Administrator

Administrator

   ‹‹የሰላም መዝሙር ለኢትዮጵያና ለኤርትራ ህዝቦች” የተሰኘ የሙዚቃ ኮንሰርትና የፓናል ውይይት ሊካሄድ ነው፡፡ የሙዚቃ ኮንሰርቱንና የፓናል ውይይቱን የሚያዘጋጀው “ሰለብሪቲ ኤቨንትስ” ባለፈው ሳምንት በሰጠው ጋዜጣዊ መግለጫ፣ የሁለቱን አገራት ህዝቦች የቀደመ ግንኙነት ወደተሻለ ደረጃ ለማድረስ ያግዛል ያለውን የሙዚቃ ድግስና የፓናል ውይይት የሚያካሂደው በቀጣዩ ዓመት ህዳር ወር ላይ ሲሆን በሙዚቃ ኮንሰርቱ ታዋቂና ዝነኛ የሁለቱ አገራት ድምፃውያን ይሳተፋሉ ተብሏል፡፡
በፓናል ውይይቱ ላይ የታሪክ ምሁራን፣ የአገር ሽማግሌዎች፣ የማህበረሰብ ሰራተኞች የመንግስትና የተቃዋሚ ፓርቲ ተወካዮች በአጠቃላይ 800 ሰዎች የሚሳተፉ ሲሆን በሁለቱ አገር ህዝቦች የወደፊት ግንኙነት ላይ ይመካከራሉ ተብሏል፡፡ የኮንሰርቱና የፓናል ውይይቱ አላማ የሁለቱ አገራት ህዝቦች ድንበርና ጥበቃ ሳይገድባቸው በችግር ጊዜ አብሮ የመቆምና የመደጋገፍ ባህልን እንዲያዳብሩ፣ እንዲሁም የቀደመ ግንኙነታቸው እንዲጠናከር ያለመ መሆኑን የሰለብሪቲ ኤቨንትስ ዋና ስራ አስኪያጅ አቶ ሀብቶም ገ/ስላሴ ለጋዜጠኞች ተናግረዋል፡፡
የፓናል ውይይቱ በመጪው ህዳር 17 የሚካሄድ ሲሆን ኮንሰርቱ ህዳር 30 በሚሊኒየም አዳራሽ እንደሚካሄድ አቶ አብርሃም ተናግረዋል፡፡ በሙዚቃ ኮንሰርቱ ላይ በኢትዮጵያ በአራቱ መጠለያዎች የሚገኙ የኤርትራ ስደተኞችም ይታደማሉ ተብሏል፡፡

በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተ ክርስቲያን የሰንበት ት/ቤቶች ማደራጃና መምሪያ ማህበረ ቅዱሳን ስር የሚገኘው የአቡነ ጎርጎሪዎስ ስልጠና ማዕከል፣በበገና እና በመዝሙራት ዙሪያ በጥናታዊ ፅሁፎች ላይ የተመሰረተ የፓናል ውይይት፣ ዛሬ ከቀኑ 8፡00 ሰዓት ጀምሮ በአምስት ኪሎ የማህበረ ቅዱሳን ህንፃ 3ኛ ፎቅ ላይ በሚገኘው አዳራሽ ያካሂዳል፡፡ ጥናታዊ ፅሁፎቹ፤ በመጥፋት ላይ ባሉት የበገናና የመዝሙራት ጉዳዮች ላይ የሚያጠነጥኑ ሲሆን ከጥናታዊ ፅሁፎቹ በኋላ ሰፊ የፓናል ውይይት ይካሄዳል ተብሏል፡፡ በውይይቱ ላይ ሊቃውንት አባቶች፣ ባለድርሻ አካላትና የቀድሞ የአቡነ ጎርጎሪዎስ የዜማ መሳሪያዎችና የልሳነ ግዕዝ ተመራቂዎች ይሳተፋሉም ተብሏል፡፡

ማይና ፕሮሞሽን ኢንተርቴይመንት ከኢትዮጵያ ሆቴል ጋር በመተባበር የሚያዘጋጀው ወርሃዊው “ህብረ ትርዒት”፣ የኪነ ጥበብ ምሽት የፊታችን አርብ ከ11፡30 ጀምሮ በኢትዮጵያ ሆቴል ይካሄዳል፡፡ በዕለቱ አጭር ኮሜዲ ተውኔት፣ ግጥም በጃዝ፣ ወግ፣ ሙዚቃና ስታንዳፕ ኮሜዲ እንደሚቀርቡ ማይና ፕሮሞሽንና ኢንተርቴይመንት ለአዲስ አድማስ አስታውቋል፡፡

   የቴሌቪዥን ተከታታይ ፊልም በውድድሩ ተካትቷል

       በሸገር ኤፍ ኤም 102.1 ሬዲዮ ላይ የሚተላለፈው የ‹‹ለዛ›› ፕሮግራም አድማጮች የሽልማት ስነ - ስርዓት 7ኛ ዙር ሊካሄድ መሆኑ ተገለፀ፡፡ በዘንድሮው ውድድር ላይ የተካፈሉት ከሐምሌ 1 ቀን 2008 ዓ.ም እስከ ሐምሌ 1 ቀን 2009 ዓ.ም ድረስ የወጡ የፊልምና የሙዚቃ ስራዎች ሲሆኑ የሽልማት ሂደቱ ከወትሮው በተለየ ምርጥ የቴሌቪዥን ተከታታይ ፊልም የሚል አዲስ ዘርፍ ማካተቱን የለዛ ፕሮግራም ዋና አዘጋጅና የሽልማቱ ፈጣሪ ጋዜጠኛ ብርሃኑ ድጋፌ ለአዲስ አድማስ በላከው መግለጫ አስታውቋል፡፡ አዲሱ ምድብ የሽልማት ዘርፎቹን ዘጠኝ ያደርሳቸዋል የተባለ ሲሆን ምርጥ አልበም፣ ምርጥ ፊልም፣ ምርጥ ተዋናይ፣ ምርጥ አዲስ ድምፃዊና ድምፃዊት፣ ምርጥ ነጠላ ዜማ፣ ምርጥ የሙዚቃ ቪዲዮና የህይወት ዘመን ተሸላሚ በሚሉ ዘርፎች ውድድሮች ይካሄዳሉ፡፡
የሙዚቃ ቪዲዮ ምድብ ተሳታፊዎች  በአልበምነት በተጠቀሰው ዓመት የቀረቡና የሙዚቃ ቪዲዮ የተሰራላቸው መሆን አለባቸው ያሉት አዘጋጆቹ፤ ይህም የተደረገው የአልበም ስራዎችን ለማበረታታት እንደሆነ ተገልጿል፡፡ የዘንድሮውም የድምፅ አሰጣጥ የመጀመሪያ ዙር በwwwshgerfm.com የሚከናወን ሲሆን፣ በሁለተኛው ዙር ምርጥ አምስቱ ከተለዩ በኋላ ኮድ ተሰጥቷቸው በ8101 በአጭር የፅሁፍ መልዕክት ተጨማሪ የድምፅ ማሰባሰብ ስራ እንደሚካሄድ ተጠቁሟል፡፡ የሙዚቃ ድምፅ አሰጣጡ መቶ በመቶ ለአድማጭ የተሰጠ ሲሆን የውድድሩን ሂደትና የድምፅ ቆጠራውን ለመቆጣጠር ጉዳዩ የሚመለከታቸው ማህበራትና ተቋማትን ለማሳተፍ እንደታቀደ አዘጋጆቹ  ተናግረዋል፡፡ በፊልም ስራው ውድድር 60 በመቶ በዳኞች፣ ቀሪው 40 በመቶ በተመልካች የሚዳኝ ሲሆን በዚህ የምርጫ ሂደት ህብረተሰቡ ንቁ ተሳትፎ እንዲያደርግና ሽልማት የሚገባቸውን የኪነ - ጥበብ ሰዎች ለመሸለም የበኩሉን አስተዋፅኦ እንዲደርግ የሽልማቱ አዘጋጅ ጋዜጠኛ ብርሃኑ ድጋፌ ጥሪ አድርጓል፡፡  

