Administrator

Administrator

    ኢንተርኮንትኔንታል አዲስ ሆቴል ያስገነባውና በምሥራቅ አፍሪካ የመጀመሪያው እንደሆነ የተነገረለት 360 ድግሪ የሚሽከረከረው ሬስቶራንት ሰሞኑን አገልግሎት መስጠት ጀመረ፡፡
ሆቴሉ በቅርቡ ግንባታውን አጠናቆ አገልግሎት ላይ ያዋለው አዲሱ ሬስቶራንት፣ 360 ድግሪ እየተሽከረከረ ደንበኞች የከተማዋን ዙሪያ እየቃኙ እንዲዝናኑ ለማድረግ ያስችላል ተብሏል፡፡ ሆቴሉ ከትናንት በስቲያ 11ኛ ፎቅ ላይ የሚገኘውን ተሽከርካሪ ሬስቶራንት ለጋዜጠኞች ባስጎበኘበት ወቅት፣ የሆቴሉ ዋና ሥራ አስኪያጅ አቶ ይልቃል በቃሉ እንደተናገሩት፣ ተሽከርካሪው ሬስቶራንት በአንድ ጊዜ 120 እንግዶችን ይዞ፣ 360 ድግሪ በመሽከርከር፣ የአዲስ አበባ ከተማን ዙሪያ ያስቃኛል፡፡ ተሽከርካሪው ሬስቶራንት ከተነሳበት ቦታ ተመልሶ ለመድረስ 55 ደቂቃዎች ይወስድበታል ተብሏል፡፡
ሬስቶራንቱ የተለያዩ ሀገራትንና  ባህላዊ የኢትዮጵያ ምግቦችን ለደንበኞቹ ያቀርባል ያሉት ሥራ አሥኪያጁ፤ ደንበኛው ላገኘው አገልግሎት የሚከፍለው ዋጋ ተመጣጣኝ እንደሆነም ገልፀዋል፡፡
በቱሪዝም እንቅስቃሴ ውስጥ ያለውን የገበያ መቀዛቀዝ ችግር መፍትሄ እንደሚያስገኝ እምነት የተጣለበት ስብሰባ፤ የፊታችን ማክሰኞ እዚሁ አዲስ አበባ ከተማ ውስጥ እእንደሚካሄድ አቶ ይልቃል በቃሉ ተናግረዋል፡፡
አምና በዚህ ወቅት በአገሪቱ ተከስቶ ከነበረው አለመረጋጋት ጋር ተያይዞ፣ ከፍተኛ የእንግዶች የፕሮግራም ስረዛ ገጥሞን ነበር ያሉት ሥራ አስኪያጁ፤ ዘንድሮ ግን በአንፃራዊ መልኩ የተሻለ እንደሆነ ገልፀዋል፡፡  

  አጠቃላይ ሃብታቸው 1.08 ትሪሊዮን ዶላር ደርሷል

       ታዋቂው ፎርብስ መጽሄት፣ የ2017 የፈረንጆች አመት፣የአለማችን የቴክኖሎጂ ዘርፍ ቀዳሚ 100 ቢሊየነሮችን ዝርዝር ከትናንት በስቲያ ይፋ ያደረገ ሲሆን በአመቱ የ6.5 ቢሊዮን ዶላር ገቢ በማግኘት የተጣራ ሃብታቸውን 84.5 ቢሊዮን ዶላር ያደረሱት  የአለማችን ቁጥር አንድ ቢሊየነር የማይክሮሶፍት መስራች ቢል ጌትስ ቀዳሚውን ስፍራ ይዘዋል፡፡
የአማዞኑ መስራች ጄፍ ቤዞስ፣ በ81.7 ቢሊዮን ዶላር የሁለተኛነትን ደረጃ ሲይዙ፣ የፌስቡኩ መስራች ማርክ ዙክበርግ፣ በ69.6 ቢሊዮን ዶላር የአመቱ የአለማችን ሶስተኛው የቴክኖሎጂ ዘርፍ ባለጸጋ መሆኑን ፎርብስ ለሶስተኛ ጊዜ ባወጣው አመታዊ ዝርዝሩ አመልክቷል፡፡
በአመቱ ከፍተኛውን ገቢ ያገኘውም ማርክ ዙክበርግ ሲሆን የዙክበርግ የሃብት መጠን አምና ከነበረው በ15.6 ቢሊዮን ዶላር ጭማሪ አሳይቷል ተብሏል፡፡ ዙክበርግ በዝርዝሩ ውስጥ ከተካተቱትና ዕድሜያቸው ከ40 አመት በታች ከሆነ 16 ባለጸጎች አንዱ መሆኑም ተነግሯል፡፡ ከዙክበርግ በመቀጠል በአመቱ ከፍተኛውን ሃብት ያፈሩት የአማዞኑ ጄፍ ቤዞስ ናቸው ያለው ፎርብስ፤ ሰውዬው ባለፉት 12 ወራት የሃብት መጠናቸውን በ15.5 ቢሊዮን ዶላር ከፍ ማድረግ መቻላቸውን አክሎ ገልጧል፡፡
ከአመቱ 100 የአለማችን የቴክኖሎጂ ቢሊየነሮች ግማሹ አሜሪካውያን ሲሆኑ ስምንቱ ከአንድ እስከ አስር ባለው ደረጃ ውስጥ የተካተቱ ናቸው፡፡ 33 ያህሉ እስያውያን ባለጸጎች ሲሆኑ ከእነዚህ ውስጥ ከግማሽ በላይ የሚሆኑት የቻይና እና የሆንግ ኮንግ ቢሊየነሮች መሆናቸው ተነግሯል፡፡
ከ100 የዘርፉ ባለሃብቶች መካከል 11 የሚሆኑት የሃብት መጠናቸው አምና ከነበረበት ቀንሷል ያለው ፎርብስ፤ ከፍተኛውን ኪሳራ ያስተናገደው ዢያኦሚ የተባለውን ስማርት ስልክ የሚያመርተው ኩባንያ መስራችና ባለቤት ሊ ጁን መሆኑንና፣ የሰውየው የሃብት መጠን በአመቱ በ2.9 ቢሊዮን ዶላር መቀነሱን አመልክቷል፡፡
የአለማችን የቴክኖሎጂ ዘርፍ ባለሃብቶች አጠቃላይ ሃብት ድምር ዘንድሮ ለመጀመሪያ ጊዜ ከአንድ ትሪሊዮን ዶላር በላይ በማለፍ፣ 1.08 ትሪሊዮን ዶላር መድረሱንም ፎርብስ አስታውቋል።

   - አገሪቱ የ300 ሚ. ዶላር ወታደራዊና ኢኮኖሚያዊ እርዳታ አጥታለች
                     - የሰብአዊ መብቶች ጥሰትን እስክታሻሽል ድረስ የ195 ሚ.ዶላር ድጋፍ ታግዷል

      የዶናልድ ትራምፕ አስተዳደር፣ አሜሪካ ለግብጽ ከምትሰጠው አመታዊ ወታደራዊና ኢኮኖሚያዊ የገንዘብ እርዳታ ላይ የ100 ሚሊዮን ዶላር ያህል ቅናሽ ማድረጉንና ተጨማሪ የ195 ሚሊዮን ዶላር ወታደራዊ ድጋፍ ማገዱን ባለፈው ማክሰኞ ያስታወቀ ሲሆን የግብጽ መንግስት በውሳኔው ክፉኛ መበሳጨቱ ተዘግቧል፡፡
የግብጽ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ባለፈው ረቡዕ ባወጣው መግለጫ፤ የትራምፕ አስተዳደር የወሰደውን የእርዳታ ቅናሽና እገዳ እርምጃ ክፉኛ የተቸ ሲሆን እርምጃው በሁለቱ አገራት መካከል ለረጅም ዘመናት የዘለቀውን ስትራቴጂካዊ ግንኙነትና ግብጽን መርዳት ያለውን ጠቀሜታ በቅጡ ካለመረዳት የመነጨ ነው ብሎታል፡፡
አሜሪካ ለግብጽ የምትሰጠውን እርዳታ መቀነሷ፣ የሁለቱን አገራት የጋራ ጥቅሞች እውን ለማድረግ በሚደረገው ጥረት ውስጥ አሉታዊ ተጽዕኖ ሊፈጥር ይችላል ሲልም ሚኒስቴሩ ባወጣው መግለጫ አስጠንቅቋል፡፡
የትራምፕ አስተዳደር፣ በግብጽ የሚታየው የሰብዓዊ መብቶች ጥሰት ሁኔታ እየከፋ በመምጣቱና የሲቪክስና መንግስታዊ ያልሆኑ ተቋማት ላይ የሚደረጉ እገዳዎችና የመብት ጥሰቶች ባለመሻሻላቸው፣ ለግብጽ ሲሰጥ የቆየውን የ65.7 ሚሊዮን ዶላር ወታደራዊ ድጋፍና የ30 ሚሊዮን ዶላር የኢኮኖሚ እርዳታ ገንዘብ፣ ለሌሎች አገራት ለመስጠት መወሰኑን ዋሽንግተን ፖስት ዘግቧል፡፡
አሜሪካ ከዚህ በተጨማሪም ለግብጽ ልትሰጥ ያቀደቺውን የ195 ሚሊዮን ዶላር የወታደራዊ እርዳታ ማገዷን የዘገበው ቢቢሲ፤ ግብጽ የሰብአዊ መብቶች ጥሰትንና መንግስታዊ ባልሆኑ ድርጅቶች ላይ የጣለቺውን አፋኝ ህግ እስክታሻሽል ድረስ ገንዘቡ በባንክ እንደሚቆይ መነገሩን አመልክቷል፡፡
ግብጽ ከአሜሪካ ከፍተኛውን አመታዊ ወታደራዊና ኢኮኖሚያዊ እርዳታ ከሚያገኙ ቀዳሚዎቹ አገራት አንዷ እንደሆነች የጠቆመው ዘገባው፤ በየአመቱ 1.3 ቢሊዮን ዶላር ወታደራዊ እርዳታ ስታገኝ እንደነበርም አስታውሷል፡፡

