Administrator

Administrator

አንዳንድ ዕውነተኛ ታሪክ ሲቆይ ተረት ይመስላል፡፡ የሚከተለውን እንደዚያው ነው።
ከዕለታት አንድ ቀን፤ አንድ፣ አገር ሳያውቀው የሞተ ሰዓሊ ነበረ፡፡ ይህ ሰዓሊ የአገሩን ባንዲራ በልዩ እሳቤ ያስጌጠ፣ ማንም ያልደረሰበት ረቂቅ ሰዓሊ ነበረ። ስለሰራው ሥራ ዋጋው አልተከፈለውም፡፡ ስለዚህም ወዳጆቹ፤ ያንን ባንዲራ “ያልተከፈለ ዕዳ” በሚል የቅፅል ስም ይጠሩታል፡፡
ይህ ሰዓሊ የተከራየው ግቢ ውስጥ አንድ ካቲካላ ‹አረቄ› የሚሸጥበት ቤት አለ፡፡ እዚህ ቤት የሚጠጡት ሰዎች ሁሉ ሰዓሊውን፤ ፀጉሩ የተንጨባረረና ነጠላ ጫማ (ሸበጥ) የሚያደርግ ስለሆነ ሰላይ ነው ብለው ይጠረጥሩታል፡፡ ስለሆነም እሱ ወደ ካቲካላው ቤት ሲገባ አፍ ሁሉ ይዘጋል፡፡ የተጀመረ ታሪክ ይቋረጣል፡፡ ሰው ሁሉ አፉ ላይ ማብሪያና ማጥፊያ የተገጠመለት ይመስል፣ በማጥፊያው ጠቅ አድርገው እንዳጠፉት ሁሉ አንዴ ጭጭ ይላል፡፡
አንድ ቀን ሰዓሊው ወደ ግቢው ሲመጣ፣ የግቢው ውሻ ይጮኽበታል፡፡ ይሄኔ ሰዓሊው ኮሮጆውን ከትከሻው ያወርድና አስፋቱ ላይ ያስቀምጣል፡፡ ከዚያም ከውሻው ፊት ለፊት ይንበረከካል፡፡ ቀጥሎም፤ “ው! ው! ው! ው!” አለ ውሻው ላይ ይጮህበታል። ውሻው ደንግጦ ዝም፤ ጭጭ ይላል፡፡ “ሁለተኛ ትጮህና እጮህብሃለሁ!” ይለዋል፡፡ ይሄንን ሲያደርግ ከሰዓሊው ጀርባ እየመጡ ያሉ ካቲካላ ጠጪዎች፣ ሁኔታውን ሁሉ ይከታተሉ ኖሯል፡፡ ቀድመው ወደ ካቲካላ ቤት ሄደው ሁኔታውን ሁሉ ለጠጪዎቹ ይናገራሉ፡፡ ሰዓሊው ቆይቶ ወደ አረቄው ቤት ሲመጣ፤
አንዱ፤ “ሁለት ስጡት!”
ሌላው፤ “ሶስት ጨምሩለት!”
ሌላው፤ “ሰው ማለት ይሄ ነው! እንጋብዘው እንጂ ጎበዝ!” እያለ ሰዓሊውን በግብዣ አንበሸበሹት፡፡
በሰላይነት መጠርጠሩ ቀርቶ እንደ ሰው ተጋበዘ! እንደ ሰው ተከበረ! ይህንን የተገነዘበው ሰዓሊ፤
“እዚህ አገር ሰው ለመሆን እንደ ውሻ መጮህ ያስፈልጋል!” አለ፡፡
የዚህን፤ የውሻን አፍ ያስዘጋ፤ የሰውን አፍ ያስከፈተ፣ ታላቅ ሰዓሊ ነብስ ይማር!!
*        *      *
ታላቅ ሰዎቻችንን እናክብር፡፡ ታላላቅ ሰዎቿን የቀበረች አገር ብዙ ያልተከፈለ ዕዳ ይኖርባታል፡፡ ዕዳው የትውልድ ነውና መጪውን ትውልድ ሳይቀር ባለዕዳ ታደርጋለች። የድንቁርና ዕዳ፣ ከዕዳ ሁሉ የከበደው ዕዳ ነው! የጤና ማጣት ዕዳ፣ ሁለተኛው ከባድ ዕዳ ነው! የዕብሪትና የማናለብኝ ዕዳ ቀጣዩ አባዜ ነው! ሁሉም ዋጋ እንደሚያስከፍለን በጭራሽ አንዘንጋ! ሁላችንም ባለሳምንት፣ የጠጣነውን ፅዋ በተራችን እንከፍላለን! ሌላው ብርቱ ችግራችን የመስባት ችግር ነው፡፡ (The fattening process እንዲሉ)
አንድ አዛውንት፤ “ስሙ አባታችን፤ እኛ እንደቀደሙት ገዢዎች ወፋፍራም አደለንም!” ቢሏቸው፤ “አዬ ልጄ፤ እነሱም ሲጀምሩ እንደናንተ ቀጫጭኖች ነበሩ!” አሉ፤ አሉ፡፡ የሀገራችን መሪዎች ችግር “አትፍረድ ይፈረድብሃል” የሚለውን መሪ ቃል መዘንጋት ነው! መጪዎች ከቀደሙት አይማሩም፡፡ የማይቀረውን ውድቀት እንደ ፅዋ መቀባበል አይቀሬ የሚሆነው ለዚህ ነው!