   በህዳር ወር 1957 ዓ.ም ላይ ነበር እስከዛሬም ድረስ መለያቸው የሆነውን “ጤና ይስጥልኝ ልጆች… የዛሬ አበባዎች የነገ ፍሬዎች…” የሚለውን ሰላምታቸውን አስቀድመው፣ በዘመኑ ብርቅዬ በነበረው ባለጥቁርና ነጭ ቀለሙ ቴሌቪዥን ለመጀመሪያ ጊዜ ብቅ ያሉት። እንዲህ እንደ ዛሬው ቴሌቪዥን በየሰው ቤት ሣይገባ የዘመኑ ልጆች የአበባ ተስፋዬን ተረትና ቀልዶች ለመስማት ቴሌቪዥን ላላቸው ጎረቤቶቻቸው የጉልበት ዋጋ ይከፍሉ ነበር፡፡ ግቢ ማፅዳት…አትክልት መኮትኮት…ቆሻሻ መድፋት.. እና የመሳሰሉት ሥራዎች የወቅቱ ልጆች ለአባባ ተስፋዬ ተረትና ጨዋታ የሚከፍሏቸው ዋጋዎች ነበሩ፡፡
ሰኔ 20 ቀን 1915 ዓ.ም በባሌ ክፍለ አገር ከዱ እየተባለ በሚጠራው አካባቢ የተወለዱት አባባ ተስፋዬ (ተስፋዬ ሳህሉ)፤ የልጅነት ህይወታቸው ያለፈው በከፍተኛ ችግርና እንግልት ነበር፡፡ ወላጆቻቸውን በሞት የተነጠቁት ገና በለጋ ዕድሜያቸው ስለነበር ያደጉት አዲስ አበባ ከተማ ውስጥ በአንድ መምህር ቤት ነበር። ግፈኛው የጣሊያን ወራሪ እኚህን አሣዳጊያቸውንም በስቅላት ገድሎባቸዋል፡፡ ይህንን መከራና ሐዘን መቋቋም ያቃታቸው አባባ ተስፋዬ፤ በከፍተኛ ሁኔታ ታመሙና ሚኒሊክ ሆስፒታል ገቡ። በሆስፒታሉ የሚሰጣቸውን ሕክምና አጠናቀው ሲጨርሱም መሄጃና መጠጊያ ስለአልነበራቸው በወቅቱ ሆስፒታሉን የሚያስተዳድረው ጣሊያናዊ በሆስፒታሉ ውስጥ በአቅማቸው እንዲያገለግሉ ፈቀደላቸውና ሥራ ጀመሩ። መርፌ ከመቀቀል፣እስከ ቁስል ማሸግና የፈንጣጣ ክትባትን መከተብ እንዲሁም የአበላዘር በሽታዎችን እስከ ማከም  ድረስ ይሰሩ ነበር፡፡
ከጣሊያን ወረራ በኋላ በ1937 ዓ.ም በአዲስ አበባ ማዘጋጃ ቤት 11 ብር ወርሃዊ ደመወዝ ተቆርጦላቸው ሥራ ጀመሩ፡፡ ሴት ተዋንያን በሌሉበት ዘመን ፀጉራቸው ላይ ሻሽ በማሰርና ፂማቸውን ሙልጭ አድርገው በመላጨት፣ እንደ ሴት ሆነው ለአራት ዓመታት ተውነዋል፡፡ የመጀመሪያ የመድረክ ቲያትራቸውም “የአርበኛው ሚስት” የሚል ሲሆን በዚህ ቲያትር ላይ የሴት ገፀባህርይን ወክለው ነበር የተወኑት፡፡ ግማሽ ምዕተ ዓመት ለሚጠጋ ጊዜ በሙያቸው አገራቸውንና ወገኖቻቸውን ሲያገለግሉ የኖሩት አባባ ተስፋዬ፤ በመድረክ ላይ ከተጫወቷቸው ቲያትሮች መካከል አፋጀሺኝ፣ የደም ድምፅ፣ ጎንደሬው ገ/ማርያም መቀነቷን ትፍታ፣ አርበኞችና ኢትዮጵያ የተባሉት ይገኙበታል፡፡
በ1944 ዓ.ም በጀነራል መንግስቱ ንዋይ ተመርጠው፣ ወደ ኮሪያ ከዘመተው የኢትዮጵያ ጦር ጋር አብረው ዘመቱ፡፡ በዚህም የሃምሣ አለቃ ማዕረግ ተሰጥቶአቸዋል፡፡ በኮሪያ ቆይታቸውም ከእውቁ ኮሚዲያን ቻርሊ ቻፕሊንና ከፊልም ተዋናይ ማርል ቦሮ ጋር የመገናኘት ዕድል ገጥሞአቸዋል፡፡
አበባ ተስፋዬ፣ የልጆች ፕሮግራምን በቴሌቪዥን ማቅረብ በጀመሩበት ወቅት ደመወዛቸው በፕሮግራም 175 ብር ነበር፡፡ በወቅቱ ሥራውን የሚቆጣጠረው አንድ እንግሊዛዊ ስለነበር  ክፍያቸው ጥሩ ነበር - “እንደ ፈረንጅ ነበር የሚከፈለኝ” ይሉ ነበር - በወቅቱ ስለነበረው ደመወዛቸው ሲናገሩ፡፡ እንግሊዛዊው ሥራውን አስረክቦ ሲሄድ ደመወዛቸው ቁልቁል ወርዶ፣ 70 ብር ሲደረግ ቅሬታ አላቀረቡም፡፡ ለዘጠኝ ዓመታት ሥራቸውን ሲያቀርቡ ከቆዩ በኋላ ደርግ ስልጣን ያዘ፡፡ ያኔ ደግሞ የአባባ ተስፋዬ ደመወዝ ወደ አምሳ ብር፣ ቀጥሎም ወደ 25 ብር እንዲያሽቆለቁል ተደረገ፡፡ ሁኔታው እጅግ የሚያበሳጭ ቢሆንም አባባ ተስፋዬ ስራቸውን ያለምንም ቅሬታ ቀጠሉ፡፡ የአገልግሎት ዘመናቸውና እያበረከቱት ያሉት አስተዋፅኦን ከግምት ውስጥ ያስገባው የወቅቱ የቴሌቪዥን ጣቢያው አስተዳደር፤ ለአባባ ተስፋዬ 750 ብር ወርሃዊ ደመወዝ ይገባዎታል ብሎ ቆረጠላቸው፡፡
ግማሽ ምዕተ ዓመት ለሚጠጋ ጊዜ አገራቸውንና ወገኖቻቸውን በትጋት ሲያገለግሉ የኖሩት የትውልድ ድልድዩ አባባ ተስፋዬ፤ የብዙ ሙያዎች ባለቤት ነበሩ። ተዋናይ፣ ደራሲ፣ ድምፃዊ፣ ሐኪም፣ የሆቴል ቤት አስተናጋጅ፣ የምትሃት ትርኢት አቅራቢ፣ ኮሜዲያን፣ መድረክ መሪ፣ ወታደር፣ ገበሬ እና የሞራል መምህር ሆነው የሚወዱትን ህዝብና አገራቸውን አገልግለዋል፡፡ እኚህን የበርካታ ሙያዎች ባለቤትና የሞራል መምህር፣ አገር በአንድ ድምፅ “አባባ” የሚል ማዕረግ ደርቦ፣ አክብሮአቸው ለዓመታት ኖረዋል፡፡ ከ42 ዓመታት በላይ የህፃናት መካሪ፣ አስተማሪና አጫዋች በመሆን ያገለገሉትን እኚህን ባለሙያ፤የማታ ማታ፣የኢትዮጵያ ቴሌቪዥን በሁለት መስመር ደብዳቤ፣የሥራ ውላቸው መቋረጡን ነግሮ ነው ያሰናበታቸው፡፡ ለዚህ ምክንያቱ ደግሞ አንዲት የ3 ዓመት ህፃን ባወራችው ቀልድ ላይ የብሔረሰቦችን ክብር የሚነካ ነገር ተናግራለች የሚል ነበር፡፡ ለዚህ ጉዳይ ተጠያቂ ሆነው የስንብት ደብዳቤው እስከተሰጣቸው መስከረም 30 ቀን 1998 ዓ.ም ድረስ በሚሊዮኖች የሚቆጠሩ ህፃናትን በስነ ምግባር ኮትኩተው አሳድገዋል፡፡
እኚህን ታላቅ የሞራል መምህርና የአገር ባለውለታ የቴሌቪዥን ጣቢያው በዚህ መልኩ ያሰናብታቸው እንጂ ለአገራቸውና ለወገኖቻቸው ያበረከቱትን አስተዋፅኦ የሚዘክርና ክብራቸውን የሚገልፅ ልዩ ልዩ ፕሮግራሞች በተለያዩ ጊዜያት በአክባሪዎቻቸውና በመንፈስ ልጆቻቸው ተዘጋጅቶላቸዋል፡፡ ከዚህም መካከል ህዳር 28 ቀን 2000 ዓ.ም በሸራተን አዲስ ተከናውኖ የነበረው ልዩ የምስጋና ምሽት ተጠቃሽ ነው። በወቅቱም ለክብራቸውና ለውለታቸው መታሰቢያነት የተዘጋጀላቸውን የወርቅ ሜዳልያ ከደጃዝማች ዶ/ር ዘውዴ ገ/ሥላሴ እጅ ተቀብለዋል፡፡
በትወና ችሎታቸው ከቀድሞው ንጉስ አፄ ኃይለ ሥላሴ የወርቅ ሜዳሊያዎችን በሽልማት ያገኙት አባባ ተስፋዬ፤ በተለያዩ ጊዜያት ልዩ ልዩ ሽልማቶችንም ለማግኘት በቅተዋል፡፡ ከእነዚህ ሽልማቶችም መካከል የኢትዮጵያ የስነ ጥበባትና የመገናኛ ብዙኃን የሽልማት ድርጅት፣ በ1991 ዓ.ም ያዘጋጀውና በቴአትር ዘርፍ በተዋናይነት የህይወት ዘመን ተሸላሚ የሆኑበት ዋንኛው ነው፡፡ ዩኒቲ ዩኒቨርሲቲ እኚህን ታላቅ የአገር ሀብት ከዓመታት በኋላ አስታውሶ፣ በዘንድሮው ዓመት፣ የክብር ዶክትሬት ሰጥቶአቸዋል፡፡

