Administrator

Administrator

 የአፍሪካ መንግስታት፣ ሽብርተኝነትንና ጽንፈኝነትን ለመዋጋት በማሰብ የሚፈጽሟቸው ድርጊቶችና የሚወስዷቸው እርምጃዎች፣ በተቃራኒው ዜጎችን ወደ ጽንፈኝነት ገፍተው እያስገቡ እንደሆነ የተባበሩት መንግስታት ድርጅት ከትናንት በስቲያ ይፋ ባደረገውና ሶስት አመታትን በፈጀው የጥናት ሪፖርት አስታውቋል፡፡
ተመድ ይፋ ያደረገው የጥናት ውጤት እንደሚለው፣በአፍሪካ ውስጥ የሚገኙ በመቶዎች የሚቆጠሩ የጽንፈኛ ቡድኖች አባላት፣ የጽንፈኛ ቡድኖችን አስተሳሰብ በመደገፍ አባል ለመሆን የወሰኑት፣ የየአገሮቻቸው መንግስታት በሚወስዷቸው የጸረ ሽብርተኝነትና ጽንፈኝነት እርምጃዎች ተገፋፍተው እንደሆነ ተናግረዋል፡፡
የአፍሪካ መንግስታት ቦኮ ሃራምንና አልሻባብን የመሳሰሉ ጽንፈኛና አሸባሪ ቡድኖችን ለመደምሰስ የሚያደርጉት ትግል፣ የአገራቱን ዜጎችና ቤተሰቦቻቸውን ተጎጂ የሚያደርጉባቸው አጋጣሚዎች በርካታ እንደሆኑ የዘገበው ዘ ጋርዲያን፤ ይህም ዜጎችን ወደ ጽንፈኝነት በመግፋት ያልተፈለገ፣ አሉታዊ ተጽዕኖ እየፈጠረ እንደሚገኝ አመልክቷል፡፡
የጽንፈኛ ቡድኖች አባላት ከነበሩና በጥናቱ ከተካተቱ 500 በላይ አፍሪካውያን መካከል 71 በመቶ የሚሆኑት፣ የአገራቸው መንግስት ጽንፈኝነትን ለመዋጋት በወሰዳቸው እርምጃዎች፣ ቤተሰቦቻቸው ወይም ጓደኞቻቸው መገደላቸው፣ መታሰራቸው አልያም የሌሎች በደሎች ሰለባ መሆናቸው፣ የቡድኖቹ አባል ለመሆን ዋነኛ ምክንያት መሆኑን መወሰናቸውን ተናግረዋል፡፡
በአፍሪካ ባለፉት ስድስት አመታት ብቻ ጽንፈኛ ቡድኖች በፈጸሟቸው የሽብር ጥቃቶችና የጥፋት እርምጃዎች ከ33 ሺህ በላይ የአህጉሪቱ ዜጎች ለህልፈተ ህይወት መዳረጋቸውን ያስታወሰው ዘገባው፣ ጽንፈኝነት በሚሊዮኖች የሚቆጠሩ አፍሪካውያንን ለመፈናቀልና ለሰብዓዊ ቀውስ መዳረጉንም አስረድቷል፡፡
አፍሪካውያንን ወደ ጽንፈኝነት እንዲገቡ ይገፋፋሉ ተብለው በጥናቱ ከተለዩት ሌሎች በርካታ ምክንያቶች መካከልም፣ ፍትሃዊ ያልሆነ የሃብት ክፍፍል እንዲሁም የትምህርትና የስራ ዕድል ዕጦት እንደሚገኙበትም ዘ ጋርዲያን በዘገባው ጠቁሟል፡፡

   በዘንድሮ የአዲስ ዓመት ዋዜማ፣ በመዲናዋ የትኞቹ ሆቴሎች፣ ቴአትር ቤቶች፣ የምሽት ክለቦች … የሙዚቃ ድግሶችና  የአውዳመት የመዝናኛ ፕሮግራሞች ተዘጋጅተዋል? ጋዜጠኛ ናፍቆት ዮሴፍ እንዲህ ቃኝታቸዋለች፡፡

                 
                   “እንቁጣጣሽ ክላሲክ ኮንሰርት” - በካፒታል ሆቴል

     ባለአምስት ኮከቡ ካፒታል ሆቴል፤ በአዲሱ አመት ዋዜማ ከምሽቱ 12፡00 ጅምሮ “እንቁጣጣሽ ክላሲክ ኮንሰርት” የሚል ስያሜ የተሰጠው የሙዚቃ ድግስ አሰናድቷል፡፡ በዚህ ድግስ ተወዳጆቹ ድምፃውያን ሳሚ ዳን፣ ሚካኤል ለማ ደምሰው፣ ፀደንያ ገ/ማርቆስ፣ የባላገሩ አይዶል አሸናፊ ዳዊት ፅጌ፣ አስገኘሁ አሸኮ (አስጌ ዴንዳሾ) ታዳሚውን በዘፈኖቻቸው የሚያዝናኑ ሲሆን ዲጄ ዊሽና ዲጄ ጆ ዋዜማውን በምርጥ ሙዚቃዎች ያደምቁታል ተብሏል፡፡
በሙዚቃ ድግሱ ላይ ለሚታደሙ ከእራት በፊት ለአንድ ሰው 699 ብር፣ እራትን ጨምሮ 1199 ብር፣ ለጥንዶች ያለ እራት 1199 ብር፣ እራትን ጨምሮ 1999 ብር የሚያስከፍል ሲሆን ዝግጅቱ እስከ ሌሊቱ 8፡00 ድረስ እንደሚዘልቅ የሆቴሉ ማርኬቲንግ ሃላፊ፣ ወ/ሪት ተወዳጅ አሰፋ ለአደስ አድማስ ገልፀዋል፡፡


-----------------

                    ልዩ የእራት ፓርቲ-በኢሊሊ ሆቴል

      ባለ አምስት ኮከቡ ኢሊሊ ኢንተርናሽናል ሆቴል ደግሞ በዘመን መለወጫ ዋዜማ ምሽት ልዩ የእራትና የሙዚቃ ድግስ አዘጋጅቷል፡፡ በዚህ ምሽት ኦሮምኛን ጨምሮ የተለያዩ የብሄር ብሄረሰቦች ሙዚቃና ባህላዊ ጭፈራ የሚቀርብ ሲሆን ስታንዳፕ ኮሚዲ፣ የባንድ ሙዚቃና ሌሎችም ዝግጅቶች ተሰናድተዋል ተብሏል፡፡ ጳጉሜ 5 ከምሽቱ 1፡00 ሰዓት ጀምሮ የሆቴሉ በሮች ለታዳሚያን ክፍት ሲሆኑ የመግቢያ ዋጋው እራትን ጨምሮ (ውስኪ መጠጦችን ለሚጠቀሙ) 1500 ብር፣ ከእራት ጋር የወይን መጠጦችን ለሚወስዱ 1 ሺህ ብር መሆኑ ተገልጿል፡፡ ሆቴሉ ከዚህ በተጨማሪም የሞሀ ለስላሳ መጠጦችን፣ ጊዮርጊስ ቢራና አኳ አዲስ ውሃን በነፃ ያቀርባል፡፡ አምራቾቹ ለበዓሉ ስፖንሰር ማድረገቸውን በመግለፅ፡፡  የመዝናኛ ድግሱ እስከ እኩለ ሌሊት እንደሚቀጥል የሆቴሉ የህዝብ ግንኙነትና ማህበራዊ ሚዲያ ሃላፊ አቶ ታሪኩ ዋሲሁን ለአዲስ አድማስ ገልፀዋል፡፡  

-----------------

                     ሀሴት አኩስፒክ ባንድ ከአዝማሪዎች ጋር በጎልደን ቱሊፕ ሆቴል

      ቦሌ ኤድናሞል ጀርባ የሚገኘው ባለ አራት ኮከቡ ጎልደን ቱሊፕ ሆቴል በበኩሉ፤ አኩስቲክ ባንድን ከአዝማሪዎች ጋር በማጣመር ዓለም አቀፍና ባህላዊ ሙዚቃን ለማቅረብ በምሽቱ ከሀሴት አኩስቲክ ባንድ ሚኪያስ ፍሬው፣ አይዳ ሰለሞንና ሌሎችም የሚሳተፉ ሲሆን ከአዝማሪዎች ቱፓክ በሚል ቅፅል ስሙ የሚታወቀው አዝማሪ ናርዶስ ከተሰኘች አዝማሪ ጋር ስራውን እንደሚያቀርብ ታውቋል፡፡
በዕለቱ በባህል ዘፈን ላይ ከፍተኛ አስተዋፅኦ ላበረከቱ ሁለት ዘፋኞች ሆቴሉ እውቅና እንደሚሰጥም ተነግሯል፡፡ በዚህ ምሽት ላይ ለመታደም ለአንድ ሰው እራትን ጨምሮ 699 ብር ሲሆን ለጥንዶች እራትን ጨምሮ 1299 ብር እንደሚያስከፍል የሆቴሉ ማርኬቲንግ ኃላፊ መርሀዊት ፀጋዬ ገልፀዋል፡፡

------------------

                         የጥበብ ድግስ - በብሔራዊ ቴአትር

      አንጋፋው ብሔራዊ ቴአትር አዲሱን አመት ምክንያት በማድረግ ለአንድ ወር የሚዘልቅ የጥበብ ድግስ እንደሚያቀርብ አስታውቋል፡፡ ከዛሬ ጀምሮ እስከ መስከረም 28 ቀን 2010 ዓ.ም በሚዘልቀው የጥበብ ድግስ፤ ከመደበኛው ሙዚቃና ልዩ ልዩ የኪነጥበባት ዝግጅት በተጨማሪ የአረጋዊያን የፋሽን ትርኢት፣ የአርበኞች ልዩ ዝግጅት፣ የአንጋፋው አርቲስት ጥላሁን ገሰሰ የመታሰቢያ ፕሮግራም የ”ሚስ ናሽናል ቴአትር” የቁንጅና ውድድርና ሌሎችም የመዝናኛ ፕሮግራሞች እንደሚቀርቡ ብሔራዊ ቴአትር አስታውቋል፡፡