ጊዜያዊ የዘመቻ ሂደት ዘላቂ ለውጥን አያመጣም፡፡ የአፍታ - ለአፍታ የፕሮፓጋንዳ ቅስቀሳ ዘላቂ ዕውቀትን አያሰርፅም! ይልቁንም ህዝብን ማሳወቅ፣ ማስተማርና ማንቃት ፈር የያዘ ብቃትን ይፈጥራል! ትውልድ ዘላቂ ንቃትና ብቃት ሲኖረው፣ እርባና ያለው ለውጥ፣ ብሎም እርባና ያለው ዕድገት ያመጣል፡፡ የአልሸነፍም ባይነት ግትርነት፣ ጊዜያዊ ሥልጣንን ሊያቆይ ይችላል እንጂ የአገርና የህዝብን ዘላቂ ዕድገት አይፈጥርም! ነባር ግንኙነቶች ቀስ በቀስ መላላታቸው፣ ቀስ በቀስ መለወጣቸው ግድ ነው፡፡ አዳዲስ የሰው ኃይል መደባለቅ ለለውጥ መምጣት አንዱ ግብዓት ነው፡፡
አዳዲስ አስተሳስብ እንዲመነጭ የአዳዲስ ሰው ተሳትፎ ያስፈልጋል፡፡ አለበለዚያ ነገሩ ሁሉ ባለበት እርገጥ ይሆናል፡፡ ምንም ያህል ብንሮጥ መላና ብልሃት ከሌለበት የጭፍን ሩጫ ነው የሚሆነው፡፡ የጣልነውን ስለረገጥነው የእኛን ዕድገት ማረጋገጫ አይሆንም፡፡
እርጋታና አደብ መግዛት ወሳኝ ነው፡፡ መንገዶች በሙሉ ሊሾ አይሆኑም። ኮረኮንቹ እንዳይበዛ መታገሉ ሁነኛ አማራጭ ነው፡፡ “ጉልቻ ቢቀያየር ወጥ አያጣፍጥም” የሚለውን ተረት ሳንዘነጋ፣ ዛሬም ተለዋጭ ኃይል ማስፈለጉን እናስብ። ልዩነትን እናድንቅ፡፡ ሌጣ የሆነን አጓጓዝ እናስወግድ፡፡ የተለየ ሀሳብ አያስበርግገን። ጉዞአችን የጭፍን እንዳይሆን መሬት የያዘ ፍጥነት ይኑረን፡፡ ከሁሉም በላይ ደግሞ የሰከነ መላ እንዘይድ፡፡ ለዚህም “የዕውር የድንብሩን ከሚሮጥ ፈረስ መንገድ የምታውቅ አይጥ ትሻላለች” የሚለውን ተረት እንገንዘብ!!

ሰማያዊ ፓርቲ ባለፈው እሁድ በአምባሳደር ሲኒማ አዳራሽ “ኢትዮጵያን ማን ይታደጋት” በሚል ርዕስ ያካሄደውን ስብሰባ አንድ ቀን ቀደም ብሎ በወጣው የአዲስ አድማስ ጋዜጣ ላይ  መዘገባችን ይታወሳል፡፡ ፓርቲው  አንጋፋ ምሁራን፣ፖለቲከኞችና ታዋቂ ግለሰቦች በህዝባዊ ስብሰባው ላይ እንደሚገኙና በደብዳቤ ጥሪ እንደደረሳቸው የገለጸ ሲሆን ስማቸውንም በዝርዝር መጥቀሱ አይዘነጋም፡፡
እሁድ በሰማያዊ ፓርቲ ህዝባዊ ስብሰባ ላይ የተገኘው ሪፖርተራችን እንደታዘበው፣ ፓርቲው የገመተውን ያህል ታዳሚ አልተገኘለትም፡፡ ፓርቲው በመድረኩ እንደሚገኙ ከዘረዘራቸው ግለሰቦች መካከልም ጥቂቶች ብቻ መገኘታቸውን ለማረጋገጥ ተችሏል። አንጋፋው ፖለቲከኛ ዶ/ር ነጋሶ ጊዳዳ፣የስብሰባው ጥሪ እንደደረሳቸው ነገር ግን በግል ምክንያት ሊገኙ አለመቻላቸውን ለአዲስ አድማስ ተናግረዋል፡፡ አቶ ክቡር ገናም በተመሳሳይ ጥሪው ደርሷቸው፣ ከሃገር ውጪ በመሆናቸው መገኘት እንዳልቻሉ ገልጸዋል፡፡ አቶ ሞሼ ሰሙ ደግሞ ጥሪው አልደረሰኝም ብለዋል - ጥሪው ቢደርሳቸው ኖሮ ይገኙ እንደነበር በመግለጽ፡፡ ወ/ሮ ሰሎሜ ታደሰ በበኩላቸው፤ጥሪው እንዳልደረሳቸውና አዲስ አድማስም ጥሪው ባልደረሳቸው ሁኔታ ፎቶግራፋቸውን ጭምር በመጠቀም ባሰራጨው ዘገባ ቅሬታ እንደተሰማቸው ለዝግጅት ክፍሉ አስታውቀዋል፡፡
ሰማያዊ ፓርቲ በበኩሉ፤ባለፈው ሳምንት በስም ተጠቅሰው ለተዘረዘሩት ታዋቂ ምሁራንና ግለሰቦች በሙሉ የጥሪ ደብዳቤ መላኩን ጠቁሞ፣ በትክክል መድረስ አለመድረሱን ግን ለዚህ ሥራ ከተመደቡት ሰዎች ጋር እንደገና እንደሚነጋገርበት ለአዲስ አድማስ አስታውቋል፡፡


 ዌስተርን ዩኒቨርሲቲ ኮሌጅ አሜሪካን ሀገር ከሚገኘው የሊንከን ዩኒቨርሲቲ ጋር በመተባበር በቢዝነስ አድምኒስትሬሽን በሁለተኛና በመጀመሪያ ዲግሪ ያስተማራቸውን ተማሪዎች  ለሁለተኛ ጊዜ ያስመርቃል፡፡
ዌስተርን ዩኒቨርሲቲ ኮሌጅ፣ ይህን የትምህርት መርሃ ግብር በተለይ የንግድ ስራ አመራር ላይ አተኩሮ የሚሰጥ ሲሆን ለ7ኛ ጊዜ በMBA እና ለ2ኛ ጊዜ በBA ፕሮግራም ያስተማራቸውን ተማሪዎች ነው ነገ በአፍሪካ ኢኮኖሚ ኮሚሽን የስብሰባ ማዕከል የሚያስመርቀው፡፡
በምርቃት ስነ ስርአቱ ላይም የፐብሊክ ፋይናንስ ኢንተርፕራይዝ ኤጀንሲ ዳይሬክተር ጀነራል ዶ/ር ስንታየሁ ወ/ሚካኤል፣ የሊንከን ዩኒቨርሰቲ ካሊፎርኒያ ፕሮፌሰርና የዩኒቨርሲቲው የባላደራ ቦርድ ሊቀ መንበር ዶ/ር አላን ሳምሶን እና የአሜሪካ ኤምባሲ ተወካይ እንዲሁም ጥሪ የተደረገላቸው የመንግስት ባለስልጣናት ይገኛሉ ተብሏል፡፡