የአባባ ተስፋዬ እውነታዎች
ወላጅ አባታቸው ኤጀርሣ በዳኔ ይባላሉ፡፡ የሚጠሩበት ሣህሉ የአሳዳጊያቸው ስም ነው፡፡
አዲስ አበባ የገቡት በ10 ዓመታቸው ነበር፡፡
የተማሩት ተፈሪ መኮንን፣ አሁን ኮከበ ፅባህ በተባለው ት/ቤት ነው፡፡
በአዲስ አበባ ማዘጋጃ ቤት ነው መጀመሪያ የተቀጠሩት፡፡
ደመወዛቸው 11 ብር ነበር፡፡
በ1947 ዓ.ም አግብተው በትዳር ለ48 አመት ኖረው፣ ባለቤታቸውን በሞት ተነጥቀዋል፡፡
ስልክ ማናገር አይወዱም ነበር፡፡
ቃጫ በጥቁር ቀለም ነክሮ፣ እንደ ዊግ መጠቀም የጀመሩት እሳቸው ናቸው፡፡
በሐረር ራስ ሆቴል፣ ከአስተናጋጅነት እስከ ኃላፊነት ደረጃ ሰርተዋል፡፡
በ1938 ማዘጋጃ ቤት ሲቀጠሩ፣ የሴት ተዋናይ ባለመኖሩ ለአራት ዓመታት እንደሴት በመሆን ተውነዋል፡፡
በአንድ ቲያትር ላይ 3 ገፀ ባህርያትን ወክለው ተውነዋል፡፡
በሚሰሩት የምትሀት ትርኢት ሳቢያ፣ ከሰው ተገልለው ነበር፡፡  
የፃፏቸውን የተረት መፃህፍት ከገበያ እየገዙ፣ በየቦታው እያዞሩ ይሸጡ ነበር፡፡
አፋጀሺኝ የተሰኘው ቲያትር ላይ፣ የንግስቲቱን ገፀባህርይ በመወከል ተውነዋል፡፡


