Administrator

Administrator

የክስታኔ ጉራጌ ሕዝብ የልማት ማህበር ከአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የኢትዮጵያ ቋንቋዎችና ባህሎች አካዴሚ ጋር በትብብር ያዘጋጀው ክስታንኛ - አማርኛ - እንግሊዝኛ መዝገበ ቃላት ነገ እሁድ ከጠዋቱ 2፡30 ጀምሮ እስከ 6፡30 ባለው ጊዜ በኢትዮጵያ ብሔራዊ ቴአትር በይፋ ይመረቃል፡፡
ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች በሚገኙበት በዚህ ሥነስርዓት ላይ በመገኘት የመርሃ ግብሩ ተሳታፊ ይሆኑ  ዘንድ ማህበሩ በአክብሮት ተጋብዘዋል፡፡


        “--የዚህ ጦርነት “ባለሞያው” ናቸው ስንል፣ እንዲኹ ከሜዳው ተነስተን አይደለም፡፡ ጥላሁን ይጽፋሉ፤ ከጻፉም ሌላ ጉዳይ የላቸውም- ይኼው የኢትዮጵያና ጣሊያን ጦርነት ብቻ!---”

    ርእስ- የኢትዮጵያና የጣሊያን ሁለተኛው ጦርነት ታሪክ
ደራሲ- ጥላሁን ጣሰው
የህትመት ዘመን -  2009 ዓ.ም
ገጽ- 209
ዋጋ- ብር 82.00  ($25.00)
ዳሰሳ፡- ሰሎሞን አበበ ቸኮል
ስለ ኢትዮ-ጣሊያን ጦርነት የትኛውንም ዓይነት መጽሐፍ ያነበበም፣ የትኛውንም ያህል የተማረውና የተመራመረውም ቢኾን፣ ይህን የጥላሁን ጣሰውን መጽሐፍ ካላነበበ፣ የተሟላ ወይም የተፈፀመ ግንዛቤ ሊኖረው አይችልም፡፡ ሌላው ቢቀር፣ “የጦርነቱ ጠቅላይ አዛዥ” ስለነበሩት ግርማዊ ቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ ከጦርነቱ ጋር ያላቸውን የታወቀ ስም ፈጽሞ የሚቀይረው ነው፡፡ ይህ የጥላሁን ጣሰው የጦርነቱ ታሪክ መጽሐፍ ዕድለ ቢሱን ንጉሠ ነገሥት፣ ታላላቅ ጦርነቶችን በሚገባ ከመሩ የጦር መሪዎች እንደ አንዱ ይቆጥራቸዋል፡፡ እስከ ማይጨው ውሎአቸው ድረስ፣ ከዚያም በስደት ላይ ሳሉም የጦር መሪም ነበሩ፡፡ እንዲያውም፣ ይህ “ኹለተኛው” የተባለው የኢትዮጵያ ጣሊያን ጦርነት ታሪክ ተከታይ ዒላማውም፣ ይኼው የንጉሠ ነገሥቱ የጦር ምሪት ታሪክ ነው ሊባል ይችላል፡፡
ወልወል ላይ በ1927፣ ኅዳር 27 ቀን ድንገት በፈጸመችው ድብደባ፣ ጣሊያን “በይፋ ሳታሳውቅ” የከፈተችው የዚህ ጦርነት “ዓዋቂ” ወይም “ተጠያቂ” (ኤክስፐርት) ሊባሉ የሚበቁት ጥላሁን ጣሰው፤ የጦርነቱን ሙሉ ታሪክ ከእነ ትንታኔው፣ በ11 ምዕራፎች፣ ከ200 እምብዛም በማይጨምሩ ገጾች ክሽን አድርገው አቅርበውታል፡፡ በ1975 ዓ.ም በኩራዝ አሳታሚ ድርጅት የታተመ፣ “አዳባይ” የተባለ በዚኹ ጦርነት ላይ የተደረገ ረዥም የውጊያ ታሪካዊ ልብ ወለድ ጽፈዋል፡፡ “ትራይንግ ታይምስ” እንደ ፈረንጆች አቆጣጠር በ1911፣ በሻማ ቡክስ የታተመላቸው፣ ሌላው “የኹለተኛው ኢታሎ- ኢትዮጵያን” ጦርነት ልብወለድ መጽሐፋቸው ነው፡፡ ከዚህ ጦርነት ማግስት የነበረችውን ኢትዮጵያ፣ የኒዮ ፋሽስቶች መነሳትና መውደቅ፣ አብዮታውያኑንና ደርጋዊውያኑን የተመለከተ ታሪክን “ፎር ላቭ፡ ሎያሊቲ ፍሪደም ኤንድ ዲግኒቲ” በሚል ርእስ የጻፉም ናቸው፡፡ ከዚህ አርበኝነት ቀጥሎ ስለነበረው የ50ዎቹና 60ዎቹ ኢትዮጵያ ኹኔታ “ፍትሕና ርትዕ” የተባለ ሥራ በአማዞን አሳትመዋል፡፡
ከእነዚህም በተጨማሪ፣ በተለይ በ”ሪፖርተር” ጋዜጣ በዚሁ ጦርነት ላይ የተለያዩ ጽሑፎችን በአማርኛና በእንግሊዝኛ አቅርበዋል፡፡ “ኢትዮጵያን ኬዝ ኦፍ ዎር ክራይምስ አጌይንስት ሙሶሊኒ፣ ባደግሊዮ፣ ግራዝያኒ” (ሪፖ፣ ሴፕቴ፣ 2012)፤  እና “ዲፋይኒንግ ካራክተርስቲክስ ኦፍ ዘ ሰከንድ ኢትዮ - ኢታሊያን ዎር” (አፕ. 28፣ 2012) በኹለቱም የቀረበ ጽሑፎቻቸው ናቸው፡፡
የዚህ ጦርነት “ባለሞያው” ናቸው ስንል፣ እንዲኹ ከሜዳው ተነስተን አይደለም፡፡ ጥላሁን ይጽፋሉ፤ ከጻፉም ሌላ ጉዳይ የላቸውም- ይኼው የኢትዮጵያና ጣሊያን ጦርነት ብቻ! ይህ መጽሐፍ ለጦርነቱ “የኢትዮጵያና የጣሊያን ኹለተኛው ጦርነት” የሚል መጠርያን ሰጥቶታል፡፡ ጦርነቱን “ከአድዋው ጦርነት” ለይቶ ለመጥራት “የማይጨው ጦርነት” ሲባል የኖረ ነው፡፡ ይህ ደግሞ ጦርነቱ ማይጨው ላይ ብቻ የተደረገ ሊያስመስለው ችሏል፡፡ ስለዚህ “ኹለተኛው የኢትዮጵያ- ጣሊያን ጦርነት ጥሩ መለያ ነው፡፡ ግልጽም ነው፤ በ1888 የተደረገው ጦርነት አንደኛ፣ ከ1927 እስከ 1933 ድረስ የነበረው ይኸኛው ደግሞ ኹለተኛው፡፡
ነገር ግን እንዲህ በቁጥር ሲለይ አብሮ መታየት የሚገባው ሌሎች ጦርነቶች የነበሩ መኾኑን ማሳጣት የለበትም፡፡ ኢትዮጵያ ከሮማውያን ጋር ያደረገቻቸውን ጦርነቶች ምሁራዊው ዓለም ባያጤነውም  ከእነአካቴው እንዳልተፈጸሙና የሌሉ አድርጎ ቢተዋቸውም፣ ለዘላለሙ እንዳይቆፈርና እንዳይወጣ፤ ራሱን የቻለ ተጨማሪ አትሞ መዝጊያ እስካልኾነ ድረስ ይህ ስያሜ አያነጋግርም፡፡ (ሮማ ዓለምን በመላ በመያዝ የዓለማቱ ኃያል መንግሥት በነበረችባቸው የጥንት ዘመኖቿ ውስጥ፣ በተለያዩ አቅጣጫዎች በተደጋጋሚ ከኢትዮጵያውያን ጋር ተዋግታለች፡፡ በዓለም አቀፍ ደረጃ ያሉ ምሑራንና ተመራማሪዎች ጽሑፍ በሚቀርብበት የአካዳሚክ ዶት ኢዲዩ (Academic.edu) መካነ ድር፤ እንዲኹም፣ የጥንት ክት ሥራዎች መጽሔት በኾነው በኮሎራዶው ዩኒቨርሲቲ ክላሲክ አንቲክ ጆርናል በፈረንጆች 2013፣ በዲ-ሴልደን (ፕሮፌሰር) የቀረበው “ሃው ዘ ኢትዮጵያን ቼንጅ ሂዝ ስኪን” የተባለው የምርምር ሥራ ይህንኑ ይጠቁማል፡፡ “በግብፅ ፈርዖናዊ እና ከሮማዊው ወረራና ጥቃት” ኢትዮጵያውያን ራሳቸውን ጠብቀው፣ የደረሱባቸውን መክተው እያጠቁና እየረቱ የኖሩ መኾናቸውን ሲገልፅ በራሱ በቄሳር አውግስጦስ “ጌስቴው” ሳይቀር የተጠቀሰ ውጊያ እንደነበረ ይጠቁማል፡፡ በእንደነ ፕሊኒ ዓይነቱ የሮማን ዘመን ታሪክና መልክዓ ምድር ጸሐፊዎችም ያነሳሱት እንደኾነ ይገልጻል፡፡
በሌላ በኩል፣ አሜሪትስ- አንድ ዐይናዋ ሕንደኬ ታሪክ ላይም የሮማን ቄሳራዊ ጦር መግጠምዋ፣ የሮማን አዛዦች ሳይቀር እንዳስደነቀች ይነገራል፡፡ እንደነዚህ ዓይነቶቹ ተለቅመው በዘመን ቅደም ተከተል ቢደረደሩ ኢትዮጵያ ከሮም/ ጣሊያን ጋር ኹለቴ ብቻ በጦር ሜዳ እንዳልተሰለፈች ያሳውቃሉ፡፡ ከኹሉም በላይ፣ እነዚህን ታላላቅና ታናናሽ ዓውደ ውጊያዎች የሚገልጹት ግን የኢትዮጵያ የታሪክ ትውፊቶች ናቸው፡፡ በጥንቲቱ የንግሥና ሥርዓት መንግሥት መፈጸሚያ ከተማ፣ ከፓታ የተገኙት የኑቢያ ሠነዶች ይህን በየዘመኑ አቅርበዋል፡፡ እነዚህም በሌሎች የታሪክና አርኬዎሎጂዎች ግኝት ሊረጋገጡ የሚችሉ ናቸው፡፡ እንግዲህ እነዚያን ጦርነቶች ለዘላለሙ ድፍንፍን አድርጎ በማተም የሚያጠፋቸው እስካልኾነ ድረስ “ኹለተኛ” መባሉ አይከፋም፡፡ (ሮማንና ኢጣሊያን አንለይም ካልተባለ፡፡)
*    *    *
መጽሐፉ ከጦርነቱ አስቀድሞ የነበረውን የኢትዮጵያ የዓለም አጠቃላይ ኹኔታ፣ በተለይም የኢትዮ-ጣሊያንን ጨምሮ ከኹለተኛው የዓለም ጦርነት ጋር የሚሰናሰሉ ጉዳዮችን በመግለጥ ይጀምራል፡፡ በቀዳሚው ምዕራፍ አርበኛና አርበኝነት የተባሉትን ቃሎችና ጽንሰ ሐሳቦች በመፍታትና በመተርጎም መጀመሩ የመጽሐፉን ጥልቀት ገና ከወዲሁ ያመለክተናል፡፡ በየዘመኑና  በየፖለቲካዊ ፍላጎት እነዚህ ቃላት ልዩ ልዩ ኮነው ይያዛሉ፡፡ ከነበረው ብሔራዊ (ሀገራዊ) ትውፊት የወጣ አዲስ ዜግነት ለመፍጠር አስፈላጊ ኾኖ በተጀመረው የ“ሲቪክስ” ትምህርት “(ለማንኛውም ነገር) የሚኖር አለቅጥ የበዛ ፍቅር” ተብሎ የተፈታው አርበኝነት፤ በጦርነቱ ወቅት ለጣልያኖቹ ሽፍትነት ነበረ፡፡ “ከ1966 ዓመጽ (አብዮት) በኋላ ደግሞ ከደፈጣ ውጊያ ጋር” እንደተተነተነ በመጠቆም፣ እንደምን ኾኖ የታሪኩን ግንዛቤያችንን ሊያስለውጥ እንደቻለ ያስረዳል፡፡
