Administrator

Administrator

· የህግ የበላይነት ከሌለ ዘመናዊ መንግሥት አይገነባም
            · የዳኝነት ተቋም ከፖለቲካ ተፅዕኖ ነፃ መሆኑን ማረጋገጥ አለበት
            · ፍትህ ሊያገኝ ወደ ፍ/ቤት የመጣ ሰው ሊንገላታ አይገባም
               አቶ ሞላ ዘገየ (የህግ ባለሙያ)

       የህግ የበላይነት ሲባል ምን ማለት ነው? በኛ ሃገርስ የህግ የበላይነት ተረጋግጧል ወይም እየተረጋገጠ ነው ለማለት የሚያስችል ደረጃ ላይ ተደርሷል?
የህግ የበላይነት ማለት በኔ እምነት በአንድ ሃገር ውስጥ ከፍተኛ የመንግስት ባለስልጣናትን ጨምሮ ሁሉም ዜጎች ከህግ በታች መሆናቸውንና በህግ ፊት እኩል መሆናቸውን የሚያመላክት ፅንሠ ሀሳብ ነው። ይሄን ስርአት መገንባት ዜጎች በሃይለኞች በተለይ ከምንም በላይ ሃይል ባለው መንግስት እንዳይጠቁ ዋስትና ይሠጣል፡፡ ያለ ህግ የበላይነት  ዘመናዊ  የመንግስት ስርአት አይገነባም። የህግ የበላይነት ከሌለ ዘመናዊ መንግስት የለም፡፡ በየትኛውም ሃገር መንግስት በህግ ካልተገደበ ትልቅ አደጋ ነው፡፡ የፈላጭ ቆራጭ ምንጩም ይሄው ነው። ስለዚህ የህግ የበላይነት ማለት ሁሉም ዜጎች በህግ ፊት እኩል መሆናቸውን ማረጋገጥ ማለት ነው፡፡
የህግ የበላይነት ለማረጋገጥ ደግሞ ተቋማት ያስፈልጋሉ፡፡ አንዱ ፍ/ቤት ነው፣ ከፍ/ቤት ጋር ደግሞ አቃቤቢ ህግ ፖሊስ፣ ማረሚያ ቤት፣ ጠበቆች እንዲሁም ሚዲያ መኖር አለባቸው፡፡ ፍ/ቤት በህገ መንግስቱ የተደነገገ ነፃነት አለው፡፡ አሁን ጥያቄው በእርግጥስ በተግባር ነፃነቱ ተከብሯል ወይ የሚለው ነው፡፡ በእርግጥ ህገ መንግስቱ መሬት ላይ ወርዷል ወይ? በኔ እምነት ይሄ አልተተገበረም፡፡
ይሄን በምሳሌዎች ሊያብራሩት ይችላሉ?