         የታወቀ ተረት ይሁን እንጂ አንድ መፅሐፍ ላይ እንደሚከተለው የቀረበ ታሪክ አለ። በአንድ ወቅት አንበሳ፤ የተፈጥሮ ጥላቻውንና ተቀናቃኝነቱን ይብቃኝ ብሎና በሆነ ምክንያት ትቶ፤ ኑሮና ሕይወትን ቀላልና ውጤታማ ለማድረግ ፈለገ፡፡ ለዚህ ደግሞ ከሌሎች እንስሳት ጋር መተባበር አስፈላጊ መሆኑን አመነበት፡፡ ይሄንኑ ለማድረግ ወደ ጅብ፣ ነብርና ተኩላ ሰፈር ሄደ፡፡
ባልተለመደ ትህትናዊ መንገድ የዱሮ ጉልበተኛነቱንና ማስፈራራቱን ሁሉ ትቶ፤ አዲሱን ዕምነቱን ነገራቸው፡፡ ሦስቱም በጣም ተደሰቱ፡፡ ዕምነቱን መጋራታቸውንና ተግባራዊ እንደሚያደርገው ለማረጋገጥ ወደ ጫካ ሄደው፤
የመጀመሪያውን ትብብር በአንድ ታላቅ አደን እናሳይ፤ ተባባሉ፡፡ ሰለባቸውን በመሻት፣ አንድ ላይ ሲጓዙ አርፍደው፤ በመጨረሻ ቋጥኝ የሚያክል ጎሽ አጋጠማቸው፡፡
እርዳ ተራዳ ብለው፤ ተባብረው ጎሽን ግዳይ ጣሉት፡፡
የንብረት ክፍፍሉ ሰዓት ደረሰ፡፡ አንበሳ፤ እንደተለመደው፣ ከውሉና ከስምምነቱ ውጪ፣ የግዳዩ ዋና አዳይና ደልዳይ እኔ ነኝ አለ፡፡ በባህሪያቸው አራቱም የተለያየ የምግብ አወሳሰድ ባህል ስላላቸው፤ አብረው መብላት አይችሉም፡፡ ነገሩን የተረዳው አንበሳ፤ ድርሻ ድርሻችንን መካፈልና መውሰድ አለብን ሲል ወሰነ፡፡ ሶስቱም በጥርጣሬ እያዩት ተስማሙ፣ ይሁን እሺ አሉት፡፡
አንበሳ ሥጋውን በአራት ከፈለውና፤
ይህ የአራዊት ንጉስ በመሆኔ ይገባኛል፤ አለ
ሁለተኛውን መደብ እያሳየ፤ ይሄ ደግሞ፤ በዚህ አደን ትልቁን ሚና ስለተጫወትኩ ዋጋዬ ነው፣ ለእኔ ይገባል
ሦስተኛውን መደብ አቅርቦ፣ ይሄ በእንስሳነቴ የእኔ የግል ድርሻዬ ነው
አራተኛውንና የመጨረሻውን መደብ እያሳያቸው፤ ‹‹ይሄን የሚነካ ወዮለት!›› አለ፡፡
*   *   *
ማንም ቢሆን፤ የባህሪውን፣ የጠባዩን ፈፅሞ አይተውም፡፡ ጅብ ማንከሱን፣ አዞ ማልቀሱን፣ እባብ መላሱን፣ ግስላ ዘራፌነቱን፣ ሰጎን አሸዋ ውስጥ አንገቱዋን መቅበሯን… አይተዉም፡፡ መቼም ቢሆን መቼም፣ የአንበሳውን ድርሻ በእኩልነት የሚካፈል እንስሳ አይፈጠርም፡፡ አንበሳ አንበሳ ነውና፣ የአራዊት ሁሉ ንጉስ መሆኑን ብቻ ነው የሚያምነው!! እንድንቀበለው የሚፈልገውም ይሄንኑ እውነት ነው፡፡ ስለሆነም ሌላው እሱን ለማገልገል እንደተፈጠረ አድርጎ ማየቱና ማስገበሩ ግድ ይመስለዋል፡፡ ሌሎቹ እንስሳት፤ ‹‹ድር ቢያብር አንበሳ ያስር›› የሚለውን ተረት አያውቁትም ብሎ ያስባል፤ ወይም እውነትም አያውቁትም!
ሙስና፤ የሹሞች፣ ከተለመደው አገርን የማገልገል ተግባር ወደ ግል ጥቅም ማፈንገጥ ነው፡፡ ሙስና ያለ ጥርጥር በሁሉም ህብረተሰብ ውስጥ ይኖራል፡፡ ሆኖም ከማህበረሰብ ማህበረሰብ መጠኑ ይለያያል፡፡ ከአንዱ ዘመን አንዱ ዘመን ውስጥ ሊጎላም ይችላል። በስሜታዊ መልኩ የሚታዩ ጭብጦች እንደሚጠቁሙት፤ የሙስና መጠን ከፈጣን ማህበራዊ ኢኮኖሚያዊ ዝመና ጋር ይተሳሰራል፡፡ በአሜሪካ በ18ኛው እና በ20ኛው ክፍለ ዘመን በነበረው ፖለቲካዊ ህይወት ውስጥ የታየው ሙስና፤ ከ19ኛ ምእተ-ዓመትዋ አሜሪካ ሙስና ይልቅ ዝቅ ያለ ነበር የሚል ግምት አለ፡፡ በብሪታኒያም እንደዚሁ፣ በ17ኛው እና በ19ኛው ምእተ-ዓመት መባቻ ላይ የታየው ሙስና፣ በ18ኛው ምእተ ዓመት ከነበረው ያነሰ ነው የሚመስለው፡፡ በአሜሪካም ሆነ በብሪታኒያ የታየው ሙስና፤ ከኢንዱስትሪው አብዮት፣ አዳዲስ የሀብትና የሥልጣን ምንጮች፣ እንዲሁም መንግስት ላይ አዳዲስ ጥያቄን ይዘው ብቅ ካሉት መደቦች መፈጠር ጋር አብሮ መከሰቱ የአጋጣሚ ነገር ነውን? አይደለም፡፡ ከቡቃያ ሀብታሞች መፈልፈል ጋር አብሮ የፈላ ነው፡፡ የእኛ ግን እንቆቅልሽ ነው! ወጡ ሳይወጠወጥ ወስከባዩ ፍጥጥ!
እናቴን ያገባ ሁሉም አባቴ ነው በሚል አስተሳሰብ፣ በተቀነበበ ህብረተሰብ ውስጥ መንግስትን ከልብ ማመን ይኖራል ማለት አዳጋች ነው፡፡ በመሰረቱ በኢትዮጵያ የሚከሰተው ለውጥ እስከ ዛሬም ሆነ አሁን፣ ከሥረ መሰረቱ ውል የያዘና ህዝብን በትክክል ያሳተፈ ባለመሆኑ፣ እኔ ምን ተዳዬ ይበዛዋል፡፡ ገዢ ሁሉ አንድ አይነት ነው። ፖለቲካ ሁሉ ወይ አባብሎ ማዘያ፣ ወይ አስፈራርቶ መግዣ፤ ዘዴ እንጂ ማንም የማንንም እንጀራ አብስሎ የሚሰጥበት ሂደት አይደለም፤ የማለት እምነት የተጠናወተው ነው፡፡ በዚህ ማህል አገር፤ ህዝብ፣ ሉአላዊነት፤ ዲፕሎማሲ ወዘተ. ከልብ የሰፈሩና ከልብ የምንታገልላቸው አጀንዳዎች መሆናቸው ይቀርና፣ ሁሉም “እኔን አዳምጡ” የሚባልባቸው ስብከቶች ይሆናሉ፡፡ ከዚህ ያውጣን!!
ተቃዋሚም ሆነ አጋር ድርጅቶች፤ከአንዱ ገንዘብ እኩል አገኛለሁ ብሎ ገበታው ላይ ዐይኑን ማፍጠጡ፣ ቢያንስ የዋህነት ነው፡፡ የፖለቲካውን መድረክ ፍትሀዊ በሆነ መንገድ ያልተጋራ፣ ከኢኮኖሚው አዝመራ ቁና ይደርሰኛል፤ የአገር ሀብት የእኔም ድርሻ አለበት ቢል፤ ‹‹ሞኝ ጎረቤት፤ከልጅህ እኩል አርገኝ አለ” የተባለውን ዓይነት የደካሞች መጃጃል፣ ወደ ፖለቲካው ጎራ ልክተት የማለትን ያህል የሽንፈት መለዮ ማጥለቅ ነው፡፡ አንበሳው ሙሉውን ሳይደክም ወስዶታል፡፡ እውነተኛው ተረት፤ ‹‹በስመ ማሪያም ብለን ያመጣነውን እንጀራ፣ ያልደከሙ እየበሉት ነው›› የሚለው ነው፡፡

በአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ ወቅት ከ390 ሺ በላይ ሚሊሻዎች ሰልጥነዋል
ከ7ሺ በላይ ተጠርጣሪዎች ክሳቸውን እየተከታተሉ ነው
የሦስት ሚኒስትሮች ሹመት ፀድቋል

