Administrator

Administrator

   የዕውቁ የታሪክ ተመራማሪና የስነ-ፅሁፍ ባለሙያ ፕሬፌሰር ፍቅሬ ቶሎሳ፣ “ስውሩና ያልተነገረው የአይሁዳውያንና ኢትዮጵያውያን ታሪክ” የተሰኘ መፅሀፍ፣ ሰሞኑን ለንባብ በቃ፡፡
መፅሀፉ በዋናነት፣ የሁለቱ አገራት ህዝቦች ከ4 ሺ ዓመታት በላይ ስላላቸው ትስስር፤ ስለ ዮዲት ጉዲት ያልተነገሩና ለኢትዮጵያ ስላደረገቻቸው መልካም ተግባራት፤ ስለ አፋር ህዝብና በስሙ ስለተሰየመው አፍሪቃና በተለያዩ ጉዳዮች ላይ ትንታኔ ይሰጣል፤ ተብሏል፡፡
ፕሮፌሰር ፍቅሬ ከዚህ ቀደም ይህንን መፅሀፍ “The hidden and untold history of the Jewish people and Ethiopian” በሚል ርዕስ በእንግሊዝኛ ፅፈው አቅርበውት እንደነበር ተገልጿል። መፅሀፉ በ238 ገፅ ተቀንብቦ፣ በ101 ብር ከ20 ሳንቲም ለገበያ ቀርቧል። ፕሮፌሰር ፍቅሬ በቅርቡ ለንባብ ካበቁት፣‹‹የኦሮሞና የአማራ እውነተኛ የዘር ምንጭ” ከተሰኘው አነጋጋሪ መፅሀፋቸው በተጨማሪ፣ በእንግሊዝኛ፣ በጀርመንኛና በአማርኛ በርካታ ግጥሞችን፣ ተውኔቶችንና ከ60 በላይ አጫጭር መጣጥፎችን ለንባብ ማብቃታቸው ይታወሳል፡፡


  እናት የማስታወቂያ ድርጅት፣ ከጀርመን የባህል ማዕከልና ከብሄራዊ ቤተ-መጻሕፍትና ቤተ- መዛግብት ኤጀንሲ ጋር በመተባበር፤ ነገ ከቀኑ 8፡ 00 ጀምሮ፣ በሩስያዊው ጸሐፊ አንቷን ቼኮብ ተጽፎ በተርጓሚ ትዕግስት ኅሩይ “ቅብጥብጧ” በሚል ርዕስ ወደ አማርኛ በተመለሰው መጽሐፍ ላይ፤ በመወዘክር አዳራሽ ውይይት ያካሂዳል፡፡ በዕለቱ፣ ለውይይቱ የመነሻ ሀሳብ የሚያቀርቡት አቶ ዓለማየሁ አሊ እንደሆኑ የገለፀው እናት የማስታወቂያ ድርጅት፣ ፍላጎት ያለው በውይይቱ ላይ እንዲሳተፍ ጋብዟል፡፡

Saturday, 02 September 2017 12:28

አዳራሹ ባዶ አይደለም!

 የ“እኔ” ስለምንላቸው ተመልካቾች መጻፍ ከፈለግሁ ቆየሁ፡፡ “እኔ” የሌለሁበት ቦታ ማግኘት አስቸጋሪ ነው፡፡ “እኔ” ስል ግን እያንዳንዳችንን ማለቴ ነው፡፡ በእያንዳንዳችን ኅሊና ውስጥ ‹ጉዳይ› የምናደርጋቸው ሃሳቦች ብቻ ሳይሆኑ ሰዎች አሉ፡፡
የእያንዳንዳችን ኅሊና ደግሞ አዳራሽ ነው፤ አዳራሹ መድረክ አለው፤ አትሮኖሱ የተዘረጋውና መጽሐፉ የተገለጠው ለአንድ ሰው ነው፡፡ አንድ ሰው ደግሞ መድረክ ላይ የሚቆመው ዲስኩር ሊያስደምጥ፤ ወይም ትርኢት ሊያሳይ ወይም ሊያሰማ ነው፡፡ ንግግርም ሆነ ትዕይንት ደግሞ ራስን ለማስደሰት ተብሎ ብቻ የሚደረግ አይደለም፡፡ ታዳሚ ይፈልጋል። ታዳሚውን ማስደመም ወይም ማበሳጨት ደግሞ መድረክ ላይ የወጣው ሰው ሚና ነው፡፡
እንደዚህ ዓይነት ነገር ወደ ጭንቅላቴ ሰርጎ መግባት ከጀመረ ዘጠኝ ዓመታት አልፎታል፡፡ ሰውን ሰው ያደረገው ሰው ነው፡፡ ስለ ሰው የማያስብ ሰው የለም፡፡ በዕለቱ እንተውናለን፤ ሲተወንም እናያለን፡፡ የቴአትር ጥበባት ተማሪ ሳለሁ፣ ስለ አዘጋጃጀት ጥበብ ያስተማረን መምሕር ተሻለ አሰፋ ‹Private audience› የሚለውን ቃል ያነሳሳልን ነበር፡፡ “ፕራይቬት ኦዲየንስ” ማለት፣ አንድ ተዋናይ ወክሎት የሚጫወተውን ገፀ ባሕርይ በጥልቀት አጢኖ፣ ገጸ ባህርዩ ማንን አስቦ ነው፣ እያንዳንዱን ቃል የሚናገረው? ማንን አስቦ ነው፣ ድርጊቱን እየተገበረ፣ ሕይወቱን እየኖረ ያለው? ለሚሉ ጥያቄዎች ተዋናዩ ምላሽ እንዲሰጥ የሚያደርግ ፅንሰ-ሀሳብ ነው፡፡
ለምሳሌ ከሼክስፒር ተውኔቶች ውስጥ ኦቴሎን እንውሰድ፡፡ ኦቴሎ የእናቱ ነገር አይሆንለትም፡፡ የእናቱን ስጦታ፣ ያቺን መሀረብ፣ እንደ ማተብ ክር ይሞትላታል። የእናቱ ምስል እየተመላለሰበት ያንፀዋል፤ ያፅናናዋል። እናቱ ናት በውስጡ ያለችው፡፡ በኢያጎ ውስጥ ግን ጎልቶና ደምቆ የሚታየው ኦቴሎ ነው፡፡ ብዙዎቻችሁ እንደምታውቁት፣ የኢያጎ መንፈስ የሚናወፀው ኦቴሎ ከፍ ብሎ ሲታይ ነው፡፡ የአንድ ጥቁር ሰው ጄኔራል መሆንና በበላይ ሹማምንት ተወዳጅ መሆን ኢያጎን ረብሾታል፡፡ የሚገባኝ ቦታ በሌላ ሰው ተይዟል ብሎ ያምናል፡፡ ስለዚህ ኦቴሎ ከክብሩ ዝቅ እንዲል፣ ዝቅ ባለም ጊዜ ያልተገባ ነገር በራሱና አብረውት በሚኖሩት ታማኞቹ ላይ እንዲፈፅም ኢያጎ ነገር መጎንጎን ይጀምራል፡፡
ዴዝዴሞና ከቃስዮ ጋር የተለየ ግንኙነት እንዳላት አስመስሎ፣ ኦቴሎ ለዴዝዴሞና የሰጣት ተወዳጁን መሀረብ ሚስቱ ሰርቃ እንድታመጣለትና ቃስዮ እጅ እንዲገባ አድርጎ፣ ቅናት አረሙን በትዳሩ ላይ ይዘራበታል፡፡ ከላይ በጠቀስነው “ኦቴሎ” ቴያትር ውስጥ፣ የኦቴሎ “ፕራይቬት ኦዲየንስ” ማለት፣ እያንዳንዱ ገፀባህርይ በሕይወቱ ውስጥ ሰፊ ስፍራ የሚሰጠውን  ተመልካች የሚመለከት ይሆናል፡፡ ሰፊ ስፍራ የሚሰጠው ደግሞ ለሚወዱት ብቻ አይደለም፤ ለሚጠሉትም ጭምር እንጂ!
በእያንዳንዱ ድርጊቶች መሃል ይሄ ስሜት አለ። የተማርንም ያልተማርንም ያው ነን፤ ብቻችንን አይደለንም፤ ይዘናቸው ወይም በማይታይ አንቀልባ አዝለናቸው የምንዞራቸው ሰዎች አሉን፡፡ ያለ እነዚህ ሰዎች አንድ ስንዝር ፈቅ ማለት ይከብደናል፡፡ እነዚህ ሰዎች ወዳጆቻችን፣ ወይም ወላጆቻችን፣ ወይም የመሰረትነው የቤተሰብ አባላት ይሆኑ ይሆናል፡፡
ይህንን የተማርኩ ዕለት፣ “ፕራይቬት ኦዲየንስ” የሚባለውን ነገር፣ ‹ለገፀባህርይ አሳሽነት ብቻ› ሳይሆን ወደ የዕለት ተዕለት ሕይወት ማውረድ ፈለግሁ፡፡ አብረውኝ የሚማሩ ተማሪዎችን አሰብኩና፣ ራሴንም ጨመርኩና፣ እነዚህ ተማሪዎች በየኅሊናቸው ይዘዋቸው የሚዞሩ፤ ወደ  ዕድገት ተራራ ባቀኑ፣ ወይም ወደ ውድቀት ሸለቆ በወረዱ ቁጥር፣ ቶሎ ወደ ጭንቅላታቸው ብቅ የሚለው “ተመልካች” ማን ይሆን? ብዬ አሰብኩ፡፡ በየኅሊናቸው አዳራሽ እንዴት ያሉ ሰዎች ወንበሮቻቸውን ይዘው ተቀምጠዋል ብዬ የማይመለከተኝን አሰሳ አካሄድኩ፡፡ እነዚህ ተማሪዎች፣ እንደ ማንኛውም ሰው ሞራላቸው ተሰብሮ ቢወድቅ “እኔን!” ብለው የሚደነግጡላቸው ሰዎች አሏቸው፡፡ በተቃራኒውም፣ “ይበላቸው!” ብለው ክፉውን ሁሉ የሚመኙላቸው ሰዎችም አሏቸው፡፡ ግና ተማሪዎቹ ማንን ደስ ለማሰኘት ወይም ማንን በንዴት ባህር ለማስዋኘት ብለው ነው፣ እየኖሩና እየተማሩ ያሉት? በእልልታና በእሪታቸው ጊዜ ቶሎ ወደ አእምሮአቸው ብቅ የሚለው አንዴት ያለ ሰው ነው? ሕይወት እንድትተውነው ባዘጋጀችላቸው ተውኔት ለመሳተፍ መድረክ ላይ ሲወጡ፣ ከእልፍ አእላፍ ተመልካቾች መሀል፣ ማንን ወይም እነማንን አስበው ነው፣ ትወናቸውን የሚያካሂዱት? ብዬ ራሴን ጠየቅኩ፡፡
አንድ ተማሪ ነበረ፡፡ እድሜው ገፋ ብሏል፡፡ የድርሰትም ሆነ የዝግጅት ዝንባሌ የለውም፡፡ የትወና ተሰጥኦም እንዳልታደለ ያውቃል፡፡ ግን ይማራል፤ ቴአትር ይማራል፤ ቴአትረኛ ለመሆንም ሆነ ለመባል ሳያጓጓውና የመንፈስ ግለት በውስጡ ሳይኖር ይማራል፤ የሚማረው ግን ንቃ የተወችውን ሴት፣ የት እንደደረሰ ለማሳየት ነው፤ አዎን፤ ንቃ የተወችውን ሴት ለማስቆጨት፣ “አመለጥኩሽ!” ለማለት!!
ይህቺን ሴት ይወዳት ነበር፡፡ ገጠር ገብቶ፣ የአንደኛ ደረጃ ተማሪዎችን በሚያስተምርበት ጊዜ፣ ይህቺ ሴት ብዙ መደናበሮችን አስረስታው ነበረ። ደስታውና ፈገግታው ሞቅ፣ ፈካ እያለ እንዲሄድ አድርጋው ነበረ፡፡ ቆይቶ ግን አንድ ነገር ተፈጠረ። አንድ ቀን ጠረኖቻቸውን ተጠጋግበው ሲያበቁ፣ “ላገባሽ ወስኛለሁ!” አላት፤ ይህንን ስትሰማ ደነገጠች፤ መጀመሪያ አይደነግጡ አደነጋገጥ ደነገጠች፤ ቀጥሎ ሣቋ መጣ፤ ከትከት ብላ ሣቀች፤ ሣቀችበት፤ አሁን ድንጋጤዋን ተረከባት፡፡ በተራው ደነገጠ፡፡ “ሰርፕራይዝ አደርጋታለሁ!” ብሎ አስቦ በተናገረው ነገር፣ “ሰርፕራይዝ” ያደረገውን ምላሽ ሰጠችው፡፡ “ድፍረትህ! እኔ እኮ እዚህ ምንም መዝናናት በሌለበት ገጠር፣ ብቻ ከመሆን ይሻላል ብዬ የፍቅር ጥያቄህን ተቀበልኩህ እንጂ እኔና አንተ እኮ አንመጣጠንም! አንኳኋንም!” አለችው፡፡ ግራ ገብቶት፣ “ለምን?” አለ፡፡ መልስ ለመስጠት ደቂቃ አልፈጀባትም፣ “አንኳኋንም!! እኔ’ኮ ዲፕሎማ አለኝ!! አንተ ደግሞ ገና የቲ.ቲ.አይ. ምሩቅ ነህ! እንዴት ቁልቁል ወርጄ ካንተ ጋር ትዳር ልመስርት?!” አለችው፤ ጥያቄውን በማቅረቡም ታዘበችው፡፡
ምንጭ፡- (ሰሞኑን ለንባብ ከበቃው የደራሲ እንዳለጌታ ከበደ፣ ”ያልተቀበልናቸው”
የወጎች መድበል የተቀነጨበ፤ ነሐሴ 2009 ዓ.ም)

  በረጅም ልብወለድ- አዳም ረታ (“የስንብት ቀለማት”)
በሥነ ግጥም- አበረ አያሌው (“ፍርድና እርድ”)
 በልጆች መፅሐፍ - አስረስ በቀለ (“የቤዛ ቡችላ”)
ኢስትዌስት ኢንተርቴይንመትና ኤቨንት ከአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ጋር በመተባበር ለመጀመሪያ ጊዜ ያዘጋጁት “ሆሄ” የሥነ ፅሑፍ ሽልማት፣ባለፈው ሰኞ ምሽት በብሔራዊ ትያትር ባካሄደው ሥነሥርዓት በየዘርፉ ተወዳድረው ያሸነፉትን  ሸልሟል፡፡ ዋናዎቹ የውድድር ዘርፎች ረጅም ልብወለድ፣ሥነግጥምና የልጆች መጻሃፍት ሲሆኑ ከሐምሌ 2008 እስከ ሐምሌ 2009 ዓ.ም ተፅፈው ለንባብ የበቁ መፅሐፍት በውድድሩ መካተታቸው  ታውቋል፡፡ ለእያንዳንዱ ዘርፍ ሶስት ሶስት ዳኞች ተመድበው ምርጫና ምዘናው መካሄዱም ተጠቁሟል፡፡ 80 በመቶ በዳኞች ምዘና ፣20 በመቶ ደግሞ በአንባቢያን ምርጫ መሰረት፣  አሸናፊዎቹ እንደተለዩ ተነግሯል፡፡
በረጅም ልቦለድ ዘርፍ ለውድድር ከቀረቡት ሥራዎች መካከል የዶ/ር ዓለማየሁ ዋሴ “ዝጎራ”፣ የአዳም ተረታ “የስንብት ቀለማት”፣ የሰብለ ወንጌል ፀጋ “መፅሀፉ”፣ የያለው አክሊሉ “ወሰብሳቤ” እና የብርሀኑ አለባቸው “የሱፍ አበባ” ለመጨረሻው ዙር ያለፉ ሲሆን  የደራሲ አዳም ረታ “የስንብት ቀለማት፣ አሸናፊ ሆኗል፡፡ ደራሲው በሃገር ውስጥ ስለሌለም፣ተወካዩ፣ ከደራሲ ሳህለ ስላሴ ብርሀነ ማሪያም እጅ ሽልማቱን ተቀብሏል፡፡
በግጥም መፅሀፍ ዘርፍ ለውድድር ከቀረቡት ሥራዎች ውስጥ የኤፍሬም ስዩም “ኑ ግድግዳ እናፍርስ”፣ የትዕግስት ማሞ “የጎደሉ ገፆች”፣ የአበረ አያሌው “ፍርድና እርድ”፣ የዶክተር በድሉ “ተስፋ ክትባት” እና የበላይ በቀለ ወያ “እንቅልፍና ሴት” የግጥም መፅሀፍት ለመጨረሻው ዙር ያለፉ ሲሆን  የአበረ አያሌው “ፍርድና እርድ” አሸናፊ ሆኖ ከገጣሚ፣ ባለቅኔና ፀሀፌ ተውኔት አያልነህ ሙላቱ እጅ ሽልማቱን  ወስዷል፡፡
በልጆች መፅሐፍ ዘርፍ ከቀረቡት ሶስት መፅሐፎች መካከል የኮሜዲያን አሥረስ በቀለ “የቤዛ ቡችላ” የተሰኘ መፅሐፍ አሸናፊ ሆኗል፡፡ ለመጨረሻው ዙር ካለፉት ሶስት የልጆች መፅሐፍት ሁለቱ የአሥረስ በቀለ ናቸው፡፡ ኮሚዲያን አሥረስ በቀለ ሽልማቱን ከተቀበለ በኋላ ባደረገው አጭር ንግግር፤ “እኔ ሁሌም ተስፋ ሳልቆርጥ ስለምሰራ ለዚህ በቅቻለሁ፤ ዛሬ ሆሄ የሽልማት ድርጅት ከሥነ-ፅሁፍ ጋር በይፋ ድሮኛል” ሲል ደስታውን ገልጧል፡፡ ኮሜዲያኑ አስከትሎም፤ “ዛሬ አበባ ተስፋዬ በህይወት ኖረው፣ ይህንን ክብር ቢያዩልኝ  ምን ያህል በታደልኩ” ሲል በቁጭት ስሜት ተናግሯል፡፡  
የ”ሆሄ” ሌሎች ተሸላሚዎች  
የላቀ አስተዋፅኦ ያበረከተ የሚዲያ ተቋም -
ሸገር ኤፍኤም 102.1 ሬዲዮ
በረጅም ዘመን የትምህርት ማስፋፋት የላቀ ባለውለታ- አቶ ማሞ ከበደ ሽንቁጥ
ለአይነ ስውራን መፅሀፍትን ተደራሽ በማድረግ የላቀ አስተዋፅኦ ያበረከተ- “አዲስ ህይወት ለአይነ ስውራን ማዕከል”
በረጅም ዘመን ጋዜጠኝነትና ስነ-ፅሁፍን በትረካ ለህዝብ በማድረስ - ጋዜጠኛ ደጀኔ ጥላሁን
በረጅም ዘመን የኃያሲነትና ስነ-ፅሁፍ ሥራ የላቀ አስተዋፅኦ በማበርከት- ኃያሲና ደራሲ አስፋው ዳምጤ
በህይወት ዘመን የስነ-ፅሁፍ ሽልማት- አለቃ አካለወልድ ክፍሌ (“መፅሀፈ ሰዋሰው ወግዕዝ”)

