Administrator

Administrator

አንድ ሁለት ሲል፣ ከወትሮው በተለየ ሁኔታ እንግሊዘኛ መቀላቀል የሚያበዛ ሰው ገጥሞዎት አያውቅም?
የዩኒቨርሲቲ ኦፍ ሊቨርፑል ተመራማሪዎች ከሰሞኑ ይፋ ያደረጉት የጥናት ውጤት፣ እንደዚህ ያሉ ሰዎችን በተመለከተ አዲስ ነገር ይዞ መጥቷል ይላል የዴይሊ ሜይል ዘገባ፡፡ ዘገባው እንዳለው፣ የዩኒቨርሲቲው ተመራማሪዎች በኒዘርላንዱ ማስትሪችት ዩኒቨርሲቲ በሚማሩና አፋቸውን በጀርመንኛ ቋንቋ በፈቱ ተማሪዎች ላይ ባደረጉት ጥናት፤ተማሪዎቹ በደህናቸው ከሚናገሩት ይልቅ አንድ ሁለት አልኮል ተጎንጭተው የሚናገሩት ሁለተኛ ቋንቋቸው የሆነው የደች ቋንቋ ንግግራቸው የተሻለ፣ የተቀላጠፈና ያማረ መሆኑን አረጋግጠዋል።
የዩኒቨርሲቲው መምህርና የጥናት ቡድኑ ባልደረባ የሆኑት ዶክተር ኢንግ ኬርስበር እንደሚሉት፤ አንድ ሰው አልኮል ወሰድሰድ ሲያደርግ ሁለተኛ ቋንቋውን የበለጠ አቀላጥፎ እንደሚናገር ለማረጋገጥ ተችሏል፡፡ ይሁን እንጂ ይላሉ ዶክተሩ፤ ይሁን እንጂ ከሞቅታ አልፎ ጥንብዝ ብሎ የሰከረ ሰው ግን፣ በደህናው ከሚናገረው  የባሰ የተበላሸ ንግግር እንደሚያደርግም በጥናቱ ተረጋግጧል፡፡

  ከግማሽ ክፍለ ዘመን በላይ ያስቆጠረው ሂልተን አዲስ አበባ ሆቴል፣ ከኢትዮጵያ ሆቴሎች በአገልግሎት ጥራት የመሪነት ደረጃን በመያዝ፣ለአራተኛ ጊዜ የ”ዎርልድ ትራቭል አዋርድ” ሽልማት ማግኘቱን አስታወቀ፡፡
ሰሞኑን በሩዋንዳ ኪጋሊ በሚገኘው ራዲሰን ብሉ ሆቴል በተደረገው የቀይ ምንጣፍ የሽልማት ስነ ስርአት ላይ ሽልማቱን የተቀበሉት የሂልተን አዲስ አበባ ዋና ሥራ አስኪያጅ ካላኦስ ኮቴነር፤ “ይህ ሽልማት ለሆቴሉና ለሰራተኞቹ ትጋት፣ትልቅ ትርጉም ያለው ስኬት ነው” ብለዋል፡፡
“አዲስ አበባ የሚመጡ በርካታ የዓለም እንግዶችን በጥሩ መስተንግዶ እየተቀበልን እንገኛለን” ያሉት ሥራ አስኪያጁ፤ ለዚህ ቀና መስተንግዶአችን ለተሰጠን እውቅና እናመሰግናለን ብለዋል፡፡
ሂልተን አዲስ አበባ ሆቴል በ”ዎርልድ ትራቭል አዋርድ” ከኢትዮጵያ ሆቴሎች በአገልግሎት አሰጣጥ ጥራት የመሪነት ደረጃውን ይዞ ከዘንድሮው ጋር ለ4 ተከታታይ አመታት ተመሳሳይ ሽልማት ለማግኘት መቻሉን ሆቴሉ ለአዲስ አድማስ ያደረሰው መግለጫ ያመለክታል፡፡ ሆቴሉ በሽልማቱ በመበረታታት የበለጠ አገልግሎቱን ለማዘመን እንደሚሰራም አስታውቋል፡፡
“ዎርልድ ትራቭል አዋርድ” በዓለማቀፍ ደረጃ ከቱሪዝምና ሆቴል አገልግሎት ጋር በተያያዘ ምርጥ የተባሉትን እየለየ፣ በየዓመቱ እውቅና የሚሰጥ አለማቀፍ ተቋም መሆኑ ታውቋል፡፡

ወረርሽኙ 815 ሺህ የመናውያንን አጥቅቷል፤ 2 ሺህ 156 ሰዎችን ገድሏል
   በእርስ በእርስ ጦርነት በደቀቀቺዋ የመን፣የተቀሰቀሰውና ባደረሰው ጥፋትም ሆነ በስርጭቱ ፍጥነት በአለማችን ታሪክ እጅግ የከፋው እንደሆነ
የተነገረለት የኮሌራ ወረርሽኝ፣ ከ815 ሺህ በላይ የአገሪቱን ዜጎች ማጥቃቱንና 2 ሺህ 156 ሰዎችን መግደሉን የአለም የጤና ድርጅት አስታውቋል፡፡
የኮሌራ ወረርሽኙ በፍጥነት በመዛመት ላይ እንደሚገኝ የጠቆመው ድርጅቱ፤ በመጪዎቹ ሁለት ወራት ጊዜ ውስጥ ከአንድ ሚሊዮን በላይ
የአገሪቱን ዜጎች ያጠቃል ተብሎ እንደሚጠበቅና ከእነዚህም መካከል ከ600 ሺህ በላይ ያህሉ ህጻናት መሆናቸውን ከትናንት በስቲያ ባወጣው መግለጫ አመልክቷል፡፡ በየቀኑ 4 ሺህ ያህል የመናውያን በኮሌራ እንደሚጠቁ የገለጸው ድርጅቱ፣ ከግማሽ በላይ የሚሆኑት ተጠቂዎች እድሜያቸው ከ5 አመት በታች የሆኑ ህጻናት መሆናቸውን የጠቆመ ሲሆን ርሃብና የምግብ እጥረት ወረርሽኙን እያባባሱት እንደሚገኝና አለማቀፉ ማህበረሰብ አፋጣኝ ምላሽ ካልሰጠ በአገሪቱ የከፋ ጥፋት እንደሚከሰትም አስረድቷል፡፡ በአገሪቱ የተከሰተውን የከፋ የኮሌራ
ወረርሽን ለመግታት የሚደረገው ጥረት በቂ አለመሆኑን የጠቆመው ድርጅቱ፤ የጽዳት ሰራተኞች ደመወዛቸው ስላልተከፈላቸው የስራ ማቆም አድማ ማድረጋቸውን ተከትሎ፣ ቆሻሻዎች በየመንገዱ እየተጣሉ አስከፊ የጤና እክል እየፈጠሩ ነው ብሏል። ሰባ በመቶ የሚሆነው የአገሪቱ ህዝብ የንጹህ የመጠጥ ውሃ አቅርቦት እንደማያገኝ የዘገበው ዘ ጋርዲያን፤ የአገሪቱ መንግስት ካለፈው አመት አንስቶ ለህዝብ የጤና ተቋማት የሚሰጠውን የገንዘብ ድጋፍ ማቋረጡንና በርካታ የአገሪቱ ዶክተሮችና የሆስፒታል ሰራተኞች ደመወዛቸውን ካገኙ ከአንድ አመት በላይ እንዳለፋቸውም አስታውሷል፡፡