        “የአለማችን ቁጥር አንድ ፉንጋ ተብዬ፣ የአገሬን ስም አስጠራለሁ!” ብሏል

   ባለማማር ውስጥ ያለውን ውበት የማሳየት ዓላማ ይዞ በዚምባቡዌ በየአመቱ በሚካሄደው የ“አቶ መልከ-ጥፉ - ዚምባቡዌ” የቁንጅና ውድድር ለሁለት ጊዜያት አሸናፊ የነበረው ሚሊያም ማስቪኑ የተባለው የአገሪቱ ዜጋ፤ዘንድሮም ክብሩን በማስጠበቅ ሃትሪክ መስራቱንና የፉንጋነቱን ዘውድ መድፋቱን ኦል አፍሪካ ዶት ኮም ዘግቧል፡፡
በመዲናዋ ሃራሬ ባለፈው እሁድ ምሽት ለአምስተኛ ጊዜ በተከናወነው የ2017 “አቶ መልከ-ጥፉ” የቁንጅና ውድድር ላይ በዕጩነት ከቀረቡ አራት ተወዳዳሪዎች መካከል አንደኛ በመውጣት ብሄራዊውን የፉንጋነት ዘውድ የደፋው ማስቪኑ፤ ከውድድሩ አዘጋጅ ድርጅት የ500 ዶላር እና የአንዲት ላም ሽልማት ተበርክቶለታል፡፡
“በመላው ዚምባቡዌ ከእኔ ጋር የሚስተካከል አስጠሊታ ሰው እንደሌለ ሳይታለም የተፈታ ነው!... በቀጣይ ይህንን ፉንጋ መልኬን ይዤ አገሬን በአለም መድረክ ላይ በኩራት ለማቆምና ስሟን ለማስጠራት የቻልኩትን ሁሉ አደርጋለሁ፡፡ እርግጠኛ ነኝ፤ የ2018 የአለማችን ፉንጋ ክብርን በመጎናጸፍ፣ የአገሬን ስም በአለም አደባባይ አስጠራለሁ!” ብሏል ማስቪኑ፤ በሽልማት ስነስርዓቱ ላይ ባደረገው ንግግር፡፡
የ2018 የአለማችን “አቶ መልከ-ጥፉ” የቁንጅና ውድድር በደቡብ አፍሪካ እንደሚካሄድ የጠቆመው ዘገባው፤ በብሄራዊ ደረጃ አሸናፊ የሆኑ የተለያዩ አገራት መልከ-ጥፉዎች፣ አገራቸውን ወክለው እንደሚወዳደሩና ከፍተኛ ፉክክር ይታይበታል ተብሎ እንደሚጠበቅም ዘገባው አክሎ ገልጧል፡፡

ትውልደ ኢትዮጵያዊው አቤል ተስፋዬ፤ በ92 ሚ. ዶላር 4ኛ ደረጃን ይዟል

    በአለማችን የሙዚቃ ኢንዱስትሪ ከፍተኛ አመታዊ ገቢ ያገኙ ድምጻውያንን ደረጃ የሚያወጣው ታዋቂው ፎርብስ መጽሄት፣ ከሰሞኑም የ2017 የፈረንጆች አመት ከፍተኛ ተከፋይ የአለማችን ድምጻውያንን ዝርዝር ይፋ ያደረገ ሲሆን ፒዲዲ በ130 ሚሊዮን ዶላር ገቢ በአንደኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል፡፡
ፒዲዲ ባለፉት 12 ወራት ብቻ በድምሩ 130 ሚሊዮን ዶላር ገቢ ማግኘቱን የጠቆመው ፎርብስ፤ ከፍተኛ ገቢ ካስገኙለት መካከልም ሲሮክ ቮድካ ከተባለው ኩባንያ ጋር የገባው የንግድ ስምምነት፣ የኩባንያዎቹን ከፊል ድርሻ መሸጡና ባድቦይ ሪዩኒየን በሚል ርዕስ ያደረገው የሙዚቃ ኮንሰርት ጉዞው እንደሚጠቀሱ ገልጧል፡፡
አሜሪካዊቷ ድምጻዊት ቢዮንሴ ኖውልስ 105 ሚሊዮን ዶላር በማግኘት በአመቱ ሁለተኛውን ከፍተኛ ገቢ ያገኘች የአለማችን ድምጻዊት ስትባል፣ ድሬክ በ94 ሚሊዮን ዶላር ሶስተኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል፡፡
በቅጽል ስሙ ዘ ዊክንድ ተብሎ የሚጠራው ትውልደ ኢትዮጵያዊው የግራሚ ተሸላሚ አቤል ተስፋዬ፣ በ92 ሚሊዮን ዶላር አራተኛ ደረጃን መያዙን የጠቆመው የፎርብስ መግለጫ፤ የእንግሊዙ የሙዚቃ ቡድን ኮልድፕሌይ በበኩሉ፣ በ88 ሚሊዮን ዶላር አመታዊ ገቢ አምስተኛ ደረጃን መያዙን አመልክቷል፡፡
83.5 ሚሊዮን ዶላር ገቢ በማግኘት በደረጃ ሰንጠረዡ ሰባተኛ ደረጃ ላይ የተቀመጠው የ23 አመቱ ራፐር ጀስቲን ቢበር፤ ከአመቱ የፎርብስ የአለማችን ከፍተኛ ተከፋይ ድምጻውያን መካከል በእድሜ ትንሹ ነው ተብሏል፡፡

በህገወጥ መንገድ በሚመረቱ፣ ጥራት በሌላቸውና ኦሪጅናል ባልሆኑ የአይፎን ቻርጀሮችና በሌሎች ቻርጀሮች የአይፎን የሞባይል ስልኮችን ቻርጅ ማድረግ የእሳት አደጋን፣ በኤሌክትሪክ የመያዝና ከፍተኛ የመቁሰል አደጋን የማስከተል እድላቸው እጅግ ከፍተኛ መሆኑን ዘ ቴሌግራፍ ዘግቧል፡፡