“የአርበኝነቱ ጦርነት ያለ መንግሥት መሪነት፣ ሕዝብ በየመንደሩ እየተሰበሰበ ያካሔደው ዓመጽ ተደርጎ ተተርጉሟል፡፡ የግራ ዘመም ኮሚኒስት አብዮተኞች በቬትናም በኋላም በእነቼጎቬራ ከተካሔዱ ዓመጾች ጋር በማመሳሰል ለመተርጎም ሞክረዋል፡፡” (ገጽ 22)
“ለሀገር ህልውና፣ ለሥርዓት፣ ለኑሮው ዘይቤ የሚደረገውን” ጦርነት በዚያ ዘመን ሠርጾ ከነበረ ፀረ ቅኝ አገዛዝና ፀረ ፋሽስት እንዲኹም በየሀገሩ ከነበረው ከጨቋኝና ተራማጅ ካልተባሉ ገዥዎች ጋር ኹሉ ያለ የቅዋሜ ስሜትና ትግል ተደርጎ ይወሰዳል፡፡ ይህን የመሰለ “አብዮታዊ አተረጓጎም” መስጠቱ የነበረውን የአርበኝነት እንቅስቃሴ ጣሊያኖች ይከራከሩበት ከነበረው ሐሳብ ጋር ሠምሮ እስከመገኘት ድረስ አድርሷል፡፡ በአምስት ዓመቱ ውስጥም፤ በኢትዮጵያ የጣሊያን አስተዳደር በከተሞችና ጥቂት መንደሮች ላይ ብቻ ካልኾነ በሰፊው የሀገሪቱ ክፍል ፈጽሞ ያልሠፈነ እንደነበረ ከሚገለጸው ጋር የሚጣላና ጣሊያንም በዓለም ዓቀፍ መድረክ ትሟገትበት በነበረው አገነዛዘብ ተስተካክሎ እስከ መገኘት ድረስ የሚታይ አተረጓጎም ይኾናል፡፡ ይልቁንም፣ በዚህ መጽሐፍ ውስጥ ይህን ቃል/ ጽንሰ ሐሳብ የመግለጹ አላስፈላጊነት የሚታየው የንጉሠ ነገሥቱን አርበኝነት ለመናገርም ማስቻሉ ነው፡፡
ይኼው ጦርነት በአርበኝነት ውስጥ ኹለት የአርበኝነት ዓይነቶች የተፈጠሩበትና የታዩበት መኾኑንም፣ “የጦርነቱ ሒደት የፈጠራቸው አዳዲስ ጽንሰ ሐሳቦች” በሚለው ንዑስ ርእስ ሥር ይቆጠራሉ። ቀድሞም ከነበረው “ተጋዳይ አርበኛ” ሌላ “የውስጥ አርበኛ” እና “የስደት ተሟጋች አርበኛ” የተባሉ የአርበኝነት ዓይነቶችን ይጠቅሳሉ - ጸሐፊው፡፡
በኢትዮጵያውን ዘንድ የነበረው “ወራሪዎችን የመዋጋትና የመቋቋም ልምድ ቻይናውያን እንዲቀስሙ” ማኦሴቱንግ ሕዝባቸውን ወይም ሕዝባዊ ቀይ ጦራቸውን ሲመክሩ እንደነበረም በዚኹ መጽሐፍ ውስጥ እናገኛለን። ከጦርነቱ ቀደም ብሎ የነበረው የዓለም ኹኔታ ተብለው የሚገለጹት ከአንደኛው የዓለም ጦርነት በኋላ የተፈጠረው የየመንግሥታቱ አወጋገን፣ ከዚያ ጦርነት በኋላ የተፈጠረው የዓለም መንግሥታት ማኅበር (ሊግ ኦፍ ኔሽን” ይባል የነበረው) እና አሠራሩ የመሳሰሉት ኹሉ ከዚኹ ጦርነት ጋር የሚያያዙበት ስላላቸው ነው፡፡ ይልቁንም ደግሞ፣ ጦርነቱ በኋላ በየሀገራቱ መንግሥታት (በአሸናፊውና በተሸናፊው) ይደረጉ የነበሩት ውሎችና አፈጻጸማቸው ላይ እንደ መሠረተ ሐሳብ የተያዙት፣ የአሜሪካ ፕሬዚዳንት ውድሮው ዊልሰን እና የሶቭየት ኅብረቱ ቭላድሚር ኢልይች ሌኒን “የራስን ዕድል በራስ የመወሰን” እሳቤዎች፣ ከጦርነቱ በፊት የኢትዮጵያን መንግሥት ማዳከምያ ፕሮፓጋንዳ ኾኖ እንደቆየ፣ ጥላሁን ይገልጹልናል፡፡
ይህን እሳቤ የኹለቱ ሀገር መሪዎች ከተለያየ ጥያቄና መነሻ ፍላጎታቸው የተነሳ ነበር ያቀነቀኗቸው። በአንደኛው ዓለም ጦርነት ወቅት አሜሪካ በዓለም ላይ ልቃና በልጽጋ ብቅ ያለችበት ጊዜ ነበር፡፡ የዚያን ጊዜዋ አውሮፓ በጦርነትና በአብዮቶች ትተረማመስ ነበር። የመጀመርያው የዓለም ጦርነት ፍትሐዊ መርሕ ላይ በተመሠረተ ስምምነት ጦርነቱ እንዲዘጋ ሩስያ ጥሪ አደረገች፡፡ ይህንን በመያዝ፣ የአሜሪካው ፕሬዚዳንት ድሮው ዊልሰን “በአውሮፓ የተያዙት ግዛቶችን ቅድሚያ ከአውሮፓውያን እጅ ውጭ ማድረግ ስላለባቸው” አጋርነታቸውን በነፃነት ቢወስኑ ለአሜሪካ ወዳጅ ይኾናሉ በማለት “የራስን ዕድል በራስ” አለ፤ የሩስያው ሌኒናዊ ኮሚኒዝም “ዓለም የወዛደሮች ትኾናለች” በሚል ሕልም (ወታደራዊ ዓለም አቀፋዊነት) በአንድ ኮሚዩኒስታዊ ፓርቲ ሥር በማደራጀት የጀመረውን አብዮት በመላው ዓለም ለማድረስ ሲል፣ “የብሔር ጥያቄ” የሚል መፍትሔ ይዞ ተነሳ፡፡ (በኹለተኛው የዓለም ጦርነት ዘመን የነበረችው ሶቭየት ኅብረት በሩሲያ ዙርያ ያሉ ሀገሮችን በኅብረቱ ውስጥ ለመቀላቀል ሲል ስታሊን አጥብቆ ያቀነቅነው ስለነበረ ብዙውን ጊዜ ይህ “የብሔር ጥያቄ” የተባለው ሐሳብ፤ ከእርሱ ጋር ተያይዞ፣በተለይ በኛይቱ ሀገር ሲገለጽና ሲተነተን እናገኘዋለን፡፡)
*     *     *
ስለ ጦርነቱ ጠቅላይ አዛዥ ስለ ግርማዊ ቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ ያለውን ከጦርነቱ ጋር የተያያዘ ግንዛቤ እናውቀዋለን፡፡ “ማይጨው ላይ አንድ መድፍ ተደግፎ ፎቶ ተነሳ” ይላሉ ፕሮፌሰር መስፍን ወ/ማርያም፡፡ ከዚያ ሸሽተው፣ በስደት እንግሊዝ ቆዩ፤ ከአምስት ዓመት በኋላ በኦሜድላ በበላያ በኩል አድርገው፣ ሚያዝያ 27ቀን 1933 አዲስ አበባ ገቡ፡፡ እሳቸው የገቡበት ቀንም የነፃነት ቀን ተብሎ ይከበራል፡፡
ይህ ነው እንግዲህ በትንሽ ትልቁ የሚታወቀው የንጉሠ ነገሥቱ የጦርነት ታሪክ፡፡ ብዙ ታሪኮችም፣ የታሪክ መምህራንና ጸሐፊዎችም የሚያጎሉት ጉዳይ ነው። የጥላሁን ጣሰው የጦርነቱ ታሪክ ውስጥ ግን የንጉሠ ነገሥቱ ታላቅ የጦር መሪነት በተጨባጭ ጎልቶ ይታያል። ቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴን እንደ ጠቅላይ አዛዥ የጦር መሪ ለመመልከትና ለመያዝ ያልተቻለበትን ምክንያት ሲያስቡት በውኑ ራስን በጥያቄ ማዕበል ማንገላታት ብቻ ነው የሚተርፈው፡፡ ግራ አጋቢ ነው! ይህ መጽሐፍ ነው እንዲህ ባለ ጥያቄ ውስጥም የሚያስገባዎት! ንጉሠ ነገሥቱ በእርግጥም የዚያ ጦርነት ጠቅላይ አዛዥ ነበሩ፡፡ ይህን ጦርነት ከአዲስ አበባ ሳይነሱ ጀምሮ፣ ማይጨው ላይም የጦርነቱ መሪ ወይም የጦሩ ጠቅላይ አዛዥ እንደነበሩ የሚያዩበት መጽሐፍ ነው፡፡ ንጉሠ ነገሥቱ ወደ ውጭ ከወጡ በኋላ በየገጠሩ፣ በየቀበሌው፣ በየጎበዝ አለቃው እየተሰባሰበ በያለበት በእንቢተኝነት እንዲተጋተግ ለማሳመን የባተሉት ጣሊያኖች እንደነበሩ በማስረጃ አስደግፈው ያቀርቡልናል፡፡ ንጉሡ ሸሽቶ ፈረጠጠ ማስባሉም ቢኾን የጣሊያኖች መቀስቀሻ እንደነበረ ተወስቷል፡፡ እነዚህኑ በመቀበል ይዘን እንደኖርንም ጭምር፡፡
በዚህ በመጨረሻው የኢትዮ ጣሊያን ጦርነት፣ በየትኛውም ጦርነት ያልተገኘ ጥቅምና ውጤት ለኢትዮጵያ እንደተገኘም ነው ጥላሁን የጻፉት፡፡ መልካም ውጤቶች ያሏቸውንም ይቆጥሩልናል፡-
“ከመረብ ወዲህና ወዲያ ማዶ” ተለያይተው የነበሩት ሕዝቦቿ ተዋሃዱ፤የኤርትራና የቀሪው ኢትዮጵያ ጸረ ፋሺስት ታጋዮች በኀብረት ቆሙ፤
ኢትዮጵያ ትመኝ የነበረውን የባህር በር ባለቤትነት አሳካች፤
በሺ ኪ. ሜትር የሚቆጠር የባሕር ጠረፍ ድንበር ባለቤት ኾነች፡፡ (ገጽ 14)
ከነዚህም ሌላ ከጦርነቱ ፍጻሜ በኋላ ኢትዮጵያ የተባበሩ መንግሥታት ድርጅትን ለመመሥረት ከበቁት ሀገሮች አንደኛዋ ኾናለች፡፡ የአፍሪካ ነፃነት እውን እንዲኾንም የጦርነቱ ውጤት ግፊት አድርጓል፡፡ (ገጽ 14)
የጥላሁን ጣሰው የጦርነቱ ታሪክ መጽሐፍ ከሚተርክልን በተጨማሪ የዚህን የጦርነት ታሪክ ዘመን፣ ከኅዳር 27 ቀን 1927 ዓ.ም ጀምሮ፣ ከጦርነቱ በኋላ በ1934 ዓ.ም ጥር 23 ከእንግሊዝ መንግስት ጋር የስምምነት ውል እስከተፈረመበት ዕለት ድረስ ያሉትን፣ በዓመት፣ ወርና ቀን ቅደም ተከተል የደረደረልንም መጽሐፍ ነው፡፡ በወቅቱ ፖለቲካዊ ካርቱን ያቀርብ የነበረው ዴቪድ ሎው፣ በሞሶሊኒና በሊጉ ይዘብትባቸው የነበሩትን ጨምሮ በርካታ ፎቶዎችም ተካትተውበታል። ብዙውን ጊዜ በመሰል ታሪክ ጸሐፊዎች (በአማርኛ) ዘንድ የማያጋጥመን የፊደል ተራ ማውጫም ያለው መጽሐፍ ነው፡፡
በአጠቃላይ ስለ ጦርነቱ እስከ ዛሬ ብዙ መጻሕፍት የቀረቡልን ቢመስልም፣ በተሟላ መጠን የቀረበበት ግን ይሄው የጥላሁን ጣሰው መጽሀፍ ነው ብለን ለመናገር ያስደፍረናል፡፡ ራሳቸው አስቀድመው እንደገለጹትም፤ስለ ጦርነቱ ለታሪክ ተመራማሪዎችና መርማሪዎችም ብሔራዊ አተረጓጎም እስከ መሆን ድረስ የበቃ ነው፡፡