በአለም አቀፍ ደረጃ በየአመቱ 43/ሚሊዮን የሚሆኑ ሰዎች ጥንቃቄ በጎደለው የህክምና አገልግሎት አሰጣጥ ምክንያት ከጉዳት ላይ ይወድቃሉ፡፡
ባለፈው እትም የሕክምና ባለሙያዎችን የህግ ተጠያቂነት በሚመለከት ለንባብ ያልነው ተከታይ እንደሚኖረው ገልጸን ነበር፡፡ እነሆ ዛሬም አቶ አበበ አሳመረ የህግ ባለሙያና ጠበቃ እንዲሁም የኢትዮጵያ የጽንስና ማህጸን ሕክምና ባለሙያዎች ማህበር የህግ አማካሪ የሰጡትን መብራሪያ እና አንዳንድ እውነታዎችን እናስነብባችሁዋለን፡፡
በአለም አቀፍ ደረጃ በየአመቱ 234/ሁለት መቶ ሰላሳ አራት ሚሊዮን የሚደርሱ የቀዶ ሕክምና አገልግሎት የሚሰጥ ሲሆን ከ25/ሀያ አምስት ቀዶ ሕክምናዎች አንዱ ድንገት በሚፈጠር የጤና ችግር ይቅር የማይባል እና በድንገት ወይንም በግድ የሚሰራ ነው፡፡ በታዳጊ አገሮች በሚደረጉ ቀዶ ሕክምናዎች ምክንያት ወደ 10/ከመቶ የሚሆን ሞት ይደርሳል፡፡ መረጃው እንደሚያሳየው በአጠቃላይ በአለም ደረጃ ለሕልፈት ምክንያት ከሚሆኑት የቀዶ ሕክምና አገልግሎቶች መካከል ወደ 50/ከመቶ የሚሆኑት ጥንቃቄ ቢደረግ ኖሮ ሊከላከሉት የሚቻል ሰዎችንም ለጉዳት የማይዳርጉ በሆኑ ነበር፡፡  
በአንዳንድ አገሮች ለማሳያነት ያህል የተጠቀሰው በህክምና አገልግሎት አሰጣጥ ስህተት ምክንያት በአመት የሚደርሱ የሞት ቁጥሮች የሚከተሉትን ይመስላል፡፡
በአሜሪካ 98‚000/ ዘጠና ስምንት ሺህ
በካናዳ 24‚000/ሀያ አራት ሺህ
በአውስትራሊያ 18‚000/አስራ ስምንት ሺህ ይሆናል፡፡
ምንጭ (Times India)
ባለፈው እትም አንስተን ያልተመለሱት ጥያቄዎች የሚከተሉት ናቸው፡፡
በሕክምና አሰጣጥ ረገድ ጥፋት የሚባለው ምንድነው?
የሚመዘንበት ደረጃስ አለ?
ማነው ጥፋት አለ ማለት የሚችለው?
አንድ ወጥ የሆነ ደረጃስ አለ? የሚሉት ናቸው፡፡
የህግ ባለሙያው አቶ አበበ አሳመረ የሚከተለውን ማብራሪያ ሰጥተዋል፡፡
በኢትዮጵያ የህክምና ባለሙያው ምናልባት ስህተት ፈጥሮአል ቢባል በአስተዳደር፣ በፍትሐ ብሔር እና በወንጀል ኃላፊነቶች ጥቅም ላይ የሚውሉ የጥፋት መመዘኛዎች ይለያያሉ፡፡ ለምሳሌም የወንጀል ሕጉ የቸልተኝነት ደረጃን ስለሚገልጽ ለወንጀል ኃላፊነት ይጠቀምበታል፡፡ ለፍትሐብሔር ኃላፊነት ጥፋት የሚባለው ነገር በግልጽ መመዘኛው ባይታወቅም ነገር ግን ማንኛውም ሰው ላደረሰው ጥፋት ኃላፊነት አለበት ስለሚል  ፍርድ ቤቶች ይህንን እየመዘኑ ጥፋት አለ ወይንስ የለም የሚለውን ያረጋግጣሉ፡፡ በዚህም መሰረት ኃላፊነት አለበት ወይንስ የለበትም ብለው ውሳኔ ይሰጣሉ፡፡ የአስተዳደር ኃላፊነት ጥፋት አለ ወይንስ የሚለውን ኮሚቴው አይቶ ይወስናል፡፡ እንግዲህ በዚህ ዙሪያ የአለምን የህክምና ማህበር ጨምሮ የሚታየው ክርክር አንድ ወጥ የሆነ የህክምና ስህተት የሚዳኝበት ደረጃ እንዲኖር ቢደረግ የሚል ነው፡፡  ይሄ ቢደረግ ጥሩ ነው ብለው የህግ ባለሙያዎች ይስማማሉ፡፡ በሶስቱም ደረጃዎች ተጠያቂ የሚሆን ባለሙያ አንድ ወጥ በሆነ አሰራር ጉዳዩ እንዲታይ የሚለው ነገር ብዙዎችን ያስማማል፡፡ ብለዋል አቶ አበበ፡፡
አቶ አበበ አክለውም በወንጀል የመጠየቅ ነገር አሁን አሁን እንዲያውም እየደበዘዘ ነው ፡፡ በእርግጥ በእኛ አገር አለ የለም ወይንም ተጠያቂነቱ ጨምሮአል ወይንም አልጨመረም ለማለት የሚያስችል መረጃ የለም፡፡ በሌሎች አገሮች ግን እየቀነሰ ነው፡፡ ለዚህ ምክንያቱ ደግሞ ሰዎች የሚሰሩት ስህተት ሰብአዊ ነው። ማንም ፍጹም ስለሌለ ስህተት ምንጊዜም ስለማይጠፋ መሳሳትም ሰው ባላሰበው መንገድ የሚፈጽመው አንዱ ተግባሩ ነው ተብሎ ይታመናል፡፡ በአገ ራችንም አባባል ‹‹…ከሰው ስህተት ከብረት ዝገት አይጠፋም…›› ቢባልም  የህክምናው አገልግሎት ስህተት ወደ እውነታው ሲተረጎም ማንኛውም የህክምና ባለሙያ ማለት በሚያስችል ሁኔታ ሰውን ለመጉዳት ብሎ የሚያደርሰው ጥፋት የለም። እንደማለት ነው፡፡ ብዙ ጊዜ ችግር የሚፈጠረውም የሰውን ሕይወት አድናለሁ ብሎ በሚሰራው ስራ ላይ በተለያዩ ምክንያቶች በሚፈጠሩ ጉድለቶች የተነሳ  ነው፡፡ በእርግጥ ይህ ማለት ግን አንዳንድ በቸል ተኝነት ወይንም በችኩልነት …ወዘተ … በመሳሰሉት ምክንያቶች ሰዎችን ለሕልፈት እንዲዳረጉ የሚያደርጉ ባለሙያዎች የሉም ማለትም አይቻልም፡፡ ስለዚህ አንዳንድ ስህተት በሚፈጠር ጊዜ ተጠያቂነቱ በፍትሐብሔር ደረጃ እንዲሆን የተፈለገበት አንዱ ምክንያት ከላይ የተጠቀሰው ሲሆን በዚህም ምክንያት ተጠያቂነትን በመሸሽ የህክምና ባለሙያዎች እጥረት እንዳያጋጥም ከሚል ነው። ለምሳሌም በአንድ ወቅት በአሜሪካ ሁለት ግዛቶች በጣም ተፈላጊ የሆኑ ባለሙያ ዎችን እስከማጣት ተደርሶ ነበር፡፡ ምንም እንኩዋን በጣም ጥቂት በሆኑ ባለሙያዎች በሚፈጠር ስህተት ምክንያት ሰዎች የሚጎዱ ቢሆንም እጅግ ብዙ ባለሙያዎች የሰፊውን ህዝብ  ሕይወት በመጠበቁ ረገድ እንዲሳተፉ ይፈለጋል፡፡ ስለሆነም የሙያው አገልግሎት ክብርም ሆነ ባለሙ ያው መጎዳት የለበትም የሚለው አስተሳሰብ አለም አቀፍ ነው፡፡
በአገራችን (ኢትዮጵያ) የተደረገ ጥናት ወይንም የሚታይ መረጃ ባይኖርም በሌሎች አገሮች ግን የሚታዩ እውነታዎች አሉ፡፡ ለምሳሌም በሕንድ የተመዘገበው የህክምና ስህተት በመድሀኒት አሰጣጥ፣ በሚወሰድ መድሀኒት መጠን አለመስተካከል፣ የአንዱን ታካሚ መድሀኒት ለሌላው በመስጠት፣ የመድሀኒት አወሳሰድ ጊዜን በትክክል ባለማሳወቅ፣ በቸልተኝነት፣ በቀዶ ሕክምና ጊዜ ሊሰጥ የሚገባውን ትኩረት በመንፈግ፣ የማደንዘዣ መድሀኒት መጠንና ጊዜ….ወዘተ በመሳሰሉት ምክንያቶች በታካሚው ላይ ችግር የሚፈጠር ሲሆን በእነዚህም ምክንያቶች የሚቀርቡ የፍትሕ ጥያቄዎች በግምት በአመት ወደ 5.2/ሚሊዮን እንደሚደርስ ይገመታል፡፡
ያለፈውን እትም ያነበቡ አድማጭ የሚከተለውን ገጠመኝ ልከውልናል፡፡
‹‹…ጊዜው ምናልባት ወደ 16 አመት ይሆነዋል፡፡ ልጅትዋ የባለቤቴ እህት ልጅ ናት፡፡ በጊዜው በግምት የ19/ አመት ልጅ ነች፡፡ አንድ ቀን በድንገት ከተኛችበት መነሳት ያቅታትና እርዳታ ትጠይቃለች፡፡ በቃ። መቀመጥ መነሳት ችግር ሆነ፡፡ ወለምታ… ቅጭት …ያልተባለ ነገር አልነበረም፡፡ በባህላዊው እና በእምነቱ መንገድ የተቻለው ሁሉ ተደረገ፡፡ አልተሳካም፡፡ ሲብስባት ወደሐኪም ቤት ተወሰደች፡፡ ከሐኪም ቤቱ የተገኙት መልሶች እና የሚታዘዙላት መድሀኒቶች የሚያስደንቁ ነበሩ፡፡ አንዱ ሐኪም በበረሐ አካባቢ ትኖር ነበር ወይ ይላል፡፡ ሌላው ጉበትዋ ላይ ምልክት አይቻለሁና ይህንን ኪኒን ትውሰድ እና ካልተሸላት መልሳችሁ አምጡ ይላል፡፡ ብቻ ጨጉዋራ… አንጀት… ጣፊያ….ያልተባለ ነገር የለም፡፡ ሕክምናውም አንድ ቦታ ሳይሆን ወደ ተለያዩ ቦታዎች ነበር የተወሰደችው፡፡ ሁሉም ቦታ የሚሰጡአት መድሀኒቶች ግን ተጨማሪ በሽታ ነበር የሆነባት። አንዱን ሐኪም በተለይም አልረሳውም፡፡ባለቤቴ ስለልጅትዋ ሕመም ሁኔታ ሊያስረዳው ሲሞከር ይህን ካወቅህማ ለምን መጣህ ይዘህ ወደቤትህ ሂድ ነበር ያለው፡፡ በስተመጨረሻው ግን ቤተሰቡ ሁሉ ተስፋ ቆረጠ፡፡ ስለዚህም የተደረሰበት ስምምነት …ከእንግ ዲህ ወዲህ ይህች ልጅ ወደሐኪም ቤት አትሄድም፡፡ በቃ። እግዚአብሔር ከማራት ይማራት፡፡ ካለበለዚያም ትሙት፡፡ የሚል ነበር፡፡ ሌላ አማራጭ ግን የተደረገው ወደጸበል መውሰድ ነበር፡፡ ልጅትዋ ከተኛችበት ቤተሰቡ ተሰብስቦ የጸበል እጣ በመውጣት ላይ እያለ አንዲት ቅርብ የሆነች ጎረቤት ልጅትዋን ልትጠይቅ መጣች። ሁኔታውን አስረዳናት፡፡ የእሱዋም መልስ እስቲ ለእኔ አንድ እድል ስጡኝና አንድ ሐኪምጋ ልውሰዳት አለች፡፡ አጎትየው አይ ሆንም፡፡ ምንሲደረግ ከዚህ በሁዋላ ሐኪም ያያታል አለ፡፡ እሱዋም ለመነች፡፡ ቤተሰቡም ጸበል መሄጃው ቀኑ እስኪቆረጥ…እንዲሁም የት እንደሆነ ቦታው እስኪታወቅ…ስንቁም እስኪዘጋጅ ድረስ ምን ቸገረህ ትውሰዳት ተባለ እና ተፈቀደላት፡፡ በሁዋላ እንደተነገረን ከሆነ ልጅት ሐኪሙ ዘንድ በሸክም ስትቀርብ አስቀድሞ ታሪክዋን ነበር የጠየቃት፡፡ የት እንደም ትኖር… ወድቃ ታውቅ እንደሆነ…ወይንም ከግኡዝ ነገር ጋር ተጋጭታ እንደነበር …ከሰው ተጣልታ ወይንም ተደባድባ እንደነበር ….ካጠና በሁዋላ መመርመሪያ አልጋው ላይ አስተኝቶ ሕመሙዋን አወቀ፡፡ ለካስ ልጅትዋ ታማ ከመተኛትዋ ሶስት ወር በፊት ወድቃለች፡፡ በምት ወድቅበት ጊዜም ጭራዋ ተመትቶ ስለነበር ውስጥ ውስጡን ሲታመም ቆይቶ ከባሰ ደረጃ ላይ ሲደርስ ነበር የጣላት፡፡ አንዴ ጨጉዋራ…ጣፊያ…አንጀት…ጉበት…ሲባል የነበረው በሽታ የጭራ በድንጋይ መመታት ሆነ፡፡ ይሄኛው ሐኪም ያዘዘውም መድሀኒት ገና በሶስተኛው ቀን ቁጭ እንድትል ከአልጋዋም ላይ በሸክም ሳይሆን እራስዋ እንድትነሳ እንድትቀመጥ አስቻላት፡፡ እናም ሐኪሞች ሁሉም አንድ አይደሉምና ከፍተኛ የሆነ ክትትል ያስፈልጋል ባይ ነኝ፡፡
(ጸጋ ቢልልኝ ከቦሌ ቡልቡላ)
 ይቀጥላል…