መሰል ቻርጀሮች ምንም እንኳን በአነስተኛ ዋጋ ቢገዙም ለአደጋ የማጋለጥ እድላቸው እጅግ ከፍተኛ መሆኑን በእንግሊዝ አገር በሰራሁት የደህንነት ፍተሻ ጥናት ደርሼበታለሁ ያለው ኤሌክትሪካል ሴፍቲ ፈርስት የተባለ የአገሪቱ ተቋም፤ ጥናት ካደረግኩባቸው ቻርጀሮች መካከል 98 በመቶው እጅግ አደገኛ እንደሆኑ አረጋግጫለሁ ብሏል፡፡
ጥናት ከተደረገባቸው አይፎንን ቻርጅ ማድረግ የሚችሉ ሌሎች 50 አይነት ቻርጀሮች ውስጥ ከአንዱ በስተቀር ሌሎቹ የተለያዩ አይነት የደህንነት መስፈርቶችን ያላሟሉ ሆነው መገኘታቸውንም ተቋሙ አስታውቋል፡፡ አይፎንን ቻርጅ በሚያደርጉ ሌሎች 400 አይነት ቻርጀሮች ላይ በአሜሪካ ባለፈው አመት በተሰራ ሌላ ተመሳሳይ ጥናት፣ ቻርጀሮቹ የመበላሸትና አደጋ የማስከተል እድላቸው 99 በመቶ ያህል መሆኑ መረጋገጡንም ዘገባው አስታውሷል፡፡

 ለአመታት ተባብሶ በቀጠለው የዲሞክራቲክ ሪፐብሊክ ኮንጎ የእርስ በእርስ ግጭት ሳቢያ፣ እየተገባደደ ባለው የፈረንጆች አመት 2017 ብቻ 1.7 ሚሊዮን ያህል የአገሪቱ ዜጎች፣ከመኖሪያ ቦታቸው መፈናቀላቸውንና ወደ ሌሎች አገራት መሰደዳቸውን ቢቢሲ ዘግቧል፡፡
በአገሪቱ ለአመታት የዘለቀው የእርስ በእርስ ግጭትና ጦርነት ዜጎችን ለከፋ የሰብዓዊ ቀውስ መዳረጉን ቀጥሏል ያለው ዘገባው፤ ባለፈው አመት መከናወን የነበረበት ምርጫ በታቀደለት ጊዜ አለመካሄዱ የእርስ በእርስ ግጭቱን ወደከፋ ሁኔታ እንዳሸጋገረውና ግጭቱን በመሸሽ ከመኖሪያ ቦታቸው የሚፈናቀሉና ወደተለያዩ አገራት የሚሰደዱ ዜጎች ቁጥር እየጨመረ መምጣቱን አመልክቷል፡፡ ኢንተርናል ዲስፕለስመንት ሞኒተሪንግ ሴንተር የተባለው ተቋም ባወጣው አዲስ ሪፖርት፤ በዘንድሮው አመት ብቻ በየዕለቱ በአማካይ 5 ሺህ 500 የዲሞክራቲክ ሪፐብሊክ ኮንጎ ዜጎች ከመኖሪያ ቤታቸው መፈናቀላቸውን አስታውቋል ያለው ዘገባው፤ የመፈናቀሉ መጠን በአለማቀፍ ደረጃ የከፋውና ብዙዎችን ተጠቂ ያደረገ ነው ማለቱን ገልጧል፡፡
በአገሪቱ ከመኖሪያ ቦታቸው የተፈናቀሉ ዜጎች ቁጥር በድምሩ አራት ሚሊዮን ያህል መድረሱንና ከሰባት ሚሊዮን በላይ ዜጎችም የምግብ እጥረት ተጎጂ መሆናቸውን የጠቆመው ዘገባው፤ ሰብዓዊ ቀውሱን ለመግታት የሚደረገው አለማቀፍ ድጋፍ ግን እጅግ አናሳ ነው መባሉን አመልክቷል፡፡
በተያያዘ ዜናም፣ ካሳኢ በተባለው የአገሪቱ አካባቢ ተባብሶ በቀጠለው የእርስ በእርስ ግጭት ሳቢያ ግማሽ ሚሊዮን ያህል የአገሪቱ ዜጎች ለምግብ እጥረት መዳረጋቸውንና ተገቢ እርዳታ አለማግኘታቸውን የአለም የምግብ ፕሮግራም ባለፈው ረቡዕ ባወጣው መግለጫ አስታውቋል፡፡

 የአሜሪካው ፕሬዚዳንት ዶናልድ ትራምፕ ባለፈው ረቡዕ “እየሩሳሌም የእስራኤል ዋና ከተማ መሆኗን እውቅና ሰጥቻለሁ፤ በእስራኤል የሚገኘውን የአሜሪካ ኤምባሲም ከቴል አቪቭ ወደ እየሩሳሌም አዘዋውራለሁ” ማለታቸውን ተከትሎ፣ መካከለኛው ምስራቅን ጨምሮ ከመላው አለም እጅግ ከፍተኛ ውግዘት እየገጠማቸው ይገኛል፡፡
የእየሩሳሌም ጉዳይ በሁለቱ ወገኖች መግባባትና ድርድር ይፈታ የሚለውንና አሜሪካ ለአስርት አመታት ስታራምደው የቆየቺውን አቋም፣ ጊዜው ያለፈበትና የማያዋጣ ብሎ በድንገት በናደውና አለምን ባነጋገረው የትራምፕ ንግግር ክፉኛ የተቆጡ ፍልስጤማውያን ተቃውሟቸውን ያሰሙ ሲሆን ጉዳዩን የሚያወግዙ መንግስታት ቁጥርም እያደገ ነው፡፡
የፍልስጤሙ ፕሬዚዳንት መሃሙድ አባስ፤”አሜሪካ ከአሁን በኋላ በእስራኤልና በፍልስጤም መካከል የአደራዳሪነትና የሸምጋይነት ቦታ የላትም” ያሉ ሲሆን፣ ይህ አደገኛ ውሳኔ በሁለቱ አገራት መካከል ያለውን የሰላም መንገድ እንዲሁም የአካባቢውን ብሎም የመላውን አለም ሰላምና መረጋጋት አደጋ ላይ የሚጥል ነው ሲሉ የትራምፕን ንግግር ነቅፈዋል፡፡
የእስራኤሉ ጠቅላይ ሚኒስትር ቤኒያሚን ናታኒያሁ በበኩላቸው፤ “ለዚህ ታሪካዊ ውሳኔዎት እጅግ አመሰግንዎታለሁ፤ አይሁዳውያንና የአይሁዳውያን አገር ሁሌም ሲያመሰግኑዎት ይኖራሉ” በማለት ትራምፕን ማመስገናቸውን ሲኤንቢሲ ዘግቧል፡፡