• “...lead us not into temptation” የሚለው አባባል ስህተት ነው ብለዋል።
      • በአማርኛ ሕትመቶች፣ “ወደ ፈተና አታግባን” ተብሎ እንደተተረጎመ ይታወቃል።

   አባታችን ሆይ ተብሎ የሚታወቀው ፀሎት እንዲሻሻል እንደሚፈልጉ የካቶሊክ ቤተክርስትያን ፓትርያርክ ፍራንሲስ፣ ለሮይተርስ ተናገሩ። “አባታችን ሆይ”፣ የዘወትር ፀሎት እንደሆነ በብዙዎች እንደሚታመንበት ሮይተርስ ጠቅሶ፣ በዚሁ ፀሎት ውስጥ፣ “...lead us not into temptation” የሚለው አባባል ስህተት እንደሆነ ፓትርያኩ አባ ፍራንሲስ እንደተናገሩ ትናንት ዘግቧል።
King James Version (KJV) ተብሎ በሚታወቀው ትርጉም ላይ “...lead us not into temptation” በሚል አገላለፅ ተተርጉሟል። ወደ ፈተና አትምራን እንደማለት ነው።
American Standard Version (ASV) ተብሎ በሚታወቀው ትርጉም ላይ ደግሞ “...bring us not into temptation” በሚል አገላለፅ ሰፍሯል። ወደ ፈተና አታድርሰን፣ ወደ ፈተና አታቅርበን፣ ወደ ፈተና አታስገባን... የሚል ተመሳሳይ ትርጉም የያዘ ነው።
ፓትርያርኩ አባ ፍራንሲስ፣ እነዚህ አባባሎች፣ በተሳሳተ አተረጓጎም ሳቢያ የተዛባ መልዕክት ያዘሉ ናቸው ብለዋል። ፈጣሪ ለፈተና ይዳርገናል የሚል የተዛባ መልዕክት የያዙ የተሳሳቱ አተረጓጎሞች እንዲስተካከሉ እፈልጋለሁ ሲሉም ተናግረዋል - ጳጳሱ። “...let us not into temptation” በሚል አባባል መስተካከል እንዳለባቸውም ጳጳሱ ገልፀዋል። ይህ አባባል፣ ከቀድሞዎቹ የእንግሊዝኛ ትርጉሞች የተለየ መልዕክት የያዘ እንደሆነ ተናግረዋል። ለፈተና አታጋልጠን፣ ከፈተና ጠብቀን፣ ከፈተና ከልለን አይነት መልእክት ይመስላል አተረጓጎሙ። እነዚህ አባባሎች፣ ከቀድሞው የአማርኛ ትርጉም፣ (ወደ ፈተና አታግባን ከሚለው አባባል) ጋር፣ የዚያን ያህል የተራራቀ መልዕክት ይዘዋል ለማለት ግን አስቸጋሪ ነው (... ወደ ፈተና አታስገባን... ከማለት ይልቅ... ወደ ፈተና አታግባን ተብሎ የተተረጎመ ከመሆኑ አንፃር)።
አባታችን ሆይ የሚለው ፀሎት በክርስትና መጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ፣ በሁለት ቦታዎች የሰፈረ መሆኑን ዘገባዎቹ አያይዘው ገልፀዋል።
ማትዮስ 6፡9-13 የሰፈረው ፅሁፍ የመጀመሪያው ሲሆን፣ እንዲህ ይላል።
በሰማያት የምትኖር አባታችን ሆይ፣  ስምህ ይቀደስ፣ መንግስትህ ትምጣ፤
ፈቃድህ በሰማይ እንደሆነች፣ እንዲሁ በምድር ትሁን፤
የዕለት እንጀራችንን ዛሬ ስጠን፤
እኛም ደግሞ የበደሉንን ይቅር እንደምንል፣ በደላችንን ይቅር በለን፤
ከክፉም አድነን እንጂ፣ ወደ ፈተና አታግባን፤ መንግስት ያንተ ናትና ኃይልም ክብርም ለዘለዓለሙ፤ አሜን።
ሁለተኛውና አጠር ብሎ የቀረበው ደግሞ በሉቃስ ወንጌል የተፃፈው ነው።
ሉቃስ 11፡2-4
በሰማያት የምትኖር አባታችን ሆይ፣  ስምህ ይቀደስ፣ መንግስትህ ትምጣ፤ ፈቃድህ በሰማይ እንደሆነች፣ እንዲሁ በምድር ትሁን፤
የዕለት እንጀራችንን ዕለት በዕለት ስጠን፤
ኃጢአታችንንም ይቅር በለን፣ እኛ ደግሞ የበደሉንን ሁሉ ይቅር ብለናልና፤ ከክፉም አድነን እንጂ፣ ወደ ፈተና አታግባን።