 ሚዩዚክ ሜይዴይ ኢትዮጵያ የመጻህፍት ንባብና ውይይት ፕሮግራም ከኢትዮጲስ ኮሌጅ ጋር በመተባበር፣ በብሩህ ዓለምነህ በተጻፈው “የኢትዮጵያ ፍልስፍና” በተሰኘው መጽሐፍ ላይ በነገው ዕለት ከ8 ሰዓት ጀምሮ በብሔራዊ ቤተ መጻህፍትና ቤተ መዛግብት ኤጀንሲ (ወመዘክር) አዳራሽ ውይይት ያካሂዳል፡፡ ለውይይቱ መነሻ ሃሳብ የሚያቀርቡት የህግ ባለሙያው አቶ ውብሸት ሙላት ሲሆኑ ፍላጎት ያለው ሁሉ በውይይቱ ላይ እንዲታደም ሚዩዚክ ሜይዴይ ጋብዟል፡፡

• በቀበሌና በወረዳ ያሉ መስህቦችን ጎብኝቼ እጨርሳለሁ ማለት ዘበት ነው
                        • ቱሪዝምን ከባህል ነጥሎ ማየት በአንድ እጅ እንደ ማጨብጨብ ይሆናል
                        • በክልሉ ገና ብዙ ያልተጎበኙ ዋሻዎች፣ ፏፏቴዎችና ሀይቆች አሉ
                                 ዶ/ር ሂሩት ካሳው (የአማራ ክልል ባህልና ቱሪዝም ቢሮ ኃላፊ)

    በአማርኛ ቋንቋ ትምህርት ዲፕሎማቸውን ካገኙ በኋላ የመጀመሪያ ዲግሪያቸውን በኢትዮጵያ ቋንቋዎችና ሥነ - ፅሁፍ ተመርቀዋል፡፡ በዚህ ሳይገደቡ ትምህርታቸውን የገፉት የዛሬዋ እንግዳችን፤ሁለተኛ ዲግሪያቸውን (MA) የአማርኛ ቋንቋን የማስተማር ዘዴ በሚል ዘርፍ ከአገኙ በኋላ በ1998 ዓ.ም ባህርዳር ዩኒቨርሲቲን በመቀላቀል፣ በኢትዮጵያ ቋንቋዎችና ሥነ ፅሁፍ አማርኛ ትምህርት ክፍል መስራት ጀመሩ፡፡ ከዚህ በፊት ግን በኦሮሚያ ክልል የአማርኛ መምህር ሆነው ከአንደኛ እስከ ሁለተኛ ደረጃ ት/ቤቶች አስተምረዋል፡፡ በባህርዳር ዩኒቨርሲቲ ለአራት ዓመታት ከሰሩ በኋላ ሶስተኛ ዲግሪያቸውን (PhD) ለመስራት ወደ አዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የመጡት እንግዳችን፤ “ተግባራዊ ስነ- ልሳን በኢትዮጵያ ቋንቋዎች ማስተማር” (Applied Lingusitcs) ተመርቀው ወደ ባህርዳር ዩኒቨርሲቲ በመመለስ የአማርኛ ቋንቋ ማበልፀጊያ ተቋም መስርተው ለሁለት ዓመታት ሰርተዋል፡፡ ከዚህ በኋላ ነው እሳቸው “የአገር ጥሪ ነው” ወደሚሉት የአማራ ክልል ባህልና ቱሪዝም ቢሮ ኃላፊነት በሹመት የመጡት -
ዶ/ር ሂሩት ካሣው፡፡ የአጋጣሚ ነገር ሆኖ ደግሞ እርሳቸው በተሾሙበት ወቅት ለክልሉ ብቻም ሳይሆን ለመላ አገሪቱ በተለይም እሳቸው ለተሾሙበት ዘርፍ ፈታኝ የሆነው አለመረጋጋት የተከሰተበት ወቅት ነው፡፡ በዚያ ላይ ለስራው አዲስ ነበሩ፡፡ ያንን ፈታኝ ወቅት እንዴት አለፉት? በዘርፉ ላይ የተጋረጠውን ፈተና እንዲሁም የአካባቢውን ገፅታ ለመመለስ ምን እንቅስቃሴዎች ተደረጉ? የዘንድሮ የዓለም ቱሪዝም ቀን እንዴት ተከበረ? የክልሉን የቱሪስት መስህቦች ይበልጥ ለማስተዋወቅ ምን ታስቧል? እና ተያያዥ ጉዳዮችን አስመልክቶ፣ የአዲስ አድማስ ጋዜጠኛ ናፍቆት ዮሴፍ፣ የክልሉ ባህልና ቱሪዝም ቢሮ ኃላፊን ዶ/ር ሂሩት ካሣውን በስፋት አነጋግራቸዋለች፡፡

