Administrator

Administrator

Saturday, 19 August 2017 12:35

የሙያ ስነምግባር (ETHIS)

   የህክምና ባለሙያዎችን የሙያ ስነምግባር በሚመለከት ለዚህ እትም ማብራሪያቸውን እንዲሰጡን የጋበዝናቸው ዶ/ር ሙኒር ካሳ የጽንስና ማህጸን ህክምና እስፔሻሊስት ናቸው፡፡ ዶ/ር ሙኒር እንደሚሉት ከሆነ አንድ ሐኪም ወደህክምና ሙያ ከመግባቱ በፊት በተወሰኑ ነገሮች ከእራሱ ጋር መስማማት ይጠበቅበታል፡፡ሐኪም ለማከም የአንድ ሰው ፈቃድ ይፈል ጋል፡፡  በአጠቃላይ ህብረተሰቡም ለእነዚህ ሐኪሞች እውቅና ሲኖራቸው የታመመን ሰው በአስፈላጊው ነገር ሁሉ ማለትም ከቀዶ ሕክምና ጀምሮ መድሀኒት ሰጥቶ እስከማከም ድረስ መፍቀዱን ያሳያል፡፡ ይህም ለምንድነው ተብሎ ሲጠየቅ ህብረተሰቡ እነዚያን ሐኪሞች ጥሩ ስራ ይሰራሉ ብሎ ስለሚያምናቸው ነው፡፡ ነገር ግን ያ እምነት እየተሸረሸረ ከመጣ ሰው ከዘመናዊ ሕክምና እየራቀ ወደባእድ አምልኮና ባህላዊ ሕክምና ይሄዳል፡፡ ለምሳሌ እንደእንግሊዝ ባሉ ሀገራት ህብረተቡ የጤና ተቋሞቻቸውን በጣም ስለሚወዱና ስለሚያምኑ ስለሚያከብሩም ጭምር ሐኪም በሚነግራቸው መመሪያ በሚገባ ምንም ሳያጉዋድሉ ይጠቀማሉ፡፡  ስለዚህ ያንን እምነት እንዲኖር ለማድረግ ሐኪሞች በማህራቸው ተሰብስበው አንድ ሐኪም በራሱና በሕመምተኞች መካከል ያለው ግንኙነት ምን መምሰል አለበት? በሐኪሞች መካከል ያለው ግንኙነት ምን መምሰል አለበት? ሐኪሙ በግሉስ ምን አይነት አቋም ይዞ መገኘት አለበት የሚለውን እና የመሳሰሉትን ነገሮች በጥንቃቄ ተመልክተው ህግ ያወጣሉ፡፡ ይህ ነው የሙያ ስነምግባር መመሪያ የሚባለው ብለዋል ዶ/ር ሙኒር ካሳ፡፡
የህክምናው የሙያ ስነምግባር ከወጣ በሁዋላ የሚመጣ አዲስ የህክምና ባለሙያ አሰቀድሞ በእነዚህ መሰረታዊ መርሆዎች ላይ መስማማት አለበት ፡፡ ሲስማማ ብቻ ነው ሐኪም የሚሆ ነው፡፡ ስለዚህም በዚህ የሚስማማ የህክምና ባለሙያ ወደሙያው ከመዝለቁ በፊት ከእርሱ በፊት በቀደሙ ባለሙያዎች የወጣውን እና የጸደቀውን ህግ በመስማማት በማመን ቃል ይገባል። በአሁኑ ጊዜ የአለም የህክምና ማህበር የጄኔቫ ስምምነት የሚባል ሐኪሞች ወደሙያው ከመግባታቸው በፊት የሚገቡዋቸው ቃለ መሀላዎች አሉ፡፡ ከእነርሱም ውስጥ የሚከተሉት ይገኙበታል፡፡
በጽኑ ሁኔታ ሕይወቴን በሙሉ የሰውን ዘር ለማገልገል ማመኔን ‘መስማማቴን ቃል እገባለሁ ይላል፡፡ ይህ ማለት ቀለም ‘ጾታ’ ዘር ‘ሀይማኖት ‘ድንበር ‘ሀብት የመሳሰሉትን ሰውን ከሰው የሚለዩት ነገሮች ሁሉ ሳይከልሉኝ በእኩል ለማገልገል ተስማምቻለሁ፡፡ ለዚህ ተግባር ሕይወቴን አሳልፌ እሰጣለሁ ብሎ ቃል ሲገባ ነው ወደሕክምና ስራው የሚገባው፡፡
ይህን የተማርኩትን ሙያ ሕሊናዬና ክብሬን በማይነካ ሁኔታ የሰውንም ክብር በማይነካ ሁኔታ ታካሚውን አገለግላለሁ ብሎ ቃል ሲገባ ነው ወደሙያው የሚቀላቀለው፡፡
ከዚህ ሁሉ በላይ ከባዱና ዋነኛው ደግሞ የህመምተኛዬን ጤና በማንኛውም ሁኔታ አስቀድማ ለሁ የሚለው ነው፡፡  ለምሳሌም ሐኪሙ ይህን ቃል ሲገባ በእሳቤው ውስጥ መግባት ያለበት በእኔ በእራሴ ሕይወትና ጤና ላይ እንኩዋን አንድ ነገር ቢፈጠር ቅድሚያ የምሰጠው የሕመም ተኛዬን ጤናና ሕይወት ማዳን ነው የሚለውን ቃል ሲገባ ነው አንድ ሐኪም ወደሙያው ሊቀላ ቀል የሚችለው፡፡ ስለዚህም አንድ ሰው ሐኪም ሲሆን ለማገልገል የሚመጣው እራሱን ሳይሆን ሌላውን ታካሚውን ወይንም ሕመምተኛውን ነው፡፡ ይህንን ቃሉን ሲያፈርስ ግን የሙያ ማህበሩ ተነጋ ግሮ ‘ማስጠንቀቂያ ሰጥቶ ‘የማይሻሻልና ህብረተሰቡን በትክክል የማያገለግል መሆኑ ሲረጋገጥ ለሙያው ብቁ አይደለም ብለው ሊያስወግዱት የስራ ፈቃዱንም ሊነጥቁት ይገባል፡፡ በእርግጥ ኢትዮጵያ ውስጥ ይህን የሚፈጽም ማህበር በተደራጀ መልክ የለም፡፡ ወደፊት ግን የሙያ ማህ በራቱ ይጀምራሉ ብለን እንጠብቃለን። የሙያ ማህበራቱ ይህንን እርምጃ ቢወስዱ ሐኪሞቹ በህብረተሰቡ ዘንድ ተአማኒነትን እንደሚያተርፉ እሙን ነው ብለዋል ዶ/ር ሙኒር ካሳ፡፡
የሙያ ስነምግባር ደንብ በኢትዮጵያ ያለው አንድ ነው፡፡ እሱም የኢትዮጵያ ሐኪሞች ማህበር ያወጣው ነው። ነገር ግን የጽንስና ማህጸን ሐኪሞች የሙያ ስነምግባር መመሪያ የላቸውም፡፡ ስለዚህም አሁን ከአሜሪካው የጽንስና ማህጸን ሐኪሞች ኮሌጅ እና ከአለምአቀፍ የስነተዋልዶ ጤና ስልጠና ማእከል በሚገኘው የገንዘብ ድጋፍ ለመስራት ዝግጁ ነን ፡፡ የጽንስና ማህጸን ሐኪሞች የስነ ምግባር መመሪያ በሐኪሞች ማህበር በፊት ከተዘጋጀው በጣም የሚለይ ነው፡፡ የዚህም ምክንያቱ ጽሁፉ ሲጀምር ታሳቢ የሚያደርገው ሐኪሙ በስነምግባር ዙሪያ ምን አይነት ችግር አለበት? ከሚለው ስለሚነሳ ነው፡፡ ስነምግባር ማለት ለአንድ ሐኪም የትኛው ትክክል ነው ?የትኛው ነው መሰራት ያለበት? የሚለውን እና መሰል ነገሮችን የሚነግረው ነው፡፡ ለዚህ ማሳያ የሚሆን አንድ ምሳሌ አለ አሉ ዶ/ር ሙኒር፡፡
አንዲት ሴት ለመውለድ ወደሐኪም ቤት  ትመጣለች፡፡ ሴትየዋ በሐኪምዋ ስትታይ ደም ከሌላ ሰው ሊሰጣት ይገባል፡፡ እስዋ ግን በእምነትዋ ምክንያት ደም ከሌላ ሰው መውሰድ እንደማትፈልግ ለሐኪምዋ ትገልጻለች፡፡ ሐኪምዋ ግን ይህች ሴት ደም ካላ ገኘች መሞትዋ መሆኑን ስለሚያውቅ ይጨነቃል፡፡ ስለዚህ ከምትሞት ደም መውሰድ አለባት ብሎ ቢወስን እስዋ ደግሞ ደም ባለመውሰድ ብትሞት በእምነትዋ የምታው ቀውንና አገኛለሁ ብላ የምትጠብቀውን የዘላለም ሕይወት ሊነፍገኝ ነው ብላ ትቃወማለች፡፡ ምን ማድረግ ነው ያለበት? እንደዚህ ያሉትን ጥያቄዎች ለመመለስ ሐኪሙ የሚመራበት የስነምግባር መመሪያ ሊኖረው ይገባል።
ከላይ የተጠቀሰውን አይነትና ሌሎች ተመሳሳይ ጥያቄዎችን ለመመለስ መሰረታዊ የማይጣሱ ደንቦች ምንድናቸው? የሚለውን ማሰብ ያስፈልጋል፡፡
በበሽተኛውና በሐኪሙ መሐከል ምን አይነት ግንኙነት መኖር አለበት የሚለው አንዱ ነው፡፡ ይህ ቃለ መሐላ የተፈጸመበትና የበሽተኛዬ ደህንነት ከሁሉ ነገር ይበልጣል የሚለውን የሚመለከት ነው፡፡
ሌላው …ስለራሱ በሽታና ስለደህንነቱ የሚወስነው ማነው? በሽተኛው ነው ወይንስ ሐኪሙ ነው? የሚ ለው ነው፡፡ ሐኪሙ መረጃ እና አማራጮችን መስጠት እንጂ መወሰን አይችልም፡፡ ስለዚህም የበሽተኛው መብት የማይደፈርና የማይገሰስ ነው፡፡
ቀጣዩ ፍትህ ነው፡፡ ፍትህ ማለት ሰውን ከሰው አላበላልጥም፡፡ ሐኪሙ ከበሽተኛ ጋር ባለኝ ግንኙነት ሁሉንም ሰው እኩል አክማለሁ ብሎ ማለት አለበት፡፡
የእራሱ የሃኪሙ ጸባይን በሚመለከትም ምግባሩ ምን ይመስላል? እንዴትስ ሊሰራ ይገባል? የሚለውን ማሳየት ያስፈልጋል፡፡ ሐኪም ምንጊዜም መዋሸት የለበትም፡፡
ሐኪም ታካሚውን መጥቀም አለበት፡፡ ሐኪም በሽተኛውን የሚጠቅም ነገር ባያደርግ እንኩዋን ጉዳት የሚያመጣ ነገር ግን አያደርግም፡፡
ሐኪሞች በየጊዜው እያነበቡ እራሳቸውን በእውቀት እየገነቡ በየጊዜው ከሚነደፈው የሳይንስ መርሐ ግብር ጋር እራሳቸውን ማዛመድ አለባቸው፡፡
ሌላው የጥቅም ግጭትን ማስወገድ ነው፡፡ አንድ ሐኪም ታካሚውን ወደሌላ ላቦራቶሪ ወይንም ክሊኒክ እንዲሄድ ሲመክር በግልጽ እዚያ ብትታከም ወይንም ምርመራህን ብታሰራ ጥሩ ቦታ ነው፡፡ በእርግጥ እኔ ኮሚሽን አገኝበታለሁ ወይንም አላገኝትም ብሎ መናገር መቻል አለበት፡፡ ይሁን እንጂ ሐኪም እንደዚህ ያለ የጥቅም ግጭት የሚፈጥር ነገር ውስጥ ከጅምሩም መግባት የለበትም ተብሎ ይታመናል፡፡
እንደማህጸንና ጽንስ ሐኪምነት ሴቶች በማህበረሰቡ ዘንድ ያላቸውን ጉዳት ይበልጥ መረዳትና መመስከር ስለሚቻል ሐኪም ብቻ መሆን ሳይሆን ስለሴቶቹ ችግር በአደባባይ ማስረዳት ወይ ንም መመስከር ይጠበቅባቸዋል፡፡ ምክንያቱም ችግሩን በውል ስለሚያውቁትና በተጨባጭ መረጃ በማስደገፍ ማስረዳት ሰለሚችሉ ተደማጭነታቸው ከፍተኛ ስለሚሆን ነው፡፡
ከላይ የተዘረዘሩት ነጥቦች አብዛኛው የማህጸንና ጽንስ ሐኪሞች በአለም ዙሪያ የሚመሩበትና የሚከተሉት መሰረታዊ መርሆዎች ስለሆኑ በኢትዮያም እንዲዘጋጅ የታቀደው የጽንስና ማህጸን ህክምና የስነምግባር መመሪያ ከዚህ የዘለለ አይሆንም እንደ ዶ/ር ሙኒር ካሳ ማብራሪያ።
የሙያው ስነምግባር ቢቀረጽ በዋነኛነት አንድ የማህጸን ሐኪም ርህራሔ በተሞላበት መንፈስ ታካሚውን እንዲረዳ ያስችለዋል፡፡