 ጉዳዩ፡- ሚሊኒየም አዳራሽ ፈርሶ፣ ባለ 5 ኮከብ ኮንቬንሽን ሴንተር


      ክቡርነትዎ፤ ይህችን አነስተኛ ማስታወሻ የጻፍኩት፣ እንደ አንድ የአገር ተቆርቋሪ፣ የአዲስ አበባ ነዋሪነቴ ነው። እንደሚታወቀው፤ የኢትዮጵያ ሚሊኒየምን ለማክበር በታቀደ ጊዜ፣ በወቅቱ  ሰፊ አዳራሽ ባለመኖሩ፣ ሼክ መሐመድ ሁሴን አላሙዲን፣ አዳራሹን ለመስራት ቃል ገቡ፡፡ ይሄን ተከትሎም ለመሥሪያ የሚሆን ቦታ (ካልተሳሳትኩ፣ከሊዝ ነፃ የሆነ) ቦሌ ዓለም አቀፍ አውሮፕላን ማረፊያ መግቢያ ላይ ተረክበው፣ አዳራሹ በፍጥነት ተሰራ፡፡ ለታለመለት ተግባርም ዋለ፡፡ ሚሊኒየሙ፣ በዘፈንና በጭፈራ በደመቀ ሁኔታ ተከበረ፡፡ ሼክ መሐመድ ሁሴን አላሙዲን፣ ቦታውን ሲረከቡ ግን፣ ይህ በጥድፊያ የተሰራ ኮንቴነር አዳራሽ ፈርሶ፣ በምትኩ በአውሮፓ ስታንዳርድ፣ ዘመናዊ አዳራሽ እንደሚገነቡ ቃል መግባታቸውን  አስታውሳለሁ፡፡
 እነሆ፤ ኢትዮጵያ ሚሊኒየሙን ካከበረች ድፍን አስር አመታት አስቆጥራለች፡፡ የዛሬ 10 ዓመት ለጊዜው ተብሎ የተሰራው ሚሊኒየም አዳራሽ፣አሁንም ባለበት ነው። የተባለው ደረጃውን የጠበቀ አዳራሽ ይሄን ሁሉ ዓመት አልተገነባም፡፡ በእኔ እምነት ሼክ መሀመድ፣ይሄንን አዳራሽ አፍርሰው፣ ባለ አምስት ኮኮብ የሆነ ዓለም አቀፍ ደረጃው የጠበቀ አስደናቂ አዳራሽ ማስገንባት  አያቅታቸውም። ከተማችን አዲስ አበባ፣ የአፍሪካ ዋና ከተማ መሆኑዋ ይታወቃል፡፡ ዓለም አቀፍ ስብሰባዎች ለማካሄድ የምትመረጥ ከተማም እየሆነች መጥታለች። በዚህም የተነሳ ደረጃውን የጠበቀ ዘመናዊ  አዳራሽ እንደሚያስፈልጋት እሙን ነው፡፡
ክቡር ከንቲባ፡-
ሚሊኒየም አዳራሽ ላለፉት 10 ዓመታት በርካታ የሙዚቃ ድግሶችንና ኤግዚቢሽኖችን እያስከፈለ ሲያስተናግድ ቆይቷል፡፡ ከዚህ አንጻር አሁን ዓለም አቀፍ ደረጃውን የጠበቀ ዘመናዊ አዳራሽ ለመስራት የሚያስችል አቅም እንደገነባ መገመት ይቻላል፡፡ እንደ ነጋዴ፣ እንዲህ ከፍተኛ ገቢን የሚያስገባ አዳራሽ ማፍረስ ሊያጓጓ ይችላል፡፡ ነገር ግን ቃል በተገባው መሠረት፣ ስታንዳርዱን የጠበቀ አዳራሽ መገንባት እንዳለበት አምናለሁ፡፡ ይሄንን የማስፈጸም ሃላፊነት ደግሞ የከተማ መስተዳድሩ እንደሆነ ይታወቃል፡፡
ከውጪ ወደ ኢትዮጵያ የሚገቡ ታላላቅ የሀገር መሪዎችና ጎብኚዎች፣ መጀመሪያ የሚመለከቱት ቦታ ላይ ተገትሮ የሚገኘው ቅርፅ የለሽ ኮንቴነርና ድንኳኖች ፈርሰው ፣አዲስ አበባ የአፍሪካን መዲናነቷን የሚመጥናት፣ ባለ አምስት ኮከብ Convention Center መገንባት አስፈላጊ ነው፡፡ በዚህ አጋጣሚ አገር ወዳድ ለሆኑትና ለኢትዮጵያ በርካታ ጥሩ ነገሮች ላበረከቱት ባለሀብት ሼክ መሀመድ፣ ያለኝን አክብሮት ለመግለፅ እወዳለሁ፡፡  ነገር ግን ለጊዜያዊ ችግር ታስቦ የተሰራው 10 ዓመታት ያስቆጠረው ሚሊኒየም አዳራሽ፣ በአዲስ ደረጃውን የጠበቀ አዳራሽ መተካት ያለበት ይመስለኛል። መስተዳደሩም ሃላፊነቱን በአፋጣኝ መወጣት ይገባዋል ብዬ አስባለሁ፡፡  
 በላይ ጨብሲ /ልማታዊ ሀብት/
This email address is being protected from spambots. You need JavaScript enabled to view it.    

   “ለሀገር አንድነት፣ ሠላም፣ እድገት … ተግተን መስራት አለብን” - ዶ/ር ነገሪ ሌንጮየመንግሥት ኮሚኒኬሽን ጉዳዮች ፅ/ኃላፊ ሚኒስትር

