Administrator

Administrator

 ካንትሪሳይድ ሆቴልስ ግሩፕ የተባለው የስዊድን ሆቴል ከቅርንጫፎቹ በአንደኛው ለተወሰነ ጊዜ በማረፍ አገልግሎቱን የሚጠቀሙ የተኳረፉ ባለትዳሮች፣ በሆቴሉ ቆይታቸው ችግራቸውን የማይፈቱና በአንድ አመት ጊዜ ውስጥ ፍቺ በመፈጸም ትዳራቸውን የሚያፈርሱ ከሆነ ካሳ እንደሚሰጥ ማስታወቁ ተዘግቧል፡፡
በትዳር ውስጥ የሚፈጠሩ አለመግባባቶችንና ግጭቶችን በውይይት የመፍታት ባህልን የማዳበር ተልዕኮ ያነገበው ሆቴሉ፤ በተለያዩ ምክንያቶች የተኳረፉ ጥንዶች ከቅርንጫፎቹ ወደ አንደኛው ጎራ በማለት፣ እየተዝናኑ ችግራቸውን በውይይት እንዲፈቱና ትዳራቸውን ከመፍረስ እንዲያድኑ ምቹ ሁኔታን የሚፈጥር ሲሆን፣ በቆይታቸው ችግራቸውን መፍታት ካቃታቸውና በ1 አመት ጊዜ ውስጥ የሚፋቱ ከሆነ፣ ለተፋቺዎቹ የሁለት ቀን አዳር ሙሉ ወጪያቸውን በካሳ መልክ እንደሚሰጥ ቢቢሲ ዘግቧል፡፡
ሆቴሉ ይህንን ያልተመለደ አሰራር የቀየሰው ባለትዳሮች በመካከላቸው ግጭትና አለመግባባት ሲከሰት፣ ከመደበኛው ህይወታቸውና በግርግር ከተሞላው አለም ለተወሰነ ጊዜ በመውጣት ገለል ብለው እየተዝናኑ በትዳራቸው ጉዳይ ላይ በሰከነ መንፈስ እንዲመክሩና ትዳራቸውን ከአደጋ እንዲታደጉ ለማበረታታት ነው ተብሏል፡፡
ከሆቴሉ ቅርንጫፎች በአንደኛው የተወሰነ ጊዜ ቆይተው በመካከላቸው ያለውን አለመግባባት ለመቅረፍ ያልቻሉና ፍቺ የፈጸሙ ባለትዳሮች፣ ከሚመለከታቸው የመንግስት አካላት የተሰጣቸውን ህጋዊ ፍቺ መፈጸማቸውን የሚያረጋግጥ ሰነድ  ለሆቴሉ በማቅረብ የተጠቀሰውን የካሳ ክፍያ ማግኘት እንደሚችሉ ተነግሯል፡፡

 ታዋቂው የፊዚክስ ሊቅ ፕሮፌሰር ስቴፈን ሃውኪንግ፤ ቨርጂን ጋላክቲክ የተባለቺው መንኩራኩር ወደ ጠፈር ልታደርገው ባቀደቺው ታሪካዊ ጉዞ ከሚካተቱ መንገደኞች አንዱ ሆኖ ወደ ጠፈር እንደሚጓዝ በይፋ ማስታወቁን ዘ ኢንዲፔንደንት ዘግቧል፡፡
“ተሳክቶልኝ ይህቺን ምድር ለቅቄ ወደ ጠፈር ርቄ እጓዛለሁ ብዬ በህይወት ዘመኔ ሙሉ አንድም ቀን አስቤ አላውቅም፤ ቨርጂን ጋላክቲክ የተባለው የጠፈር ጉዞ ኩባንያ ባለቤት የሆነው ሪቻርድ ብራንሰን የጉዞው አካል እንድሆን ሲጋብዘኝ ሳላቅማማ ነው በደስታ ተውጬ ግብዣውን የተቀበልኩት” ብሏል ስቴፈን ሃውኪንግ፡፡ ምንም እንኳን ኩባንያው መንገደኞችን በማሳፈር ወደ ጠፈር የንግድ ጉዞ ለማድረግ ያቀደው ከስምንት አመታት በፊት ቢሆንም፣ በተለያዩ ሰው ሰራሽና ተፈጥሯዊ እንቅፋቶች ሳቢያ ዕቅዱ ለአመታት መጓተቱን ያስታወሰው ዘገባው፣ ስቴፈን ሃውኪንግን ያካትታል የተባለው የጠፈር ጉዞም በቅርቡ ይከናወናን ተብሎ እንደሚጠበቅ እንጂ ጉዞው የሚደረግበት ትክክለኛ ጊዜ አሁንም ይፋ አለመደረጉን አክሎ ገልጧል፡፡