 “ከእንግዲህ ወዲህ አርማችሁንም ኢትዮጵያዊነትን አድርጉ!”
ይህን ደብዳቤ የምፅፍላችሁ እንደ አንድ ለሃገሩ ተቆርቋሪ ግለሰብ ሆኜ፣እናንተ አሁን በምትመሯት ኢትዮጵያ ላይ ፍቅር፣ አንድነት፣ ሰላም፣ እኩልነትና ዲሞክራሲ ይሰፍኑ ዘንድ ይረዳ ይሆናል በማለት ነው። ቀጥሎም፣ በኢህአዴግ ውስጥ የተደራጁት የእናንተ አባላት ለሆኑት ለኦሮሞና አማራ ክልሎች ፕሬዚዳንቶች ለማ መገርሳ እና ገዱ አንዳርጋቸው፤ ኢትዮጵያዊነትን እንዲያራምዱ በመከርኳቸው መሰረት፣ ሃሳቤን ብትጥሉትም ብታፀድቁትም የበኩሌን እንደ መርህ እናንተንም ለመምከር ነው። ከዚህም በተጨማሪ፣ ህሊናዬ ይህን ደብዳቤ ፃፍላቸው ስለ አለኝ፣ ለህሊናዬ ታዛዥ ሆኜ ነው።
ተጋሩን፣ ጉራጌን፣ አማራን፣ አፋርን፣ ኦሮሞን፣  ከምባታን፣ ሀዲያን፣ ሲዳማን፣ ሱማሌንና ሌሎቻችንን በኢትዮጵያም ሆነ በውጪ ሀገር የምንኖረውን ኢትዮጵያውያንንና ትውልደ ኢትዮጵያውያንን ሁሉ የሚያዛምደን፣ ኢትዮጵያን በስሙ ያስጠራት የንጉሦች ንጉሥ፣ የካህኖች ካህን የነበረው አባታችን ኢትዮጵ ነው። ኢትዮጵ የኖረው በጣና ደሴቶች ላይ ሲሆን ዘመኑም ከ4000 ዐመታት በፊት ነው። እሱም 10 ወንዶችና 3 ሴቶች ልጆች ወልዶ ነበር። 10ሩ ወንዶች ልጆች 10 ነገዶች ሆነው፣ ለ4000 ዐመታት በመባዛት እኛን የዛሬዎቹን ኢትዮጵያውያንን አስገኝተዋል። የኢትዮጵ አስሩ ወንዶች ልጆች ስሞችም፡- አቲባ፣ ቢዖር፣ ተምና፣ አቴር፣ አሻን፣ አክዚብ፣ በሪሳ፣ ቴስቢ፣ ቶላ፣ እና አዜብ ነበሩ።  ከሶስት ሴት ልጆቹ አንድዋ ሱባ ትባል ነበር። የዛሬ 4000 ዐመት ከወጡት ከእነዚህ ስሞች ውስጥ አንዳንዶቹ አሁንም ድረስ ኢትዮጵያ ውስጥ አሉ። ለምሳሌ አዜብ፣ በሪሳ፣ ቶላ፣ አሻን እና ሱባ የተባሉት። ከአባታችን ከኢትዮጵ በኋላ የተከተሉት ነገሥታት ልጆቹ፣ የኢትዮጵያን ስልጣኔ በመላው አፍሪካ አሰራጭተው፣ ዛሬ አፍሪካ የሚባለው ሰፊ ምድር እስከ ዛሬ ሁለት መቶ ዐመታት ድረስ ኢትዮጵያ ተብሎ ይጠራ ነበር። LOWER እና UPPER ETHIOPIA ብለው ከፍለውት ነበር።  ከእዚህም በላይ የህንድ ውቅያኖስና ከምእራብ አፍሪካ ብብት ስር ያሉት ውቅያኖሶች ሁሉ የኢትዮጵያ ውቅያኖሶች ይባሉ ነበር።  አሁንም ቢሆን አፍሪካ፣ አፍሪካ የተባለችው በእኛው በአፋሮች ስለሆነ ደስ ይለናል እንጂ አንቆጭም። እስያም እስያ የተባለችው ንግሥተ ሳባ ዙፋኑን በተካችው በዐፄ እስያኤል ስለሆነ በዚህም እንታበያለን። ኢትዮጵያ የሚለው ቃል ትክክለኛ ትርጉሙ  “የተቃጠለ ፊት” ሳይሆን “ቢጫ ወርቅ” ስጦታ ለእግዚእብሄር ነው። ቅዱስ ስሟን ለመፋቅ ወይም ለመቀየር የተመኙ ሁሉ የኢትዮጵያ ስም ከእግዚአብሄር ጋራ የተያያዘ በመሆኑ ምኞታቸው ከሽፎ፣ የእግዚአብሄር ዐይኖች ኢትዮጵያ ላይ ተተክለዋል። በቅዱስ መፅሃፉ ውስጥ እግዚእብሄር ኢትዮጵያን ደጋግሞ የሚጠራት ያለ ምክንያት አይደለም። ከማንም ይልቅ ኢትዮጵያን ስለሚወዳት ነው። በነቢዩ አሞፅ አፍ እግዚአብሄር እንዲህ ይላል፡-
“እናንተ የእስራኤል ልጆች ሆይ፤ እናንተ ለኔ እንደ ኢትዮጵያውያን ልጆቼ አይደላችሁምን?”  (አሞፅ 9: 7) ከእዚህ ጥቅስ የምንማረው እኛን ኢትዮጵያውያንን እግዚአብሄር ከእስራኤላውያን ይበልጥ ወይም እኩል እንደሚወደን እና ልቡ ውስጥ እንደአለን ነው። ስለዚህ እሱ ጥሎ አይጥለንም።
የንግሥት ሳባ የልጅ፣ ልጅ፣ ልጅ የነበረው አፄ አክሱማይ በገነባትና በስሙ በሰየማት በአክሱም ከተማ የተመሰረተው የኢትዮጵያ ስልጣኔ፣ ለበርካታ ምዕተ ዐመታት ገንኖ፣ ኢትዮጵያን አስከብሯት ነበር። ብልሁና ፍትሃዊው አፄ አክሱማይ፣ ከኢትዮጵያ ዳር ድንበር አልፎ፣ ኢትዮጵያ በዛን ጊዜ ታስተዳድራቸው በነበሩት የግብፅ፣ የሊብያና የኑብያ እንዲሁም የባቢሎን ህዝቦች ሳይቀሩ ንጉሦቻቸው ሲበድሉአቸው ለአቤቱታ ወደ እሱ ይጎርፉ ነበር። በእዚህ ምክንያት የነገሥታት እራስ፣ የዐለም አባት ተብሎ ይጠራ ነበር።
የኢትዮጵያን ሰንደቅ ዐላማ እያውለበለቡ፣ ከአክሱማይ ልጅ ከአፄ አውሳብዮስ ጀምሮና ከሱም በኋላ የነገሡት ነገሥታትም፣ ንግሥት ዮዲት (እሳቶ የሚል የቅፅል ስም ጠላቶቿ የሰየሙላት) እስከ አሳደደችው እስከ አንበሳ-ሰገድ ድረስ ለ850 ዐመታት አክሱምን መናገሻ ከተማቸውና ማእከል በማድረግ ለ850 ዐመታት ያህል በኢትዮጵያ ላይ ነግሠዋል። ከቀዳማዊ ምንይልክ ዘመን ከጀመርን ደግሞ በአክሱም ላይ የነበረው የንግሥና ዘመን ወደ 950 ዐመታት ገደማ ይሆናል። በላስታ ላሊበላ ለ343 ዐመታት ያህል የነገሡት የዛግዌ ስርወ-መንግሥት አባላትና ከአፄ ዩኩኖአምላክ ጀምሮ እስከ ቀዳማዊ ኅይለሥላሤ ድረስ በሸዋ በቀዳማዊ ምንይልክ ዙፋን ላይ የነሡትም ነገሥታት ምንጫቸው ከአክሱም እንደ ነበር በኩራት ይናገሩ ነበር። በተጨማሪም የታላቁ የኢትዮጵ ዘር ነን ብለው በኢትዮጵያዊነታቸው ይታበዩና ይጀነኑ ነበር። ሁልጊዜም የገናናው የኢትዮጵ ዘር፣ ኢትዮጵያውያን ነን ይሉ ነበር። በቅርቡ ከአፄ ቴዎድሮስ ቀጥለው በኢትዮጵያ ላይ የነገሡት የትግራዩ ተወላጅ አፄ ዮሐንስም በኢትዮጵያዊነታቸው ከመኩራት አልፈው ተርፈው አፄ ቴዎድሮስ የጀመሩትን የኢትዮጵያ አንድነት ቀጥለውበት የኢትዮጵያን ዳር ድንበር እያስፋፉና እየጠበቁ ህይወታቸውን አሳልፈዋል። አፄ ዮሐንስ የቆሙት ለትግራይ ብቻ ሳይሆን ለመላዋ ኢትዮጵያ ነበር። እሳቸው ለአንዲት ካልኢትም እንኳን ኢትዮጵያዊነታቸውን ጥያቄ ውስጥ አስገብተው አያውቁም። ጣልያንን በዶግአሊና በአድዋ ያርበደበዱት የሳቸው የጦር አበጋዝ ጅግናው ራስ አሉላ አባ ነጋም ተጋሩነታቸው እንደተጠበቀ ሆኖ፣ እስከ አጥንታቸው ጥልቀት ድረስ የጠሩና የነጠሩ ኢትዮጵያዊ ነበሩ። በኢትዮጵያዊነታቸው ለአፍታም ያህል ከጣልያኖች ጋር ያልተደራደሩት  ተጋሩው ባሻ አውአሎም እንኳን ለአድዋ ድል ወሳኝ የሆነውን መረጃ ለጌታቸው ለአፄ ምንይልክ ያቀበሉት በዚያው በኢትዮጵያዊነት ፍቅራቸው ተቃጥለው አልነበረምን? እንግዲህ የእናንተስ የትግራዋይ ተወላጆቹ ኢትዮጵያዊነት ጥያቄ ውስጥ ሊገባ ይገባልን? እናንተስ የእነዚህ ታላላቅ ኢትዮጵያውያን ዝርያ አይደላችሁምን? እባካችሁ የእነሱ ዝርያ መሆናችሁን አስታውሳችሁ፤ ኢትዮጵያዊነትን አጥብቃችሁ ያዙ። ለሌሎችም አርአያ ሁኑ። ተራዎቹንና ብርቱ ክርስትያን የሆኑትን ክቡራኑን የትግራዋይ እባቶቻችሁንና እናቶቻችሁን እስቲ ተመልከቱአቸው። በኢትዮጵያዊነታቸው ኮርተው አስከሬናቸው በኢትዮጵያ ሰንደቅ አላማ ተጠቅልሎ አይደለምን የሚቀበሩት? እናንተስ ከእነሱ አብራክ የወጣችሁ አይደላችሁምን? አሁንም ኢትዮጵያን ካለችበት ማጥ የሚያወጣት ኢትዮጵያዊነት ብቻ እንጂ በቋንቋ ላይ የተገነባው፣ በልማድ ብሄር ብሄረሰቦች የሚባለው በትክክለኛ አጠራሩ ግን ጎሳና ነገድ በሆነው ክልለኝነት አይደለም። ይህ ጎሰኝነትና ክልለኝነት፣ የጎሳንና የነገድን የብሄር ብሄረሰብን መብት አስከብራለሁ ቢልና መብቱ ተገቢ ቢሆንም ድንበር እየሳተ፣ እውስጡ ያሉትን የአናሳዎች መብት እየገፈፈ፣ አያሌ ቀውስ እንዳስከተለ ከእናንተ የተሰወረ አይደለም።  ለ26 ዐመታት ተሞክሮም ከጥቅሙ ይልቅ ጉዳቱ አይሏል።
