Administrator

Administrator

Tuesday, 02 January 2018 10:07

ያልታየ ዕድል!

 በመረረ ሀዘን ውስጥ እያለፈም ደስተኛ ነበር። በለቅሶ ሸለቆ መሀል፤ በሰቀቀን እንብርት ቆሞም መሣቅ ይችላል፡፡ በተለይ በትዳሩ ደስተኛ ነው። አንድ ልጁ ደመቀ ከመጣ ወዲህ ደሞ በጊዜ ቤቱ ገብቶ የልጁን ሁለት ጥርሶች ፈገግታ ሲያይ፣ ሁሉንም ነገር ይረሳዋል፡፡ ባለቤቱ በቀለችም መልካም ሰው ናት። አንዳንዴ ፊቱን ፀሀይ አክስሎት፣ አሻሮ መሥሎ ሲመጣ፣ ኮቱን ተቀብላ፤ ስማ፣ የሞቀ የእግር ውሃ ታቀርብለታለች፤ ያኔ ደስታው ሀዘኑን ይዳምጠዋል።
ከሠፈር ሲወጣም የሠፈሩን ደብር ተሣልሞ፣ “በቀኝ አውለኝ” ይላል፡፡ ዛሬ ግን በቀኝ አውለኝ ብሎ ወጥቶ ፣ በግራ ነው የዋለው፡፡ የቀጠረው ድርጅት ሥራ አስኪያጅ፣ ያልሆነ ነገር ተናግሮታል፡፡ በዚያ ላይ ጉርሻ የሚባል ነገር አልቀመሰም፤ እንዲያውም ጠዋት ሲወጣ፣ የልጁን ጡጦ ለመቀየርና ካናቴራ ነገር ሊገዛም አስቦ ነበር፡፡ አልተሳካም፡፡
ቀን አሥር ሰዐት ላይ ነበር ግምገማቸው። የሥራ ባልደረባው ታደለ፣ ከርሱ በፊት ሥራ አስኪያጁ ቢሮ ሲገባ ፈገግ ብሎ ነበር ያየው፡፡ ሲወጣም እንደዚያው ደስተኛ ነበር፡፡
እርሱ ሲገባ ግን የአለቃው ፊት ልክ አልነበረም። ከዚያም “ባለፈው ወር ምሥጉን ሰራተኛ አንተ ነበርክ፤ አሁን ግን ቁልቁል ወርደሃል፤ ስለዚህ የመጨረሻ ማሥጠንቀቂያ ነው፡፡… ሥራህን በደንብ ካልሠራህ የልጅ አባት ነኝ፤… የቤተሰብ ሃላፊ ነኝ---ማለት ተቀባይነት የለውም፡፡” አለው፤ሥራ አስኪያጁ፡፡
ጭንቅላቱ ሁለት ቦታ ተከካ፡፡
“ምንድነው ጥፋቴ?”
“ጥፋትህን እንደማታቅማ አትሁን!”
“እንዴት እያወቅኩ በእንጀራዬ እቀልዳለሁ!?”
አለቃው ጠረጴዛውን በእስክርቢቶ እየቀበቀበ፤ “…የተፈጠረልህ ዕድል አልገባህም፤ ምን ዐይነት ታላቅ ሥራ እንደሆነ  አላስተዋልክም…..”
አቀርቅሮ ዝም አለ፡፡ ሥራ ቢያገኝ፤ መቀየር ይፈልጋል፡፡ ግን ሥራ የለም፤ ሥራውን በግዱ ለምዶታል እንጂ እንደ ጥሩ ዕድል አያየውም፡፡
“ከትናንት ወዲያ ያስቀበርካቸው ሰው ምን እንደሆኑ ታውቃለህ?”
“ጭምጭታ ሠምቻለሁ፣ አሜሪካ ሀገር የኖሩ ፕሮፌሰር ናቸው አሉ…”
”እርሳቸውን የሚያህል፣ ሀገር የሆነ ሰው፣ ለማስቀበር ብቃት አለኝ ብለህ ታምናለህ?”
“በፍፁም!”
“የስንተኛ ክፍል ተማሪ ነህ?”
“አምስተኛ”
“አየኸው ልዩነታችሁን!”
አቀርቅሮ ለአፍታ በዝምታ ከቆየ በኋላ፤ “…ምንድነው ጥፋቴ ግን…?”
“ጥፋትህ…ጥፋትህ?”
በዓይኖቹም በጆሮዎቹም ጠበቀ- መልሱን፡፡
“አንደኛ…”
“አ?
“አስክሬን ተሸክመህ በፈገግታ መዋልህ፤ ያን ያህል የሀገር ዋርካ ወድቆ ጠላትህ የሞተ ይመስል…”
“እኔ ግን ፈገግ አላልኩም፣ እንዲያውም እህትየው በጣም ሲያለቅሱ ሆዴ ባብቶ እንባዬ ሲመጣ.. ሀሳቤን ወደ ትንሹ ልጄ ወሰድኩትና የጥርሶቹ ፈገግታ ሲታሰበኝ፣ ምናልባት ፈገግ ብዬ ይሆናል፡፡ ሌላ ምን ፈገግ የሚያሰኝ ነገር አለ? ያው ልጄ ነው። ለሥራ የሚያበረታኝም፣ የሚያነቃቃኝም እርሱ ነው፡፡ ከወለድኩ በኋላ… ህይወቴ ተለውጧል፡፡”
“ባትወልደው ይሻላል…”
“ለምን ጌታዬ…ፈጣሪ የሰጠኝን…”
“እርሱም እንዳንተ ሬሳ ተሸክሞ የሚሥቅ ጅል ነዋ የሚሆነው!”
ሀዘን ልቡን ሰበረው፡፡ ሥራውን ጥሎ ሊወጣ አስቦ ነበር፡፡ የቤት ኪራዩ፣ የልጁ ነገር፣ የሚስቱ ህይወት..ገታው፡፡
ስድብ ጠገበ፡፡ ዘለፋና ንቀት ፈሰሰበት፡፡
“የዛሬ ስድስት ወር የሞቱት ፕሮፌሰር ወንድም ግን ሸልመውኝ ነበር፡፡…” አለና፤ ከአፉ ያመለጠው ያህል  ደንግጦ ዝም አለ፡፡
“ዕድለኛ ነህ አልኩህ’ኮ!... ከፕሮፌሰሮች ጋር ትውላለህ”
“ኡይ ጋሽዬ --- ሰርግ ላይ እኮ አይደለም፣ ቀብር ላይ ነው፡፡ በለቅሶ ላይ ማንም ይገኛል፡፡ ሥልጣንና ዕውቀትም አይደለም፡፡ የኔ ቢጤውስ ይመጣ የለ!?”
“አይደለማ! አንተ’ኮ… የታላላቅ ሰዎችን አስክሬን ትሸከማለህ፤ የህይወት ታሪካቸው ሲነገር ታደምጣለህ፡፡ ላንተ ዩኒቨርሲቲ ነው ይሄ ዕድል!... እኔ አሜሪካ የኖርኩት፣ የሰው ሽንት ቤት እያጠብኩ ነው--”
“ሬሳ መሸከም ዕድል ነው ጋሼ?”
“የማንም ድሃ ሬሳ እንዳይመስልህ… የምትሸከመው..”
“…ቄሱ፤ ከሞተ አንበሳ በህይወት ያለ እንትን ይሻላል ነበር ያሉት--”
“በቃ ዝጋ!  ልታስተምረኝ ነው!”