  እጅግ ከፍተኛ ዋጋ የሚያወጡ የቅንጦት መኪኖችን በማምረት የሚታወቀው ላምቦርጊኒ፤ አሁን ደግሞ አልፋ ዋን የተባለና 2ሺህ 450 ዶላር የሚሸጥ በአይነቱ የተለየ የቅንጦት ሞባይል አምርቶ በገበያ ላይ ማዋሉ ተዘግቧል፡፡
ባለፈው ማክሰኞ በይፋ የተመረቀውና 4 ጊጋ ባይት ራም እና 64 ጊጋ ባይት ስቶሬጅ ያለው አልፋ ዋን ስማርት ፎን፣ ተጨማሪ 128 ጊጋ ባይት ሚሞሪ እንደሚቀበል የዘገበው ሜይል ኦንላይን፤ ባለ 20 ሜጋ ፒክስልና ባለ 8 ሜጋ ፒክስል ካሜራዎች እንደተገጠሙለትም አመልክቷል፡፡
ሁለት ሲም ካርድ የሚወስደውና በውድ የጣሊያን ቆዳ የተለበጠው አልፋ ዋን፤ በመጀመሪያው የሽያጭ ምዕራፍ ለእንግሊዝና ለተባበሩት የአረብ ኢሜሬትስ ገበያ እንደቀረበ ቢነገርም፣ የመሸጫ ዋጋው እጅግ ከመጋነኑ የተነሳ በብዛት የመሸጥ ዕድሉ ጠባብ እንደሆነ እየተነገረ ነው፡፡
የአልፋ ዋን የመሸጫ ዋጋ በዚህ አመት ለገበያ ከቀረቡት ሌሎች ታዋቂ ዘመናዊ ስማርት ፎኖች በ300 እጥፍ ያህል እንደሚበልጥ የጠቆመው ዘገባው፤ ይዞታው ከሌሎች ስማርት ፎኖች ጋር ተመሳሳይ እንደመሆኑ የመሸጫ ዋጋው ይሄን ያህል መጋነን አልነበረበትም የሚል ትችት እየተሰነዘረበት እንደሚገኝም አስረድቷል፡፡
ሰሞኑን ለገበያ የቀረበው አዲሱ ጋላክሲ ኤስ 8 ስማርት ፎን፣ በ900 ዶላር እየተሸጠ እንደሚገኝና አዲሱ የአፕል ምርት አይፎን 8 ደግሞ ቢበዛ 1 ሺህ ዶላር የመሸጫ ዋጋ ሊተመንለት እንደሚችል እየተነገረ መሆኑን የጠቀሰው ዘገባው፤ አልፋ ዋን 2 ሺህ 500 ዶላር መሸጡ አግባብ አለመሆኑን የሚናገሩ መብዛታቸውን ገልጧል፡፡

     “ጥይቱ ባቡር” በሰዓት 350 ኪ.ሜ ይበርራል

      ፉዢንግ የሚል ስያሜ ያለውና በፍጥነቱ በአለማችን አቻ የማይገኝለት ቻይና ሰራሽ ባቡር፣ ከስድስት አመታት በፊት በደረሰበት አሰቃቂ አደጋ፣ 40 ሰዎችን ለህልፈተ ህይወት፣ 191 ያህሉን ደግሞ ለመቁሰል አደጋ መዳረጉን ተከትሎ፣ የአገሪቱ መንግስት ባቡሩ ቢበዛ በሰዓት 300 ኪሎ ሜትር ብቻ እንዲፈጥን ማዕቀብ ጥሎበት ነበር፡፡ ከሰሞኑ ግን፣ ይሄው እንደ ጥይት የሚወነጨፍ ባቡር ዳግም በሙሉ አቅሙ ሊከንፍ እንደሆነ ተዘግቧል፡፡
ፉዢንግ ከመጪው ሳምንት ጀምሮ በሰዓት 350 ኪሎ ሜትር ፍጥነት፣ ከመዲናዋ ቤጂንግ ወደ ሻንጋይ ሊወነጨፍ ሞተሩን እያሞቀ ነው ሲል የዘገበው ቢቢሲ፤ 1ሺህ 250 ኪሎ ሜትር የሚደርሰውን ይሄን ርቀት በ4 ሰዓት ከ30 ደቂቃ ጊዜ ውስጥ ያጠናቅቀዋል ተብሎ እንደሚጠበቅ አመልክቷል፡፡
ቢቢሲ እንደዘገበው፣ ቻይና በርካታ ፉዢንግ ባቡሮች ቢኖሯትም፣ በፍጥነታቸው ሳቢያ አደጋ እንዳያስከትሉ በመስጋት እስከ መጪው መስከረም ወር አጋማሽ ድረስ ሰባቱን ብቻ በከፍተኛው የፍጥነት አቅማቸው እንዲበርሩ ልትፈቅድላቸው አቅዳለች፡፡
ቻይና የባቡሮቹን የፍጥነት አቅም የበለጠ በማሳደግ ባለፈው ሰኔ ወር በሰዓት 400 ኪሎ ሜትር መጓዝ የሚችል ባቡር መስራቷን ያስታወሰው ዘገባው፤ በአገሪቱ በድምሩ 19 ሺህ 960 ኪሎ ሜትር እርዝመት ያላቸው የፈጣን ባቡር ሃዲድ መስመሮች እንደተገነቡና እስከ 2020 ድረስም ተጨማሪ 10 ሺህ ኪሎ ሜትሮችን ለመዘርጋት መታቀዱን አመልክቷል፡፡
አገሪቱ በአለማችን እጅግ ትልቁ የሆነውን የፈጣን ባቡር ሃዲድ መስመሮች ኔትወርክ መሰረተ ልማት ለመዘርጋት 360 ቢሊዮን  ዶላር  ወጪ እንዳደረገችም ዘገባው አክሎ ገልጧል፡፡

  አንድ ደቡብ አፍሪካዊ፣ የሰው ስጋ መብላት ሰለቸኝ ሲል ለፖሊስ እጁን መስጠቱን ተከትሎ፣ በ”ሰው በላነት” ተሳትፈዋል የተባሉ 5 ሌሎች ተጠርጣሪዎች በፖሊስ  ቁጥጥር ስር መዋላቸውን ዘ ኢንዲፔንደንት ከትናንት በስቲያ ዘግቧል፡፡
ግለሰቡ ለረጅም ጊዜ የሰዎችን ስጋ በመብላት እንደቆየ ባለፈው ረቡዕ ለፖሊስ የተናዘዘ ሲሆን ደብቆት የነበረውን ቁራጭ የሰው እጅና እግርም ለፖሊስ አስረክቧል ተብሏል፡፡ ፖሊስ የግለሰቡን ጥቆማ መሰረት በማድረግ፣ ክዋዙሉ ናታል በተባለው የአገሪቱ ግዛት ባደረገው ፍተሻ፣ በርካታ የሰው አካላት ቁርጥራጮችን ማግኘቱን ዘገባው ገልጧል፡፡ ተጠርጣሪዎቹ ሰው በመግደል፣ በመቆራረጥና የሰውነት ክፍሎችን በቤት ውስጥ በመደበቅ ክስ እንደሚመሰረትባቸው የጠቆመው ዘገባው፤ በአገሪቱ አንዳንድ ማህበረሰቦች ዘንድ የሰው ስጋ መብላት፣ ከእርኩስ መንፈስና ከበሽታ ይፈውሳል የሚል አጉል እምነት እንዳለ አመልክቷል፡፡