      ከባህር ዳር ዩኒቨርሲቲ እንዴት ወደ ክልሉ ባህልና ቱሪዝም ቢሮ ኃላፊነት  መጡ?
እኔ ይህንን የአገር ጥሪ ነው ብዬ ነው የተቀበልኩት። አንድን ሰው አገሩ ይሆነኛል፣ ያገለግለኛል ብላ ስትጠራው፣ በሙያው አቅሙ በቻለ መጠን ማገልገል አለበት፡፡ እኔም ይህን ስለማምን ጥሪውን ተቀበልኩት እንጂ ቀደም ብሎ፣ በዚህ ቦታ ላይ ተሹሜ እሰራለሁ የሚል እቅድ አልነበረኝም፡፡ በህልሜም በእውኔም አስቤውም አላውቅም፡፡ እንዳልኩሽ የአገር ጥሪ ነው፤ ጥሪውን ተቀብዬ ማገልገል ጀመርኩ፡፡ ወደ ቢሮው ኃላፊነት የመጣሁት፣ በታህሳስ ወር 2009 ዓ.ም ነው፤ አሁን ዘጠኝ ወሬ ነው ማለት ነው፡፡   
ከመጀመሪያ እስከ ሦስተኛ ዲግሪ የተማሩት ከኢትዮጵያ ቋንቋዎችና ሥነ ፅሁፍ ጋር በጣም የተዛመደ ነው፡፡ የተማሩበት ዘርፍና የተሰጥዎ  ሃላፊነት ይጣጣማሉ?
እንዳልሺው ሁሉም የትምህርት ዝግጅቴ በአብዛኛው ከኢትዮጵያ ቋንቋዎችና ሥነ - ፅሁፍ ጋር ይገናኛል፡፡ ነገር ግን ሦስተኛ ዲግሪዬ (አፕላይድ ሊንጉስቲክስ) በጣም ሰፋ ያለ ነው፡፡ በቋንቋ ላይ የሚመጣ ተፅዕኖና ቋንቋ በማህበረሰቡ ላይ የሚያመጣው ተፅዕኖ ላይ የሚያተኩር ስለሆነ፣ ቋንቋን ማህበረሰብን ስታጠኚ በዚያውም የማህበረሰቡን ባህልና ማንነት አብረሽ ታጠኚያለሽ። እንደውም ከቋንቋና ከባህልም ያልፋል፡፡ ሦስተኛ ዲግሪዬ የሚዳስሰው የባህል መገለጫ ስንል፣ አልባሳትንና ከላይ የሚታዩ ጌጣጌጦችን ብቻ ሳይሆን የሰውን ልጅ የአስተሳሰብን ውጤት ሳይቀር ይመረምራል፡፡ የሰው ልጅ የአስተሳሰብ ውጤቶች በቋንቋ ላይ ተፅዕኖ ሲያደርጉ ወይም ቋንቋ በተቃራኒው ያለውን ተፅዕኖ የሚዳስስ ስለሆነ እስከ ማስተማር ይደርሳል፡፡ ትምህርቱ በዚህ መልኩ እገዛ አለው፡፡ ነገር ግን ባህልና ቱሪዝም ከመምጣቴ በፊት ትኩረት የማልሰጣቸው ነገሮች ግን ትኩረት ማድረግ የሚገቡኝን ነገሮች እንዳስተውል አድርጎኛል። ቱሪዝም የሚለውን ነገር በአግባቡ ለማወቅና ለመረዳት ወሳኙ ነገር ባህልን ማወቅ ነው። ቱሪዝምን ከባህል ነጥሎ ማየት በአንድ እጅ እንደ ማጨብጨብ ይሆናል፡፡ ስለ ባህል ትልቅ ግንዛቤ የሌለው ሰው፤ የቱሪዝም ሀብቶችን ማወቅና መለየት አይችልም፡፡ በአጠቃላይ ሦስተኛ ዲግሪዬ፣ አሁን ለተሾምኩበት ስራ ጥሩ ግንዛቤ እንዲኖረኝ ከፍተኛ አስተዋፅኦ አድርጎልኛል፡፡
እርስዎ የሚመሩት ቢሮ በሰው ሰራሽም ሆነ በተፈጥሮ የቱሪስት መስህቦቹ ብዛትና ስፋት ግዙፍ ነው፡፡ በዩኔስኮ ከተመዘገቡ ቅርሶች አብዛኞቹ ያሉትም በዚህ ክልል ይመስለኛል፡፡ ይህንን ግዙፍ የክልል ቢሮ መምራት አይከብድም?
በክልሉ ያለውን እያንዳንዱን የቱሪዝም ሀብት ማወቅ በጣም ከባድ ነው፡፡ እኔ በፊት የሚመስለኝ ኃላፊው ቢሮ ተቀምጦ፣ በስሩ ያሉት ኃላፊዎች ሄደው፣ መረጃውን አምጥተውለት፣የሚነግሩትን የሚያስተባብር ዓይነት ነበር፡፡ በፍፁም እንደዚያ አይደለም!! ለማስተባበርም መጀመሪያ የክልሉን ሀብት ዞረሽ ማየት፣ መገንዘብ፣ ሁኔታዎችን ማጤን ያስፈልግሻል፤ ይሄ የግድ ነው፡፡ ምክንያቱም ቢሮ ቁጭ ብለሽ ልትሰሪው የምታስቢውና ሄደሽ በአካል የምትመለከቺው ነገር እጅግ በጣም ይለያያል፡፡ ሲነገርሽ ትንሽ የሚመስል፣ በአካል ስታገኚው ትልቅ ሀብት መሆኑን ታስተውያለሽ፡፡
ከዚህ አንፃር እርስዎ ምን ያህሉን የክልሉን የቱሪዝም መስህቦች ተዘዋውረው ተመልክተዋል?
ሁሉንም አይቻለሁ ማለት ይከብዳል፡፡ እንደ ብዙሃኑ አስተሳሰብ፤ ሰው የቱሪስት መስህብ ሲባል ፋሲል ግንብ፣ ላሊበላ፣ አክሱም፣ ሶፉመርና ሌሎች በዩኔስኮ ተመዝግበው እውቅና ያገኙ መስህቦች ይመስላቸዋል፤ ግን አይደለም፡፡ በተለይ በአማራ ክልል በየመንደሩ በየወረዳው እጅግ አስደናቂ የሆኑ፣ በርካታና ለቁጥር የሚያታክቱ መስህቦች አሉ፡፡ በእያንዳንዱ ቀበሌና ወረዳ፣ በየመንደሩ ያሉ መስህቦችን ጎብኝቼ እጨርሳለሁ ማለት ዘበት ነው፡፡
አሁን ለምሳሌ በአዊ ብሄረሰብ ዞን ብቻ የሚገኙትን እንደ ፏንግ ፏፏቴ፣ የደንና አስካስታ ዋሻዎች፣ ደንዶር ፏፏቴ፣ ጥርባ ሃይቅ---የሚባሉትን ማየት ቀርቶ ስማቸውንም ሰምተን አናውቅም። አንቺም የነዚህን ፏፏቴዎች፣ ሀይቆችና ዋሻዎች ታሪክ ስትሰሚና በአካል ተገኝተሸ ስትመለከቺ፣ ኢትዮጵያን እንደማታውቂያት ይገባሻል፡፡ ስለዚህ እየተዘዋወርኩ እጎበኛለሁ ግን ሁሉንም ለማዳረስ ጊዜም አይበቃም፤ በጣም ሰፊ ነው፡፡ ሁሉንም ጎብኝቻለሁ ማለት አልችልም፡፡ ምክንያቱም በየዞኑ አይደለም፣ በየመንደሩ ያለውን ሀብት እየሄዱ መጎብኘት ከባድ ነው፡፡ ለዚህ እንደ መፍትሄ የተቀመጠው፣ እስከ ወረዳ ድረስ የተዘረጋው መዋቅር ነው፡፡ እነዚህ በየወረዳው ያሉ የቱሪዝም ባለሙያዎች፣ በየመንደሩና በየጥጋጥጉ ያሉ የቱሪዝም ሀብቶቻቸውን ባህላዊ፣ ሰው ሰራሽም ሆነ ተፈጥሯዊውን በሶፍት ኮፒ እንዲያቀርቡ እናደርጋለን፡፡ በዚህ አማካኝነት ነው ለማወቅ የምንሞክረው፡፡ በአንድ ወረዳ አዊ እንኳን ከ12 በላይ ፏፏቴዎችና ዋሻዎችን ነው የተመለከትነው። ከየወረዳዎች የሚመጡልንን መስህቦች እናይና፣ የትኛው ቅድሚያ ተሰጥቶት ይተዋወቅ፣ የትኛው ይከተል የሚለውን ለመወሰን ቦታው ድረስ እንሄዳለን፡፡  
ዘንድሮ በክልሉ ለ25ኛ ጊዜ፣ “ቱሪዝም ለዘላቂ ልማት” በሚል ከመስከረም 23 እስከ 29 በተከበረው የዓለም የቱሪዝም ቀን፣ በዓሉን ለማክበሪያና ለጉብኝት ምዕራብ ጎጃም ዞን፣ አዊ ብሔረሰብ ዞንና ሰሜን ጎንደር ዞን  የተመረጡበት ምክንያት ምንድን ነው?
የዘንድሮውን የዓለም የቱሪዝም ቀን በዋናነት ያልታዩና ያልተጎበኙ የቱሪስት መስህብ ቦታዎችን በማስተዋወቅ ማክበር ላይ ነው ትኩረት ያደረግነው። ሁለተኛው ዓላማ፣ በክልሉ ያለው የሰላም ሁኔታ ምን ይመስላል የሚለውን ጋዜጠኞች በአካል ቦታው ላይ ተገኝተው እንዲያረጋግጡ ማድረግ ነው፡፡ በመጎብኘት ረገድ ምዕራብ ጎጃም ዞንና አዊ ማህበረሰብ ዞን ተመርጠው፣ ያላቸው የቱሪስት መስህቦች እንዲጎበኙ ሆነዋል፡፡ ያው አንቺም እንዳየሽው፣ አስደናቂ ፏፏቴዎች፣ ትልልቅ ርዝመት ያላቸው ዋሻዎች፣ የሰባት ቤት አገው የፈረስ ትርኢት ተጎብኝተዋል፡፡