በሚገባ! ለምሣሌ እስከ ዛሬ ዳኞች እንዴት ነው የሚመለመሉት? የዳኞች አመላመልና አሿሿም ግልፅነት ይጎድለዋል፡፡ ሊሆን ይገባዋል ብዬ የማምነው አንድ ዳኛ የሚሆን ሰው መመልመል ያለበት በግል ነው፡፡ ለዳኝነት የሚያስፈልጉ መስፈርቶች በግልፅ ወጥተው እነዚህ መለኪያዎች በአደባባይ በሚዲያ ጭምር ማስታወቂያ ወጥቶ፣ እነዚህን መለኪያዎች አሟላለሁ የሚል ዜጋ ሁሉ አመልክቶ፣ በየደረጃው ተጣርቶ፣ መመዘኛውን የሚያሟሉ ጥቂቶች ብቻ ተመርጠው፣ አግባብ ባለው አካል አማካኝነት ለፓርላማ ቀርበው መሾም አለባቸው የሚል እምነት አለኝ፡፡
ለምሳሌ አንድ እጩ በተማረበት ት/ቤት፣ በሚኖርበት ሰፈር በግልፅ ፎቶግራፉ ተለጥፎ፣ ዜጎች በሰውየው ላይ አስተያየት መስጠት አለባቸው፡፡ ዜጎች በግልፅ በሰውየው ላይ ባህሪውን፣ አስተዳደጉን፣ ስነምግባሩን በተመለከተ አስተያየታቸውን ሊሠጡ ይችላሉ፡፡
በዚህ መንገድ መመልመሉ ሰውየው ላይ ህዝብ እምነት እንዲኖረው ያደርጋል፡፡ ሌላው የእድሜ ጉዳይ ነው፡፡ ዳኝነት ትልቅ ሃላፊነት ነው፡፡ በከፍተኛ ፍ/ቤት የሚሾም ሰው ከማንም የፖለቲካ ስልጣን የተለየ ከባድ ሃላፊነት ነው ያለበት፡፡ ከማንኛውም ባለስልጣን በተለየ የመጨረሻውን ፍርድ የሚሠጥ ዳኛ፣ የሞት ፍርድና ንብረትን የሚያሳጣ ፍርድ የሚወስን ዳኛን እንዲህ በቀላሉ መመደብ አይገባም። ባህሪ፣ እድሜ፣ የስራ ልምድ ተደማምረው ነው ዳኛ መሾም ያለበት፡፡ አሁን ባለው አሠራር ይሄን ልምድ አላይም፡፡ ግልፅ አይደለም፡፡
የእድሜ ጉዳይ የሚያመጣው ችግር ምንድን ነው?
ለምሳሌ በ20ዎቹ ውስጥ ያለን ሰው በዳኝነት አስቀምጦ፣ የትዳር ጉዳይ እንዲዳኝ ቢቀርብለት እንዴት ነው የሚዳኘው? ምን ልምድ አለው? አላገባም! አያውቀውም፤ እንዴት ነው ነገሮችን የሚገነዘበውና የሚያመዛዝነው? ይሄን ስል ስለ ትዳር ለመወሠን ሁሉም ዳኛ ማግባት አለበት ማለቴ አይደለም፡፡ እድሜ ለማመዛዘን ወሣኝነት አለው፡፡ እድሜ የልምድ ጥርቅም ነው፡፡
ሌላው አንድ አዲስ ወጣት ዳኛ፤ መጀመሪያ በረዳት ዳኝነት መስራት አለበት፡፡ ይሄን ስል አንዳንድ ከእድሜያቸው በላይ የበሠሉ ወጣት ዳኞች የሉም ማለቴ አይደለም፡፡ በኔ እምነት አንድ ሠው በዳኝነት መንበር ላይ ተቀምጦ ውሣኔ ለመስጠት፣ እድሜው ከ30 አመት በታች መሆን የለበትም ባይ ነኝ፡፡ 30 ዓመት የኖረ ሰው የህይወት ልምድ ይኖረዋል። በ30 ዓመቱ በረዳት ዳኝነት ተሹሞ በትንሹ ለ3 እና 4 ዓመት ቢሠራና በ35 አመቱ የዳኝነት ሃላፊነት ቢወስድ፣ የቀረበለትን ጉዳይ አመዛዝኖ መርምሮ መወሰን ይችላል የሚል እምነት አለኝ፡፡ እድሜን ሣነሳ ለእኔ የሚያሳስበኝ የማገናዘብ ጉዳይ ነው፡፡ እኔ በጥብቅና ስራ 28 አመቴ ነው እና ብዙ የምታዘባቸው ነገሮች ስላሉ ነው ይሄን የምለው፡፡
በሌላ በኩል ዳኞች በግልጽ መስፈርት ይለዩ የምልበት ምክንያት ደግሞ ይሄ አሁን ገለልተኛ አይደሉም የሚለውን ሃሜት ያስቀረዋል፤ እስካሁንም በግልፅ ቢሠራ የፍትህ አካሉ ለዚህ ሃሜት አይዳረግም ነበር፡፡
የዳኝነት ተቋሙ አሁን ባለው ሁኔታ ምን ያህል ከፖለቲካ ተፅዕኖ ነፃ ነው ብለው ያስባሉ?