ሀገር ቤት ሄዶ ሚስቱን በቀለችን ያገባበት ቀን ትዝ አለው፡፡ ሙሽራ ሆኖ ኮትና ሱሪ አድርጎ፣ ቬሎ ያጠለቀች ሚስቱን ዐይነ ርግብ ገልጦ ሲስማት፣ እልልታው አሰከረው፡፡ እልልታና ሣቅ ከረሳ ቆይቷል፡፡ ውሎው ለቅሶ ነው፤ ቀብር ነው፡፡ ድንግርግር አለው፡፡ ሙሾውን እንደ ዘፈን ለምዶታል፤ ብዙ ግጥሞችም ያውቃል፡፡ በተለይ ከባላገር የመጡ አልቃሾች፣የሚደረድሩት ቅኔ ያሥደንቀዋል፡፡
ኸረ ሚዜው ደሃ ነው፤ ሽቶው ውሃ ነው፡፡
ክንዱን በክንድዋ ቆልፎ ወደ መኪና ሲገባም ተዐምር ነበር የሆነበት፡፡ በልቡም ሥራ ሊቀይር አሥቦ ነበር፡፡ ሚስቱ እስካሁን ሥራውን አታውቅም፡፡ መርካቶ የሚሠራ ነው የሚመሥላት፡፡ አንዳንዴ በጎ ሰዎች አግኝተው፣ ጉርሻ የሰጡት ቀን፣ ሥጋ ይዞ ሲገባ፤ ብርቱካን ሲሸምት-- በለስ የቀናው ይመሥላታል፡፡
አንዴ በተለይ ሚኒስትር የነበሩ ሰው ቀብር ላይ አስከሬናቸውን ተሸክሞ ሄዶ፣ ሥርዐተ ቀብር ከተፈፀመ በኋላ ስለ ሰውየው ታሪክ ሲሰማ፣ እንባውን መቆጣጠር አቃተው፡፡ ጓደኞቹ ሁሉ የጎሪጥ እያዩ በትዝብት አላገጡበት፡፡ ኋላ እንደሚተርቡት አሰበ። ግን ምንም ማድረግ አልቻለም፡፡
በተለይ ሰውየው በየገጠሩ የአንደኛ ደረጃ ትምህርት ቤቶችን ለመክፈት ያደረጉትን ጥረት፤ ከሥራ ጊዜያቸው በተጨማሪ በትርፍ ጊዜያቸው ሳይቀር፤ የገጠር ትምህርት ቤቶችን እየጎበኙ፣ ጎበዝ ተማሪዎች እንዲሸለሙ በማድረግ፣ የድሀ ልጆችንም በግላቸው እየረዱ፣ የህይወት ዘመናቸውን እንደፈፀሙ ሲሰማ አለቀሰ፡፡
“የዚህ ዐይነት ሰው ቢገጥመኝ፣ዛሬ እኔ እዚህ አልገኝም ነበር፡፡” ብሎ ነው - ለራሱ ያለቀሰው፡፡
መጨረሻ ላይ የሚኒስትሩ ወንድም ወደ ቤት ሊመለሱ ሲሉ፣ በእጅ ምልክት ጠሩትና፣ በጆሮው “አንተ ትልቅ ሰው ነህ፤ ልብህ እንዴት እንደተነካ አይቻለሁ፤ ወንድሜ እንዳንተ ላሉት ምስኪኖች ኖሮ የሞተ ወገን ወዳድ ነበር!” ብለው አምስት መቶ ብር በትንሽ ፖስታ ጠቅልለው በእጁ አሥያዙት፡፡ ደነገጠ፡፡ ድንጋጤው ለረጅም ሰዓታት አልለቀቀውም ነበር፡፡ የዛሬ ወር ገደማ---
እጁን የኋሊት አድርጎ በሀሳብ ጭልጥ እንዳለ፤ “ይህ የመጨረሻ ዕድልህ ነው!... አሁን መሄድ ትችላለህ!” አለው አለቃው፡፡ መረረው፡፡ በሌላ በኩል ደግሞ ያ ሁለት ጥርሶቹን ብልጭ የሚያደርግ ልጁ ትዝ አለው፡፡ የህይወቱ ተስፋ፣ የመኖሩ ጉልበት እርሱ ነው፡፡
ባለቤቱ በተራዋ ፊቱ ድቅን አለችበት፡፡ እያሰላሰለ  አጎንብሶ ሲወጣ፤
“ምን አለህ?...ምን አለህ?” አሉት ጓደኞቹ፡፡
መልስ አልሰጠም፡፡ “በቃ፤ ከዛሬ ጀምሮ ሬሳ አልሸከምም!” ብሎ በቀጥታ ወደ ቤቱ አመራ፡፡
 ቤት ሲሄድ፤ “ምነው በዛብህ! ሥራ የለም እንዴ?”
በዝምታ ፊቱን ወደ ግድግዳ መልሶ ተኛ፡፡ ልጁም አልጋው ጥግ ላይ ተኝቷል፡፡
እንቅልፉ እምቢ ሲለው፣ ጉርሻ የተቀበለበትን ፖስታ ድንገት ከኪሱ አገኘው፡፡ ለካ ውስጡ ያላያት ብጣሽ ወረቀት ነበረች፡፡  
“እንዳንተ ላለው ሀገር ወዳድ ወጣት፣ ልቤና በሬ ክፍት ነው፡፡ ደስ ባለህና ሥራ በፈለግህ ጊዜ “አድማስ” የተባለው ባለ አራት ኮከብ ሆቴል ብቅ በል፡፡ ስልጠና ላዘጋጅልህ ፍቃደኛ ነኝ--”
እንደ እብድ ብድግ ብሎ ከቤቱ ወጣ፡፡ ለካስ ዕድል አለ!!

  አንዳንድ ተረት አድማጭ ሲያጣ ተደጋግሞ ይነገር ዘንድ ግድ ይሆናል፡፡ ያ ከዓመታት በፊት ያቀረብነው ተረት ስለ ጅቦቹና ስለ አህዮች ነው፡፡ ጅቦቹም፣ አህዮቹም ዛሬም አሉ፡፡ ስለዚህ ደግመን እንተርከዋለን፡፡
ከዕለታት አንድ ቀን ሶስት አህዮች በጠፍ ጨረቃ ሣር ሊግጡ ይወጣሉ-እንደ ሰው፡፡
አንድ ሣሩ የለመለመ መስክ ያገኙና መጋጥ ይጀምራሉ፡፡ ጥቂት እንደጋጡ ጅቦች ይመጡና ይከቧቸዋል፡፡ ጅቦቹ መደፈራቸው አናዷቸዋል፡፡ ስለዚህ ሊፈርዱባቸው ችሎት ተቀመጡ፡፡
1ኛ ጅብ ዳኛ፡- የመጀመሪያዋ አህያ እንድትቀርብ ያዛል፡፡
አህያ ገባች፡፡
የማህል ጅብ ዳኛ፡- “ወይዘሮ አህያ፤ በጠፍ ጨረቃ፣ በእኛ ግዛት፣ ሣር ልትግጪ ለመውጣት የቻልሺው ማንን ተማምነሽ ነው?”
1ኛ አህያ፡- “አምላክን ተማምኜ ነው፡፡ አምላኬ ምንም አደጋ እንዳይደርስብኝ ይጠብቀኛል፡፡ አደጋም ከደረሰብኝ በሆነ መንገድ ይበቀልልኛል፡፡ ለእሱ ምን ይሳነዋል?”