   ብክለትን ለመቀነስ የወጣው ህግ 176 ፋብሪካዎችን ያዘጋል፣ 60 ሺህ ሰራተኞችን ያፈናቅላል

        የኬንያ መንግስት፤ የፕላስቲክ ከረጢት ወይም ፌስታል ባመረተ ወይም በተጠቀመ ላይ እስከ 4 አመት እስር እና 40 ሺህ ዶላር የገንዘብ ቅጣት የሚጥልና በአለማችን በመስኩ እጅግ ጥብቅ የተባለ ህግ አውጥቷል፡፡
በኬንያ ከሰኞ ጀምሮ የፕላስቲክ ከረጢት ይዞ የተገኘ የአገሪቱ ዜጋ፣ በፖሊስ ቁጥጥር ስር ውሎ ተገቢው ቅጣት እንደሚጣልበት የጠቆመው ዘገባው፤ የፕላስቲክ ከረጢቶችን የሚያመርቱ ፋብሪካዎችም ቁጥጥር እንደሚደረግባቸው አመልክቷል፡፡
የፕላስቲክ ምርቶች በአካባቢ ብክለት ረገድ የሚፈጥሩትን ተጽዕኖ ለመቀነስ ታስቦ የወጣው ይህ እጅግ ጥብቅ ህግ፤ ከቀጣዩ ሰኞ ጀምሮ በስራ ላይ እንደሚውል የዘገበው ዘ ጋርዲያን፣ በአገሪቱ የፕላስቲክ ከረጢቶች በየቦታው እየተጣሉ ከፍተኛ ብክለት እየፈጠሩ እንዳሉም አመልክቷል፡፡
የፕላስቲክ ከረጢቶች ለመበስበስ እስከ 1000 አመታት የሚደርስ ጊዜ እንደሚፈጁ የገለጸው ዘገባው፤ እንስሳትም ያገለገሉ የፕላስቲክ ከረጢቶችን በመመገብ ለጤና ችግር እንደሚጋለጡና በመዲናዋ ናይሮቢ በሚገኙ የከብት ማረጃ ቄራዎች ከአንድ ከብት ሆድ ዕቃ ውስጥ እስከ 20 የሚደርሱ ያገለገሉ የፕላስቲክ ከረጢቶች እንደሚገኙ ጠቁሟል፡፡
የፕላስቲክ ከረጢት ምርቶችን ወደ ውጭ አገራት በመላክ፣ከአካባቢው አገራት በቀዳሚነት የምትሰለፈው ኬንያ፣ የአካባቢ ብክለትን ለመቀነስ በሚል ያወጣቺው ይህ ህግ፣ በአገሪቱ የሚገኙ 176 ፋብሪካዎችን የሚያስዘጋና ከ60 ሺህ በላይ ዜጎችን ከስራ የሚያፈናቅል ነው በሚል የአገሪቱ የአምራች ኩባንያዎች ማህበር  ክፉኛ ተችቶታል፡፡
ቻይና፣ ፈረንሳይ፣ ሩዋንዳና ጣሊያንን ጨምሮ የተለያዩ 40 የአለማችን አገራት፣ የፕላስቲክ ከረጢቶችን ምርት በከፊል ወይም ሙሉ ለሙሉ የሚከልክሉ ተመሳሳይ ህጎችን አውጥተው በስራ ላይ ማዋላቸውንም ዘገባው አስታውሷል፡፡

     ሀብታሙ አለባቸው፣ ዛሬም ብዕሩንና ብራናውን አጣምሮ፣ የኢትዮጵያን ፖለቲካ ለመቃኘት ሞክሯል።  ቅኝት በመቃኘት ይታዘዛል። ጥሩ ቃኚ፣ ጥሩ ዜማን እንደሚያወጣ እሙን ነው፡፡ ሀብታሙ በቅኝቱ ጥሩ ዜማን አውጥቶ ይሆን የሚለው እንደ አድማጮቹ የሚወሰን ነው፡፡ በበኩሌ ያልተደፈረውን የቤተ መንግስት ጓዳ፣ ያልተደፈረውን የኢትዮ-ኤርትራ ጦርነትና ያልተለመደውን የኢህአፓ ዘመን ድብብቆሽ ባለፉት ስራዎቹ ለመቃኘት መሞከሩን ወድጄለታለሁ፡፡
ዛሬ በወፍ በረር ለመቃኘት የፈለግሁት “ታላቁ ተቃርኖ” የተሰኘውን ስራውን ነው፡፡ በእርግጥ ይህንን መጽሐፍ ለማሔስም ሆነ ጥናታዊ ዳሰሳ ለማድረግ አቅሉም አቅሙም ኖሮኝ አይደለም፡፡ ሆኖም እንደ አንባቢና በአገር ጉዳይ ላይ ለመሳተፍ/ለመጠየቅ/ እንዲሁም የግል አስተያየትን መስጠት የተፈጥሮ መብትና/ግዴታ ከመሆኑ አንጻር፣ ስለ መጽሐፉ ጥቅል ሐሳብ የተሰማኝን ለማስቀመጥ  ነው፡፡
በበኩሌ የምስማማበት ጉዳይ (ከሌሎች ጋር አለመስማማት እንዳለ ሆኖ) የኢትዮጵያን ፖለቲካዊና ታሪካዊ ችግር ከአንድ ነጠላ መንግስት እና “ሬዥም” ጋር ማያያዙ የውድቀታችን መነሻ ነጥብ ነው፡፡ በዚህም አግባብ ዳግማዊ ምኒልክ ኢትዮጵያ፣ ታሪክ ማጠንጠኛ “የትክተት ነጥብ” ሆነው ሲወሰዱ፤ ልንወጣው ወደማንችልበትና ሸክማችንን የሚያበዙ ጋሬጣዎችን ይሰበስባሉ። ሌላኛው አስከፊ ችግር ጋሬጣዎች መብዛታቸው ብቻ ሳይሆን ጋሬጣውን የምናስወግድበት እሾኩ ላይ ይሆናል፡፡
ሀብታሙ አለባቸው፣ የዚህ ምሳሌ ማሳያ ሆኖ የሚቀርብ ይመስለኛል፡፡ በመጽሐፉ ሽፋን፣ የመሃል ኢትዮጵያንና የሰሜን ጫፍ ድንበርን እንደ መነሻ በማድረግ፣ “ታላቁ ተቃርኖ”ን በማመልከት፤ “አጼ ምኒልክ ሠርተውት ያለፉት ነገር በትክክል ምንድን ነው?” ሲል የአጼ ሚኒልክን ምስል አስቀምጦ፣ይጠይቃል፡፡ በእርሱ አተያይና ጥልቅ ምርምር፣ የኢትዮጵያ መሰረታዊ ችግር የተገለጸው ወይም የተጠቀለለው በአጼ ሚኒሊክ ዘመነ መንግስትና ከዚህ ወዲህ ነው ማለት ነው፡፡
ይህን መሰል የምሁራን ቅኝት (ቅዠት ላለማለት)፤ ከ1960ዎቹ የምዕራባዊያንና የምስራቁ ዓለም የፖለቲካ ርዕዮተ ዓለም ውዥንብር በፈጠራቸው አስተሳሰቦች (የያ ትውልድ አባላት) ኢትዮጵያን ቀርጸው (የፈጠሯት እስኪመስል ድረስ) የዘመናችንን ትኩሳትና የወደፊት እጣ ፈንታችን በየመቶ አመት ታሪክ ብሂል ውስጥ ይቀብረናል። ይህ በራሱ የታላቁ ተቃርኖ አንኳር መነሻ ነው፡፡ (በኢትዮጵያ የመቶ አመት ታሪክ የክርክር ሐሳብ፤ እነ ዮሐንስ አድማሱን፣ እሸቱ ጮሌን፤ ፈቃደ አዘዘንና ፕ/ር መስፍን ወልደማርያምን ተችተው የተነሱበትን ዘመን ያስታውሷል)
የፖለቲካ ድንበርና የአገርን ማስተዳደር ቅርጽ፣ መልኩን ቀይሮ፣ የምዕራባዊያን ጣልቃ ገብነት በተስፋፋበት ዘመን ላይ ቆመን፤ መፍትሄም ይሁን የጥናታችንን ዛቢያ በዚህ ማዕቀፍ ውስጥ ብቻ ሆነን ስናንዣብብ “የታላቁ ተቃርኖ” መነሻም መድረሻም እንደሚሆን አስባለሁ፡፡ “የኤርትራ” ችግር እና “የደቡብ ቅራኔ” በምኒልክ መጀመሩን እንደ ፖለቲካዊ ትንታኔ አድርጎ መነሳት፣ የሃብታሙ አለባቸውና የመሰሎቹ የፖለቲካ ልሂቃን ውድቀት መሆኑ የዚህ ጽሑፍ ጭብጥ (የግል እይታዬ) ነው፡፡
የዳዕማት ሥልጣኔ አንድምታው ምንድን ነው? የአሁኑ ትውልድ ምን ያህል ያውቀዋል? የአክሱምን ሥልጣኔ ማን አቆመው?  ማን መራው? ማን ማን ገበረ? የትኛው ሕዝብ በየትኛው ህዝብ ትስስሩን ፈጠረ? በምን መንገድ ከየት ወደየት? ሕዝብ በምን ተለያየ? በምን ተሳሰረ? የዛጉዌ ሥልጣኔ ከየት የት ይደርስ ነበር? የውጭው ዓለም በወቅቱ በምን መልኩ ይረዱት ነበር? በዚህ ወቅት የደቡቡ ይዞታ በምን መልኩ ይተሳሰር ይተዳደር ነበር?
የመካከለኛው ዘመን የይኩኖ አምላክ መንግሥት፤ ከደቡቡ ጋር የነበረው ትስስር? የሸዋ ነገሥታትና ቀሪው ማሕበረሰብ የነበራቸው ገጽ፤ አጼ ዘርዓ ያዕቆብ ሶማሌ ድንበር ድረስ ሄደው የገነቡት ልማት፣ ጥፋት፣ የትዳርም ይሁን የማስገበር/የመገበር ታሪካችን፣ የኢትዮጵያ ሰንደቅ ዓላማ እስከ ቀይ ባሕርና ህንድ ውቅያኖስ ወይም የአፍሪካ ቀንድ ጫፍ መታየት፤ የልብነ ድንግል ንጉሳዊ ስም አጠራር በራሱ የሚሰጠው ትርጓሜ፤ የምስራቁ ዘመቻ ወደ ሰሜን ያመጣው ለውጥ፤ ለምላሹም የተሰጠው አጸፋ (አሉታዊም አዎንታዊም የአገር ግንባታ ሂደት...)
የእነ ሰርጸድንግል ታሪክ፤ የጎንደር ነገሥታት ከደቡቡ በተለይም ከኦሮሞው ሕዝብ ጋር የነበራቸው ትስስር፤ የየጁ መሳፍንት በጎንደር ዘመን የነበራቸው ሚና፣ ኦሮምኛ በጎንደር የነበረው ቦታ፤ ባሕረነጋሽ/ኤርትራ የነበረችበት ሁኔታ (ይዞታ)፤ የአጼ ቴዎድሮስ አነሳስ፣ ዘመኑ የጠየቀው መስፋፋት ምክንያት፤ ለምን አጼ ቴዎድሮስ? በዘመኑ የነበረው የግዛት አወሳሰን እንዴት ይገለጽ ነበር? ነው ወይስ “አቢሲኒያ”ን ቀርጸን ማነብነብ ይቀልለናል? …
(እዚህ ላይ ትልቅ የሚዘነጋ ሐሳብ ይታየኛል፤ ይሄውም የአጼ ቴዎድሮስ ዜና መዋዕል ከታቢና ምጡቅ ግለሰብ አለቃ ዘነብ፣ የኦሮምኛን ቋንቋ ማጥናታቸው፤ ብሎም መጽሐፍ ቅዱስን በኦሮምኛ ለመተርጎም ማሰባቸው፤ አስበውም መተግበራቸው በምን መልኩ የሚታይ ነው?)
በአጼ ዮሐንስ ዘመን መባቻ ላይ የተደረገው የባዕዳን ወረራና ተጽዕኖ፤ ሃይማኖታዊ ርዕዮተ ዓለም ለምን?  የባሕረ ነጋሽስ ይዞታ፤ የሂወት ውል፤ የምዕራባዊያን ቅኝ ግዛት ዘመቻ፤ የፖለቲካ አስተሳሰብ ዘመቻ፤ የመንግሥታት ትብብር ሐሳብ፤ የዘመናዊነት ትርጓሜ፤ … ወዘተ እንዲህ እንዲህ እያልን ጥናታዊ ምርምር፤ የታሪክ ጥናት የሚጠይቀውን መነጽር እየተጠቀምን፣ “ታላቁ ተቃርኖ” በሚል ሐሳብ እያላወስን፤ የኢትዮጵያን ችግር ነቅሰን እናውጣ ቢባል፣ አዕምሮዬንም ሆነ ስሜቴን የሚገዛ ጭብጥ የማገኝ ይመስለኛል፡፡
ዋናው ሀብታሙ አለባቸውን የምሞግትበት ነጥብም ይሄው ነው፤ ከእነዚህ ጭብጦች ውስጥ ነበር የአጼ ምኒልክን ቦታ ፈልቅቀን በማውጣት፣ ወዳለንበት ደረጃ ደርሰን፣ ተቃርኖንም ይሁን የግጭት መንስኤዎችን አልያም ስኬቶችን ልንገልጽ የምንገደደው፡፡ ከአንድ ትልቅ ሰፌድ ውስጥ አንዱን ሰንደዶ አውጥቶ፣ የሰፌዱን ሕልውና አድርጎ መውሰድ፣ በሰፌዱና በሌሎች ሰንደዶዎች ላይ የሚሰራ ደባ ሆኖ መታሰቡ አይቀሬ ነው! ኤርትራ ከምኒልክ በፊት የኢትዮጵያ ግዛት የሆነችበትና ያልሆነችበት ጊዜ በታሪክ ተፈትሾ ሲጠና፤ የደቡቡን ይዞታና ትስስር ቅድመ ታሪክ ጥናት ሳናደርግ፤ ምኒልክን መነሻም መድረሻም ማድረጉ ትልቅ የታሪክ ሸፍጥ ሆኖ ይታየኛል፡፡ ምኒልክ ሳይፈጠሩ ኤርትራ የነበረችና ለበርካታ ነገስታት የድልም የውድቀትም የስኬትም የክሽፈትም ማጠንጠኛ ሆና የዘለቀች በመሆኗ፤ “ኤርትራ” “ኤርትራ” የምንለው የምዕራባዊያኑ እርኩስ መንፈስ ወርሶን ለመግባቢያነት የምንጠቀምበት የቦታ ስም ብቻ ሳይሆን ለውድቀታችን የተበተብነው የቄሳሩ መንፈስ አዚም /አዙሪት/  ነው፡፡ ደቡቡንም በመቶ አመት ውስጥ የተፈጠረ መልክዓ ምድራዊ ይዞታ እስኪመስል ድረስ፤  ስለ ሺሕ አመታት የኢትዮጵያ ታሪክ ሂደት እያወራን ቦታና የሕብረተሰብን ፍልሰት ሳናጤን፤ የጥንቱን ስያሜ በዘመነኛ “ሰካራም” ስያሜ እየሰጠን፤ በአሁኑ ትርጉምና ዘመን አመጣሽ መቀመርያ መመዘን፤ የውድቀታችን መነሻና የታላቁ ታቃርኖ ክስተት መደምደሚያው/መፈጸሚያው/ ነው፡፡
ሀብታሙ አለባቸው፣ በመጽሐፉ በርካታ የአገር ውስጥ እና የባዕዳንን ስም እየጠቀሰ፤ የሐሳብ ክርክሩን ለማጠናከር ሲሞክር እናስተውላለን። የምሑራኑን ሐሳብም እየጠቀሰ፣ ለ“ታላቁ ተቃርኖ” መፍትሄ ‹‹ፋይዳ የሌለው›› እና ‹‹ያለው›› እያለ ሲገልጽ እናስተውላለን፤ በተለይም ከአገር ውስጥ ገብረሕይወት ባይከዳኝንና ፕ/ር መስፍን ወልደማርያምን በተደጋጋሚ ሲገልጽ ማስተዋላችን አልቀረም፡፡
በበኩሌ ፕ/ር መስፍን ወልደማርያምን ስለ ኢትዮጵያ ታሪክ ባሕልና ፖለቲካ ትንታኔ አረዳድ በአንድ እና በሁለት መጽሐፎቻቸው ዙሪያ ብቻ በማተኮር፣ አጠቃላይ ሐሳባቸውን መተቸቱም ሆነ መፍትሄ የለውም ብሎ መነሳቱ  ጸሐፊውን ያስገመግመዋል ባይ ነኝ፡፡ “አዳፍኔ” ይህንን አላስቀመጠም ብሎ ወደ ፍረጃ መሄድ ጸሐፊው የተልዕኮ ማስፈጸሚያ አንደበት መያዙን ያሳብቅበታል፡፡ (አንባቢ ሆይ፤ በሀብታሙ አለባቸው መጽሐፍ ውስጥ ከበርካታ ምሁራን ሐሳቦች ከመጡ መደምደሚያዎች አንጻር፤ “መስፍን ወልደማርያም በዘመናቸው ያልጠቀሱት ሐሳብ (መፍትኄ) ይሄ ነው” ብሎ የሚያሳየኝ ሰው ካለ፣ ለመቀጣት ዝግጁ ነኝ! - ፕሮፌሰሩ ከጻፏቸው መጽሐፍት ውስጥ እንደ ዋቢ የጠቀሳቸው ከሶስት አለመብለጡን ያጤኗል!)
መጽሐፉ የበርካታ ምሁራንን ሐሳቦች በቁንጽልም ቢሆን መያዙ ምሁራኑ ተሰባስበው እንዲመካከሩበትና እንዲወያዩበት፣ የኢትዮጵያን ትልቁን ቁልፍ ችግር ለመያዝም ሆነ የተዘጋብንን ደንቃራ አስተሳሰብ ለመክፈት፤ ብሎም ቁልፉን ለእያንዳንዱ ዜጋ ሰጥቶ ወደ ብርሃናማው “የታሪክ አቅጣጫ” እንድንዘልቅ ለማድረግ ያግዛል ብዬ አስባለሁ፡፡ ሆኖም ጸሐፊው፣ ለመማርም ይሁን ለመታረም ዝግጁነቱን ሲያሳይና በአካለ መንፈስ ሲገኝ ብቻ ነው ብዬ አምናለሁ፡፡
መጽሐፉን በተደጋጋሚ እየተመለስኩ ለማንበብ ሞክሬያለሁ፡፡ ምርምራዊ ሂደትን ለመከተል የታሰበ ከመሆኑ አንጻር አሁንም ልዩ ትኩረትና አንጽንዖት ተሰጥቶት ሊታይ የሚገባው ነው፡፡ እንደ መቋጫ ሁለት ነጥብ ብቻ ላንሳ፡፡ አንደኛ፤ የኔ የአስተሳሰብ አድማስ ልኬት በእጅጉ የተወሰነ መሆኑን ወይንም በሌላኛው ጎን የጸሐፊው ሐሳብ በኢትዮጵያ ታሪክና ፖለቲካ ዙሪያ አዲስ አስተሳሰብን ይዞ ስለመጣ ለመረዳት አዳግቶኛል፡፡ በበኩሌ ጸሐፊው (ለእኔ) ይህንን የፈጠረበት ምክንያት  ምንድን ነው ብዬ ሳስብ አንዳንድ ነጥቦችን ማስቀመጥ ይኖርብኛል። በተቻለኝ መጠን በማሳጠር በሦስት ነጥቦች ብቻ ላጠቃልል፡፡
የኢትዮጵያን ችግር ከአጼ ምኒልክ ጋር አቆራኝቶ በመነሳቱና የመፍትኄ ሐሳቡንም እዚያው ዙሪያ በማድረጉ፣
በኢትዮጵያ ታሪክ ውስጥ የባዕዳን ተልዕኮና ጫና ራሱን የቻለ ሰፊ ቦታ ያለው ቢሆንም ጸሐፊው ጥናቱን በዚያ ላይም ባለማድረጉ፣
አሁንም በምሁራን እይታ ይቀርቡ የነበሩ ቃላትንን ለምሳሌ፤ ብሔር፣ አገር፣ ሐገረ መንግስት፣ ስልጣኔ፣ ባሕል፣ መንግስት ሬዥም…. ወዘተ መሰል ቃላትን አጠቃቀማቸውን ከእነ ልዩነታቸው ለማስረዳት ቢሞክርም በተለያዩ ገጾች ላይ ግን ራሱ ሲዳክርባቸው መመልከታችን አልቀረም።
ሶስቱን ነጥቦች በመያዝ ሌላ አንድ ረዥም ትንተና የሚያስፈልገው ጽሑፍ ማሰናዳት ይቻላል፡፡
ለማጠቃለል ግን፣”ታላቁ ተቃርኖ” በባዕዳን አስተሳሰብ የተቃኘ የምሁር እይታ መሆኑን መካድ አልችልም፡፡ የገብረህይወት ባይከዳኝ ሐሳቦች ላይ አተኩሮ ሚዛኑን እሱ ላይ መድፋቱን ሲገልጽ እናየዋለን፡፡ የሌሎች ባዕዳን አስተሳሰቦች/ጥናታዊ እይታ/ ከውስጣዊ ታሪካችን ጋር እያነጻጸሩ ለመግባቢያነት መቀመጡ፣ በተደጋጋሚ ውስጤን ኮርኩሮታል፡፡ የበርካታ ምሑራንን ሐሳቦች፣ ጥናታዊ ስራዎችና የምርምር ውጤቶችን ጠልቆ ገብቶ ዋኝቶ በመውጣት - የ”አዕምሯዊ ጅምናስቲክ” ጽሁፍ  እንዳይሆን ጸሎቴን አድርሼ፤ በመጽሐፉ ዙሪያ የወጡ አስተያየቶችን ለማንበብም ሆነ ለመሳተፍ ዝግጁነቴን ጀምሬያለሁ፡፡ መጽሐፉ አሁንም በተደጋጋሚ ሊመረመርና ሊታይ የሚገባው መሆኑን ግን የሚክድ አንደበት የለኝም፡፡

 የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ በተነሳ ማግስት በኦሮሚያ የተለያዩ አካባቢዎች የንግድ ሥራና የትራንስፖርት አገልግሎት ማቆም አድማ ባለፈው ሳምንት ተደርጓል፡፡ እነዚህ አድማዎች ምን አንደምታ አላቸው? በኢኮኖሚ ላይ የሚያሳድሩት ተጽዕኖ ምን ያህል ነው? በቱሪዝም ዘርፉና በኢንቨስትመንት ላይስ? በመንግስት ላይ የሚያሳርፈው ፖለቲካዊ ጫና ምንድን ነው? አድማዎቹ ተባብሰው ወዳልተፈለገ አቅጣጫ እንዳይሻገሩ መፍትሄው ምንድን ነው ? የአዲስ አድማስ ጋዜጠኛ
አለማየሁ አንበሴ፤ ዶ/ር ቆስጠንጢኖስ በርሄን፣አቶ ሞሼ ሰሙንና አቶ ክቡር ገናን በጉዳዩ ዙሪያ አወያይቷቸዋል፡፡ ሁሉም ሃሳባቸውን፣ አስተያየታቸውን፣ ስጋታቸውንና የመፍትሄ ሃሳቦቻቸውን ሰንዝረዋል፡፡ ለፖለቲካዊ ችግሮች መፍትሄው ፖለቲካዊ ውይይት ብቻ ነው፡፡

                    “በማንኛውም የሀገሪቱ ጉዳይ ህዝብን ማሳተፍ ያስፈልጋል”
                          ዶ/ር ቆስጠንጢኖስ በርሄ (የኢኮኖሚ ባለሙያ)

      የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ በተነሳ ማግስት የንግድና ትራንስፖርት አገልግሎት ማቆም አድማ ባለፈው ሳምንት በኦሮሚያ የተለያዩ ከተሞች ተደርጓል፡፡ በእንዲህ ያሉ አድማዎች ማነው ተጎጂው?
እንዲህ ያለ አድማ ሁሉንም ነው የሚጎዳው፤ ሸማቹን፣ ነጋዴውን፣ መንግሥትን ይጎዳል። በአጠቃላይ እንደ ሀገር ደግሞ መረጋጋቱን ስለሚያበላሽ፣ ኢንቨስተሮች በሀገሪቱ ላይ የሚኖራቸውን መተማመን ይቀንሳል፡፡ ብዙ ኢንቨስተሮች እንደ ቢቢሲ ላሉት፣ የውጪ ሚዲያ በሚሰጡት ቃለ ምልልስ፣ በተለይ የቻይና ኢንቨስተሮች፣ ኢትዮጵያን የመረጡበት አንዱ መመዘኛ፣ አገሪቱ የተረጋጋች፣ ሰራተኛውም ሰላማዊ በመሆኑ እንደሆነ ሲናገሩ ይደመጣሉ፡፡ እንደነዚህ አይነቱ ረብሻዎችና አድማዎች የሚያሳዩት፣ በአንድ መልኩ፣ ህዝቡ በህገ መንግስቱ ላይ የሰፈረውን  የመናገር መብቱን መጠቀሙ ነው፡፡ ጉዳዩ ወደ መጥፎ ሁኔታ ሲሸጋገር ደግሞ መንግስት ህግ የማስከበር ኃላፊነት አለበት፡፡ በዚህ አጋጣሚም የተለያየ አላማ ያላቸው ወገኖች፣ የህዝቡን ቅሬታ ለራሳቸው አላማ ሊጠቀሙበት ይችላሉ፡፡ ይህ እንዳይሆን መንግስት፣ ህዝቡን በየጊዜው ቀርቦ ማነጋገር አለበት፡፡ በተለይ በወረዳ ደረጃ ያሉ ኃላፊዎች፣ ለህዝቡ ቀጥተኛ መፍትሄ መስጠት አለባቸው፡፡
ለምሳሌ በኦሮሚያ ለተደረገው አድማ በምክንያትነት ከቀረቡት ጉዳዮች አንዱ የግብር ጉዳይ ነው---
በየትኛውም አገር ነጋዴ በተቻለ አቅም ታክስ ባይከፍል ይመርጣል፡፡ የአሜሪካን ፕሬዚዳንት ትራምፕ እንኳ ታክስ አይከፍሉም ተብለው ሲብጠለጠሉ የሰጡት ምላሽ፤ “እኔ ብልህ ስለሆንኩ ነው ታክስ የማልከፍለው” የሚል ነበር፡፡ አብዛኛው ነጋዴ ታክስ መክፈል አይፈልግም፡፡ ያገኘውን ቆጥቦ ንግዱን ማስፋፋትና ኑሮውን ማሻሻል ነው የሚመርጠው፡፡ መንግስት ደግሞ መሰረተ ልማት ለማሟላት፣ ሀገር ለመገንባት ገንዘብ ያስፈልገዋል። ስለዚህ በግብር ዙሪያ ያሉ አለመግባባቶችንና ችግሮችን በውይይትና  በሰለጠነ መንገድ መፍታት ያስፈልጋል፡፡
መንግስት የግብር ሰብሳቢ ሰራተኞችን ሁኔታም መፈተሽ ይኖርበታል፡፡ የአቅም ጉዳይ መታየት አለበት፡፡ ሌላው የንግድ መደብሮችን እያሸጉ ጉቦ የሚጠይቁ እንዳሉም ይሰማል፡፡ እነዚህ ነገሮች ላይ ትኩረት ሰጥቶ መከታተል ያስፈልጋል፡፡ የህዝብን ብሶት የሚቀሰቅሱት እንዲህ ያሉ ህገ ወጥ አሰራሮች ናቸው፡፡ በስፋት አድማ የሚያደርጉ ነጋዴዎች፣ ትልልቆቹ ወይም ለማህበረሰቡ በእጅጉ የቀረቡ አይደሉም፡፡ በየመንደሩ ያሉ ከህብረተሰቡ ጋር የቅርብ ግንኙነት ያላቸው አነስተኛ ነጋዴዎች ናቸው። የእነዚህ ነጋዴዎች ተፅዕኖ ቀላል አይደለም።
አድማው በመንግስት ላይ ምን ዓይነት ተጽዕኖ ያሳርፋል?
እርግጥ ነው ለጊዜው በመንግስት ላይ ምንም አይነት ቀጥተኛ ተፅዕኖ ላይኖረው ይችላል፤ ምክንያቱም የጸጥታ ኃይሉን ልኮ ህግ ሊያስከብር ይችላል፡፡ ነገር ግን አድማና ረብሻ ባለበት ቦታ ቱሪስት ሊመጣ አይችልም፡፡ ለምሳሌ ከዚህ ቀደም ከቱሪዝም በየዓመቱ ይገኝ የነበረው በቢሊዮን ብር የሚገመት ገቢ፣ አማራ ክልል ወይም ትግራይ ውስጥ ረብሻና አለመረጋጋት ከተከሰተ፣ ቱሪስት ወደ አካባቢው አይመጣም፤ ገቢውም አይገኝም። በዚህ በቀጥታ ተጎጂ የሚሆኑት የጎጃም የጎንደር ወይም የትግራይ ነዋሪዎች ናቸው፡፡ ህዝቡ ሲጎዳ ደግሞ መንግስት ላይ ነው ጫናው የሚያርፈው፤ ስለዚህ በአጠቃላይ ጉዳቱ በአገር ደረጃ ነው የሚሆነው፡፡ ሀገሪቱ ከፍተኛ የውጭ ምንዛሬ በምትፈልግበት፣ ግድቦች በሚገነቡበት፣ የባቡርና ሌሎች ሰፋፊ ፕሮጀክቶችን በዘረጋችበት አሁኑ ወቅት ከቱሪዝም የሚገኝ ገቢን ማጣት አገሪቱን ክፉኛ ይጎዳታል፡፡
በየዓመቱ በመቶ ሺህ የሚቆጠር ወጣት ከዩኒቨርሲቲ እየተመረቀ ነው፡፡ በሚሊዮን የሚቆጠር ወጣትም ከኮሌጅና የሙያ ተቋማት እየተመረቀ ነው የሚገኘው፡፡ እነዚህ ምሩቃን ሥራ እስካላገኙ ድረስ ይሄን አድማ በመጠቀም ጉዳዩን ወደ ሌላ ነገር የማሸጋገር ሁኔታ ሊፈጠር ይችላል፡፡ ባለፈው ዓመት እንደተመለከትነው፡- ፋብሪካ ማቃጠል፣ እርሻዎች ማውደም፣ መኪና መሰባበር ወዘተ --- የመሳሰለ አደገኛ ውጤት ሊኖረው ስለሚችል፣ የመንግስት ኃላፊዎች ለጉዳዩ ትኩረት ሊሰጡት ይገባል፡፡ እርግጥ የህግ አስከባሪዎች በምንም ሁኔታ  እንዲህ አይነት ነገር እንዲኖር አይፈቅዱም። ነገር ግን እንዲህ ያሉ አድማዎችና ተቃውሞዎች እየተጠናከሩ በሄዱ ቁጥር ህዝብ በገዥው ፓርቲ ላይ ያለው እምነት እየመነመነ ሊሄድ ይችላል፡፡ ሀገሪቱ ያላት አንፃራዊ ሰላምና መረጋጋት በተለይ በዓለም አቀፍ ሚዲያዎች መጥፎ ገፅታ እየያዘ ከመጣ፣ ኢንቨስተሮች እዚህ ሀገር መጥተው ኢንቨስት እንዳያደርጉ እንቅፋት ይሆናል፡፡ እንዲህ ያሉ አድማዎች በተራዘሙ ቁጥር ደግሞ የሰው የስራ ተነሳሽነት ስሜት እየቀዘቀዘ፣ ወደ ረብሻ የሚገፋፋበት ሁኔታ ሊፈጠር ይችላል። ይሄ አይነቱን ክስተት በተለያዩ የአፍሪካ ሀገራት ተመልክተነዋል፡፡
መፍትሄው ታዲያ ምንድን ነው?
በዚህ ጉዳይ የሲቪክ ማህበረሰቡና ሚዲያዎች ትልቅ ሚና እንዲጫወቱ ማድረግ ያስፈልጋል። በተለይ የምርመራ ስራ የሚሰሩ ሚዲያዎች መጠናከር አለባቸው፡፡ በሀገራችን በሚሊዮኖች የሚቆጠሩ የህዝብ ስብስቦች አሉ፡፡ የህዝብ ስብስቦች ስንል እድሮችን፣ ማህበሮችን ያካትታል። እነዚህ ቁልፍ አካላት ናቸው፡፡  እነዚህን የሲቪክ ማህበራት ማጠናከር ያስፈልጋል፡፡ በሌላው ዓለም መንግስት የማያውቀውን ነገር አጉልቶ በማውጣት እርምት እንዲደረግ በመጠቆም ረገድ ሚዲያው ያለው ሚና ቀላል አይደለም፡፡ በሀገራችን ግን በሲቪክ ማህበራትም ሆነ በሚዲያ በኩል እስከ ዛሬ ያለው እንቅስቃሴ ደካማ ነው፡፡ በተለይ ሙስናን ለመዋጋት ሚዲያና የሲቪክ ማህበራት ወሳኝ ናቸው፡፡ አንድ ሰው ያለአግባብ ሀብት ሲያካብት ቀድሞ ሊያውቁ የሚችሉት በየአካባቢው ያሉ የህዝብ ማህበራት ናቸው፡፡ ስለዚህ ከእነዚህ ጋር ተቀራርቦ መስራት መጀመር አለበት፡፡ አንድ ወረዳ ላይ መንገድ በአግባቡ ላለመሰራቱ ዋናው ምስክሮች የሚሆኑት በወረዳው ያሉ ማህበራት ናቸው፡፡፡
ሌላው የዲሞክራሲ መንሰራፋት ጉዳይ ነው፡፡ ዲሞክራሲ ስንል የፖለቲካ ባህልን መቀየር ማለት ነው፡፡ እኛ ገና የፖለቲካ ባህላችን እየዳበረ ያለ ሀገር ነን፡፡ ባለፉት 10 ዓመታት በተለይ ከ97 በኋላ ብዙ ነገሮች ተለውጠዋል፡፡ ልማታዊ መንግስት ሲባል፣ መንግስት ብቻ አይደለም መስራት ያለበት። ህዝቡ ቀጥተኛ ተሳታፊ መሆን አለበት፡፡ ህዝቡን ለማሳተፍ ደግሞ የሲቪክ ማህበራት ወሳኝ ናቸው። በማንኛውም ጉዳይ የህዝብ ተሳትፎ ሲጠናከር ነው፣ ይህቺን ሀገር ወደፊት ሊያራምዳት የሚችለው። መንግስት ወደ ህዝቡ የበለጠ ቀርቦ፣ በአገሩ ጉዳይ በያገባኛል ስሜት እንዲሳተፍ ማበረታታትና መገፋፋት አለበት፡፡