 ልጅ መውለድ ተፈጥሮአዊ ሂደት ነው፡፡ ልጅ መውለድ ተፈጥሮ እራስዋ የምታዘጋጀው መገታት የማይችል ፍላጎት ነው፡፡ የሰው ልጅ ልጅ መውለድን በሕይወቱ ውስጥ እንደ አንድ ዋስትና አድርጎ ይቆጥረዋል። ሰው ልጅ መውለድ ካልቻለ ትልቅ ነገር እንደጎደለው የሚ ቆጥርበት አጋጣሚ በብዛት ይስተዋላል፡፡ በእርግጥ አልፎ አልፎ አለመውለዳቸውን በፀጋ የሚቀበሉ ቢኖሩም የብዙዎች ስሜት ግን ሲጎዳ ይታያል፡፡
ዶ/ር መብራቱ ጀምበር
የጽንስና ማህጸን ሕክምና እስፔሻሊስት
ልጅን ስለ መውለድ ለዚህ እትም እንግዳ ያደረግነው ዶ/ር መብራቱ ጀምበር የጽንስና ማህጸን ሕክምና እስፔሻሊስት ናቸው፡፡ ልጅን መውለድ በምጥ ወይንስ በኦፕራሲዮን? ለሚለው ሀሳብ ማብራሪያቸውን እንደሚከተለው ለአንባቢ አጋርተዋል፡፡
ጥ /    ልጅ በምን መንገድ ይወለዳል?
መ/ እስከአሁን ድረስ የሚታወቁት የልጅ መውለጃ መንገዶች ሁለት ናቸው፡፡ አንደኛው በተፈጥሮ መንገድ በምጥ ሲሆን ሌላ ደግሞ በኦፕራሲዮን ነው፡፡ በኦፕራሲዮን የሚወልዱት በተፈጥሮአዊ መንገድ በተለያዩ ምክንያቶች መውለድ የማይችሉት ናቸው፡፡ በምጥ መውለድ ማለት ተፈጥሮአዊውና የተፈቀደው መንገድ በመሆኑም ትክለኛው የአወላለድ ዘዴ ሲሆን አብዛኛውን ጊዜ በዚህ መንገድ ልጆች ይወለዳሉ፡፡ በኦፕራሲዮን የሚወለደው በምጥ ከሚወለደው ቁጥሩ ያነሰ ነው፡፡ ቴክኖሎጂው ወይንም የህክምና ጥበቡ ባላደገበት ወቅት ብዙ እናቶች በተፈጥሮ መንገድ ልጅ መውለድ እያቃታቸው ለተለያዩ አካላዊ ጉዳቶች መጋለጥ እንዲሁም የሚወለዱት ልጆች ላይም ጫና የመድረስ ከዚህም ባለፈ እናቶች ብዙ የሚጎዱበት ሁኔታ ነበር፡፡ አሁን ግን በኦፕራሲዮን ማዋለዱ በስፋት እና ደረጃውን በጠበቀ መልኩ እየተሰራ ስለሆነ በምጥ መውለድ ያቃታቸው ሴቶችም ይሁኑ መወለድ ያቃታቸው ልጆች ከጉዳት ላይ የሚወድቁበት አጋጣሚ የለም ማለት ይቻላል፡፡
ጥ/    በምጥ የመውለድ ጠቀሜታ ምንድነው?
መ/    በምጥ መውለድ ብዙ ጥቅሞች አሉት፡፡ የመጀመሪያው ተፈጥሮአዊ ሂደት በመሆኑ የሚሰጠው ደስታ በጣም ከፍተኛ ነው፡፡ በምጥ የወለዱ ሴቶች አቅማቸው ቶሎ ይጠነክራል፡፡ አምጠው ሲወልዱ የእናትነት ፍቅሩም የተሻለ ይሆናል የሚል ግምት አለ። በምጥ ሲወልዱ ቶሎ ያገግማሉ፡፡ ከልጃቸውም ጋር ወዲያውኑ ስለሚገናኙ ቶሎ ጡት መስጠት ይችላሉ። ይህ በፍጥነት መገናኘት ፍቅሩንም ከፍ ያደርገዋል። ለዚህም ሲባል ልጁ በምጥ እንደተወለደ እትብቱ ሳይቆረጥ ከእናቱ ሆድ ላይ እንዲያርፍና ጡት እንዲይዝ በመደረግ ላይ ነው፡፡  ልጆቹም ቶሎ የእናታቸውን አይን ማየታቸው ትልቅ ስሜት እንዳለው ጥናቶች ያረጋግጣሉ።
ጥ/    በኦፕራሲዮን የመውለድ ጠቀሜታ ምንድነው?
መ/    በኦፕራሲዮን የመውለድ ጠቀሜታው በመጀመሪያ እናትየው በምጥ ብትወልድ ሊደርስ ባት የሚችለውን ጉዳት ማስወገድ መቻሉ ነው፡፡ ከዚህም በተጨማሪ ልጁ በምጥ ቢወ ለድ የከፋ ጉዳት የሚደርስበት ከሆነ  እና አደጋ ሊደርስ ይችላል ተብሎ በሕክምናው ሲረጋገጥ ወደኦፕራሲዮን ይኬዳል፡፡  ነገር ግን በአሁን ጊዜ ያስቸገረው ነገር በፍላጎት በኦፕራሲዮን ካልወለድኩ የሚሉ ሴቶች መብዛታቸው ነው፡፡ የዚህም ምክንያቱ አንዳንዶቹ በፍርሀት ሲሆን አንዳንዶቹ ደግሞ አስቀድመው በማንበብ ብልት አካባቢ የጡንቻ መላላት ሊያስከትልብኝ ይችላል ከሚል ስጋት የተነሳ ነው፡፡
ጥ/    በምጥ መውለድ የሚያደርሰው ችግር አለ?
መ/    በምጥ መውለድ ችግር ሊገጥመው ከሚያስችላቸው ነገሮች አንዱ ያልተመጣጠነ የምጥ ሁኔታ ከተፈጠረ ነው፡፡ ይም ማለት የልጁ ኪሎ ከእናትየው የመውለድ አቅም ጋር ካልተመጣጠነ በምጥ ሰአት በእናትየውም …በሚወለደውም ልጅ ላይ ጉዳት ሊከተል ይችላል፡፡ በምጥ ሰአት ምጡ ከባድ እና ረዥም ሰአት የሚወስድ ከሆነ የፊኛ፣ የሰገራ መውጫ መቀደድ፣ የፌስቱላ ሕመም ሊያጋጥም ይችላል፡፡ እነዚህን ነገሮች አስቀድሞ መተንበይ ስለሚቻል የእርግዝና ክትትል የምታደርግ ሴት ከሆነች ሐኪምዋ በምን መውለድ እንዳለባት አስቀድሞ መወሰን ይችላል፡፡
ጥ/    በኦፕራሲዮን መውለድ  የሚያደርሰው ችግር አለ?
መ/    በኦፕራሲዮን መውለድንና በምጥ መውለድን ስናወዳድር በኦፕራሲዮን መውለድ የበለጠ አሳሳቢ ነገር አለው፡፡ አስቀድሞ ከማደንዘዣው ጋር በተያያዘ ሊፈጠር የሚችል ጉዳት ሊኖር ይችላል፡፡ በኦፕራሲዮን ወቅት በማህጸን አካባቢ ያሉ ሌሎች የሰውነት ክፍሎችም ሊጎዱ የሚችሉበት አጋጣሚ ሊፈጠር ይችላል። ለምሳሌም አንጀት፣ ፊኛ፣ የሽንት መሽኛ መስመር፣ የሰገራ መውጫ ከውስጥ በኩል ሊጎዳ ይችላል።  በእርግጥ ይህ አልፎ አልፎ በተለይም ቀደም ብለው በኦፕራሲዮን የወለዱ ሴቶች ላይ የሚያጋጥም እንጂ ሁልጊዜ የሚከሰት አይደለም፡፡ አጋጣሚው ሊፈጠር ሚችለውም በአስቸኳይ ወይንም በአጣዳፊ በሚሰራበት ጊዜ ነው። በእርግጥ ጉዳቱ ከታየ የሚስተካከል ሲሆን መጥፎ የሚሆነው ግን ጉዳቱ መፈጠሩ ሳይታይ ከቆየ ነው፡፡ ስለዚህ ሁሉም ባለሙያ እንደዚህ ያለ አጋጣሚ ሊከሰት እንደሚችል አስቀድሞ ስለሚያውቅ ስራውን ሲጨርስ ሁኔታዎችን ሳያረጋግጥና ሳይፈትሽ አይወጣም። ኢንፌክሽን ወይንም መመረዝን በሚመለከት ግን በምጥም ይሁን በኦፕራሲዮን በመውለድ ጊዜ ሊያጋጥም የሚችል ሲሆን ነገር ግን በኦፕራሲዮን በመውለድ ጊዜ የሚፈጠረው የበለጠ አስከፊ ይሆናል፡፡ ስለዚህ ወላዶች ከሐኪማቸው በሚነገራቸው መመሪያ መሰረት በጥንቃቄ ሁኔታዎችን መከታተል ይገባቸዋል፡፡
ጥ/    የምጥ ሕመም እንዳይሰማ የሚያደርግ መድሀኒት አለ?
መ/    በአለም ላይ በአሁኑ ወቅት በስራ ላይ የሚገኝ እንደግማሽ ማደንዘዢያ የሚቆጠር ሙሉ ለሙሉ የምጡን ሕመም ስሜት አጥፍቶ ሌላ ሰውነት ግን እንዳይደነዝዝ የሚያደርግ መድሀኒት አለ፡፡ በአገራችን ግን ገና ያልተለመደ ነው፡፡
ጥ/    በኦፕራሲዮን የሚወለዱ ልጆች አእምሮአቸው በምጥ ከተወለዱት ይልቅ ንቁ ነው ይባላል? እውነት ነውን?
መ/    ይሄ አሻሚና በትክክል ለመመስከር የሚያስቸግር ነው፡፡ አንዳንድ ጥናት አቅራቢዎች በኦፕራሲዮን የተወለዱ ህጻናት ጭንቅላታቸው በምጥ ስላልተገፋ ይበልጥ አእምሮአቸው ንቁ ናቸው ሲል አንዳንዶች ደግሞ ይልቁንም አንድ ሕጻን ከመወለዱ በፊት በሳንባው እና በአንጀት አካባቢ ውሃ ስለሚኖረው በምጥ ወቅት እየተገፋ በሚያልፍበት አጋጣሚ በሂደት እየተጨመቀ ውሀው ከሰውነቱ እንዲወጣ ስለሚያግዝ ጠቃሚ ነገር ነው፡፡ ስለዚህ ቅድሚያ የሚሰጠው በተፈጥሮ መንገድ በምጥ መውለድ ነው፡፡
ጥ/    ልጅ ወልጃለሁ ብላ የምትደሰተው የትኛዋ ናት?
መ/    ልጁ እንደተወለደ በእናቱ ሆድ ላይ እንዲቀመጥ ወዲያውኑ ጡት እንዲጠባ በፍጥነት ከእናቱ ጋር እንዲተያይ በመደረጉ ምክንያት በምጥ የወለደች ሴት እርካታዋ ፈጠን ያለ ይሆናል፡፡ ከነአባባሉም “ምጡን እርሽው ልጁን አንሽው” ይባላል፡፡ የነበረው ሕመም ሁሉ ልክ ልጁ ሲታይ ስለሚጠፋ ነው፡፡ በኦፕራሲዮን የምትወልደው ደግሞ ምንም እንኩዋን በፍጥነት ከልጁዋ ጋር ባትገናኝና ጡት ባታጠባውም እሱን ለማግኘት ስትል በከፈለችው መስዋእትነት የተነሳ በሰላም ከወለደችው ልጅ ጋር ለመገናኘት በመብቃትዋ ደስተኛ ትሆናለች። ስለዚህ ደረጃው ይለያይ እንጂ ሁለቱም ደስተኞች ይሆናሉ፡፡
ጥ/    የምጥ ሕመም እንዳይፈራ  ምን ማድረግ ይጠቅማል?
መ/    ማስተማር ነው፡፡ አስቀድሞ በእርግዝና ወቅት ሁኔታውን እንዲያውቁት ማድረግ ይጠቅማል። በእንግሊዝኛው አራት ..ፒ..ዎች አሉ፡፡ (passage, passenger, psychology, power) ይህ ማለትም ስለምጥ እውቀት እንዲኖር ከልጁ አፈጣጠር ጀምሮ እስከ ምጥ ድረስ ያለውን ሂደት በሚመለከት የስነልቡና ዝግጅት በማድረግ አቅምን እንዴት አምቆ ልጁን መውለድ እንደሚቻል የሚያሳይ ስልጠና ነው፡፡ ያረገዙ እናቶች በዚህ መልክ ቢዘጋጁ እና ምጥ ማለት ተፈጥሮአዊ ሂደት መሆኑን እንዲቀበሉ ቢደረግ  ትክክለኛውን መንገድ እንደያዙ ይቆጠራል፡፡

