ
የፈረንጆች 2017 በማይንማር ለሚኖሩ የሮሂንጋ ሙስሊሞች፣ ከመቼው ጊዜ የከፋ የመከራና የስቃይ ሆኖ ነበር ያለፈው፡፡ የማይንማር ወታደሮች በወራት ጊዜ ውስጥ ከ6 ሺህ 700 በላይ የሮሂንጋ ሙስሊሞችን መግደላቸው ተነግሯል፡፡ ቤታቸው በእሳት ሲጋይባቸው፣ ወገኖቻቸው አይናቸው እያየ ሲታረዱባቸው፣ ነፍሳቸውን ለማዳን በየጫካው የተበተኑና አገራቸውን ጥለው ወደ ጎረቤት ባንግላዴሽ የተሰደዱ የሮሂንጋ ሙስሊሞች ከ600 ሺህ በላይ እንደሚደርሱም የመገናኛ ብዙኃን ዘግበዋል፡፡  የተባበሩት መንግስታት ድርጅትም ሆነ አለማቀፉ ማህበረሰብ የሚገባውን ያህል ትኩረት አልሰጠውም የተባለው የሮሂንጋ ሙስሊሞች ቀውስ፤ ለመጪው 2018 የፈረንጆች አመትም ባለበት ሁኔታ ይቀጥላል ተብሎ እየተነገረ ነው፡፡
የሽብር ጥቃቶች
ግንቦት 22 ቀን ምሽት ላይ…
በእንግሊዟ ማንችስተር የተዘጋጀውን የአርያና ግራንዴ የሙዚቃ ኮንሰርት ለመታደም በአዳራሽ ውስጥ የተገኙ የሙዚቃ አፍቃሪያን ራሳቸውን ያላሰቡት መከራ ውስጥ አገኙ፡፡ በአዳራሹ ውስጥ የተሰማው ድንገተኛ ፍንዳታ፣ ተደጋግሞ ቀጠለ፡፡ ሁሉም ነፍሱን ለማዳን በየአቅጣጫው ተራወጠ። 22 ያህል ሰዎችን ለሞት፣ በመቶዎች የሚቆጠሩ ሌሎችም ለመቁሰል አደጋ ተዳረጉ፡፡
ልክ እንደ ማንችስተር ሁሉ፣ ከስቶክሆልም እስከ ባርሴሎና፣ ከበርሊን እስከ ፓሪስ በርካታ የአውሮፓ አገራት ከተሞች በሽብር ጥቃቶች እየተናወጡ ነበር አመቱን የገፉት፡፡ የሽብር ጥቃቱ አውሮፓ ላይ አያበቃም፡፡ አሜሪካን ጨምሮ በርካታ አገራት በአይሲስ እንዲሁም በተለያዩ ጽንፈኛ ቡድኖችና ወፈፌ ገዳዮች ሲሸበሩ ነው የከረሙት፡፡
የሙጋቤ መውረድ
አፍሪካ በአመቱ ካስተናገደቻቸው አነጋጋሪና ጉልህ ክስተቶች መካከል፣ ላለፉት 37 አመታት አገራቸውን የገዙት የዚምባቡዌው ፕሬዚዳንት ሮበርት ሙጋቤ ስልጣን መልቀቅ አንዱ ነበር፡፡ ወታደሩ በሙጋቤ ላይ መፈንቅለ መንግስት አደረገ በሚል አስደንጋጭ ዜና የጀመረው የዚምባቡዌ ጉዳይ፤ አገሪቱን ወደ ከፋ የእርስ በእርስ ግጭት ይከታታል ተብሎ ሲገመት፣ ባልተጠበቀ ሁኔታ፣ ሙጋቤ በሰላማዊ መንገድ ስልጣናቸውን ለተፎካካሪያቸው ምናንጋዋ አስረክበዋል፡፡
ዛሬም የባሪያ ፍንገላ
ሲኤንኤን አመቱ ከመጠናቀቁ በፊት ከወደ ሊቢያ ያሰማው ወሬም ሌላኛው አለምን ያስደነገጠ ጉዳይ ነበር፡፡ የባርነት ዘመን አበቃ ተብሎ ከታወጀ ከረጅም አመታት በኋላ፣ አፍሪካውያን በሊቢያ እንደ ሸቀጥ እየተሸጡና ለባርነት እየተፈነገሉ መሆኑን  የሚያትተው ይህ ዘገባ፤ ብዙዎችን አስደንግጧል፡፡ የተሻለ ኑሮን ፍለጋ ከሞት ጋር እየታገሉ አሰቃቂውን የውቅያኖስ ጉዞ ለመጋፈጥ አገራቸውን ጥለው ወደ አውሮፓ የስደት ጉዞ የጀመሩ በመቶዎች የሚቆጠሩ አፍሪካውያን፤ ሊቢያ ላይ በጨካኞች መዳፍ ላይ ወድቀው ለባርነት መሸጣቸው አለምን እያነጋገረ አመቱ ተገባድዷል፡፡