ከመስከረም 28 ቀን 2009 ዓ.ም ጀምሮ ለ11 ወራት በሥራ ላይ የቆየው የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ  በትላንትናው ዕለት ተነሳ፡፡
የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ትናንት የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ እንዲነሳ የቀረበውን የውሳኔ ሃሳብ ያፀደቀ ሲሆን ባካሄደው አንደኛው አስቸኳይ ስብሰባ ላይ በቀረበው ሪፖርት መሰረት፤ የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ ከታወጀበት መስከረም 28 ጀምሮ በኦሮሚያ 233 ሺ 070፣ በአማራ 143 ሺ 459 እንዲሁም በደቡብ 16 ሺ 475 ሚሊሺያዎች መሰልጠናቸው ተገልጿል። በተጨማሪም በየክልሉ ያሉ የብሔራዊ ተጠባባቂ የሰራዊት አባላትን የማጠናከር ሥራ ተሰርቷል ተብሏል፡፡
የተፈጠረውን አለመረጋጋት ለማስቆምና የህግ የበላይነትን ለማረጋገጥ የሚያስችሉ ሥራዎችን በተመለከተም በሁከትና ብጥብጡ ተሳትፈዋል የተባሉ ከኦሮሚያ ክልል 4136፣ ከአማራ ክልል 1888፣ ከደቡብ ክልል 1166፣ ከአዲስ አበባ 547 በድምሩ 7737 ተጠርጣሪዎች በተለያየ ደረጃ ባሉ ፍርድ ቤቶች ክሳቸውን እየተከታተሉ መሆኑ ተጠቁሟል፡፡ ከ21 ሺ በላይ ተጠርጣሪዎችም በሁለት ዙር የተሃድሶ ስልጠና ወስደው፣ ወደ ህብረተሰቡ እንዲቀላቀሉ መደረጉ በሪፖርቱ ላይ ተመልክቷል። ኮማንድ ፖስቱ የታጠቁ አሸባሪዎችንና ፀረ-ሰላም ሃይሎችን ለመቆጣጠር የተሰሩ ሥራዎች ብሎ ባቀረበው ሪፖርት ላይ እንደተገለፀው፤ በኦሮሚያ 325፣ በአማራ 275፣ በደቡብ 109 በድምሩ 709 ሸማቂዎችና የታጠቁ ኃይሎች፣ ከህዝብና ከመስተዳደር አካላት ጋር በመሆን ለመቆጣጠር እንደተቻለ ጠቁሟል፡፡ ህገወጥ የመሣሪያ ዝውውርን ለመቆጣጠር ከ97 በላይ አዳዲስ ኬላዎችን በማቋቋምና 196 ነባር ኬላዎችን በማጠናከር የተለያዩ የነፍስ ወከፍና የቡድን ጦር መሳሪያዎችን በቁጥጥር ሥር ማዋሉንም አስታውቋል፡፡ ከነበረው ሁኔታ ልምድ በመውሰድ የጦር መሣሪያ አያያዝና አጠቃቀም ላይ ረቂቅ አዋጅ እየተዘጋጀ መሆኑንና አዋጁ በሥራ ላይ ሲውል የዚህ አይነት ችግሮችን ለመፍታት ከፍተኛ አስተዋፅኦ እንደሚኖረውም ተጠቁሟል፡፡
በቅርቡ ከግብር ክፍያ ጋር በተያያዘ ተከስቶ የነበረውን የፀጥታ ችግር የየክልሉ የፀጥታ አካላት በራሣቸው አቅም መፍታት መቻላቸው፣ የኮማንድ ፖስቱ አስፈላጊነት ወሣኝ አለመሆኑን አመላክቷል ያለው ሪፖርቱ፤ የፌደራል የፀጥታ አካላትና የክልል የፀጥታ አካላት በአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ ወቅት ያዳበሩትን በጋራ ተቀናጅቶ የመስራት ልምድ በመጠቀም ችግሮችን ለመፍታት እንደሚቻል ጠቁሟል፡፡ ኮማንድ ፖስቱ ሲያከናውን የቆያቸውን ሥራዎች ደረጃ በደረጃ በአካባቢው ላሉ የፀጥታና የሚመለከታቸው አካላት እያስረከበ፣ የቅርብ ድጋፍ ሲያደርግ መቆየቱም ተገልጿል፡፡
በየቦታው እያጋጠሙ ያሉ ጥቃቅን ክስተቶችና ያልተቋጩ መለስተኛ ሥራዎች ቢኖሩም እነዚህ ሥራዎች በመደበኛ ሁኔታ፣ በየደረጃው ካሉ የፀጥታና የመስተዳድር አካላት አቅም በላይ ሊሆኑ ስለማይችሉ የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ እንዲነሳና ቀሪ ሥራዎች በመደበኛው የህግ አግባብ እንዲፈፀሙ ለምክር ቤቱ የውሣኔ ሀሳብ ቀርቧል፡፡ ምክር ቤቱ የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ በመነሣቱ ጉዳይ ላይ ድምፅ መስጠት የሚጠበቅበት ባለመሆኑ፣ የምክር ቤቱ አባላት ድምፅ ሣያስፈልግ የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ ከትላንት ሐምሌ 28 ቀን ጀምሮ መነሣቱ ተገልጿል፡፡  
በሌላ በኩል በትላንትናው ዕለት ለአስቸኳይ ስብሰባ የተጠራው ምክር ቤቱ፤ የ3 ሚኒስትሮችን ሹመትም አፅድቋል፡፡ በዚህም መሰረት ባለፈው ህዳር ወር የኢትዮጵያ ገቢዎችና ጉምሩክ ባለስልጣን ዋና ዳይሬክተር ሆነው የተሾሙት አቶ ከበደ ጫኔ፤ የፌደራል አርብቶ አደር ልማት ጉዳዮች ሚኒስትር፣ በትምህርት ሚኒስቴር የአጠቃላይ ትምህርት ዘርፍ ሚኒስቴር ዴኤታ የነበሩት ዶ/ር ጥላዬ ጌቴ፣ የትምህርት ሚኒስትር እንዲሁም የኢትዮጵያ ገቢዎች ጉምሩክ ባለስልጣን የጉምሩክ ዘርፍ ምክትል ዋና ዳይሬክተር የነበሩት አቶ ሞገስ ባልቻ፣ በሚኒስትር ማዕረግ ዋና ዳይሬክተር ሆነው ተሹመዋል፡፡  


   • በአዳዲስ አቅጣጫዎች መጠናከሩን ቀጥሏል
                    • ከ10 በላይ ጋዜጠኞች ለዓለም ሻምፒዮናው ለንደን ይጓዛሉ
                    • አዲስ ድረገፅ ያስመርቃል
                    • የክልል ጋዜጠኞችን በሚያሳትፍ መዋቅር የመስራት እቅድ አለው