        መንግስት ያለፈውን ዓመት እንዴት አሳለፈ? ሊጋፈጣቸው ያልቻላቸው ተግዳሮቶች ምን ነበሩ? ስህተቶቹንና ጉድለቶቹን ያውቃቸዋል? ካወቃቸው … ለማረም ምን አደረገ? የአዲሱ ዓመት ፈተናዎችና ተስፋዎች ምንድን ናቸው ይላል? የመንግስት ኮሚኒኬሽን ጉዳዮች ፅ/ቤት ኃላፊ ሚኒስትር ዶ/ር ነገሪ ሌንጮ በ2010 ዋዜማ ላይ ለአዲስ አድማስ ጋዜጠኛ አለማየሁ አንበሴ የገለፁትን እነሆ፡-
ያለፈው አመት በመንግሥት በኩል ምን ተከናወነ? እንዴትስ አለፈ? ምንስ ተግዳሮት ገጠመው?
በአንድ ዓመት ውስጥ የተከናወኑ ስኬቶችና ተግዳሮቶችን በተወሰኑ ደቂቃዎች ውስጥ በዝርዝር ለመግለፅ ያስቸግራል፤ ነገር ግን በተወሰነ ደረጃ አንዳንድ ጉዳዮችን ማንሳት ይቻላል፡፡ በ2008 ዓ.ም በተለይ በኦሮሚያ፣ አማራና ደቡብ ክልል አንድ ዞን ላይ በተከሰቱ ችግሮች ምክንያት አዳዲስ አሰራሮችን የተከተልንበት ጊዜ ነው - 2009 ዓ.ም፡፡ የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁም የነበረበት ዓመት ነው፡፡ በአጠቃላይ ግን ሀገርን ለማሳደግ፤ በኢኮኖሚ፣ በማህራዊ መስክ ሀገሪቱን ወደፊት ለመውሰድ የታቀዱት ስራዎች፣ በታቀደላቸው እየሄዱ እንደሆነ ነው፤ ግምገማው የሚያሳየው፡፡ ውጤትም ተገኝቶባቸዋል፡፡ ይሄ ውጤት የመጣው ግን እንዲሁ አልጋ በአልጋ በሆነ ሁኔታ አይደለም፡፡ ብዙ ተግዳሮቶች የታለፈበት ነው፡፡ ይሄም ሆኖ በዓመቱ መንግስት ትላልቅ አላማዎችን አስቀምጦ፣ ከህዝቡ ጋር በመተባበር አከናውኗል፡፡ በተለይ የሠላም ጉዳይ ለህዝባችን ወሳኝ ነው፡፡ የኢትዮጵያ መንግስት በ2008 አካባቢ የነበሩ የሰላም ችግሮችን በመቅረፍ ረገድ ከህዝቡ ጋር በመተባበር፣ ትልቅ ውጤት የተገኘበት አመት ነበር ማለት ይቻላል፡፡ መንግስት የያዛቸው እቅዶችም ነበሩ፡፡ ዓመቱ ተግዳሮቶችን በመቋቋም፣ ውጤት የተገኘባቸው ጊዜ ነበር፡፡ ይህም የሆነው በህዝብ ትብብርና በመንግስት መሪነት ነው፡፡ በኢኮኖሚው ትልቅ ውጤት ተገኝቷል፡፡
በተለይ በ2009 መሪው ፓርቲ ራሱን የፈተሸበት ዓመት ነው፡፡ እንደገና ደግሞ በመንግስት ደረጃ ያሉትን ችግሮች በመዳሰስ፣ አስፈላጊ የሆኑ እርምጃዎችን ወስዷል፡፡ በሺዎች የሚቆጠሩ የፓርቲው አባላትና አመራር ላይ እርምጃ በመውሰድ፣ የአቅም ግንባታን በመስራት፣ የአመለካከት ቀረፃ ላይ በሚፈለገው ደረጃ የህዝብ አገልጋይነት መንፈስ እንዲሰፍን፣ መሪው ፓርቲ ትልቅ ስራ ሰርቷል፡፡ በፌደራልና በክልል ደረጃ ትልልቅ ለውጦች የተካሄዱበት ዓመት ነው ማለት ይቻላል፡፡ ከካቢኔ ለውጥ ጀምሮ በርካታ ትልልቅ ለውጦች ተደርገዋል፡፡
የተለያዩ የመንግስት ባለስልጣናት እንደ ጥፋታቸው መጠን፣ ከኃላፊነታቸውና ከፓርቲው እንዲባረሩ የተደረገበት ሁኔታ አለ፡፡ በዚህ ጉዳይ ሚዲያው ምን ያህል ትኩረት ሰጥቶ፣ ለህዝቡ አሳውቋል የሚለው ነው ጥያቄው እንጂ በ2009 መንግስት ትልልቅ ስራዎችን የሰራበት አመት ነው ማለት እንችላን፡፡ ለምሳሌ ጊዜያቸው ተጓትቶ የነበሩ ሜጋ ፕሮጀክቶች በፍጥነት እንዲጠናቀቁ የተደረገበት አመትም ነበር፡፡ የኢንዱስትሪ ፓርኮችም ተመርቀው አገልግሎት መስጠት ጀምረዋል፡፡ ሌሎችም የኢንዱስትሪ ፓርኮች ግንባታ ተጀምሯል፡፡
ከሰላምና መረጋጋት ጋር በተያያዘም ትልቅ ስራ ተሰርቷል፡፡ በዚህ መሃል ግን በአንዳንድ ክልሎች የወሰን ግጭቶች ነበሩ፡፡ ለምሳሌ በኦሮሚያና በኢትዮጵያ ሶማሌ ክልል፣ በጋምቤላና በኦሮሚያ፣ በቤንሻንጉልና በኦሮሚያ፣ በአፋርና በትግራይ፣ በአማራ፣ በደቡብ አጎራባች ክልሎች … ህዝብን ያጋጩ የነበሩ የድንበር ችግሮችን ለመፍታት፣ በትጋት ተሰርቷል፡፡
በሌላ በኩል ገዥው ፓርቲና ተፎካካሪ ፓርቲዎች የሚያደርጉት ድርድር አለ፡፡ የሲቪክና የዲሞክራሲ ተቋማት እንዲበረታቱ የተደረገበት ሁኔታም አለ። የሚዲያ ተቋማት፣ ዲሞክራሲና የመልካም አስተዳደር ጉዳዮች ላይ ያተኮረ መድረኮችን እንዲያዘጋጁ፣ ፖለቲካ ፓርቲዎችን እንዲያሳትፉ … ጥረት ተደርጓል፡፡ በሚዲያው ረገድ አጠቃላይ ሪፎርም ለማከናወን እየተሰራ ነው ያለው፡፡
ከጎረቤት ሀገራት ጋር ያለን ግንኙነት የተሻሻለበት ሁኔታ አለ፡፡ ከአባይ ተፋሰስ ሀገራት ጋርም ትልቅ ዲፕሎማሲያዊ ድሎች ተገኝተዋል። ከሩቅ ሆነው ሀገሪቷን ለማተራመስ የሚሞክሩ፣ በተለይ በአሜሪካ፣ በአውሮፓ ሆነው፣ የሀገሪቷ ጉዳይ ያገባናል የሚሉ ነገር ግን ከልማቷ ወደ ኋላ ለማስቀረትና ጫና ለማድረግ የሚያስቡ አካላት አላማቸው እንዳይሳካ የተደረገበት አመት ነበር፡፡ በዚህም ትልቅ ድል ተገኝቷል፡፡
ድርቅ አንደኛው ተግዳሮት ነው፡፡ ከድርቅ ጋር በተያያዘ በሚሊዮን የሚቆጠሩ ዜጎቻችን ለጎዳበት ተዳርገዋል፡፡ እነሱን ለመታደግ መንግስትና ህዝብ በጋራ ተረባርቧል፡፡ በሚገርም ሁኔታም አንድ ክልል እህል፣ ግጦሽና ውሃ እየጫነ፣ ለሌላው የሚያደርስበት መተሳሰብና መተጋገዝ የታየበት ሁኔታም ነበር። መንግስት ጉዳት እንዳይደርስ ከፍተኛ ርብርብ አድርጓል፡፡
ሌላው ተግዳሮት፣ በ2008 መገባደጃ እና በ2009 መጀመሪያ አካባቢ የነበረው ያለመረጋጋት ነው፡፡ ያ የሰላምና መረጋጋት ችግር ባይኖር ኖሮ፣ በሙሉ አቅም በልማት ላይ መስራት ይቻል ነበር። የመልካም አስተዳደር ችግርም ቀላል ተግዳሮት አይደለም፡፡ ጊዜ የፈጀ ጉዳይ ነበር፡፡ የተፈጥሮ አደጋዎችም ነበሩ፡፡
መንግስት አዲሱን ዓመት ከወትሮው በእጅጉ በተለየ መልክ ለመቀበል ምን አሳሰበው?
በሚሊኒየሙ መግቢያ፣ መሪዎቻችን ኢትዮጵያን ወደ ሚፈለገው ስልጣኔ ለመምራት “መጪው የኢትዮጵያ ህዳሴ ነው” ብለው ከህዝቡ ጋር ቃል የገቡበት ነበር፡፡ ባሳለፍነው 10 ዓመት ውስጥ ያገኘናቸው ስኬቶች ምንድን ናቸው? ጉድለቶቻችንስ? ብለን የምናስብበት ነው፡፡ መጪው አስር ዓመት ደግሞ በቀላሉ የሚታይ አይደለም፡፡ በ2017 መካከለኛ ገቢ ካላቸው ሀገራት ተርታ ለመሰለፍ በጥንካሬ እየተሰራ ነው፡፡ ስለዚህ ዜጎቻችን ይሄን አላማ ማወቅ አለባቸው፡፡ ለአላማው ስኬት መነቃቃት አለባቸው፡፡ የሀገር ፍቅር ስሜታችን መነሳሳት አለበት፡፡ ኢትዮጵያን እንደ ሀገር ለማስቀጠልና በዓለም ደረጃም የምንፈልጋት ሀገር ለማድረግ የምናስታውሳቸው እሴቶቻችን ስላሉ ነው፣ ቀናቶችን ሰይሞ መዘከር ያስፈለገው። ለሠላም፣ ለሀገር አንድነት፣ ለሀገር ፍቅር፣ ለአረጋውያን፣ ለመሪዎቻችን፣ ለታዳጊዎች ያሉን እሴቶች አሉ፡፡ 2010ን በመነቃቃት የምንቀበል ከሆነ፣ ሁሉም በየፊናው፣ በንቃት ተሳትፎ፣ ለውጥ የምናመጣበት ይሆናል፡፡
የመንግስት የአዲስ ዓመት ተስፋዎች ምንድናቸው?
በሚቀጥለው ዓመት በመንግስት በኩል የተያዙ ትላልቅ የልማት እቅዶች አሉ፡፡ በዋናነት ህዝባችንን ማብቃት ነው የሚያስፈልገው፡፡ የህዝብ ተሳትፎ በላቀ ደረጃ እንዲያድግ፣ መንግስት በቁርጠኝነት ይንቀሳቀሳል፡፡ ቁርጠኝነቱ ከጊዜ ወደ ጊዜ እየጨመረ ነው፡፡ የተሻለ ውጤት ለማስመዝገብ፣ እያንዳንዱ ዜጋ፣ የተሻለ አመራርና ተስፋ እንዳለ ማየት አለበት። ለያዝነው የእድገት እቅድም ሁኔታዎች የተሻሉ እንደሆነ መገንዘብ ያስፈልጋል፡፡ መንግስት ህዝቡን ለማዳመጥና ለማገልገል ያለው ቁርጠኝነት በጣም ተስፋ ሰጪ ነው፡፡ ኃላፊነቱን፤ ተጠያቂነት ባለው መልኩ ለመወጣት፣ እየሰራ ያለው ስራ፣ ተስፋ ሰጪ በመሆኑ ሁላችንም የተሻለ መልካም ውጤት የምናስመዘግብበት ዓመት ይሆናል፡፡
አዲሱ ዓመት የተሻለ፣ ብሩህ ዘመን እንደሚሆን በማወቅ መቀበል አለብን፡፡ ሀገራችንን የተሻለች የምናደርገው እኛው ነንና፣ በውጪም ሆነ በሀገር ውስጥ የምንኖር ሁሉ፣ ከምንም በላይ ለሀገር አንድነት፣ ለሀገር ሰላም፣ ለሀገር እድገት … ተግተን መስራት አለብን፡፡ በተረፈ መልካም አዲስ ዓመት ይሁንልን!!