ይሄ ወሳኝ ጉዳይ ነው፡፡ የዳኝነት ተቋም ነፃነቱን ማረጋገጥ አለበት፡፡ ከፖለቲካ ተፅዕኖ ነፃ መሆኑን ማረጋገጥ አለበት፡፡ ይሄን ማረጋገጡ የሚታየው ዳኞች በሚሰጡት ውሳኔ ላይ ነው፡፡ እኛ ሀገር ዳኝነቱ ነፃነት የለውም የሚለው ሃሜት የበረከተው በሚታዩ ነገሮች መነሻነት ነው፡፡
በአንዳንድ ሀገሮች ዳኞች ነፃነታቸውን የሚያስጠብቅ የሙያ ማህበር አላቸው፡፡ እኛ ሀገር የለም፡፡ ይሄ ማህበር ሊኖራቸው ይገባል፡፡ ማህበሩ ከምን ይጠብቃቸዋል ከተባለ አንደኛ በህሊናቸው ተመርተው ህግን መሰረት አድርገው በሰጡት ውሳኔ የሚደርስባቸውን ተፅዕኖ ለመከላከል ያስችላቸዋል፤ በሁለተኛ ደረጃ ደግሞ ጥቅማጥቅማቸውን ለማስከበር ይረዳቸዋል፡፡
ዳኞች የደህንነት ስሜት እንዲሰማቸው ከተፈለገ ይህ የሙያ ማህበር ያስፈልጋቸዋል፡፡ ዳኛ ህግን መሰረት አድርጎ ውሳኔ ለመስጠት ከውሳኔው በኋላ በስራዬ፣ በህይወቴ፣ በቤተሰቤ ምንም ነገር አይደርስብኝም የሚል መተማመን ሊኖረው ይገባል፡፡ ይሄ በራስ መተማመን ሊፈጠር የሚችለው በማህበር ተደራጅቶ፣ ራሱን መከላከል ሲችል ነው፡፡ ይሄ አሁን ባለው ሁኔታ እኛ ሀገር የለም። የህግ የበላይነትን ለማምጣት ከሆነ ጥረቱ አሁንም አንድ ገለልተኛ የሆነ ኮሚሽን በአስቸኳይ ተቋቁሞ የእስከ ዛሬውን የዳኞችን አሰራር የሚገመግምና አጠቃላይ የፍትህ ስርአቱን ችግሮች የፈተሸ ሪፖርት ማቅረብ አለበት፡፡ ነፃ የሆነ የማንኛውም የፖለቲካ ተፅዕኖ የሌለበት፣ ይህ ኮሚሽን ተቋቁሞ፣ ዳኝነቱ ነፃ የሚወጣበትን መፍትሄ የሚያፈላልግ፣ በጥናት ላይ የተመሰረተ ሪፖርት አቅርቦ በፖለቲካ ተፅዕኖ ስር የወደቀው የዳኝነት ስርአቱ ነፃ የሚወጣበት መፍትሄ መበጀት አለበት፡፡ የዳኝነት ተቋሙ በህገ መንግስቱ መሰረት በነፃነት ስራውን ሰርቷል ወይ? የሚለው ጥያቄ መልስ ማግኘት አለበት፡፡ ይሄ ካልሆነ የህግ የበላይነት ተረጋግጧል ወይ የሚለው  የሁልጊዜ ጥያቄ ሆኖ ይቀጥላል፡፡ የህግ የበላይነት ሊረጋገጥ የሚችለው ይህ ገለልተኛ ተቋም የሚያቀርበውን የምርመራ ሪፖርት መነሻ አድርጎ ሊወሰዱ በሚችሉ እርምጃዎች ብቻ ነው፡፡