      የኢትዮጵያ ስፖርት ጋዜጠኞች ማህበር በአዳዲስ የስራ አቅጣጫዎች ተጠናክሮ እንደሚቀጥል ፕሬዝዳንቱ አቶ ዮናስ ተሾመ ለስፖርት አድማስ ገለፁ፡፡ ማህበሩ ከዓለም አቀፍ የስፖርት ማህበራት ጋር የላቀ ግንኙነት ፈጥሮ በመስራት አባላቱን ተጠቃሚ እያደረገ ነው ብሏል። በአዲስ መልክ ተደራጅቶ ከተቋቋመ ሁለተኛ የስራ ዘመኑን የያዘው ማህበሩ በዛሬው እለት ከአትሌቲክስ ፌደሬሽን አብይ ስፖንሰር ‹‹ሶፊማልት›› ባገኘው ድጋፍ ለሁሉም የስፖርት ጋዜጠኞች በ16ኛው የዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና ላይ ያተኮረ ስልጠና አዘጋጅቷል፡፡ በስልጠናው ላይ የኢትዮያ አትሌቲክስ ፌደሬሽን ፕሬዝዳንት ኃይሌ ገብረስላሴ እንዲሁም የሶፊ ማልት እና የሄኒከን ብራንድ ማናጀር ራህዋ ገብረመስቀል በክብር እንግድነት ይገኛሉ፡፡ ስልጠናውን የሚሰጠው እውቅ የአትሌቲክስ ጋዜጠኛ፤ የአይኤኤኤፍ ዘጋቢ እና የማህበሩ አባል ኤልሻዳይ ነጋሽ ነው፡፡ በስልጠናው የዓለም ሻምፒዮናውን የሚመለከቱ ወቅታዊ መረጃዎች፤ የዘገባ ሁኔታዎችና አሰራሮችን በጥልቀት ይዳሰሳሉ፡፡ ኃይሌ ገብረስላሴ አጋጣሚውን በመጠቀም ለስፖርት ጋዜጠኞች ልዩ መልዕክት እንደሚያስተላልፍ የሚጠበቅ ሲሆን፤ የስፖርት ጋዜጠኞች ማህበር ኦፊሴላዊ ድረገፁንም እንደሚያስመርቅ ታውቋል፡፡ በሌላ በኩል ለንደን የምታዘጋጀውን 16ኛው የዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና በተለያዩ የሚዲያ አውታሮች ለመዘገብ ከ10 በላይ የማህበሩ አባላት  እንደሚጓዙ ለስፖርት አድማስ የጠቀሰው ፕሬዝዳንቱ አቶ ዮናስ፤  ስራ አስፈፃሚው በሁለተኛው የስራ ዘመን የመጀመርያው አንድ ዓመት ውስጥ በርካታ ጋዜጠኞችን ዓለም አቀፋዊ እና አህጉራዊ ውድድሮችን እንዲዘግቡ እድሉን በመፍጠር በትጋት መስራቱን በተለይ ደግሞ የ4 ጋዜጠኞችን ሙሉ ወጭ በመሸፈን ድጋፍ መስጠቱን አመልክቷል፡፡
በሁለተኛው የስራ ዘመን ላይ የሚገኘው የማህበሩ ስራ አስፈፃሚ  በመጀመርያው የስራ ዘመን የነበሩ የኮሚቴ አባላቱን ይዞ በመቀጠል ሁለት አዳዲስ አባላት ተጨምረውበት ለተጨማሪ አራት አመታት እንዲቀጥል የተወሰነው ከዓመት በፊት ነበር፡፡ ስለሆነም የማህበሩ ፕሬዝዳንት ዮናስ ተሾመ፣ ፀሀፊ መንሱር አብዱልቀኒ፣ ደረጃ ጠገናው፤ የማህበሩ ገንዘብ ያዥ ቆንጂት ተሾመ ውጪ ፍቅር ይልቃል፣ ሀና ገ/ስላሴ፣ አርአያት ራያ፣ ግርማቸው ከበደ፣ ታደለ አሰፋ፣ ዳግም ዝናቡ፣ ኃይለእግዚአብሔር አድሃኖም በስራ አስፈፃሚነት ኮሚቴ እያገለገሉ ናቸው፡፡ የስራ አስፈፃሚ አባላቱ በ4 ንዑስ ኮሚቴዎች እና ሁለት ኮሚሽኖች በመከፋፈል እየሰሩም ይገኛል፡፡
የኢትዮጵያ የስፖርት ጋዜጠኞች ማህበር የሙያተኛውን አቅም ለማጎልበት ትኩረት ማድረጉን የገለፀው ፕሬዝዳንቱ በየዓመቱ ከ4 በላይ ስልጠናዎችን ለማዘጋጀት እቅድ መያዙን ስልጠናዎቹን በአዲስ አበባ እና በክልል ከተሞች ለመስጠት እንደሚፈልግና በተለይ በክልል የሚሰሩ የስፖርት ጋዜጠኞችን በሚያሳትፉ እንቅስቃሴዎች ይሰራል ብሏል፡፡
በየዓመቱ ከዓለም ዓቀፉ የአትሌቲክስ ፌዴሬሽኖች ማህበር (IAAF) የሚገኙ ዕድሎች  በፍትሃዊነት ለሁሉም መገናኛ ብዙሃን ለማዳረስ ጥረት እናደርጋለን ያለው አቶ ዮናስ፤  ባለፈው 1 ዓመት በተለያዩ ዓለም አቀፋዊ እና አህጉራዊ ውድድሮች ለዘገባ የተላኩ ጋዜጠኞች በየሚዲያ አውታሮቻቸው ከበፊቱ በተሻለ የሰጧቸው የዘገባ ሽፋኖች እንደሚያበረታቱ ገልጿል፡፡
በዓለም ዓቀፍ የስፖርት ማህበራት  የሚኖረውን እውቅናና የተቀባይነት ደረጃ ለማሳደግ ከዓለም አቀፉ የአትሌቲክስ ፌደሬሽኖች ማህበር እና ከዓለም አቀፉ የስፖርት ጋዜጠኞች ማህበር ያለው ግንኙነት እየጠናከረ መጥቷል፡፡ በኢትዮጵያ የሚከናወኑ የስፖርት እንቅስቃሴዎችና ዓለም አቀፍ ትኩረት ሊያገኙ የሚገባቸው የዜና እና የዘገባ ሽፋኖች እየበዙ ናቸው፡፡ በአገር ውስጥ ከሚገኙ የስፖርቱ ባለድርሻ አካላት እና አጋሮች ጋር በተለያዩ ርእሰ ጉዳዮች በስፋት ለመንቀሳቀስ እየሞከረ ነው፡፡ በተለይ ከኦሎምፒክ ኮሚቴው፤ ከአትሌቲክስ እና ከእግር ኳስ ፌደሬሽኖች ጋር ነው፡፡
የማህበሩ አደረጃጀት የዓለም አቀፉን የስፖርት ጋዜጠኞች ማህበር ስርዓት እንዲከተል እንፈልጋለን በማለት ለስፖርት አድማስ የተናገረው ፕሬዝዳንቱ አቶ ዮናስ ተሾመ፤ በሚቀጥሉት ሁለት ዓመታት በአፍሪካ የስፖርት ጋዜጠኞች ማህበር ያለውን ተፅእኖ ፈጣሪነት በማሳደግ አህጉራዊውን ጉባኤ ለማስተናገድ ማቀዱን ጠቁሟል፡፡ ከሁለት ዓመታት በፊት በታላቁ ሩጫ በኢትዮጵያ አማካኝነት አዲስ አበባ ላይ የዓለም አቀፉ የስፖርት ጋዜጠኞች ማህበር ስራ አስፈፃሚ ልዩ ስብሰባ በአዲስ አበባ መስተናገዱ ይታወሳል፡፡  
የኢትዮጵያ የስፖርት ጋዜጠኞች ማህበር በአሁኑ ወቅት ከ100 በላይ አባላት ያሉት ሲሆን፤ ከነዚህ መካከል 85ቱ ዓለም ዓቀፍ የስፖርት ጋዜጠኞች ማህበር አባል ናቸው፡፡