 የምዕራብ ጎጃም ዞን ዋሽራ የባህል ቡድን፣ የተለያዩ ዋሻዎችን የደጃች ሀይለየሱስ ፍላቴ (አባ ሻወል) ሀውልት ታይተዋል፡፡ እነዚህ ላይ በደንብ መስራትና ሀብት ማግኘት ስለሚያስፈልግ ማለት ነው፡፡ ሌላው የሰሜን ተራሮች ብሄራዊ ፓርክ፣ ሊማሊሞና “የንግስት ማረፊያ” የተባለው ታሪካዊ ቦታና በወገራ ወረዳ ኮሶዬ የተባለ አካባቢ ያለው የቱሪስት መስህብ ተጎብኝተዋል። ይህ ሰሜን ጎንደር ዞን፣ ከሰላም አለመኖር ጋር በተያያዘ አሁንም ብዙ ይወራል፤ ግን አካባቢው መቶ በመቶ ሰላም የሰፈነበትና የተረጋጋ ነው፡፡ ይህንን እናንተ እንድታዩና እንድትታዘቡ ለማድረግ ነው አላማው፡፡
ግን እኮ በቅርቡም አሜሪካ ኤምባሲ በአካባቢው መረጋጋትና ሰላም እንደሌለ በመግለፅ፣ ዜጎቹ ወደ አካባቢው እንዳይሄዱ ክልከላ አውጥቷል፡፡ ይሄ እንዴት ነው?
ያው እንደሚታወቀው ባለፈው ዓመት አለመረጋጋት እንደነበር ግልፅ ነው፡፡ ይህ አለመረጋጋት ቱሪዝሙን መጉዳቱም የሚካድ አይደለም፡፡ ነገር ግን በተለያዩ ጥረቶች አካባቢው አሁን ሰላም ነው፤ እናንተም ቦታው ላይ ተገኝታችሁ ያጋጠማችሁ ችግር የለም፡፡ የበፊቱን ያህል ባይሆንም አሁንም የቱሪስት የጉብኝትም ሆነ የስራ ጉዞ ክልከላ ሚዛናዊ ነው ብዬ አላምንም፡፡ ምክንያቱም የአሜሪካ ኤምባሲ ሰዎች፣ በየቀኑ እየመጡ እዚህ ከተማ ላይ፣ በክልሉ ሌሎች ከተሞችም ስራ ሰርተው፣ ስብሰባ ተሰብስበው በሰላም ይመለሳሉ፡፡ እኔና አንቺ አሁን እየተነጋገርን ባለንበት ወቅት እንኳን (ማክሰኞ ምሽት ነው ቃለ ምልልሱ የተደረገው) የአሜሪካ አምባሳደር ነገ ጠዋት እዚህ ባህርዳር ለስራ ይመጣሉ፡፡ ሰላም ከሌለ ለምን ይመጣሉ? እሳቸው ከመጡስ ሌሎች ዜጎቻቸውን ለምን ይከለክላሉ? ይሄ ለኔም የሚገርመኝ ጥያቄ ነው፡፡
በአዊ ብሄረሰብ ዞን ያሉ ሁለት ቦታዎችን ይበልጥ ለማስተዋወቅና የቱሪስት መዳረሻ ለማድረግ ፕሮጀክት መቀረፁን ቀደም ብለው ነግረውኝ ነበር። ሁለቱ መስህቦች እነማን ናቸው? የተቀረፀው ፕሮጀክትስ ምን ይመስላል?
በዚህ ዓመት ሁለቱ ፕሮጀክት የተቀረፀላቸው መስህቦች፣ የሰባት ቤት አገው የፈረሰኞች ማህበርና ዘንገና ሀይቅ ናቸው፡፡ ፕሮጀክቱ የሰባት ቤት አገው ፈረሰኞች ማህበር፣ 78 ዓመት ዕድሜ ያስቆጠረ፣ ከ48 ሺህ በላይ አባላት ያሉት በመሆኑ፣ ይህ የፈረስ ትርኢት በአገራችን ብሎም በአፍሪካ አለ ወይ የሚለውን መለየት ነው፡፡ ማህበሩ ከፈረስ ትርኢት ባለፈ ለኢትዮጵያ ህዝብ ያልተነገረው ታሪክም አለውና፡፡ አንድም በፈረስ ማህበሩ ላይ ጥናት ማድረግ፣ ሁለትም ከዞን ትርኢትነት አልፎ አገር አቀፍ ፌስቲቫል ማድረግ ሲሆን በዚህ ዓመት ጥር 23 ብዙ ቱሪስቶች የሚገኙበት በርካታ የየክልል ባህል ቱሪዝም ሀላፊዎች በሚገኙበት በሰፊው የፈረስ ፌቲቫሉን ማካሄድ ነው፡፡ ለዚህም ከቢአርሲ ባጀት አስጎብኚ ድርጅት ጋር የስምምነት ፊርማ ሲካሄድ እናንተም ተመልክታችኋል፡፡ ዘንገና ሃይቅም ባለፈው ሀሙስ የፈረስ ትርኢቱ ከእንጅባራ ተነስቶ ፍፃሜውን ያደረገው ዘንገና ሀይቅ ላይ ነው፡፡ ሀይቁም ማራኪና ቀልብን የሚስብ ሆኖ ሳለ በአካባቢ ጎብኚዎች አረፍ ብለው ሻይ ቡና የሚሉበት ምንም አይነት አገልግሎት የሚሰጥ ነገር የለም፡፡ ዘንድሮ በአካባቢው ይህን አገልግሎት የሚሰጡ መሰረት ልማቶች እንዲስፋፉ ይደረጋል፡፡ እርግጥ ቀደም ሲል ሎጆችን በሀይቁ ዙሪያ እንዲሰሩ ለባለሀብቶች ቦታ ተሰጥቷቸዋል ግን አንዳንዶቹ ጀምረው ትተውታል፤ሌሎቹ ቦታውን ወስደው ግንባታም አልጀመሩም፡፡  
ለምን ይሆን ባለሃብቶቹ  መገንባት ያልፈለጉት?
እንግዲህ መሬት ወስዶ አጥሮ ረጅም ጊዜ ማቆየት እዚህ አገር እንደ ባህል ተቆጥሯል፤ ስለዚህ እርምጃ ወስዶ ለሌላ ባለሀብት ቦታውን መስጠት ያስፈልጋል፡፡ የዞን አስተዳደሪውም ቦታውን በአስቸኳይ የማያለሙ ከሆነ ለሌሎች ባለሀብቶች እንደሚሰጡት ሲያስጠነቀቅ አብረን ሰምተናል። ግንባታውን የጀመሩት ደግሞ ለምን እንዳቆሙ ሲጠየቁ፣ አንዳንድ የዲዛይን ለውጥ ስለሚያስፈልግ፣ ያንን አስተካክለን ወደ ስራ እንገባለን የሚል ምክንያት እንዳቀረቡ ሰምቻለሁ። በዕለቱም ከዞኑ አስተዳዳሪ ጋር እንደተነጋገርነው፣ እነዚህ ሎጆች በዚህ ዓመት ያልቃሉ፡፡ እነዚህ ፕሮጀክቶች ከተተገበሩ የፈረስ ፌስቲቫሉም ዘንገና ሀይቅም የቱሪስት መስህብነታቸው ወደተሻለ ደረጃ ያድጋል የሚል እምነት አለኝ፡፡ በነገራችን ላይ ጥር 23 የሚካሄደው የፈረስ ፌስቲቫል፣ እቅድ ሰፋ ያለ ነው፡፡ ጥር 23 አዊ ላይ ይካሄድና፣ ጥር 25 ደቡብ ጎንደር የራሳቸው የፈረስ ፌስቲቫል አላቸው፡፡ እዚያ ተከብሮ ፍፃሜው ሁለቱም ተቀላቅለው ፌስቲቫሉን ባህርዳር ላይ በማሳየት ይጠናቀቃል፡፡
ዘንገና ላይ ሎጅ የሚገነቡትን ባለሀብቶች በተመለከተ ከነሱ ጋር ውይይት በማድረግ፣ ጥቅሙን በማስረዳት፣ ለሌሎች ኢንቨስትመንቶች የሚደረገው ማበረታቻና ድጋፍ ተደርጎላቸው፣ እንዲሰሩና እንደ ሌሎቹ ኢንቨስተሮች ከቀረጥ ነፃ የሚያስገቡትም ካለ እሱ ተፈቅዶላቸው፣ ስራውን እንዲያፋጥኑ አናደርጋለን። በዚህም ላይ ተወያይተናል፡፡ አካባቢው የሚያስፈልገውን መሰረት ልማት፡- ውሃ መፀደጃና ሌሎችንም ነገሮች ማሟላት ያስፈልጋል፡፡ ይሄ የተጀመረ ስለሆነ ይሰራል የሚል ጠንካራ እምነት አለን፡፡ ይሄ ይሄ ሲደረግ በአካባቢው ያሉ ዋሻዎች፣ ፏፏቴዎችና ሀይቆች አብረው የመጎብኘት እድልና የመታወቅ አጋጣሚ ስለሚኖራቸው ጠቀሜታቸው ብዙ ነው። በሌላ በኩል በ2010 በየአካባቢው አንድ አንድ የቱሪስት መዳረሻዎችን ማልማት እቅድ ተይዟል፡፡ እቅዱ ግን የመንግስት በጀት ላይ የተጣለ አይደለም። ባለሀብቶችንና የአካባቢውን ሰው በማሳመንና በማስረዳት፣ ህዝቡ ያለማዋል ተብሎ የተያዘ እቅድ ነው፡፡
ከአካባቢው ተወላጅ ባለሀብቶችና ከማህበረሰቡ ባለፈ በቱሪዝም መስፋፋት ላይ የሚሰሩ የውጭ አገር ተቋማትና መንግስታዊ ያልሆኑ ድርጅቶች ጋር ግንኙነቶችን በመመስረት፣ ሃብት በማፈላለግና የቱሪስት መዳረሻዎችን በማስፋፋት በኩል ክልሉ ምን ያህል ሰርቷል?
በዚህ በኩልም በግሌ ብዙ ተሰርቷል ብዬ አላምንም፡፡ እርግጥ ለዋና ዋና መዳረሻዎች በአብዛኛው ለምሳሌ ለፋሲል ግንብ፣ ለላሊበላ፣ ለጠና ባዮስፌርና ለመሳሰሉት በዩኔስኮም ስለተመዘገቡና የዓለም ሀብቶች ስለሆኑ ፕሮጀክቶች አሉ፡፡ ለአዳዲሶቹ ብዙ ስላልሰራን አላገኘንም፡፡ እንዳልሺው ቱሪዝምን ለማስፋፋት ትልቅ የሀብት ማፈላለግ ስራ መሰራት አለበት፡፡ ሀብት ማፈላለጉ ከውጭም ከውስጥም መሆን አለበት፤ የሚጠብቀን ትልቅ የቤት ስራም ይሄው ነው፡፡