    · “ለኔ የምንግዜም ምርጥ ኃይሌ ነው” ሎርድ ሴባስቲያን ኮው
        · በዓለም ሻምፒዮናና በኦሎምፒክ ሞ ፋራህ 10፤ ቀነኒሳ 8፤ ኃይሌ 6 የወርቅ ሜዳሊያዎች
        · ብዙ ሪከርዶች ያስመዘገበው - ኃይሌ፤ በ10ሺ እና በ5ሺ ላፉት 12 ዓመታት የሪከርድ ባለቤት - ቀነኒሳ
          · በ2 ኦሎምፒክና በ2 የዓለም ሻምፒዮና ተከታታይ ድርብ ድሎች በማስመዝገብ - ሞ ፋራህ
          · ከ20 ሚ. ዶላር በላይ የስፖንሰርሽፕና የተለያዩ ንግድ ገቢዎች - ሞ ፋራህ
           · የገንዘብ ሽልማት ኃይሌ 3.6 ሚ. ዶላር፤ ቀነኒሳ 1.9 ሚ. ዶላር፤ ሞ ፋራህ 647.2 ሺህ ዶላር
            · 145 ድል ሞ ፋራህ፤ 142 ድል ኃይሌ፤ 115 ድል ቀነኒሳ
               · ብዙ የተፃፈለት ኃይሌ፤ ሁለቴ የዓለም ኮከብ የተባለ ቀነኒሳ