ኢየሩሳሌም
አመቱ ከመጠናቀቁ በፊት፣ አለምን ያስደነገጠ ነገር ከወደ ዋይት ሃውስ ተሰማ…
ፕሬዚዳንት ዶናልድ ትራምፕ፣ ባልተጠበቀ ሁኔታ የኢየሩሳሌምን የእስራኤል መዲናነት እውቅና እንደሚሰጡ አስታወቁ፡፡ ይህን ተከትሎ እስራኤል በደስታ ስትፈነድቅ፣ ፍልስጤምና ፍልስጤማውያን ደግሞ በቁጣ ነድደው፣ አደባባይ በመውጣት፣ ትራምፕንና አሜሪካን አወገዙ፡፡ የመካከለኛው ምስራቅ አገራት ብቻ ሳይሆኑ በርካታ የአለማችን አገራት፣ በእስራኤልና በፍልስጤም መካከል ያለውን ለዘመናት የዘለቀ የይገባኛል ውዝግብ፣ ወደ ከፋ ምዕራፍ ያሸጋገረና ተገቢነት የሌለው ነው በማለት በይፋ የትራምፕን ውሳኔ አወገዙት፡፡
የተባበሩት መንግስታት ድርጅትም የትራምፕን ውሳኔ ውድቅ የሚያደርግ ውሳኔ ለማስተላለፍ አባል አገራቱ ድምጽ እንዲሰጡ አደረገ፡፡ 128 ያህል የአለማችን አገራት ሃሳቡን ደግፈው ድምጻቸውን በመስጠታቸውም፣ የትራምፕ ውሳኔ ውድቅ ተደረገ፡፡


  ስለ ጉዳዩ አስተያየት ከሰጡ ቻይናውያን፣ 90 በመቶው እርምጃውን ደግፈውታል

   የኢንተርኔት ነጻነትን በመጣስና ጥብቅ ቁጥጥር በማድረግ የሚታወቀው የቻይና መንግስት፤ ባለፉት 3 አመታት ብቻ ህግና መመሪያዎችን ጥሰዋል በሚል ከ13 ሺህ በላይ የተለያዩ ድረ-ገጾችን በመዝጋት ከአገልግሎት ውጭ ማድረጉን ሮይተርስ ዘግቧል፡፡
ቻይና በተለይ ደግሞ ፕሬዚዳንት ዢ ፒንግ ስልጣን ከያዙ በኋላ፣በነበሩት ያለፉት አምስት አመታት ሃሳብን በነጻነት የመግለጽ መብትን በሚጥስ መልኩ በኢንተርኔት ተጠቃሚዎች ላይ የምታደርገው ጥብቅ ቁጥጥርና ቅጣት በከፍተኛ ሁኔታ ተባብሶ ቀጥሏል ያለው ዘገባው፤ የአገሪቱ መንግስት የሚሰነዘሩበትን ትችቶች ለማፈን፣ ብዙ ድረገጾችን እየዘጋ እንደሚገኝ አመልክቷል፡፡
አለማቀፍ ተቋማት የቻይናን ጥብቅ የኢንተርኔት ቁጥጥር በተደጋጋሚ ቢተቹትም፣ የአገሪቱ መንግስት ግን “ሁሉም አገራት የሚያደርጉትን ነው እያደረግሁ ያለሁት፤ በኢንተርኔት ላይ ጥብቅ ቁጥጥር የማደርገው ብሄራዊ ደህንነቴን ለመጠበቅና ማህበራዊ መረጋጋትን ለመፍጠር በማሰብ ነው” ሲል ምላሽ መስጠቱ ተነግሯል፡፡
የመብት ተሟጋች ተቋማት፤ የቻይና መንግስት የዜጎቹን መብት እየጣሰ ነው ሲሉ ቢወነጅሉትም፣ የድረገጾቹን መዘጋት በተመለከተ አስተያየታቸውን እንዲሰጡ ከተጠየቁት ቻይናውያን መካከል ከ90 በመቶ በላይ የሚሆኑት በአንጻሩ እርምጃውን እንደሚደግፉ መናገራቸውንም የሮይተርስ ዘገባ አስረድቷል፡፡