ሶስቱ ልጆቹ በህይወቱ አይቶት የማያውቀውን ጥልቅ ደስታ እንዳጎናጸፉት የሚናገረው ስቴፈን ሃውኪንግ፣ በቅርቡ ወደ ጠፈር የሚያደርገው ጉዞ የተለየ ደስታን ይሰጠኛል ብሎ እንደሚያስብ መግለጹንም ዘገባው አመልክቷል፡፡

 ቻይና በማምረትም በመሸጥም አለምን ትመራለች

    ያለፈው የፈረንጆች አመት 2016 በአለማችን የመኪና ሽያጭ ታሪክ አዲስ ክብረ ወሰን የተመዘገበበትና ከፍተኛ ቁጥር ያላቸው መኪኖች የተሸጡበት እንደነበር የጠቆመው ቢዝነስ ኢንሳይደር ድረገጽ፣ በአመቱ 88.1 ሚሊዮን ያህል መኪኖች መሸጣቸውን ዘግቧል፡፡
በ2016 በአለማቀፍ ደረጃ የተመዘገበው የመኪኖች ሽያጭ መጠን በ2015 አመት ከነበረው ጋር ሲነጻጸር የ4.8 በመቶ እድገት ማሳየቱን የጠቆመው ዘገባው፣ የሽያጭ እድገቱ ባለፉት አራት አመታት ከተመዘገቡት ከፍተኛው እንደሆነም ገልጧል፡፡
በአመቱ 24.38 ሚሊዮን መኪኖችን በመሸጥ ከአለማችን አገራት ቀዳሚዋ ቻይና ስትሆን፣ ከአመቱ አለማቀፍ የመኪና ሽያጭ ገበያ የ13 በመቶ ድርሻን የያዘቺው አገሪቱ፣ ባለፈው አመት ከሸጠቻቸው የ3.2 ሚሊዮን መኪኖች ጭማሪ ማሳየቱንም ዘገባው አስረድቷል፡፡
ቻይና በአመቱ ከአለማችን አገራት ከፍተኛውን የመኪና ሽያጭ ለማስመዘገቧ በምክንያትነት ከሚጠቀሱ የተለያዩ ጉዳዮች መካከል በአነስተኛ መኪኖች ላይ የ50 በመቶ የታክስ ቅናሽ ማድረጓ አንዱ እንደሆነም ዘገባው አብራርቷል፡፡
በ2009 የፈረንጆች አመት ከተከሰተው አለማቀፍ የገንዘብ ቀውስ በኋላ በነበሩት አመታት፣ የአለማችን የመኪኖች ሽያጭ መሻሻል እያሳየ መቀጠሉንም አክሎ ገልጧል፡፡ ስታቲስታ የተባለው አለማቀፍ የመረጃ ትንተና ተቋም በበኩሉ፣ ባለፈው የፈረንጆች አመት 2016 በአለማቀፍ ደረጃ 72 ሚሊዮን ያህል የህዝብ ትራንስፖርት አገልግሎት የሚሰጡ የተለያዩ አይነት መኪኖች መመረታቸውን ይገልጻል፡፡
የአለማችን የመኪና ምርቱ በ2015 ከነበረው የአምስት በመቶ ያህል እድገት እንዳሳየ የጠቆመው ድረገጹ፣ በአመቱ 24 ሚሊዮን መኪኖችን ያመረተቺው ቻይና ከአለማችን አገራት በአንደኛነት መቀመጧንና ከአለማችን የህዝብ ትራንስፖርት አገልግሎት የሚሰጡ መኪኖች ምርት 34 በመቶውን ያህል እንደምትይዝ ገልጧል፡፡
ከቻይና ታላላቅ ትርፋማ የመኪና አምራች ኩባንያዎች መካከል ከታዋቂው የአሜሪካ መኪና አምራች ኩባንያ ጄኔራል ሞተርስ ጋር በጥምረት የሚሰራው ሲያክ ሞተር ኮርፖሬሽን እንደሚገኝበትም አክሎ ገልጧል፡፡

  ኢትዮጵያ ባለመረጋጋት ከአፍሪካ 10ኛ ደረጃ፤ ፊንላንድ በመረጋጋት ከአለም 1ኛ ደረጃ ይዘዋል ተብሏል

      ፈንድ ፎር ፒስ የተባለውና ተቀማጭነቱ በአሜሪካ የሆነው የጥናት ተቋም በቅርቡ ይፋ ባደረገው የ2017 የዓለማችን አገራት ያለመረጋጋት ደረጃ ሪፖርት መሰረት፣ ደቡብ ሱዳን ከአለማችን መረጋጋት የራቃትና የመፈራረስ ከፍተኛ ዕድል ያላት ቀዳሚዋ አገር ሆናለች፡፡