በእውነትም አሁን ኢትዮጵያ ላለችበት ችግር መፍትሄው፣ኢትዮጵያዊነት እንጂ በቋንቋ ላይ የተገነባ ጎሰኝነት አይደለም። ጎሳ ማለት ቋንቋ ማለት ነው፤ “ጎሰአ”፣ ማለትም  ተናገረ  ከሚለው የግዕዝ ቃል የፈለቀ ነው። ስለዚህ ቋንቋ ማለት ጎሳ ነው። ጎሳ ማለትም ቋንቋ ነው።  በሌላ አነጋገር፣ ጎሳ የቋንቋ ክፍል እንጂ የደም ወይም የዘር ዘርፍ አይደለም። አንድ ዐይነት ቋንቋ የሚናገሩ ሰዎች በሞላ በዛ ቋንቋ አፍ ከፈቱ የዛ ቋንቋ  ወይም ጎሳ አባላት ይሆናሉ። ይህን ሁልጊዜ በምጠቅሰው ምሳሌ ላሳይ። እኔ በፈረንሳይ፣ በጀርመንና እንግሊዝ ሃገሮች ኖሬ፣ ሶስት ልጆች ብወልድና እነሱ ፈረንሳይኛ፣ ጀርመንኛና እንግሊዝኛ ቢናገሩ፣ የእኔ አፍ መፍቻ ደግሞ ኦሮምኛ ቢሆን ልጆቼ ሶስት የተለያዩ ቋንቋዎች በመናገራቸው ጎሳቸው ፈረንሳይ፣ ጀርመንና እንግሊዝ ቢሆንም የእርስበርስ ዝምድናቸው አይፋቅም።  እኔም ኦሮምኛ ስለተናገርኩ ጎሳዬ ኦሮሞ ቢሆንም አባትነቴ አይሰረዝም። እኛን የሚያዛምደን የኔ ደም ወይም ዘር እንጂ ቋንቋ ወይም ጎሳ አይደለምና። ስለዚህ ሰዎችን በስጋ የሚያዛምድ ደም ወይም ዘር ነው እንጂ ቋንቋ ወይም ጎሳ አይደለም።  ደሞ ቋንቋ ሊረሳም ሊለዋወጥም ስለሚችል አስተማማኝ የማንነት መለያ ሊሆን አይችልም። ኢትዮጵያ ውስጥ 82 ቋንቋዎችና ዳያሌክቶች እንደ አሉ ይነገራል። ቋንቋ ማለት ጎሳ ማለት ስለሆነ በዚህ ቁጥር መሰረት 82 ጎሳዎች አሉ ማለት ነው። በልጆቼ ምሳሌ እንደምናየው፤ ደም እንጂ ቋንቋ አያዛምድም።  እነዚህ ሁሉ የቋንቋ ተናጋሪዎች በደም ወይም በዘር የሚዛመዱት ሁሉም ከኢትዮጵ ወይም ከእሱ 10 ልጆች አብራክ ስለፈለቁ ብቻ ነው። በተጨማሪ ደግሞ በጋብቻ ደም ስለተደበላለቁና በኢትዮጵያ ግዛት ለሺዎች ዐመታት አብረው ኖረው በባህል፣ በልቦና እና እምነት ስለተሳሳቡ እና ስለተወሳሰቡ እንዲሁም የጋራ የማንነት እሴቶችን ስለአካበቱ  ነው።  እንግዲህ እናንተንም የኢትዮጵያን ህዝቦች የሚያዛምዳችሁና አንድ የሚያደርጋችሁ፣ ከዛም አልፎ የሚያኗኑራችሁ፣ ኢትዮጵያዊነት እንጂ ጎሰኝነት ወይም በቋንቋ ላይ የተመሰረተ ክልል አለመሆኑን ተረድታችሁ፣ የኢትዮጵያን ችግር ለመፍታት ተጋሩነታችሁ እንደተጠበቀ ሆኖ ኢትዮጵያዊነት ላይ አተኩሩ።
ኢትዮጵያዊነት ላይ አትኩራችሁም የአመራር ሚና እየተጫወታችሁ፣ ሌሎቹንም ኢትዮጵያውያንንም፣ ማለትም ብዙሃኑን የኦሮሞን፣ የአማራን፣ የአፋርን፣ የተጋሩንም ጭምር፣ የሲዳማን፣ የጉራጌን፣ የሃዲያን፣ የከምባታን፣ የሱማሌን፣ የከፋንና ሌሎቹን ሁሉ የኢትዮጵያ ህዝቦች ተወካይዎች ጋብዛችሁ ተመካክራችሁ፣  ኢትዮጵያ ውስጥ ፍትህና ርትእ፣ የሰብአዊና የሃብት እኩልነትን አስከብሩ። የንግግርና የፅሁፍ ነፃነት፣ በድፍን ኢትዮጵያ የመንቀሳቀስና የመኖር መብትን አስከብሩ። በጎሰኝነት ጦስ በከንቱ የሚፈሰውን ደም አስቁሙ። የፖለቲካ እስረኞችን ሁሉ በአስቸኳይ ፍቱ። ኢትዮጵያ ውስጥ እና ከኢትዮጵያ ውጪ የአሉትን የፖለቲካ ፓርቲዎችና የህብረተሰባዊ ማህበራትን ሳትንቁ በማሰባሰብ፣ እነሱም የሃገራቸውን ወደፊት እንዲወስኑ ዕድል ስጡአቸው። ከእንግዲህ ወዲህ አርማችሁንም እስከ መጨረሻው ድረስ ኢትዮጵያዊነትን አድርጉ። አሁን በሃረር የሶማልያ ክልል፣ በእብሪተኞች መሰሪነት ከመኖሪያቸው የተፈናቀሉት ኦሮሞዎችና ከነሱ ጋር በሰላም ለዘመናት የኖሩት ሶማሌዎች ወደ ቀድሞ ቦታቸው እንዲመለሱ ጣሩ። የጎንደር ህዝብ ጥያቄ እንዲመለስ የተቻላችሁን ፈፅሙ። ይህን ሁሉ ብትፈፅሙ ኢትዮጵያ ውስጥ ሰላም፣ ፍቅር፣ አንድነት፣ እኩልነት፣ የንግግርና የፅሁፍ ነፃነት፣ የመሬት ባለቤትነት፣ የሰብአዊ መብት፣ ዲሞክራሲና የህግ የበላይነት ይሰፍናሉ። ኢትዮጵያም በነፃነቷ ለዘላለም ትኖራለች።
እነዚህን አንገብጋቢ ጉዳይዎች በመፈፀም ፈንታ እንደ ቀድሞው ለብቻችን ስልጣኑን ጨብጠን፣ እንደ በፊቱ በጦር ኅይል ብቻ ችግሩን እንፈታዋለን ካላችሁ፣ ውጤቱ ይብስ እልቂት፣ ይብስ ሰቆቃ ይሆናል። አመፅ አመፅን ይወልዳልና የአመፅ ክበት እየተሽከረከረ ሁሉንም ያወድማል። አሁን ሁሉም ሰው በፖለቲካ ስለበሰለና መብቱንና ማንነቱን ስለአወቀ፣ ፍርሃቱን አሽቀንጥሮ ጥሎ ለመብቱና ነፃነቱ ሲዋደቅ እየታየ ነውና። ደሞም የአሁኗ ኢትዮጵያ፣ የዛሬ 26 ዐመትዋ አይደለችምና። ስለዚህ ቡናው ፈልቶ መንተክተኩን ማሽተት ይገባችኋል። እናንተ ባላችሁበት የስልጣን ማማ ላይ ሆናችሁ፣ ሰፊውን የትግራይን ህዝብ ጨምሮ ለመላው የኢትዮጵያ ዜጎች ህይወት መጠበቅና ደህንነት ሃላፊነት አለባችሁ። ለራሳችሁም ደህንነት እንዲሁ። እምብዛም ብልሃት ያደርሳል ከሞት፣ እምብዛም ስለት ይቀዳል አፎት ተብሏልና። ደሞም ኅያል ሁልጊዜ በጦሩ ብዛት አያሸንፍምና። አዱኛና ጊዜም ከዳተኛ ናቸውና። በዚህ ዐለም ላይ ለዘላለም ፀንቶ የሚኖር ምንም ነገር የለምና። ሁሉም ነገር ማብቂያ ወቅት አለውና። የእናንተም ጉልበት እንደ ድሮው አይደለም። በዱር በገደሉ 17 ዐመታት፣ በከተማዎች 26 ዐመታት፣ በጠቅላላው ቢያንስ ለ43 ዐመታት ታግላችሁ እረፍት አግኝታችሁም አታውቁም። ለመሆኑ ጡረታ ወጥታችሁ እፎይ ብላችሁ የምትተርፋችሁን አጭር እድሜ የምትዝናኑባት መቼ ነው? ከእናንተ በዕድሜ ለሚያንሱት፣ ጉልበትና አዲስ ሃሳብ አዲስ እውነታ ለሚያፈልቁት ወጣት ኢትዮጵያውያን ስልጣን አስተላልፋችሁ፣ እናንተ የታፈራችሁ እንዲሁም የተከበራችሁና እንደ አርአያ የምትታዩ አረጋውያን ዜጎች የምትሆኑበት ወቅትስ መቼ ይሆን?  እባካችሁ ሥልጣን በሰላማዊ መንገድ በመልቀቅ፣ለወጣቱ ትውልድ እንዲሁም ለአፍሪካ አምባገነን መሪዎች አርአያ ሁኑ፡፡ እናንተም በአገራችሁ ከሥልጣን በኋላ እፎይ ብላችሁ ኑሩ፡፡ ለኢትዮጵያም እፎይታ ስጡአት፡፡ ይበልጥ ክብርና ድል እንጂ ሽንፈትና ውርደት አይሆንባችሁም። ሥልጣናችሁን በክብር እንጂ በውርደት እንደማትቋጩት አምናለሁ፤ እመኛለሁም። ስለዚህ የኔን ትንሿን ምክሬን ሳትንቋት እንደምትተገብሯት እምነቴ የፀና ነው።
የኢትዮጵያ ታሪክ የ100 ዐመት ሳይሆን በሺህዎች የሚቆጠር መሆኑን የአክሱም ታሪክ ብቻ እማኝ ነው። መላው አፍሪካ ድሮ ኢትዮጵያ ይባል እንደነበር የሚመሰክር ጥንታዊ ካርታ እታች ሰፍሮአል። ያኔ አፍሪካ የታችውና የላይኛው አፍሪካ ተብሎ ነበር የተከፈለው። ዝቅ ብላችሁ እሱን ከማየት አትዘናጉ።
 በሚቀጥለው ገፅ የአለው ካርታ ደግሞ ከምዕራብ አፍሪካ ብብት በታች ያለው ውሃ ሁሉ የእትዮጵያ ውቅያኖስ ይባል አንደ ነበር ያሳብቃል። ዛሬ የህንድ ውቅያኖስ የሚባለውም ጥንት የኢትዮጵያ ውቅያኖስ ይባል እንደነበር የሚያሳይ ካርታም ዐይቻለሁ።
ምእራብ አፍሪካ ብብት ስር በእንግሊዝኛ የኢትዮጵያ ውቅያኖስ የሚለውን ፅሁፍ አስተውሉ።