እርስዎ በተሾሙበት ወቅት እንዳጋጣሚ ሆኖ በአገሪቱ ላይ ሰላምና መረጋጋት የጠፋበት አስቸጋሪ ጊዜ ነበር፡፡ ከሴትነት፣ ለስራው አዲስ ከመሆንና ከወቅቱ ሁኔታ  አንፃር ፈተናውን እንዴት ተወጡት?
እርግጥ ነው ወቅቱ ፈታኝ ነበር፡፡ ያስደነግጥም ነበር፡፡ የተፈጠረው አለመረጋጋት በክልል ተወስኖ የቀረ ሳይሆን አገራዊ ችግር ነበር ማለት ይቻላል። ዞሮ ዞሮ እንዳልሺው ሴትም ብሆን፣ ለስራው እንግዳም ብሆን ከአጋሮቼ ጋር ሆኜ ችግሩን ለመቋቋም፣ ሴትነቴም ለስራው አዲስ መሆኔም አላገደኝም። እርግጥ ነው ችግሩ ቱሪዝሙን ብቻ ሳይሆን አጠቃላይ ኢኮኖሚውንም ሁሉንም ያዛባል፡፡ ችግሩ እኛ የምንሰራው ዘርፍ ላይ የሚበረታ ቢሆንም። ዞሮ ዞሮ እኔ በግሌ የማመጣው ነገር ባይኖርም ሌላው ቀርቶ ችግሩ በአንድ ቢሮ ላይ የሚጣል ጉዳይም አልነበረም፡፡ ከክልሉ መንግስት ጀምሮ እስከ ነዋሪው ድረስ መሰራት አለበት፡፡ የሰላም ጉዳይ በመሆኑ የሰላሙም መልሶ መስፈን የእነዚህ ሁሉ ውጤት ነው፡፡ እኔም እንደ ቢሮም እንደ ግሌም ችግሩ ሲከሰት ማድረግ የምችለውን የአቅሜን የማድረግ ግዴታ አለብኝ፡፡ ስለዚህ ከሁሉም ጋር ተባብሬ የበኩሌን በማድረግ ችግሩን መቋቋም ችለናል፡፡ ችግሩ እኔ የምመራውን ቢሮ ለይቶ ችግር ላይ የሚጥል ስላልሆነ ማለቴ ነው፡፡
እዚህ ከተማ ላይ አንዳንድ ባለ ሆቴሎችን ተዘዋውረን እንዳነጋገርነው፣ በክልሉ አለመረጋጋት ከተከሰተ በኋላ በስራቸው ላይ ተፅዕኖ ማሳደሩን የእርስዎ ቢሮም ሆነ የክልሉ የሆቴሎች ማህበር መስራት ያለበትን ያህል ባለመስራቱ አካባቢው ከተፅዕኖው እንዳልተላቀቀ ገልጸልናል፡፡ ይሄ ምን ያህል እውነት ነው? የተከሰተው ችግር ሙሉ በሙሉ መጥፋቱንና አካባቢው ሰላም መሆኑን ለማስተዋወቅ ቢሮው ምን ምን ስራዎችን ሰርቷል?
ብዙ ባይሆንም ቢሮው የሚችለውን ያህል ሙከራ አድርጓል፡፡ አካባቢው ፍፁም ሰላም መሆኑን የሚያመላክቱ የተለያዩ ዝግጅቶችን አድርገናል። ለምሳሌ ከዚህ ክልልና ከተማ ውጭ ሆኖ ለሚያስብ ሰው፣ በከተማዋ የተለያዩ ጉባኤዎችና ትልልቅ እንቅስቃሴዎች ይደረጋሉ ቢባል ለማመን ይቸግራል። ሰው ከሌላ አካባቢ መጥቶ ስብሰባ የሚካሄድ፣ የተለያዩ ፌስቲቫሎች፣ ባዛሮችና ጉብኝቶች የሚካሄዱ አይመስለውም ግን ተካሄደዋል እየተካሄዱም ነው፡፡ የባህልና የሙዚቃ ፌስቲቫሎች ይካሄዳሉ፡፡
ተካሂደዋል ከተባሉት ጉብኝቶች፣ ጉባኤዎች እና ፌስቲቫሎች በምሳሌነት የሚጠቅሷቸው ካሉ ቢነግሩኝ?
እኛ እንግዲህ ባህርዳር ብቻ ሳይሆን ጎንደርም ውስጥ ትልልቅ ስብሰባዎች እንዲካሄዱ አድርገናል በተለይ ከፌዴራል አካባቢ የሚደረጉትን በነዚህ ከተሞች እንዲካሄዱ አድርገናል በኢፌድሪ ባህልና ቱሪዝም ሚኒስቴር በኩል የሚካሄዱት ከሚኒስትር እስከ ቢሮ ያሉ የቱሪዝም ስብሰባዎች ጎንደርና ባህርዳር እንዲከርሙ በማድረግ ሰላም መስፈኑን እንዲያረጋግጡ አድርገናል፡፡ ከዚ ውጭ ጥምቀትን ለማክበር ከጥምቀት ጋር የተያያዙ ስራዎች የሚሰሩ ማህበረሰቦችን በማወያያት ጥምቀት በድምቀት እንዲከበር አድርገናል እንዲህ እያለ ጎንደር ላይ ሌላውም ቀጠለ ማለት ነው፡፡
ባህርዳር ላይም የተለያዩ ትልልቅ ስብሰባዎችን አካሂደናል፡፡ ከዚያ እኛ የክልሉን የባህል ፌስቲቫል ለአንድ ሳምንት በድምቀት አካሂደናል ይሄ ሰላም መኖሩን ያረጋግጣል፡፡ የሚገርምሽ በዚህ ፌስቲቫል መዝጊያ ላይ ትልልቅ ደራሲያን ሀያሲዎች ገጣሚዎችና ጋዜጠኞችን የያዘ የጉብኝት ቡድን ሙሉ አለም አዳራሽ ተገኝቶ መዝጊያውን አድምቆት ነበር፡፡ አንደኛ ደራሲያን ማህበር ከደብረ ማርቆስ ጀምሮ በባህርዳር ጣናን በማቋረጥ እስከ ጎንደር ጉብኝት ሲያደርግ አካባቢው ሰላም መሆኑን ማሳያ ነው፡፡ እንደነገርሺኝ ከደራሲያን ማህበር ጋር አንቺም ነበርሽ፡፡ የሆቴል ማህበሩ ከቢሮው ጋር በመሆን የክልሉን ገፅታ ለመመለስ ብዙ እየሰራ ነው እንደውም ባዛሮችን ስናዘጋጅ ሌሎች ዝግጅቶችን ስንሰራና የገንዘብ እጥረት ሲገጥመን ሆቴል ማህበሩ ስፖንሰር እየሆነን አመቱን ሙሉ ከእኛ ጋር ሲለፉ ስለነበር እንቅስቃሴ አላደረገም የሚለው ላይ አልስማማም፡፡ ሌላው ቀርቶ በባህል ፌስቲቫሉ ሰው አይገባባቸውም ሲባል በመዝጊያው አዳራሹ ሞልቶ ሰው ቆሞ ሁሉ ዝግጅቱን ሲከታተል ነበር፡፡ በ2010 ዓ.ም መግቢያ የምግብ አውደርዕይ ኤግዚቢሽን ለአምስት ቀን ተካሄደ በነገራችን ላይ ይህንን ኤግዚቢሽን በዋናነት ያዘጋጀው የሆቴል ማህበሩ ከዘንባባ መልቲ ሚዲያ ጋር በመተባበር ነበር በድምቀት ነው የተጠናቀቀው፡፡ በርካታ የአዲስ አበባ ነጋዴዎችም ተሳትፈውበታል ይህንን ሰርተናል ሆኖም አሁንም የበለጠ መስራት እንደሚጠበቅብን አምናለሁ፡፡ በባዛሩ ላይ በላይነህ ክንዴ የተባሉ የሰከላ ወረዳ ተወላጅ ትልቅ ድጋፍ አድርገውልናል፡፡
ምንም እንኳን ሰላም ቢሰፍንም ቱሪስት ፍሰቱ እየተሻሸለ ቢመጣም ክልሉ ከተፅዕኖ እንዳልወጣ የሚናገሩ አሉ፡፡ ይህንን ጉዳይ የበለጠ ግልፅ ለማድረግ እንደ ጀርመን ፈረንሳይና መሰል የቱሪስት አመንጪ አገራት ኤምባሲዎች ጋር ቀርባችሁ በግልጽ የመነጋገር ጉዳይ ላይ ምን የተሰራ ነገር አለ?
በዚህ ጉዳይ ላይ አምናም የፌዴራል ባህልና ቱሪዝም ሚኒስቴር ከአሜሪካና ከጀመርን ኤምባሲዎች ጋር ውይይት አድርጓል፡፡ ከውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ጋር በመተባበር የተደረገ ውይይት አለ እኛም ወደ ክልላችን የሚመጡ ቱሪስቶች የሚታወቁ ስለሆነ ከነዚህ ኤምባሲዎች ጋር ደብዳቤ በመፃፍም ሆነ በአካል በመቅረብ ሰላም መሆኑን በማስረዳት አብረን እንድሰራ ጥያቄ አቅርበናል፡፡ አሁን መሻሻል አለ፡፡
በመጨረሻ ቀሪ የሚሉት ካለ?
ጥሩ ቆይታ አድርገናል ክልላችን ሰላም ነው መጥታችሁ ጎብኙ ስራ ስሩ እላለሁ፡፡ አለመረጋጋት በነበረበት ወቅት እንኳን እንድም ቱሪስት ላይ የደረሰ አደጋ የለም፡፡ አሁን ሙሉ በሙሉ ሰላም ነው ይህንን ግንዛቤ ውስጥ በማስገባት ክልሉ ያለውን ልዩ የተፈጥሮና ሰው ሰራሽ መስህቦች ጎብኙ እላለሁ አመሰግናሁ፡፡