የሃማሱ መሪ ኢስማኤል ሃኒ በበኩላቸው፤ ከጋዛ ሰርጥ ባስተላለፈው መልዕክት፣ “ትራምፕ በፍልስጤማውያን ላይ ጦርነት አውጇልና፣ ሴት ወንድ ህጻን አዛውንት ሳትሉ ታጥቃችሁ ተነሱ፤ ከእስራኤል ጋር ለምንፋለምበት አዲሱ ኢንቲፋዳ ተዘጋጁ” ሲሉ ለፍልስጤማውያን በይፋ የክተት አዋጅ ጥሪውን አስተላልፈዋል፡፡ ይህን ተከትሎም፣ በርካታ ፍልስጤማውያን ከትናንት በስቲያ መደበኛ እንቅስቃሴያቸውን አቋርጠው፣ ወደ ጋዛ ጎዳናዎች በመጉረፍ፣ በቁጣ እየነደዱ የትራምፕን ፎቶግራፍና የአሜሪካን ባንዲራ አቃጥለዋል፡፡
“ሰውዬው መካከለኛው ምስራቅ ላይ የማይጠፋ እሳት ለኮሰ!” ሲሉ የትራምፕን ንግግር አደገኛነት የገለጹት የቱርኩ ፕሬዚዳንት ጠይብ ኤርዶጋን ሲሆኑ፣ የግብጹ አቻቸው አብዱል ፋታህ አልሲሲ በበኩላቸው፤ የትራምፕ አካሄድ የሰላም ዕድሎችን የሚዘጋ ነው ሲሉ ተደምጠዋል፡፡
ኢራን፣ ሊባኖስና ኳታር የትራምፕን ውሳኔ በአደባባይ የነቀፉ ሲሆን ወገንተኝነቷ ለአሜሪካ ነው የምትባለው ሳዑዲ አረቢያ ሳትቀር፣ የትራምፕን ውሳኔ ተገቢነት የሌለውና ሃላፊነት ከማይሰማው ሰው የሚጠበቅ ስትል ነቅፋዋለች፡፡ የአሜሪካ ወዳጅ የምትባለው ዮርዳኖስም በተመሳሳይ ሁኔታ የትራምፕን ንግግር በአደባባይ አውግዛለች፡፡
የተባበሩት መንግስታት ድርጅት የትራምፕ ውሳኔ ለእስራኤላውያንና ለፍልስጤማውያን የማይበጅ፣ የሰላም ጥረትን የሚያጨናግፍ አደገኛ አካሄድ ነው ማለታቸውን የዘገበው ቢቢሲ፤ እንግሊዝ፣ ጣሊያንና ፈረንሳይን ጨምሮ ስምንት የተመድ የጸጥታው ምክር ቤት አባል አገራት ያቀረቡትን ጥያቄ መሰረት በማድረግ፣ ምክር ቤቱ በጉዳዩ ዙሪያ ለመምከር ትናንት ቀጠሮ መያዙንም አመልክቷል፡፡
የአውሮፓ ህብረት ትርጉም ያለው የሰላም ሂደት እንደገና እንዲቀጥል ጥሪ ያቀረበ ሲሆን የእንግሊዝ መንግስት የትራምፕን ውሳኔ “የማያተርፍ” ሲል በይፋ ነቅፎታል፤ ስዊድን፣ ፈረንሳይና ጀርመንም “ጉዳዩ በሁለቱ አገራት የጋራ ስምምነት እልባት ማግኘት ሲገባው ትራምፕ ጣልቃ ገብተው አደገኛ ነገር መናገራቸውን አልወደድነውም” የሚል ተመሳሳይ አቋም አንጸባርቀዋል፡፡
አለም በአንድ ድምጽ ውግዘቱን የሚያወርድባቸው ትራምፕ ግን፣ “ጉዳዩ የምታጋንኑትን ያህል አይደለም፤ ለእውነታ እውቅና መስጠት ነው” ሲሉ ምላሻቸውን ሰጥተዋል፡፡
በመካከለኛው ምስራቅ እና በአንዳንድ የአፍሪካ አገራት የሚገኙ የአሜሪካ ኢምባሲዎች በበኩላቸው፤ ሊቀሰቀሱ ከሚችሉ ተቃውሞዎች፣ አመጾችና ብጥብጦች ራሳችሁን ጠብቁ ሲሉ ዜጎቻቸውን አስጠንቅቀዋል፡፡
አደገኛ ጥፋትን የሚያስከትል አጉል ውሳኔ ሲል የትራምፕን አካሄድ ያወገዘው የአረብ ሊግ አባል አገራት፤ ዛሬ በቱርክ ተሰብስበው በጉዳዩ ዙሪያ ለመምከር ቀጠሮ መያዛቸውንም ቢቢሲ ዘግቧል፡፡

ተወልደው ያደጉት በባህርዳር ዙሪያ ጣና አካባቢ ነው፡፡ ቤተሰቦቻቸው ዓሳ አስጋሪዎች ነበሩ፡፡ ከልጅነታቸው አንስተው ዓሳ እያሰገሩ ነው ያደጉት፡፡ የዓሳ ኮርፖሬሽን የሚባለው የመንግስት ድርጅት ተቋቁሞ፣በግል ዓሳ ማስገር ሲከለከል የሥራ ዘርፋቸውን ቀየሩ፡፡ የተለያዩ ሸቀጣ ሸቀጦችን እየገዙ በበቅሎ መሸጥ እንደጀመሩ ይናገራሉ - የዛሬው ኢንቨስተር አቶ ካሣሁን ምስጋናው፡፡ በ1982 ዓ.ም በራሳቸው ስም ንግድ የጀመሩት ባለሃብቱ፤ከመንግስት ለውጥ በኋላ በፀደቀው የንግድ ህግ መሰረት ድርጅታቸውን ቢአኤካ ጀነራል ቢዝነስ ፒኤልሲ ብለው በማቋቋም በከፊል ተቋራጭነትና በማሽነሪ ኪራይ ሥራ የጀመሩ ሲሆን ዛሬ የ5 ቢሊዮን ብር ኢንቨስትመንት ባለቤትና የ5 ሺህ ሰራተኞች ቀጣሪ ለመሆን በቅተዋል፡፡
         ባለሀብቱ በቅርቡ በባህርዳር 360 ሚ. ብር የፈጁ የእብነበረድና የቀለም ፋብሪካዎችን ገንብተው አስመርቀዋል፡፡ በቅርቡ ሥራ የሚጀምር የዘይት ፋብሪካም እየተከሉ ነው፡፡ የአዲስ አድማስ ጋዜጠኛ ናፍቆት ዮሴፍ፤ ባለሀብቱ ከዓሳ ማስገር ተነስተው አሁን እስከደረሱበት ስኬት ያለውን ጉዞ ከባለሃብቱ ጋር ባደረገችው ቃለ ምልልስ ታስቃኘናለች፡፡ የወደፊት ዕቅዳቸውንና ህልማቸውንም አውግተዋታል፡፡ የአቶ ካሣሁን ምስጋናውን አስደማሚ የንግድ ሥራ ግስጋሴ ከአንደበታቸው እነሆ፡-


    ቢአኤካ ጀነራል ቢዝነስ እንዴት ነው የተመሰረተው?