   ከዕለታት አንድ ቀን፣ አንድ ዕውቅ የአገር ፈላስፋ፣ አንድ ወንዝ ዳር እየተቀመጡ ምርምር፣ ምህላና ጥልቅ - ፀሎት ያደርጉ ነበር ይባላል፡፡ ወንዙ በፀጥታ መጥቶ፣ በፀጥታ በአዛውንቱ ፈላስፋ አጠገብ ያልፍና ቁልቁል በተዳፋቱ ይወርዳል፡፡ ይሄ ፀጥ ብሎ የሄደ ወንዝ፤ የአዛውንቱን ተመስጦ አልፎ በጨዋ ደንብ ያለ አንዳች ድምፅ ይወርድና አንድ የሚገርም ጩኸት ያሰማል፡፡ አዛውንቱ ፈላስፋ በወንዙ ቅላፄና ጠባይ ለብዙ ዓመታት ሲገረሙ ኖረዋል፡፡
አንድ ቀን አንድ እረኛ ከብቶቹን ውሃ ሊያጠጣ ወደ ወንዙ መጥቶ አዛውንቱን ያገኛቸዋል።
“እንደምን ዋሉ አባቴ?” ይላል፤ በአገሩ ደንብ እጅ እየነሳ፡፡
“ደህና፤ እግዚአብሔር ይመስገን” ይሉታል፤ በአክብሮት፡፡
“ምን እያደረጉ ነው?”
“የተመስጦ ፀሎት እያደረስኩና ይሄ ወንዝ የእኔን ምህላ ሳይረብሽ፣ በፀጥታ ማለፉ እየገረመኝ ተፈጥሮን እያደነቅሁኝ ነው”
“ይሄ እንዴት ያስደንቅዎታል? ከእርሶ ከተለየ በኋላኮ ወንዙ መጮሁ አይቀርም”
“ከእኔ በኋላ ምን ያስጮኸዋል?”
“ከእርሶ በኋላ ቁልቁለቱን ሲወርድ አንድ ትልቅ ቋጥኝ ድንጋይ አለ፡፡ ያንን ድንጋይ ውሃው ይገጨዋል፡፡ ከፍተኛ ድምፅ ይፈጥራል፡፡ ውሃው ያንን ቋጥኝ ሲመታው ታላቅ ጩኸት ይጮሃል፡፡ ‹ውሃውን ምን ያስጮኸዋል? ድንጋይ› የሚባለው አነጋር የመጣው ከዚህ ነው”
አዛውንቱ ተገረሙና፤
“ዕድሜ ልኬን እዚህ ስኖር፣ ወደዚህ ወንዝ የምመጣው የእኔን ፀሎት አክብሮ በፀጥታ ማለፉን ለማየት ብቻ ነበር፡፡ እኔን ካለፈ ወዲያ የሚጮኸው በአምላክ ትዕዛዝ ነው እል ነበር፡፡ ለካ እንዳንተ የተፈጥሮን ተዓምር የሚያይ ሰው ከጎኔ እንዲኖር ያስፈልግ ኖሯል”
እረኛውም፤
“አባቴ፤ እኔ የነገርኩዎት ማንም የሚያየውንና የሚያውቀውን ነገር ነው፡፡ ይልቁንስ የሚያስገርመው ለዓመታት ውሃው ውስጥ የተቀመጠው ቋጥኝ ድንጋይ የሚያስበው ነገር ነው፡፡ ሁልጊዜ የሚኮፈሰው ‹በዋና ከእኔ የሚበልጥ ማንም የለም› እያለ መሆኑ ነው፡፡”
“ይገርማል” አሉ አዛውንቱ፤ “የቆመው ሁሉ የሄደ፣ ውሃው የገጨው ሁሉ የዋኘ፣ ከመሰለው እንቅስቃሴ ከንቱ ቀረ ማለት ነው፡፡ ከዚህ ይሰውረን!” አሉ፡፡
*       *      *
አካባቢያችንን በቅጡ ካላየንና በሚገባ ካልመረመርን፣ እያሰብን ሳይሆን እየተኛን ነው! ከተኛን ደግሞ የተመኘነው ለውጥ አይመጣም፡፡ በሀገራችን የምንናገረውን የሚያዳምጥ፣ ያዳመጠውንም የሚያውጠነጥን ዜጋ ከሌለ የለውጥና የተሀድሶ ተስፋ ይጨልማል፡፡ ማንም የምንሰጠውን አስተያየት ከጉዳይ ካልጣፈ መግባባት ድራሹ ይጠፋል፡፡ የመናገርና ሀሳብን የመግለፅ ዲሞክራሲያዊ ነፃነት አለ የምንለው፣ የምንናገረውን እህ ብሎ የሚሰማ፣ ሰምቶም እራሱን የሚመረምርና የሚለውጥ የበላይ አካል ሲኖር ነው! ይሄ ከሌለ በድንጋይ ላይ ውሃ ማፍሰስ ነው ትርፋችን፡፡ ለውጥ አይኖርም፡፡ እንቅስቃሴ አይኖርም፡፡ የኑሮ መልክ እየተጎሳቆለ ይመጣል፡፡ የሰማው ያላንዳች ፋይዳ ያልፋል፡፡ ያልሰማው እንደ አዲስ ኃይል መጥቶ ያደነቁረናል፡፡ ገጣሚና ተርጓሚ ከበደ ሚካኤል፤ “አዝማሪና ውሃ ሙላትን” የፃፉት ያለነገር አይደለም፡፡ እነሆ፡-
“አንድ ቀን፣ አንድ ሰው፣ ሲሄድ በመንገድ
የወንዝ ውሃ ሞልቶ፣ ደፍርሶ ሲወርድ
 እዚያው እወንዙ ዳር፣ እያለ ጎርደድ
አንድ አዝማሪ አገኘ፣ ሲዘፍን አምርሮ
በሚያሳዝን ዜማ፣ ድምፁን አሳምሮ
“ምነው አቶ አዝማሪ፣ ምን ትሠራለህ?”
ብሎ ቢጠይቅ፤
“ምን ሁን ትላለህ?”
“መንገዴን ዘግቶብኝ የውሃ ሙላት
እያሞጋገስኩት፣ በግጥም ብዛት
ሆዱን አራርቶልኝ፤ ቢያሻግረኝ ብዬ”
“አሁን ገና ሞኝ ሆንክ፣ ምነዋ ሰውዬ
 ነገሩስ ባልከፋ፣ ውሃውን ማወደስ
 ግን እንደዚህ ፈጥኖ፣ በችኮላ ሲፈስ
ምን ይሰማኝ ብለህ፣ ትደክማለህ ከቶ
ድምፁን እያሽካካ፣ መገስገሱን ትቶ
 እስኪ ተመልከተው፣ ይህ አወራረድ
 ያልሰማው ሲመጣ፣ የሰማው ሲሄድ
 ተግሳፅም ለጠባይ፣ ካልሆነው አራሚ
 መናገር ከንቱ ነው፣ ካልተገኘ ሰሚ!”
የሚሰማ ሳይኖር መናገር፣ አገርን አያበለፅግም፡፡ አስቦ የሚናገር ከሌለ፣ መደነቋቆር አይቀሬ ነው፡፡ ለሀገር የሚያስብ ሰው ምን ጊዜም አስፈላጊ ነው፡፡ የሚያስብን ሰው የሚያከብር ትውልድ መኖር አለበት፡፡ ተኪው የተተኪው ዱካ በመልክ በመልኩ ለክቶ ይያዝ እንጂ በጭፍን አይከተል፡፡ “መንገኝነት ማንንም የትም አያደርስም” የሚባለው ለዚህ ነው፡፡