አስራ ሁለት ያህል ፖለቲካዊ፣ ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ቁልፍ አመልካቾችን መሰረት አድርጎ የአለማችንን አገራት የመፈራረስ ዕድል ተጋላጭነት ደረጃ የሚያስቀምጠው ተቋሙ፣ በ2017 ሪፖርቱ ካካተታቸው 178 የአለማችን አገራት ደቡብ ሱዳንን እጅግ በከፋ ሁኔታ ላይ የምትገኝ ሲል በቀዳሚነት አስቀምጧታል፡፡ ባለመረጋጋት ከደቡብ ሱዳን ቀጥሎ በቅደም ተከተላቸው እስከ አስረኛ ያለውን ደረጃ የያዙት የአፍሪካ አገራት ሶማሊያ፣ መካከላዊ አፍሪካ ሪፐብሊክ፣ ሱዳን፣ ዲሞክራቲክ ሪፐብሊክ ኮንጎ፣ ቻድ፣ ጊኒ፣ ናይጀሪያ፣ ዚምባቡዌ እና ኢትዮጵያ መሆናቸውንም ሪፖርቱ ገልጧል፡፡
በተቋሙ ሪፖርት መሰረት፤ እንደ አምናው ሁሉ ዘንድሮም በመረጋጋት ከአለማችን አገራት የአንደኛ ደረጃን የያዘቺው ፊላንድ ስትሆን፣ ኖርዌይ፣ ስዊዘርላንድ፣ ዴንማርክና አየርላንድ ይከተላሉ፡፡
ከፍተኛ ያለመረጋጋት ችግር ካለባቸው የአለማችን አገራት መካከል ሶማሊያ፣ መካከላዊ አፍሪካ ሪፐብሊክ፣ የመንና ሶርያ እንደሚጠቀሱ የገለጸው ሪፖርቱ፣ ከአምናው ደረጃቸው አንጻር የመረጋጋት ሁኔታቸው በከፍተኛ ሁኔታ ካሽቆለቆለባቸው የአለማችን አገራት መካከል ሜክሲኮ፣ ኢትዮጵያና ቱርክ እንደሚገኙበትና ኢትዮጵያ ባለመረጋጋትና ለመፈራረስ ተጋላጭ በመሆን ከአፍሪካ አገራት 10ኛ ደረጃ መያዟንም አመልክቷል፡፡
ተቋሙ አመታዊ ሪፖርቱን ማውጣት ከጀመረ 13 አመታት ያህል ቢሆነውም፣ ከአጠናን ስልቱ፣ ከሚዛናዊነቱና ሊገመቱ የሚችሉ ሁነቶችን ወይም ክስተቶችን ቀድሞ ከመተንበይ አቅሙ ጋር በተያያዘ በስፋት እንደሚተች ዘገባዎች ያመለክታሉ፡፡

  አለማቀፍ የሆቴሎች ኔት ወርክ የተሰኘው ተቋም፤እንግዶች የሰጧቸውን የግብረ መልስ አስተያየት መነሻ በማድረግ፣ ሒልተን አዲስ ሆቴልን “የኢትዮጵያ የአመቱ ምርጥ ሆቴል” ሲል ሽልማት አበርክቶለታል፡፡
በመላው ዓለም በአለማቀፍ ሆቴሎች የሚጠቀሙ ደንበኞች በሚሰጡት የአገልግሎት እርካታ አስተያየት፤ ከኢትዮጵያ ሒልተን ሆቴል ጥሩ መስተንግዶ እንዳለው መመስከራቸውን ተከትሎ የእውቅና ሽልማት እንደተበረከተለት፣ የሆቴሉ የማርኬቲንግና የህዝብ ግንኙነት ኃላፊ ወ/ሮ ሃበን ክልሞን ለአዲስ አድማስ አስታውቀዋል፡፡ ለሽልማቱ ሆቴሉ ያለው አለማቀፍ እውቅና አስተዋፅኦ እንዳበረከተ ኀላፊዋ አልሸሸጉም፡፡  
ባለፈው ዓመት በተደረገው የኢትዮጵያ ሆቴሎች የደረጃ ምዘና፣ሒልተን አዲስ ባለ 3 ኮከብ ደረጃ ማግኘቱ አይዘነጋም፡፡