ሩሲያውያን አንድ ተረት አላቸው፡፡
ከዕለታት አንድ ቀን፣ አንድ ንጉሥ በዋናው ከተማ ውስጥ እየተዘዋወረ ሳለ የጣት ቀለበቱ ይጠፋበታል፡፡ ወዲያው በጋዜጣ ላይ ማስታወቂያ ያወጣል፡፡ “የጣት ቀለበቴን አግኝቶ ላመጣልኝ ሰው ወሮታውን እከፍላለሁ” የሚል ነው ማስታወቂያው፡፡ አንድ ተራ ወታደር ዕድለኛ ሆነና ቀለበቱን አገኘ፡፡ “ምን ባደርግ ይሻላል” ሲል አሰበ፡፡ “ወደ ዋናው ጦር ክፍሌ ሄጄ ሪፖርት ባደርግ ጉዳዩ ወደ በላይ ይመራል፡፡ እያንዳንዱ የበላይ የራሱ የበላይ አለው፡፡ ስለዚህ ወደ በላይ ይመራዋል፡፡ ሃምሣ አለቃው ለመቶ አለቃው፤ መቶ አለቃው ለሻምበሉ፤ ሻምበሉ ለሻለቃው፣ ሻለቃው ለኮሎኔሉ፣ ኮሎኔሉ ለብርጋዲየር ጄኔራሉ እያለ ማለቂያ በሌለው የዕዝ ሰንሰለት ውስጥ ሲቀባበሉት መኖሩ ነው፡፡ ስለዚህ በቀጥታ ወደ ንጉሱ ሄጄ ቀለበቱን ባስረክባቸው ይሻላል” ብሎ ይወስናል፡፡
ወደ ቤተ - መንግሥቱ ይመጣል፡፡
የጥበቃ መኰንኑ፤ “እዚህ ምን ልታደርግ መጣህ?” ይለዋል፡፡
“የንጉሱን የጣት ቀለበት አግኝቼ ለማስረከብ ነው የመጣሁት” ይለዋል ተራ ወታደሩ፡፡
“በጣም ጥሩ ነው ወዳጄ፡፡ ለንጉሱ እነግርልሃለሁ፡፡ ነገር ግን በአንድ ቅድመ ሁኔታ ነው፡፡ ይኸውም ንጉሱ ቀለበቱን ስላገኘህላቸው ከሚሸልሙህ ነገር ግማሹን ለእኔ የምትሰጠኝ ከሆነ ነው፡፡ ተራ ወታደሩም በሆዱ፤
“ወቸ ጉድ! በዕድሜዬ ዛሬ አንድ መልካም ዕድል ቢገጥመኝ፤ እሷኑ የሚቀራመተኝ አዘዘብኝ፡፡ ግን ይሁን ግዴለም፡፡ ይካፈለኝ” ይልና ወደ ጥበቃ መኮንኑ ዞሮ፤ “ይሁን ከሽልማቱ ግማሹን ላካፍልህ እስማማለሁ፡፡ ነገር ግን በአንድ ቅድመ - ሁኔታ ነው” ይለዋል፡፡
“ምንድነው ቅድመ ሁኔታው?” ሲል ይጠይቃል የጥበቃ መኮንኑ፡፡
“ከማገኘው ሽልማት ግማሹን አንተ፤ ግማሹን እኔ እንደምወስድ የሚገልጽ ማስታወሻ ፃፍልኝ” ሲል ይጠይቃል፡፡
የጥበቃ መኮንኑ ማስታወሻውን ጽፎ ይሰጠዋል፡፡ ከዚያም ሄዶ ለንጉሱ ቀለበቱን ያገኘ ሰው መምጣቱን ይናገራል፡፡ ንጉሱም ቀለበታቸውን ስለማግኘቱ ያን ተራ ወታደር እጅግ አድርገው ያመሰግኑትና፤
“በጣም አመሰግናለሁ ጀግና ወታደር! ሁለት ሺህ ብር በሽልማት መልክ ሰጥቼሃለሁ” ይሉታል፡፡
“የለም ንጉሥ ሆይ፤ ለወታደር የሚገባው ሽልማት ሁለት ሺ ብር ሳይሆን ሁለት ሺ ጅራፍ ነው፡፡” ይላል፡፡
ንጉሡም፤ እየሳቁ፡-
“ምን ያለው ጅል ነው?” ብለው “እሺ ጅራፉ ይምጣ” አሉና አዘዙ፡፡
ተራ ወታደሩ ልብሱን ማወላለቅ ሲጀምር፣ በድንገት አንዲት ወረቀት ዱብ ትላለች፡፡
“የምን ወረቀት ነው እሱ?” ሲሉ ይጠይቃሉ ንጉሱ፡፡
“ንጉሥ ሆይ፤ ይህ ማስታወሻ የሽልማቴን ግማሹን የጥበቃ መኮንንዎ እንዲወስድ የተስማማንበትን ውል የሚጠቁም ነው”
ንጉሱ ሳቁና የጥበቃ መኮንኑን አስጠሩት፡፡ ከዚያም “እንግዲህ መቶው ጅራፍ ያንተ ነው ማለት ነው” አሉት፡፡
ቀጥሎም የጥበቃ መኮንኑን በጅራፍ ገራፊው ይገርፈው ጀመር፡፡ የመጨረሻው አሥር ጅራፍ እንደቀረ፣ ያ ተራ ወታደር ወደ ንጉሱ ጆሮ ጠጋ ብሎ፤ “ንጉሥ ሆይ፤ እኔ እንደሱ ስስታም ሰው አይደለሁም፤ የቀረውን ግማሹን ሽልማቴንም ሰጥቼዋለሁ!” ይላቸዋል፡፡
“እንዴት ያለህ ደግ ሰው ነህ ጃል” አሉና ንጉሡ፤ የጥበቃ መኮንኑ ሌላውን የጅራፍ ሽልማት እንዲወስድ አዘዙ፡፡ ያ የጥበቃ መኮንን በእምብርክኩ እስኪሄድ ድረስ ተለጠለጠ፡፡
ከዚያም ንጉሱ ተራ ወታደሩን ጠሩና፤ “በል ከዛሬ ጀምሮ ከሥራ መደብህ በክብር ተባረሃል፡፡ ለመቋቋሚያ ይሆንህ ዘንድ ሶስት ሺ ብር ተሸልመሃል?” አሉና አሰናበቱት፡፡
*   *   *
ከበላይ ወደ በላይ ሲመራ ከሚውል ጉዳይ ይሰውረን፡፡ በየደረጃው ሽልማትህን አካፍለኝ ከሚሉም ያውጣን! ለበቀል ብለን የመዘዝነው ጅራፍ፣ በራሳችን ላይ እንደሚዞር ማስተዋያ ልቦና አያሳጣን፡፡ ባሳበቅንበት ሊሳበቅብን፣ ባስቀጣነው ልንቀጣ፣ ባጨበጨብንበት ሊጨበጨብብን እንደሚችል፤ በጭራሽ አንዘንጋ፡፡
“አፈር ወስዶ ብለን፣ ያማረርነው አባይ
የሚያጨበጭብ ሰው፣ ይዞ ነጐደ ወይ?”
አለ አሉ ገጣሚ፤ ሆይ ሆይ ሲል ውሃ የወሰደውን ሰው አይቶ፡፡ እንሸለም ብለን ሌላውን መጉዳት፣ ውሎ አድሮ የከፋ ጉዳት ወደማስተናገድ ሊያመራ እንደሚችል ዐይናችንን ገልጠን እንይ፡፡ ተማርን የምንል፣ ሥልጣን ላይ ያለን፣ በሞቅ ሞቅ ሙስናችንን ለመሸፈን የምንፍጨረጨር፣ የባለቤቱ ልጅ ነን የምንል፤ ከሁሉም በላይ ደግሞ ፊታችን ያለው እየወደቀ፣ እያየን እኔን አይመለከትም እያልን የምንስቅ፣ “አቤቱ ወደ ፈተናም አታግባን” ብንል ይሻላል፡፡
አንድ አዛውንት፤ “በዚህ ዘመን ዘርዛራ ወንፊት፣ ቀጥሎ ጠቅጣቃ ወንፊት መኖሩን አዳሜ አያውቅም፤ ከዘርዛራው ወንፊት ያመለጠው፣ በጠቅጣቃው ወንፊት የተያዘውን እየሰደበና እያዋረደ ብዙ የሚቆይ ይመስለዋል” ሲሉ ስለ ስብሰባዎች ተናግረዋል፡ አንዱ ባንዱ ሲስቅ ጀምበር ጥልቅ አለ ነው ነገሩ፡፡
በሰው ገንዘብ፣ በሰው ንብረት ላይ መፍረድ ቀላል ነው፡፡ እርዳታ ላያደርጉ፣ ይሄ ይሁን ይሄ አይሁን ማለትም እጅግ ቀላል ነው፡፡ የማያግዝ “ቤቱን አስፍታችሁ ሥሩ” ይላል፤ እንደተባለው ነው፡፡
ሳናወያይና ሳናጠና መመሪያ አናውጣ፡፡ ሳናስብ አንናገር፡፡ ከተናገርን አንፈር፡፡ ካፈርኩ አይመልሰን ብለንም በግትርነት አንደንፋ፡፡ ላወቅነውና ላለምነው ጉዞ በልባምነት እንገስግስ፡፡
አለቃ ተክለየሱስ ዋቅጅራ የተባሉ ደራሲ “የጐጃም ትውልድ በሙሉ፤ ከአባይ እስከ አባይ” በተባለ መጽሐፋቸው፤ “የማኖ የላስታ ሰው ነው፡፡ ጀግና ፈረሰኛ ነበር፡፡ ሥነፀሐይን ሲያጭ “ምን ገንዘብ አለህ” ቢሉት፤ “ልብና ፈረስ አለኝ” አለ፤ አሉ፡፡ ዓላማ ያለው፣ ለሀገርና ለህዝብ አሳቢ የሆነ ሰው፤ ልብና ፈረስ ያስፈልገዋል፡፡ በቀላሉ ተስፋ መቁረጥ የለበትም፡፡ አርቆ አስተዋይ ሊሆን ይገባል፡፡ የዛሬን ብቻ ሳይሆን የነግ ተነግወዲያውን ሊያሰላ፣ ሊያሰላስል ያሻል፡፡ ዕድገትና ብልጽግና የዚህ መርህ የልጅ ልጆች ናቸው፡፡ “መልካም አስተዳደር ይኑር፡፡ ፍትሕ አይጓደል፤ የግለሰብም ሆነ የቡድን ወገናዊነት ይውደም፤ ሙስና ይወገድ፣ የዲሞክራሲ መብቶች ይከበሩ” እየተባለ ነጋ ጠባ የሚወተወተው፣ ለአንድ ሀገራችን ዕድገት እንጂ ጥቂቶች የሚያወለውሉባትና ብዙሃን በአጥንታቸው የሚሄዱባት አገር ትሆን ዘንድ አደለም፡፡ ያውም ለሀብታሞቹ እንኳ ባልተመቸው በአሁኑ ዓለም!!
ፕሮፌሰር ሳች የተባሉ ምሁር፤ “በዛሬ ጊዜ፤ ሀብታሞቹ የአናሳ ፍትሕና የተትረፈረፈ አለመረጋጋት ሰለባ ይሆናሉ (A Less Just and more unstable world) የሚሉትን አባባል በጥሞና ማውጣት ማውረድም ይኖርብናል፡፡ ፍርሃትንና የደህንነት ምቾት ማጣትን የምንቋቋምበት ሥርዓት መፍጠር ይኖርብናል፡፡ “የተገደበውን የፖለቲካ መንቀሳቀሻ ሥፍራ የሚተካ/የሚያካክስ መላወሻ ሜዳ መፈጠር አለበት” እንደሚለን ማለት ነው ፒተር ጊልስ፡፡ ዛሬ እንደ ዋዛ የዘጋነው በር ነገ ከናካቴው ተከርችሞ፤ ቆላፊውም ተቆላፊውም መንገድ እንዳያጡ ስጋቱን መግለፁ ነው፡፡
በጥቃቅን እርምጃዎቻችን ከባባድ ለውጥ ያመጣን አስመስለን ከማጋነን መቆጠብ ይኖርብናል፡፡ ችግሮቻችን ዝሆን አከል ናቸው፡፡ የዝሆንን ግዙፍ አካል እለካለሁ ብላ እንደተነሳችው ጉንዳን እንዳንሆን መጠንቀቅ ተገቢ ነው፡፡ ሥር - ነቀልና ሥር የያዘ ለውጥ እያመጣን መሆኑን እያስረገጥን መጓዝ አለብን፡፡ በዚያው በትላንቱ ልባችንና አካሄዳችን እያለምን፤ ዛሬን አዲስ ነው ብለን ለማሳየት መሞከር፤ “ኖሮ በይው ልብሱን፣ ሰውዬውስ የቅድሙ ነው” እንደሚባለው የጉራጊኛ ተረት ይሆናል፡፡ Old wine in a new bottle እንደሚሉት መሆኑ ነው ፈረንጆቹ፡፡

የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ በ2009 በጀት ዓመት ካደረጋቸው አጠቃላይ እንቅስቃሴዎች 31.9 ቢሊዮን ብር ገቢ ማግኘቱንና ከታክስ በፊት 14.6 ቢሊዮን ብር ማትረፉን አስታወቀ፡፡
ባንኩ በላከው ጋዜጣዊ መግለጫ ላይ እንደተገለፀው፤ በዓመቱ በተለያዩ ዘርፎች ባደረጋቸው እንቅስቃሴዎች ከወጪ ንግድ፣ ከሃዋላ፣ ከወጪ ምንዛሪ ግዥና ሌሎች አገልግሎቶች 4.5 ቢሊዮን ዶላር ማግኘቱንም አስታውቋል፡፡ ባንኩ ከብድር ተመላሽ መሰብሰብ የቻለው 64.6 ቢሊዮን ብር ሲሆን 94.5 ቢሊዮን ብር ለልዩ ልዩ የሥራ መስኮች አዲስ ብድር መሰጠቱን ገልጿል፡፡
ህብረተሰቡ ስለቁጠባ የተሻለ ግንዛቤ እንዲኖረው ለማድረግ በሽልማት ላይ የተመረኮዘ ቁጠባን የማበረታታት ሥራ መሠራቱም ተገልጿል፡፡ በእነዚህ ተግባራት አማካኝነትም 76.4 ቢሊዮን ብር ተጨማሪ ተቀማጭ ገንዘብ ማሰባሰብ መቻሉን መረጃው አመላክቷል፡፡ ይህ ክንውን የባንኩን ጠቅላላ ተቀማጭ ገንዘብ በ2008 ከነበረበት 288.4 ቢሊዮን ወደ 364.9 ቢሊዮን ብር ማድረስ አስችሏል ተብሏል፡፡
የባንኩ ጠቅላላ ሀብት 485.7 ቢሊዮን ብር መድረሱንና የባንኩ ካፒታል ወደ 40 ቢሊዮን ብር ማደጉ ተገልጿል፡፡  የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ በአሁኑ ወቅት 1222 ቅርንጫፎች መድረሱንና፣ ሂሳብ ያላቸው የባንኩ ጠቅላላ ደንበኞች ቁጥርም 15.9 ቢሊዮን መድረሱን መግለጫው አመልክቷል፡፡

ቀድሞ የተከሰሱበት የሽብር ወንጀል ቀርቶ፣ በወንጀለኛ ህጉ ይከላከሉ በሚል ፍ/ቤት ብይን የሰጠባቸው የኦፌኮ ተቀዳሚ ምክትል ሊቀመንበር፣ አቶ በቀለ ገርባ፣ “ከእስር ቢለቀቁ በድጋሚ አመፅ ሊያነሳሱ ይችላሉ” በሚል የዋስትና ጥያቄያቸው ውድቅ ተደረገ፡፡  
በኦሮሚያ አካባቢዎች ከተቀሰቀሰ ህዝባዊ አመጽ ጋር ተያይዞ በፖሊስ ቁጥጥር ስር ውለው፣ በሽብር ድርጊት በመሳተፍ ወንጀል፣ ክስ የተመሰረተባቸው አቶ በቀለ ገርባ ጉዳይን የሚመለከተው ፍ/ቤት፤ ሐምሌ 7 ቀን 2009 ዓ.ም በሰጠው ብይን፣ በአቃቤ ህግ የቀረበባቸው የማስረጃ ዝርዝር፣ የሽብር ወንጀልን የሚያመላክቱ ባለመሆናቸው፣ “ግዙፍ ባልሆነ መሰናዳትና መገፋፋት” ወንጀል እንዲከላከሉ መወሰኑ ይታወሳል፡፡  
ይህን ተከትሎም እንዲከላከሉ ብይን የተሰጠበት አንቀፅ ዋስትና የሚፈቀድበት በመሆኑ፣ ለፍ/ቤቱ የዋስትና ጥያቄ ያቀረቡ ሲሆን አቃቤ ህግ በበኩሉ፤ሁለት ምክንያቶችን በማቅረብ ዋስትናው እንዳይፈቀድ ተቃውሟል፡፡ “መጀመሪያውኑ ዋስትናውን የተከለከሉት በሽብር ወንጀል ጉዳይ ነው፤ አሁን የክሳቸው አንቀፅ ቢቀየርም የዋስትና ጥያቄ መነሳት የለበትም፤” ያለው አቃቤ ህግ፤ ተከሳሹ ከሀገር ውጭ ካሉ ሰዎች ጋር የሚገናኙ በመሆኑ ከአገር ቢወጡ አይመለሱም ሲል ተከራክሯል፡፡ በተጨማሪም ተከሳሹ  ከእስር ቢለቀቁ ህዝብን የማነሳሳት ተግባራቸውን ሊቀጥሉበት ይችላሉ በማለት የዋስትና ጥያቄው ውድቅ እንዲደረግ ፍ/ቤቱን ጠይቋል፡፡  
የአቶ በቀለ ገርባ ጠበቆች በበኩላቸው፤ የተከሰሱበት አንቀጽ የዋስትና መብት የማይከለክል መሆኑን በመጥቀስ እንዲሁም አቶ በቀለ ገርባ ከዚህ ቀደም ከሀገር ወጥተው የተመለሱ በመሆናቸው ወጥተው ይቀራሉ የሚለው ግምት አይኖርም  በማለት የዋስትና ጥያቄ  ለፍ/ቤቱ ማቅረባቸውን ለማወቅ ተችሏል፡፡  
የግራ ቀኙን ክርክር የመረመረው ፍ/ቤቱም፤”ተከሳሹ ከእስር ቢወጡ ህዝብን የማነሳሳት ተግባራቸውን ላለመቀጠላቸው ማረጋገጫ የለም” በሚል የዋስትና ጥያቄያቸውን ውድቅ ማድረጉን ጠበቃ አመሃ መኮንን፣ ለአዲስ አድማስ አስረድተዋል፡፡ አቶ በቀለ ገርባ፣ከፊታችን ሰኞ ነሐሴ 8 ጀምሮ የመከላከያ ምስክሮቻቸውን እንደሚያቀርቡ ታውቋል፡፡