 “በፍተሻው ወቅት ወደ ቢሯቸው ፈጥነው ገብተው ሽጉጡን ለመሰወር ሞክረዋል”

     በአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት ነፋስ ስልክ ላፍቶ ክ/ከተማ፣ የሳሪስ ፈለገ ብርሃን ቅ/ሥላሴ ቤተ ክርስቲያን ደብር፣ ተመዝብሯል ስለተባለ ገንዘብ ለማጣራት፣ የሀገረ ስብከቱ ልኡካንና የሰበካ ጉባኤ አባላት ፍተሻ በሚያደርጉበት ወቅት፤ በደብሩ አስተዳዳሪ መልአከ ልዑል አማረ ታዬ የቢሮ ጠረጴዛ መሳቢያ ውስጥ ሕገ ወጥ ሽጉጥ መገኘቱ አነጋጋሪ ሆነ፡፡
የደብሩን አስተዳዳሪና የጽ/ቤቱን ሓላፊዎች፣ ከሰበካ ጉባኤ አባላት እና ከምእመናን ጋር ውዝግብ ውስጥ የከተታቸው ጉዳይ፤ በወር 105ሺ ብር ያህል ገንዘብ የሚያስገኙ የወፍጮ ቤትና የሱቅ ገቢዎች፣ ላለፉት ስድስት ወራት የደረሰበት ባለመታወቁ እንደሆነ የጠቆሙት ምንጮች፤ የደብሩ አስተዳዳሪ፣ ት/ቤት አሠራለሁ በማለት ላለፉት 3 ዓመታት ከምእመናን መጠኑ የማይታወቅ ገንዘብ ማሰባሰባቸውንና ገንዘቡ የት እንደደረሰ እንደማይታወቅ ይገልጻሉ፡፡
ለሕንፃ ቤተ ክርስቲያን ግንባታ በሚል ያለጥናት ቦታ መመረጡንና በቁፋሮ የወጣው ገረጋንቲ ድንጋይ፣ በአንድ በጎ አድራጊ ትብብር በነጻ ከስፍራው ቢነሣም፣ በክፍያ ነው ብለው በግል መጠቀማቸውን ምንጮቹ አክለው ያስረዳሉ፡፡ በእነዚህ ውዝግቦች የጀመረው አለመግባባት፣ የአካባቢው ወጣቶችና ምዕመናን፣ የደብሩን አስተዳዳሪ ቢሮ በኃይል በይደው እስከ ማሸግ አድርሷቸዋል፡፡ ከአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት የተላኩ የአጣሪ ኮሚቴ አባላትና የፀጥታ አካላት፣ ማክሰኞ ኅዳር 26 ቀን 2010 ዓ.ም. ከጠዋቱ 3 ሰዓት ገደማ፣ በታሸጉት የጽ/ቤቱ ቢሮዎች ላይ ፍተሻ ለማካሔድ በሚከፍቱበት ወቅት፣ ከደብሩ አስተዳዳሪ ቢሮ ጠረጴዛ መሳቢያ ውስጥ ሽጉጡ መገኘቱን ምንጮች አስታውቀዋል፡፡ አስተዳዳሪው ቢሯቸው በሚከፈትበት ወቅት፣ ፈጥነው ወደ ውስጥ በመዝለቅ፣ ከመሳቢያ ውስጥ ሽጉጡን አውጥተው ወደ መታጠቂያቸው ለመደበቅ ሲሞክሩ፣ በሰበካ ጉባኤው አባላት እጅ ከፍንጅ መያዛቸውንና ወደ ክፍለ ከተማው ፖሊስ ጣቢያም ተወስደው ምርመራ ሲካሔድ፣ መሣሪያው ሕገ ወጥ ኾኖ መገኘቱ ታውቋል፡፡ ተጠርጣሪው አስተዳዳሪ፣ በበነጋው ረቡዕ ኅዳር 27 ቀን በዋስትና ቢለቀቁም፣ ቀደም ብሎ በማኅበረ ምእመናኑ ማስጠንቀቂያ ወደ ደብሩ እንዳይገቡ ከሌሎች የጽ/ቤት ሓላፊዎች ጋር የተላለፈባቸው እገዳ፣ አሁንም ጸንቶ እንደሚገኝ ምንጮቹ ጠቁመዋል፡፡
ምእመናኑና የሰበካ ጉባኤ አባላቱም፣ አስተዳዳሪው፣ የሒሳብ ሹሙ፣ ተቆጣጣሪው፣ ገንዘብ ያዡና የስብከተ ወንጌል ሓላፊው በሕግ እንዲጠየቁላቸው፤ በምትካቸውም “ለሃይማኖቱ ቀናዒ የኾነና የተመሰከረ የሥነ ምግባር ግለ ማኅደር ያለው የሃይማኖት አባት” እንዲመደብላቸው ባለፈው ሰኞ ከሀገረ ስብከቱ ዋና ሥራ አስኪያጅ ጋር ባደረጉት ውይይት ጠይቀዋል፡፡ ዋና ሥራ አስኪያጁ መምህር ጎይቶም ያይኑ በበኩላቸው፣ ለምእመናኑ ጥያቄ በአፋጣኝ መፍትሔ እንደሚሰጡ ማረጋገጣቸው ታውቋል፡፡  