  በደራሲና ጋዜጠኛ መልሰው በሪሁን የተሰናዳው ‹‹እኔ የሌለው እኔ›› የተሰኘ መፅሐፍ ሰሞኑን ለንባብ በቃ፡፡ መፅሀፉ ‹‹ክብ ታሪኮች››፣ ‹‹አበቃቀል›› እና ‹‹መብተክተክ›› በሚሉ ሶስት ዋና ዋና ክፍሎች የተከፈለ ሲሆን እነዚህ ሶስት ሀሳቦች በአንድም በሌላም መንገድ የሚገናኙና የሚሰናሰሉ በመሆናቸው ‹‹Tripod of life›› የሚለው ሃረግ እንደሚገልፃቸው ደራሲው በመግቢያው አስፍሯል፡፡
ሶስቱም ክፍሎች በሶስቱ ክብ ሀሳቦች የተሳሰሩ ፍልስፍናዊ ሀሳቦች ያሉበት፤ በመብተክተክ ሀሳቦችን የሚፈትሹ ናቸው ተብሏል፡፡ በመፅሀፉ ‹‹የኔ ፊርማ በታችም መስመር በላይም መስመር አለው››፣ ‹‹የፊት ቅርፅ እና እሳቤ››፣ ‹‹የማፍቀር አርኪ ገፅታ››፣ ‹‹የአባቴ ሱሪዎች›› የተሰኙና ሌሎችንም ወጎች አካትቷል፡፡ ደራሲው መልሰው በሪሁን በአሁኑ ወቅት በአማራ ክልል ቴሌቪዥን በጋዜጠኝነት እያገለገለ ይገኛል፡፡

 በደራሲ አበበ ዓለማየሁ የተፃፈውና በኩባና በኢትዮጵያ ህዝብና መንግስት መካከል ያለውን የግንኙነት ደረጃ ለኢትዮጵያ ህዝብ ያስተዋውቃል የተባለው ‹‹የማይረሳ ውለታ›› መፅሀፍ ዛሬ ጠዋት ከ2፡30 ጀምሮ በብሄራዊ ቴአትር አዳራሽ ይመረቃል፡፡
   መፅሀፉ በዋናነት በወራሪው የሶማሌ ጦር አገር ስትወረር አገራችንን ለመደገፍ የመጡትን የኩባ ወታደሮችና የከፈሉትን መስዋዕትነት እየዳሰሰ ኢትዮጵያውያን ተማሪዎች ኩባ ሄደው በመማር አገራቸውን እንዴት እያገለገሉ እንዳሉና የሁለቱ አገራት መንግስታት ህዝቦች ያላቸውን የጠበቀ የወዳጅነት ግንኙነት ያሳያል ተብሏል፡፡ አንድ የስነ ፅሁፍ ባለሙያም በመፅሀፉ ዙሪያ ዳሰሳ ያቀርባል ተብሏል፡፡ መፅሀፉ በ232 ገፆች ተቀንብቦ፣ በ100 ብር ለገበያ ቀርቧል፡፡ ደራሲው አቶ አበበ አለማየሁ ካሳ ኩባ ሄደው እንዲማሩ እድል ካገኙት የዘመኑ ተማሪዎች አንዱ እንደነበሩ
በመፅሀፉ ጀርባ ባሰፈሩት ማስታወሻ ገልፀዋል፡፡

    የሚከተለውን የፃፉልን እጓለ ገብረ ዮሐንስ ናቸው፡፡
“የከፍተኛ ትምህርት ዘይቤ” በሚለው መጽሐፋቸው ውስጥ ነው፡፡
በግሪክ ሜቶሎጂ የሚገኝ አንድ ትልቅ ተረት አለ፡፡
(ይህም ስለ ፕሮሚሴቭስ የሚነገረው ነው፡፡ ትልቅ ምሥጢር በውስጡ ደብቆአል፡፡ ፕሮሚሴቭስ በሚል አርእስት የቀድሞውን ተረት መሠረት በማድረግ፣ ኤስሂሎስ የሚባለው ትራጀዲን የፈጠረ ባለቅኔ፣ አንድ ትሪሎጂ - ማለት ሦስት ድራማዎች ጽፎአል፡፡ እሱን በመከተል ሸሊ ባይረን ጌቴ ጽፈዋል። የፕሮሚሴቭስ መንፈስ በአውሮፓ የመንፈስ ታሪክ ውስጥ መካከለኛውን መሥመር የያዘ ነው፡፡ አሁን የጠቀስናቸው ሰዎች በአውሮፓ የሥነ ጽሑፍ ጠፈር ላይ በጣም ጐልተው የሚታዩ ከዋክብት ናቸው፡፡)
የፕሮሚሴቭስ ተረት እንደሚቀጥለው ነው፡፡ ፕሮሚሴቭስ በከፊል አምላክ፣ በከፊል ሰው የሆነ ሕላዌ ነበር፡፡