ጅቡ ዳኛ ወደ ጥግ እንድትቆም ያዟታል፡፡
“ሁለተኛዋ አህያ ግቢ” ይላሉ፡፡
ሁለተኛዋ አህያ ገብታ ትቆማለች፡፡
የመሀል ዳኛው ጅብ፡- “ወይዘሮ አህያ፤
በጠፍ ጨረቃ፣ በእኛ ግዛት፤ ሣር ልትግጪ ለመውጣት ያስቻለሽ ድፍረት ከየት መጣ? ማንን ተማምነሽ ነው?”
ሁለተኛዋ አህያ እንዲህ ስትል መለሰች፡-
“ጌታዬ፣ ባለቤቱን፣ እሱን ተማምኜ ነው፡፡ ማንም ጉዳት ቢያደርስብኝ ይበቀልልኛል፡፡ ንብረቱ ነኝና ንብረቱን በሚነካ ላይ እርምጃ መውሰዱ አይቀርም!”
ጅቡ መሀል ዳኛ፤ “ወደ ዳር ቁሚ” አላት፡፡
አህዩት ወደ ዳር ቆመች፡፡
“ሦስተኛዋ አህያ ግቢ” አሉ፤ የቀኝ ጅቡ ዳኛ፡፡
ገባች፡፡
“ወይዘሮ አህያ፤ በጠፍ ጨረቃ፣ በእኛ ግዛት ሣር ልትግጪ የወጣሽው ማንን ተማምነሽ ነው?”
ሦስተኛዋ አህያ መለሰች፡-
“እናንተ ጌቶችን፤ ደጋጎቹን ጅቦች ተማምኜ ነው፡፡ ሩህሩህ በመሆናችሁ እንደማትጨክኑብኝ ስለማውቅ ነው!”
ወደ ጎን እንድትቆም ታዘዘች፡፡ የተባለችውን አደረገች፡፡
ሦስቱ ዳኞች ጅቦች ተመካከሩ፡-
“ያችን አምላክን የተማመነችውን ብንበላት ዕውነትም ነገ ከነግ-ወዲያ አምላክ ይበቀለናል”
“ጌታዋን የተማመነችውን ብንበላት፣ ነገ ከነግ-ወዲያ፣ ጌታዋ ፍለጋ ከወጣና ካገኘን አይምረንም”
“እቺን በእኛ የተማመነችውን ብንበላት ማን ይጠይቀናል?”
“ዕውነት ነው የማንጠየቅባትን ብንበላ ነው ሰላም የምናገኘው!”
በሃሳቡ ተስማምተው ሁለቱን አሰናብተው ሶስተኛዋን ተቀራመቷት፡፡
* * *
ከማያስተማምን ሰለባ የሚያስተማምን ሰለባ ይሻላል-ለበይው! የሀገራችን ፖለቲካ ህይወት በዚህ ተረት የተመሰለውን ዓይነት ነው! ስንቱ ካድሬ ቀልጧል! ስንቱ ባለሥልጣን ተበልቷል! ስንቱ ጅል “ሆዱን ያየ ሆዱን ተወጋ” ሆኗል! ስንቱ ነብሰ ገዳይ “አስተማማኝ መሳሪያ ነኝ”፣ ማንም አይነካኝ” ሲል፤ በሠፈረው ቁና ተሰፍሯል? ስንቱ በሰው ግዛት ሲግጥ ተግጧል! የሚገርመው አሁንም ባለተራው ታማኝ ነኝ እያለ እጁን አጣጥፎ መቀመጡ ነው! ክቡ ቀለበት “በዲሞክራሲያዊ” መንገድ ሰው መዋጥ መሰልቀጡን ይቀጥላል፡፡ በመላከክ (Blame-Shifting) አንዳች ፍሬ የምናገኝ እየመሰለን፣ በመጠቆም እንኮራለን! በማስወጋት እንተማመናለን! ሎሬት ፀጋዬ ገ/መድህን፡-  “እንቅልፍ ነው እሚያስወስድህ” በሚለው ግጥሙ…
ትቻቸዋለሁ ይተውኝ
አልነካቸውም አይንኩኝ
ብለህ ተገልለህ ርቀህ
ዕውነት ይተውኛል ብለህ
እንዴት ተስፋ ታደርጋለህ?
የተወጋ በቅቶት ቢተኛ፣ የወጋ መች
እንቅልፍ አለው
የጅምሩን ካልጨረሰው….” የሚለን ባላንጣችን፤ መቼም እንደማይተኛልን ለማስገንዘብ ነው! ልብና ልቦና ይስጠን፡፡
ማርክ ትዌይን ስለ ተራ ተርታ ሰዎችና ስለ ደናቁርት የሚያስገነዝበንን ነገር አንርሳ፡-
“ካለህበት የላቀ ቦታ ጎትተው ያወርዱህና በእነሱ ሜዳ፣ ባገኙት ልምድ በመጠቀም ያሸንፉሃል!”
ዛሬም ዘዴው ያው ነው!
ፍርድ እንዳይዛባ ብለን ብዙ መመሪያ አውጥተናል፡፡ የመጣነውን መንገድ ርዝመት በክፋታችን ልክ እንዳንለካ መጠንቀቅ ይገባናል፡፡
All men are equal but some men are more equal (ሁሉም ሰዎች እኩል ናቸው፡፡ አንዳንድ ሰዎች ግን የበለጠ እኩል ናቸው እንደማለት ነው) ይለናል - ጆርጅ ኦርዌል በ “አኒማል ፋርም” ውስጥ። የእኛው ሎሬት ፀጋዬ ገብረመድህን ጥሩ አድርጎ ያብራራዋል፡-
“ሞትን ለሚሻ ሞትን ነው መንፈግ!
ህይወትን አለመቸር፡፡
ማህል ቤት ነው ጥቅም የሚሰጥ፡፡
ሰው ሆኖ ካሹት ጥቅም የማይሰጥ የለም!” ይለናል፡፡ ይህ እንግዲህ ነገ ለሚገደልና እባካችሁ መሞቴ ካልቀረ አሁኑኑ ለምን አትገድሉኝም? ለሚለው እሥረኛ የሰጡት ምላሽ ነው፡፡ ይሄ ሟች ዓርበኛ፤
“የሚያባርረኝ ጣሊያን እንቅፋት መትቶት በሞተ ነብስ-ገዳይ ተብዬ ታሠርኩኝ እንጂ፤ እኔስ ዓርበኛ አይደለሁም” የሚል ነው! ግፍ ይህ ወሰንህ፣ ይህ ዲካህ የሚባል አይደለም፡፡ ጊዜያችን ከደረሰ የተፃፈልንን ሞት ማግኘታችን አይቀሬ ነው፡፡ ሆኖም ወይ በመጣደፋችን፣ ወይ ሳንደራጅ ዘራፍ በማለታችን ለጥፋት እንዳረጋለን፡፡ እኛም ጠፍተን ጦሳችን ለሌላ ይተርፋል! “ጊዜዋ የደረሰ ቀበሮ አዳኝን ታስመሰግናለች” ማለት ይሄና ይሄ ብቻ ነው! ከዚህ ይሰውረን!!