በየመን የባህር ዳርቻ በህገ ወጥ የሰዎች አዘዋዋሪዎች 120 ኢትዮጵያውንና ሶማሊያውያን ሆን ተብሎ ከጀልባ ላይ ወደ ባህር ተጥለው 50 የሚደርሡ ሰዎች መሞታቸው የአለም መገናኛ ብዙሃንን መነጋጋሪያ ሆኗል፡፡
አለማቀፉ የስደተኞች ድርጅትን (IOM) ጠቅሶ ዘገባውን ያሠራጨው ሲኤንኤን ረቡዕ እለት ወደ የመን እያመራች ባለች ጀልባ የተሣፈሩ 120 ኢትዮጵያዊያንና ሶማሊያውያን በአዘዋዋሪዎቹ ወደ ባህሩ ተጥለዋል ብሏል፡፡
በዚህም  50 ያህሉ መሞታቸው ሲረጋገጥ፣ 22ቱ የደረሱበት አለመታወቁን እንዲሁም 29ኙ በአይኦ ኤም የነፍስ አድን ሰራተኞች ህይወታቸው መትረፉ ተዘግቧል።
የስደተኞቹ አማካይ እድሜ 16 አመት መሆኑን የጠቆመው አይኦኤም፤ የታዳጊዎች ስደት መበራከት አሳሳቢ መሆኑን አስታውቋል፡፡  ከጥር 2009  ጀምሮ 55 ሺህ ያህል የምስራቅ አፍሪካ ዜጎች በየመን አቋርጠው ወደ መካከለኛው ምስራቅ ሃገራት መግባታቸውን የሚጠቁመው የስደተኞች ድርጅቱ ሪፖርት፤ ከነዚህም ውስጥ 30 ሺህ ያህሉ እድሜያቸው ከ18 ዓመት በታች፣ ሲሶ ያህሉም ሴቶች መሆናቸውን ያመለክታል፡፡

በአዲስ አበባ የሚገኘው የአሜሪካ ኤምባሲ፤ ከአዲስ አበባ ጅግጅጋ ባለው መስመር፣ በሃረር እና በባቢሌ ከተሞች አካፋይ ላይ በመሳሪያ የታገዘ ግጭት መኖሩን በመጠቆም፣ ዜጎቹ ወደ አካባቢዎቹ እንዳይንቀሳቀሱ ትናንት አስጠንቅቋል፡፡ ኤምባሲው ባወጣው መግለጫ፣ በአካባቢዎቹ የተከሰተውን ግጭት ተከትሎም መንገዱ በፀጥታ ኃይሎች መዘጋቱንና የመከላከያ ሰራዊትም ወደ ስፍራው ማምራቱን አስታውቋል፡፡ የአሜሪካ ዜጎች በሥፍራው ከተገኙም እንቅስቃሴያቸው ጥንቃቄ የተሞላበት እንዲሆንና ግርግር ከበዛበት አካባቢ እንዲርቁም ኤምባሲው አሳስቧል፡፡
ባለፈው ዓመትና ዘንድሮ በከፊል፣ የአሜሪካ መንግስት በኦሮሚያና በአማራ ክልል የተፈጠሩ አለመረጋጋቶችን ተከትሎ፣ በተደጋጋሚ ተመሳሳይ የጉዞ ማስጠንቀቂያዎችን ለዜጎቹ ሲያስተላልፍ እንደነበር ይታወሳል፡፡

አባትና ልጅ ወደ አንድ ማህበር ስብሰባ ለማድረግ በፈረስ ሆነው ይሄዳሉ አሉ፡፡ መንገድ ላይ ሳሉ ክርክር ያነሳሉ፡-
አባት - ይሄ ፀሐይ እየጠነከረ ሲመጣ፣ የፈረሱ ጥላ በስተቀኝ በኩል ይሆናል
ልጅ - የለም በግራ ነው የሚሆነው
አባት - አይሆንም፡፡ ምክንያቱም ዳገቱን ከወጣን በኋላ፣ እኛ ወደ ግራ ስለምንዞር ፀሐይ ጀርባውን ሳይሆን ጐኑን ነው የምትመታው፡፡ ግራ ጐኑን ስትመታው፣ ጥላው ወደ ቀኝ ይወድቃል፡፡
ልጅ - የለም የለም፡፡ ፀሐይ ወደ መሀል ሰማይ እየወጣች ስለምትሄድ፣ የፈረሱ ጥላም አቅጣጫውን ይቀይራል፡፡
አባት - እኛ ፈረሱ ላይ ስላለን ጥላው በደምብ አይታየንም
ልጅ - እንግዲያው ወርደን እንየዋ?
አባት - ልክ ነው፡፡ ብንወርድ በደምብ ይታየናል
ከፈረሱ ወርደው ፈረሱን ጉብታው ላይ አቆሙት፡፡ ፈረሱ መሳቅ ጀመረ፡፡
አባት - ይሄ ፈረስ ምን የሚያስቅ ነገር አግኝቶ ነው የሚስቀው?
ልጅ - ለምን አንጠይቀውም?
አባት - እሺ እንጠይቀው
ወደ ፈረሱ ተጠጉ፡፡
አባት - አንተ ፈረስ ምን የሚያስቅ ነገር አግኝተህ ነው የምትስቀው?
ፈረሱም እንዲህ ሲል መለሰ:-
“የምስቀው ስለገረማችሁኝ ነው”
አባት - ምናችን ነው ያስገረመህ?
ፈረስ - ከቤት ከወጣችሁ ጀምሮ ስለ እኔ ጥላ ስትጨቃጨቁ ሳዳምጥ ነበር። አሁን የእኔ ጥላ በቀኝ ወደቀ በግራ ፋይዳው ለእናንተ ምንድን ነው? ስንት ቁም ነገር ልትሰሩበት የምትችሉበትን ጊዜ በከንቱ ጭቅጭቅ ስታባክኑት ማየቴ ሲገርመኝ፤ ጭራሽ መሬት ወርዳችሁ ጥላዬን ለማየት ስትሞክሩ ተመለከትኩ፡፡ የሚያሳዝነኝ ለስብሰባ የሚጠብቃችሁ ማህበርተኛ ህዝብ ነው፡፡
አባትና ልጅ ፈረሱ ስለታዘባቸው በጣም ተናደዱ፡፡
አባት - አንተን በማያገባህ ገብተህ በእኛ ላይ በመሳቅህ መቀጣት አለብህ፡፡ እንዲያውም ካሁን ወዲያ እንዳትናገር አፍህ መለጐም አለበት፡፡
ፈረሱን አፉን ለጐሙት፡፡ ፈረሱ ግን በሆዱ መሳቁን ቀጠለ፡፡ እነሱም ስለጥላው አወዳደቅ ንትርካቸውን ቀጠሉ፡፡
*    *   *
በህዝብ ጊዜ፤ በሀገር ሰዓት የሚቀልዱ አያሌ ናቸው፡፡ ያም ሆኖ እንዳላጠፉ በመቁጠር መልሰው ህዝቡን ይወቅሳሉ፡፡ ዞረው ሀገርን ያማርራሉ፡፡ በተናገሩት ሲያፍሩ ያዳመጣቸውን ጥፋተኛ ያደርጋሉ፡፡ ፀሐፌ-ተውኔት ፀጋዬ ገ/መድህን፤
“የሚያባርረኝ ጠላት እንቅፋት መቶት በሞተ አርበኛ ተብዬ ታሰርኩ እንጂ እኔስ አርበኛ አልነበርኩም” እንዳለው መሆኑ ነው፡፡ ባጠፉት ጥፋት ሌሎችን መራገም፣ የዛሬ ህመማችን ብቻ አይደለም፡፡ የቆየ፤ የሰነበተ ደዌ ነው፡፡ በእንቶ ፈንቶውና በአርቲ-ቡርቲው ዘመን እያሳለፍን፣ ለሀገር እንደሰራን አድርገን ስንገበዝ ውዱ ጊዜ ይነቅዛል። ድምር ውጤቱ የኢኮኖሚው መንኮታኮት፣ የፖለቲካው መላ-ማጣት፣ የማህበራዊ ኑሮው መመሰቃቀል ይሆናል፡፡
የባህል መሸርሸር አደጋ፣ የትምህርት መውረድ አባዜ፣ የሃይማኖት ግጭት ሥጋት፣ የንግድ ሥርዓት ቅጥ-ማጣት፣ የመልካም አስተዳደር እጦት፣ የፍትሕ መዛባት፣ ዐይን-ያወጣ የሙስና ፖለቲካዊ-ኢኮኖሚ ቁጣ፣ የእከክልኝ - ልከክልህ ወገናዊነት ፖለቲካዊ ዘይቤ፣ የትውልድ ንቅዘት (degeneration)፣ የዘመቻ ሥራና መንገኝነት… ምኑ ቅጡ! ድምር ውጤታቸው ከቤተሰብ እስከ ህብረተሰብ የሚያናጋ ጉዳይ ነው፡፡ አንዳንዶች ክስተቱን መግለፅን እንደ አሉታዊነት ያዩታል፡፡ እውነታው ግን ድክመታችንን አይተን መላ እንፍጠር የሚል ነው፡፡ “…ሳሩን አየህና ገደሉን ሳታይ” የሚል የማስጠንቀቂያ ደወልም አለው፡፡ “አትፍረድ ይፈረድብሃል” የሚል አንድምታም አያጣም! “መሄድ ቢሉሽ መሄድ ነወይ…” ብንልም ያስኬዳል፡፡
“አንተም እሳት ነበርክ እሳት አዘዘብህ
እንደገና ዳቦ እሳት ነደደብህ” የሚለውን ለማስተዋል ጭንቀላትን ይዞ መተከዝ አይጠይቅም!
መልካም የተሰራን ማመስገን ደግ ነው፡፡ የሚያስወቅሰው፣ አድሮም የሚያስጠይቀው እንከን - የሞላውን ነገር እንከን - የለሽ ነው ማለት ስንጀምር ነው! ፍፁም ነው ማለት ስንጀምር አዛዥ ናዛዥ እንሆናለን! ይሄኔ ግራ የገባው የራስ ወገን ሳይቀር፤
“ያ ንሥር እንደኔ ዓይነት ሆኖ፣ ምን አየር ላይ አወጣው?” ይለናል፤ እንደ ዶሮው!