------------------

                            “ህገ መንግስትን ሁልጊዜ መንከባከብ ያስፈልጋል”
                               አቶ ክቡር ገና

      በኦሮሚያ የተደረገው የንግድ ሥራና የትራንስፖርት አገልግሎት ማቆም አድማ አንደምታው ምንድን ነው?
 ሁሌም እንዲህ አይነት የስራ ማቆም አድማ ሲደረግ የማይበላሽ ነገር የለም፡፡ በተለይ ትራንስፖርት የሀገሪቱ የንግድ አንቀሳቃሽ ዋና ሞተር ነው፡፡ በየአካባቢው ያለው የንግድ ስራ ማቆም በቀላሉ የሚታይ አይደለም፡፡ የህዝቡንም ኑሮ እንደሚያናጋ ግልፅ ነው፡፡
እነዚህ አድማዎች ከግብር ትመናው ጋር ብቻ የተገናኙ ናቸው ወይስ ሌላም ሰበብ አላቸው?
በመሰረቱ ግልፅ ሆኖ የሚታየው የፖለቲካም ችግር እንዳለ ነው፡፡ የፖለቲካ ችግርን ደግሞ በጊዜ መፍታት ያስፈልጋል፡፡ አንዳንዱ የፖለቲካ ችግሮችን በፖለቲካዊ ውይይቶች ለመፍታት ይሞክራል። አንዳንዱ ደግሞ በኃይል ለመፍታት ይሞክራል። ይሄ እንደየ ሀገራቱ ተጨባጭ ሁኔታ ይለያያል፡፡ እንደ‘ኔ ግን ፖለቲካዊ ችግሮችን በኃይል ለመፍታት ከመሞከር ይልቅ በንግግርና በውይይት መፍታት የተሻለ ዘላቂ ውጤት ያመጣል ብዬ አምናለሁ፡፡  
እንዲህ ያሉ አድማዎች መንግስት ላይ ምን ዓይነት ተጽዕኖ ያሳርፋሉ?
እንዲህ ያሉ አድማዎች የሚደረጉት መልዕክት ለማስተላለፍ ነው፡፡ መልዕክት ለማስተላለፍ ሌሎች አማራጮች ሳይኖሩ ሲቀር ህዝብ እንዲህ ያሉ መንገዶችን ለመጠቀም ይገደዳል፡፡ እነዚህ ችግሮች የመጡበትን ዋና ምክንያት ለይቶ ቀጥተኛ መልስ ካልተሰጠ ጉዳቱ ይጨምራል፡፡ አድማ የሚያደርጉ አካላትም እኮ ደልቷቸው አይደለም ሱቃቸውን የዘጉት፤ ሱቅ ሲዘጉ መቸገራቸው አይቀርም፡፡ ስለዚህ እነዚህ ችግሮች በቀላሉ የሚታዩ አይደሉም። መሰረታዊ የሆኑ ለረጅም ጊዜ ሲንከባለሉ የመጡ ናቸው፡፡ አሁንም ችግሩ አንድ ሳምንት ጠፍቶ ተመልሶ የሚመጣ አይነት ከሆነ፣ መሰረታዊ ችግሩ አልተፈታም ማለት ነው፡፡
በዚህ ሂደት አንዱ ከአንዱ የበለጠ ይጎዳል ማለት አይቻልም፡፡ ሁሉም ተያይዞ ነው የሚጎዳው። ተፅዕኖው በመንግስት ላይም ቀላል አይሆንም። ፈረንጅ ሀገር የሚደረጉ አድማዎች አሉ፡፡ ግን የእነሱ ምላሽ የሚያገኝበት የራሱ ጥበብ አለው፡፡ በኛ ሀገር እንዲህ ያለው አድማ መፍትሄ ሳይሰጠው የሚደጋገም ከሆነ  ጉዳቱ ቀላል አይሆንም፡፡ አድማው በየጊዜው ያዝ ለቀቅ እያለ የሚሄድ ከሆነ፣ ኢትዮጵያ በኢንቨስትመንት ተፈላጊነት ላይ ያላት ቦታ እየቀነሰ ሊመጣ ይችላል፡፡
የእነዚህ አድማዎችና ውጥረቶች መደጋገም ምን ያህል አሳሳቢ ነው?
ከብዙ ሰዎች ጋር ስወያይ፣ ጉዳዩ አሳሳቢ እንደሆነ ነው በመጨነቅ የሚናገሩት፡፡ በኔ አስተያየት፤ ከመንግስት በኩል ግን የችግሩ አሳሳቢነት ጎልቶ የወጣ አይመስልም፡፡ የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ መነሳቱ ጥሩ ነው፡፡ ነገር ግን በድጋሚ አስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ከመጣ፣ እንደገና ኃይልን መምረጥ ነው የሚሆነው። እንዲህ ያለውን ችግር ለመፍታት የሚመረጠው ኃይል ነው ወይስ ውይይት? ይሄ ጠርቶ መቀመጥ አለበት፡፡ ሌላ አዲስ መፍትሄም መፈለግ ያሻል፡፡  
ለምሳሌ ምን ዓይነት መፍትሄ?
እኔ እንደሚገባኝ ጥያቄዎች ግልፅ አይደሉም። እንደየ አካባቢው ብዙ አይነት ናቸወ፡፡ የመሬት ጉዳይ የሙስና፣ የሃብት ፍትሃዊ ክፍፍል የመሳሰሉ ጉዳዮች ይነሳሉ፡፡ በየቦታው የሚነሱ ጉዳዮች ምን እንደሆኑ ተጠንተው መቅረብ አለባቸው፡፡ ሀገር ማስተዳደር እንዲህ ቀላል አይደለም፡፡ ህገ መንግስት ስላለ ብቻ ሀገር አለ ማለት አይደለም፡፡ የህዝብ ጥያቄ ተፈታ ማለት አይደለም፡፡
ህገ መንግስትን ሁልጊዜ መንከባከብ ያስፈልጋል። ጥያቄዎች በህገ መንግስት እንኳ የማይመለሱ ከሆነ፣ ሀገርን ለማዳን ሲባል ከተቃዋሚ ኃይሎች ጋር በጥያቄዎቻቸው ላይ መነጋገር ያስፈልጋል፡፡ ከባዱን ነገር ተጋፍጦ መፍትሄ መሻት ያስፈልጋል፡፡ ዋና ዋና ጥያቄዎችን ለይቶ፣ ከህዝብ ጋር ቁጭ ብሎ በመወያየት መመለስ ወሳኝ ነው፡፡ ይሄ ሊደረግ ይገባዋል ባይ ነኝ፡፡     

--------------------
                                      “በሀገሩ ጉዳይ የተገለለ ሰው መኖር የለበትም”  
                                         አቶ ሞሼ ሰሙ

      ከአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ መነሳት በኋላ የተደረገው የንግድና የትራንስፖርት አገልግሎት ማቆም አድማ ተቃውሞው ማገርሸቱን ከማሳየት ባሻገር ምን?
ከአስቸኴይ ጊዜ አዋጁ በፊት የነበሩ እንቅስቃሴዎች  ወይም  አድማዎችና አሁን  የሚታዩት  ባህሪያቸው የተለያየ ነው፡፡ የመጀመሪያው ኢትዮጵያ ውስጥ የተፈጠረውን መሰረታዊ ኢኮኖሚያዊ ችግር ማዕከል አድርጎ የዲሞክራሲ፣ የሰብአዊ መብት፣ የሙስና፣ የመሬት አጠቃቀም፣ ፍትሃዊ የሀብት ክፍፍል ጥያቄዎች ላይ ያነጣጠረ ነበር፡፡ ኢህአዴግ ስልጣን ከያዘ ጀምሮ ባሉት ከ20 በላይ አመታት ውስጥ ተወልደው፣ በትምህርት ሂደት አልፈው ለአቅመ ስራ የደረሱ በሚሊዮን የሚቆጠሩ ወጣቶች አሉ፡፡ እነዚህ ወጣቶች ራሳቸውን የሚችሉበት ስራ አለማግኘታቸው አንዱ ችግር ነበር፡፡ በዚህ ሳቢያ የተነሳው ተቃውሞ መንግሥት በወሰደው የማመቅ እርምጃ ሁነኛ ምላሽ ሳያገኝ በእንጥልጥል ነበር የቀረው፡፡ ይህ ችግር ባለበት ሁኔታ ደግሞ የነጋዴውን ሰርቶ የመኖር አቅም የሚፈታተን አሉታዊ የግብር ትመና መጣሉ የተዳፈነውን ተቃውሞ ቀስቅሶታል፡፡ ይሄ አጀንዳ ማቀጣጠያ ነው እንጂ ዋናው መንስኤ ለዘመናት የተከማቹ አስቀድሜ የገለፅኳቸው ችግሮች ድምር ነው፡፡ እነዚህ ችግሮች ታይቶ በማይታወቅ ደረጃ ለብዙ የህይወት መጥፋት ምክንያት ሆነዋል፡፡ ኢንዱስትሪና ፋብሪካዎችን እስከ ማቃጠል አድርሷል፡፡ ይሄ በኢትዮጵያ ታሪክ ውስጥ የተለመደ አይደለም፡፡ ምናልባት በፊት አውቶቡሶች ይሰበሩ ይሆናል እንጂ ህዝቡ መጠቀሚያው በሆኑ መሰረተ ልማቶች ላይ ጉዳት ሲያደርስ ታይቶ አይታወቅም፡፡ ይሄ የቁጣው ደረጃ ምን ያህል እንደሆነ ነው የሚያሳየው፡፡
የእነዚህ አድማዎች ኢኮኖሚያዊ አንደምታዎች እንዴት ይገለጻል? በኢንቨስትመንት ላይ የሚያሳድረው ተጽዕኖስ?
ከኢንቨስትመንት ጋር በተያያዘ የሚያሳድረው ተፅዕኖ አለ፡፡ የውጭ ሀገር ኢንቨስተሮች ባለመረጋጋት መሃል ባለች ሀገር ኢንቨስት ለማድረግ ፍላጎቱ አይኖራቸውም፡፡ ሰላም በሌለበት ሀገር ውስጥ ንብረቱን ይዞ መጥቶ ኢንቨስት ለማድረግ የሚፈለግ አይኖርም፡፡ ሰላም፣ መረጋጋት፣ በቂ የኃይል አቅርቦት፣ የሰው ኃይል--- እነዚህን ፈትሾ ነው ኢንቨስተር የሚመጣው፡፡ አድማና አለመረጋጋት መኖሩን ሲያውቅ ግን ሃሳቡን ይሰርዛል፡፡ ኢንቨስተሮች ከዚህ ሽሽት ወደዚህ ሀገር ባመምጣታቸው ሊገኝ የሚችልን የውጪ ምንዛሬ ያሳጣል፣ የስራ እድል አይኖርም፡፡ ገበያውም በአቅርቦት ችግር መመታቱ አይቀርም፡፡ በተለይ የትራንስፖርት መቋረጥ በዚህ ላይ ቀጥተኛ ተፅዕኖ አለው፡፡ በሌላ በኩል፤ የሀገር ቤት ባለሀብትም በኢኮኖሚው ላይ የሚኖረውን አስተዋፅኦ መገደቡ አይቀርም፡፡ ገንዘቡን በአገሩ ላይ ኢንቨስት ከማድረግ ይልቅ በውጭ ምንዛሬ እየለወጠ ወደ ውጪ ማሸሽ፣ ገንዘቡ ወደ ሀገሪቱ የኢኮኖሚ እንቅስቃሴ እንዳይገባ አፍኖ መያዝ፣ የራሱን የንግድ እንቅስቃሴ ማቀዝቀዝ፣ ፋብሪካ መዝጋትና የመሳሰሉት ውስጥ ይገባል፡፡ ይሄን የሚያደርገው ሀብቱ እንዳይባክን በመስጋት ነው፡፡ ይሄ ደግሞ በፊናው በኢኮኖሚ ውስጥ መንቀሳቀስ የሚገባውን ገንዘብ ይገድባል፣ ሀገሪቱ ከውጪ ገበያ ገቢ እንዳታገኝ ያደርጋል የንግድ ተቋማትና ፋብሪካዎች በቆሙ ቁጥር ለኪሳራ መዳረጋቸው አይቀርም፡፡ በዚህ ደግሞ መንግስት ከግብር የሚያገኘውን ገቢ ያጣል፡፡
ሌላው ደግሞ ማህበረሰቡ በቁጣ ተነሳስቶ የሚያደርሰውን ውድመት ተከትሎ፣ መንግስት ንብረቱን ለባለቤቶቹ የመተካት ግዴታ አለበት፡፡ እንደ አጋጣሚ ሆኖ ሀገሪቱ ለኩባንያዎች አለማቀፍ የኢንሹራንስ ሽፋን የላትም፡፡ ይህ አለመኖሩ ደግሞ መንግስት ለወደመ ንብረት ከበጀቱ ላይ ቀንሶ ለተጎጂዎች እንዲከፍል ነው የሚያስገድደው፡፡ ሌላው በዚህ ሂደት ውስጥ እንዲህ ያሉ ውጥረቶች ያለ መፍትሄ በተራዘሙ ቁጥር በማህበረሰቡ ውስጥ ግንኙነቱ ይላላል፣ አንድነቱ አደጋ ላይ ይወድቃል፣ ሰዎች ተስፋ በመቁረጥ ስደትን አማራጭ ሊያደርጉ ይችላሉ፡፡ ችግሮቹ  በጊዜ እልባት ካላገኙ በሰው ልብ ውስጥ ተቀብረው የሚፈነዱበትን የተመቻቸ ሁኔታና ጊዜም ሊጠብቁ ይችላሉ፡፡
በዚህ ግርግር መሃል ደግሞ በአቋራጭ ለመክበር የሚፈልጉ ሰዎች ገበያ ላይ ያሉ እቃዎችን ይደብቃሉ፣ በገበያው ላይ እጥረት ለመፍጠር ይሯሯጣሉ፡፡ ይሄ ደግሞ በህብረተሰቡ ላይ የገበያ እጥረት ይፈጥራል፤ የዋጋ ንረትም ያስከትላል፡፡ ከዚህ ሲያልፍ ደግሞ የቱሪዝም ገቢያችን ይቀዛቀዛል፡፡ ጎብኚዎች ቅድሚያ ለህይወታቸው ደህንነትና ሰላም ይፈልጋሉ፡፡ ቱሪስቶች ባለመምጣታቸው ደግሞ በዘርፉ ሰንሰለት ውስጥ ያሉ ሆቴሎች፣ አስጎብኚዎች፣ የትራንስፖርት አገልግሎት ሰጪዎች ይጎዳሉ፡፡
አገሪቱ ለውጭ ኢንቨስተሮች  አለማቀፍ ኢንሹራንስ መግባት ያስፈልጋታል ማለት ነው?
ኩባንያዎች ላይ ጉዳት የሚደርሰው በተቃውሞ በሚፈጠር ቀውስ ብቻ አይደለም፡፡ በየጊዜው የክልል ድንበር ግጭቶች፣ የብሔር ግጭቶች የመሳሰሉ ይፈጠራሉ፡፡ በዚህ መሃል ንብረት ሊወድም ይችላል፤ የውጭ ሀገራት ሰዎች ንብረት ሲወድም በሀገር ውስጥ ኢንሹራንስ ለመሸፈን ከባድ ነው፡፡ ስለዚህ የውጭ ሀገር ኢንሹራንስ መኖሩ እንደ ኢትዮጵያ ላለ ሀገር በጣም ጠቃሚ ነው፡፡ እነዚህ ኢንቨስተሮች አደጋ በንብረታቸው ላይ ቢደርስ፣አለማቀፍ አስተማማኝ ኢንሹራንስ እንደተገባላቸው ሲያውቁ ይረጋጋሉ፡፡ እንደ አንድ ሁነኛ ዋስትና ነው የሚቆጥሩት፡፡ ይህ ባልሆነበት ለእነዚህ ሰዎች ለንብረታቸው መተኪያ ስትከፍል ዞሮ ዞሮ የህብረተሰቡ ኪስ ነው የሚጎዳው። ለመሰረተ ልማት ይውል የነበረውና ከሰው የተሰበሰበው ግብር ነው ተመልሶ ለነዚህ ሰዎች የካሳ ክፍያ የሚውለው። ከዚህ ውጭ  መንግስት ያለ አግባብ ተጨማሪ ገንዘብ ካላተመ በስተቀር ከየትም አይመጣም፡፡
በእንዲህ ያሉ አድማዎች የመጀመሪያ ተጎጂ የሚሆነው ማን ነው? መንግሥት ላይ የሚፈጥረው ጫናስ ምን ያህል ነው?
ሁለት የማህበረሰብ ክፍሎች በጣም ተጎጂ ይሆናሉ፡፡ አንደኛ ለእለት ጉርሳቸው በየእለቱ የሚያገኙትን ገቢ የሚያጡ ዜጎች አሉ፡፡ በሸክም ስራ፣ በጥበቃ፣ በጫኝ አውራጅነት የሚሰሩ፣ የእለት ገቢ ላይ ብቻ ተመስርተው የሚኖሩ አሉ፡፡ እንቅስቃሴዎች ሲቆሙ እነዚህ ሰዎች የመጀመሪያዎቹ ተጎጂዎች ይሆናሉ፡፡ ሁለተኛ በአጠቃላይ ማህበረሰቡ ተጎጂ ይሆናል፡፡ አብዛኛው ሰው ኑሮው ከእጅ ወደ አፍ ነው፡፡ በአቅርቦቱ መቋረጥ የእለት ጉርሱን የሚያጣው የማህበረሰብ ክፍል ቀላል አይደለም፡፡ ሶስተኛ ተጎጂ የሚሆነው ሀገር ነው፡፡ መንግስት ተገቢውን ግብር የማግኘት እድሉን ስለሚያጣ ስራ መስራት አይችልም፡፡ እንቅስቃሴ የሌለበት ኢኮኖሚ ደግሞ የሚያስከትለው ተፅዕኖ ቀላል አይሆንም፡፡ ከፍተኛ አለመረጋጋትም ያስከትላል፡፡
የእነዚህ አድማዎች ፖለቲካዊ አንድምታስ ምንድን ነው?
እነዚህን አድማዎች በመጀመሪያ ያመጣው ህብረተሰቡ በመንግሥት ላይ ያለው መተማመን መሸርሸሩ ነው፡፡ መንግስት ለጥያቄ ምላሽ ይሰጣል ብሎ የሚያምን ማህበረሰብ፣ ለህዝባዊ እምቢተኝነት ወይም ለአድማ አይነሳሳም፡፡ መንግስት ቦታ እያጣ መምጣቱን ማሳያው ይኸው ህዝባዊ እምቢተኝነት ነው፡፡ አንድ ማህበረሰብ በራሱና በቤተሰቡ ላይ ጉዳት ሊያስከትል የሚችል እንቅስቃሴ ሲያደርግ ተስፋ የመቁረጥ ምልክት መሆኑ  ግልፅ ነው፡፡ የስራ እድል የፈጠረለት ተቋም ላይ እርምጃ ሲወስድ ተስፋ የመቁረጥ ምልክት ነው፡፡ አሁን ከግብር ጋር በተያያዘ የመጣው እምቢተኝነት፣ የመጀመሪያው እምቢተኝነት ተቀጥላ ነው፡፡ ስለዚህ በቀጣይ አመት ምን እንደሚፈጠር ለመገመትም አስቸጋሪ ነው፡፡ ለምሳሌ የተጣለው ግብር ከ40 በመቶ በላይ ስህተት ነበር ብለዋል፤ ጠ/ሚኒስትሩ፡፡ 40 በመቶ ስህተት ካለ፣ ለእርማትም የሚመች አይደለም ማለት ነው፡፡ ስለዚህ ወዲያው ነው መቆም የነበረበት፡፡ እንደገና እንደ አዲስ ነው ጉዳዩ መታየት ያለበት፡፡ በዚህ ምክንያት ለተፈጠረው ምስቅልቅል፣ ቁጣ እና አለመረጋጋት ኃላፊነትስ የሚወስደው ማን ነው? መንግስት ትመናው 40 በመቶ  ስህተት አለው ብሎ ካመነ፣ለተፈጠረው ችግር ኃላፊነት መውሰድ አለበት፡፡
እነዚህ አድማዎች በመንግስት ለይስ የሚኖራቸው ተፅዕኖ ምን ያህል ነው?
ህዝቡ መጀመሪያ የሚያደርገው እነዚህ በደሎችና እሮሮዎችን ማሰማት ነው፡፡ ለእነዚህ ምላሽ ሲያጣ ደግሞ ተደራጅቶ በአንድ ላይ ወጥቶ መንግሥት ላይ ግፊት ይፈጥራል፡፡ ጉዳዩ ወደ ዲሞክራሲ፣ ፍትሃዊ የሀብት ክፍፍል፣ የህግ የበላይነት ጥያቄዎች ሊያመራ ይችላል፡፡ ይሄን ደግሞ ህዝብ በራሱ እንዲከውነው እየተገደደ ነው ያለው፡፡ ምክንያቱም ሊወክሉት የሚችሉ ኃይሎች፣ አጀንዳውን ተቀብለው ማስተናገድ ላይ ውስንነት አለባቸው፡፡ ይሄ እንግዲህ ችግሩ ምን ያህል መልኩንና ቅርፁን እየለወጠ እንደመጣ ያሳያል፡፡ ህዝብ እዚህ ደረጃ ላይ ሲደርስ ደግሞ ሁኔታው አስቸጋሪ ነው የሚሆነው፡፡ የዲሞክራሲ፣ የህግ የበላይነት፣ ፍትሃዊ የሀብት ክፍፍል ጥያቄዎች በፊት በተቃዋሚ ፓርቲዎች ወይም በፕሬሶች ነበር የሚነሱት፡፡ እነሱ በየጊዜው እየተመናመኑ ከጨዋታ ውጪ ሲሆኑ፣ ህዝቡ ትግሉን ራሱ ለመውሰድ ተገደደ፡፡ ይሄ ፖለቲካዊ አንድምታው ቀላል አይደለም፡፡ ልክ እንደ አፄው ሥርአት ጊዜ ፋታ … ትንሽ ፋታ በማለት ብቻ የሚቆም አይደለም፡፡ ችግሮች በፋታ የሚፈቱ አይመስልም፡፡
ለዚህ ሁሉ ችግር መፍትሄው ምንድን ነው?
አጭሩ መፍትሄ ትክክለኛውን የህዝብ ስሜትና ጥያቄ አውቆ፣ ለዚያ የሚመጥን መልስ መስጠት ብቻ ነው፡፡ የህዝቡን ጥያቄ ሁሉ የውጭ ኃይሎች ሴራና የፀረ ሰላም ኃይሎች ነው ብሎ ችላ ማለት ዋጋ ያስከፍላል፡፡ መቼም ህዝብ አይሳሳትም። በዚህ ደረጃ በውጪ ኃይሎች የተሳሳተ ህዝብ አለ ከተባለም፣ ለስህተቱ ተጠያቂ የሚሆነው መንግስት ነው፡፡ ምክንያቱም መንግስት ለህዝቡ ተስፋ የሚሰጥ ስራ አልሰራም ማለት ነው፡፡ ሌላው መፍትሄ ከህዝቡ ጋር መወያየት ነው፡፡ ጊዜ ለሁሉም ነገር ወሳኝ ነው፡፡
በጊዜ መልስ መስጠትና ማረሚያ መውሰድ ከፀፀት ያድናል፡፡ ይሄ ጉዳይ ለሥርአቱ ብቻ ሳይሆን ለሀገሪቱም አደጋ ነው፡፡ ስለዚህ በሀገሩ ጉዳይ የተገለለ ሰው መኖር የለበትም፤ በሀገሩ ጉዳይ ማንም ሰው የመገለል ስሜት እንዲሰማው መደረግ የለበትም፡፡