    አመልካች እኔ ሳምሶን ጌታቸው ተክለሥላሴ, በሀገረ ኢትዮጵያ የዋና ከተማዋ አዲስ አበባ ነዋሪ ስሆን፤ ሰሞኑን በሀገሬ ላይ በተከሰቱ አንዳንድ አስፈሪ የፖለቲካ ጉዳዮች የተነሳ, ይህንን የአቤቱታ ደብዳቤ ለመጻፍ ተገድጃለሁ፡፡ ይህን አቤቱታ በዚህ መልክ ከመጻፌ በፊት ነገሮች በራሳቸው ጊዜ ወይም በሆኑ የሀገራችን ሰዎች አማካይነት ይስተካከሉ ይሆናልም ብዬ ተስፋ አድርጌ ነበር፡፡ እያንዳንዱ ሰው እየተነሳም በትላልቅ የሀገር ጉዳዮች በዚህ መልኩ አቤቱታ ላሰማ ካለም ለአሰራርም ሆነ ለውጤታማነቱ አስቸጋሪ እንደሆነም ስለማውቅ እና በሌሎች ተያያዥ ምክንያቶች በግሌ ለብዙ ጊዜያት ዝም ማለትን መርጬ ነበር፡፡ ነገር ግን የነገሮች አደገኛ ጎርፍ፣ ሀገሬንና ሕዝቦቿን ባለንበት ጠራርጎ ሊወስደን እየተንደረደረ መሆኑን ስመለከት፤ ቢያንስ የአቅሜን ማበርከት አለብኝ ብዬ በመወሰኔና በዚያም መንፈስ ሆኜ ይኼንን ደብዳቤ ልጽፍ ወደድሁ፡፡
በመጀመሪያ ከሁሉ አስቀድሜ ለዘመናት የሀገሬ ኢትዮጵያ የልብ ወዳጅ፣ የችግሯ ጊዜ ሁሉ ፈጥኖ ደራሽ፣ የዕድገቷና የሥልጣኔዋ ጉዞ ፍፁም አጋዥ እና ደጋፊ ለሆነችው፣ የዓለም ኃያሏ ሀገር ዩናይትድ ስቴትስ ኦቭ አሜሪካ ሕዝብ እና መንግሥት የከበረ ሠላምታዬን በታላቅ ትህትና አቀርባለሁ፡፡ በዚሁ የተለየ አጋጣሚ ሀገሬ እና ሕዝቦቿ ወደ ሥልጣኔ በሚያደርጉት እርምጃ እና ጉዞ ሁሉ ከአሜሪካ ሕዝብ እና መንግሥት ለተደረገልንና እየተደረገለን ስለሚገኘው ውለታ፣ እንዲሁም ይህንኑ ከቅንነት፣ ከርኅራኄ እና ከፍቅር የመነጨ ድጋፍ ባለኝ የዜግነት ድርሻዬ በሀገሬ ስም ከልብ የመነጨ ምሥጋናዬን ላቀርብ እወዳለሁ፡፡ 
በመቀጠልም ሀገሬ ኢትዮጵያ በአሁኑ ሠዓት አንገት ለአንገት እየተናነቀች ከምትገኘው የከፋ ድህነት እና ኋላቀርነት ባሻገር፣ በቀላሉ የማይታይ የፖለቲካ ችግርም እየተስተዋለባት እንደሚገኝ በአደባባይ የዋለ ሀቅ ከሆነ ከራርሟል፡፡ የፖለቲካ ችግሯ በተለያየ ደረጃና መንገድ ተጉዞ አሁን የደረሰበት አደገኛ ደረጃ ላይ መገኘቱ፣ ከወዳጃችን የአሜሪካ መንግሥት የተደበቀና ድንገተኛ ክስተት እንዳልሆነም ይታወቃል፡፡ ይህንንም ስል የአሜሪካ መንግሥት በተለያዩ ጊዜያት የሚስተዋሉ መሠረታዊ የአስተዳደርና የአካሄድ ችግሮችን፣ በዚህ ደረጃ ሥር ሳይሰዱ መስተካከል ይችሉ ዘንድ በተለያዩ መንገዶች የወዳጅ ምክሮችን ሲያስተላልፍ እንደነበር ይታወሳልና ነው፡፡
የሆነው ሆኖ ለተፈጠረው የፖለቲካ ውጥንቅጥ የመፍትሔ አካል ሆኖ ከመገኘት ይልቅ ይበልጥ የሚያወሳስብ እና የከፋ መልክ እንዲይዝ የሚያደርጉ ሁኔታዎች እየተስተዋሉ ይገኛል፡፡ በእኔ ዕይታ እና አስተውሎት ከመንሥዔው ባልተናነሰ የችግሩ ዋነኛ አባባሾች እና አወሳሳቢዎች ደግሞ አንዳንድ በአሜሪካ ሀገር በነዋሪነት የሚገኙ የኢትዮጵያ ሰዎች ናቸው፡፡ የዚህ የአቤቱታ ማመልከቻ ደብዳቤዬ ዋነኛ መነሻዎቹም እነሱ ናቸው፡፡ እነዚሁ ወንድሞቻችን የአሜሪካ ሕዝብ እና መንግሥት ባመቻቹላቸው የኑሮ፣ የትምህርት እና የሥራ ዕድል ተጠቅመው፤ በተማሩት ትምህርት፣ በቀሰሙት ዕውቀት፣ በተግባር በተመለከቱት የሥልጣኔ ምጥቀት መሠረት፣ የሀገራቸውን የኢትዮጵያ አንድነት አስጠብቀው እና የሕዝባቸውን የፍትሕ፣ የዴሞክራሲ እንዲሁም የሥልጣኔ ጥማት ለማርካት እንደመጣር፣ በሀገሪቱ የተፈጠረውን ትልቅ የፖለቲካ ሥህተት የሚታረምበትን መንገድ እና የተሻለ አማራጭ እንደመፈለግ፤ በተቃራኒው እነሱ ግን ሁኔታውን እንደ ምቹ አጋጣሚ በመጠቀም ጭራሽ ወደ ከፋ ሁኔታ እንዲያመራ እና እንዲባባስ በማድረግ፣ ሀገራችን ኢትዮጵያን ሊበታትን እና ሕዝቦቿን ሊያበጣብጥ በሚችል ደረጃ፣ በክልላዊ ብሔርተኝነት ስም በጥላቻ ላይ የተመሠረተ የጎሣ ፓለቲካ ሥራ ላይ ተሰማርተው ይገኛሉ፡፡
በኢትዮጵያ ሕዝብ አሰፋፈር እና ስብጥር፣ መልክዓ ምድራዊ አቀማመጥ፣ ታሪካዊ፣ ባሕላዊ እና ሐይማኖታዊ አኗኗር፣ ማኅበራዊና ኢኮኖሚያዊ ትሥሥር እንዲሁም የደም ለደም ውህደት ምክንያት ፈፅሞ ሊተገበሩ ቀሮቶ ሊታሰቡ የማይችሉ የተሳሳቱ የጎሣ ፖለቲካ አስተሳሰቦችን፣ በመስበክ እና በመቀስቀስ፣ ዛሬን ብቻ አሸናፊ መስለው ለማለፍ በመሞከር፣ ሕዝባችንን በተሳሳተ እና ፍፁም አደገኛ በሆነ በክልል ብሔርተኝነት ላይ በተንጠለጠለ የጎሰኝነት ሥነ ልቦና ላይ እንዲገኝ ከፍተኛ አስተዋጽኦ በማድረግ ላይ ይገኛሉ፡፡ የዚሁ ድርጊታቸው ውጤትም ከተራ ቅስቀሳነት አልፎ መርዛማ ፍሬውን አፍርቶና በመጠኑም ቢሆን በስሎ በተግባር በተለያዩ ሁኔታዎች መታየት ጀምሯል፡፡ ከቅርብ ጊዜያት ወዲህ በተለያዩ የኢትዮጵያ ክፍላተ ሀገር የተከሰቱ እንቅስቃሴዎችን መመልከት ይቻላል፡፡
የሀገራችን ሕዝቦች ለዘመናት ሲታገሉለት የኖሩትን የፍትሕ፣ የመብትና እና የመልካም አስተዳደር ጥያቄዎችን በመጥለፍና ተገቢውን አቅጣጫ በማሳት፤ ጥላቻ አዘል የጎሣ ፖለቲካ ያለከልካይ እየሰበኩ እና እያራገቡ ሀገራችንን የመበተን አቅሙን ከዕለት ወደ ዕለት በዕጃቸው እያስገቡት ይገኛል፡፡ ዛሬ ላይ ይኸው ድርጊታቸው ምናልባት ጀብድ እንደሚወድ ትንሽ ልጅ “እኔ ነኝ ይኼን ያደረኩት፣ ጉልበቴም እዚህ ድረስ ነው” ከማለት ያለፈ አንዳች ዘላቂ ጥቅም በግላቸው አያስገኝላቸውም፡፡ ነገር ግን ችግሩ የሚጀምረው ስህተታቸው ሥር ሰዶ መጨረሻው ደረጃ ላይ የደረሰ ቀን ነው፡፡ በዚህም ምክንያት በእነሱ ያልተገባ የፖለቲካ ጨዋታ የመከራ ደመና በሀገሬ ኢትዮጵያ ሰማይ ላይ እያንዣበበ እንደሚገኝ ይሰማኛል፡፡ አይበለውና ይኼው የመከራ ደመና ከዘነበ፤ ሀገሬ ኢትዮጵያ በአፍሪካም ሆነ በቅርቡ በመካከለኛው ምሥራቅ አንዳንድ ሀገራት ከተከሰተው ያልተናነሰ፤ ምናልባትም ከዚያም በከፋ ታይቶ በማይታወቅ ሁኔታ አሰቃቂ የሕዝብ ፍጅት እና ዕልቂት ልታስተናግድ ትችላለች፡፡
የእነዚሁ ወንድሞቻችን ከበዙ አደገኛና አጥፊ ድርጊቶቻቸው መካከል እንደ አንድ ምሳሌ ለመጥቀስ ያህል ብሞክር፤ ኢትዮጵያን እነሱ በመሰላቸውና በዘፈቀደ እንዲሁም ለጊዜያዊ የፖለቲካ ጥቅማቸው ሲሉ ባሴሩበት መንገድ ብቻ፣ የወደፊት ሀገራችን ብለው የዛሬዎቹን የክልሎች ስያሜ ተከትለው፣ የራሳቸውን ድንበር በወረቀት ላይ አካለው እስከመጨረስ ደርሰዋል፡፡ ከጅምሩ የተነሱበት ሀገርን የመገነጣጠል ፖለቲካቸው በዕውነተኛ የሕዝቦች ጥያቄ ላይ የተመሠረተ ስላልነበረ እና እነሱ ራሳቸው በፈበረኩት የልብወለድ ታሪክ ለይ የተንጠለጠለ በመሆኑ፤ ጉዳዩን በተጨባጭ መሬት ላይ ለማውረድ በሚጥሩበት ጊዜ ደግሞ የማይያዝና የማይጨበጥ ሆኖ ሲያስቸግራቸው ይታያል፡፡ ለዚህም የሚነድፏቸው የድንበር ወሰን አመላካች ካርታ፣ አንደኛው የእኔ ግዛት ብሎ ያሰፈረው እና ሌላኛውም የእኔ የድንበር ወሰን ብሎ ከደነገገው ጋር እርስ በእርስ ተደራርቦ መገኘቱን መጥቀስ ይቻላል፡፡ ይህን ድርጊት አሁን ላይ እንደ ቀልድ አይቶ መተው ቢቻልም፤ በሂደት ግን በሀገራችን ሕዝቦች መካከል ያልተገባ ከፍተኛ እና ማባሪያ የሌለው ግጭት የማስነሳት ዕምቅ አቅም ያለው እና ጊዜውንም ጠብቆ ሊፈነዳ የሚችል አጥፊ ተግባር ነው፡፡ ይህን ጉዳይ ዛሬ ላይ ተሁኖ በዝምታ ማለፍ በተዘዋዋሪም ቢሆን የዚያ የጥፋት ድርጊት ተባባሪ እንደመሆን ያስቆጥራል፡፡ እንዲህ ያለውን አጥፊ ድርጊት የረጅም ዕደሜ እና ሠፊ ታሪክ ባለቤት በሆነች ሉዐላዊት ሀገር ላይ ለመተግበር ከመሞከር የባሰ ምንስ በደል ምንስ ሕገ-ወጥነት ይኖራል?
ይኼንኑ ድርጊት በማስረጃነት ለመጥቀስ ያህል ከዚህ ደብዳቤ ጋር በአባሪነት በብዙ ሰዎች ቅብብሎሽ በየኢንተርኔቱ ለመቀስቀሻነት በመሰራጨት ላይ የሚገኙ በየብሔሩ የተሸነሸነችውን የኢትዮጵያ ካርታ የሚያሳይ ምስል አያይዣለሁ፡፡
በእውነቱ እንዲህ ያለው የጭካኔ ሥራ አርቃቂ እና አስፈፃሚ ሆኖ መገኘት፣ በታሪክ ተወቃሽ ከማድረጉም አልፎ ጊዜውን ጠብቆ የሕግ ተጠያቂነትን የሚያስከትል ያልተገባ ተግባር እንደሆነ፣ በዚህ መልኩ ያለፉ ሀገራትን ልምድ ወደኋላ ዞር ብሎ መመልከት ብቻ በቂ ትምህርት ነበር፡፡ ከአንድ ሀገሩን እና ሕዝቦቿን በቅንነት ከሚወድ ዜጋ በሚጠበቅ ደረጃ የሚያኮራ ድርጊት እንዳልሆነም ይታወቃል፡፡