 “ለምን እቀናለሁ” እያልኩ አስባለሁ
ሰርክ እጨነቃለሁ
“ከሚሊዮን አትሌት ከህይወት ማራቶን
ሁሌም ከፊት ልሮጥ እንዴት እችላለሁ፡፡
እያልኩ አስባለሁ
ግን የሆነ ሆኖ…
ከፊት በሚሮጠው ዛሬም እቀናለሁ…
እኒህ የግጥም ስንኞች የተመዘዙት ሰሞኑን አንባቢያን እጅ ከደረሰው የገጣሚ ዳንኤል ሥዩም መንገሻ “ፍቅር እና ሽንቁር” የተሰኘ የግጥም መድበል ውስጥ “ቃየንን ፍለጋ” በሚል ርዕስ ከቀረበው ግጥም ነው፡፡ በ84 ገፆች የተቀነበበው መድበሉ፤ 46 ግጥሞችን ያካተተ ሲሆን በ40 ብር ለገበያ ቀርቧል፡፡

የሳዑዲ ዜግነት ያገኘቺዋ ሮቦት፣ ልጅ አማረን ብላለች

    በአለማችን የተለያዩ አገራት የሚገኙ 800 ሚሊዮን ያህል ሰራተኞች እ.ኤ.አ እስከ 2030 ባሉት በመጪዎቹ 13 አመታት ጊዜ ውስጥ  የስራ መደቦቻቸውን እነሱን ተክተው መስራት በሚችሉ ሮቦቶች ይነጠቃሉ ተብሎ እንደሚጠበቅ ቢቢሲ ዘግቧል፡፡
ማኬንዚ ግሎባል ኢንስቲቲዩት የተባለው አለማቀፍ አማካሪ ተቋም ሰሞኑን ይፋ ባደረገውና በ46 የአለማች አገራት ውስጥ በሚገኙ 800 ያህል የተለያዩ የስራ መስኮች ላይ ባካሄደው ጥናት እንዳለው፣ ሮቦቶች በተጠቀሰው ጊዜ ውስጥ በርካታ ስራዎችን ከሰዎች በመንጠቅ ተክተው የሚሰሩ ሲሆን ይህም ሃያ በመቶ የሚሆነውን የአለማችንን ሰራተኛ ሃይል ተጎጂ ያደርጋል ተብሎ ይጠበቃል፡፡
ጀርመንና አሜሪካን በመሳሰሉ ያደጉ አገራት ከሚገኙ ሰራተኞች መካከል ከ35 በመቶ በላይ የሚሆኑት አበክረው ሌላ ስራ ቢፈልጉ እንደሚሻላቸው የመከረው ተቋሙ፤የድሃ አገራት ዜጎችን በአንጻሩ እናንተን እንኳን አይመለከትም አትስጉ፤ ምክንያቱም መንግስቶቻችሁ ለሮቦት ማሰሪያ የሚሆን ገንዘብ የላቸውም ሲል አረጋግቷል።
ስራዎቻቸውን በሮቦቶች የመነጠቅ እድላቸው ከፍተኛ ከሆኑ ሰራተኞችና ባለሙያዎች መካከል አካውንታንቶችና የሪልእስቴት ደላላዎች እንደሚገኙበት የጠቆመው ዘገባው፤ ሰው መሆንን በሚሹና የበዛ ህያው መስተጋብርን በሚሹ የሙያ መስኮች ላይ የተሰማሩ ዶክተሮችንና መምህራንን የመሳሰሉት ግን በሮቦት የመፈናቀል እድላቸው አነስተኛ ነው መባሉን አመልክቷል፡፡
ከቴክኖሎጂ መስፋፋትና ከሮቦት ኢንዱስትሪ መጠናከር ጋር በተያያዘ የአገራት መንግስታት በርካታ የሙያ መስኮችን ከሰዎች ይልቅ በሮቦቶች ማሰራት አዋጪ መሆኑን በማመን የስራ መደቦችን ለሮቦቶች አሳልፈው የመስጠት እርምጃ ይወስዳሉ ተብሎ እንደሚጠበቅ የጠቆመው ተቋሙ፤ በተጠቀሰው ጊዜ ውስጥ በእንግሊዝ 20 በመቶ ስራዎች ለሮቦቶችና ለኮምፒውተራይዝድ አሰራር ተላልፈው ሊሰጡ እንደሚችሉ አመልክቷል፡፡
በተያያዘ ዜና፣ ባለፈው ወር የሳኡዲ ዜግነት በማግኘት በአለማችን ታሪክ በአንድ አገር ዜጋነት የተመዘገበች የመጀመሪያዋ ሮቦት የሆነቺው ሶፍያ፤ እንደ ሰው መቆጠሯ አነጋግሮ ሳያበቃ ልጅ መውለድና መሳም እፈልጋለሁ ማለቷን ሀንሰን ሮቦቲክስ የተባለው ኩባንያ ከሰሞኑ ይፋ አድርጓል፡፡
የሶፍያ ፈጣሪ የሆነው የሆንግ ኮንጉ ኩባንያ ሃንሰን ሮቦቲክስ፤ተመራማሪዎቹ አይኗን በአይኗ ለማየት ያማራትን ሶፍያን በመጪዎቹ ጥቂት አመታት ውስጥ አስረግዘው እንደሚያገላግሏት ያለውን ተስፋ ገልጧል፡፡

 ከአገሪቱ ዜጎች 75 በመቶው በአውሮፕላን ተጉዘው አያውቁም

    ባለፈው ሳምንት አርብ ብቻ በድምሩ 969 በረራዎችን ያስተናገደው የህንዱ ሙምባይ አለማቀፍ የአውሮፕላን ማረፊያ ጣቢያ በአንድ ቀን ውስጥ በርካታ በረራዎችን በማስተናገድ ክብረ ወሰን መያዙን ፎርቹን ዘግቧል፡፡
ሁለት የማኮብኮቢያ መስመሮች ቢኖሩትም በአንዴ በረራ ለማካሄድ አመቺ ባለመሆናቸው በአንዱ ብቻ የሚጠቀመው የሙምባይ አለማቀፍ የአውሮፕላን ማረፊያ ጣቢያ፣ በአንድ መስመር በአንድ ቀን ይህን ያህል በረራ በማስተናገድ ታሪክ መስራቱን የጠቆመው ዘገባው፤ ከዚህ በፊት በአንድ ቀን እስከ 900 የሚደርሱ በረራዎችን ያስተናግድ እንደነበር አስታውሷል፡፡ የሙምባይ አለማቀፍ የአውሮፕላን ማረፊያ ጣቢያ ከፍተኛ የስራ ሃላፊዎችን ጠቅሶ ዘገባው እንዳለው፣ በቀጣይም ዕለታዊ የበረራ መስተንግዶውን 1 ሺህ በማድረስ ክብረ ወሰኑን ለማሻሻል ዝግጅት እየተደረገ ይገኛል።
የህንድ አየር መንገዶች ባለፈው አመት ብቻ 100 ሺህ ያህል የአገር ውስጥ መንገደኞችን ማመላለሳቸውን የጠቆመው ዘገባው፤ ይህን ቁጥር በመጪው አመት 437 ለማድረስ እየተሰራ እንደሚገኝም አመልክቷል፡፡
ስፓይስጄት የተባለውን የአገሪቱ አየር መንገድ ጠቅሶ ዘገባው እንዳለው፣ ከአጠቃላዩ የአገሪቱ ህዝብ 75 በመቶ የሚሆኑት ወይም 1.3 ቢሊዮን ህንዳውያን፣ በህይወት ዘመን ቆይታቸው አንድም ጊዜ በአውሮፕላን ተሳፍረው አያውቁም፡፡

 የደቡብ ኮርያ መንግስት አነስተኛ ገቢ ያላቸውን የህብረተሰብ ክፍሎች የገንዘብ ጫና ለማቃለል በሚል 1.6 ሚሊዮን ለሚደርሱ ዜጎቹ የነበረባቸውን የገንዘብ ዕዳ በከፊል ለመሰረዝ ማቀዱን ቢቢሲ ከትናንት በስቲያ ዘግቧል፡፡
የአገሪቱ መንግስት የዕዳ ስረዛውን ተግባራዊ የሚያደርገው እስከ 9ሺህ 128 ዶላር ዕዳ ላለባቸውና የመክፈል አቅም ለሌላቸው ዜጎቹ መሆኑን የጠቆመው ዘገባው፤ ስረዛው የሚመለከታቸው ዜጎች ከመጪው የካቲት ወር ጀምሮ የዕዳ ስረዛ እንዲደረግላቸው ማመልከቻ እንዲያስገቡ ጥሪ ማቅረቡን አመልክቷል፡፡ ለዕዳ ስረዛው ማመልከት የሚችሉት ዜጎች ወርሃዊ ገቢያቸው ከ910 ዶላር በታች የሆነና ዕዳቸውን ለመክፈል ከአስር አመታት በላይ የተሰቃዩና ያልተሳካለቸው መሆናቸውን የሚያረጋግጥ መረጃ ማቅረብ የሚችሉ ብቻ እንደሆኑም ዘገባው ገልጧል፡፡
የአገሪቱ መንግስት “የደስታ እርዳታ” በሚል የሰየመውና ዕዳቸውን ለመክፈል ያልቻሉ ችግረኛ ደቡብ ኮርያውያንን አቅም የማጎልበት አላማ ያለው ፕሮግራሙ፤ ከዜጎች ያገኝ የነበረውን ገንዘብ ከሌሎች አበዳሪዎች አግኝቶ ለማካካስ ማቀዱንም ዘገባው አስረድቷል፡፡