 የዩኒቨርሲቲ ፕሬዝዳንትነት: ጥሪ፥ ችሎታ ወይስ ሹመት?
          “ከማይኾን ሹመት የሚመነጭ እኩይ ፍሬን እንደማየት አስከፊ ነገር የለም፡፡ በአንጻሩ፥ ችሎታ ያለው፣ ሠናይ እና ፍትሐዊ የኾነ ሰው በቦታው ላይ ሲሠየም እንደማየት በእጅጉ ደስ የሚያሰኝ ነገር የለም፡፡” (ቻርለስ ደብሊው ኤሊየት፣ ሐርቫርድ ዩኒቨርሲቲ 1869)
             ዶ/ር ዳኛቸው አሰፋ

      የአድማሱ ጸጋዬ ከአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ፕሬዝዳንትነት መነሣት፣ ለተቋሙ እንደ አንድ ትልቅ ዕድል ተደርጎ በብዙዎች ዘንድ ተወስዷል፡፡ ይኹን እንጂ፣ በቅርቡ በየብዙኃን መገናኛው በሰፊው እንደተሰማውና፣ በፓርላማ ፊት የፌዴራል ዋና ኦዲተር መሥሪያ ቤት ባቀረበው፣ “የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የ2007 በጀት ዓመት የኦዲት ግኝት ሪፖርት ውጤት” መሠረት፣ በዩኒቨርሲቲው ከፍ ያለ የፋይናንስና የንብረት አያያዝ ችግሮች በመገኘታቸው፣ የቀደሙት ዐሥር ያህል ዓመታት ተጨማሪ ምርመራ ማድረግ አስፈልጎ፣ ከውጪ ልዩ ኦዲተር ተሠይሞ፣ በምርመራ ላይ ባለበት በዚህ ወቅት፤ እኛም እንደ ዜጋ፤ “የዐቃቤ ሕግ ያለህ!” እያልን በምጮንህበት በዚህ ሰዓት፣ መንግሥት ፕሬዝዳንቱን “አምባሳደር” ብሎ በመሾም ከዐይን እንዲርቁ ማሸሹ፣ ብዙ ቁጭት እና ንዴት ቀስቅሷል፡፡ ይህ ድርጊት ከሞራል አንጻር ሓላፊነት የጎደለው ውሳኔ ይመስላል፡፡
በተጨማሪም፣ ነገሩን አስገራሚ የሚያደርገው፣ የኢ.ፌ.ዴ.ሪ. ፕሬዝዳንት ሙላቱ ተሾመ፣ ለአዲሶቹ አምባሳደሮች የሹመት ደብዳቤ ሲሰጡ፣ ይህን እውነታ ወደ ጎን ባደረገ መልኩ፣ በታላቅ የምስጋና ቃላት የተመላ “ቃለ-ቡራኬ” መስጠታቸውም ጭምር ነው፡፡ የሌሎቹን ተሿሚዎች ትቼ፣ አድማሱ ጸጋዬ እና አቶ ካሳ ተክለ ብርሃን፣ በውዳሴ የተመላው “ቃለ ቡራኬ” ተቋዳሽ መኾናቸው፣ በእጅጉ አስገራሚ ኾኖ አግኝቼዋለኹ፡፡ በተለይ አቶ ካሳ ተክለ ብርሃን በቦርድ ሊቀ መንበርነት፣ አድማሱ ጸጋዬ ደግሞ በፕሬዝዳንትነት ይመሩት የነበረው ዩኒቨርሲቲ፣ ከላይ የተገለጸው ዓይነት፣ ከፍ ያለ የፋይናንስና የንብረት አያያዝ ችግሮች እንደተገኘበትና እነዚህ ተሿሚ ግለሰቦችም፣ ማንም እንደሚገምተው፣ በቀዳሚነት ሓላፊነት መውሰድ እንዳለባቸው፣ ብሎም ከመወደስ ይልቅ ተወቃሽነታቸው የሚያመዝን ኾኖ ሳለ፤
“…በከፍተኛ የሀገር ስሜት የተጣለባችሁን ሓላፊነት ስትወጡ እንደነበረ ሁሉ፣ ወደፊትም በተሰማራችሁበት የዲፕሎማሲ መስክ ስኬታማ እንድትኾኑ እመኝላችኋለሁ፡፡…” የሚል፣ በአድናቆት የታጀበ “ቃለ ቡራኬ” እና መልካም ምኞት፣ ከኢፌዴሪው ፕሬዝዳንት አንደበት ሲቀበሉ መስማት፣ ፕሬዝዳንቱ የሚያቀርቡትን ንግግር በጥርጣሬ እንዲታይ ያደርገዋል፡፡
ቀደም ሲል በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ላይ የተሠራው ይፋ የወጣ ጥፋት የሚያጠያይቀውን ያህል፣ አሁን ደግሞ፤ የዩኒቨርሲቲው የፕሬዝዳንት ቦታ ገና ክፍት እንደኾነ በማመን፣ አዲስ ተሿሚ ከመሠየሙ በፊት ትኩረት የሚሹ ወሳኝ ጉዳዮችን ማዘከር አስፈላጊ ኾኖ ይታያል፡፡ ከዚህም አንጻር፣ ይህን ጽሑፍ ማቅረብ ወቅታዊና ተገቢ ኾኖ አግኝቼዋለሁ፡፡ በተጨማሪም ይህ ጽሑፍ፣ ከላይ በጥቅስ እንደተቀመጠው፣ ችሎታ ያለው ሰው በቦታው በሚሾምበት ጊዜ ደስ ማሰኘቱ እንደማያጠያይቀው ኹሉ፣ እኔም እንደ አንድ ዜጋ፣ ለወደፊቱ የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የተሻለ ሰው እቦታው ላይ ቢቀመጥ/ብትቀመጥ፤ ለሀገርም፣ ለተቋሙም፣ ብሎም ለመላው ማኅበረሰብ በእጅጉ ይበጃል፤ ከሚል እሳቤ የማቀርበው ጽሑፍ ነው፡፡ እዚህ ላይ ወደ ዋናው ጉዳይ ከመግባቴ በፊት፣ ስለ ጽሑፉ የአቀራረብ መንፈስ የሚገልጹ፣ ኹለት ነጥቦችን ላንሣ፡፡
የዚህ ጽሑፍ አቀራረብ በኹለት መደብ የተከፈለ ነው፡፡ በመጀመሪያ፣ የዩኒቨርሲቲን ትርጉምና ምንነት በጥቂቱ ከገለጸ በኋላ፤ ምን ዓይነት የትምህርት፣ የልምድ፣ የአስተዳደርና የሞራል እርካብ ያለው ሰው ለዩኒቨርሲቲ ፕሬዝዳንትነት መታጨት እንዳለበት በኹለተኛ ደረጃ ያትታል፡፡ በመጨረሻም፤ አጠር ያለ መደምደሚያ በማቅረብ ያጠቃልላል፡፡
የጽሑፉ አቀራረብ መንፈስ፣ በቀዳሚነት የሚነሣው፣ አሁን በገሐድ ያሉት ዩኒቨርሲቲዎች ላይ በማተኮር ብቻ ሳይኾን፣ ዩኒቨርሲቲ በሐሳብ ዓለምም ውስጥ ምን ሊኾን እንደሚገባው፤ ከማጠየቅም ጭምር ነው፡፡ በመኾኑም፣ “ዩኒቨርሲቲ ምንድር ነው?” ብለን መጠየቅ ብቻ ሳይኾን፣ ጥያቄያችንን ሰፋ አድርገን፣ “ዩኒቨርሲቲ ምን መምሰል አለበት?” የሚለውንም መጠየቅ በእጅጉ የተገባ ይኾናል፣ ብዬ አምናለሁ፡፡ ይህ አጠይቋዊ ትንታኔ፣ አቀራረባችንን ታሪካዊ ይዘት ካለው የወግ አተራረክ፣ ወደ ፍልስፍናዊ የአጠይቆ ሐቲት እንዲሸጋገር ያደርገዋል፡፡
ኹለተኛው አቀራረብና መንፈስ ደግሞ፤ በዚህ ጽሑፍ የማቀርበው ሐተታ ለውይይት እና ለሒሳዊ ትችት አንባቢን የሚጋብዝ ነው፡፡ ይህን ሐቲት ሳቀርብ፣ ራሴን ሙሉ በሙሉ ትክክለኛ እንደኾንኩ በማሰብ ሳይኾን፣ ለትቺና ሙግት ዝግጁ መኾኔን በማስታወስም ጭምር ነው፡፡ ይኸውም፣ ከሒስ በእጅጉ ተጠቃሚ እኾናለሁ፤ የሚል ልባዊ እምነት ስላለኝ ነው፡፡   
የዩኒቨርሲቲ ምንነት እና ተገብሮ፣
ይህ ሐሳብ፣ በ20ኛው መ/ክ/ዘመን አጋማሽ ላይ፣ በፕሮፌሰር ኤድገር ደብልዩ. ናይት የተሰበሰበውና አሁን እንደ ወትረ ህልው(ክላሲክ) ድርሳን የሚታየውን፣ “What College Presidents Say” በሚል ርዕስ፣ በርካታ የዩኒቨርሲቲ ፕሬዝዳንቶች፣ በመቶ ዓመታት ውስጥ፣ በአጠቃላይ ስለ ኮሌጅ ፕሬዝደንሲ የተናገሩትን ሐሳብ የያዘውን መድበል በመመርኮዝ የቀረበ ነው፡፡
የዩኒቨርሲቲን ምንነት አጠይቆ ይዘን ለመነሣት የምንገደደው፣ ዩኒቨርሲቲን ማን ይምራው? የሚለው መጠይቅ፣ “ከዩኒቨርሲቲ ምንነት” ተነጥሎ ስለማይታይ ነው፡፡ የዩኒቨርሲቲን ምንነት በተመለከተ፣ ኹለት ተፎካካሪ ፍልስፍናዎችን እናገኛለን፡፡ ኹለቱም በዩኒቨርሲቲ ምንነትና ፍልስፍና ላይ ኹነኛ አሻራ የተዉ ፍልስፍናዎች ናቸው፡፡ አንደኛው፥ ዩኒቨርሲቲን ከኀልዮታዊ (ሥነ ሐሳባዊ) ትኩረት አንጻር የሚያይ ሲኾን፣ ኹለተኛው ደግሞ፣ ዩኒቨርሲቲን በግብራዊ(ፕራክቲካል) መደቡ የሚቃኝ ወይም የሚፈትሽ ነው፡፡ አሁን ባለንበት ዘመን የተደረሰበት፣ የዩኒቨርሲቲን ምንነት የተመለከተ ስምምነት ግን፣ ኹለቱንም አዝማሚያዎችና ተቃርኖዎች አዋሕዶ ወይም አቻችሎ ማስኬድ አስፈላጊ እንደኾነ ያረጋግጣል፡፡
ከ100 ዓመታት በፊት፣ ካርዲናል ኒዩማን፣ “The Idea of A University” በሚለው አስደናቂ ድርሰታቸው ፣ ለዩኒቨርሲቲ የሚከተለውን ትርጉም ሰጥተውታል፡፡ ዩኒቨርሲቲ፥ “ዕውቀት፣ ሳይንስ፣ መረጃ፣ መርሕ፣ ምርምር፣ ግኝት፣ ሙከራ፣ የመላምት ግኝት እና የአእምሮን መልክአ ሐሳብ …ወዘተ. የሚዘረጋ ተቋም፣ ነው፡፡” ስለኾነም ለካርዲናሉ፤ ዕውቀት በራሷ የምንሻትና አቅደን ለመጎናጸፍ የምንጥርባት መዳረሻ ናት፡፡ ሌላ ተቀጥያ ዐቅድ አያስፈልጋትም፡፡ እንደ ካርዲናሉ አባባል፣ የትምህርት ዓላማ እና ግብ፣ “ትምህርት” ራሷ ብቻ ናት፤ ማለት ነው፡፡
በአንጻሩ አብርሃም ፍሌክስነር፣ “The Idea of A Modern University” በሚል ጽሑፋቸው ላይ፣ ቀደም ያለውን ሐሳብ የሚቃረን ሌላ ጽንፍ ያሳዩናል፡፡ እንደ ፍሌክስነር፣ ዩኒቨርሲቲ ማለት፣ “የተወሰነ ግብ እና ዓላማ ይዞ፣ ለማኅበረሰቡ ረብሕ፣ ተጨባጭ ነገር የሚያበረክት ተቋም ማለት ነው፡፡” ዩኒቨርሲቲ ከማኅበረሰቡ በላይና ባሻገር ለብቻው ተነጥሎ የሚቀመጥ ተቋም አይደለም፡፡ የሰውን ልጅ ለመጥቀም፣ የጊዜውን መንፈስ አቅፎ የያዘና ምርምርን ማዕከል አድርጎ የሚንቀሳቀስ ከመኾኑም በላይ፣ ወደ ውጤት ለመተርጎም ምንጊዜም የተሰናዳ ተቋም ነው፤ የሚል ንጻሬ አላቸው፡፡አሁን የተደረሰበት አስተሳሰብ፣ ኹለቱን የአመለካከት አፍላጋት ያዋሐደ ኾኖ እናገኘዋለን፡፡ ከዚህ ተነሥተው፣ ስለ ዩኒቨርሲቲ ምንነት ረዘም ላለ ጊዜ ጥናት እና ምርምር ያካሔዱ አሳቢዎች እንደሚነግሩን፣ የተቋሙ ተቀዳሚ ተልዕኮ፣ ሦስት ክፍሎችን የያዘ ነው፡፡ እነርሱም፤ አንደኛ፡- ዕውቀትን ለመጨበጥ መሻትን፣ ኹለተኛ፡- የተገኘውን ዕውቀት ለተማሪዎች ማስተላለፍን፣ ሦስተኛ፡- ዕውቀትን መተግበርን የሚሉ ክፍሎች ናቸው፡፡         
አንድ ዩኒቨርሲቲ፣ በምንም መልኩ የተመሠረተበትን የአእምሯዊ ፍጽምና ማሕቀፉን (አይዲያል) መልቀቅ የለበትም፡፡ ይህንንም ዓላማ በሚገባ ለመተግበር ሲባል፣ ለዩኒቨርሲቲው ማኅበረሰብ አካዳሚያዊ ነጻነት ያለገደብ እንዲሰጥና እንዲታወቅ የግድ ይላል፡፡ በተጨማሪም፣ ማንኛውም ዩኒቨርሲቲ የበጀት አቅራቢዎችን ግዳጅ ፈጻሚ ብቻ ሳይኾን፣ የራሱን ዓላማ አንግቦ የሚንቀሳቀስም ተቋም መኾን ይገባዋል፡፡
ተቋም ስንል፡-
የምንፈልገው ግብ ላይ ለመድረስ፣ ያሰበነውንና የወጠንነውን አካላዊ ህልውና የምንሰጥበት ነው፡፡ የትምህርት እንቅስቃሴም፤ ኮርሶችን፣ ካሪኩለሞችን፣ ፈተናዎችን፣ ዲፕሎማዎችን፣ ዲግሪዎችን ወዘተርፈ. ይዞ አካዳሚያዊ ሕይወትን እውን የሚያደርግ ነው፡፡ ተቋምን በአንድ ዐረፍተ ነገር መግለጽ ቢያስፈልግ፣ “የታሰበ ወይም የተወጠነ ዕቅድን፣ እንዲተገበር ወይም እውን እንዲኾን የሚያስችል፣” ማለት ነው። ያለተቋም፣ ሐሳብ ብቻውን ሕያው ሊኾን አይችልምና።
ዩኒቨርሲቲ ርእዩን በተቋሙ አማካይነት ገቢራዊ ማድረግ ካልቻለ፣ ርእዩ ብቻውን ትርጉም ያጣ ይኾናል። በመኾኑም ያንድ ዩኒቨርሲቲ የደረጃ ኹኔታ የሚለካው፣ በገነባው ተቋማዊ ብቃት ነው፡፡ እዚህ ላይ ልብ ልንለው የሚገባን፣ ተቋሙ የዩኒቨርሲቲን ፍጹማዊ ቅርጽና መልክ (አይዲያል) በተሟላ መልኩ ይይዛል ማለት አይደለም። ስለዚህ፣ በዩኒቨርሲቲው “አይዲያል” እና “በተቋማዊ  አደረጃጀቱ” መካከል ውጥረት መኖሩ ተፈጥሯዊ ነው፡፡ ኹለቱን ለማጣጣም በየጊዜው ሒሳዊ ፍተሻ በራሱ ላይ ማካሔድ ይኖርበታል፡፡
የሰዎች ሚና፡-
ያለ ሰው፣ ተቋም ብቻውን ምንም የሚያደርገው ነገር የለም፡፡ ስለኾነም፣ በተቋሙ አወቃቀር ውስጥ የሰዎች ሥፍራ ወይም ሚና ምን ይመስላል? ብሎ መጠየቅ ተገቢ ነው፡፡ አንድ ዩኒቨርሲቲ ወደ ልቅናው የሚመነደገው በውስጡ ባሉት ምርጥ ምሁራንና እነርሱም የማስተማር ተግባራቸውንና ምርምራቸውን ለማካሔድ የሚያስችል ምቹ ኹኔታ መፍጠር ሲችል ነው፡፡ በዩኒቨርሲቲውና በውስጡ ባሉት ሰዎች መካከል የሚታየው ባሕርይ፣ ተወራራሽና አንዱ በአንዱ ላይ የተመሠረተ ነው፡፡ ማንኛውም ዩኒቨርሲቲ፣ የተለያዩ ዓይነት ቅራኔዎችን የተሸከመ ነው፡፡ ፕሮፌሰር ዶናልድ ሌቪን፣ በዩኒቨርሲቲ ውስጥ ስላሉት ቅራኔዎችና ውጥረቶች ካቀረቡበት፣ “Powers of The Mind: The Renovation of Liberal Learning in America.” ከተሰኘው መጽሐፋቸው፣ አንዳንድ የትችት ነጥቦችን እንደ ዳራ በመውሰድ፣ እኔም በአዲስ አበባ ዩኒቨርሰቲ አሉ ብዬ ስለማምናቸው ውጥረቶች በአጭሩ ለማቅረብ እሞክራለሁ፡፡
ዩኒቨርሲቲ በኹለቱ ምክንያታዊነቶች መካከል፤
ዩኒቨርሲቲው እንደ አንድ የጥናት ተቋም በሚያቀርበው “ምክንያታዊነት” እና በበጀት አቅራቢው “ምክንያታዊነት” መካከል ውጥረት ይታያል፡፡ ዩኒቨርሲቲው እንደ ጥናት ተቋምነቱ የራሱ ጥሪ ይኖረዋል። በጀት አቅራቢው አካልም የራሱ ፍላጎት ይኖረዋል፡፡ የዩኒቨርሲቲው ምክንያታዊነት ለፈተና የሚዳረገውና ህልውናውም አጠያያቂ የሚኾነው፣ የተነሣበትን ዓላማ እና ግብ ወደ ጎን ትቶ፣ የበጀት አቅራቢውን ፍላጎት ለማስፈጸም ሥምሪት ሲያደርግ ነው። ይህ በሚኾንበት ጊዜ፣ የዩኒቨርሲቲው “ምክንያታዊነት” ለበጀት አቅራቢው “ምክንያታዊነት” መሥዋዕት እንዲሆን ተፈረደበት ማለት ነው፡፡ አዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲም ውስጥ በገሐድ የሚታየው እውነታ ይኸው ነው፡፡
 ለማሳያነት የሚከተሉትን እንጥቀስ፤ የዩኒቨርሲቲውን የተማሪ ቅበላ በተመለከተ፤ ብዛቱን የመወሰን ቀጥተኛ ሓላፊነት፣ የትምህርት አስተዳደሩ ድርሻ ኾኖ ሳለ፣ መንግሥት የፈለገውን ቁጥር ያህል ተማሪዎች እንዲገቡ መደረጉ፣ በትምህርቱ ጥራት ላይ የሚያስከትለው አሉታዊ ተጽዕኖ ችላ መባሉን ያሳያል፤ አንድን ዩኒቨርስቲ ብቁ ነው የሚያሰኘው፣ የመምህራን ችሎታ ብቻ ሳይኾን፣ ጥራትና ተወዳዳሪነት ያላቸውን ተማሪዎችንም ሲቀበል ነውና፡፡ አሁን ያለው የትምህርት ፖሊሲ ግን፣ በብዛት ላይ የተመረኮዘ በመኾኑ፣ ከዩኒቨርሲቲዎች የቅበላ አቅም በላይ ተማሪዎች እንዲገቡባቸው እየተደረገ ነው፡፡
በኹለተኛ ደረጃ፡- የትምህርት ውጤት አሰጣጥ፣ ከአስተማሪዎች ቁጥጥር ውጪ በኾነ መልኩ፣ በስኬል እንዲወሰን ከመደረጉም በላይ፣ መምህሩ ተማሪዎችን በውጤት አሰጣጥ ‘ደግፎ’ (የማይገባቸውም ቢኾኑ) እንዲያሳልፍ መደገደዱ፤ ሦስተኛው ግልጽ ማሳያ፤ ተማሪዎችም ኾኑ መምህራን “የአንድ ለአምስት አደራጃጀት” ተሳታፊ እንዲኾኑ መደረጉ የመሳሰሉት፤ “የዩኒቨርሲቲው ምክንያዊነት” አደጋ ውስጥ ለመውደቁ ማሳያዎች ናቸው፡፡
በሊብራል ትምህርት እና በሞያ
ትምህርት መካከል፤
‘በንድፈ ሐሳብ’ እና ‘በተግባር መካከል’፣ ‘በቁጥር’ እና ‘በጥራት’ መካካከል ውጥረት ይታያል፡፡ የነገረ ሰብእ፣ የሥነ ጥበብ፣ የፍልስፍና እና የታሪክ፣ በአጠቃላይም፤ የማኅበረሰብ ሳይንስ ትምህርቶች ወደ ጎን ተገፍተው፣ በተግባራዊ ሳይንስ፣ “ችግር ፈቺ ናቸው፤” ተብለው ለተቀመጡ ትምህርቶች ብቻ የተሰጠው ትኩረት፣ በንድፈ ሐሳብ እና በተግባር የትምህርት አዝማሚያዎች መካከል በዩኒቨርሲቲው የተፈጠረውን ውጥረት የሚያሳይ ነው፡፡
መኾን ይገባዋል ብዬ የማምነው ግን፣ ምሁራዊና ተግባራዊ መንገዱን አቻችለውና አጣምረው መጓዝ የሚችሉ ምሉዓን ተማሪዎችን የማፍራቱ ጉዳይ ነው፡፡ ይህም ማለት፥ ትጉህ፣ ውጤታማና የተኮተኮተ አእምሮ ያላቸው ዜጎች ማውጣት የዩኒቨርሲቲ ተቀዳሚ ተግባር ሊኾን ይገባል፣ ማለት ነው፡፡
ዩኒቨርሲቲ በማኅበረሰባዊ ጥቅም እና በብሔር ጥቅም መካከል፤
የዩኒቨርሲቲው ማኅበረሰባዊ (ኮምዩኒያል) ጥቅም፣ የበላይነት መያዙ ቀርቶ፣ የግልና የብሔር ጥቅም የሰፈነበት ግቢ ኾኗል፡፡ ይህም የግልንና የብሔርን ጥቅም ማሳደድ፣ ያልታወጀ ሕግ ኾኗል፡፡ እዚህ ላይ ሦስት ማሳያዎችን እንጥቀስ፤
ሀ. “ብሔርተኝነት”፡-
በሀገራችን፣ በፖለቲካ እና በማኅበረሰቡ ውስጥ እንደሚታየው፣ በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ፣ “በብሔር” እና “በዜጋ” መካከል ትልቅ ፍጥጫ አለ፡፡ ከግቢው ውጪ፣ “ብሔርተኝነት”፣ “ከሀገራዊነት”፣ የበለጠ የበላይነት እንደያዘው ኹሉ፤ በዩኒቨርሲቲውም፣ ብሔሮች በዜጎች ላይ ፍጹም የበላይነት አላቸው፡፡
“ብሔርተኝነትን” በመገለጫነት የያዙት ወገኖች፣ ጎሣንና ነገድን በበላይነትና እንደ ማንነት ብቸኛ መገለጫ በመያዝ፣ “ኢትዮጵያዊነትን” ባልተገባ መልኩ፣ የቀጨጨ ትርጉም እንዲይዝ ያደረጉት ሲኾን፤ የኹሉ ነገር መመልከቻ መነጽራቸው፣ ከብሔራቸው ህላዌና ተጠቃሚነት አኳያ ብቻ በሚመነጭ እይታ የተቃኘ ነው፤ ማለት ነው፡፡ በአንጻሩ “ዜግነትን” የያዙት ደግሞ፣ ኢትዮጵያዊነትን የምሉዕ ማንነታቸው ኹለንተናዊ መገለጫ በማድረግ የተቀበሉት ናቸው፡፡
በዩኒቨርሲቲው የሚታየው የብሔርተኝነት መንገሥ፤ ጠንካራ ፍልስፍናዊ ምርኩዝ የያዘ ሳይኾን፣ ከቅጽሩ ውጭ ባለው መንግሥታዊ የፖለቲካ ድጋፍ ላይ የተመሠረተ ነው። ይህን ውጫዊ አቅም በመተማመን፣ ብሔር ዘመሞቹ፣ በግቢው ውስጥ፣ በዜጎች ላይ ጫና እና ግፊት ያሳድራሉ፡፡
ለ. የአስተማሪዎች ግለኝነት፡-
በመሠረቱ፣ የአስተማሪነት ተቀዳሚ ዓላማ፣ ማስተማርና ምርምር ሲኾን፣ መምህራኑም ሙሉ ጊዜያቸውን እዚህ ተግባር ላይ ማዋል እንደሚኖርባቸው ያጠይቃል፡፡ አኹን በየኒቨርሲቲው የሚታየው የአብዛኛው መምህራን አካሔድ ግን፣ በግል ጥቅም ሩጫ የተጠመደ ኾኗል፡፡ ከማስተማሩ ይልቅ፣ ከመንግሥት እስከ ግል ተቋማት ድረስ በሞያቸው ተሠማርተው እየሠሩ ስለሚገኙ፣ “በማኅበራዊ ሠናይነት” እና “በአስተማሪዎች ግለኝነት”፣ መካከል ቀላል ያልኾነ መገዳደር ይታያል፡፡
ሐ. የተማሪዎች፣ የተማሪነት ዲሲፕሊን ድቀት፡-
በዩኒቨርሲቲው ቅጥር ግቢ፣ በፈተና የተማሪዎች መኮራረጅና የጥናት ጽሑፎችም ግልበጣ በገሐድ እየታየ ነው። ተማሪዎች፥ ያልሠሩትን እንደሠሩ፣ ያልጻፉትን እንደጻፉ፣ ያልተመራመሩትን እንደተመራመሩ እያደረጉ የማይገባቸውን ውጤት ለማግኘት እየተሯሯጡ እንደ ኾነ ማስተዋል ብዙም አይከብድም፡፡
 በመኾኑም፤ በአንድ በኩል፣ ለማወቅ በመፈለግ፣ በትጋት እና በድካም ለማደግ፣ በሌላ በኩል፤ ያለልፋትና ያለድካም ውጤት ለማግኘት በሚደረግ የትንቅንቅ ጉዞ መካከል ግልጽ ቅራኔ የሚታይበት ግቢ ኾኗል፡፡