ቻይና 13 ሺህ ድረገጾችን በመዝጋቷ ሳቢያ 10 ሚሊዮን ያህል አካውንቶች ከአገልግሎት ውጭ ሆነዋል ያለው ዘገባው፤ “የአገሪቱ መንግስትም የተባለው ነገር እውነት መሆኑን አምኖ፣ ልቅ ወሲብና ብጥብጥ የሚያጭሩ መረጃዎችን የሚያሰራጩ አካላትን አደገኛ ድርጊት ለማስቆም ስል ህገወጥ ድርጊቱን ሲፈጽሙ ያገኘኋቸውን ድረገጾች ዘግቻለሁ” ብሏል፡፡

ነዋሪነቷ በአሜሪካ ፔንሲልቫኒያ ግዛት የሆነው ሜሪ ሆሮማንስኪ በከፍተኛ ድንጋጤ ክው አለች። ያየቺውን ነገር ለማመን ቸግሯት በድንጋጤ ተንቀጠቀጠች፡፡ በህልሟ ይሁን በእውኗ እርግጠኛ መሆን አልቻለችም ነበር፡፡
ህልም እንዲሆን እየተመኘች፣ አስደንጋጩን ሰነድ በድጋሚ አየቺው - 284 ቢሊዮን ዶላር! እንደተመኘቺው ህልም አልሆነም፡፡ የግዛቲቷ የኤሌክትሪክ ሃይል መስሪያ ቤት፣”ባለፈው ህዳር ወር ለተጠቀምሺው የኤሌክትሪክ ሃይል አቅርቦት፣ 284 ቢሊዮን ዶላር ክፈይኝ” የሚል ሰነድ ነው የላከላት፡፡ በፍርሃት እየተንቀጠቀጠች ወደ መስሪያ ቤቱ ደወለች፡፡
“ምን ጉድ ነው የምታሰሙኝ?!...” ስትል ከዚህ የቁም ቅዠት እንዲገላግሏት ጓጉታ ጠየቀች፡፡
“እጅግ ይቅርታ እንጠይቃለን!... የቁጥር ስህተት ፈጽመናል፤መክፈል የሚጠበቅብሽ 284 ዶላር ብቻ ነው!” የሚል ከጭንቀት የሚገላግል፣ የምስራች የሆነ ምላሽ ሰጧት - የመስሪያ ቤቱ ተወካይ፡፡
እፎይ አለች! - ቢቢሲ ነው የዘገበው፡፡


    በቀዳማዊ ቴዎፍሎስ ፓትሪያርክ ህይወትና መንፈሳዊ አገልግሎት ዙሪያ በሚያጠነጥነው መፅሀፍ ላይ ዛሬ ከቀኑ 7፡30 ጀምሮ በኢትዮጵያ ሆቴል ዳሰሳና ጥናታዊ ፅሁፍ እንደሚቀርብ የፕሮግራሙ አዘጋጆች ገለፁ፡፡
 “የፓትሪያርክ ቴዎፍሎስ አሻራዎች” በሚል ርዕስ በሚካሄደው በዚህ ፕሮግራም ላይ አቡነ ማቴዎስ (ዶ/ር)፡- የፓትሪያርክ ቴዎፍሎስ አሻራ ከትምህርት አንፃር፣ ዶ/ር አግደው ገዴ፡- የፓትሪያርኩ አሻራ ከልማት አኳያ፣ ዶ/ር ምክረስላሴ ገ/አማኑኤል፡- ከውጭ ግንኙነታቸውና ከታሪክ አንፃር፣ መምህር ዳንኤል ሰይፈሚካኤል ከቤተክርስቲን አደረጃጀት ፅንሰ ሀሳብ አንፃርና ዶ/ር አሰፋ ዘሩ፡- በአጠቃላይ በመፅሀፉ ላይ ዳሰሳ እንደሚያቀርቡ የፕሮግራሙ አዘጋጆች ጠቁመዋል፡፡  በፕሮግራሙ ላይ ፓትሪያርኩ አቡነ ማቲያስንጨምሮ የባህልና ቱሪዝም ሚኒስትሯ ዶ/ር ሂሩት ወ/ማሪያም፣ የቅርስ ጥናትና ጥበቃ ባለስልጣን ዋና ዳይሬክተር፣ የወመዘክር ሀላፊዎችና የተለያዩ የሀይማኖት አባቶች እንደሚገኙም ታውቋል፡፡