  ይድረስ ለላንቺና ላንተ አምድ አዘጋጆች ከነታዳሚዎቻችሁ እንደምንሰነበታችሁ የሚለውን ሰላምታ ያገኘነው ከአንድ አንባቢ ነው፡፡ የግል ታሪኩን የብዙዎች ሰዎች ገጠመኝ ሊሆን ስለሚችል እባካችሁ አስነብቡልኝ ብሎናል፡፡ የአምዱ ዝግጅት ክፍልም በሀሳቡ በመስማማት እነሆ ለንባብ ብሎአል፡፡
እኔ ያደግሁት በጣም ብዙ ቤተሰብ ውስጥ ነው፡፡ እናትና አባቴ አስር ልጆች ነበር የወለዱት፡፡ እኔ አራተኛ ስሆን ወንድ ለመወለዱ ግን የመጀመሪያ ነበርኩ። የእኔ ታላላቆች ሴቶች ናቸው፡፡ የሚገርመው ነገር ከእኔም በሁዋላ ወንድ አልተወለደም፡፡ ስለዚህም ስሜ የወንድወሰን ተባለ፡፡ እናትና አባቴ ሁልጊዜ የሚናገሩት ነገር ነበረ፡፡ ይኼውም እኔ ወንድ ልጅ ስለሆንኩ ከመንደር ልጆች ጋር ኳስ ስጫወት እውላለሁ፡፡ ወደእኔ ቤት ይመጣሉ ወደእነሱ ቤት እሄዳለሁ፡፡ ታዲያ እናቴ ምርር ሲላት “ምን የመንደር ውሪ ተሰበስባለህ? እዚህ ያለው ሰው መች አነሰና ነው? አርፈህ አትቀመጥም? የሁልጊዜ ንግግርዋ ነበር፡፡ እኔ ግን ልጅ በጣም እወድ ስለነበር ብቻዬን መሆን አልፈልግም ነበር፡፡ አባቴ ደግሞ በበኩሉ “እኔ በበኩሌ የምፈራው ይህ ልጅ ካለዘር እንዳይቀር ነው” ይል ነበር፡፡ በዚህ ንግግሩ እንዲያውም እናትና አባቴ ሁልጊዜ ነበር የሚጣሉት፡፡
ትዳር መያዝ አይቀርምና ጊዜው ደርሶ ተዳርኩኝ፡፡ ነገር ግን አመታት እየተቆጠሩ ሄዱ፡፡ ልጅ አልመጣም። አባቴም “ይኼውላችሁዋ… እኔ የሚሰማኝ አላገኘሁም እንጂ ብዬ ነበር” ሲል እናቴ ደግሞ “ብዬ ነበር ማለት ምን ማለት ነው? ልጅ በሰው እጅ አይሰራ…ምን ማድረግ ይቻል ነበር? መካንነቱ ከእሱ ቢሆንስ?” አባቴም “ተይ ባክሽ ይቺ… ምን ትላለች… እኔ እንደሆንኩ በዘሬም መካን የለም…. በእርግጥ ያንቺን አላውቅም…” እናቴም ትመልስና “ወገኛ ነህ እባክህ፡፡ ስለእኔ እንኩዋን አሳምረህ ታውቃለህ፡፡ በልጅቱም በኩል የሆነ እንደሆነ ዘር ማንዘርዋን አሳምረን እናውቀዋለን፡፡ ወላዶች ናቸው። የራስ ልጅ ቢሆንስ መካን የሆነው? ምን ልትል ነው? ትለዋለች፡፡
የእናትና የአባቴ ንትርክ ጠዋት ማታ መሆኑን ታናናሽ እህቶቼ ይነግሩኛል፡፡ እኔ ያስጨነቀኝ ግን የእነሱ ጉዳይ አልነበረም፡፡ የእራሴ የትዳር መቀጠልና አለመቀጠል … እንዲሁም የልጅቱም ሆነ የእኔ ቤተሰቦች ፍላጎት መሟላት አለመቻሉ ነበር፡፡ ነገር ግን በቃ… አልኩና ቆርጬ ተነሳሁ፡፡ ይህ ነገር ስንፍና አይፈልግም ብዬ ከሐኪሞች ጋር መመካከር ጀመርኩኝ፡፡ ወደ ሕክምናው የሄድነው በተጋባን በ5 አመታችን ነበር። በጊዜው እኔ ማለትም ወንድየው ወደ 40 አመት የገባሁ ስሆን ባለቤቴ ደግሞ በሰላሳዎቹ መጀመሪያ ላይ ነበረች። በእርግጥ በእነዚህ የትዳራችን 5 አመታት ለማርገዝ አስበን ባይሆንም እራሳችንን ግን አላቀብንም። ምክንያቱ ምንድነው? የሚለውን መልስ ለማግኘት ወደ ሐኪም ስንቀርብ ግን ዶክተራችን ጥሩ የጤና ሁኔታ ላይ እንደምንገኝ እና በትእግስት እንድንቆይ  ነግሮናል፡፡ ታዲያ ብንጠብቅ ብንጠብቅ  እርግዝናው በፍጹም እውን ሊሆን አልቻለም፡፡ ብዙ ሞከርን፡፡ ግን አልተሳካም፡፡ በጣም በንዴት ለዶክተሩ እንዲህ አልኩት፡፡ “እኔ ገና የ40 አመት ሰው ነኝ፡፡ ሚስቴ ደግሞ የ32 አመት ሴት ናት፡፡ ምን ምክንያት ቢገኝ ነው የማታረግዘው?” ብዬ ጠየቅሁት፡፡ የእሱም መልስ አሁንም ጤነኛ ናችሁ ሞክሩ የሚል ሆነ። እኛ በጉጉት በራሳችን መንገድ አላማችንን ለማሳካት ጥረታችንን ጀመርን፡፡ ስንጀምረው ሁለታችንም ቶሎ እንደሚሆን አምነን ነበር። ምክንያቱም ሁለታችንም እንዋደዳለን፡፡ ባለቤቴም የእርግዝና መከላከያ ሞክራ እንኩዋን አታውቅም፡፡ እንዲያውም የወርአበባ ማስተካከያ እየተባለ ለማርገዝ ስንፈልግ በሞከርነው ሕክምና ኪኒኑን የዋጠችበት ወቅት ነበር፡፡ ምንም ቢደረግ ግን የወር አበባዋ  አይቀርም…. እርግዝና የለም። እናም ግራ ገባን፡፡ ትክከለኛው ጊዜ ሲደርስ ሊሆን እንደሚችል ለራሳችን ነግረን ጥረታችንን ኮስተር ብለን በቅንነት ቀጠልን፡፡ በኋላ ላይ ነበር ልጅ ለመውለድ የምናደርገውን ጥረት የሚያውክ ነገር በሁለታችንም መካከል መኖሩን ያመንኩት፡፡ እንዴት አወቅህ ብትሉኝ ስለጉዳዩ ማንበብ በመጀመሬ ነው፡፡ ሰዎች ልጅ መውለድ አልቻሉም ወይንም የማይችሉ ናቸው የሚባለው ካለምንም ጥንቃቄ ለአመታት ወሲብ እየፈጸሙ ነገር ግን ልጀ መውለድ ካልቻሉ እና ወይንም ቀደም ሲል የተወሰነ ልጅ ወልደው ነገር ግን ሴትዋ ድጋሚ ማርገዝ ሲያቅታት ነው፡፡ ይላል፡፡ እኛ ግን ከመጀመሪያውኑም ስላልወለድን ምክንያቱን ለማወቅ አሁንም የቻልኩትን ያህል ማንበብ ጀመርኩኝ፡፡ በዚህ ዙሪያ የተጻፉት መጽሐፎች ብዙ ነገር ይመክራሉ፡፡ ለምሳሌም፡-
የሴትዋ እድሜ በተለይም በተቻለ መጠን 29 አመት እስኪሆን ባለው ጊዜ ማርገዝ ብትችል፣
በተለያዩ ሕመሞች ምክንያት የተለያዩ መድሀኒቶችን መውሰድ፣
በወንድ ተፈጥሮአዊ ሁኔታ እና እንዲሁም በሴትዋ ተፈጥሮአዊ ሁኔታዎች ማለትም በስነተዋልዶ አካላት ላይ ሊፈጠሩ በሚችሉ ችግሮች፣
በአኑዋኑዋር ምክንያት ሰውነት ላይ ሊፈጠሩ የሚችሉ አንዳንድ ጫናዎች ማለትም፡-
ቅጥ ያጣ ውፍረት፣
መጠጥ መጠጣት፣
አንዳንድ እንደ ሲጋራ ማጤስ የመሳሰሉ አጉዋጉል ባህሪዮች፣
የአመጋገብ ሁኔታ፣‘
በቂ የሆነ የሰውነት እንቅስቃሴ አለማድረግ የመሳሰሉት ነገሮች ልጅ ለማግኘት የሚደረገውን ጥረት ሊያውክ እንደሚችል ተረዳሁ፡፡
ከዚህም በመነሳት ለባለቤቴ የሚከተሉትን ጥያቄዎች ለየራሳችን አናቅርብ አልኩዋት፡፡ ጥያቄዎቹም የሚከተሉት ነበሩ፡፡ ምንም የጤና እክል ከሌለብን እንዴት እነዚህ ልጅ መውለድ አልቻልንም? ምንድን ነበረ ማስተካከል የሚገባን? ሰውነታችንን በትክክል ባለመጠበቃችን ነው?  ወይንስ አልኮል በመጠጣታችን ጫት በመቃማችን? እያልን ለእራሳችን ጥያቄውን ለየብቻችን መልሰን ከዚያም በጋራ እንድንነጋገር ተስማማን፡፡ መልሱ ሲመጣ ግን የሁለታችንም ሀሳብ አንድ አይነት ነበር፡፡ ሁለታችንም… ልጅ የለን …ለማን ብለን ነው? እረ ብዪ …አረ ብላ… አረ ጠጪ… አረ ጠጣ…እየተባባልን በጣም እንበላለን… በጣም እንጠጣለን፡፡ ከዚያም በሁዋላ ቅዳሜና እሁድ ከጫት የሚለየን ማንም የለም፡፡ አንዳንድ ማህበራዊ ጉዳዮች ሲገጥሙን እንኩዋን ምክንያት እየሰጠን የምንቀርባቸው ጊዜያት በጣም ብዙ ናቸው፡፡ ይህ ልጅ ላለመውለድ ብቻም ሳይሆን ለራሳችንም ጤንነት ስህተትና ሊታረም የሚገባው መሆኑን አመንን፡፡
አንድ ቀን ሳንደባበቅ እንድንነጋገር ተስማማን። ከአዲስ አበባ ወጣ ብለን ማለትም ወደ ናዝሬት በመሔድ ለሁለት ቀን ቆየን፡፡ በዚያ መዝናኛ እያለን እስቲ የየሆዳችንን እንነጋገር ተባባልን፡፡ እውነታው እንደሚከተለው ነበር፡፡ እኔ ባልየው በተለይ በጣም ነበር የምበሳጨው፡፡ አባቴ እንደተናገረው መሐን ሆኜ መቅረቴ ነው…ወይኔ? እያልኩ ባለቤቴ ሳታየኝ እጅግ በጣም እበሳጭ ነበር፡፡ የሁዋላ ሁዋ ላም ባለቤቴን ሳናግራት…እኔ እኮ በየምሽቱ ከፈጣሪ ጋር እነጋገር ነበር፡፡ … ምን በድዬህ ነው ፈጣሪዬ? አረባክህ ከሰው አስተካክለኝ? እያልኩ እጅግ በጣም ነው የምጨነቀው፡፡ እንዲያውም ወሲብ ወደመፈጸም ስናመራ ለእራሴ…ምን ያደርግልኛል …ልጅ እንደሆነ አልወልድ…እያልኩ አማርራለሁ…ነበር ያለችኝ፡፡  
በሁኔታው እጅግ ተገርሜ እና አዝኜ ነበር ብድግ ብዬ ያቀፍኩዋት፡፡ ከዚህ በሁዋላ ለእኔ አንቺ እንደ ልጄ ነሽ የምቆጥርሽ … በቃ እርም ያድርግብኝ… ሁለተኛ ስለዚህ ነገር ብናስብ እግዚአብሔር ይፍረድብን አልኩዋት፡፡ እሱዋም እኔ ላንተ እያዘንኩ ነው እንጂ የምሰቃየው የምወድህ ባሌ ወንድሜ ስለሆንክ አንተን ካልከፋህ አረ እኔ ሁለተኛ ስለዚህ ነገር አላስብም አለችኝ፡፡ በዚህ ጊዜ ከተጋባን ወደ ስምንት አመት ሆኖናል፡፡ ሁለታችንም ስለወደፊቱ አኑዋኑዋራችንን ለእራሳችን ስንል ሁኔታዎችን እናስተካክል በሚለው ተስማምተን …አንዳንችን ለአንዳችን ቃል ገብተን በሙሉ ልብ በፍቅር ካለጭንቀት እንደ አዲስ ፍቅረኛ ተቃቅፈን አደርን፡፡ ወደቤታችንም ስንመለስ ያንኑ ቀጠልን፡፡ አዲስ ሕይወት ጀመርን፡፡  ልብ በሉ ብቻ፡፡ ይህ በሆነ በሶስተኛ ወሩ የወር አበባዋ ቀረ፡፡ አረ ተይው …አረ ተወው… እያሾፈብን ነው፡፡ ይልቅስ ሕመም እንዳይመጣ ታከሚ አልኩዋት፡፡ በሁለተኛውም ወር አልመጣም፡፡ ሕመም እንዳይሆን ፈርቼ ወደሕክምና ብወስዳት የምርመራው ውጤት እርግዝና ነው ተባለ፡፡ እኔና ባለቤቴ ተገርመን አሁንም ተነጋገርን፡፡ ከሆነ ይሁን ካልሆነም የራሱ ጉዳይ ብለን እራሳችንን ቅጥ ካጣ ደስታ ገደብን፡፡ ነገር ግን ሐኪማችንም እንደመሰከረው በመነጋገርና ጭንቀትን በማስወገድ ብቻ…እነሆ ዛሬ የሶስት ልጆች እናት እና አባት ነን፡፡ የመጀመሪያዋ ልጃችን ዘንድሮ ስምንተኛ ክፍልን ተፈተነች፡፡ ስለዚህ ኑሮን በአቅም ከማስተካከል …ባህርይን ከማረቅ ጀምሮ ወለድኩ አልወለድኩ ብሎ አለመጨነቅ ልጅ ለማግኘት ይረዳል፡፡