በዩኒቨርሲቲ ልቀት እና ዝቅጠት(Excellence vs. Mediocrity) መካከል ያለ ውጥረት፤
የዚህ ውጥረት መገለጫዎች በመምህራኑም ኾነ በተማሪዎቹ ላይ የሚታዩ ናቸው፡፡
ሀ. የዩኒቨርሲቲ መምህራን፡-
ዩኒቨርሲቲ በመሠረቱ የልሂቃን ማዕከል ነው። እዚህ ተቋም ውስጥ በምሁራዊነት ለመሠየም ልሂቅነት ያሻል፡፡ የዩኒቨርሲቲው የቆየ ባህልም ይህንኑ ልማድ የሚያመለክት ነው፡፡ አሁን ግን ልሂቃዊነት እንደ መሥፈርት መወሰዱ ቀርቶ፣ የፖለቲካ ቅርርቦሽ ተተክቷል፡፡ የትምህርት ውጤታቸው ዝቅተኛ ቢኾንም፣ በፖለቲካ አስተዋፅኦና በብሔር ተዋፅኦ ተመርጠው በመምህርነት መንበር ላይ እንዲቀመጡ ኾነዋል። ይህ ዓይነቱ አካሔድ፣ በልሂቃዊነትና በጥራዝ ነጠቅነት መካከል ትልቅ መገዳደር እንዲከሠት አድርጓል፡፡
 ለ. ተማሪዎች፡-
እንደ ደራሽ ውኃ እየጎረፉ በሚገቡት ተማሪዎችና የትምህርቱን ጥራት በማስጠበቅ መካከል ትልቅ ውጥረት አለ፡፡ አንዳንድ ፈላስፎች ይህን ዓይነቱን መጥለቅለቅ፣ “ሶሻል ሱናሚ” ይሉታል፡፡ በብዙዎች ትችት ውስጥ፣ የጥራት እና የቁጥር ተቃርኗዊ ወደር ተደጋግሞ ይነሣል። ኾኖም ጥራት ስንል፣ በተቀመጠው ግብ የሚለካ በመኾኑ፣ የጥራት ጥያቄ ከትምህርት ዓላማ ተነጥሎ የሚታይ አይደለም፡፡ ይህም ማለት፣ ጥራት የሚለካው፣ የትምህርትን ዓላማ እና ግብ መሠረት በማድረግ ነው፡፡
የዩኒቨርሲቲ ፕሬዝዳንትነት በቀደሙ
ፕሬዝዳንቶች ዐይን፤
“አንድ የዩኒቨርሲቲ ኮሌጅ ወጣት ፕሬዝዳንት፣ ዕድሜው ከገፋና ለዓመታትም የዩኒቨርሲቲ ፕሬዝዳንት ከነበረ ሽማግሌ ጋራ ስለ ዘመነ ፕሬዚደንሲያቸው አስቸጋሪ ጊዜያት ሲወያዩ፣ ወጣቱ ፕሬዝዳንት፣ ‘ለእኔ የመጀመሪያ ዓመቱ ዘመኔ በጣም ከባድ ነበር፣’ ይለዋል። ሽማግሌው ቀበል አድርጎ፣ ‘በእኔ ተሞክሮ ደግሞ፣ ሦስተኛው ዓመት ላይ ነው እንደ ፕሬዝዳንት ችግር የገጠመኝ፤ ምክንያቱም፣ ሦስተኛ ዓመት ላይ መምህራኑ በሙሉ ውሸታምና አጭበርባሪ መኾኔን አወቁብኝ’ ይለዋል፡፡” (The College Presidents. p,16.)
የእኛው ‘ጎበዝ’ ግን፣ ዕድለኛ ኾኖ፣ እንደ ሽማግሌው ፕሬዚዳንት፣ በሦስተኛው ዓመትም ባይኾን፣ በስድስተኛው ዓመት ላይ፣ አብዛኛው የዩኒቨርሲቲው ማኅበረሰብ ማንነቱን ሊረዱት ችለዋል፤ ከጥቂት ካድሬዎች በስተቀር፡፡
ከላይ በጠቀስነው የፕሮፌሰር ኤድገር ደብልዩ ስብስቦች፣ የሚከተለው የሐርቫርድ ፕሬዝዳንት ቻርለስ ደብልዩ ኤልየት ጥቅስ ይገኛል፡-
“ዩኒቨርሲቲ ለዓምባገነኖች በእጅጉ የራቀ ቦታ ነው። መማር በባህርይዋ ሪፐብሊካን ናትና፡፡ በትምህርት ዓለም የምናደንቃቸው እና የምናከብራቸው ሰዎች ይኖራሉ እንጂ፣ እንደ ጌቶች የምንወስዳቸው ሰዎች አይኖሩም፡፡”
ከኹሉ አስቀድሞ፣ ዩኒቨርሲቲን በበላይነት የሚያስተዳድሩ ሰዎች፣ በሥራቸው የሚገኘውን የዩኒቨርሲቲ ማኅበረሰብ፣ በእኩል ዐይን ማየት ይገባቸዋል፡፡ እዚህ ላይ፣ የአንድ ሓላፊ ድርጊት፣ ሰውን በእኩልነት ከማየት የሚመነጭ እንጂ፣ ከወገናዊነት አንጻር የሚፈጸም ሊኾን አይገባውም። የድርጊቱ መሠረትም፣ ሕግን ለኹሉ እንዲኾን አድርጎ እንደሚያወጣ ሕግ አውጪ መርሐዊነት ሊቃኝ ይገባል። ይህን በሚያደርግበት ጊዜ፣ ለአጠቃላይ የተቋሙ ፍላጎት ሲል፣ ጓደኞቹንም ኾነ ወገኖቹን የሚያስቀይም እንኳ ቢኾን ወደ ኋላ ማለት አይኖርበትም፡፡
አንድ ፕሬዚዳንት፣ ሩኅሩኅ ጠባይ ሊኖረው ይገባል። ይህም ማለት ራሱን በሌሎች ቦታ አድርጎ፤ “እኔ በዚህ ቦታ ብኾንስ” ብሎ ራሱን በሌሎች ጫማ ውስጥ ከትቶ የሚያይ ሲኾን፣ የሥነ ልቡና ሊቃውንት “የማስተዋል ሐሞት”(perceptual courage) የሚሉት፣ እንዲኖረው ያስፈልጋል፡፡ እዚህ ላይ የቀድሞው ፕሬዝዳንት አድማሱ ጸጋዬ፣ ይኸው የማስተዋል ሐሞት እንዴት እንደሌላቸው ደጋግመን በተለያየ ጊዜ አይተናል፡፡ ከኹሉም በላይ፣ ማንም በማይስተው መልኩ ያሳዩትን ሞራላዊ ድቀት እንጥቀስ። እንደሚታወቀው ዶ/ር መረራ ጉዲና፣ ዩኒቨርሲቲውን ከ30 ዓመታት በላይ አገልግለው 60 ዓመት ሲሞላቸው፣ የኮንትራት ዕደሳ ሊሰጣቸው ይገባ ነበር፡፡ ዲፓርትመንቱና ኮሌጁም እንደሚፈልጋቸው በደብዳቤ ማሳወቁም ይታወሳል። በምትኩ ግን፣ በአድማሱ ጸጋዬ ውሳኔ ያለምንም በቂ ምክንያት፣ ከዩኒቨርሲቲው ተባረዋል፡፡     
የዩኒቨርሲቲው ቢሮና መንበር ዘላለማዊ ሳይኾን ጊዜያዊ ነው፡፡ በዚህች ውስን ጊዜ የምትሠራውና የምትወስነው አሉታዊ ወይም አዎንታዊ ጉዳይ ግን፣ ዘላቂ አንድምታ ሊኖረው ይችላል ብለህ አስብ፡፡ የትኛውም ዓይነት ሓላፊነት ላይ ስትኾን፣ የውሳኔህ ወይም የተግባርህ ስኬት በጎም ይሁን መጥፎ፤ ለታሪክ ሚዛን ትቶ ማለፍ ተገቢ ነው፡፡
አንድ ፕሬዝዳንት፣ በምክክር ሊያምን ይገባዋል። ይህ ማለት ግን ከአማካሪዎቹ ጋራ በአንድነት መወሰንን አይመለከትም፡፡ ውሳኔ በጎ የሚኾነው፣ ፕሬዝዳንቱ የብቻውን ጥሞና ወስዶ፣ አሰላስሎ የሚደርስበት ሲኾን ነው። ጽሞናው፣ ያገኛቸውን ምክሮች የሚመዝንበትን ዕድል ይሰጠዋል። ፕሬዚዳንቱ፣ በዩኒቨርሲቲው ማኅበረሰብ ውስጥ፣ በአንድ በኩል ተሳታፊ በሌላ ጎኑ ደግሞ ገለልተኛ መኾን ይኖርበታል።
ከሊቀ ነቢያት ሙሴ ጀምሮ፣ እስከ ዛሬ ያልተሻረው የአስተዳደር ብሂል፣ ሥልጣንን በተዋረድ የመወከሉ ጉዳይ ነው፡፡ አንድ የአስተዳደር ሓላፊ ኹሉንም ነገር፣ “እኔ ብቻዬን እፈጽመዋለኹ፤” ብሎ ከተነሣ፣ ምናልባት ጥቂት ነገር ይፈጽም ይኾናል፡፡ ይችውም ጥቂት ተግባር ግን ዘላቂና የተሟላች ለመኾን አቅም ያንሳታል፡፡
አንዳንድ ሰዎች ፕሬዝዳንቱ ፍጹማዊ ሥልጣን ቢሰጠው ብዙ ነገር ሊከውን ይችላል፤ ሲሉ፣ ሌሎች ደግሞ ከላይ የጠቀስናቸውን የሐርቫርድ ዩኒቨርሲቲ ፕሬዝዳንትን ሐሳብ በመጋራት፣ የአንድ ሰው ጠቅላይነት ለመንግሥት በጎ ያለመኾኑን ያህል ለዩኒቨርሲቲም በተመሳሳይ ጥሩ አይኾንም ብለው ይሞግታሉ፡፡ እንዲያውም አውቶክራሲ አደገኛ መንገድ በመኾኑ፣ ሔዶ ሔዶ ችግርና ውድቀት ያስከትላል፤ ይላሉ፡፡
አውቶክራሲ፣ አብዛኛውን ጊዜ የሚመረኮዘው በእብሪታዊው ኹሉን አወቅነት መንፈስ ላይ በመኾኑ ተቀባይነት አይኖረውም፡፡ ዩኒቨርሲቲ ውስጥ፣ ሐሳብን አሸናፊና የሚያሠራ ማድረግ የሚቻለው፣ በውይይት እንጂ በጉልበት እና በፖለቲካ ጫና መኾን የለበትም፡፡
የፕሬዚዳንት ምርጫ፤
በአሜሪካ ዩኒቨርሲቲዎች የ100 ዓመታት ሒደት ውስጥ እንደታየው፣ በርካታ ኮሌጆች የተቋቋሙት፣ በፕሮቴስታንት ሚኒስትሪዎች አማካይነት ስለኾነ፣ በአብዛኛው ኮሌጆቹን በፕሬዝዳንትነት የመሩት የቤተ እምነቱ ካህናት ነበሩ። በ20ኛው መ/ክ/ዘ መባቻ ላይ ደግሞ፣ ለፕሬዝዳንትነት ምርጫ፣ ንግድን የመምራት ችሎታ አስፈላጊ ኾኖ ስለነበር፣ የኮርፖሬት መሪዎች ኮሌጆቹን በፕሬዝዳንትነት እንዲመሩ ተደርጎ ነበር፡፡ በ20ኛው መ/ክ/ዘ መካከል ላይ ግን የሚከተሉትን ሦስት መሥፈርቶች ያሟሉ፣ ማለትም፥ የዳበረ ስኮላርሺፕ እና የአስተዳደር ችሎታ ያላቸው፤ የሥነ ትምህርት ጠበብት የኾኑና የሥነ ምግባር አርኣያነትን የተላበሱ ሰዎችን በፕሬዝዳንትነት መመደብ የተሻለ እንደኾነ ታመነበት፡፡
ሀ. ስኮላርሺፕ፡-
በምሁርነቱ ነቅዕ የሌለበት እንዲሁም፣ ከተማረው ትምህርት ባሻገር የእይታ አድማሱ የሰፋ፣ በተለያዩ የዕውቀት መስኮች ላይ የማወቅና የማድነቅ ፍላጎት ያለው፣ ዘወትር ራሱን ለማስተማር የሚተጋ መኾን ይኖርበታል፡፡
ትምህርት፣ ራሱን የቻለ የማያልቅ ጉዞ መኾኑን የተረዳ፣ ኹሌም ለመማር የተዘጋጀ፣ ከየትኛውም የትምህርት መስክ ይምጣ ኹሉንም የትምህርት ዓይነቶች የሚገነዘብ፣ የነገረ ሰብእንና የሳይንስን ባህሎች በአድማሳዊ እይታ አገናኝቶ ተዋስኦ መፍጠር የሚችል መኾን ይኖርበታል፡፡
ከኹሉም በላይ፣ ዩኒቨርሲቲ የስኮላሮች አምባ ነው። እነኚህ ስኮላሮች ተቀዳሚ ሥራቸው፣ እንደ ኢንደስትሪ ወይም ፋብሪካ ዕቃ እምራች ሳይኾኑ፣ እእምሮን ኮትኳችና ተከባካቢ ናቸው፡፡ ለአብነት ያህል፣ ምሁሩ፣ አሶሼት ፕሮፌሰር ሲባል፣ ኦፊሴል ለመኾን እንደበቃው አነጋገር “ተባባሪ” ማለት ሳይኾን፣ የዩኒቨርሲቲው፣ የምሁራን ኮምዩኒቲ አባል ኾነ ማለት ነው፡፡ ይህ ማኅበር፣ እስከ ዘመናችን ድረስ ቁልፍ የዩኒቨርሲቲ ማዕከል ነው፡፡ የምሁራኑን ማኅበር ድጋፍ ያላገኘ ተመራጭ ፕሬዝዳንት፣ በምንም መልኩ ለወንበሩ የሚመጥን ይኹንታ ሊያገኝ አይችልም፡፡ ይኸውም፣ ተመራጩ ፕሬዝዳንት፣ በችሎታው ልቅና በምሁራኑ ማኅበር ዘንድ ጥያቄ የማይነሣበትና ክብርና አመኔታ የተቸረው ሊኾን ይገባዋል፤ ማለት ነው፡፡
ለ. የአስተዳደር ችሎታ፡-
የትምህርት አስተዳደር ከማንኛውም ዓይነት የአስተዳደር ዘይቤ ልዩ ነው፡፡ ለምሳሌ፣ የኮርፖሬሽን ፕሬዚዳንት እና የዩኒቨርሲቲ ፕሬዚዳንት ሰፋ ያለ ልዩነት አላቸው። የዩኒቨርሲቲው ፕሬዚዳንት  በአስተዳዳሪነቱ፣ ሰፋ ያለ የማደራጀት አቅም አለው፡፡ ሓላፊነትን እንደሚገባ ለማደልና ሰዎችን በሚመጥናቸው ቦታ ለማስያዝ፣ ሰብእናቸውን የመለካት ችሎታ ሊኖረው ያስፈልጋል፡፡
የሥርዓተ ትምህርትና የትምህርት ፍልስፍና አረዳዱ ከፍ ያለ መኾን ይገባዋል፡፡ ካሪኩለም እና የትምህርት ፍልስፍና የጎደለው አስተዳዳሪ፣ ቻርት እንደሌለው የመርከብ ካፒቴን ነው፡፡ ከዚህ እውነታ ስንነሣ፣ አሁን በቅርቡ፣ የኢፌዴሪ ትምህርት ሚኒስትር ኾነው የተሾሙት ዶ/ር ጥላዬ ጌቴ፣ በትምህርታቸውም ኾነ በሥራቸው፣ የሥነ ትምህርት ባለሞያ መኾናቸው፤ ለበርካታ ዓመታት በፖሊቲካ ሹምነት ብቻ ሲያዝ የነበረውን ቦታ ሞያዊ ባርኮት እንደሰጠው አምናለሁ፡፡
ሐ. የሞራል ኮምፓስ
አንድ የዩኒቨርሲቲ ፕሬዝዳንት፣ ስኮላርሽፑ እንኳ ጠንካራ ባይኾን፣ በግብረ ገብነት የማይታማና በምግባሩ አርኣያ መኾን አለበት፡፡ ይህ ቦታ ሰዎች እግረ መንገዳቸውን፣ በፖለቲካ ኃይሎች ስለ ተወደዱ ብቻ የሚይዙት ሳይኾን፣ ራሱን የቻለ ጥሪ ነው፡፡ እንዲያውም አንዳንድ ፕሬዝዳንቶች፣ የዚህን ቦታ ሹመት እንደ መንፈሳዊ ጥሪ አድርገው የሚቆጥሩትም አሉ፡፡
ማጠቃለያ
በመንግሥት እና በዩኒቨርሲቲ መካከል ያለውን ግንኙነት አስመልክቶ፣ የ20ኛው መ/ክ/ዘ  ጀርመናዊ ፈላስፋ፣ ካርል ያስፐርስ፣ “The Idea of the University” በሚል ርእስ ካቀረቡት ድርሳን ውስጥ ጥቂት ነጥቦችን እንዋስ፡፡ ዩኒቨርስቲ፣ በመንግሥት ውስጥ ያለ “መንግሥት” አይደለም። እንደ ማንም የመንግሥት ተቋምም፣ ፖሊሲ አስፈጻሚም አይደለም፤ በማለት በስፋት ያብራራሉ፡፡ ታድያ ምንድር ነው? ብለን እንጠይቅ፡፡ እንደ ያስፐርስ ገለጻ፣ ከመንግሥት ዐይን ነጻ ባይኾንም፣ እንደ ፖሊሲ አስፈጻሚ አካላት በመዳፉ ውስጥ የወደቀ አይደለም፡፡ ይኸውም፣ የዩኒቨርስቲነት ርእዩን በተቀዳሚነት እያስፈጸመ፣ የማኅበረሰቡንም ችግር እያየ የሚፈቱበትን አማራጮች ማመላከት ሌላው ተግባሩ ነው፡፡  
በርግጥ ዩኒቨርሲቲ፣ ያለ መንግሥትና ማኅበረሰብ ድጋፍ ህልውና አይኖረውም፡፡ መንግሥት እየደገፈውም፣ እየደጎመውም በውስጥ ሥራው ጣልቃ መግባት አይገባውም። የመንግሥት ጣልቃ ገብነት፣ በታሪክ በተደጋጋሚ እንደታየው፣ የአድሏዊነት መልክ ይዞ ይቀርባል፡፡ ዩኒቨርሲቲ ልዕልናው ከተጠበቀ፣ በምንም መልኩ የተመሠረተበትን የአእምሯዊ ፍጽምና አይዲያል አያጣም፡፡
መንግሥት፣ ዩኒቨርሲቲውን ሱፐርቫይዝ የማድረግ ሓላፊነት አለበት፡፡ ኾኖም፣ ይህን ለመተግበር፣ ሥልጣን የሚሰጣቸው ግለሰቦች፥ ምሁራዊ ብቃት፣ የሥነ ትምህርት ዕውቀትና የማስተማር ተሞክሮ እንዲኖራቸው ግድ ይላል። መንግሥት፣ ከዩኒቨርሲቲ ጥቅም ፈላጊ ብቻ ሳይኾን፣ ዩኒቨርሲቲ የአንድ ሀገር “አእምሯዊ ንቃት” አስጠባቂ እንደኾነ ዕውቂያ ሊሰጥ ይገባዋል፡፡
ወደ አዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ስንመጣ፣ የመንግሥት ጣልቃ ገብነት ሦስት መልኮችን ይዞ እናገኘዋለን፡፡
“ዩኒቨርሲቲገዳም ስላልኾነና በተጨማሪም ቀለቡን የምሠፍርለት እኔ ስለኾንኩ፣ ከእኔ ጋር ተሰልፎየልማቱ አጋር መኾን አለበት፡፡ ቲዮሪ የሚለውን ወደኋላ አሽቀንጥሮ፣ ውጤት ተኮርምርምር ላይ ብቻ ማተኮር አለበት፡፡”
“ሀገሪቱ፣ ኅብረብሔራዊ ስለሆነች፣ የዩኒቨርሲቲ የአስተዳደር እና የአካዳሚክ ሥልጣኖች ምደባ በብሔር ተዋፅኦመኾን አለበት፡፡” በመኾኑም፣ እንደ ማንኛውም ዩኒቨርሲቲ፣ልሂቅነትና ስኮላርሺፕ የቦታና የሓላፊነት ማደላደያ መስፈርት መኾኑ ቀርቶ፣የብሔር ተዋፅኦና የፖሊቲካ ወገንተኝነት ቅድሚያ እንዲሰጠው ተደርጓል፡፡
የዩኒቨርሲቲ የተማሪ ቅበላ ምጣኔ መብት ተገፎ፣የገዢው ግንባር ሓላፊዎች፣ካድሬዎችና አባሎች ዩኒቨርሲቲ የሚያስገባ አቅምም ባይኖራቸው፣የአካዳሚክ ሳይኾን የፖለቲካ መስፈርት በመወሰዱ በጉልበትእስከ ፒኤችዲእንዲደርሱተደርጓል፡፡
የሀገራችንን ኹኔታ ለማሻሻል የምንችለው በትምህርት መኾኑ እየታወቀ፣ የትምህርትን ይዞታ የሚወስነው ግን መንግሥት በመኾኑ አዙሪት ውስጥ ገብተናል፡፡ ከዚህ አዙሪት ልንወጣ የምንችለው፣ ጠንካራ አመራር በመስጠት ዩኒቨርሲቲው ከተለጣፊነት መንፈስ ወጥቶ፣ መንግሥት የሚያቀርበውን መንገድ ብቻ ሳይከተል፣ በራሱ እግር ቆሞ ርእዩን መከተል ሲችል ነው፡፡
በቅርቡ የዩኒቨርሲቲውን ፕሬዝዳንታዊ ሥልጣን ይረከባል ወይም ትረከባለች ብለን የምንጠብቀው ወይም የምንጠብቃት ሰው/ሴት፣ ከበድ ያለ ሥራ ይጠብቃቸዋል፡፡ ሥራቸውን ክቡድ የሚያደርገው፣ የሚገቡበት ቤት የነተበና የፈራረሰ በመኾኑ ነው፡፡ በእኔ እምነት፣ ዩኒቨርሲቲው በሚከተሉት ሦስት ጉዳዮች ላይ ግንባታ ያስፈልገዋል። መጀመሪያ፣ የህልውና ማንበር ተግባር ቀዳሚውን ቦታ ይይዛል፡፡ ኹለተኛው፣ ዩኒቨርሲቲውን መልሶ በምሁራን ማኅበር(Community of scholars) እጅ ማስገባት ያስፈልጋል፡፡ ሦስተኛው፣ በግቢው ውስጥ የሰፈነውን የፍርሃት ድባብ አስወግዶ፣ አካዳሚያዊ ነጻነት ቦታውን እንዲይዝ ማድረግ ያስፈልጋል፡፡
ሀ. ልዕለ ተቋምነት(ኢንተግሪቲ)
ከኹሉም በላይ አንድ ዩኒቨርሲቲ ራሱን የሚገልጽበትና የሚገለገልበት አካዳሚያዊ ቋንቋ እና ይትበሃል እንዲኖረው የግድ ይላል፡፡ ይህንንም የምንለው፣ ላለፉት ጥቂት ዓመታት ይህ የአካዳሚው ሥርዓተ ስያሜና ይትበሃል(ኖሚና ክላቱራ) ወደ ጎን ተገፍትሮ፣ ለዩኒቨርሲቲው ባይተዋር የኾነ ፖለቲካና ካድሬያዊ ቋንቋ የበላይነት በመያዙ ነው፡፡ በመኾኑም፣ በአንድ በኩል፣ የዩኒቨርሲቲው አካዳሚያዊና ሞራላዊ ልዕለ ተቋምነት የቀደመ ቦታው ላይ ሊመለስ የሚችለው፣ አካዳሚያዊ ቋንቋውና ይትበሃሉ ሲመለስለት ነው፡፡ ለምሳሌ፡- አእምሯዊ ፍጽምናው(አይዲያል)፣ ስኮላርሺፕ፣ ተዋስዖ(ዲስኮርስ)፣ ርእይ፣ ደረጃ፣ ክሂል፣ ምርምር፣ አጠይቆ፣ አስተምህሮ፣ ትውፊት፣ ሥነ ውበታዊ ተማኅልሎ፣ ሜታ ፊዚክስ፣ ነገረ መለኰት፣ አንድምታ፣ ሥነ ድርሳን፣ ሰዋስው፣ ተጻሮ፣ የመሳሰሉት ቃላት ከነዐውዳቸው ሲመለሱ፣ የዩኒቨርሲቲው የሐሳቦች ዓምባነት ተመልሶ ቦታውን ይይዛል፡፡
ለ. የምሁራን ማኅበር
ከላይ ለማሳየት እንደሞከርኩት፣ ዩኒቨርሲቲ ማለት አንድ የምሁራን ኁባሬ የሚገኝበት ተቋም ማለት ነው፡፡ እዚህ ተቋም ውስጥ በአባልነት ሊገቡ የሚችሉት ሰዎች፣ በተወሰነ አካዳሚያዊ ደረጃ ውስጥ ያለፉ ብቻ ናቸው፡፡ ይኸውም፣ ባሳዩት ልሂቃዊ ብቃትና ስኮላርሺፕ ነው፡፡ ወደዚህ አዳራሽ ለመግባት በየዲሲፕሊኑ የተሰለፉ የዕውቀት አጋፋሪዎች ስላሉ፣ የእነርሱን ይኹንታ ሳያገኝ ማንም ሰው፣ የአዳራሹን ደጃፍ ሊዘልቅ አይችልም፡፡
ሐ. አካዳሚያዊ ነጻነት
አንድ ዩኒቨርሲቲ፥ ምርምር የማካሔድ፣ የምርምር ግኝቱን የማሳተምና ይፋ የማድረግ ምሉዕ ነጻነት ሲኖረው፣ አካዳሚያዊ ነጻነቱ ለመከበሩ አንዱ ማሳያ ነው፡፡ አንድ ምሁር በሚያደርገው ምርምር አንዳች እውነት ላይ ለመድረስ፣ ከተጽዕኖ ነጻ መውጣት አለበት፡፡ በተጨማሪም ምሁሩ፣ ከተሰለፈበት ዲሲፕሊን ውጪ እንደ አንድ ዜጋ በሀገሩ ጉዳይ ላይ፣ ሐሳቡን የማቅረብ መብት አለው፡፡ ይኸውም የዛሬ መቶ ዓመት ከጸደቁት አራት የአካዳሚ ነጻነት ምሶሶዎች ውስጥ አንዱ ማለትም፣ `Extra Mural Right` የሚባለው ነው። በአጠቃላይ፣ የዩኒቨርሲቲው አካዳሚያዊ ነጻነት ማለት፣ ውይይት እና የተለያዩ የሐሳብ ምሕዋሮች የሚንቀሳቀሱበት ነጻ ድባብ መፍጠር ማለት ነው፡፡
የጽሑፌ መደምደሚያ፣ በአካል ንጉሤ፣ “ፍላሎት”: የነፍስ አሻራዎች፤ በሚል ርእስ፣ በ2006 ዓ.ም. ካሳተመው አስደማሚ የግጥም መድበል ውስጥ፣ “ብርሃን ከላይ” የተሰኘችው የስንኝ ቋጠሮ ናት፡፡ የዩኒቨርሲቲው የአብርሆት ተልእኮ በግዑዝ የፎቆች ጋጋታ መወረሱን ታሳይልኛለችና ማሳረጊያዬ አድርጌያታለሁ፡፡
ብርሃን ከላይ
ብርሃን እንደ ዝሃ
ህላዌን እንደ ማግ
አድርቼና አቅልሜ
ሸምኜ
ሸምኜ
ያን የብርሃን ሸማ - ደርቤ ብለብሰው
ጨለማ ወረሰው
ለካንስ)
ብርሃን መኾን እንጅ - ብርሃንን መደረብ
 አይጠቅመውም ለሰው፡፡