አሜሪካንን በሚያህል የአንድነት፣ የዴሞክራሲ፣ የሕዝቦች ዕኩልነት፣ የሥልጣኔ፣ የዕውቀትና ብልፅግና ተምሣሌት በሆነች ሀገር ላይ ሲኖሩ፤ የተማሩትን፣ ያዩትን፣ የቀሰሙትን ዕውቀት እና ልምድ ወደ ሀገራቸው በሚመጥን መልኩ አምጥተው ለመተግበር እንደመጣር፣ ያን ያህል ዕውቀት እና ልፋት በማይጠይቀው የሀገርን አንድነት በመበታተን እና በማፈራረስ ተግባር ላይ ተሰማርቶ መገኘት ምን ይባላል፡፡ ይህም ድርጊታቸው የጋራ ሀገራችን ለሆነችው ኢትዮጵያ አውዳሚ ሲሆን፤ ዕድሉን ሰጥታ በከፍተኛ ወጪ ላስተማረቻቸው አሜሪካ ደግሞ ኪሳራ ነው፡፡ በእርግጥ ለቅንነት እና ለፍቅር ልቡን መስጠት ለማይችል ሰው የዕውቀት ዕድል ቢመቻችለትም ትርፉ እንዲህ ያለው ጥፋት ነው፡፡ መገለጫውም አፍራሽ ሥራ ነው፡፡ በጣም ያሳዝናል፡፡ ሆኖም ይህን ስል ግን ከአስቸጋሪዎቹ የሀገራችን ሰዎች በተቃራኒው ቁመው፤ ዕድሜያቸውንና ዕውቀታቸውን ሁሉ ለሀገራችን ዕደገት፣ ሰብአዊ መብቶች መከበር፣ ለዴሞክራሲያዊ ሥርዓት ግንባታ እና ብልፅግና የሚተጉ ብዙ ቁጥር ያላቸው ወንድሞቻችንም መኖራቸውም የታወቀ ነው፡፡
ኢትዮጵያ ካላት ከፍተኛ የሕዝብ ብዛት አንፃር፣ ብዙም መረጋጋት በማይስተዋልበት የምሥራቅ አፍሪካ ክልል ከመገኘቷም ጭምር፤ የእሷ መተራመስ በቅድሚያ የገዛ ሕዝቦቿን በሚዘገንን መልኩ የመከራው ዋና ተጠቂዎች ቢያደርግም፤ የውድቀቱ ንዝረት እና ርዕደት ደግሞ በመላው ዓለም ከጫፍ እስከ ጫፍ በሁሉም አቅጣጫ መሰማቱ እና ማናወጡ አይቀርም፡፡ በዚህም ምክንያት ዓለም ለብዙ ጊዜያት ሲታገለው እና ሲፋለመው ረዥም ርቀት የተጓዘበትን የሽብርተኝነት ተግባር፣ እንደ አዲስ እንዲያንሰራራ እጅግ የተመቻቸ ሁኔታን ስለሚፈጥርለት፣ የዓለምን ሽብርተኝነትን የመታገልና የመደምሰስን ልፋት መልሶና ቀልብሶ በብዙ ርምጃዎች እንደገና ወደኋላ የሚመልስ ውጤትም ማስከተሉ አይቀርም፡፡ በተጨማሪም በሰው ልጆች ታሪክ ውስጥ ከተከሰቱና አስከፊ ከሚባሉ የሕዝብ ፍልሰትና ስደት ታሪኮች ባልተናነሰ ምናልባትም የባሰ ሁኔታ በዓለም ላይ ሊያስከስት ይችላል፡፡
ስለሆነም ያ አሰቃቂ ጥፋት እና መከራ ከመከሰቱ በፊት፣ በእኔ ዕይታ የአሜሪካ መንግሥት ጉዳዩን ትኩረት ሠጥቶ በጥሞና ቢመለከተው ነገሩን በአጭሩ ማስቀረት የሚያስችል መፍትሔ እንደሚገኝለት እተማመናለሁ፡፡ የአሜሪካ ምድር ለሰው ልጆች ሁሉ የመብትና የነፃነት ምድር እንደሆነች ይታወቃል፡፡ ይሁን እንጂ መብትንም ሆነ ነፃነትን በመጠቀም ጊዜ ደግሞ፣ በሌሎች ሰዎች ላይ አሉታዊ ተጽዕኖ ወይም ውጤት እንዳያመጣ በሚገባ መጠንቀቅ ዋነኛው የመብቱ ተጠቃሚ ኃላፊነት መሆኑም የታወቀ ነው፡፡ ነገር ግን ከላይ ለመጥቀስ በተሞከረው መሠረት በሀገሬ ኢትዮጵያ ላይ ያልተገባ የክልል ብሔርተኝነትን አስተሳሰብ በማቀጣጠል ላይ ያሉት ወንድሞቻችን፣ በመሠረታዊ ደረጃ ይህን የመብት አጠቃቀም አግባብነት ባላገናዘበ ወይም ሆን ተብሎ ወደ ጎን በተወ መልኩ፣ የአሜሪካ ሀገር ነዋሪነታቸውን ብቻ ተገን በማድረግ እየፈፀሙ ስለመሆናቸው አልጠራጠርም፡፡ በዚህም ምክንያት እነዚሁ የሀገሬ ሰዎች የተሰጣቸውን መብት እና ነፃነት ላልተገባ ዓላማ እያዋሉት እንደሚገኙ አምናለሁ፡፡ በመሆኑም ይህ ድርጊታቸው ኢትዮጵያን ማለቂያ ወደሌለው የጎሣና የማንነት ጥያቄ ትርምስ፣ የድንበር ይገባኛል ውዝግብ፣ የነፃ አውጪዎች ጋጋታ፣ የሐይማኖት ቡድንተኝነት መዘዝ እናም በአጠቃላይ አሰቃቂ የእርስ በእርስ መተላለቅ ወደሚያስከትል የመከራ ገደል እየገፋት ይገኛል፡፡
አሜሪካ ሽብርተኝነትን አጥብቃ የምትኮንነው እና የምትዋጋው የዘመናችን አስከፊ የሰው ልጆች ሁሉ ጠላት የሆነ ተግባር እንደሆነም ይታወቃል፡፡ ሽብርተኝነት ደግሞ ብዙ መልክ እና መገለጫዎችም እንዳሉት እርግጥ ነው፡፡ በእኔ አረዳድ ለማንኛውም ዓላማ ሲባል፤ በሠላማዊ ሕዝቦች መካከል እልቂትን የሚፈጥር ቅስቀሳ ማድረግ፣ ነውጥን መጠንሰስ፣ ማስተባበር ብሎም ተግባራዊ ማድረግ፣ የሀገርን ብሔራዊ አንድነት የሚያናጋ የትርምስ ተግባራት ማቀድና መሳተፍ፣ በአጠቃላይ በሰው ልጆች እና በሀገር ላይ የሚፈፀሙ አውዳሚ ተግባራት ሁሉ የሽብር ድርጊቶች ናቸው፡፡ ጥፋቱ በገዛ ሀገር እና ሕዝብ ላይ ሲፈፀም ደግሞ ከሽብር ድርጊትነቱ በተጨማሪ የሀገር መክዳትን ተጠያቂነትም አብሮ የሚያስከትልና የሚያካትትም ይመስለኛል፡፡
የአሜሪካ መንግሥት ከሌሎች ሀገራት የተቃውሞ ፖለቲካ አራማጆች በተለየ፣ ለእኛዎቹ የኢትዮጵያ ሰዎች ሠፋ ያለ የመጫወቻ ሜዳ ሳያመቻችላቸው አልቀረም፡፡ ይህም ለሀገራችን ካለው የወዳጅነት ስሜት የመጣ እንደሆነ እርግጠኛ ሆኖ መናገር ይቻላል፡፡ ነገር ግን ይህን የተመቸ ዕድል በኃላፊነት ተጠቅመው ለሀገራቸውና ለሕዝባቸው የተሻለ የፖለቲካ አማራጭ እንደማስተዋወቅ፤ አሜሪካንን እንደ የጦር ዕዝ ሠፈር በማስመሰል ኢንተርኔትን ደግሞ እንደ ጦር መሣሪያ በመቁጠር የውጊያ መመሪያ መስጫ የማድረግ ሙከራዎች እየተስተዋሉ ይገኛል፡፡ ይህም መብት እና ነፃነትን በአግባቡ የመጠቀምን አስፈላጊነት እና ግዴታን ወደጎን ከመተው አንዳንዴም ከግድየለሽነት በመነጨ መልኩ ስለመሆኑ፣ ከድርጊታቸው በመነሳት እርግጠኛ ሆኖ መናገር ይቻላል፡፡
ታላቋ አሜሪካ ዛሬ ለምትገኘው ሀገሬ ኢትዮጵያ በፍፁም ወዳጅነት እና አጋርነት ያበረከተችው አስተዋጽኦ እና ድጋፍ በሀገሪቱ ታሪክ ሁሉ የሚረሳ አይደለም፡፡ በአጠቃላይ በማኅበራዊ፣ በኢኮኖሚያዊ እና በፖለቲካዊ ጉዳዮች ሁሉ በወንድማዊ ስሜት የተደረገልን ልባዊ ድጋፍ ለሁል ጊዜ ሲዘከር ይኖራል፡፡ በመሆኑም አሜሪካ በአንድም ሆነ በሌላ መንገድ፣ ስለኢትዮጵያ ከእኛ ከዜጎቿ ባልተናነሳ ከፍተኛ አቅሟን አውጥታ ስትለፋ ኖራለች፡፡ የዚህ ሁሉ የአንድ ክፍለ ዘመን ዕድሜ በላይ የአሜሪካ ሕዝብ እና መንግሥት ልፋት እና ጥረት ደግሞ የተረጋጋችና የበለጸገች ኢትዮጵያን የማየት ራዕይ እንደሆነ የታወቀ ሀቅ ነው፡፡
ስለሆነም ታላቋ ሀገር ዩናይትድ ስቴትስ ኦቭ አሜሪካ ለኢትዮጵያ ባላት እጅግ የላቀ ወዳጅነት፣ አጋርነት እና ተሰሚነት ምክንያት የሚከተሉትን አንኳር ነጥቦችን የያዙ ሁለት ጥያቄዎችን በአክብሮት ለማቅረብ እወዳለሁ፡፡
1ኛ) ዩ ኤስ አሜሪካ በዓለም መድረክ በተግባር ከምትታወቅበት ለፍትሕ፣ ለሰው ልጆች መብትና ዴሞክራሲ ከመቆሟ አንፃር፤ በአሜሪካ የሚኖሩ የአንዳንድ ወንድሞቻችን ድርጊት በእርግጥ በዚያ ትክክለኛ ማዕቀፍ ውስጥ መሆኑን የአሜሪካ መንግሥት እንዲያጤነው፣ አጢኖም ከላይ እኔ በዘረዘርኩት መጠን የአካሄድ ስህተት መኖሩ ከታወቀ ደግሞ፣ ይህን የተወገዘ እና ያልተገባ ድርጊት በሀገረ አሜሪካ ላይ ቁጭ ብለው በገዛ ትውልድ ሀገራቸው ላይ እየፈፀሙ የሚገኙትን የሀገራችንን ሰዎች ተግባር ጉዳዩን ከሕግ አግባብነት፣ በሀገሬ ኢትዮጵያ እና ሕዝቦቿ ላይ ከሚያስከትለው ጉዳትና ውድመት አንፃር ተመልክቶ የእርምት እርምጃ እንዲወስድ
2ኛ) ከላይ ባልተገባ ድርጊታቸው ከወቀስኳቸው ወንድሞቻችን ባልተናነሰ፤ ሀገራችን ኢትዮጵያ አሁን ለምትገኝበት አስፈሪ የፖለቲካ ሁኔታ እና ውጥንቅጥ፣ ከጅምሩም ሆነ አሁን ለደረሰበት ደረጃ የሀገሬ መንግሥት ዋናው ባለድርሻ አካል መሆኑን አምናለሁ፡፡ የሆነው ሆኖ አሁን የደረስንበት አደገኛ ሀገራዊ ሁኔታ ከመወነጃጀል አልፈን ነገሮችን በጣም በፍጥነት፣ በቅንነት እና በእርቅ መንፈስ ለማስተካከል ካልተጣረ፣ መጪው ቅርብ ጊዜ ለሀገሬ ኢትዮጵያ ማንም ምንም የማያተርፍበት እጅግ የከፋ የውድመት እና የመከራ ሊሆን እንደሚችል መገመት አያዳግትም፡፡
በአሁኑ ሰዓት ሁሉንም ሰው በብሔር ማንነቱ ጥግ የማስያዝ ክፉ አስተሳሰብ ሀገራችን ላይ በመስፈሩ፣ ለሁሉም የሀገራችን “ፖለቲከኞች” በጋራና በዕኩልነት ተሰሚነት ያለው ሀገራዊ የሚባል አስታራቂ እና መካሪ ትልቅ ሰው እንዳይኖረን ተደርጓል፡፡ ስለሆነም ከፊት ለፊታችን ከተደቀነብን አስከፊ ሀገራዊ ጥፋት ለመዳንና መፍትሔ ለማግኘት፣ ሌላ የጋራ ወዳጅ እና ገለልተኛ አካል ማስፈለጉ ተገቢ መስሎ ይሰማኛል፡፡ በመሆኑም በእኔ ዕውቀት በዚህ ሰዓት ከታላቋ አሜሪካ መንግሥት በላይ ለኢትዮጵያ የቀረበ ተሰሚነት እና ተጽዕኖ ያለው አጋር መኖሩን እጠራጠራለሁ፡፡
ስለሆነም የአሜሪካ መንግሥት ሀገሬ ኢትዮጵያ በጉልህ የተደቀነባትን አስፈሪና አደገኛ ሁኔታ ቅርብነትና ድርስነት ከግምት ውስጥ አስገብቶ፣ ልዩ ተኩረት እንዲሰጠው እና መንግሥታችንን ጨምሮ በሁሉም ጎራ በያገባኛል ስሜት የሚንቀሳቀሱ የፖለቲካ ሰዎችን፣ በተገቢው ጫና እና ምክር ወደሚበጀው ሀገራዊ ስምምነት እንዲመጡ ጥረት እንዲያደርግልን፣ የአሜሪካ መንግሥት የተለመደ የወዳጅነት እና የመፍትሔ አፈላላጊነት ሚናውን እንዲያበረክት ከልብ በመነጨ አክብሮት ባለኝ የዜግነት ድርሻዬ እማፀናለሁ፡፡ ኢትዮጵያ እና ሕዝቦቿ የተደቀነባቸው አስከፊ ውድመት ከመከሰቱ በፊት ዛሬ አድኑልን፡፡ ከውድመት እና ከፍጅት በኋላ የሚደረጉ ርብርቦሾች በሁሉም ነገሩ አስከፊ፣ አክሳሪ፣ የማይሽር ቁስል ጥሎ የሚያልፍ እና ወደነበረበት የመመለስ ዕድሉም በበዙ መልኩ የመነመነ ነውና፡፡
ከልባዊ አክብሮት ከመነጨ ምሥጋና ጋር
ሳምሶን ጌታቸው ተክለሥላሴ