 የእንግሊዝ መንግስት ፈጣን የብሮድባንድ ኢንተርኔት አገልግሎት ማግኘት በመጪዎቹ ሶስት አመታት ጊዜ ውስጥ የሁሉም የአገሪቱ ዜጎችና ተቋማት ህጋዊ መብት እንደሚያደርግ አስታውቋል፡፡
የቴሌኮም አገልግሎት በመስጠት ላይ የሚገኙ የአገሪቱ ተቋማት የብሮድባንድ ኢንተርኔት እንዲያቀርቡላቸው ለሚጠይቋቸው ሁሉም ዜጎችና ተቋማት ቢያንስ እስከ 10 ሜጋ ባይት በሰከንድ ፍጥነት ያለው የኢንተርኔት አገልግሎት መስጠት ግዴታቸው እንደሚሆን የአገሪቱ መንግስት አስታውቋል፡፡
በአሁኑ ወቅት በተለይ በአገሪቱ የገጠር  አካባቢዎች የሚገኙ ከ1 ሚሊዮን በላይ የግለሰብ መኖሪያ ቤቶች፣ የፈጣን ኢንተርኔት አገልግሎት ተጠቃሚ እንዳልሆኑ የጠቆመው ዘገባው፤ እ.ኤ.አ ከ2020 ጀምሮ ግን ሁሉም የአገሪቱ ዜጎች የፈጣን ብሮድባንድ ኢንተርኔት አገልግሎት ማግኘት ህጋዊ መብታቸው እንደሚሆንና ተገቢውን አገልግሎት በአፋጣኝ በማይሰጡ የቴሌኮም ተቋማት ላይ እርምጃ እንደሚወሰድ መነገሩንም አመልክቷል፡፡
እንግሊዝ በብሮድባንድ ኢንተርኔት አገልግሎት ፍጥነት ከሌሎች የአለማችን ያደጉ አገራት ጋር ሲነጻጸር፣ እጅግ ዝቅተኛ ደረጃ ላይ እንደምትገን የጠቆመው ዘገባው፤ በጃፓን 97 በመቶ ያህሉ የኢንተርኔት አገልግሎት በሙሉ ፋይበር መስመር የሚሰሩ ሲሆን በእንግሊዝ ግን በተመሳሳይ ሁኔታ የሚሰሩት 3 በመቶ ብቻ መሆናቸውንም አክሎ ገልጧል፡፡


 የኡጋንዳ ፓርላማ የአገሪቱን ፕሬዚዳንት የዕድሜ ገደብ የሚያስቀረውንና አምስት አመት የነበረውን አንድ የስልጣን ዘመን ወደ ሰባት አመት ከፍ በማድረግ፣ ከ30 ዓመት በላይ አገሪቱን የገዙትን ዮሪ ሙሴቬኒንን የስልጣን ቆይታ ከአርባ አመታት በላይ የሚያደርሰውን የህገ መንግስት ማሻሻያ አጽድቆታል፡፡
ሙሴቬኒ በ2021 በሚካሄደው ቀጣዩ ፕሬዚዳንታዊ ምርጫ ወቅት 77 አመት የሚሆናቸው ሲሆን ህጉ ግን ለመሪነት መወዳደር የሚችለው ዕድሜው ቢበዛ 75 አመት የሆነ ነው ይላል፡፡ ፕሬዚዳንቱ በምርጫው ለመወዳደርና ስልጣናቸውን ለማራዘም ሲሉ ህጉ እንዲሻሻል ባቀረቡት ሃሳብ ላይ ለሶስት ቀናት በከፍተኛ ሁኔታ የተከራከሩት የፓርላማ አባላቱ፤ በስተመጨረሻም ባለፈው ረቡዕ በሰጡት የድጋፍ ድምጽ እንዳጸደቁት ቢቢሲ ዘግቧል፡፡
የፓርላማው አባላት በጉዳዩ ዙሪያ ያደረጉትን የተራዘመ ክርክር ሲያጠናቅቁ በሰጡት ድምጽ፣ በ315 ድጋፍና በ62 ተቃውሞ በአብላጫ ድምጽ የህገ መንግስት ማሻሻያውን ማጽደቃቸውን የጠቆመው ዘገባው፤ ይህን ተከትሎም የተቃዋሚ ፓርቲዎች ደጋፊዎች ተቃውሞና ብጥብጥ ሊያስነሱ ይችላሉ ተብሎ በመሰጋቱ፣ ፖሊስ በተጠንቀቅ እንዲቆም መታዘዙን አመልክቷል፡፡
ማሻሻያው የሙሴቬኒን ስልጣን ለማራዘም ሆን ተብሎ የተደረገ ነው በሚል ሃሳቡን ሲቃወሙ የነበሩ ስድስት የተቃዋሚ ፓርቲዎች አባላት ከፓርላማው መባረራቸውን የጠቆመው ዘገባው፤ ባለፈው መስከረም ወር ላይ ጉዳዩ ለፓርላማ ቀርቦ በተደረጉት ውይይቶች ላይ በተፈጠሩ ውዝግቦች የፓርላማው አባላት በወንበር እየተወራወሩ እስከመፈነካከት ደርሰው እንደነበርም አስታውሷል።
ረቂቅ ሃሳቡ ለፓርላማ ውሳኔ ከቀረበ ቆየት ቢልም፣ በአፋጣኝ ድምጽ ሊሰጥበት ያልቻለው የአገሪቱ ህግ አውጪዎች፤ ውሳኔውን የሚያጸድቅ የድጋፍ ድምጽ ለመስጠት ከሙሴቬኒ መንግስት ለእያንዳንዳቸው 83 ሺህ ዶላር በሙስና መልክ እንዲከፈላቸው በመጠየቃቸው ነው መባሉን ባለፈው ሳምንት ኦልአፍሪካን ኒውስን ጠቅሰን መዘገባችን  ይታወሳል፡፡

በየመን የኮሌራ ተጠቂዎች ቁጥር 1 ሚ. ደርሷል ተባለ

    በደቡብ ሱዳን ላለፉት አራት አመታት ያህል የዘለቀው የእርስ በእርስ ግጭት አፋጣኝ መፍትሄ ሳይበጅለት በዚሁ የሚቀጥል ከሆነ በመጪዎቹ ጥቂት ወራት ውስጥ ከ5 ሚሊዮን በላይ ህዝብ ወይም ከመላው የአገሪቱ ህዝብ ግማሽ ያህሉ የከፋ የምግብ እጥረት ተጠቂ ሊሆን ይችላል ሲል ተመድ አስጠነቀቀ፡፡
በአገሪቱ 1.2 ሚሊዮን ያህል ደቡብ ሱዳናውያን የረሃብ ተጠቂዎች መሆናቸውን የጠቆመው የተባበሩት መንግስታት ድርጅት፤ በተለይም አዮድ በተባለቺው የአገሪቱ አውራጃ ችግሩ የከፋ መሆኑንና 8 ሺህ ያህል ዜጎች፣ የከፋ ረሃብ ሰለባ መሆናቸውን አስታውቋል፡፡
በሌላ በኩል በየመን የተከሰተው አስከፊ የኮሌራ ወረርሽኝ በከፍተኛ ሁኔታ እየተስፋፋ እንደሚገኝና በበሽታው የተጠቁ የአገሪቱ ዜጎች ቁጥርም 1 ሚሊዮን ያህል መድረሱን አለማቀፉ የቀይ መስቀል ኮሚቴ ማስታወቁን ቢቢሲ ዘግቧል፡፡