     የዓለማችን የምንግዜም ምርጥ የረጅም ርቀት ሯጭ ማነው? የሚለው ጥያቄ የአትሌቲክሱን ዓለም በየጊዜው ሲያከራክር ቆይቷል፡፡ በ16ኛው የዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና ሰሞን በተመሳሳይ አጀንዳ የወጡ ዘገባዎች፤ ክርክሮችና ውይይቶች ነበሩ፡፡ እንግሊዛዊው  ሞ ፋራህ በ10ሺ ሜትር የመጨረሻ ውድድሩን በዓለም ሻምፒዮና ከማድረጉ ጋር ተያይዞ ነው፡፡ በ10 ሺ ሜትር ውድድሩ ላይ የኬንያ፣ የኢትዮጵያ፣ የኡጋንዳ የኤርትራ አትሌቶችን በፍፁም የበላይነት በማሸነፍ 10ኛ የወርቅ ሜዳልያውን በዓለም ሻምፒዮናው ሲወስድ  በብዙዎቹ የእንግሊዝና የአውሮፓ ሚዲያዎች በረጅም ርቀት የምንግዜም ምርጥ ሯጭ ተብሎ ተወድሷል፡፡ የሁለቱን የኢትዮጵያ ታላላቅ የረጅም ርቀት ሯጮች ኃይሌ ገብረስላሴ እና ቀነኒሳ በቀለን  ስኬቶችን ከግምት ያላስገቡ ውዳሴዎች ነበሩ እንጅ።
በ2012 እኤአ ላይ ለንደን 30ኛው ኦሎምፒያድ ባስተናገደችበት ወቅት ከኦሎምፒኩ በፊት እና በኋላ ይሄው ጉዳይ አበይት መነጋገርያ ነበር፡፡ አትሌቲክስ ዊክሊ  የዓለማችን የምንግዜም ምርጥ የረጅም ርቀት ሯጭ  ማነው? በሚል ጥያቄ መነሻነት ከአንባቢዎቹ ድምፅ በማሰባሰብ  የሰራው ሪፖርት በተለይ ሊጠቀስ ይችላል፡፡ በወቅቱ ኃይሌ ገብረስላሴ አንደኛ ደረጃ የወሰደው ከተሰበሰበው ድምፅ 45.6 በመቶ ድርሻ በማስመዝገብ ነበር፡፡ ኤሚል ዛቶፔክ 20.3፤ ቀነኒሳ በቀለ 15.2፤ ሞ ፋራህ 8.6፤ አበበ ቢቂላ 8፤ ፓቮ ኑርሚ 5.5 እንዲሁም ላርስ ቪረን 3 በመቶ የድምፅ ድርሻ በማስመዝገብ ከሁለት እስከ ሰባት ያለውን ደረጃ ወስደዋል፡፡  በ2016 እኤአ ላይ ደግሞ  የብራዚሏ ሪዮ ዲጄኔሮ 31ኛውን ኦሎምፒያድ ስታዘጋጅ አሁንም በተመሳሳይ አጀንዳ በአትሌቲክሱ ዓለም ክርክሩ አገርሽቶ ነበር፡፡ ሞ ፋራህ በ10ሺ እና በ5ሺ ሜትር ለሁለተኛ ተከታታይ ኦሎምፒክ ድርብ ድል ካስመዘገበ በኋላ የዓለማችን የምንግዜም ምርጥ የረጅም ርቀት ሯጭ በሚለው ውዳሴ ሲደነቅ ብዙ ሙግት ነበር፡፡
በ2013 እ.ኤ.አ ላይ በሞስኮ ተካሂዶ በነበረው የ14ኛው የዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና ላይ ሞ ፋራህ በ10 ሺህና በ5 ሺ ሜትር ድርብ ድል ለመጀመርያ ጊዜ ሲያስመዘግብ የእንግሊዝና የአውሮፓ ሚዲያዎች የምንግዜም ምርጥ እያሉ ሲያወድሱት ነበር፡፡ በሞስኮ ሉዝንስኪ ስታድዬም ከዓለም ሻምፒዮናው ጋር በተያያዘ በተዘጋጀ ጋዜጣዊ መግለጫ የምንግዜም ምርጥ እየተባለ መጠራቱ ተገቢ አለመሆኑን በሚያመለክት ስሜት ያቀረብኩለት ጥያቄ ነበር፡፡
“የምንግዜም ምርጥ የረጅም ርቀት ሯጭ ለመባል የዓለም ሪከርዶች ማስመዝገብ አያስፈልግም ወይ….” በሚል ሞ ምላሹን ሲሰጥ “ለሪከርዶች የቀረበ ብቃት ቢኖረኝ ደስተኛ ነኝ፡፡ በርግጥ ያሉትን ክብረወሰኖች ለመስበር ብዙ ጥረት አላደርግም፡፡ ዋናው ትኩረቴ የዓለም እና የኦሎምፒክ ሻምፒዮናን በመሆን ተደጋጋሚ ድሎች ማስመዝገብ እና ለአገሬ ብዙ ሜዳሊያዎችን መሰብሰብ ነው፡፡” ብሎ ነበር፡፡
የዓለም አቀፉ የአትሌቲክስ ፌዴሬሽኖች ማህበር (laaf) ፕሬዝዳንት የሆነው  እንግሊዛዊው ሎርድ ሴባስቲያን ኮው በ16ኛው የዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮናው ሰሞን የዓለምን የምንግዜም ምርጥ የረጅም ርቀት ሯጭ ማነው ተብሎ ተጠይቆ ነበር።  ‹‹ሞ ፋራህ የሚደነቅ አትሌት ቢሆንም፤ ለእኔ የምንግዜም ምርጥ ኃይሌ ገብረስላሴ ነው፡፡ በረጅም ዓመታት የሩጫ ዘመኑ፣ በብዙ ርቀቶች በመወዳደር እና በተደጋጋሚ የዓለም ሪከርዶችን በማስመዝገብ የሚፎካከረው ስለሌለ፡፡” በማለት ምክንያቱን አቅርቧል ፡፡ በርግጥ የምንግዜም ምርጥ አትሌትን ለመለየት የሚካሄዱ ምርጫዎችና ውጤቶቻቸው አከራካሪነታቸው ይጠበቃል፡፡ የማወዳደርያና የመለኪያ መስፈርቶች፤ የማነፃፀርያ መንገዶች እና መመዘኛዎች፤ የሩጫ ውድድር አይነቶች፤ እድሜና ሌሎች ሁኔታዎች …ታላላቆቹን አትሌቶች  በእኩልነት ለመመልከት የማያመቹ ናቸው፡፡ ሞ ፋራህ በረጅም ርቀት ተወዳዳሪነት በአትሌቲክሱ ዓለም የነገሰው ባለፉት 6 ዓመታት ነው፡፡ ኃይሌ ገብረስላሴ እና ቀነኒሳ በቀለ ደግሞ በረጅም ርቀት ውድድሮች ከ20 ዓመታት የውጤት የበላይነት ሲያሳዩ የኖሩ ናቸው፡፡ በተጠቀሰው የሩጫ ዘመን ሁለቱ የኢትዮጵያ አትሌቶች ከኬንያውያን ምርጥ አትሌቶች ከፍተኛ ፉክክር ይገጥማቸው ነበር።   የ10ሺ እና የ5ሺ ሜትር የዓለም ሪከርዶችን በማስመዝገብ ያበረከቱት አስተዋፅኦም መጠቀስ ያለበት ነው፡፡ ይህ የስፖርት አድማስ ትንታኔ ሶስቱን የዓለማችን የረጅም ርቀት ታላላቅ አትሌቶች በተለያዩ ሁኔታዎች የሚያነፃፅር ሲሆን የምንግዜም ምርጥ የረጅም ርቀት ሯጭ ማነው የሚለውን ጥያቄ ምላሽ የሚሰጥ ይሆናል፡፡
በዓለም ሻምፒዮና፤ በኦሎምፒክ ሜዳልያዎችና ሌሎች
በ10ሺ ሜትር እና 5ሺ ሜትር ውድድሮች በተለይ በኦሎምፒክ እና በዓለም ሻምፒዮና  10 የወርቅ ሜዳልያዎችን በመሰብሰብ ብልጫ የሚወስደው ሞ ፋራህ ነው፡፡ ቀነኒሳ በቀለ በ8 የወርቅ ሜዳልያዎች ሲከተለው ኃይሌ ደግሞ 6 የወርቅ ሜዳሊያዎች ተጎናፅፏል፡፡ በኦል አትሌቲክስ ድረገፅ ላይ የሶስቱን አትሌቶች ዝርዝር የውጤት ታሪክ በመዳሰስ መገንዘብ የሚቻለው ግን የተለየ ነው፡፡ ከዓለም ሻምፒዮና እና ከኦሎምፒክ ሜዳልያዎች ባሻገር በሌሎች ስኬቶች ቀነኒሳ እና ኃይሌ እንደቅደም ተከተላቸው ከሞ ፋራህ በእጅጉ ብልጫ አላቸው፡፡
ቀነኒሳ በቀለ 3 ጊዜ የኦሎምፒክ ሻምፒዮንና 5 ጊዜ የዓለም ሻምፒዮን ከመሆኑ በላይ  12 ጊዜ የዓለም አገር አቋራጭ አሸናፊ በመሆን ከሁለቱ አትሌቶች በተለየ ከፍተኛውን ውጤት አስመዝግቧል። በተጨማሪም 3 ጊዜ የዓለም አትሌቲክስ ፍፃሜ አሸናፊ ፤1 ጊዜ የዓለም የቤት ውስጥ አትሌቲክስ ሻምፒዮን ፤2 ጊዜ የአፍሪካ ሻምፒዮን፤ 1 ጊዜ የኦል አፍሪካን ጌምስ አሸናፊ ፤1 ጊዜ የዓለም ግማሽ ማራቶን ሻምፒዮን፤ 2 የዳይመንድ ሊግ ውድድሮችና 17 የጎልደን ሊግ ውድድሮች ያሸነፈ ነው - ቀነኒሳ በቀለ። ኃይሌ ገብረስላሴ 2 ጊዜ የኦሎምፒክ ሻምፒዮንና 4 ጊዜ የዓለም ሻምፒዮን ሆኗል፡፡ ከቀነኒሳ እና ከሞ ፋራህ በተለይ የሚልቅበት ውጤቱ ግን 4 ጊዜ የዓለም የቤት ውስጥ አትሌቲክስ ሻምፒዮን መሆኑና 9 ዓለም አቀፍ የማራቶን ውድድሮች ማሸነፉ ነው። ሞ ፋራህ 4 ጊዜ የኦሎምፒክ ሻምፒዮንና 6 ጊዜ የዓለም ሻምፒዮን በመሆኑ ከሁለቱ የላቀ የውጤት ታሪክ ሆኖ ሲመዘገብለት፤ 18 ጊዜ የዳይመንድ ሊግ ውድድሮች ማሸነፉም ይጠቀሳል፡፡
በሪከርዶች፤ በምንግዜም ፈጣን ሰዓቶች እና ሌሎች ደረጃዎቹ
በዓለም አቀፍ አትሌቲክስ ውድድሮች በሩጫ ዘመናቸው ባስመዘገቧቸው ሪከርዶች ሶስቱ አትሌቶች ሲነፃፀሩ የላቀ ሆኖ የሚገኘው ኃይሌ ገብረስላሴ ነው፡፡ ምርጥ የረጅም ርቀት ሯጭ ለመባል በውድድር ርቀቶቹ የዓለም ሪከርዶችን ማስመዝገብ ወሳኝ ነው፡፡ ኃይሌ ገብረስላሴ እና ቀነኒሳ በቀለ ስማቸውን በተደጋጋሚ በሪከርድ መዝገብ ሊያሰፍሩ በመቻላቸው  ከሞ ፋራህ ይበልጣሉ፡፡ ኃይሌ ገብረስላሴ በ10ሺ ሜትር እና 5 ሺ ሜትር በሩጫ ዘመኑ 7 ሪከርዶችን ያስመዘገበ ሲሆን ቀነኒሳ በቀለ 3 ጊዜ ሪከርዶችን አስመዝግቧል፡
በረጅም ርቀት ባስመዘገባቸው የበዙ ሪከርዶች በተለይ መጠቀስ ያለበት ኃይሌ ሲሆን ከ1999 እስከ 2009 እኤአ ባሉት 19 የውድድር ዘመናት 27 ሪከርዶች እና ምርጥ ፈጣን ሰዓቶችን ስላስመዘገበ ነው፡፡ ከ27ቱ መካከል በአይኤኤኤፍ የፀደቁለት 20 የዓለም ሪከርዶች የተነበሩ ናቸው፡፡ ኃይሌ  ሪከርዶቹን  በ17 የተለያዩ የአትሌቲክስ የውድድር አይነቶች ማስመዝገቡም በልዩ ስኬት ሊጠቀስለት ይበቃል፡፡ በ2000 እና 3000 የቤት ውስጥ አትሌቲክስ፤ በ5ሺ ሜትር የቤት ውስጥ አትሌቲክስና በትራክ ፤ በ2 ማይል የቤት ውስጥ እና ትራክ፤ በ10ሺ ሜትር በትራክ፤ በማራቶን፤ በጎዳናላይ ሩጫዎች በ10 ኪሎሜትር፤ በ15 ኪሎሜ፤ በ20 ኪሎሜ፤ በ25 ኪሎሜትር፤ በ10 ማይል፤ በግማሽ ማራቶንና በማራቶን ውድድሮች ክብረወሰኖችን ሊያስመዘግብ መቻሉ ለኃይሌ አድናቆት ያሰጠዋል፡፡
በሌላ በኩል በ5ሺ ሜትር እና በ10ሺ ሜትር ቀነኒሳ በቀለ ሁለት የዓለም ሪከርዶችን ላለፉት 12 ዓመታት ይዞ በመቆየቱ ከኃይሌ ገብረስላሴ ቀጥሎ የሚያስጠቅሰው የላቀ ስኬት ነው፡፡ በ5ሺ ሜትር  የዓለም ሪከርድ በ2004 እኤአ የተመዘገበው በቀነኒሳ በቀለ በ12 ደቂቃዎች ከ37.35 ሴከንዶች ሲሆን ከእሱ በፊት ኃይሌ ገብረስላሴ ለ4 ጊዜያት በርቀቱ ሪከርዶች ሲያስመዘግብ 25.25 ሰከንዶችን አራግፏል፡፡ በ10ሺ ሜትር ውድድር የዓለም ሪከርድ በ2005 እኤአ ላይ የተመዘገበው በቀነኒሳ በቀለ በ26 ደቂቃዎች ከ17.53 ሰከንዶች በሆነ ጊዜ ሲሆን ከእሱ በፊት ኃይሌ ለ2 ጊዜያት ሪከርዱን ሲያሻሽል 13.80 ሰከንዶችን ቀንሷል፡፡