በከፊል አምላክ እንደመሆኑ ዐሥራ ሁለቱ የግሪክ አማልክት በኦሉምቦስ ተራራ ሆነው ስለ ሰውና ስለ ዓለም አስተዳደር ሲመክሩ ይሰማ ነበር፡፡ በከፊል ሰው እንደመሆኑ የሰው ሥቃይና መከራ በጣም ያሳዝነው፣ ይጸጽተው ነበር፡፡ ሰው ቤት ንብረት ሳይኖረው በበረሃ፣ በጫካ፣ በዱር፣ በገደል፣ በዋሻ፣ በቁር፣ በሀሩር እንዲኖር ተፈርዶበት ነበር፡፡ ይህ መሆኑ አማልክት መክረው ዘክረው፣ ለሰው የዕውቀት ምንጭ የሆነውን ብርሃንን የሰጡት እንደሆን ከዕለታት ባንድ ቀን ሰጭነታቸውን ክዶ፣ በነሱ ላይ በመነሳት የሚያምፅ መሆኑን በመረዳት፣ ብርሃንን ከሰዎች ደብቀው ከማይደርሱበት ቦታ በመሠወራቸው ነው፡፡ በዚህ ምክንያት ሰዎች በጭለማና የርሱ ተከታይ በሆኑት ችግሮች ሥር ሲሰቃዩ ይኖራሉ፡፡
ይህ የሰዎች መራራ ዕድል ወገናቸው በሚሆን በፕሮሚሴቭስ ላይ ርህራሄ አሳድሮበት ብርሃንን አማልክት አርቀው ከደበቁበት ሰርቆ ለሰዎች ወስዶ ሰጠ፡፡ ያንጊዜ ማናቸውም ነገር ግልጽ ሆኖ ታያቸው፡፡ በብርሃን ምክንያት ጥበብና ማናቸውም የዕውቀት ስልት ስለተገለጸላቸው፣ ራሳቸውን ከገዛ ራሳቸው በተገኘው ዘዴ ለማስተዳደር ጀመሩ፡፡
ፕሮሚሴቭስን ግን ለሰዎች ብርሃንን ሰጥቶ፣ በጐ በመሥራቱ አማልክት ቀንተው፣ በብርቱ ስቃይ ይቀጣ ዘንድ አዳኝ ከማይደርስበት ገደል ላይ ከቋጥኝ ድንጋይ ጋር በሰንሰለት ተቆራኝቶ፣ አሞራ ለዘለዓለም እንዲበተብተው ፈረዱበት፡፡
*   *   *
ከፕሮሚሴቭስ ዕጣ -ፈንታ ይሰውረን፡፡ ይህ ፕሮሚሴቭስ የሰውን ዕድል ለማሻሻል የሚታገሉት የዕውቀት ሰዎች፣ የመምህራንና የሊቃውንት ምሳሌ ነው፡፡ እሱ ብርሃንን አማልክት ከደበቁበት ቦታ ወስዶ ለሰው እንዳበረከተ፣ የዕውቀት ሰዎችም ዕውቀት በመለኮታዊ ምሥጢርነት ከሰው ተደብቃ ስትኖር ሳለ በብዙ ትግል አግኝተው፣ ከገዛ ራሳቸው አሥርፀው የወገኖቻቸውን ዕድል ለማሻሻል ያበረክታሉ፡፡ ዋጋቸውም ሌላ ሳይሆን ስቃይ መከራ ነው፡፡ ለምሳሌ ያህል ሶክራቲስ በመርዝ ተገድሎአል፡፡ ጆርዳኖ ብሩኖ የጧፍ ቀሚስ ተጐናጽፎ በእሳት ተቃጥሎአል፡፡
እነዚህ ሰዎች እንደ ጧፍ መብራት ማለት ናቸው፡፡ ራሳቸው ነደው ተቃጥለው ያልቃሉ። ለሌሎች ግን ብርሃን ይሰጣሉ፡፡ የፕሮሜሴቭስ ምሳሌ አንድ ትልቅ ሕግ ጉልህ አድርጐ ያሳያል። ይህም “ዕውቀት በሥቃይ የሚገኝ ነው” (Learn through suffering) የሚል ነው፡፡  
ልጆቻችንን ይህን ለሌሎች ስንል መታገል፣ መሰዋት፣ ማድረግ እንደምን እናስተምር? ብርሃን የሚያመጡ ሰዎች ያስፈልጉናል፡፡