ከዕለታት አንድ ቀን ሶስት ሌቦች ወደ አንድ ሀብታም ግቢ ይገቡና፣ ጌትየው መተኛቱን ካረጋገጡ በኋላ ምን ማድረግ እንዳለባቸው ይመክራሉ፡፡
አንደኛው፡-
እኔ ጌትየው አካባቢ ሆኜ መንቃት አለመንቃቱን እያየሁ ልጠብቅ
ሁለተኛው፡-
እኔ ደግሞ ቀስ ብዬ የበረቱን በር ልክፈትና ከብቶቹን ላስወጣ
ሦስተኛው፡-
እኔ፤ እደጅ ልሁንና የወጡትን ከብቶች ራቅ ወዳለ ጫካ ነድቼ እናንተ እስክትመጡ ልጠብቅ
አንደኛው፡-
ከዚያስ ስንገናኝ ቀጥለን ምን እናደርጋለን? ከብቶቹን እንከፋፈላለን
ሁለተኛው፡-
ደሞ የምን ከብት መከፋፈል አመጣህ? በሚቀጥለው መንደር ገበያ ወስደን መቸብቸብ ነው እንጂ!
ሦስተኛው፡-
እኔ ገበያ ወስዶ በመሸጡ ሀሳብ ተስማምቻለሁ፡፡ ግን እስክንሸጥ ጌትየው ቢደርስብንስ?
ሁለተኛው፡-
እሱ ነቅቶ ወዲያ ማዶ መንደር እስኪመጣ ምን እንጠብቃለን? በተገኘው ዋጋ ሸጠን ከዐይን መሰወር ነው እንጂ?
ሦስተኛው፡-
ይሄ ድንቅ ሀሳብ ነው፡፡ በሉ አሁን ጊዜ አናባክን፡፡ ወደ ስምሪታችን እንሂድ፡፡
እንደተባባሉት የመጀመሪያው ሰውየው ተኝቶ ወደሚያንኮራፋበት መኝታ ቤት አካባቢ ሄዶ በተጠንቀቅ ቆመ፡፡ ሁለተኛው፤ በቀጥታ ወደ በረቱ አመራ፡፡ ሦስተኛው፤ ደጅ ወጥቶ የሚወጡትን ከብቶች ሊነዳ ተዘጋጀ፡፡
ሁሉም ነገር ያለምንም እንከን ተጠናቀቀ፡፡ ከዚያ ወደሚቀጥለው መንደር ከተማ መንገድ ጀመሩ፡፡ ሰውዬው እንቅልፍ ላይ እንደነበር ታውቋልና ዘና እያሉ ተጓዙ፡፡
ገበያ ውስጥ ገብተው፣ ቀንቷቸው፣ እንዳሉት በአንድ ጊዜ ቸበቸቡና ወጡ፡፡ ከዚህ በኋላ ወደ አንድ ጫካ ሄደው፣ ገንዘባቸውን ቆጥረው ሊካፈሉ ወሰኑ፡፡ ገንዘቡን ከመቁጠራቸው በፊት ግን አንደኛው አንድ ሀሳብ አመጣ፡፡
“ጎበዝ፤ ረሀብ አልተሰማችሁም?”
ሁለተኛው፡-
“እኔ በጣም ርቦኛል፡፡ ለምን አንዳችን ከከተማ ምግብ ገዝተን አንመጣም?”
ሦስተኛው፡-
“በጣም ጥሩ፡፡ እንግዲያው ዕጣ እናውጣ?”
በዕጣው ተስማሙና ዕጣው ወጣ!
የመጀመሪያው ሰው ላይ ወጣና፣ ገንዘብ ይዞ ወደ ከተማ ሄደ- ምግቡን ሊገዛ፡፡
ምግቡ ተገዝቶ እስኪመጣ፣ የቀሩት ሁለቱ መዶለት ጀመሩ፡፡
ሁለተኛው፡-
“አሁን ምግብ ሊገዛ የሄደው ጓደኛችን፣ ገንዘብ ክፍያው ውስጥ ባይኖርበት’ኮ ለሁለት ነበር የምንካፈለው?”
ሦስተኛው፡-
“ዕውነትክን’ኮ ነው፡፡ ታዲያ ለምን በሆነ ዘዴ አናስወግደውም?”
ሁለተኛው፡-
“ብንገድለውስ?”
ሦስተኛው፡-
“ጥሩ ዘዴ ነው፡፡ ደብድበን ለመግደል እንችላለን”
ሁለቱ ይህን እየዶለቱ ሳሉ ምግብ ሊገዛ የሄደው ደግሞ በበኩሉ ያሰበው ነገር ኖሯል፡፡
“አሁን የምገዛውን ምግብ መርዝ ባደርግበት’ኮ እነሱ ያንን መርዝ በልተው ክልትው ሲሉልኝ፤ የዚያ ሁሉ ገንዘብ ብቸኛ ባለቤት እኔ እሆናለሁ፡፡”
ስለዚህ የመጀመሪያው ሌባ፣ ከምግቡ ውስጥ መርዝ ጨምሮ ወደ ጫካው ተመለሰ፡፡
እንደደረሰ ሁለቱ አስቀድመው የዶለቱበት ሌቦች፣ ሳያስበው በዱላ ቀጥቅጠው ገደሉት፡፡ በመግደላቸው ተደስተው፣ ምግቡን አቅርበው በሉ፡፡ ሆኖም ምንም ሳይቆዩ ሁለቱም በያሉበት ክልትው ብለው ቀሩ!
*          *         *
“ደባ ራሱን ስለት ድጉሡን” ማለት ይሄ ነው፡፡ አብዛኛውን ጊዜ ለሌላው ማጥፊ ያሰቡት ተንኮል፤ ዞሮ የራስ መጥፊያም ሆኖ ይገኛል፡፡ በሀገራችን ይሄ አያሌ ጊዜ ተከስቷል፡፡ ለሌላው ብለው ያመጡት ህግ፣ መልሶ በራሰ ላይ ሊመጣ እንደሚችል የሚያስተውል የለም፡፡ ማንም ቀድሞ ከተመታው ጓደኛው አይማርም፡፡ “እሱ ጥፋተኛ ስለሆነ ነው የተመታው፡፡ እኔ ግን ንፁህ ነኝ!” የሚለው አስተሳሰብ፣ በታሪክ ክር ላይ ደጋግሞ ሲጠነጠን አይተናል፡፡ አባራሪው ተባራሪ ይሆናል፡፡ አሳሪው ታሳሪ ይሆናል! የዛሬው ገምጋሚ፣ የነገው ተገምጋሚ ነው፡፡ የለውጥ ሕግ የማይሰራበት ቦታ የለም፡፡ Every rule changes, except the rule of change እንዲሉ ፈረንጆቹ፡፡ ከለውጥ ህግ በስተቀር ሁሉም ህግ ተለዋጭ ነው እንደማለት ነው! በእርግጥም የጊዜ ጉዳይ ነው እንጂ ለውጥ ማንንም አይምርም! ህዝብም ስለሚያየው ለውጥ ተገቢውን ጥያቄ አያቀርብም! በሆነውና በሚሆነው ሁሉ እሰየው ያለ ይመስል ነገሩን አዳምቆ፣ አዳንቆና ሆይ ሆይ ብሎ፣ የሆዱን በሆዱ ይዞ፣ ደግሞ መጪውን ድርጊት ወይም ክስተት ይጠብቃል፡፡ የአስተሳሰብ ለውጥ ያስፈልገዋል፡፡ የትላንትናው አካሄድ ምን ጠቀመኝ? ምን ዓይነት ለውጥ ያሻኛል? ሁሌ “ቃና ውስጤ ነው” እያልኩ እዘልቀዋለሁ ወይ? እያደግሁ ነው ወይስ እያጠርኩ በመሄድ ላይ ነው ያለሁት? ብሎ መጠየቅ ማወቅ አለበት፡፡ ጥቂቶች የወርቅ ክምር ጉልላት ላይ የተቀመጡባት፣ ብዙዎች የፒራሙዱ ግርጌ ላይ ተረፍርፈው የሚተኙባት አገር “የዕንቁልልጬ” አገር ናት! ራስን የማያረካ፣ መንግሥትን የማያረካ፣ አገርን የማያረካ ሥራ፣ ሥራ ተብሎ የሚኖርባት አገር፣ የ“ሆድ ሲያውቅ ዶሮ ማታ” አገር ናት! አብዛኛው ሕዝብ፣ ምሁሩም ጭምር፣ በብዥታ የሚጓዝባት አገር የራዕይ አገር ልትሆን ከቶ አትችልም፡፡ የዕንቁልልጩ አገር እንጂ! የታቀደው አልሳካ ሲል ወደ ዘመቻ የሚኬድበት አገር በዕቅድ ትመራለች ማለት ዕንቁልልጩ ነው! ትላንትን ሳናጣጥም፣ ዛሬን ሳንኖር፣ ነገን እየፈራን መኖር እርግማን ነው! ሼክሲፒር በፀጋዬ ገ/መድህን ብዕር እንደሚለው፡፡
“… በምናውቀው ስንሰቃይ፣ የማናውቀውንም ፈርተን በሕሊናችን ማቅማማት፣ ወኔያችንንም ተሰልበን፣ ከዕለት ወደ ዕለት ተስበን፣ ከአባቶች በወረስነው ጋድ እያደቀቅን እየደቀቅን፣ መጓተት በጥንቱ ልማድ፣ በሃሳብ ጭጋግ ስንዋኝ፣ መንፈስ ንቁነት ጥቅሙ የአድራጎት ምግባር አምሃ፣ የመንቀሳቀስ አቅሙ እያደር ከሕሊናችን፣ ይደመሰሳል ትርጉሙ!...”
የተግባር ሰዎች እንሁን! ዐይናችን የሚያየውን ከልባችን አንሸሽገው፡፡ በራሳችን እንተማመን፡፡ ዕውነታን አንካድ! “ዕምነት ሲታመም፣ ሺህ ወረቀት መፈረም” የሚለውን የአበው ብሂል አንርሳ! ሌቦችን ሌቦች ማለት እንልመድ! የዛፉን አክል በቅርንጫፉ ላይ አንላክክ! የዘገየ ፍርድ፣ ከሌለው አንድ መሆኑን አንዘንጋ! አሁንም አዲስ ነገር የምንፈልግ ከሆነ፣ አዲስ ልቦና እንግዛ! አዲሱን ዓመት በአዲስ መንፈስ ለመቀበል ዝግጁ እንሁን! የሚታየውን አንካድ! ተጨባጩ ላይ ዐይናችንን አንጨፍን! “ዝሆን ይኸውና ቢሉት፣ ዱካው የታለ፤ አለ” የሚለው ተረት የሚያጠነክረው ይሄንኑ ነው!!
መልካም አዲስ አመት!