ከ10ሺ እና ከ5ሺ ሜትር ባሻገር ኃይሌ የዓለም ማራቶን ሪከርድን  ለሁለት ጊዜያት ማስመዝገቡ በከፍተኛ ስኬት የሚነሳ ይሆናል፡፡  ኃይሌ ሁለቱን የማራቶን ሪከርዶች በበርሊን ማራቶን ያስመዘገባቸው ሲሆኑ በ2007 እኤአ ላይ 2 ሰዓት ከ04 ደቂቃዎች ከ26 ሰኮንዶች   በሆነ ጊዜ ፤ በ2008 እኤአ ላይ ደግሞ 2 ሰዓት ከ03 ደቂቃዎች ከ59 ሰኮንዶች በሆነ ጊዜ ርቀቱን በመሸፈን ነበር።  በአጠቃላይ በሁለቱ ማራቶን ሪከርዶቹ የርቀቱን ክብረወሰን በ46 ሰከንዶች አፍጥኖታል፡፡ ኃይሌ በሩጫ ዘመኑ ካስመዘገባቸው በአይኤኤኤፍ የፀደቁ  20 የዓለም ሪከርዶች መሮጥ ካቆመ በኋላ  ያልተሰበሩ ሁለት ዓለም አቀፍ ሪከርዶች አሉ፡፡ በ20 ኪሎሜትር የጎዳና ላይ ሩጫ በ2007 እኤአ በቼክ ኦስትራቫ 56 ደቂቃዎች ከ25.98 ሰከንዶች  እንዲሁም በ1 ሰዓት ሩጫ አሁንም በ2007 እኤአ 21285 ሜትሮች ርቀትን በመሸፈን የተመዘገቡት ናቸው፡፡ ለሞ ፋራህ ብቸኛ የሪከርድ ታሪኩ በአውሮፓ ደረጃ የተወሰነ ነው፡፡ በ1500 ሜ፣ በ3000 ሜ፣ በ2 ማይል፣ በ5 ሺ እና በ10 ሜትር 5 የአውሮፓ ሪከርዶችን በስሙ ስላስመዘገበ ነው፡፡
በ10ሺ ሜትር የምንግዜም ፈጣን ሰዓቶች ደረጃን የሚመራው ባለሪከርዱ ቀነኒሳ በቀለ ሲሆን  እስከ 10 ባለው ደረጃ ሶስት ፈጣን ሰዓቶች ያሉት ኃይሌ በዚሁ ደረጃ ላይ በ1998 የ10ሺ ሜትር ርቀትን በ26 ደቂቃ ከ22.75 ሰኮንዶች በሆነ ጊዜ የሸፈነበት ጊዜ በሶስተኛ ደረጃ ላይ ነው፡፡  በ5ሺ ሜትር ውድድር  የምንግዜም ፈጣን ሰዓቶች ደረጃን አሁንም ባለሪርዱ ቀነኒሳ በቀለ ሲመራው ኃይሌ ገብረስላሴ ሁለተኛ ደረጃ ላይ ነው፡፡ ሞ ፋራህ በ5 ሺህ ሜትር ያስመዘገበው ሰዓት ከዓለም 31ኛ በ10 ሺ ሜትር ያስመዘገበው ሰዓቱ ደግሞ ከዓለም 16ኛ ደረጃ ላይ ነው፡፡
ቀነኒሳ 21፣ ኃይሌ 18 እና ሞፋራህ 3 ውድድሮችን በ5 ሺ ሜትር ከ13 ደቂቃ በታች የገቡ ሲሆን  በ10 ሺ ሜትር ደግሞ ከ27.30 … በታች በመግባት  ኃይሌ 18 ቀነኒሳ 5 እና ሞፋራህ 4 ውድድሮችን አስመዝግበዋል፡፡
በማራቶን የምንግዜም ፈጣን ሰዓት ደረጃ ላይ ቀነኒሳ በቀለ የበርሊን ማራቶን በማሸነፍ ያስመዘገበው 2፡03፡03 የሆነ ጊዜ በሁለተኛ ደረጃ የተቀመጠ ሲሆን የኢትዮጵያ ሪከርድም ነው፡፡ የኃይሌ ገብረስላሴ የማራቶን ፈጣን ሰዓት 2፡03፡59 እስከ 10ኛ ደረጃ የሚመዘገብ ሲሆን የሞፋራህ ደግሞ 2፡08፡29 ከ20ኛ ደረጃ የሚያልፍ ነው፡፡
በ10ሺ እና በ5ሺ ድርብ ድሎች
በዓለም ሻምፒዮና እና በኦሎምፒክ በ10 ሺ እና በ5 ሺ ድርብድሎችን በማስመዝገብ የላቀ የሚሆነው ሞ ፋራህ ነው፡፡በዓለም ሻምፒዮና በ2013 እና በ2015 እኤአ እንዲሁም በኦሎምፒክ በ2012 እና በ2016 እኤአ ሞ ፋራህ በ10ሺ እና በ5ሺ ሜትር ድርብ የወርቅ ሜዳልያዎችን ማስመዝገብ ችሏል፡፡ በቅርብ ርቀት ሊፎካከረው የሚችለው በዓለም ሻምፒዮና በ2009 እኤአ ላይ እንዲሁም በኦሎምፒክ በ2008 እኤአ ላይ በ10ሺ እና በ5ሺ ሜትር ድርብ ድሎችን ያስመዘገበው ቀነኒሳ በቀለ ሲሆን ኃይሌ ግን በዓለም ሻምፒዮናም በኦሎምፒክም ድርብ ድሎችን አስመዝግቦ አያውቅም፡፡
በብዙ የሩጫ ውድድር አይነቶች በመሳተፍ
በተለያዩ ርቀቶች ለረጅም የውድድር ዘመናት በመሮጥ ቀዳሚ የሚሆነው ኃይሌ ገብረስላሴ ነው፡፡ ለ27 አመታት በቆየበት የሩጫ ስፖርት ከመካከለኛ ርቀት 800 ሜትር አንስቶ፤ በረጅም ርቀት የ10ሺ እና 5ሺ ሜትር የትራክ እና የቤት ውስጥ ውድድሮች፤ ከ1 ማይል እስከ 10 ማይል በሚወስዱ ሩጫዎች፡ ከ10 እስከ 25 ኪሎሜትር በሚለኩ የጎዳና ላይ ሩጫዎች እና በማራቶን እና በግማሽ ማራቶን ውድድሮች በአጠቃላይ እስከ 26 በሚደርሱ የሩጫ ውድድር ዓይነቶች በመወዳደር እና አስደናቂ ውጤት በማግኘት በታሪክ መዝገብ ስሙን ያሰፈረ ነው። ሞ ፋራህ በ1500ሜ፤ በ3000ሜ፤ በ2 ማይል፤ በ5ሺ እና በ10ሺ ሜትር በግማሽ ማራቶን እና በማራቶን ተወዳዳሪነቱ ይታወቃል፡፡ ቀነኒሳ በቀለ ከሁለቱ የሚለየው በመካከለኛ ርቀቶች ምንም አይነት ተመክሮ ሳይኖረው በ10ሺ እና በ5ሺ ሜትር እንዲሁም በማራቶን በመሳተፉ ሲሆን በዓለም አገር አቋራጭ ሰፊ ልምድ በማካበት ኃይሌና ሞ ፋራህ አይስተካከሉትም፡፡
በስፖንሰርሺፕ፤ በሩጫ ኢንቨስትመንት እና ዘመናዊ ስልጠና
ከሪዮ ኦሎምፒክ ማግስት በታዋቂ የቢዝነስ ሚዲያዎች እንደተዘገበው ከሆነ ሞ ፋራህ በስፖንሰርሺፕና በተለያዩ የንግድ ገቢዎቹ ከኃይሌና ከቀነኒሳ ይበልጣል፡፡ ሞ ፋራህ  በሩጫ ዘመኑ እስከ 20 ሚሊዮን ዶላር በላይ ሃብት ማካበቱን የሚያመለክቱ መረጃዎች በደሞዝ፣ በገንዘብ ሽልማቶች ለተለያዩ የቦነስ ክፍያዎች እስከ 11 ሚሊዮን ዶላር እንዲሁም በማስታወቂያ እና በተለያዩ የንግድ ገቢዎች ከ9 ሚሊዮን ዶላር በላይ ማግኘቱን ገልፀዋል፡፡ ቨርጂን ሚዲያ፣ ሉሚዝ፣ ቪየተን እና ሃያንዳይ ማስታወቂያ ሞ ፋራህን የሚያሰሩ ኩባንያዎች ናቸው፡፡ ኃይሌ ሯጭ በነበረበት ወቅት ዋና ስፖንሰሮቹ፤ አዲዳስ እና ፓወር ባር ነበሩ፡፡ ሞ ፋራህ በልምምድ መርሃ ግብሮቹ ከኃይሌና ከቀነኒሳ የተለየ ነው፡፡  በቀን 120 ማይሎች የሚጠጋ ርቀትን ለልምምድ የሚሮጥ ሲሆን ለትልልቅ ውድድሮች በሚዘጋጅበት ወቅት የእረፍት ቀን የለውም፡፡ በስልጠና ወቅት አብረውት የሚሰሩት ከ12 በላይ ባለሙያዎች ሲሆኑ 3 ዶክተሮች ናቸው፡፡ በስነምግብ፤ በስነልቦና፤ በፊዚዮቴራፒ ከሚያገለግሉት ከእነዚህ ባለሙያዎች ጋር ዘመናዊ የስልጠና መርኃ ግብር በመከተል እየሰራ ስኬታማ ሊሆን ችሏል፡፡ በየዓመቱ  ለ6 ወራት በካምፕ ዝግጅት ያደርጋል፡፡
በገንዘብ ሽልማት
በዓለም አቀፉ የጎዳና ላይ ሩጫዎች ስታስቲክስ እና ውጤት አሰባሳቢ ተቋም በተሰራ ስሌት የምንግዜም ከፍተኛ የሽልማት ገንዘብ ያገኙ አትሌቶች ደረጃን የሚመራው  ኃይሌ ገብረስላሴ ሲሆን  በሰበሰበው 3 ሚሊዮን 546ሺ 674.80 ዶላር ነው፡፡ ቀነኒሳ በቀለ 1,882,063 ሚሊዮን ዶላር በማግኘት 5ኛ ደረጃ ላይ ሲሆን ሞፋራህ በ647,153 ዶላር 19ኛ ደረጃ ላይ ይገኛል፡፡ የጎዳና ላይ ሩጫዎች የስታትስቲክስ ባለሙያዎች ዓለም አቀፍ ማህበር (ARRS/ Associations of Road racing statisticians)  በድረገፁ ይፋ እንዳደረገው  ኃይሌ ገብረስላሴ በሩጫ ዘመኑ በ142 ውድድሮች ያሸነፈ ሲሆን ሞ ፋራህ 145  እንዲሁም ቀነኒሳ 115 ውድድሮችን ማሸነፋቸው ተመዝግቧል፡፡
በመፅሃፍት
ስለሩጫ ህይወታቸው በተዘጋጀው መፅሐፍት ኃይሌ ገብረሥላሴ ግንባር ቀደም ነው፡፡ ቢያንስ አምስት እውቅ መፅሃፍት የሩጫ ዘመን ስኬቱንና ህይወት ታሪኩን በመንተራስ ለንባብ በቅተዋል። “ዘ ግሬተስት፡ ዘ ሃይሌ ገብረስላሴ ስቶረሪ” የሚባለው መፅሃፍ በራሱ ሃይሌ ገብረስላሴ እና በጂም ዴኒሰን የተፃፈ ነው፡፡ ሁለተኛው መፅሃፍ ደግሞ “ኃይሌ ገብረስላሴ ዘ ግሬተስት ራነር ኦፍ ኦል ታይም” በሚል ርእስ በክላውስ ዊዴት የተፃፈው ነው፡፡ ሶስተኛው በጀርመንኛ ቋንቋ የተፃፈውና ስለልምምድ ፕሮግራሙ እና የውድድር ብቃቱ “ላውሪን ዊዝ ሃይሌ ገብረስላሴ፤ ዳትሬኒንግ ፕሮግራም” በሚል ርእስ አበበ በተባለ ግለሰብ፤ በቀድሞ አሰልጣኙ ወልደመስቀል ኮስትሬ እና በራሱ በኃይሌ ገብረስላሴ ትብብር የተዘጋጀው ነው፡፡ አራተኛው መፅሃፍ  በታዋቂው ጃፓናዊ የአትሌቲክስ ፎቶግራፈር ጂሮ ሞቺዙኪ ‹ኃይሌ ገብረስላሴ ኤምፐረር ኦፍ ሎንግ ዲስታንስ› በሚል ርእስ በተለያዩ ፎቶዎች ታጅቦ የቀረበ ነው፡፡ አምስተኛው መፅሃፍ ደግሞ “ኃይሌ ገብረስላሴ፤ አፍሪካ ሌጀንድ ሲርዬስ” በሚል በኤልዛቤት ቴብላ የተዘጋጀው ነው፡፡ በሞ ፋራህ ዙሪያ ከተጻፉት 3 እና 4 መፅሐፍት “ትዊንአምቢሽን፡ ማይ አውቶ ባዮግራፊ” እና “ሬዲ ስቴዲ ሞ” ዋናዎቹ ናቸው። በሌላ በኩል በቀነኒሳ ዙሪያ ሊጠቀስ የሚችለው መፅሐፍ “Kenenisa Bekele” በሚል ርዕስ የሩጫ ዘመኑ ታሪክ አሀዛዊ መረጃዎችና ስታስቲኮች የተጠናቀሩበት በኤምሪ ክሪስ ፒል የተዘጋጀ ነው፡፡  
በክብር ሽልማት
በዓለም አትሌቲክስ ልዩ የክብር ሽልማቶችን በመጎናፀፍ አሁንም ኃይሌ ቀዳሚ ሆኖ ቢጠቀስም ሁለት ጊዜ የዓለም ኮከብ አትሌት የተባለው ቀነኒሳ ነው፡፡ በኦሎምፒኳ ከተማ ሉዛን ውስጥ  86 ዓመታት እድሜ ያለው በ‹ዘ አሶሴሽን ኢንተርናሲዮናሌ ዴላ ፕሬስ ስፖርትስ›  ልዩ ክብር ሽልማት፤ በስፔን ትልቅ ክብር የሚሰጠውን‹ፕሪንስ ኦስተሪዬስ አዋርድስ ፎር ስፖርትስ› በስፖርት የሰው ልጅን የላቀ ብቃት እና ችሎታ ያሳደገ አትሌት በመባል ከስፔን ንጉሳውያን ቤተሰብ እጅ የተቀበለው ሽልማት እንዲሁም በዓለም አቀፉ የጎዳና ላይ ሩጫዎች ማህበር በ2006፤2007 እና 2008 እኤአ የዓለም ምርጥ አትሌት ተብሎ ተሸልሟል፡፡
አትሌት ቀነኒሳ በቀለ በ2004 እና በ2005 እ.ኤ.አ በኣለም አቀፍ የአትሌቲክስ ፌዴሬሽኖች ማኅበር የዓመቱ ኮከብ አትሌት በመባል ከፍተኛውን ሽልማት አግኝቷል፡፡