በአገሪቱ ለአመታት የዘለቀው የእርስ በእርስ ግጭት ግማሽ ያህሉን የጤና ተቋማት ማውደሙን ያስታወሰው ዘገባው፤ በስራ ላይ የሚገኙ ተቋማትም ቢሆኑ የባለሙያና የመድሃኒት አቅርቦት ችግር ያለባቸው ከመሆናቸው ጋር በተያያዘ ወረርሽኙን ለመግታትም ሆነ ለታመሙት ተገቢ ህክምና ለመስጠት ከአቅማቸው በላይ በመሆኑ በሽታው እጅግ እየተስፋፋና ብዙ ዜጎችን ተጠቂ እያደረገ መቀጠሉን አመልክቷል፡፡
ከውጭ አገራትና ከለጋሾች የሚላኩ ወረርሽኙን ለመግታትና ታማሚዎችን ለመታደግ የሚያስችሉ መድሃኒቶችና የህክምና ቁሳቁሶች፣በእርስ በርስ ግጭቱ ሳቢያ መንገዶች በመዘጋጋታቸውና በወቅቱ ሊደርሱ ባለመቻላቸው ችግሩን የበለጠ እንዳከፋውም ተነግሯል፡፡
ባለፉት ሰባት ወራት ጊዜ ውስጥ ከ2 ሺህ 226 በላይ የመናውያን በኮሌራ ሳቢያ ለህልፈተ ህይወት መዳረጋቸውን ያስታወሰው ዘገባው፤ በሰኔ ወር ላይ ወረርሽኙ በከፍተኛ ሁኔታ በመስፋፋት ከአገሪተ 23 ግዛቶች በ22ቱ፣ በአንድ ሳምንት ጊዜ ውስጥ ብቻ ከ50 ሺህ በላይ ሰዎችን ማጥቃቱን አክሎ ገልጧል፡፡
የአለም የጤና ድርጅት በበኩሉ፣ ባለፈው ሳምንት ብቻ 7 ሺህ 600 ያህል የመናውያን በኮሌራ ወረርሽኝ ተጠቂ ሆነዋል ተብሎ እንደሚገመት ማክሰኞ ዕለት ይፋ ባደረገው መረጃ ማስታወቁን የጠቆመው ዘገባው፤ ከአጠቃላዩ የአገሪቱ ህዝብ 80 በመቶ ያህሉ የምግብ፣ የንጹህ ውሃና የህክምና አገልግሎት እንደማያገኙና መፍትሄ ያልተገኘለት የኮሌራ ወረርሽኝም የመናውያኑ ን ለተጨማሪ የከፋ ስቃይ እየዳረገ እንደሚገኝ አመልክቷል፡፡
በየመን ተቀናቃኝ ሃይሎች መካከል የሚካሄደው ጦርነት ከ2015 አንስቶ 8 ሺህ 670 ያህል የአገሪቱ ዜጎችን ለህልፈተ ህይወት መዳረጉንም ዘገባው አስታውሷል፡፡


የትራምፕን ውሳኔ፡
128 አገራት ተቃውመውታል፤
9 አገራት ደግፈውታል፤
35 አገራት “ከነገሩ ጦም እደሩ” ብለዋል
ፕሬዚዳንት ዶናልድ ትራምፕ፤ኢየሩሳሌም የእስራኤል ዋና ከተማ ለመሆኗ የሰጡትን እውቅና ለመሰረዝ የተባበሩት መንግታት ድርጅት በጠራው የድምጽ መስጫ ጉባኤ ላይ ውሳኔያቸውን በመቃወም ድምጻቸውን ለሰጡ አገራት በእርዳታ መልክ ሊሰጡት የነበረውን በቢሊዮኖች የሚቆጠር ዶላር እንደሚያስቀሩ ዝተዋል፡፡
የተባበሩት መንግስታት ድርጅት አባል አገራት ከትናንት በስቲያ በጉዳዩ ላይ ያላቸውን አቋም በመግለጽ ድምጽ ሰጥተል፡፡  128 አገራት ውሳኔውን በመቃወም፣9 አገራት በመደገፍ ድምጽ የሰጡ ሲሆን 35 አገራት ደግሞ ድምጸ ተዓቅቦ አድርገዋል።
ትራምፕ በቅርቡ ለኢየሩሳሌም የእስራኤል መዲናነት የሰጡት እውቅና በበርካታ የአለም አገራት በጋራና በተናጠል ሲነቀፍ መሰንበቱን ያስታወሰው ዘገባው፤ የተባበሩት መንግስታት ድርጅት የጠራው ስብሰባ የአገራት ድምጽ ድምር ውጤትም የትራምፕን ውሳኔ እውቅና በመንፈግ፣ “የኢየሩሳሌም ጉዳይ በፍልስጤምና በእስራኤል መካከል በሚደረግ ሰላማዊ ድርድር ይቋጭ” የሚል ድምዳሜ ላይ ደርሷል ብሏል፡፡
አሜሪካ፣ እስራኤል፣ ጓቲማላና ቶጎ የትራምፕ ውሳኔ እንዳይሻር፣ ድምጻቸውን ከሰጡ ዘጠኝ አገራት መካከል መሆናቸውን የዘገበው ዘ ጋርዲያን፤ ካናዳ፣ ፖላንድ፣ ቼክ ሪፐብሊክና ሮማንያ ደግሞ ድምጽ ተዓቅቦ ካደረጉት 35 የአለማችን አገራት መካከል እንደሚገኙበት ጠቁሟል፡፡
የትራምፕ ውሳኔ መሻሩን በመደገፍ ድምጽ በመስጠት ረገድ የመካከለኛው ምስራቅ አገራት በብዛት ቀዳሚነቱን የያዙ ሲሆን ጀርመን፣ ፈረንሳይና እንግሊዝን ጨምሮ በርካታ የአውሮፓ አገራትም ይህንን ቡድን መቀላቀላቸውን ዘገባው አስረድቷል። ኢትዮጵያም ከእነዚህኞቹ ተርታ ተሰልፋለች፡፡
በተያያዘ ዜናም፣ አሜሪካ የሰብዓዊ መብቶች ጥሰት ፈጽመዋል፤ በሙስና ተዘፍቀዋል በሚል 52 በሚሆኑ የደቡብ ሱዳን፣ ጋምቢያና ማይንማር ከፍተኛ ባለስልጣናት፣ ባለሃብቶችና ተቋማት ላይ ከትናንት በስቲያ ማዕቀብ መጣሏን ሮይተርስ ዘግቧል፡፡
ማዕቀቡ ከተጣለባቸው መካከልም የሮሂንጋ ሙስሊሞች ለከፋ እልቂት ሲዳረጉ ችላ ብለዋል የተባሉት የማይንማሩ የጦር ሃይል አዛዥ፣ የደቡብ ሱዳኑ ፕሬዚዳንት ሳልቫ ኬር አማካሪና የቀድሞው የጋምቢያ መሪ ያያ ጃሜህ እንደሚገኙበት ዘገባው አመልክቷል፡፡

 የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ በጋምቤላ ክልል ከ9 ነጥብ 7 ሚሊዮን ብር በላይ በሆነ ወጪ ያስገነባውን ጤና ጣቢያ ያስመረቀ ሲሆን ተመሣሣይ ጤና ጣቢያዎችን በሁሉም ክልሎች እየገነባ መሆኑን አስታውቋል፡