   · የቤተ ክህነት የብዙኃን መገናኛ ድርጅት: “ፕሮግራሙን አላውቀውም፤” አለ
        · “የቤተ ክርስቲያኒቱን የቴሌቪዥን ጣቢያ መጠቀም ስላልቻልን ወደ ሌላ ሔድን”
        · “እያስተማርን መጥተናል፤ እንቀጥላለን፤ልዩ ፈቃድ አይጠበቅብንም፤”
        · “ቅዱስነታቸው፥ የራሳቸውን ፕሮግራም ይጀምሩ፤ብለዋል፤”

      ማኅበረ ቅዱሳን፣ ከነገ በስቲያ የዘመን መለወጫ ዕለት፣በአሌፍ የቴሌቪዥን ጣቢያ ላይ መደበኛ ሥርጭቱን  እንደሚጀምር ያስታወቀ ሲሆን፤ የጠቅላይ ቤተ ክህነቱ ብዙኃን መገናኛ አገልግሎት ድርጅት በበኩሉ፣ “የቴሌቪዥን መርሐ ግብሩን  አላውቀውም፤” አለ፡፡
ማኅበሩ ለአዲስ አድማስ እንደገለጸው፤ አሜሪካን ሀገር በሚገኘው አሌፍ የቴሌቪዥን ጣቢያ ላይ የአየር ሰዓት በመግዛት በሳምንት ለ7 ሰዓታት፥ በአማርኛ፣ በአፋን ኦሮሞና በትግርኛ ቋንቋዎች ትምህርተ ወንጌል  ለማስተላለፍ ዝግጅቱን ያጠናቀቀ ሲሆን፤ ከነገ በስቲያ የመክፈቻ መርሐ ግብሩን እንደሚያቀርብ አስታውቋል፡፡
የጠቅላይ ቤተ ክህነቱ ብዙኃን መገናኛ ድርጅት፣ ለፓትርያርክ አቡነ ማትያስ በጻፈው ደብዳቤ፥ ማኅበሩ በአሌፍ ቴሌቭዥን ጣቢያ፣ በቤተ ክርስቲያኒቱ ስም ሥርጭት እንደሚጀምር በድረ ገጹ ቢያስተዋውቅም፣ ድርጅቱ ግን የሰጠው ፈቃድ እንደሌለ ገልጿል፡፡ ቀደም ሲል በተመሳሳይ ጉዳይ ለኢቢኤስ ቴሌቭዥን ጣቢያ በተጻፈው ደብዳቤ፣ በማኅበራትና ቡድኖች ላይ የተላለፈውን እገዳ የሚጥስ አካሔድ እንደሆነም ጠቅሷል፡፡
የድርጅቱ ቦርድ በጉዳዩ ላይ አስቸኳይ ስብሰባ በመጥራት ከተወያየ በኋላ የተጻፈው ይኸው ደብዳቤ፤ ጉዳዩን ለፓትርያርኩ ከማሳወቅ ውጭ ሌላ የገለጸው ነገር እንደሌለ ምንጮቹ አስረድተዋል። “ክፈቱም ዝጉም ማለት አንችልም፤የላይኛው አካል ይወስንበት፤” ተብሎ በተደረሰው ስምምነት መሠረት እንደተጻፈ፣ ጉዳዩም በሒደት ላይ እንዳለና ውሳኔ አለማግኘቱን ጠቁመዋል፡፡
የብዙኃን መገናኛ ድርጅቱ፣ የጻፈውን ደብዳቤ በተመለከተ አዲስ አድማስ የጠየቃቸው የማኅበረ ቅዱሳን ዋና ጸሐፊ አቶ ተስፋዬ ቢሆነኝ፤ በመረጃ ደረጃ ከመስማት በቀር ከየትኛውም ወገን በይፋ ለማኅበሩ የደረሰ ክልከላ ወይም እግድ እንደሌለ አስታውቀዋል፡፡
“ቅዱስ ሲኖዶስ ለማኅበራችን አስቀድሞ በሰጠው እውቅና፣ ትምህርተ ወንጌልን በተለያዩ የመገናኛ አውታሮች ለትውልዱ የማስተላለፍ ሓላፊነት አለብን፤” ያሉት አቶ ተስፋዬ፣ “የቴሌቪዥን ሥርጭቱም ከመገናኛ ዘዴዎቹ አንዱ በመሆኑ በደንቡ የተፈቀደ ነው፤ እያስተማርን መጥተናል፤ አሁንም እንቀጥላለን፤ ልዩ ፈቃድ አይጠበቅብንም፤ በቤተ ክርስቲያናችን መዋቅር ዕውቅና ያለን ማኅበር ነን፤” ብለዋል፡፡
ማኅበሩ ባለፉት 25 ዓመታት በመጽሔት፣ በጋዜጣ፣ በራድዮና በመሳሰሉት የመገናኛ ዘዴዎች የሃይማኖቱን አስተምህሮ ሲያስተላለፍ እንደቆየና የዚሁ አካል ተደርጎ የሚታየው የቴሌቪዥን መርሐ ግብሩም የተለየ ተግባር እንደማይሆን አስረድተዋል - አቶ ተስፋዬ፡፡
ማኅበሩ የቤተ ክርስቲያኒቱን የቴሌቪዥን ጣቢያ ለመጠቀም እስካለፈው ግንቦት ድረስ የአየር ሰዓት በተደጋጋሚ ጠይቆ ምላሽ እንዳልተሰጠው የገለጹት ዋና ጸሐፊው፣ በርክበ ካህናት ቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ ላይ በቀረበበት ወቅት፣ ፓትርያርኩ፤ “አቅም ስላላቸው የራሳቸውን ጣቢያ መክፈት ይችላሉ፤” ማለታቸውን ተናግረዋል።
በአሌፍ ቴሌቭዥን ጣቢያ መርሐ ግብሩን ለመጀመር የተነሳሳውም ከዚህ በኋላ እንደሆነ ጠቁመዋል፡፡ በዚህም መሠረት፣ በዘመን መለወጫ በሚጀምረው የማኅበሩን የቴሌቭዥን መርሐ ግብር ላይ የሚቀርቡ ተቃውሞዎች ተቀባይነት አይኖራቸውም፤ ብለዋል።
መቀመጫውን በአሜሪካ ካደረገውና በባህላዊ፣ በማኅበራዊና በኢኮኖሚያዊ ጉዳዮች ላይ ከሚያተኩረው የአሌፍ ቴሌቭዥን ጣቢያ ጋራ መዋዋሉን በተመለከተ፣ “ለምን ደግማችሁ ለጠቅላይ ጽ/ቤቱ አላሳወቃችሁም?” በሚል ለቀረበላቸው ጥያቄ፣ “ተስፋችን የነበረው ከጠቅላይ ቤተ ክህነቱ የብዙኃን መገናኛ ድርጅት ጋራ አብረን እንሠራለን፤ ኃይል እንሆናለን ብለን ነበር፣ አልሆነም፤ ወትሮም መተዳደርያ ደንቡ ማኅበሩ እንዲሠራ ይፈቅድለታል፤ ቅዱስነታቸውም፣ የራሳቸውን መጀመር ይችላሉ፤ እያሉ ሌላ ፈቃድ መጠየቅ አይጠበቅብንም፤” ሲሉ ምላሽ ሰጥተዋል። ይህም ሆኖ፣ ማኅበሩ፣ ከብዙኃን መገናኛ ድርጅቱ የጠየቀው የአየር ሰዓት ቢፈቀድለት፣አሁንም ተመልሶ ለማገልገል ዝግጁ እንደሆነ አረጋግጠዋል፡፡
ማኅበሩ፣ በተለያዩ ቋንቋዎች የዘመኑን ትውልድ ለማስተማር የሚያስችል ሞያዊ አቅምና ዝግጅት እንዳለው አቶ ተስፋዬ ገልጸው፣ “የቤተ ክርስቲያን አቅም ነው፤ ልትጠቀምበት ይገባል፤” ሲሉ ሞግተዋል፡፡ በቤተ ክርስቲያኒቱ ላይ ከሚነሣው የተደራሽነት ጥያቄና ካለው ክፍተት አንጻርም፣ አንድ ብቻ ሳይሆን ብዙ የቴሌቭዥን ጣቢያዎች እንደሚያስፈልጓትም አስገንዝበዋል፡፡  
የጠቅላይ ቤተ ክህነቱ የብዙኃን መገናኛ ድርጅት በተቋቋመበት ደንብ፣ በማንኛውም መልክ በቤተ ክርስቲያኒቱ ስም የሚሠራጩ ሚዲያዎችን የማስተዳደርና ፈቃድ የመስጠት፤ የአየር ሰዓት ኪራይ ለሚጠይቁትም ውል የመዋዋል ሥልጣን እንዳለው የጠቀሱት የቦርዱ ምንጮች፤ ፓትርያርኩ በቅዱስ ሲኖዶሱ ላይ የሰጡት ምላሽ እንደ ውሳኔ አልያም ፈቃድ መስጫ ተደርጎ ሊወሰድ እንደማይችል ይከራከራሉ፡፡ ከዚህ ቀደም፣ ማኅበሩ በኢቢኤስ ያስተላልፍ የነበረው ፕሮግራም መታገዱን ያስታወሱት ምንጮች፤በተመሳሳይ ከነገ በስቲያ በአሌፍ ቴሌቪዥን ጣቢያ ይጀመራል ተብሎ የሚጠበቀው የማኅበሩ መርሐ ግብርም እንዳይሰራጭ ሊታገድ  እንደሚችል ስጋታቸውን ገልጸዋል፡፡