• ሆስፒታሉ በአገልግሎት ጥራት መጓደል ማስጠንቀቂያ ተሰጥቶታል
• ቅዱስ ሲኖዶስ፤ ሆስፒታሉ እንደ አዲስ እንዲደራጅ ትእዛዝ ሰጥቷል

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን፣ ብቸኛ ሆስፒታሏን በአግባቡ መቆጣጠርና ማስተዳደር ባለመቻሏ ለከፍተኛ ምዝበራ መጋለጡን በሆስፒታሉ ላይ የቀረበ ሪፖርት ያረጋገጠ ሲሆን፤ ቋሚ ሲኖዶስ፤ ምዝበራ ፈጽመዋል የተባሉ ሐኪሞችና የአስተዳደር ሠራተኞች ተባርረው፣ ሆስፒታሉ እንደ ዐዲስ እንዲደራጅ ወስኗል፡፡  
በቤተ ክርስቲያኗ ገንዘብ ከ23 ዓመት በፊት የተቋቋመው የምግባረ ሠናይ ጠቅላላ ሆስፒታል፤ በቤተ ክርስቲያኗ አስተዳደር ትኩረት ተነፍጎት በመቆየቱ ለግለሰቦች ምዝበራና መጠቀሚያ ውሏል፤ ይላል - የምርመራ ሪፖርቱ፡፡
ቋሚ ሲኖዶሱ፣ ባለፈው ሐምሌ 28 ቀን 2009 ዓ.ም ባሳለፈው ውሳኔ፤ በሆስፒታሉ ውስጥ አላግባብ የሚፈጸም የደመወዝ ክፍያን ጨምሮ በሆስፒታሉ ላይ ከፍተኛ ብክነትና ምዝበራ እየተፈጸመ መሆኑን ከሪፖርቱ መረዳቱን በመግለጽ፣ ምዝበራ ፈጽመዋል ያላቸውን የሕክምና ባለሞያዎችና ሌሎች ሠራተኞች  የሥራ ውላቸው ተቋርጦ እንዲሰናበቱ ትእዛዝ ሰጥቷል። ሆስፒታሉም የቤተ ክርስቲያኒቱን ማኅበራዊ ተልእኮ ለማሳካትና ሥራንና ሠራተኛን ለማገናኘት በሚያስችል መልኩ ዳግም እንዲደራጅ ወስኗል፡፡  
ሆስፒታሉ፣ በቂ ካፒታልና በጀት ሳይኖረው፣ የጡረታ ጊዜያቸው ያለፈ የአስተዳደር ሓላፊዎች ለራሳቸው ከፍተኛ የደመወዝ ጭማሪ በማድረግ፣ የሕክምና ባለሞያዎችን ሲበድሉ መቆየታቸውም በሪፖርቱ ተጠቁሟል፡፡ አሠራሩ የዘመድ አዝማድ በመሆኑም ተመሳሳይ የሞያ አገልግሎት በሚሰጡ ሐኪሞች መካከል ከፍተኛ የደመወዝ ልዩነት መኖሩን የሚጠቅሰው ሪፖርቱ፤ ሙሉ ጊዜያቸውን በሆስፒታሉ ተቀጥረው የሚሠሩ አንድ ሐኪም በወር 31 ሺሕ 943 ብር ሲከፈላቸው፣ በሳምንት ለተወሰኑ ቀናት ብቻ በትርፍ ጊዜያቸው የሚሠሩ ሌላ ሐኪም በአንጻሩ፣ 75 ሺሕ 169 ብር እንደሚከፈላቸው ይገልጻል፡፡
የሠራተኛ ቅጥርና ዕድገት ከሕግና መመሪያ ውጪ፣ ያለውድድርና ማስታወቂያ፣ በሥራ ሓላፊዎች የግል ይኹንታ ብቻ እንደሚፈጸም በሪፖርቱ የተጠቀሰ ሲሆን፣ ለሠራተኞች ተገቢው ሞያዊ ክብር ሳይሰጥ መቆየቱና የመልካም አስተዳደር ችግር መኖሩ ተጠቁሟል። ለማጣራቱና ርምጃው መነሻ የሆነውን አቤቱታ ለጠቅላይ ጽ/ቤቱ ያቀረቡት እማሆይ ምስጢረ ሥላሴ ከበደ፣ በነርስነት እያገለገሉ በትርፍ ጊዜያቸውና በግል ጥረታቸው ተምረው በጤና መኮንነት ተመርቀው የሞያ ፈቃድ ቢያገኙም፣ መድቦ ሊያሠራቸው አለመቻሉ በማሳያነት ቀርቧል፡፡ “የጤና መኮንነት የሞያ ሥራ ፈቃድ በሆስፒታሉ ውስጥ የሥራ መደብ ስለሌለው መድበን ልናሠራቸው አልቻልንም፤” በማለት ሥራ አስኪያጁ የሰጡት ምላሽም፣ ተገቢነትና ፍትሐዊነት የጎደለው ነው፤ ተብሏል፡፡ ሆስፒታሉን ከጠቅላይ ቤተ ክህነት እስከ ቅዱስ ሲኖዶስ ድረስ የሚቆጣጠር ሥርዓት ባለመዘርጋቱ፣ የሥራ አመራር ቦርዱም ተገቢ ክትትል ባለማድረጉ፣ የቤተ ክርስቲያኒቱን ብቸኛ ሆስፒታል የመዘጋት አደጋ ላይ እንደጣለውም ታውቋል፡፡
በአጠቃላይ የሆስፒታሉ አስተዳደር ሙሉ በሙሉ በጡረተኞች እጅ ከመውደቁ የተነሳ ከተቋማዊ ዕድገት ይልቅ የግለሰቦች ጥቅም እንዲንሰራፋ ዕድል መክፈቱን የሚገልጸው ሪፖርቱ፤ ተገቢውን የሕክምና አገልግሎት መስጫ መሣሪያዎች ባለማሟላትና ደረጃውን የጠበቀ አገልግሎት መስጠት ባለመቻሉም  ከአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ጤና ቢሮ የመጨረሻ ማስጠንቀቂያ እንደተሰጠው ይጠቁማል፡፡ ማስጠንቀቂያውን ተከትሎ፣ ሆስፒታሉ ከተሰጠው ቀነ ገደብ በፊት ጉድለቱን ለማሟላት ያደረገው ጥረት እንደሌለና አፋጣኝ የእርምት ርምጃ መውሰድ ካልተቻለ፣ ቤተ ክርስቲያኗ ብቸኛ ሆስፒታሏን የማጣት አደጋ ተጋርጦባታል፤ ይላሉ - ምንጮች፡፡
አስተያየት ሰጪዎች እንደሚሉት፣ ምንም እንኳን ርምጃው የዘገየ ቢሆንም፣ ቋሚ ሲኖዶሱ ሪፖርቱ በደረሰው በአጭር ጊዜ ውስጥ “ምዝበራ ፈጽመዋል፤ ለሆስፒታሉ ዕድገት ማነቆ ሆነዋል፤” በሚል የተጠቆሙትና የተጠረጠሩት ሥራ አስኪያጁ፣ የፋይናንስ መመሪያ ሓላፊው፣ የንብረትና የሰው ኃይል መምሪያ ሓላፊው እና የትርፍ ጊዜ ተቀጣሪ ጡረተኛ ሐኪሞች በሙሉ የሥራ ውላቸው ተቋርጦ፣ ሆስፒታሉ በሞያ ብቁ በሆኖ ባለሞያዎች በድጋሚ እንዲደራጅና እንዲመራ መወሰኑ ትልቅ ርምጃ ነው፡፡ አሁንም ግን ጠንካራ የቁጥጥር ሥርዓትና ማኔጅመንት ማበጀት የግድ መሆኑን ምንጮች ይገልጻሉ፡፡

“በትግራይ በሃይማኖት ምክንያት የማይግባባ ማኅበረሰብ እየተፈጠረ ነው” /ምእመናን/

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስ፣ ግድፈት አለበት በሚል በመቐለ ከተማና አካባቢዋ ሊቃውንትና ምእመናን ተቃውሞ የቀረበበት የትግርኛ መጽሐፍ ቅዱስ ትርጉም እንዳይሠራጭ ያገደ ሲሆን፤ አተረጓጎሙና ይዘቱ በሊቃውንት ጉባኤ እንዲመረመር አዘዘ፡፡
የኢትዮጵያ መጽሐፍ ቅዱስ ማኅበር በ2007 ዓ.ም. ያሳተመው የትግርኛ ትርጉም፤ ቤተ ክርስቲያኒቱ፣ ከኢትዮጵያ ካቶሊካዊትና ወንጌላውያን ኅብረት አብያተ ክርስቲያናት በጋራ ያሳተመችው ቢኾንም፤ ትግራይን ጨምሮ በማንኛውም አህጉረ ስብከት እንዳይሠራጭ፣ ቅዱስ ሲኖዶሱ ለማኅበሩ ማስታወቁ ተገልጿል፡፡
የቋንቋ አጠቃቀም፣ አተረጓጎምና ይዘት፣ በቤተ ክርስቲያኒቱ የሊቃውንት ጉባኤ እንዲመረመር ትእዛዝ የሰጠው ቅዱስ ሲኖዶሱ፣ “ውጤቱ ታይቶ ውሳኔ እስኪሰጥ ድረስ ኅትመቱ የታገደ መኾኑ እንዲታወቅ ለሚመለከተው ኹሉ ይገለጥ፤” ሲል ወስኗል፡፡
መጽሐፍ ቅዱሱ በትግርኛ ቋንቋ መተርጎሙ፣ ለኅብረተሰቡ አስፈላጊ እንደኾነ ቢታመንበትም የተዛባ መኾን እንዳልነበረበት በአቤቱታቸው የተቹት ሊቃውንቱና ምእመናኑ፤ በመላው ትግራይ መለያየትና ሁከት እየፈጠረ እንደኾነና ወደ ወረዳዎች የተበተነው የኅትመቱ ቅጅ እንዲሰበሰብ ወይም ማስተካከያ ደብዳቤ ወደ ኹሉም ወረዳዎች እንዲጻፍ፣ ካለፈው ግንቦት ጀምሮ ሲጠይቁ ቆይተዋል፤
ከ92 በመቶ በላይ የክልሉ ሕዝብ፣ የኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ሃይማኖት ተከታይ በኾነበት፣ አተረጓጎሙ ለሌሎች የክርስትናው እምነቶች አስተምህሮ እንዲመችና መሠረታዊ ዶክትሪኗን በሚፃረር መልኩ መታተሙ፣ ቤተ ክርስቲያኒቱ፣ ከማኅበሩ ከምትጠቀም ይልቅ የምትጎዳበት እያመዘነ እንደመጣ ያመለክታል፤ ብለዋል፡፡ ቅዱሳት መጻሕፍቱን በጥንቃቄ የሚመረምር የሊቃውንት ጉባኤ በሀገርና በአህጉረ ስብከት ደረጃ ማጠናከርና ራሱን የቻለ የዲጅታል ኅትመት ተቋም እንድታቋቁምም ጠይቀዋል፡፡
በሌላ በኩል፤ ምእመናኑ፣ በመቐለ ቅዱስ ፍሬምናጦስ አቡነ ሰላማ ከሣቴ ብርሃን መንፈሳዊ ኮሌጅና በክልሉ የተለያዩ ወረዳዎች፣ የቤተ ክርስቲያኒቱን የእምነት ነጻነት እየተጋፉ ነው፤ ያሏቸው የሌሎች ቤተ እምነቶችና ምልምሎቻቸው ድርጊት ሳቢያ፣ “በሃይማኖት ምክንያት የማይግባባ ማኅበረሰብ እየተፈጠረ ነው፡፡ ይህም ለቤተ ክርስቲያን ብቻ ሳይኾን ለአገርም አለመረጋጋት የሚፈጥር ነው፤” ብለዋል ምእመናኑ፡፡ መቐለንና አካባቢዋን ጨምሮ ኵሓ፣ ፈለገ ዳዕሮ፣ ሓውሰዋ፣ ደንጎላትና ሌሎች የደቡብ ምሥራቅ አካባቢዎች ችግሩ እንደሚታይባቸው ጠቅሰው፣ ሊወሰዱ ይገባሉ ያሏቸውን የጥንቃቄ ርምጃዎችም በአቤቱታቸው አመልክተዋል፡፡
መንፈሳዊ ኮሌጁ፣ ችግሩ ባለባቸው ደቀ መዛሙርት ላይ፣ ካለፈው 2008 ዓ.ም ጀምሮ የሚወስደውን የመለየትና የማጥራት ርምጃ አጠናክሮ እንዲቀጥል፤ በተማሪዎች ምልመላ ጥንቃቄ እንዲደረግ፤ አስተዳደሩና መምህራኑም በጥልቀት እንዲጤኑ የሚሉት፣ በመፍትሔነት ከዘረዘሯቸው ተግባራት ይገኙበታል። የሀገረ ስብከቱ ሊቀ ጳጳስና ሀገረ ስብከቱም፣ የሚጠበቅባቸውን እንዲወጡና ይህን አስመልክቶም በጠቅላይ ጽ/ቤቱ ቀደም ሲል የተላለፉ ውሳኔዎች ተግባራዊ እንዲደረጉላቸው ምእመናኑ ጠይቀዋል፡፡