     የሰማያዊ ፓርቲ ብሔራዊ ምክር ቤት አቶ ነገሠ ተፈረደኝን፣ የብሔራዊ እርቅና መግባባት ጉዳዮች ኃላፊ አድርጐ ሾመ፡፡ ባለፈው ነሐሴ 14  የተሰበሰበው የሰማያዊ ፓርቲ ብሔራዊ ምክር ቤት፤ ያለፉትን ሁለት ወራትና በጠቅላላ የዓመቱን የሥራ ክንውን ሪፖርት ያዳመጠ ሲሆን የስራ አስፈፃሚውን አሠራር በግልና በቡድን ገምግሟል፡፡
ምክር ቤቱ ሰኔ 11 ቀን 2009 ዓ.ም. ባደረገው ስብሰባ፣ የብሔራዊ እርቅና መግባባት ቋሚ ኮሚቴን ወቅታዊነትና አስፈላጊነት በመግለፅ፣ በመተዳደሪያ ደንብ 10/7 መሠረት ሲሰራ፣ አስፈፃሚ ውስጥ እንዲካተት ማፅደቁ ይታወሳል፡፡
በዚህ መሠረት የፓርቲው ሊቀመንበር አቶ የሺዋስ አሰፋ፣ አቶ ነገሠ ተፈረደኝን በኃላፊነት መድበው፣ ለብሔራዊ ምክር ቤት በማቅረብ  ያፀደቁ ሲሆን ኃላፊነትና ተግባራቸውንም በዝርዝር አቅርበው አፀድቀዋል፡፡ ምክር ቤቱ የአቶ ነገሠን ሹመት በከፍተኛ ድምፅ ያፀደቀ ሲሆን እርሳቸውም የተሰጣቸውን ሃላፊነት በፅናት ለመወጣት ቃል ገብተዋል፡፡
የብሔራዊ እርቅና መግባባት ጉዳዮች ኃላፊ፣ ከሚወጣቸው የሥራ  ሃላፊነቶች  መካከል፡- የድርድር ጥያቄዎች ሲመጡ በኃላፊነት ያስተባብራል፣ አስፈላጊ ሆኖ ሲገኝ የድርድር ሀሳቦችን በማመንጨትና ለሥራ አስፈፃሚ ኮሚቴው በማፀደቅ ለመንግስት፣ ለገዥው ወይም ለሌሎች ፓርቲዎችና ድርጅቶች ያቀርባል፣ የብሔራዊ እርቅ ተሞክሮ ያላቸውን ሀገሮች፣ ፓርቲዎችና ድርጅቶች በማጥናት ለውይይት ያቀርባል፣ ብሔራዊ እርቅና መግባባትን  የተመለከቱ ትምህርትና ስልጠናዎች ያዘጋጃል፣ ለብሔራዊ እርቅ የሚረዱ የሀገር ውስጥና የውጭ ሀገር የልምድ ልውውጦችን ያሳልጣል የሚሉት ይጠቀሳሉ፡፡
ምክር ቤቱ ያካሄደው  የዘንድሮን  የመጨረሻ 5ኛ ዓመት፣ 6ኛ መደበኛ ስብሰባ ሲሆን የቀጣዩን ዓመት ዕቅድ ለማፅደቅ፣ ለነሐሴ 28 ቀን 2009 ዓ.ም ቀጠሮ ይዟል፡፡