    ከዕለታት አንድ ቀን፣ አንድ በጣም አባቱን የሚፈራ ልዑል ነበር፡፡ በፍርሃቱ ምክንያት የሠራውን ሥራ ሁሉ ለንጉሡ ከመናገር ይቆጠባል፡፡ ከሁሉም በላይ ልጅየውን፣ ልዑሉን የሚያስደነግጠው አባትየው ምንም ነገር ቢሰማ አይደነቅም፡፡ ስለዚህ፤ አንድ አዲስ ነገር ሲያቀርብለት፤
“በርታ፤ ገና ይቀርሃል” ይላል፡፡
ልዑሉም፤
“ምን ባደርግ ነው አባቴ ደስ ብሎትና ፍንድቅድቅ ብሎ፤ ‹ይሄ ነው የእኔ ልጅ! እንኳን ወለድኩህ! ዕውነተኛው የአባትህ ልጅ አንተ ነህ!!› የሚለኝ?” እያለ ወደ መኝታው ይሄዳል፡፡
አንድ ቀን ልዑሉ የአባቱን ጦር ይዞ ወራሪ ጉረቤት ሊዋጋ ከቤተመንግሥት ይወጣል፡፡ ጦርነቱ ድንበር ላይ የሚካሄድ ነው፡፡
ንጉሡ ልጅ፤ ጦር “እየመራ ወደ ጠረፍ መሄዱን ሰምቶ፣ ኖሮ ወደ ጦር ሜዳው” በድብቅ ሄደ፡፡
ጦርነቱ ተጀመረ፡፡ ከሁለቱም ወገን በርካታ ሰው እንደ ቅጠል ይረግፍ ጀመር፡፡ ልዑሉ አልተበገረም። “ወደፊት እንግፋ፤ ማፈግፈግ የለም!” እያለ እራሱ ከፊት ከፊት እየተወነጨፈ የሚያስደንቅ ጀግንነት አሳየ፡፡ ጠዋት የተጀመረው ጦርነት፣ ረፋዱ ላይ ጋብ ያለ ይመስልና ደግሞ እኩለ-ቀን አካባቢ እንደገና ትርምስምሱ ይወጣል፡፡ ውጊያው ይፋፋማል! ከሁለቱም ወገን ሰው ይረፈረፋል! በመጨረሻ ግን በርካታ ወገን ይለቅበት እንጂ ልዑሉ በአሸናፊነት ተወጣው! ድል የእሱ ሆነ! የማረካቸውን የጠላት ወታደሮች ይዞ፣ ወደ ቤተ-መንግሥቱ ተመለሰ፡፡
ከጥቂት ሰዓት በኋላ ንጉሡ፤ ልዑሉን ወደ ዙፋኑ እንዲቀርብ አስጠራው፡፡ ልዑሉ መጣ፡፡ የጦር ልብሱን፣ ጥሩሩን እንደለበሰ ነው የቀረበው! የጀግንነት ስሜቱ ፊቱ ላይ ይነበባል፡፡
ንጉሡ፡-
ልጄ ሆይ! ገድልህን አይቻለሁ፡፡ አንተ ሳታየኝ ጦር ሜዳ ድረስ መጥቼ ሁኔታውን ሁሉ ተከታትያለሁ። ወራሪውን በአኩሪ ደረጃ ድል መትተሃል! ለመሆኑ ለምን ሳትነግረኝ ወደ ጦር ሜዳ ሄድክ?
ልዑሉ፡-
አባቴ ሆይ! እኔ ልጅህ በራሴ የምኮራ መሆኔን እንድታውቅ እፈልጋለሁ፡፡ አንተ በቤተ መንግሥት ወግ አሳድገኸኛል፡፡ ፈረስ ጉግሥ፣ ጦር ውርወራ፣የሠራዊት አመራር፣ ዳኝነት፣ የጠላትን መረጃ ማግኘት፣ ካሰፈለገ መጥለፍ ሁሉ አስተምረኸኛል፡፡ የተማርኩትን በሥራ ላይ ማዋል፤ የእኔ ፋንታ ነው፡፡ በዚያ ረገድ አላሳፈርኩህም ብዬ አምናለሁ፡፡
ንጉሥ፡-
ዕውነት ነው ልጄ፣ ከቶም አላሳፈርከኝም
ልዑል፡-
እንግዲያው አባቴ፤ “በርታ፤ ገና ይቀርሃል” አትለኝም ማለት ነው፤ አይደደል?
ንጉሥ፡-
ልጄ ሆይ! አሁንም ገና ይቀርሃል!
ልዑል፡-
ደሞ ምን ቀረኝ አባቴ?
ንጉሥ፡-
አትቸኩል፡፡ እነግርሃለሁ፡፡ በጠላት ወገን ብዙ ወታደር አልቋል፡፡ ያም ሆኖ ካንተም ወገን ብዙ ሰው ወድቋል፡፡ መሆን አልነበረበትም፡፡
ልዑል፡-
ስለዚህ ምን ማድረግ ነበረብኝ?
ንጉሥ፡-
“ማፈግፈግ! ማፈግፈግ ማወቅ አለብህ፡፡ ላወቀበት፣ ማፈግፈግ ከማጥቃት አንድ ነው፡፡ የምትለቅለት ሥፍራ የወጥመድህ ዋና አካል ነው፡፡ የአሸናፊነትና የመደላደል ስሜት ሲሰማው፡- አንተ ስስ-ብልቱን አገኘህ ማለት ነው፡፡ ያኔ ሠራዊትህን ሳታስጨርስ ዒላማ ታደርገዋለህ፤ በቀላሉ ትደመስሰዋለህ! የማፈግፈግ ስልት ማወቅ ምን ጊዜም የማይለይህ ጥበብ ይሁን! ከሁሉም በላይ ግን ድሉ የአገርህ ድል መሆኑን ተማር! ብርታትን ሁሉ አብዝቶ ይለግሥህ ልጄ! በሚቀጥለው ጊዜ እንደምትክሰኝ ተስፋ አለኝ! ያኔ ጣፋጭ ድል ታገኛለህ!” አለና አሰናበተው፡፡
* * *
ሀገራችን ጦርነት፣ ግጭት፣ ደም መፋሰስና ቅራኔ ተለይቷት አያውቅም፡፡ በመሣፍንት  ያየችውን፣ በነገሥታት እየደገመች፣ የነገሥታቱን ታሪክ በወታደር በትጥቅ ትግል እያጎላች፤ ብዙ ዘመን ተጉዛለች፡፡ ይህን ዚቅ እንገላገለው ዘንድ ሰላምን ያልተመኘንበት ጊዜ አልነበረም፡፡ ሆኖም መልኩን እየቀያየረ ሰላም መደፍረሱ አልቀረም፡፡ ከሥጋት፣ ከፍርሃት፣ ከጥርጣሬ፣ ከተስፋ-ማጣት ያልተላቀቀ ማህበረሰብ፤ ሰላም አለው ለማለት አያስደፍርም፡፡ የሀገራችንን ነገር በቅንነት ላስተዋለ አደፍራሹ ብዙ ነው፡፡ የውስጥም የውጪም ሰላም-ነሺ በርካታ ነው፡፡ ቅራኔን በአግባቡ መፍታት እስካልቻልን ድረስ፤ እኛም የማደፍረሱ ሂደት አካል መሆናችን አይቀሬ ነው፡፡ ኢ-ፍትሐዊ ሁኔታ ሰላም ይነሳል፡፡ ኢ-ሰብአዊ ሁኔታ ሰላም ይነሳል፡፡ ምዝበራ ሰላም ይነሳል፡፡ የአገር ገንዘብ እየዘረፉ ማሸሽ ሰላም ይነሳል። በትልቅ በትንሹ ጠብ ያለሽ-በዳቦ የሚል ብሶተኛ መኖር፣ ሰላም ነሺ የሆነውን ያህል፤ እሱ አደብ-እንዲገዛ ለማድረግ የሚሰነዘረው ምላሽም ሰላም ነሺ ከሆነ፤ ተያይዞ ገደል ነው፡፡ ከአንዱ ሰላም-ማጣት ወደ ሌላ ሰላም ማጣት መሸጋገር ከድጡ ወደማጡ መዝቀጥ ነው! አገርን በሆደ-ሰፊነት የሚመራ፣ በብልህነት የተቃኘ፣ “ትዕግሥት ፍርሃት አይደለም” የማይል፤ መልካም አስተዳደር ሙሉ ትርጉም የገባው አመራር ያስፈልገናል! ቆም ብሎ የሚያይ፤
“ጀግናው ጉተናዬ፤
ሎጋው ተዋጊዬ፤
ጥቃት ቢሰነዝር፣ ምን ድሉ ቢቀናው
ማፈግፈግ ካልቻለ፣ ገና ነው ፈተናው፡፡
የሚለው ግጥም በግልፅ የተጤነው፤ የማይደናበር፣ አስተዋይ የአገር ሰው ያስፈልገናል፡፡ የአገር ሽማግሌ ጠፍቶብናል፡፡ እርቅ ያለ አስታራቂ፣ ሰላም ያለ ሰላማዊ ሰው እንደማይመጣ ተዘንግቶናል! ነገር ማነሳሳት፣ ቅራኔን ማሾር፣ አለመግባባትን ማቀጣጠል፣ መፍትሄ ይሁንም አይሁን በጅልነት “አረረም መረረም ማ’በሬን ተወጣሁ” ማለትን፣ “እሳት ሳይኖር ጭስ አይታይም” የሚለውን ብሂል ዘንግቶ፣ ምንም እንዳልተፈጠረ አድርጎ ነገርን መናቅን፣አለመገንዘብ አደገኛ ነው፡፡ ከቶውንም ይሁን ይሁን ተብሎ የተወሰነ ነገር፣ ነገ ፍሬ አለው የለውም ብሎ አለመጠየቅ፤ “ማሳደግ እንጂ ማስረገዝ አይከብድም” የሚለውን የጋሞኛ ተረት ያስታውሰናልና ጠንቀቅ እንበል!!  