   • 7.3 ሚ ዶላር የሽልማት ገንዘብ ተዘጋጅቷል፡፡
         • ከ660 ሺ በላይ ትኬቶች ተሸጠው ሪከርድ ተመዝግቧል፡፡
         • ብሬንዳን ፎስተርና ፖል ቴርጋት ልዩ የክብር ሽልማት ተሰጥቷቸዋል፡፡
         • ቦልት፤ ሞ ፋራህ እና ጥሩነሽ የመጨረሻ ተሳትፏቸውን ያደርጋሉ፡፡
         • ጥሩነሽ 6ኛዋን የወርቅ ሜዳልያ በ10ሺ ሜ እንደምታገኝ ብዙ ሲገመት፤ ለኢትዮጵያ ሌላ የወርቅ ሜዳልያ የተጠበቀው በወንዶች ማራቶን ብቻ ነው፡፡
         • ገንዘቤ በ1500 ሜትር ፤ አልማዝ አያና በ5 ሺ ሜ፣ እንዲሁም ማሬ ዲባባ በማራቶን የሻምፒዮናነት ክብራቸውን ሊነጠቁ ይችላሉ፡፡ የአትሌቲክስ    ዊክሊእና የትራክ ኤንድ ፊልድ ኒውስ ትንበያዎች
     16ኛው የዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና በለንደን ከተማ በሚገኘው ኦሎምፒክ ስታድዬም ትናንት ተጀምሯል። 205 አገራትን የሚወክሉ 2000 አትሌቶች ለ10 ቀናት በሚካፈሉበት ሻምፒዮናው 7.3 ሚሊዮን ዶላር የሽልማት ገንዘብ ተዘጋጅቷል፡፡ በሽልማቱ ዝርዝር አከፋፈል መሰረት ለወርቅ ሜዳልያ 60ሺ ዶላር፤ ለብር ሜዳልያ 30ሺ ዶላር እንዲሁም ለነሐስ ሜዳልያ 20ሺ ዶላር የሚታሰብ ሲሆን ለአራተኛ ደረጃ 15ሺ ዶላር፤ ለአምስተኛ ደረጃ 10ሺ ዶላር፤ ለስድስተኛ ደረጃ 6ሺ ዶላር፤ ለሰባተኛ ደረጃ 5ሺ ዶላር እንዲሁም ለስምንተኛ ደረጃ 4ሺ ዶላር የሚበረከት ይሆናል፡፡ በሌላ በኩል በሻምፒዮናው ላይ አዲስ የዓለም ሪከርድ ለሚያስመዘግቡ አትሌቶች የውድድሩ አብይ ስፖንሰሮች ቲዲኬ 100ሺ ዶላር እንዲሁም በተጨማሪ ቶዮታ 100ሺ ዶላር እንደሚሰጡ ታውቋል። ሻምፒዮናውን የሚያስተናግደውና የዌስትሃም ክለብ ሜዳ የሆነው የኦሎምፒክ ስታድዬም በ563 ሚሊዮን ዶላር የተገነባ ነው፡፡
ለ16ኛው የዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና  1.04 ሚሊዮን ስታድዬም የመግቢያ ትኬቶች ለገበያ ቀርበው ከ660 ሺ በላይ የተሸጡ ሲሆን ይህም በ2009 እኤአ ላይ በበርሊኑ የዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና በ417, 156 የተመዘገበውን የትኬቶች ሽያጭ ክብረወሰን ያሻሻለ ሆኗል፡፡
በሻምፒዮናው ዋዜማ ላይ የዓለም አቀፉ የአትሌቲክስ ፌደሬሽኖች ማህበር 51ኛው የኮንግረስ ጉባኤ የተካሄደ ሲሆን ከ200 በላይ አገራት ተሳትፈውበታል፡፡ በዚሁ ጉባኤ ላይ ለታዋቂው እንግሊዛዊ የረጅም ርቀት ሯጭ እና፤ የታላቁ ሩጫ ኩባንያ በእንግሊዝ መስራች ብሬንዳን ፎስተር የአይኤኤኤፍ ‹‹ጎልደን ኦርደር ኦፍ ሜሪት›› ፤ ለኬንያዊው የረጅምር ርቀት ሯጭ ፤ የዓለም አቀፉ ኦሎምፒክ ኮሚቴ አባል ፖል ቴርጋት ደግሞ የአይኤኤኤኤፍ ‹‹ፕላግ ኦርደር ኦፍ ሜሪት›› ሽልማቶች ተበርክተዋል፡፡
በዓለም ሻምፒዮና ላይ ለመጨረሻ ግዜ በመሳተፍ ልዩ  ትኩረት ከሳቡት መካከል ጃማይካዊው ዩሴያን ቦልት፤ እንግሊዛዊው ሞ ፋራህ፤ እና ኢትዮጰያዊቷ ጥሩነሽ ዲባባ ዋናዎቹ ናቸው፡፡ በዓለም ሻምፒዮና የተሳትፎ ታሪኩ 11 የወርቅ ሜዳልያዎችን የሰበሰበው ጃማይካዊው ዩሴያን ቦልት ከለንደን የዓለም ሻምፒዮና የመጨረሻ ተሳትፎው በኋላ ጡረታ ለመውጣት መወሰኑ ሲያነጋግር ሰንብቷል፡፡
ቦልት በዓለም ሻምፒዮናው ለመጨረሻ ጊዜ በ100 ሜትር እና በ4 በ100 ሜትር ውድድሮች በመሳተፍ 2 የወርቅ ሜዳልያዎች ማግኘት ከቻለ በሻምፒዮናው ታሪክ በአጭር ርቀት 13 የወርቅ ሜዳልያዎች በመጎናፀፍ ከፍተኛውን የውጤት ክብረወሰን የሚያስመዘግብ ይሆናል፡፡ ዩሴያን ቦልት በሩጫ ዘመኑ  60 ሚሊዮን ዶላር ሃብት ያካበተ ሲሆን በውድድር ያገኛቸው ሽልማቶች እስከ 2.24 ሚሊዮን ዶላር ብቻ ነው፡፡ ዘ ቴሌግራፍ በሰራው ትንታኔ ዩሴያን ቦልት አብዛኛውን ገቢ የሚያገኘው ከስፖንሰሮቹ ሲሆን በተለይ እስከ 2025 እኤአ ከፑማ ኩባንያ ጋር በፈፀመው ውል በየዓመቱ የሚከፈለው 3.1 ሚሊዮን ዶላር ትልቁ ገቢው ነው። ጋቶርዴ፤ ሁብቦልት፤  ቨርጂን ሚዲያ፤ ቪዛ ካርድ እና ኒሳን ሞተርስ ሌሎች የአትሌቱ ስፖንሰሮች ናቸው። የዩሲያን ቦልትን የአትሌቲክስ ገቢ ቴሌግራፍ ሲያሰላ በዓለም ሻምፒዮና 728ሺ ዶላር እንዲሁም 23 ጊዜ የዳይመንድ ሊግ ውድድሮችን በማሸነፍ 210ሺ ዶላር ማግኘቱን ጠቅሶ በ2009 እኤአ በርሊን ባስተናገደችው 11ኛው የዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና ላይ 2 የዓለም ሪከርዶችን በ100 ሜትር 9.58 ሰከንዶች እንዲሁም በ200 ሜትር 19.19 ሰኮንዶች ሲያስመዘግብ የወሰደው 200ሺ ዶላር የሪከርድ ቦነስ መሆኑን አመልክቷል፡፡ በሌላ በኩል የ34 ዓመቱ እንግሊዛዊ ሞ ፋራህ በዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና የመጨረሻውን ተሳትፎ የሚያደርግ ሲሆን በሶስት ተከታታይ የዓለም ሻምፒዮናዎች በ5ሺ ሜትር እና በ10ሺ ሜትር ውድድሮች ድርብ የወርቅ ሜዳልያዎች በመሰብሰብ በታሪክ የመጀመርያው አትሌት ለመሆን አነጣጥሯል፡፡በዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮናው ለስድስተኛ ጊዜ የምትሳተፈው ጥሩነሽ ዲባባ 6ኛውን የወርቅ ሜዳልያ በ10ሺ ሜትር በመሳተፍ ማስመዝገቧ አዲስ የታሪክ ከፍተኛ የውጤት ክብረወሰን ሆኖ ሊጠቀስ ይችላል፡፡
በታዋቂዎቹ የአትሌቲክስ ዘጋቢ ድረገፆች ትራክ ኤንድ ፊልድ ኒውስ እና አትሌቲክስ ዊኪሊ ድረገፆች ለ16ኛው የዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና ተዘጋጅተው  የወጡ የሜዳልያ ትንበያዎች ለኢትዮጵያ ዝቅ ያለ ግምት ሰጥተዋል፡
ከ1 ሳምንት በፊት ተሻሽሎ የተሰራጨው የትራክ ኤንድ ፊልድ ኒውስ እንዲሁም የአትሌቲክስ ዊክሊ  የወርቅ፤ የብርና የነሐስ ሜዳልያዎች ዝርዝር ግምት እንዲሁም ያለፉት 15 የዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮናዎች የውጤት ታሪክ፤ የውድድር ፕሮግራሞች እና ኢትዮጵያን የሚወክሉ አትሌቶች ከዚህ በታች ቀርበዋል፡፡
በ800 ሜትር
ለኢትዮጵያ የተሰጠ የሜዳልያ ግምት የለም
ባለፉት 15 ሻምፒዮናዎች (1 የወርቅ ሜዳልያ በወንዶች)
በ16ኛው የዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና ላይ ኢትዮጵያን በመወከል የሚሳተፉት አትሌቶች ሐብታም አለሙ፤ ኮሬ ቶላ ፤ ማህሌት ሙሉጌታ(በሴቶች) እንዲሁም  መሃመድ አማን (በወንዶች) ናቸው፡፡ ለኢትዮጵያ በዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና በ800 ሜትር ብቸኛው ውጤት በወንዶች የመጀመርያውን የወርቅ ሜዳልያ ድል በ2013 እኤአ ላይ በሞስኮ ያስመዘገበው መሃመድ አማን ነው፡፡ አትሌቲክስ ዊኪሊ በሰራው ትንብያ በወንዶች ምድብ የወርቅ ሜዳልያው ለኬንያዊው ኢማኑዌል ኮሪር፤ የብር ሜዳልያው ለቦትስዋናው ኒጄል አሞስ እንዲሁም የነሐስ ሜዳልያው ለኬንያው ኪፕዮጌ ቤት የተገመተ ሲሆን በሴቶች ምድስብ ደግሞ የወርቅ ሜዳልያው ለደቡብ አፍሪካዋ ካስተር ሴማንያ፤ የብር ሜዳልያው ለብሩንዲዋ ፍራንኪሶ ኒኮሻ እንዲሁም የነሐስ ሜዳልያው ለአሜሪካዋ አጄ ዊልሰን ተሰጥቷል፡፡