 ባንኩ ማህበራዊ ሃላፊነቱን ለመወጣት በየአመቱ ከፍተኛ በጀት መድቦ እየተንቀሳቀሰ መሆኑን በተለይ በጤና፣ በትምህርት፣ በአከባቢ ጥበቃ፣ በአካል ጉዳተኞች በአረጋዊያን፣ በህፃናት እና ሴቶች ዙሪያ የድጋፍ እንቅስቃሴዎች እያደረገ መሆኑን አስታውቋል፡፡
ከሠሞኑ የዚህ ፕሮጀክት አካል የሆነውንና በጋምቤላ ክልል በኢታንግ ልዩ ወረዳ በሌር ቀበሌ ያስገነባውን ጤና ጣቢያ የክልሉ ምክትል ርዕሠ መስተዳደርና የፐብሊክ ሠርቪስና የሠው ሃብት ልማት ቢሮ ሃላፊ አቶ ሰናይ አኩኑር በተገኙበት አስመርቋል፡፡
ምክትል ርዕሠ መስተዳደሩም በምረቃ ስነ ስርዓቱ ላይ ባንኩ ለክልሉ ህዝብ አጋርነት ማሣየቱን አመስግነው ህዝቡ ጤና ጣቢያውን በአግባቡ እንዲጠቀምበት አሣስበዋል፡፡
በምረቃ ስነ ስርአቱ ላይ የተገኙት የባንኩ የኮሚኒኬሽን ስራ አስኪያጅ አቶ በልሁ ታከለ በበኩላቸው በቀጣይም ባንኩ በጤናው ዘርፍ ተመሣሣይ ስራዎችን እንደሚያከናውን አስታውቀዋል፡፡
በአሁኑ ወቅትም በዘጠኙም ክልሎች በጠቅላላው ከ66 ሚሊዮን ብር በላይ ወጪ በማድረግ ተመሣሣይ ጤና ጣቢያዎች እየስገነባ መሆኑን አቶ በልሁ አስታውቀዋል፡፡


   ፍሊንትስቶን ኢንጅነሪንግ አ.ማ ለተለያዩ የንግድ አገልግሎቶች በልደታ የገነባውን ባለ 7 ፎቅ የ“ልደታ - መርካቶ የገበያ ማዕከል ህንፃ ትናንት አስመርቆ ለደንበኞቹ አስረከበ፡፡
ይህ ባለ 7 ፎቅ ህንፃ መደበኛ መብራት በሚጠፋበት ወቅት የሶላር ኤሌክትሪክ ኃይልን የሚጠቀም መሆኑ ተነገረለት ሲሆን ከህንፃው ስር ባለ ሁለት ወለል የመኪና ማቆሚያ ያካተተ መሆኑ ተገልጿል፡፡  ህንፃው በጠቅላላው 380 የንግድ ሱቆች ያሉት ሲሆን ከ1-3ኛው ወለል ያሉ ሱቆች ለአዋቂ አልባሳትና ጫማዎች መሸጫዎች ብቻ፣ 4ኛ ወለል የመዋቢያዎችና ጌጣጌጦች መሸጫ ሱቆች፣ 5ኛ ወለል ኤሌክትሮኒክስ መሸጫ ሱቆች፣ 6ኛ ፎቅ የህፃናት አልባሳት መሸጫ ሱቆች እንዲኖሩት ታስቦ ለደንበኞች ሽያጭ መከናወኑ ተገልጿል፡፡
7ኛ ፎቅም የሲኒማ እና ጌም ዞን አገልግሎት ይኖረዋል ተብሏል፡፡
የዚህ ህንፃ ዲዛይን በተለየ ሁኔታ በስፔናዊ አርክቴክት መሰራቱንና የምድር ቤቱም ለዕቃ ማከማቻ አገልግሎት ይውላል ተብሏል፡፡  

  ‹‹…እኔ የኤችአይቪ ቫይረስ በደሜ ውስጥ የተገኘው የዛሬ ሀያ ሶስት አመት ነው፡፡ ዛሬ   እድሜዬ 45 አመት ደርሶአል፡፡ በጊዜው ሳይውል ሳያድር ተመርምሬ ችግሩን በማወቄ እነሆ እስከዛሬ ድረስ ካለምንም ችግር እራሴን በአግባቡ እየመራሁ እገኛለሁ፡፡ ጤንነቴም ተጉዋድሎ አያውቅም፡፡ አበባ እንደመሰልኩ እኖራለሁ፡፡ ሕመም ገጠመም አልገጠመም በተወሰነ ጊዜ ምርመራ እያደረጉ እራስን መጠበቅ ጠቃሚ ነው፡፡…››
(የኤችአይቪ ቫይረስ በደምዋ ውስጥ የሚገኝ ሴት እማኝነት)
ኤይድስ HIV (human immunodeficiency virus) ከሚባል የቫይረስ አይነት የሚከሰት ገዳይ የሆነ በሽታ ነው፡፡ ኤይድስ በአለም አቀፍ ደረጃ በመጀመሪያ መኖሩ የታወቀው እንደፈረንጆቹ አቆጣጠር በ1981/ዓም ነው፡፡ ለዚህ የማይድን በሽታ ኤይድስ የሚል ስያሜ የተሰጠውም እንደ ፈረንጆቹ አቆጣጠር ጁላይ 27/1982/ዓ/ም ነው፡፡
በየአመቱ በውጭው አቆጣጠር ዲሴምበር 1/ አለም አቀፍ የኤችአይቪ ቀን በሚል እንደ ውጭው አቆጣጠር ከ1988/ዓ/ም ጀምሮ ሲከበር ቆይቶአል፡፡ ዲሴምበር 1/ አሁንም ኤችአይቪን በተመለከተ  የተለያዩ ነጥቦች በአለም ዙሪያ የሚንጸባረቁበት ቀን ሆኖአል፡፡ ይህ አለምአቀፍ ቀን ኤችአይቪን በሚመለከት ትምህርቶችን በመስጠት ግንዛቤ በማስጨበጥ እና ስርጭቱን ለመግታት የተለያዩ እንቅስቃሲዎች የሚደረግበት ነው፡፡  
በ2016/በአለም አቀፍ ደረጃ በደማቸው የኤችአይቪ ቫይረስ ያለባቸው ሰዎች ቁጥር በአማካይ 36.7/ሚሊዮን ሲሆን 1.8/ሚሊዮን የሚሆኑ ሰዎች በአለም አቀፍ ደረጃ በአመት አዲስ በቫይረሱ የሚያዙ ሰዎች ናቸው፡፡ በአለም አቀፍ ደረጃ በየአመቱ ወደ 2/ሚሊዮን የሚደርሱት ሰዎች ከኤችአይቪ ጋር በተያያዘ ለሕልፈት የሚዳረጉ ሲሆን ከነዚህም 10 በመቶ የሚሆኑት ሕጻናት ናቸው፡፡
ኤይድስ በአሁኑ ወቅት በአፍሪካ ውስጥ እድሜያቸው ከ10-29/ አመት የሆናቸውን ሰዎች በመግደል ዋነኛው ምክንያት ሲሆን በአለምአቀፍ ደረጃ ደግሞ በወጣቶች ገዳይነቱ በ2ኛ ደረጃ የተመዘገበ ነው፡፡