 11 ወጣት ሴቶችን የገደለው ሜክሲኳዊ በ430 አመታት እስር ተቀጣ

      በዓለማችን በየቀኑ 20 ሺህ ልጃገረዶች የየአገራቱ የጋብቻ ህጎች ከሚፈቅዱት ውጭ ያለ ዕድሜያቸው በህገወጥ መንገድ ወደ ትዳር እንዲገቡ  እንደሚደረግ የአለም ባንክ እና ሴቭ ዘ ችልድረን ባወጡት አዲስ የጥናት ውጤት አስታወቁ፡፡ ተቋማቱ ባለፈው ረቡዕ ይፋ ባደረጉት በዚህ አለማቀፍ የጥናት ውጤት መሰረት፤ በመላው ዓለም በየዓመቱ 7.5 ሚሊዮን ያህል ልጃገረዶች  በተመሳሳይ መልኩ በህገወጥ መንገድ ወደ ትዳር እንዲገቡ ይደረጋሉ፡፡አገራት ልጃገረዶች ወደ ትዳር መግባት የሚችሉበትን የዕድሜ ገደብ ቢያስቀምጡም፣ በአንጻሩ በበርካታ አገራት ህጉ ተግባራዊ ሳይደረግ ልጃገረዶቹ በለጋ እድሜያቸው ወደ ትዳር እንዲገቡ እንደሚገደዱ በ112 የአለማችን አገራት ላይ የተሰራው ይሄው ጥናት አመልክቷል፡፡
ልጃገረዶች ያለዕድሜያቸው ወደ ትዳር እንዲገቡ ከሚደረጉባቸው አካባቢዎች መካከል ቀዳሚነቱን የሚይዙት የምዕራብና መካከለኛው አፍሪካ አገራት ናቸው ያለው ዘገባው፤ በማደግ ላይ ከሚገኙ አገራት ሶስት ልጃገረዶች አንዷ ከ18 አመት በታች ወደ ትዳር እንድትገባ ትደረጋለች ብሏል። በተለያዩ የአለማችን አገራት 100 ሚሊዮን ያህል ልጃገረዶች ያለእድሜያቸው እንዳይዳሩ የሚከለክል ህግ እንዳልተቀመጠላቸው በጥናቱ መረጋገጡንም ዘገባው አመልክቷል፡፡በተያያዘ ዜናም፣ ከአምስት አመታት በፊት ሲዩዳድ ጁአሬዝ በተባለው የሜክሲኮ ገጠራማ አካባቢ 11 ወጣት ሴቶችን በአደንዛዥ እጽ በማደንዘዝ
ወደ ወሲብ ንግድ ካስገባ በኋላ በጭካኔ ገድሏል የተባለው ሜክሲኳዊ፣ ባለፈው ሰኞ ፍርድ ቤት ቀርቦ፣ በ430 አመታት እስር መቀጣቱን ዘ ጋርዲያን ዘግቧል፡፡ግለሰቡ ድርጊቱን ከፈጸመ በኋላ የሴቶቹን አስከሬን በሸለቆ ውስጥ ጥሎት መገኘቱን ያስታወሰው ዘገባው፤ ጥቃቱን ያደረሰባቸው ሴቶች እስከ 15
አመት እድሜ ያላቸው እንደነበሩም አክሎ ገልጧል፡፡

ታዋቂው ፎርብስ መጽሔት በአጠቃላይ ዕድገትና በትርፋማነት አለምን ይመራሉ ያላቸውን የ2017 ቀዳሚ ኩባንያዎች ዝርዝር ባለፈው ማክሰኞ ይፋ ያደረገ ሲሆን፣ ዳማክ ፕሮፐርቲስ የተባለው የተባበሩት አረብ ኤሜሪትስ የሪልስቴት ኩባንያ የአንደኛነት ደረጃን ይዟል፡፡ፎርብስ የኩባንያዎችን የሽያጭ፣ የትርፍ፣ የሃብት መጠንና የገበያ ዋጋ መሰረት በማድረግ ለመጀመሪያ ጊዜ ይፋ ባደረገው በዚህ የቀዳሚ ባለዕድገት ኩባንያዎች ደረጀ ዝርዝር 1ኛ ደረጃን የያዘውና በ2016 የ1.9 ቢሊዮን ዶላር ገቢ ያገኘው ዳማክ ፕሮፐርቲስ፣ በመላው መካከለኛው ምስራቅ ሰፋፊየግንባታ ፕሮጀክቶችን እንደሚሰራ ተነግሯል።
መርሴድስ ቤንዝን ጨምሮ ከ50 በላይ የተለያዩ ውድ መኪኖችን በማከፋፈል የሚታወቀውና በ2016 28.03 ሚሊዮን መኪኖችን በመሸጥ ከፍተኛ ገቢ ያገኘው የቻይና ግዙፉ የመኪና አከፋፋይ፣ ቻይና ግራንድ አውቶሞቲቭ ሰርቪስስ፣ በፎርብስ ዝርዝር የ2ኛነት ደረጃን ይዟል፡፡በሪልስቴት ዘርፍ የተሰማሩት ግሪንላንድ ሆልዲንግስ እና ሜልኮ ኢንተርናሽናል የ3ኛ እና የ4ኛ ደረጃን ሲይዙ፣ ሸቀጣሸቀጦችን ለተጠቃሚዎች በማድረስ ዘርፍ የተሰማራው ኤስኤፍ ሆልዲንግስ የተባለ ኩባንያ በበኩሉ፣ 5ኛው የአለማችን ቀዳሚ የእድገት ገስጋሽ ኩባንያ ሆኗል፡፡ፎርብስ ከዚህ በተጨማሪም በዓመቱ እጅግ ከፍተኛ ከበሬታንና ታማኝነትን ያገኙ የዓለማችን ኩባንያዎች ደረጃ ይፋ ያደረገ ሲሆን፣ 351 ሺህ ሰራተኞችን ቀጥሮ የሚያሰራውና በ2016 ዓ.ም የ90 ቢሊዮን ዶላር ሽያጭ አስመዝግቦ፣ 6.4 ቢሊዮን ዶላር ያተረፈው  የጀርመኑ ሲመንስ ኩባንያ

ቀዳሚነቱን ይዟል፡፡
የፈረንሳዩ የጎማ አምራች ሚሼሊን ግሩፕ እና አልፋቤት ጎግል ከፍተኛ ተአማኒነትን በማግኘት ከዓለማችን ኩባንያዎች ሁለተኛና ሶስተኛ ደረጃን