ዕውቀትን ለሀገር ለማጎናፀፍ የሚጥሩ መምህራን ያሹናል፡፡ የዕውቀት ብርሃን ለመጪው ትውልድ ታትሮ ለማለፍ ፣ ልብና ልቡና ይፈልጋል፡፡ አረፍ ብሎ ወዴት እያመራን ነው ብሎ መጠየቅን ግድ ይላል፡፡ ዕውቀት ከትምህርት ብቻ የሚገኝ አይደለም፡፡ ከኑሮአችን፣ ከልምዳችን፣ ከትግላችን እንጂ። ይህ ወረድ ብሎ አፈሩን መዳሰስን፣ ህዝቡን ማግኘትን፣ የልብ ትርታውን ማወቅን ይጠይቃል፡፡ ምን ጎደለው? ስለዚህ ጉዳይ ግንዛቤ አለ ወይ? በምን ዓይነት መንገድ የጎደለውን ዕውቀት ለማሟላት እችላለሁ? ማለትን ይጠይቃል፡፡ መንገዱን ካገኙ በኋላም፤ ጧት ማታ ሳይታክቱ መታተርን ይጠይቃል። ይህን ከልብ ካደረግን አገር መውደድ ገብቶናል፡፡ ያንድ ሰሞን ሞቅ ሞቅ ብቻ አገርን ከገባችበት ማጥ አያወጣትም፡፡ “ኦሆ በሀሊ፣ ያርጓጅ አናጓጅ፣ በደመቀበት ቦታ ሁሉ የሚያጨበጭብ አንድም የተለየ ነገር ለማስገኘት አይችልም” ይላሉ ዶክተር እጓለ፡፡ ሉቃስን በመጥቀስም እንዲህ ይሉናል። “ውሰብአ አቴናሰ ወእለ ይነግድ ኲሎሙ ህየ በእደ ትካዘ አልቦሙ ዘእንበለ ዳእሙ ለአፅምኦ ወነቢብ ዘሐዲስ”። አቴናውያን አዲስ ነገር ከመስማት ወይም ከመናገር በስተቀር ሌላ ምኞት አልነበራቸውም። ባለው ላይ ቆሞ አዲስ ነገር ለማግኘት የሚጣጣር ሰው ሁል ጊዜ ወደፊት ይሄዳል - ማለት ነው፡፡
እንደ አቴናውያን፤ በአለው ላይ ቆመን አዲስ ነገር ለማግኘት የምንጣጣር ከሆነ ወደፊት እንሄዳለን። ትምህርትንና ዕውቀትን መሰረቱ ያደረገ ትውልድ ከፈጠርን የራሱን ጥያቄ፣ የራሱን ነገ ራሱ ይወልዳል። የሚኖርበት ቤት ሲጠበው ቤቱን ራሱ አስፋፍቶ ይሰራዋል፡፡ ሁሉን እኛ እናድርግልህ ካልነው - ሁሉን ቀላቢ እንሁንለት ካልን፤ ዞሮ ዞሮ ተቀላቢ ትውልድ ነው የምናፈራው፡፡ ፈረንጆቹ እንደሚሉት - Spoon – Feeding mentality ይጠቀልለዋል - የአጉሩሱኝ አስተሳሰብ እንደማለት ነው፡፡
ለወጣቱ የመንግሥቱ ለማን ግጥም “መርፌ - ትሰራለህን” ማንበብና በዚያ አቅጣጫ መጓዝ የአባት ነው፡፡
በየትኛውም አቅጣጫ! ወጣቱ በሥነ ምግባር ረገድ፣ የሰውን ፀባይና ችሎታ በሚመረምር መልኩ አዕምሮው መታነፅ አለበት፡፡ ዕውቀትን መሰረት ሳያደርግ ለትግል ብቻ ብናዘጋጀው የፕሮፖጋንዳ ወይም የአጀንዳ ማስተላለፊያ አሸንዳ ቱቦ ነው የሚሆነው፡፡ ይህ በታሪክም የታየ ነው፡፡ በማህበራዊ ኑሮው የእያንዳንዱ መብትና ተግባር የሚጠበቅበት፣ “ሰው በንፁህ ተምኔቱ መሰረት በሰላም ተደስቶ የሚገኝበትን ሕግ” ይዞ መጓዝ እንዳለበት ሊረዳ ይገባል፡፡ ህይወት እንደ ጂኦሜትሪ ትምህርት በቀጥታ መሥመር የተሞላና የተለካ አይደለም፡፡ ቀላል ሂሳብም አይደለም፡፡ እንዴት እንደሚገነባ፣ ከራሱ ህይወት ተነስቶ እንዴት ለማደግ እንደሚችል፣ ትምህርትን ባሰላሰለ መልኩ ማጤን እንጂ “ሳይገሉ ጎፈሬ፣ ሳያረጋግጡ ወሬ” መሆን የለበትም፡፡ እስከ ዛሬ አጭር ተመልካች፣ አጭር ተጓዥ ሳናደርገው (Myopic) አልቀረንም፡፡ አጭር ግቦች አጭር ያደርጉናል!