  ውሻውን በናይጀሪያው ፕሬዚዳንት ሙሃመድ ቡሃሪ ስም በመሰየሙ ባለፈው አመት የታሰረውና ሰላም የሚያደፈርስ ተግባር ፈጽሟል በሚል ክስ የተመሰረተበትን ናይጀሪያዊው ጆአኪም ኢሮኮን ጉዳይ ሲመረምር የቆየው ፍርድ ቤት፣ ግለሰቡን ከጥፋተኝነት ነጻ የሚያደርግ ውሳኔ አስተላልፏል፡፡
የፍርድ ቤቱ ዋና ዳኛ፤ ግለሰቡ የአገሪቱን ሰላም የሚያደፈርስ ተግባር ስለመፈጸሙ የሚያረጋግጥ በቂ ማስረጃ ባለመቅረቡ ተጠያቂ ሊሆን አይችልም በማለት ባለፈው ረቡዕ ነጻ መሆኑን የሚያረጋግጠውን ውሳኔ እንዳስተላለፉ ቢቢሲ ዘግቧል፡፡
ግለሰቡ ውሻውን በፕሬዚዳንቱ ስም መሰየሙን ለፖሊስ የጠቆመውና ያሳሰረው አንድ ጎረቤቱ የሆነ ሰው እንደነበር ያስታወሰው ዘገባው፤ እስራቱ  በመላ አገሪቱ ተቃውሞ ገጥሞት እንደነበርም ዘገባው አውስቷል፡፡
በአነስተኛ የንግድ ስራ ላይ ተሰማርቶ ህይወቱን የሚገፋው የ41 አመቱ ተከሳሽ፣ በውሻው ግራና ቀኝ ጎን ላይ ቡሃሪ የሚል ጽሁፍ በመለጠፍ፣ የፕሬዚዳንቱ ደጋፊዎች በሚበዙበት አካባቢ ሲንቀሳቀስ ታይቷል፤ ይህም ድርጊት ጸብ አጫሪና ሰላምን የሚያደፈርስ ነው በማለት ፖሊስ በቁጥጥር ስር አውሎ ክስ እንደመሰረተበትም ዘገባው አስታውሷል፡፡
ፍርድ ቤቱ ውሳኔውን ማስተላለፉን ተከትሎ፣ ግለሰቡ በሰጠው መግለጫ፣ “የምወደውን ውሻዬን በማደንቀው ጀግናዬ በፕሬዚዳንት ቡሃሪ ስም መሰየሜ ከመልካም ስሜት የመነጨ ነው፤ መታሰሬ አግባብ እንዳልነበር አውቃለሁ፣ ድርጊቱን በመቃወም ከጎኔ የቆማችሁትን ሁሉ አመሰግናለሁ” ማለቱንም ዘገባው ገልጧል፡፡