ስለ ቢአኤካ ከመናገሬ በፊት በግል ስሜ ነበር የንግድ ስራዬን የጀመርኩት፡፡ እስከ 1982 ዓ.ም በግል ስሜ ስሰራ ከቆየሁ በኋላ በአገራችን በተፈጠረው የኢኮኖሚ እንቅስቃሴና ለውጥ ፒኤልሲ የሚባል ነገር ሲመጣ፣ ቢአኤካ ጀነራል ቢዝነስ በሚል አቋቁመን መስራት ጀመርን ማለት ነው፡፡ ቢአኤካ ጀነራል ቢዝነስ  ቀደም ብለው የነበሩትን የእኔን ልምዶችና ሀብት ይዞ ነው የተመሰረተው፡፡
ቢአኤካ ሲመሰረት መጀመሪያ ምን ነበር የሚሰራው?
መጀመሪያ የተነሳነው በኮንስትራክሽን ሥራ ነበር፡፡ ስራ የጀመርነው ከፊል ተቋራጭ በመሆንና የኮንስትራክሽን ማሽነሪዎች በማከራየት ነው፡፡ ከዚያ በኋላ ደግሞ ወደ ግብርና ገባን፡፡ ግብርናው በቡና እርሻ ላይ ያተኮረ ነው፡፡ ዛሬ ቢአኤካ ጀነራል ቢዝነስ፣ 2700 ሄክታር መሬት ላይ ቡና ያለማል፡፡ ሰፊ የቡና እርሻ ያለው ድርጅት ነው፡፡
በአስመጪና ላኪነት ላይም መሰማራታችሁን ሰምቻለሁ---
እውነት ነው፡፡ እንግዲህ ሰፊ የቡና እርሻ ባለቤት እንደመሆናችን፣ ቡና በአብዛኛው ወደ ውጭ የሚላክ በመሆኑ የራሳችንን ቡና በጥራት እሴት ጨምረን ለመላክ በኤክስፖርቱ ዘርፍ ተሰማራን፡፡ ቡናው ለመላክ እስኪደርስ በሰሊጥና በአጠቃላይ በጥራጥሬና በቅባት እህሎች የላኪነት ስራውን ስንሰራ ቆየን፡፡ ድርጅታችን በቅባት እህሎችና ጥራጥሬ ይዞት የቆየውን ልምድ በመንተራስ፣ ከራሱ እርሻ “ስፔሻሊቲ ቡና” የሚባል የቡና ምርት ለውጭ ገበያ መላክ ጀመረ፡፡
የቡና እርሻችሁ የት ነው የሚገኘው?
የቡና እርሻው በማጂንግ ዞን ጎደሬ የተባለ ወረዳ ውስጥ ይገኛል፤
የምትልኩት “ስፔሻሊቲ ቡና” ከሌላው የቡና ምርት ልዩነቱ ምንድን ነው?
ቡናው በጣም ኦርጋኒክ ነው፤ ከየትኛውም ንክኪ ነፃ የሆነና ደረጃውን የጠበቀ ቡና ሲሆን ለዚህም የተሰጠን ሰርተፍኬት አለ፡፡ አሁን በቅርቡ መንግስት ባሻሻለው የቡናና ሻይ አዋጅ፤ “አውት ግሮስ” የተባለ የአካባቢውን ቡና እርሻ ያላቸው ኢንቨስተሮች፣ ጥራቱን በጠበቀ መልኩ ይላኩ በሚለው መሰረት፤ እኛም የአካባቢውን ቡና እየገዛን፣ ከራሳችን ቡና ጋር እያደረግን ደረጃውን የጠበቀ “ስፔሻሊቲ ቡና” በተለይም ለአውሮፓ ገበያ እንልካለን፡፡ ድርጅታችን ኤክስፖርቱን በማስፋፋት ለውጭ ገበያ የሚቀርቡ ምርቶችን ወደ ማምረት የማኑፋክቸሪንግ ኢንዱስትሪ ገብቷል፡፡ በቅርቡ ሥራ የጀመረው “ኮከብ የእብነበረድ ፋብሪካ” ለዚህ ተጠቃሽ ነው፡፡ ፋብሪካው ለጊዜው የእብነበረድ ምርቱን ለአገር ውስጥ ገበያ ያቅርብ እንጂ በሁለት መልኩ ለውጭ ገበያ ያቀርባል፡፡
በሁለት አይነት ሲባል ምን ማለት ነው?
አንደኛው ቀጥታ ከቦታው የእብነብረድ ቋጥኝ ቆርጦ እንዳለ መላክ ነው፡፡ ሁለተኛው በደንብ ሰርቶና እሴት ጨምሮ ያለቀለት ምርት መላክ ነው። እንግዲህ ይህ ፋብሪካ ከ”ኮከብ ቀለም ፋብሪካ” ጋር በአንድ ላይ በ18ሺህ ካሬ ሜትር ላይ አርፎ፣ በባህርዳር ተገንብቷል፡፡ የእብነበረድና የቀለሙ ፋብሪካ በአጠቃላይ 360 ሚ. ብር ነው የወጣበት። የቀለም ፋብሪካው የተቋቋመበት ዋና አላማ የእብነበረዱን ተረፈ ምርት እየተጠቀመ፣ ጥራት ያለው የኳርትዝና የውሃ ቀለም ለማምረት ታስቦ ነው፡፡ ስለዚህ በተረፈ ምርትነት የሚጣል ነገር አይኖረውም፡፡ ፋብሪካዎቹ በሙሉ ሀይላቸው ስራ ሲጀምሩ ለ500 ሰዎች የስራ እድል ይፈጥራሉ። ሌላው እንግዲህ ምርቱ ወደ ውጭ ገበያ ሲቀርብ ትልቅ የውጭ ምንዛሪን ያመጣል፡፡ ጥቅማቸው ዘርፈ ብዙ ነው፡፡
የእብነበረዱ ጥሬ እቃ ምንጩ ከየት ነው?