አንድ ደራሲ እንደሚለው፤ “… የውጪ ጉዳዮችን ካገር ውስጥ ኃይሎች አሰላለፍ፣ ኢኮኖሚያዊ ችግሮችን ከጥበብ ሽግግርና ከውጪ ርዳታ፣ የቋንቋ መዘበራረቅና ጉራማይሌነትን ከባህላዊ ድቀት፣ የሐሳብ ነፃነትን ከጋዜጣ፣ ራዲዮና አጠቃላይ ውይይት ምህዳር መጥበብ ጋር…” የሚያነፃፅር ወጣትም ሆነ አዋቂ ያስፈልገናል፡፡
ወጣቱ አገሩን ያውቅ ዘንድ ጥልቅ አስተሳሰብ፣ ረዥም ርዕይና በግብረገብ የታነፀ ድፍረትና መስዋዕትነት ያስፈልገዋል፡፡ መጪውን አዲስ ዓመት እንዲህ እናስብ! የሀገራዊነት፣ የወገን አሳቢነት፣ የኢ-ራስ - ወዳድነት፣ የሁሉን - አውድም አስተሳሰብ አለመያዝ፣ ሁሉን - ረጋሚ ያለመሆን አመለካከት፣ ኢ-ፅንፋዊነት ወዘተ እንደ መርህም፣ እንደ ኑሮም ሊሰርፁበት ይገባል፡፡ አለበለዚያ አፋሮች እንደሚሉት፤ “አገሩን የማያውቅ ሰው፣ መሬትን እየረገጠ መሬትን ይረግማል” ይሆናል፡፡   

    የኢትዮጵያ አየር መንገድ ወደ ሲንጋፖር የቀጥታ በረራ አገልግሎት መጀመሩን አስታወቀ። አየር መንገዱ ባለፈው ረቡዕ ማታ ቦሌ ዓለም አቀፍ አየር መንገድ በሚገኘው ቢሮው በሰጠው መግለጫ፤ የቀጥታ በረራው በሳምንት አምስት ቀናትና በጣም ፈጣን በሆነ ሰዓት ከሲንጋፖር ወደ 53 የአፍሪካ አገራትና ከአፍሪካ አገራት ወደ ሲንጋፖር መብር የሚያስችል መሆኑን የአየር መንገድ ዋና ስራ አስፈፃሚ አቶ ተወልደ ገ/ማሪያም ለጋዜጠኞች አስታውቀዋል፡፡ ሲንጋፖር በአሁኑ ሰዓት በጣም ያደገች፣ 5 ሚ. ህዝብ ያላትና የዜጎቿ የነፍስ ወከፍ ገቢ ከፍተኛ ከሆኑ የዓለም አገራት በሶስተኛ ደረጃ ላይ የምትገኝ በመሆኗ የቀጥታ በረራ አገልግሎቱ በኢኮኖሚው እድገትም ሆነ የቱሪስትን ፍሰት ከመጨመር አኳያ ትልቅ ፋይዳ ያለው ነው ብሏል - ዋና ሥራ አስፈጻሚው፡፡   
ሲንጋፖር አየር መንገድ እንደ ኢትዮጵያ አየር መንገድ፤ የስታር አሊያንስ አባል በመሆኑ ሁለቱ አየር መንገዶች በመተባበር ትልቅ ስራ መስራት እንደሚችሉም አቶ ተወልደ ተናግረዋል። ሲንጋፖርን ጨምሮ አብዛኞቹ የእስያ አገሮች ወደ አፍሪካ ቀጥታ በረራ እንደሌላቸው የገለፁት ኃላፊው፤ ከጆሀንስበርግና ከኬፕታውን ወደ ሲንጋፖር የሚበር አንድ አየር መንገድ እንዳለና አፍሪካንና ሲንጋፖርን የሚያገናኝ ይሄኛው ሁለተኛው መስመር እንደሆነ ገልፀዋል፡፡
ሲንጋፖር ኢትዮጵያ ውስጥ ኤምባሲ እንደሌላት ተጠቅሶ፣ የሁለቱ አገራት ዲፕሎማሲያዊ ግንኙነት ምን ይመስላል በሚል ጥያቄ የቀረበላቸው ሥራ አስፈጻሚው፤ ”ሲንጋፖር እዚህ ኤምባሲ የላትም፤ የሲንጋፖር የኢትዮጵያ አምባሳደርም የሚቀመጠው ሲንጋፖር ነው፤ ምንም እንኳን ኤምባሲ እዚህ ባይኖራቸውም ሁለቱ አገሮች ጥሩ ዲፕሎማሲያዊ ግንኙነት አላቸው፤ የቀጥታ በረራው ሁለቱንም አገራት ተጠቃሚ ያደርጋል” ብለዋል፡፡
የኢትዮጵያ አየር መንገድ አለም አቀፍ መዳረሻዎች ከ95 በላይ የደረሱ ሲሆን ባለፈው ሰሞን ወደ ቼንዶ፣ መጋቢት መገባደጃ ላይ ቪክቶሪያ ፎልስ፣ ማዳጋስካር አንታናናሪቮ፣ እንዲሁም ኖርዌይ የቀጥታ በረራ ከፍቷል፡፡
ከሚያዝያ እስከ ግንቦት ባሉት ሁለት ወራት ውስጥ አምስት አዳዲስ የቀጥታ በረራ መስመሮችን መክፈቱንም አቶ ተወልደ ገ/ማርያም ገልፀዋል፡፡


  አባቱ ቦብ ማርሊ ሲሞት 2 ዓመቱ የነበረው የመጨረሻው ልጅ ዲሚያን ጁኒየር ጎንግ ማርሊ፤ ማክሰኞ ግንቦት 29 ቀን 2009 ዓ.ም በግዮን ሆቴል ኮንሰርት እንደሚያቀርብ አዘጋጆቹ አስታወቁ፡፡
አዘጋጆቹ ባለፈው ረቡዕ በራማዳ አዲስ ሆቴል በሰጡት ጋዜጣዊ መግለጫ፣ ዲሚያን 20 የሬጌ ሙዚቃ አባላትን ይዞ እንደሚመጣ ጠቅሰው፣ እዚህ ካሉት አርቲስት ዘለቀ ገሠሠና አርቲስት ጆኒ ራጋ ጋር ብላክ ኖት ሂፕ ሃፕን በማካተት፣ “ዋን ላቭ” የተሰኘ የዓመቱን ትልቅ ኮንሰርት እንደሚያቀርብ ገልጸዋል፡፡
በበርካታ የዓለም አገራት (ፓሪስ፣ ለንደን፣ ኬንያ፣ ደቡብ አፍሪካ፣ ሲሼልስ …) እየዞረ ኮንሰርት በማቅረብ ላይ የሚገኘው ዲሚያን፤ በ1976 (እ.ኤ.አ) ‹‹ሚስ ዎርልድ›› ከነበረችው አሜሪካዊት ሲንዲ ብረክስፓር የተወለደ ብቸኛው የቦብ ማርሊ ልጅ እንደሆነ ተገልጿል፡፡
በአገራችን ኮንሰርት ማካሄድ የተለመደው ቅዳሜና እሁድ ነው ያሉት አዘጋጆቹ፤ የዚህኛው ኮንሰርት ማክሰኞ መሆን ያልተለመደ ስለሆነ ቢራ ፋብሪካዎች ስፖንሰር ለማድረግ ፈቃደኞች አልሆኑም ብለዋል፡፡ የኮንሰርቱ መግቢያ ዋጋ 400 ብር፣ ቪአይፒ 600 ብር ሲሆን ቀድመው ለሚገዙ ውሱን ቲኬቶች በ350 ብር እንደሚሸጡ ተነግሯል፡፡
ዲሚያን፣ በሚመጣው ረቡዕ በኬንያ ኮንሰርት አቅርቦ በዚያው ወደ ሲሼልና ደቡብ አፍሪካ እንደሚሄድ ጠቅሰው፣ አዲስ አበባ የሚገባው ሰኞ ማታ እንደሆነ፣ በማግስቱ ማክሰኞ ኮንሰርቱን አቅርቦ፣ ‹‹አገሬ ናት›› የሚላትን ኢትዮጵያን እንደሚያይ፣ ረቡዕ ወደ ላሊበላ እንደሚጓዝ፣ ከተቻለም ታላቁን የሕዳሴ ግድብ ለማየት እንደሚሞክር፣ ከዚያ መልስ ወደ ገርጂ መሄጃ ኢምፔሪያል አደባባይ የሚገኘውን የአባቱን የቦብ ማርሊን ሀውልት እንደሚጎበኝና ዓርብ በ20 የአውሮፓ አገሮች ኮንሰርት ለማቅረብ ወደ ለንደን እንደሚጓዝ ገልጸዋል፡፡