የኬንያ ፖሊስ በህገ ወጥ መንገድ ወደ አገሪቱ ገብተዋል ያላቸውን 13 ኢትዮጵያውያን ባለፈው ረቡዕ ምሽት በመዲናዋ ናይሮቢ በቁጥጥር ስር ማዋሉንና ለፍርድ ለማቅረብ በምርመራ ላይ እንደሚገኝ ዥንዋ ከትናንት በስቲያ ዘግቧል፡፡
በህገወጥ መንገድ ድንበር አቋርጠው ወደ ኬንያ ገብተዋል የተባሉት ኢትዮጵያውያኑ፣ በመዲናዋ ናይሮቢ በተከራዩት አንድ ቤት ውስጥ ለቀናት ተደብቀው እንደቆዩ የጠቆመው የከተማዋ ፖሊስ፤ ወደ ደቡብ አፍሪካ ሊያሸጋግራቸው የተስማማን አንድ ህገወጥ የሰዎች አዘዋዋሪ በመጠበቅ ላይ ሳሉ በቁጥጥር ስር መዋላቸውን አመልክቷል፡፡
በእስር ላይ የሚገኙት ኢትዮጵያውያን ሁሉም ወንዶች ሲሆኑ በተለያዩ ወንጀሎች ተከስሰው ቅጣት እንደሚጣልባቸውና ወደ አገራቸው እንደሚመለሱ ያስታወቀው ፖሊስ፣ ህገወጥ የሰዎች አዘዋዋሪውንና በወንጀሉ ተሳትፈዋል ያላቸውን ሁለት ሴቶች በቁጥጥር ስር ለማዋል ዘመቻ እንደጀመረም ገልጿል፡፡
ወደ ታንዛኒያ እና ደቡብ አፍሪካ ለመሻገር በማሰብ፣ በህገወጥ መንገድ ወደ ኬንያ ገብተው የሚገኙ ኢትዮጵያውያን ቁጥር በከፍተኛ ሁኔታ መጨመሩን የጠቆመው ፖሊስ፤ በየአመቱ እስከ 100 የሚደርሱ ኢትዮጵያውያን ስደተኞች በኬንያ ፖሊስ ቁጥጥር ስር እንደሚውሉም አመልክቷል፡፡