በአለም አቀፍ ደረጃ በቀጣይነት እንዲተገበር ለታቀደው ልማት አንዱና ዋነኛው እቅድ በማናቸውም እድሜ ክልል ለሚገኙ ሰዎች ጤናማ ሕይወትን መምራት እና ደህንነትን ማረጋገጥ መሆኑ እሙን ነው፡፡ በዚህም ውስጥ ኤችአይቪ ኤይድስ እስከ 2030/ ስርጭቱን እስከወዲያኛው እንዲያከትም አለም አቀፍ ስምምነት ተደርጎአል፡፡
ኤችአይቪ ኤይድስ ከእናት ወደ ልጅ እንዳይተላለፍ ምንም ጥረት ካልተደረገ በአለም አቀፍ ደረጃ ከ15-45/ በመቶ በሚደርስ ደረጃ ከእናት ወደ ልጅ በሚተላለፍባቸው መንገዶች ቫይረሱ ሊተላለፍ ይችላል። በ2016 በተደረገው የዳሰሳ ጥናት እንደተገኘው መረጃ ከሆነ መተላለፉን ለመከላከል በአለም አቀፍ ደረጃ በተወሰዱ እርምጃዎች ቫይረሱ በደማቸው ውስጥ የሚኖር 76 ከመቶ የሚሆኑ እርጉዝ እናቶች ፀረኤችይቪ መድሀኒትን በትክክል እንዲጠቀሙ ተደርጎአል፡፡ በዚህም ጥረት ከኤችአይቪ ነጻ የሆነ ትውልድ እንዲመጣ ምክንያት ይሆናል ተብሎ ይታመናል፡፡ ባጠቃላይም በአለም አቀፉ ኤችአይቪ ቀንም ሆነ በሌሎች ጊዜያቶች በአለም አቀፍ ደረጃ አገራት እንዲሁም የሚመለከታቸው ድርጅቶች እና ህብረተሰብ ለጉዳዩ ቅድሚያ ትኩረት ሊሰጡትና ጥንቃቄ ሊያደርጉበት የሚገባ ሲሆን የህክምናው አገልግሎትም ከጊዜ ወደጊዜ እንዲሻሻል የተቻለው ጥረት እንዲደረግ አለምአቀፍ ስምምነት አለ፡፡
ምንጭ ፡-WHO…2017/
ኤችአይቪ በአሁኑ ወቅት አነጋጋሪ እየሆነ ነው። በመሆኑም አለም አቀፉን የኤችአይቪ ኤይድስ ቀን ምክንያት በማድረግ የጋንዲ የእናቶችና ሕጻናት ሆስፒታል ለሆስፒታሉ ሰራተኞችና በወቅቱ ለነበሩ ታካሚዎች ስለኤችአይቪ ገለጻ የማድረጊያ ፕሮግራም አከናውኖአል። ኤችአይቪ ኤይድስን በሚመለከት የሆስፒታሉን ስራአስኪያጅ ሲ/ር ሕይወት ገ/ሚካኤልን አነጋግረን ለንባብ ብለናል፡፡
ሲ/ር ሕይወት እንደሚሉት ኤችአይቪን በሚመለከት በአሁኑ ወቅት የመዘናጋት ነገር አለ፡፡ ለምሳሌም በአዲስ አበባ አሁን ያለው ስርጭት መጠን ቀደም ሲል ከነበረው ጨምሮ ይታያል፡፡ ለዚህም እንደ ምክንያት ከሚቆጠረው ውስጥ አንዳንድ ቫይረሱ በደማቸው ውስጥ የሚገኝ ሰዎች የፀረኤችአይቪ ኤይድስ መድሀኒት በሚወስዱበት ጊዜ የጤናቸው ሁኔታ ስለሚሻሻል ጨርሰው የተፈወሱ እየመሰላቸው መድሀኒቱን ስለሚያቋርጡ ነው፡፡ አንዳንዶች ደግሞ የባህርይ ለውጥ ማምጣት የሚባለውን ወደጎን በመተው እና 5ቱን መ…ዎች… ማለትም …መጠንቀቅ… መታቀብ… መመርመር…መድሀኒት መጠቀም… ኮንዶም መጠቀም የሚሉትን በትክክል ተግባር ላይ አለማዋል ይታይባቸዋል፡፡ ሌላው ደግሞ ቫይረሱ በደማቸው ውስጥ እንዳለ ሲነገራቸው ወደ ሕክምና ተቋም ከመሄድ ይልቅ በተለያዩ ልማዳዊና የእምነት ቦታዎች በመሄድ በቃ ከሕመሙ ፈውስ አግኝተናል ብለው ስለሚያስቡ ቫይረሱ እየጎዳቸው ይገኛል፡፡ ከጤና ባለሙያውም ይሁን ከመገናኛ ብዙሀን እንዲሁም ከተለያዩ ከሚመለከታቸው አካላትም በጉዳዩ ላይ ግንዛቤ የመስጠትና ሰዎች አካሄዳቸውን እንዲያስተካክሉ የሚያደርግ ስራ ከመስራት ቆጠብ የተባለበት ሁኔታ ስለአለ አጠቃላይ ሁኔታውን መዘናጋት ልንለው እንችላለን ብለዋል፡፡
ሲ/ር ሕይወት አስከትለውም የጋንዲ ሆስፒታል የእናቶችና የጨቅላ ህጻናቶች መታከሚያ እንደመሆኑ አንዲትም እናት የእርግዝና ክትትል በምታደርግበት ጊዜ የኤችአይቪ ምርመራ የማታደርግ የለችም፡፡ ይህም ሁለት ጥቅም ያለው ነው፡፡
ክትትል ለማድረግ ከሆስፒታል የመጣችው እናት ዛሬ ከቫይረሱ ነጻ ብትሆን እንኩዋን ነገ በቫይረሱ አትያዝም ማለት ስላልሆነ በቀጣይ ሕይወትዋ እንዴት እንደምትኖር አስፈላጊው የግንዛቤ ማስጨበጫ ትምህርት የሚሰጥበት ነው፡፡  
የእርግዝና ክትትል የምታደርገው እናት ቫይረሱ በደምዋ ውስጥ ቢገኝባት ባለቤቷን ጭምር በመጋበዝ ከቫይረሱ ነጻ የሆነ ልጅ እንዴት መውለድ እንደሚቻል እና ባልና ሚስቱም በቀጣይ ምን አይነት የህክምና ክትትል ማድረግ እንደሚገባቸው የምክር አገልግሎት የሚሰጥበት ነው፡፡
ስለዚህም የደም ምርመራ ማድረግ ቅድመ ጥንቃቄ ለማድረግና መድሀኒት ለማስጀመር በጣም ወሳኝ ስለሆነ ለሁሉም እርጉዝ ሴቶች የምክር አገልግሎትና የኤችአይቪ ምርመራ ማድረግ ወሳኝ ነው፡፡ በጋንዲ ሆስፒታል የእርግዝና ክትትል ሲያደርጉ ቫይረሱ በደማቸው ከተገኘባቸው እናቶች የተወለዱ ሕጻናት በሙሉ ቫይረሱ በደማቸው አልተገኘም፡፡ ይህ ወደፊት ከቫይረሱ ነጻ የሆነ ትውልድን በማግኘቱ ረገድ እጅግ ጠቃሚ መሆኑ አይካድም፡፡