ትራክ ኤንድ ፊልድ ኒውስ ለሴቶች የሰራው ትንበያ ከአትሌቲክስ ዊክሊ ጋር የተመሳሰለ ሲሆን በወንዶች ግን የወርቅ ሜዳልያው ለቦትስዋናው ኒጄል አሞስ፤ የብር ሜዳልያው ለኢማኑዌል ኮሪር እንዲሁም የነሐስ ሜዳልያው ለኬንያው ኪፕዮጌ ቤት ነው የተገመተው፡፡
በ1500 ሜትር
የዓለም ሻምፒዮንና የዓለም ሪከርድ ባለቤት ገንዘቤ የነሐስ ሜዳልያ ተገምቶላታል
ባለፉት 15 ሻምፒዮናዎች በሴቶች 1 የወርቅ ሜዳልያ ፤ በወንዶች 1 የብር ሜዳልያ
በ16ኛው የዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና ላይ ኢትዮጵያን በመወከል የሚሳተፉት አትሌቶች በሴቶች ገንዘቤ ዲባባ (ሻምፒዮን)፤ ጉዳፍ ፀጋዬ፤ በሱ ሳዶና  ፋንቱ ወርቁ ሲሆኑ በወንዶች ደግሞ አማን  ወጤ፤  ሳሙኤል ተፈራና ተሬሳ ቶሎሳ ናቸው፡፡ ለኢትዮጵያ በዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና በ1500 ሜትር ብቸኛውን የወርቅ ሜዳልያ በ2015 እኤአ በቤጂንግ ያስመዘገበችው በሴቶች ገንዘቤ ዲባባ ናት፡፡ በወንዶች ደግሞ ብቸኛውን ውጤት በ2009 እኤአ በርሊን ላይ ደረሰ መኮንን በብር ሜዳልያ አስመዝግቦታል፡፡ አትሌቲክስ ዊኪሊና ትራክ ኤንድ ፊልድ ኒውስ በሰሩት ትንበያ የሜዳልያ ውጤቶቹን በወንዶች ምድብ ለኬንያውያን ሙሉለሙሉ ሰጥተዋል። በሴቶች ደግሞ የወርቅ ሜዳልያውን ለኬንያዊቷ ፌዝ ኪፕዮጌ፤ የብር ሜዳልያውን ለባህሬኗ ትውልደ ኢትዮጵያዊት ሲፋን ሃሰን እንዲሁምየነሐስ ሜዳልያውን ለገንዘቤ ዲባባ አትሌቲክስ ዊክሊ ሲገምት ትራክ ኤንድ ፊልድ ኒውስ ደግሞ የወርቅ ሜዳልያውን ለባህሬኗ ሲፋን ሃሰን ሰጥቶ የብር ሜዳልያውን ለኬንያው ፌዝ ኪፕዮጌ በመገመት ገንዘቤ ዲባባን ለነሐስ ሜዳልያ ጠብቋታል፡፡
በ3ሺ ሜ. መሰናክል
ለኢትዮጵያ የተሰጠ የሜዳልያ ግምት የለም
ባለፉት 15 ሻምፒዮናዎች በሴቶች 1 የብር 1 የነሐስ ሜዳልያዎች
በ16ኛው የዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና ላይ ኢትዮጵያን በመወከል የሚሳተፉት አትሌቶች በሴቶች ሶፍያ አሰፋ፤  እቴነሽ ዲሮና ብርቱካን ፈንቴ ሲሆኑ በወንዶች ደግሞ ጌትነት ዋሴ፤ ታፈሰ ሰቦቃና ተስፋዬ ድሪባ ናቸው፡፡ ለኢትዮጵያ በዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና በ3ሺ ሜትር መሰናክል በሁለቱም ፆታዎች  የወርቅ የሜዳልያ ውጤት ተመዝግቦ አያውቅም፡፡ በ2013 እኤአ  በሞስኮ ሲካሄድ በሴቶች የብር እና የነሐስ ሜዳልያዎች ተገኝተዋል፡፡ አትሌቲክስ ዊክሊና ትራክ ኤንድ ፊልድ ኒውስ በሁለቱም ፆታዎች የሜዳልያ ግምቱን ለኬንያውያን ሰጥተዋል፡፡
በ5ሺ ሜትር
በሴቶች ሪከርድ ሊሰበር እንደሚችል፤ የወርቅ ሜዳልያው በኬንያ እንደሚነጠቅ ቢገመትም፤ የኢትዮጵያ አትሌቶች ከ1 እስከ 3 ተጠብቋል፡፡
በወንዶች ትልቁ ግምት ለሙክታር ኢድሪስ የተሰጠው የብር ሜዳልያ ነው፡፡
ባለፉት 15 ሻምፒዮናዎች  በሴቶች  5 የወርቅ ፤ 1 የብርና 8 የነሐስ ሜዳልያዎች በወንዶች 1 የወርቅ፤ 3 የብርና 3 የነሐስ ሜዳልያዎች
በ16ኛው የዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና ላይ ኢትዮጵያን በመወከል የሚሳተፉት አትሌቶች በሴቶች ሻምፒዮናነቷን ለማጠበቅ የምትሰለፈው አልማዝ አያና፤ ገንዘቤ ዲባባ፤  ሰንበሬ ተፈሪና  ለተሰንበት ግደይ ሲሆኑ በወንዶች ደግሞ ሙክታር እድሪስ፤  ሰለሞን ባረጋ፤ ዮሚፍ ቀጄልቻና በዳይመንድ ሊግ አሸናፊነቱ በቀጥታ መሳተፍ የሚችለው ሃጎስ ገ/ህይወት ናቸው፡፡ በዚህ ርቀት 16ኛው የዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና ላይ አዲስ የዓለም ሪከርድ ሊመዘገብ እንደሚችል በርካታ ዘገባዎች ይጠቅሳሉ፡፡ በተለይ ኢትዮጵያውያኑ ሴት አትሌቶች ገንዘቤ ዲባባ እና አልማዝ አያና ከመሳተፋቸው ጋር ተያይዞ ነው፡፡  በ5ሺ ሜትር ሴቶች ፍፁም የበላይነት ያላት ኢትዮጵያ ባለፉት ሁለት የዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮናዎች የወርቅ ሜዳልያዎችን መውሰድ የቻለች ሲሆን በተሳትፎ ታሪኳ ከወንዶች እጅግ የላቀ ውጤት አላት፡፡ በ15 የዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮናዎች በሴቶች  5 የወርቅ ፤ 1 የብርና 8 የነሐስ ሜዳልያዎችን ሰብስባለች። በ1999 እና በ2001 እኤአ ላይ በተደረጉት ሁለት ተከታታይ የዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮናዎች አየለች ወርቁ ሁለት የነሐስ ሜዳልያዎችን በማግኘት ፈርቀዳጅ ነበረች፡፡ ከዚያም በ2003 እኤአ ጥሩነሽ ዲባባ የወርቅ፤ በ2005 እኤአ ጥሩነሽ ዲባባ የወርቅ፣ መሰረት ደፋር የብር እንዲሁም እጅጋየሁ ዲባባ የነሐስ፤ በ2007 እኤአ መሰረት ደፋር የወርቅ፤ በ2009 እና በ2011 እኤአ መሰረት ደፋር ሁለት የነሐስ ሜዳልያዎች፤ በ2013 እኤአ ላይ  መሰረት ደፋር የወርቅ እንዲሁም አልማዝ አያና የነሐስ ሜዳልያዎች፤ በ2015 እኤአ ደግሞ አልማዝ አያና የወርቅ ሰንበሬ ተፈሪ የነሐስ ሜዳልያዎችን ማግኘት ችለዋል።  በወንዶች 5ሺ ሜትር በሻምፒዮናው ታሪክ ከአንድ ጊዜ በላይ የወርቅ ሜዳልያው ለማግኘት ለኢትዮጵያ ለማግኘት ሳይቻል  ቆይቷል፡፡ የመጀመርያው የሜዳልያ ውጤት የተመዘገበው በ1991 እኤአ ላይ በፊጣ ባይሳ በተገኘው የብር ሜዳልያ ነው፡፡ ከዚያ በኋላ በ1993 እኤአ ላይ ሃይሌ ገብረስላሴ የብርና ፊጣ ባይሳ የነሐስ፤ በ2001 እኤአ ላይ ሚሊዮን ወልዴ የብር፤ በ2003 እኤአ ላይ ቀነኒሳ በቀለ የነሐስ፤ በ2005 እኤአ ላይ ስለሺ ስህን የብር፤ በ2009 እኤአ ላይ ቀነኒሳ በቀለ የወርቅ እንዲሁም በ2011 እኤአ ላይ ደጀን ገብረመስቀል እንዲሁም በ2013 እኤአ ደጀን ገብረመስቀል  የነሐስ ሜዳልያዎች፤ በ2015 እኤአ ደግሞ ሐጎስ ገብረህይወት የብር ወስደዋል፡፡ በአጠቃላይ በዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና በ5ሺ ሜትር ወንዶች ለኢትዮጵያ ያስመዘገቡት በወንዶች 1 የወርቅ፤ 3 የብርና 3 የነሐስ ሜዳልያዎች ብቻ ናቸው፡፡
አትሌቲክስ ዊከሊና ትራክ ኤንድ ፊልድ ኒውስ በሰሯቸው የሜዳልያ ትንበያዎች በሁለቱም ፆታዎች ተመሳሳይ ሆነዋል፡፡ በሴቶች የወርቅ ሜዳልያውን ኬንያዊቷ ሄለን ኦቡሪ እንደምትወስድ ገምቶ የብር ሜዳልያውን ለገንዘቤ ዲባባ የነኘስ ሜዳልያውን ደግሞ ለአልማዝ አያና ሲሰጥ፤ በወንዶች ደግሞ የወርቅ ሜዳልያው ለሞ ፋራህ፤ የብር ሜልያው ለሙክታር ኢድሪስ እንዲሁም የነሐስ ሜዳልያ ለአሜሪካው ፖል ቼሌሞ እንደሚጠበቅ አመልክተዋል፡፡
በ10ሺ ሜትር