በአደጋው 140 እንስሳት ሞተዋል፤በሰብልና በንብረት ላይ ጉዳት አድርሷል
   በዘንድሮ ክረምት በሀገሪቱ የተለያዩ አካባቢዎች በመብረቃ አደጋ የ40 ሰዎች ህይወት ያለፈ ሲሆን 149 እንስሳትም በዚሁ አደጋ መሞታቸውን ለማወቅ ተችሏል፡፡ በሰውና በእንስሳት ላይ ከደረሰው አደጋ በተጨማሪ በሰብልና በመኖሪያ ቤቶች ላይም  ከፍተኛ ጉዳት አድርሷል ብለዋል - የአደጋ ስጋትና ስራ አመራር ኮሚሽን፣ የቅድመ ማስጠንቀቂያ አስቸኳይ ጊዜ ምላሽ ዳይሬክተር ወ/ሮ አልማዝ ደምሴ፡፡
አደጋዎቹ የደረሱት በደቡብ፣ በኦሮሚያ፣ በአማራ፣ በትግራይ፣ በአፋርና በቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልሎች በሚገኙ የተለያዩ የገጠር ወረዳዎች መሆኑ ታውቋል፡፡
በክረምቱ መጀመሪያ ሰኔ ወር ላይ፣ በሃዲያ ማሻ በመብረቅ፣ 1 ሰው ህይወቱ ሲያልፍ፤ በምዕራብ ሸዋ፣ በሚዳገንና በአሶሳ በድምሩ 44 ከብቶች ሞተዋል። በሐምሌ ወር ደግሞ በአማራ ክልል ስማዳ፣ ሰሜን ሸዋ፣ ዋግ፣ ዳህኑ፣ ወልዲያ እንዲሁም በኦሮሚያ ክልል፡- ዶዶላና  ሄሪ እንዲሁም በትግራይና አፋር ክልሎች በተከሰተው የመብረቅ አደጋ፣ በጠቅላላው የ13 ሰዎችን ህይወት ሲቀጥፍ፣ 25 ከብቶችንም መግደሉ  ታውቋል፡፡
ከነሐሴ ወር ጀምሮ እስከ አሁን ባሉት 15 ቀናት ውስጥ ደግሞ በሃረር፣ ወለጋ፣ መንዝ፣ ዋግህምራ፣ ወረባቡ፣ አልቡኮ፣ ጎንደር፣ አድዋ፣ አሶሳ፣ በከማሼና በአፋር በደረሰ የመብረቅ አደጋ 18 ሰዎች ሲሞቱ፣ 80 ከብቶችም እንደተገደሉ፣ ከአደጋ ስጋት አመራር ኮሚሽን  ያገኘነው መረጃ ይጠቁማል። ባለፈው ረቡዕ በሰሜን ሸዋ የደረሰ የመብረቅ አደጋ፣ በአረም የግብርና ስራ ላይ የነበሩ የ9 ዓመት ህፃንን ጨምሮ የ8 ሰዎች ህይወትን እንደቀጠፈም ታውቋል፡፡ በእንስሳትና በሰው ላይ ከደረሰው አደጋ በተጨማሪ በሃረር - ጃርሶ፣ አልቡኮ ወረዳዎች በድምሩ 12 ቤቶች ሲፈርሱ፣ 79ሺህ ሄክታር መሬት ላይ የነበረ ሰብልም ጉዳት እንደደረሰበት ወ/ሮ አልማዝ አስታውቀዋል፡፡ የመብረቅ አደጋ ሊከሰት የሚችለው በዝናብ ወቅት ትላልቅ ዛፎች ስር በመጠለል መሆኑን የጠቀሱት ወ/ሮ አልማዝ፤ ክረምቱ ቀጣይነት ያለው እንደመሆኑ፣ ሰዎች ዛፍ ስር መጠለል እንደሌለባቸው አሳስበዋል፡፡