መያዛቸውን የገለጸው ፎርብስ፤ የጃፓኑ ኒንቲዶ አራተኛ ደረጃ ላይ መቀመጡን ጠቁሟል፡፡

 የመከላከያ ሠራዊት ግጭቱን ሙሉ በሙሉ እንዲያስቆም ተጠየቀ

     ሰማያዊ ፓርቲ እና የመላ ኢትዮጵያዊያን አንድነት ድርጅት (መኢአድ)፤ በኦሮሚያና በሶማሌ ክልል አዋሳኝ አካባቢ የተፈጠረውን ግጭት፣ አጣሪ ኮሚቴ ልከው ማጣራታቸውን ያስታወቁ ሲሆን ግጭቱን ያባባሰው የአንድ ባለሀብት መገደል ነው ብለዋል፡፡ መንግስት በበኩሉ፤ በፓርቲዎቹ ሪፖርት ላይ አስተያየት መስጠት አልችልም ብሏል፡፡
ሁለቱ ፓርቲዎች የሁኔታውን አሳሳቢነት ከግምት ውስጥ በማስገባት፣ አጣሪ ኮሚቴ ወደ ግጭቱ አካባቢ ልከው ጉዳዩን  ማጣራታቸውን፣በዚህም ግጭቱ ወደ ከፋ ደረጃ እስኪሸጋገር ድረስ የፀጥታ ኃይሎች ጣልቃ ገብተው የማረጋጋት ስራ አለመስራታቸውን ማረጋገጣቸውንም ሰሞኑን ባቀረቡት ሪፖርት አስታውቀዋል፡፡
ግጭቱ ከመስከረም 2 ቀን 2010 ዓ.ም ጀምሮ በዋናነት የተባባሰበት ምክንያት በምስራቅ ሃረርጌ አወዳይ ከተማ፣አንድ የሶማሌ ተወላጅ ባለሀብት ላይ ግድያ ከተፈጸመ በኋላ መሆኑን የጠቆመው አጣሪ ኮሚቴው፤ ይህን ተከትሎ በከተማዋ በተነሳው ብጥብጥም፣በኦሮሞ ተወላጆች ላይ ቤታቸውን ማቃጠል፣ ንብረታቸውን መዝረፍና ግድያ መፈፀሙን ተረድቻለሁ ብሏል፡፡
በዚህ አላስፈላጊ ግጭት ከቤት ንብረታቸው የተፈናቀሉ ዜጎች፤ በቂ ምግብና አልባሳት፣ እንዲሁም  የመኝታ ፍራሽ እንደማያገኙ፣ በዚህም የተነሳ በባዶ መጋዘን በደረቅ ወለል ላይ እንደሚተኙ አጣሪ ኮሚቴው ማረጋገጡን የገለፁት ፓርቲዎቹ፤ በምግብና በንፁህ ውሃ እጥረት የተነሳ ህፃናት ለተቅማጥ በሽታ መዳረጋቸውንም ጠቁመዋል፡፡  
መንግስት ለደረሰው ሰብአዊ ውድመት ተጠያቂ መሆኑን በመግለጫቸው ያስታወቁት ፓርቲዎቹ፤ ጉዳት የደረሰባቸውን ወገኖች በይፋ ይቅርታ እንዲጠይቅ፣ለሞቱት ቤተሰቦች የሞራል ካሣ እንዲከፍልና ቤት ንብረታቸው ለወደመባቸው ወገኖች፣ በአፋጣኝ መቋቋሚያ ሰጥቶ፣ ወደተረጋጋ ኑሮአቸው እንዲመለሱ ጠይቀዋል፡፡
የመከላከያ ሠራዊትም ግጭቱን በአስተማማኝ ደረጃ እንዲያስቆም በመጠየቅ፣ ለወደፊትም ይህ ዓይነቱ የዜጎችን መብት የሚጥስ ድርጊት እንዳይደገም  ጥሪ አቅርበዋል - ፓርቲዎቹ፡፡
እያንዳንዱ ሀገር ወዳድ ኢትዮጵያዊና ዓለም አቀፍ ግብረሠናይ ድርጅቶች፣የተፈናቀሉ ወገኖቻችንን ለማቋቋም የበኩላቸው ድጋፍ እንዲያደርጉ ጥሪ እናቀርባለን ያሉት ፓርቲዎቹ፤ በእነሱ በኩልም ድጋፍ የሚጠይቁ ደብዳቤዎችን ለተመረጡ አካላት ለማሰራጨት እየተንቀሳቀሱ መሆኑን አስታውቀዋል፡፡ ለተጎጂዎች እርዳታ የሚሰባሰብበትን የባንክ ሂሳብ ቁጥርም በቅርቡ ይፋ እንደሚያደርጉ አመልክተዋል፡፡
ፓርቲዎቹ በግጭቱ ላይ አደረግነው ባሉት ማጣራት ላይ ተመስርተው ያወጡትን  ሪፖርት በተመለከተ ከአዲስ አድማስ አስተያየት የተጠየቁት የመንግስት ኮሚኒኬሽን ጉዳዮች ሃላፊ ዶ/ር ነገሪ ሌንጮ፤ “ሪፖርቱ ባልደረሰን ሁኔታ የመንግስትን አቋም ለመግለፅ እቸገራለሁ” ብለዋል፡፡
የኢትዮጵያ ሰብአዊ መብት ኮሚሽን በበኩሉ፤ የግጭቱን መንስኤና ጉዳት አስመልክቶ ያጠናቀረውን የምርመራ ሪፖርት በዚህ ወር ያቀርባል ተብሎ እንደሚጠበቅ መዘገባችን የሚታወስ ሲሆን የፌደራል መንግስቱም በዋናነት ይሄን ሪፖርት እየተጠባበቀ መሆኑን በተደጋጋሚ አስታውቋል፡፡

 “የክልሉን ህዝቦች አንድነት ለማበላሸት የተወጠነ ሴራ ነው”

      ሰሞኑን በኦሮሚያ የተለያዩ ከተሞች በተቀሰቀሰው ተቃውሞ  የ8 ሰዎች ህይወት መጥፋቱን የገለጸው የክልሉ መንግስት፤የተቃውሞ እንቅስቃሴው እየተጠናከረ የመጣውን የክልሉን ህዝቦች አንድነት ለማበላሸት የተወጠነ ሴራ ነው ብሏል፡፡   
ባለፈው ረቡዕ  በአምቦ፣ ወሊሶ፣ ሻሸመኔ፣ ዶዶላ፣ ሃረር - ጨለንቆና በኬ ከተሞች ተቃውሞ የተደረገ ሲሆን ከ20 ሺህ በላይ ህዝብ ተሳትፎበታል ሲሉ የአይን እማኞች በገለፁት የሻሸመኔው የተቃውሞ እንቅስቃሴ የ5 ሰዎች ህይወት ማለፉን የክልሉ መንግስት አስታውቋል፡፡  
በተጨማሪም በምዕራብ ሃረርጌ ዞን ቦኬ ወረዳ በተካሄደ ሰልፍ ላይም የ3 ሰዎች ህይወት ማለፉን የገለጸው  የክልሉ መንግስት፤ አጥፊዎችን ተከታትዬ ለህግ አቀርባለሁ ብሏል፡፡
ከትናንት በስቲያ ሐሙስ ደግሞ በወሊሶና በአምቦ ከተሞች ተቃውሞ አይሎ መስተዋሉን ምንጮች ጠቁመዋል፡፡ በተቃውሞ  ሰልፎቹ ላይ በስፋት ከተደመጡ መፈክሮች መካከልም፤ “አቶ ለማ መገርሳ ፕሬዚዳንታችን ነው፤ ከጎኑ እንቆማለን!”፣ “የታሰሩ የኦፌኮ አመራሮች ዶ/ር መረራ እና በቀለ ገርባ ይፈቱ”፣ “የወገኖቻችን መፈናቀል ይቁም!” የሚሉና የመንግስት ለውጥን የሚጠይቁ ይገኙበታል ብለዋል፤ ምንጮች፡፡
በአምቦ የተካሄዱት የተቃውሞ ሰልፎች ከዚህ ቀደም ከነበረው በተሳታፊ ብዛት የላቁ ናቸው የሚሉት ምንጮች፤ ወጣቶች ብቻ ሳይሆኑ መላው የከተማዋ ነዋሪዎች የተሳተፉበት ነው የሚመስለው ብለዋል፡፡
በሰሞኑ የኦሮሚያ ከተሞች የተቃውሞ እንቅስቃሴ ላይ ማብራሪያ የሰጡት የኦህዴድ ጽ/ቤት ኃላፊ እና የክልሉ ም/ፕሬዚዳንት ዶ/ር አብይ አህመድ፤ በአሁኑ ወቅት የክልሉ መንግስት እየሰራ ያለው ስራ በኦሮሞ ህዝብ ዘንድ ከፍተኛ ተቀባይነት እያገኘ እንዲሁም አንድነትን እያጠናከረ መምጣቱን ጠቁመው፣ “አፍራሽ ኃይሎች” ለኦሮሞ ህዝብ ጥቅም የቆሙ በማስመሰል፣ ወጣቱን በስሜት አነሳስተው፣ ሰላማዊ ሰልፍ በመጥራት የተጀመሩ ስራዎችን ለማክሸፍ እየተንቀሳቀሱ ነው ብለዋል፡፡ ህዝቡ የእነዚህን አካላት ጥሪ እንዳይቀበልም ዶ/ር አብይ ጠይቀዋል፡፡
የተቃውሞ እንቅስቃሴዊቹ በተደረጉበት ወቅት የኦሮሚያ ፖሊስ አባላት ያለጦር መሳሪያ ህዝቡን ወደየቤቱ እንዲመለስ ሲመክሩና ሲያግባቡ መታየታቸውን ጉዳዩን አስመልክቶ ለቪኦኤ መረጃ የሰጡ የአይን እማኞች አስረድተዋል፡፡
በሻሸመኔ እና በበኬ ከደረሰው የሞት አደጋ በስተቀር በሌሎቹ ከተሞች የተደረጉ የተቃውሞ ሰልፎች በሰላም መጠናቀቃቸውን የየአካባው ምንጮች አስታውቀዋል፡፡