የአልማዝና የጥሩነሽ ፍጥጫ እንዲሁም ብቸኛው የወርቅ ሜዳልያ ለኢትዮጵያ በሴቶች ተጠብቋል፡፡
ባለፉት 15 ሻምፒዮናዎች በሴቶች 6 የወርቅ፣ 6 የብርና 4 የነሐስ ሜዳልያዎች በወንዶች 9 የወርቅ፣ 4 የብርና 5 የነሐስ ሜዳልያዎች
በ16ኛው የዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና ላይ ኢትዮጵያን በመወከል የሚሳተፉት አትሌቶች በሴቶች የዓለም ሪከርድ የያዘችውና የኦሎምፒክ ሻምፒዮኗ አልማዝ አያና፤ የምንግዜም የረጅም ርቀት ምርጥ ሯጭ ጥሩነሽ ዲባባ እና  ደራ ዲዳ ሲሆኑ በወንዶች አባዲ ሃዲስ፤ ጀማል ይመርና  አንዱአምላክ በልሁ ናቸው፡፡
በርግጥ በዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና ዋንኛው የኢትዮጵያ የበላይነት   በ10ሺ ሜትር እንደሆነ የሚታወቅ ነው፡፡ ከ1983 እኤአ ጀምሮ በተካሄዱ 15 የዓለም ሻምፒዮናዎች ኢትዮጵያ 9 የወርቅ ሜዳልያ በወንዶች እንዲሁም 5 የወርቅ ሜዳልያ በሴቶች በማግኘት ተሳክቶላታል፡፡ በዓለም ሻምፒዮና ላይ በ10ሺ ሜትር ወንዶች የመጀመርያው የሜዳልያ ድል የተመዘገበው በ1993 እኤአ በኃይሌ ገብረስላሴ በተገኘው የወርቅ ሜዳልያ ነበር፡፡ ከዚያም በኋላ በ1995፣ በ1997 እና በ1999 እኤአ ላይ ሶስት የወርቅ ሜዳልያዎችን አከታትሎ የተጎናፀፈውም ራሱ ኃይሌ ገብረስላሴ ነበር፡፡ በ1999 እኤአ ላይ አሰፋ መዝገቡ ተጨማሪ የብር ሜዳልያ ወስዷል፡፡ በ2001 እኤአ ላይ አሰፋ መዝገቡ የብርና ኃይሌ ገብረስላሴ የነሐስ፤ በ2003 እኤአ ቀነኒሳ በቀለ የወርቅ፣ ኃይሌ ገብረስላሴ የብርና ስለሺ ስህን የነሐስ፤ በ2005 እኤአ ላይ ቀነኒሳ በቀለ የወርቅ እና ስለሺ ስህን የብር፤ በ2009 እኤአ ቀነኒሳ የወርቅ እንዲሁም በ2011 እኤአ ላይ ኢብራሂም ጄይላን የወርቅ እና ኢማና መርጋ የነሐስ ሜዳልያዎችን እንዲሁም በ2013 እኤአ ኢማና መርጋ የነሐስ ሜዳልያ በመሰብሰብ የኢትዮጵያን የበላይነት ለረጅም ጊዜ አስጠብቀዋል፡፡ በአጠቃላይ ኢትዮጵያ በዓለም ሻምፒዮና የተሳትፎ ታሪኳ በ10 ሺ ሜትር በወንዶች 9 የወርቅ፣ 4 የብርና 5 የነሐስ ሜዳልያዎችን ሰብስባለች ማለት ነው፡፡ በ2013 እኤአ እና በ2015 እኤአ በሁለት የዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮናዎች የወርቅ ሜዳልያዎቹን ከኢትዮጵያ የነጠቀው ሞፋራህ ነው፡፡ በሌላ በኩል በ10ሺ ሜትር ሴቶች በዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና የኢትዮጵያ የመጀመርያው የሜዳልያ ድል የተመዘገበው በ1995 እኤአ ደራርቱ ቱሉ በተጎናፀፈችው የብር ሜዳልያ ነበር፡፡ በ1999 እኤአ ላይ ጌጤ ዋሚ የወርቅ፤ በ2001 እኤአ ደራርቱ ቱሉ የወርቅ፣ ብርሃኔ አደሬ የብር እና ጌጤ ዋሚ የነሐስ፤ በ2003 እኤአ ብርሃኔ አደሬ የወርቅ እና ወርቅነሽ ኪዳኔ የብር፤ በ2005 እኤአ ጥሩነሽ ዲባባ የወርቅ፣ ብርሃኔ አደሬ የብር እና እጅጋየሁ ዲባባ የነሐስ፤ በ2007 እኤአ ጥሩነሽ ዲባባ የወርቅ፤ በ2009እኤአ መሰለች መልካሙ የብርና ዉዴ አያሌው የነሐስ ሜዳልያዎች አግኝተዋል፡፡ በአጠቃላይ ኢትዮጵያ በዓለም ሻምፒዮና የተሳትፎ ታሪኳ በ10 ሺ ሜትር ከ4 አመት በፊት ምንም አይነት የሜዳልያ ውጤት ባይኖራትም በ2013 እኤአ ላይ ጥሩነሽ ዲባባ የወርቅ ሜዳልያ በመውሰድ ክብሩን መልሳለች፡፡ በላይነሕ ኦልጅራ ደግሞ ነሐስ ወስዳ ነበር፡፡ ይሁንና በ2015 እኤአ ኬንያ የወርቅ ሜዳልያ ነጥቃለች፡፡የብር ሜዳልያ የወሰደችው ደግሚ ገለቴ ቡርቃ ነበረች፡፡ በአጠቃላይ ባለፉት 15 የዓለም ሻምፒዮናዎች በሴቶች 10ሺ ሜትር 6 የወርቅ፣ 6 የብርና 4 የነሐስ ሜዳልያዎችን አግኝታለች፡፡
አትሌቲክስ ዊክሊ በሰራው ትንበያ በወንዶች የወርቅ ሜዳልያ ለሞ ፋራህ፤ የብር ሜዳልያው ለጄፍሪ ኪዋሪር እንዲሁም የነሐስ ሜዳልያው ለአባዲ ሃዲስ ሲገመት በሴቶች የወርቅ ሜዳልያው ለጥሩነሽ ዲባባ፤ የብር ሜዳልያው ለአልማዝ አያና እንዲሁም የነሐስ ሜዳልያው ለማትሰለፈው ገለቴ ቡርቃ ተጠብቋል፡፡ትራክ ኤንድ ፊልድ ኒውስ በበኩሉ በወንዶች የወርቅ ሜዳልያውን በተመሳሳይ ለሞ ፋራህ ሰጥቶ የብር ሜዳልያውን ለአባዲ ሃዲስ እንዲሁም የነሐስ ሜዳልያውን ለኬንያው ቤዳን ሙቹሪ ሲጠብቅ በሴቶች ደግሞ የወርቅና የብር ሜዳልያውን ጥሩነሽ ዲባባ እና አልማዝ አያና እንደሚያሸንፉ በመገመት የነሐስ ሜዳልያውን ለኬንያዋ አሊስ ንዋንዋ ሰጥቷታል፡፡
በማራቶን
በሴቶች ለኢትዮጵያ ከወርቅ ውጭ፤ የብርና የነሐስ ሜዳሊያ
ለታምራት ቶላ የወርቅ ሜዳሊያ ድል ብዙ ግምት አለ
ባለፉት 15 ሻምፒዮናዎች በሴቶች 1 የወርቅና 1 የነሐስ ሜዳልያዎች በወንዶች 1 የወርቅ 2 የብርና 3 የነሐስ ሜዳልያዎች
በ16ኛው የዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና ላይ ኢትዮጵያን በመወከል የሚሳተፉት አትሌቶች በሴቶች ማሬ ዲባባ (ሻምፒዮን)፤ ብርሃኔ ዲባባ፤ ሹሬ ደምሴና  አሰለፈች መርጋ ሲሆኑ በወንዶች ደግሞ ታምራት ቶላ፤  ፀጋዬ  መኮንንና  የማነ ፀጋዬ ናቸው፡፡
ኢትዮጵያ በዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና የተሳትፎ ታሪኳ በማራቶን ውድድር በሁለቱም ፆታዎች ሁለት የወርቅ ሜዳልያዎች ብቻ አስመዝግባለች፡፡ በወንዶች ማራቶን ኢትዮጵያ የመጀመርያ የሜዳልያ ድሏን በመጀመርያው የዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና በ1983 እኤአ ላይ ያገኘችው ከበደ ባልቻ ባስመዘገበው የብር ሜዳልያ ነበር፡፡ ከዚያ በኋላ በ2001 እኤአ ላይ ገዛሐኝ አበራ ብቸኛውን የወርቅ ሜዳልያ ድል አስመዘግቧል። በ2009 እኤአ በፀጋዬ ከበደ ፤በ2011 እኤአ በፈይሳ ሌሊሳ ሁለት የነሐስ ሜዳልያዎች፤  በ2013 እኤአ ሌሊሳ ዴሲሳ የብር ሜዳልያ እንዲሁም በ2015 በየማነ ፀጋዬ የነሐስ ሜዳልያ ተገኝቷል ፡፡በሴቶች ማራቶን ኢትዮጵያ በዓለም ሻምፒዮናው የመጀመርያ የሜዳልያ ድል በ2009 እኤአ ላይ አሰለፈች መርጊያ ያስመዘገበችው የነሐስ ሜዳልያ ሲሆን በ2015 እኤአ ላይ ማሬ ዲባባ የወርቅ ሜዳልያ ወስዳለች፡፡
 አትሌቲክስ ዊክሊ  በሰራው ትንበያ በወንዶች ማራቶን የኬንያ ዋንጂሩ የወርቅ ሜዳልያውን እንደሚወስድ ተገምቶ ታምራት ቶላ የብር ሜዳልያ እንዲሁም ፀጋዬ መኮንን የነሐስ ሜዳልያዎች እንደሚያገኙ የተጠበቀ ሲሆን በሴቶች ኤድና ኪፕላጋት ከኬንያ የወርቅ ሜዳልያውን እንደምታሸንፍ እንዲሁም ብርሃኔ ዲባባ እና ማሬ ዲባባ የብርና የነሐስሜዳልያዎች ተገምቶላቸዋል። በትራክ ኤንድ ፊልድ ኒውስ ትንበያ ደግሞ በሴቶች ምድብ ለባህሬኗ ዩሪስ ጅፕኪሪዊ የወርቅ ሜዳልያ፤ ለኢትዮጵየዊቷ ማሬ ዲባባ የብር ሜዳልያ እንዲሁል ለኬንያዋ ኤድና ኪፕላጋት የነሐስ ሜዳልያ ሲሰጥ በወንዶች ምድብ የወርቅ ሜዳልያው ለታምራት ቶላ፤ የብር ሜዳልያው ለዳንኤል ዋንጂሩ እንዲሁም የነሐስ ሜዳልያው ለፀጋዬ መኮንን ተገምተዋል፡፡