PEPFAR ETHIOPIA/ በ2017 እንዳወጣው መረጃ በኢትዮጵያ 15 ሺህ በደማቸው ውስጥ ኤችአይቪ ቫይረስ የሚገኝባቸው እርጉዝ ሴቶች ፀረኤችአይቪ መድሀኒት ተጠቃሚ ናቸው፡፡
የአለም የጤና ድርጅት በአለም አቀፍ ደረጃ ኤችአይቪን ስለመከላከል ያወጣው ቁልፍ መልእክት፡-
ከኤችአይቪ ኤይድስ ጋር በተያያዘ የማንም ሰው ጉዳይ ቸል ሊባል አይገባውም፡፡
ኤች አይቪ የሳንባ በሽታ እና ሄፒታይተስ ለተባሉት ሕመሞች ከሚሰጠው አገልግሎት ጋር የተቀናጀ ነው፡፡
ኤችአይቪ ቫይረስ በደማቸው ውስጥ ለሚገኝባቸው ሰዎች የሚሰጠው አገልግሎት ከፍተኛ ጥራት ያለው መሆን አለበት፡፡
የኤችአይቪ ቫይረስ በደማቸው ውስጥ ያለባቸው ሰዎች በሚችሉት መንገድ ደህንነታቸውን መጠበቅ እንደሚችሉ ሊያውቁ ይገባል፡፡
ኤችአይቪን በሚመለከት ያለው ምላሽ በጎ እና ጠንካራ የጤና አጠባበቅ ዘዴ እንዲኖር ማድረግ ያስችላል፡፡
ሲ/ር ሕይወት በስተመጨረሻውም እንደተነገሩት ህብረተሰቡን ከኤችይቪ ኤድስ ጋር በተያያዘ ከሚደርስ ጉዳት ለመጠበቅ የጤና ተቋማት እንዲሁም መገናኛ ብዙሀን እና ተመሳሳይ መድረኮች የምክር አገልግሎትና ትምህርት መስጠት ይጠበቅባቸዋል፡፡ በተጨማሪም ሁሉም የህክምና ተቋማት ወይንም የሚመለከታቸው አካላት ለታዳጊዎች እና ለወጣቶች በነጻነት የሚጠቀሙበት የምክር አገልግሎ መስጫ ክሊኒኮች ቢያመቻቹ ጠቃሚ ይሆናል፡፡ የጋንዲ ሆስፒታል  በዚህ አመት አንዱ እቅዱ Adolescence clinic በመክፈት ለታዳጊውና ለወጣቱ በማንኛውም ሰአትና ቀን የምክር አገልግሎት የሚሰጥበትን ሁኔታ ማመቻቸት ነው፡፡ ብለዋል፡፡

ከዕለታት አንድ ቀን አንድ ጨካኝ የናዚ ጄኔራል ነበር፡፡ አንዲት ባሏ የታሰረባት ሚስት ወደ ጄኔራሉ ቀርባ “ባለቤቴ የደረሰበት አልታወቀም፤ እባክዎ ይርዱኝ” አለችው። ጄነራሉም፤
“ተገድሎ ሊሆን ስለሚችል ካሣ ይሰጣት” ብሎ ሃያ ሺህ ዶች ማርክ እንዲከፈላት አስደረገ፡፡ በሳምንቱ ባሏ ሌላ እሥር ቤት እንዳለ ታወቀ፡፡
“ባለቤቴ እንዲህ ያለ እሥር ቤት እንዳለ ተረገግጧልና ገንዘቡን መልሼ ይፈታልኝ” ስትል አመለከተች፡፡
ጄነራሉም፤
“እቺ ሴት እኛን ውሸታም ልታደርገን ፈልጋለች እንዴ? ግደሉትና ገንዘቧን ይዛ ትቀመጥ!” አለ፡፡
ገዳዮቹ ባሏን እንደግሉ ጄኔራሉ የሰጠው ትዕዛዝ፤
“ራቅ አድርጋችሁ ውሰዱና ተኩሱ፤ ለከተማው የማይሰማበት ቦታ ግደሉት!” የሚል ነበር፡፡
ገዳዮቹ ሰውዬውን ራቅ አድርገው ሲወስዱት፣ መንገዱ እጅግ ረዥም ስለሆነበት፤
“ጎበዝ! መገደሌ እርግጥ ከሆነ፣ ለምን ይሄን ያህል ታደክሙኛላችሁ? ሰውነቴ በጣም ዛለ‘ኮ?! ለምን እዚሁ አትገድሉኝም?” አላቸው፡፡
ገዳዮቹም፤
“ኧረ ዝም ብለህ ሂድ! አንተስ ሞተህ እዚያው ትቀራለህ፡፡ እኛ አለን አደለም እንዴ ገና የምንመለሰው!” አሉት፡፡
*      *      *
ጨካኝ ሥርዓት ለማንም አይበጅም፡፡ መፍትሄ የሚመስሉንን ምላሾች ደግመን ደጋግመን እንመርምራቸው፡፡ ለህዝብ የሰጠናቸው መፍትሄዎች ምን ውጤት አመጡ? ምን ፍሬ አፈሩ? ብለን እንጠይቅ፡፡ የፈየዱት ፋይዳ ከሌለ፣ ሌላ አማራጭ እንፈልግ፡፡ የሰጠነው መፍትሔ መሬት ጠብ አይልም፤ ከእኛ ሌላ ለአሳር ነው፤ ብትቀበሉ ተቀበሉ፤ ብለን ተአብዮ አይሰማን፡፡ ከህዝብ ጋር ልብ ለልብ ተግባብቶ፣ ተማምኖ መጓዝ ነው - አገር ከችግር የሚያወጣው፡፡ “ብቆጣም እመታሻለሁ፤ ብትቆጪም እመታሻለሁ” የሚል አካሄድ፣ ከቶ ሁነኛ አካሄድ አይሆንም፡፡
እኛ ወደ መንገዱ እንሄዳለን እንጂ መንገዱ ወደ እኛ አይመጣም፡፡ ባልባለቀ ዲሞክራሲ፣ አጥጋቢ ባሆነ ፍትሕ፣ በሙስና ባህር ውስጥ በተዘፈቀ ሂደት “አገር እድገት እያሳየች ነው” ብለን አንገበዝ፡፡ እርቅና ድርድር መልካም ገፅታ የሚኖረው፣ ልባችን ንፁህ ሆኖ ሁላችንም በአንድ ቅኝት ስለ አገር መዘመር ስንችል እንጂ ተነጣጥለን በመጓዝ አይደለም፡፡ በሁሉም ወገን የጥሞና ጊዜ ያስፈልጋል፡፡ የአርምሞ ገዳም ያሻናል፡፡ እስከ ዛሬ የተጓዝንበት መንገድ ምን ያህል ሰላምን ያቀፈ ነበር? የህዝባችንን ድምፅ ምን ያህል አዳምጠናል? መሰረታዊ ለውጥ አድርገናል ወይስ የለመድነውን መዝሙር ደግመን እየዘመርን ነው? ልዩነት ያስፈልገናል፡፡ vive la difference! የሚሉት ፈላስፎቹ; ልዩነት ለዘለዓለም እንዲኖር xeneji ሌጣ እንድንሆን አይደለም!
እንስከን!! እንዘጋጅ!! “ሲሮጡ የታጠቁት፣ ሲሮጡ ይፈታልን” አንርሳ! አለበለዚያ “አንጋጠው ቢተፉ ተመልሶ ባፉ” እንደሚሆን እንገንዘብ፡፡ ለህዝብና ለአገር የሚበጀው ይሄ ነው!!