      ከኢህአዴግ ጋር በድርድር ላይ ከሚገኙ ተቃዋሚዎች መካከል መኢአድ እና ኢዴፓን ጨምሮ 12 ፓርቲዎች በጋራ ተወካዮች ለመደራደር
ተስማምተዋል፡፡ ፓርቲዎቹ ከትናንት በስቲያ በሰጡት መግለጫ፤ አንድ ዓይነት የመደራደሪያ አጀንዳዎችን በጋራ ቀርፀው ለአደራዳሪው አካል ማስገባታቸውን ጠቁመዋል፡፡ ለድርድሩ በጋራ ለመቅረብ የተስማሙት ፓርቲዎች፡- የመላው ኢትዮጵያውያን አንድነት ድርጅት (መኢአድ)፣ የኢትዮጵያውያን ዲሞክራሲያዊ ፓርቲ (ኢዴፓ)፣ ቅንጅት ለአንድነትና ለዲሞክራሲ፣ አንድነት ለፍትህና ለዲሞክራሲ፣ የአዲስ ትውልድ ፓርቲ (ኢትፓ)፣ የወለኔ ህዝቦች ዲሞክራሲያዊ ድርጅት፣ የኢትዮጵያ ዲሞክራሲያዊ አንድነት ንቅናቄ (ኢድአን)፣ የመላ ኢትዮጵያውያን ብሔራዊ ንቅናቄ (መኢብን)፣ የመላ ኢትዮጵያውያን ዴሞክራሲያዊ ፓርቲ (መኢዴፓ)፣መሆናቸው ታውቋል፡፡ ፓርቲዎቹን በተደራዳሪነት እንዲወክሉም የመኢአድ ም/ፕሬዚዳንት አቶ ሙሉጌታ አበበ፣ የኢዴፓ ፕሬዚዳንት ዶ/ር ጫኔ ከበደና የአንድነት ለፍትህና ለዲሞክራሲ ሊቀ መንበር አቶ ትዕግስቱ
አወሉ ተመርጠዋል፡፡ ድርድሩ ላይ የተበታተነ ሀሳብ ይዞ ከመቅረብ ይልቅ በአንድ አላማና አቋም ገዥውን ፓርቲ ለመገዳደር በማሰብ ፓርቲዎቹ በጋራ ለመቅረብ መወሠናቸውን አስታውቀዋል፡፡

  አንጋፋው ብርሃንና ሰላም ማተሚያ ድርጅት፤ ከጀርመኑ ሙልባወር ኩባንያ ጋር በመተባበር የስማርት ካርድ ህትመት ሊጀምር መሆኑን አስታወቀ፡፡
ማተሚያ ቤቱ ከዚህ ቀደም ሚስጥራዊ ህትመቶችን በወረቀትና በቀለም ቴክኖሎጂ ያከናውን እንደነበር የጠቆሙት የድርጅቱ ዋና ስራ አስኪያጅ አቶ ተካ አባዲ፤ በዓለማቀፍ ደረጃ በአብዛኛው ሚስጥራዊ ህትመቶች ወደ ዲጂታል ቴክኖሎጂ እየተሸጋገሩ በመሆኑ፣ ማተሚያ ድርጅቱ ራሱን ለማዘመን ቴክኖሎጂውን ወደ ሀገር ውስጥ በማስገባት፣ የስማርት ካርድ ምርቶችን ለመጀመር ማቀዱን አስታውቀዋል፡፡
በዚህ ቴክኖሎጂ በመታገዝ በከፍተኛ የውጪ ምንዛሬ በውጪ ሀገራት በስማርት ካርድ ቴክኖሎጂ የሚታተሙ የባንክ ገንዘብ ማውጫ ካርዶች፣ ሲም ካርዶች፣ የመታወቂያ ካርድ፣ ፓስፖርት የመሳሰሉትን በሀገር ቤት ለማተም ያስችላል ተብሏል፡፡
የማተሚያ ቤቱ አመታዊ ትርፍ ከነበረበት 8 ሚ. ወደ 1.5 ቢሊዮን ብር ማደጉንና ትርፋማ መሆኑን ያወሱት ስራ አስኪያጁ፤ ቴክኖሎጂውን በስራ ላይ ለማዋል የገንዘብ አቅም ችግር የለብንም ብለዋል፡፡ ቴክኖሎጂውን ለመተግበር ከ125 እስከ 150 ሚሊዮን ብር እንደሚያስፈልግ በመጠቆም፡፡ አገልግሎቱም ከ6-8 ወር ባለው ጊዜ ውስጥ እንደሚጀመር አቶ ተካ ተናግረዋል፡፡

እሳትና ውሃ ቀርቦላታል፤ እጇን ወዳሻት መስደድ የእሷ ምርጫ ነው- ዶናልድ ትራምፕ

       ባለፈው ማክሰኞ ባልተጠበቀ ሁኔታ ባለስቲክ ሚሳኤል ወደ ጃፓን በማስወንጨፍ አለምን በድንጋጤ ክው ያደረገቺው ሰሜን ኮርያ፣ “ይህ እኮ በፓሲፊክ አካባቢ የማደርገው ወታደራዊ ዘመቻ ጅማሬ ነው፤ ገና ብዙ ሚሳኤሎችን ወደ አካባቢው አስወነጭፋለሁ” ስትል በይፋ ተናግራለች፡፡
የሰሜን ኮርያው ፕሬዚዳንት ኪም ጆንግ ኡን፤ ሚሳኤሉን ያስወነጨፍነው አሜሪካና ደቡብ ኮርያ እያደረጉት ለሚገኘው ወታደራዊ ልምምድ ምላሽ ለመስጠት ነው፣ የአገሬ ጦር በፓሲፊክ አካባቢ የሚያካሂደውና የአሜሪካ ግዛት የሆነቺውን ጉኣም ለማጥቃት ያለመው ቀጣይ ወታደራዊ ዘመቻ ጅማሬ ነው ሲሉ በይፋ ማስታወቃቸውን ኬሲኤንኤ የተባለው የአገሪቱ መንግስት መገናኛ ብዙሃን ዘግቧል፡፡
“ያስወነጨፍነው ሚሳኤል አሪፍ መነቃቂያ ነው፤ ከፍተኛ እርካታ ተሰምቶኛል” ሲሉ በይፋ የተናገሩት ፕሬዚዳንቱ፤ በቀጣይም ተመሳሳይ በርከት ያሉ ሚሳኤሎችን ወደ አካባቢው እንዲያስወነጭፍ ለአገሪቱ የጦር ሃይል ትዕዛዝ ማስተላለፋቸውንም ዘገባው አመልክቷል፡፡
ሰሜን ኮርያ ከሚሳኤል ሙከራዋ እንድትታቀብ በተባበሩት መንግስታት ድርጅትና በአገራት መንግስታት ተደጋጋሚ ጫና ቢደረግባትም ባለፉት ወራት በተጠናከረ ሁኔታ የሚሳኤል ሙከራ ስታደርግ መቆየቷን ያስታወሰው ዘገባው፤ የማክሰኞው የሚሳኤል ማስወንጨፍ ድርጊት ግን ብዙዎችን ያስደነገጠ ነው ብሏል፡፡
ከፒንግያንግ አቅራቢያ ከሚገኝ ጣቢያ ወደ ጃፓን አቅጣጫ የተወነጨፈው ይህ ሚሳኤል፤ 2ሺህ 700 ኪሎ ሜትሮች ያህል በመጓዝ በሰሜናዊ ጃፓን በሚገኘው ሆካይዶ ደሴት ላይ ቢያርፍም በነዋሪዎች ላይ ምንም አይነት ጉዳት አለማድረሱን ያስታወሰው ዘገባው፣ ድርጊቱ የጃፓንን መንግስት በከፍተኛ ሁኔታ ማስደንገጡንና ይህን ተከትሎ፣ የአገሪቱ ጠቅላይ ሚኒስትር በሰጡት መግለጫ፤ ድርጊቱ ያልተጠበቀ፣ አጅግ አደገኛና አውዳሚ ስጋት ነው ሲሉ ሰሜን ኮርያን መኮነናቸውን አመልክቷል፡፡
የተባበሩት መንግስታት ድርጅት፤ የሰሜን ኮርያ ድርጊት ለጃፓንና ለአካባቢው አገራት ብቻ ሳይሆን ለሁሉም የተመድ አባል አገራት ከፍተኛ ስጋት ነው በሚል ድርጊቱን በይፋ ያወገዘው ሲሆን ሩስያና ቻይና ግን በአካባቢው ውጥረት እንዲነግስ ያደረገው የአሜሪካ ወታደራዊ ልምምድ ነው ሲሉ አሜሪካን ኮንነዋል፡፡
የአሜሪካው ፕሬዚዳንት ዶናልድ ትራምፕ በበኩላቸው፤ ድርጊቱ ሰሜን ኮርያ ለጎረቤት አገራት ያላትን ጥላቻ ያሳየችበት ነው፣ ከአሁን በኋላ እሳትና ውሃ ቀርቦላታል፤ እጇን ወዳሻት መስደድ የእሷ ምርጫ ነው ሲሉ ተናግረዋል፡፡