ማዕድኑ የሚወጣው ማንኩሽ ከተባለ ቦታ ነው፡፡ እዛው ቦታ ላይ “ዳይመንድ ዋየር” የተባለ የእብነበረድ ፕሮስስ ማድረጊያ ፋብሪካም ተክለናል። ይህ ፋብሪካ የእብነበረዱ ማዕድን እንደወጣ እዛው እየቆረጠና እያስተካከለ ኤክስፖርት ለማድረግ ያግዛል፡፡ የቀለም ፋብሪካውንም ብንወስድ በዓመት 25 ሚ. ሊትር በላይ የማምረት አቅም ያለው ነው፡፡ ከአገር ውስጥ ገበያ ተርፎ ለጎረቤት አገራት ምርቱን ኤክስፖርት የማድረግ እቅድ ይዞ ነው እንቅስቃሴውን የጀመረው፡፡ ለዚህም ነው ከአገራችን አቅም በላይ የሆኑ የአውሮፓ ማሽኖችን መርጠን አምጥተን የተከልነው፡፡ ማሽኖቹ የጣሊያን የዴንማርክና የቤልጂየም ስሪት ናቸው፡፡ እነዚህ ማሽነሪዎች ኤክስፖርት የሚደረጉ ምርቶችን ለማምረት የሚረዱ ናቸው፡፡ በአሁኑ ሰዓት ሁለት ፋብሪካዎች በከፊል ስራ ጀምረዋል፡፡ እስካሁን በአንድ ሺፍት ነው የሚሰሩት፤ከ200 በላይ ሰራተኞች ሥራ ላይ ተሰማርተዋል፡፡
ቢአኤካ ጀነራል ቢዝነስ በአሁኑ ወቅት ጠቅላላ ኢንቨስትመንቱ ምን ያህል ነው? በአጠቃላይ ምን ያህል ሰራተኞች አሉት?
የድርጅቱ ጠቅላላ ኢንቨስትመንት ወደ 5 ቢ. ብር ነው፤ በስሩ ከ5 ሺህ በላይ ሰራተኞችን ይዟል። እንግዲህ በቀጣይ የሚከፈቱ ፋብሪካዎች አሉ፡፡ ከ5ሺህ ሰራተኞች ውስጥ ግማሽ ያህሉ በእርሻውና በኮንስትራክሽኑ ዘርፍ ላይ እየሰሩ ይገኛል፡፡
የኮንስትራክሽኑ ዘርፍ ምን ምን ስራዎችን ያከናውናል?
ኮንስትራክሽኑ በአገራችን የሚሰሩ ትልልቅ መንገዶችን፣ የባቡር መንገዶችንና እንደ ሳሊኒ ባሉ ትልልቅ ዓለማቀፍ ኩባንያዎች የሚገነቡ ፓወር ሀውሶችን “Earth work” ወይም የአፈር ስራዎችን በከፊል ቢአኤካ ነው የሚሰራው፡፡
የእብነበረድ ፋብሪካው የማምረት አቅሙ ምን ያህል ነው?
በዓመት 500 ሺህ ሜትር ካሬ ያለቀለት እብነበረድ ያመርታል፡፡ ይሄ በዳይመንድ ዋየር እየተቆረጠ እንዲሁ የሚላከውን ያላለቀለት እብነበረድ አይመለከትም፡፡ በዚህም በዓመት እስከ 5 ሚ. ዶላር የውጭ ምንዛሬ ለማግኘት እንደ ጅምር እቅድ የያዝን ሲሆን በሙሉ ሀይላችን ወደ ስራ ስንገባና የውጭ ገበያን ስናስፋፋ ገቢውን ወደ 10 ሚሊዮን ዶላር ለማድረስ አቅደን እየሰራን ነው፡፡ ይሄ ለአገርም ኢኮኖሚ የሚያበረክተው አስተዋፅኦ ቀላል አይደለም፡፡
ቢአኤካ እያስገነባቸው ያሉና በቀጣይ የሚገነቡ ፋብሪካዎችም እንዳሉ ይነገራል፡፡ እስቲ ስለዚህ ጉዳይ ያብራሩልን?
እንግዲህ ድርጅታችን ትኩረቱን ወደ ማኑፋክቸሪንግ ዘርፍ አድርጓል፡፡ በቅርቡ የሚጠናቀቅና በአዲስ አበባ ዙሪያ ታጠቅ ኢንዱስትሪ መንደር እየተገነባ ያለ ትልቅ የዘይት ፋብሪካ አለን፡፡ ፋብሪካው 200 ሚ. ብር ነው የወጣበት፡፡ ዋና መጭመቂያ ማሽኑ የመጣው ከአሜሪካ ሲሆን መፍጫው ከቻይና፣ ማጣሪያው ከህንድ ነው የመጣው፡፡ በአሁኑ ሰዓት የውጭ አገር ባለሙያዎች መጥተው፣ የማሽን ተከላ ስራ እያካሄዱ ሲሆን ከአንድ ወር በኋላ ወደ ስራ ይገባል፡፡ ፋብሪካው በዓመት 10 ሚሊዮን ሊትር የሱፍ የኑግ፣ የሰሊጥ፣ የአኩሪ አተርና የተልባ ዘይት የማምረት አቅም ያለው ነው፡፡ ከፋብሪካው ብዙ ጠቃሚ አላማዎች መካከል አንዱ ደህንነቱ የተጠበቀ ዘይት ለአገራችን ህዝብ ማቅረብ ነው፡፡ ሁለተኛ ከውጭ የምናስመጣውን የፓልም ዘይት በማስቀረት የውጭ ምንዛሪን ማዳን ነው፡፡ በሌላ በኩል ለ200 ሰዎችም የስራ እድል የሚፈጥር ነው። እኛ ሰሊጥ ኑግ፣ አኩሪ አተር፣ ተልባና ሱፍ ወደ ውጭ እየላክን የፓልም ዘይት እናስገባለን፡፡ ያለንን ምርት እዚሁ ጤናማ ዘይት ለምን አናመርትበትም በሚል ታስቦ ነው የተቋቋመው፡፡ ከስድስት ወር በኋላ ወደ ተከላ የሚመጡ ሌሎች ፋብሪካዎችም አሉን፡፡ እነዚህ ፋብሪካዎች የግራናይትና የቴራዞ ፋብሪካዎች ናቸው፡፡ እነዚህ ሁለት ፋብሪካዎች ልክ እንደ እብነበረዱና እንደ ቀለሙ ፋብሪካ ተመጋጋቢ ናቸው፡፡ የግራናይት ፋብሪካ ተረፈ ምርት ለቴራዞ ፋብሪካው ዋና ግብአት የሚሆን ነው፡፡ የማርብልና ግራናይት ፍቅፋቂ በመፍጨትና መልሶ በመጋገር ደረጃውን የጠበቀ ቴራዞ መስራት ይቻላል፡፡ እነዚህ ፋብሪካዎች በባህርዳር ነው የሚገነቡት፡፡ የሁለት ዓመት ዕቅድ የተያዘላቸው የሴራሚክስና የጥቅል መስታወት ፋብሪካዎችም ጠቅላላ ንድፍና ስራ አልቆ ከሁለት ዓመት በኋላ እውን ይሆናሉ፡፡ መሬት ወስደን ጨርሰናል፡፡ የነዚህ ምርቶች 98 በመቶ ጥሬ እቃ ከአገር ውስጥ የሚገኝ ነው፡፡
ሌላው በአዲስ አበባ ንፋስ ስልክ ላፍቶ ክፍለ ከተማ በ50 ሺህ ካሬ ሜትር ላይ “ጀነራል ኬሚካል እና ፓኪንግ” የሚባል ፋብሪካን ግንባታ ላይ ነው ያለነው፡፡ በዚህ መልኩ የማኑፋክቸሪንግ ኢንዱስትሪውን በሰፊው እየተቀላቀልን እንገኛለን፡፡ ለዚህም ቀን ከሌሊት ያለ እረፍት ነው የምንሰራው።
በንግድ ሥራ ስኬታማ ለመሆን የረዳዎት ትምህርት ወይም ልምድ ካለ ቢነግሩኝ---
እንግዲህ ወደ ኋላ ልትመልሺኝ ነው፡፡ እኔ ባህር ዳር ዙሪያ ነው ጣና አካባቢ ተወልጄ ያደግሁት። ዓሳ በማስገር ህይወት የሚመራ ቤተሰብ ልጅ ነኝ። ዓሳ በማስገርም ላይ ነበርኩ፡፡ በ1982 ዓ.ም አካባቢ የለውጡ ሰሞን ዓሳ ኮርፖሬሽን የሚባል ተቋቋመና ዓሳው ሁሉ ለኮርፖሬሽኑ እንዲሆንና ግለሰቦች ዓሳ እንዳያሰግሩ ሲከለከል፣ ከ7ኛ ወደ 8ኛ ክፍል ባለፍኩበት ወቅት ነበር ትምህርቴን አቋርጨ ሸቀጣ ሸቀጥ እየገዛሁ በበቅሎ እየሸጥኩ ንግድ የተለማመድኩት፡፡ ከ1983 ዓ.ም ለውጡ ተደርጎ አገር ነፃ ሆነ ከተባለ በኋላ መጀመሪያ ላይ እንደነገርኩሽ፣ መጀመሪያ በግል ስሜ፣ ከዚያም ፒኤልሲ ከፍቼ ስሰራ ቆይቼ እዚህ ደርሻለሁ፡፡ ይሄው ነው፡፡
እንዲህ አይነት ሰፊ ኢንቨስትመንት ላይ ለመሰማራት ከንግድ ፈቃድ ጀምሮ መሬት እስከመረከብ ከፍተኛ ውጣ ውረድና ቢሮክራሲ እንደሚያጋጥማቸው ብዙ ባለሀብቶች ሲያማርሩ ይሰማል፡፡ እርስዎ በዚህ ረገድ የገጠመዎት ችግር አለ?
ብዙዎች ቦታ ይወስዱና ለረጅም ጊዜ አጥረው ያስቀምጣሉ፡፡ እኛ አካባቢ አጥሮ የሚያስቀምጠውንና ቶሎ ወደ ሥራ የሚገባውን ለመለየት ከሚወስደው ጊዜ በስተቀር ምንም ችግር የለም፡፡ እኔም እስከ ዛሬ እሰራለሁ ያልኩትን በወቅቱና በአግባቡ እየሰራሁ በማሳየት ነው እዚህ የደረስኩት፡፡ እንደውም የበለጠ ትብብርና ድጋፍ እንጂ ያጋጠመኝ ችግር የለም፡፡ በዚህ ላይ ደግሞ የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር አቶ ገዱ አንዳርጋቸው በፋብሪካው ምርቃት ላይ ባደረጉት ንግግር፤ ምስክርነታቸውን ሰጥተዋል፡፡ በስራ ላይ አንዳንድ ችግሮች አይጠፉም ግን በትዕግስት ማለፍ ያስፈልጋል፡፡ ያው በፋብሪካዎቹ በርካታ ሰዎች በመቅጠር ከሴራሚክሱ በካሬ 10 ብር፣ ከቀለም ፋብሪካው ከሊትር 10 ሳንቲም በመቁረጥ እንቦጭን ለመዋጋት የሚደረገውን ትግል በማገዝ፣ ለአገራችንና ለወገናችን የበኩላችንን እያደረግን እንገኛለን፡፡

 በደራሲና ዳይሬክተር በሀይሉ ዋሴ (ዋጄ) ተፅፎ የተዘጋጀውና በእውነት መልቲ ሚዲያ ፕሮዳክሽን ተዘጋጅቶ፣ በኧርሊ ኤ. ኤም መልቲ ሚዲያ የቀረበው “በእናት መንገድ” የተሰኘ ፊልም ከነገ በስቲያ ሰኞ ከቀኑ 11፡30 ጀምሮ በብሄራዊ ቴአትር እንደሚመረቅ አስተባባሪው ኢጋ ሚዲያ ኮሚዩኒኬሽን አስታወቀ፡፡
የድራማ ዘውግ ያለውና 1፡35 ርዝመት ያለው ፊልሙ፣ ተሰርቶ ለመጠናቀቅ 1 ዓመት ጊዜ እንደፈጀ የተነገረ ሲሆን 850 ሺ ብር እንደወጣበትም ተገልጿል፡፡  በፊልሙ ላይ ደሞዝ ጎሽሜ፣ ሜላት ሰለሞን፣ መስፍን ሀይለየሱስ፣ ብርሀኔ ገብሩ፣ አሸናፊ ዋሴ፣ ለምለም አበራ፣ ሰለሞን ተስፋዬና ሌሎችም የተወኑበት ሲሆን በሜላት ሰለሞን ፕሮዱዩስ መደረጉ ታውቋል፡፡