ኮሚሽኑ ችግሩን ከእነ መፍትሄው ማቅረብ አለበት። አሁን ሁሉም ሰው ያሉትን ችግሮች በራሱ እይታ ነው የሚተረጉመው፡፡ ሊቋቋም ይገባዋል ብዬ የማምነው ገለልተኛ ኮሚሽን፤ የዳኞች አሿሿምን፣ የፖሊስ አሠራርን፣ የአቃቤ ህግ አሰራርን፣ የጠበቆች አሠራርን፣ የማረሚያ ቤት አሰራርን፣ በጥልቀት የሚፈትሽና ለአንዴና ለመጨረሻ ጊዜ አጠቃላይ የፍትህ ስርአቱን ከፖለቲካ ተፅዕኖ ነፃ የሚያወጣ መሆን አለበት፡፡ ይሄ በአስቸኳይ ካልተፈፀመ ስለ ህግ የበላይነት የሚነሡ ጥያቄዎች ይቀጥላሉ ማለት ነው፡፡
ብዙዎቹ የሃገሪቱ ችግሮች የሚመነጩት’ኮ በሃገራችን የህግ የበላይነት ባለመኖሩ ብቻ ነው፡፡ የህግ የበላይነት የለም ማለት ደግሞ ፍትህ የለም ማለት ነው፡፡ እስከዛሬ ድረስ ይህቺን ሃገር ያስተዳደሩና የገዙ መንግስታት አንዱ ትልቁ ችግራቸውና ድክመታቸው እንዲሁም ሊወቀሡበት የሚገባቸው ከፓርቲና ከመንግስት ተፅዕኖ ነፃ የሆኑ ዲሞክራሲያዊ ተቋማትን አለመፍጠራቸው ነው፡፡ አሁንም እነዚህ የሉም። ምናልባት ሙከራዎች ሊደረጉ ይችላሉ እንጂ ነፃ ተቋማት የሉም፡፡
ከዚህ በመነሣት ነው የሃገራችን ችግር የህግ የበላይነት አለመኖር ነው የምለው፡፡ የህግ የበላይነት የሌለው ደግሞ የፍትህ ተቋማት ከፖለቲካ ነፃ ሆነው መስራት ባለመቻላቸው ነው፡፡ ስለዚህ ይሄ በዚህ በሚቋቋመው ኮሚሽን አማካኝነት መጣራት አለበት። ደህንነቱን ከፖለቲካ ጫና ነፃ ማውጣት አለበት፡፡ የፍትህ አካሉ ለምንድን ነው ተደጋግሞ የሚወቀሠው የሚለው በአፋጣኝ የመጨረሻ ምላሽ ማግኘት አለበት።
ሰሞኑን 7ኛው የፍትህ ሣምንት መሪ ቃል፤ ‹‹የህግ የበላይነት ለዘላቂ ሠላምና ለህዝቦች አንድነት›› ይላል፤ ይሄ አስገራሚ ነው፡፡ ይሄንን ማረጋገጥ ያለበት ገለልተኛ ኮሚሽን ነው፡፡
ሌላው ኢትዮጵያ ውስጥ ብቻ ነው ዳኛ የተከበሩ ሲባል ከርሞ፣ አንድ ቀን ደግሞ ጠበቃ የሚሆነው። ይሄ ስህተት ነው፡፡ አንድ ጊዜ በዳኝነት ወንበር ላይ የተቀመጠ ሰው የሚሞተው እዚያው በዳኝነቱ ወንበር ላይ ነው እንጂ ዳኛ ሆኖ ወደ ጠበቃ መምጣት ለፍትህ አሠጣጡም ተገቢ አይሆንም፡፡ ፍትህ ይዛባል። አላማቸው ጠበቃ መሆን ስለሆነ ፍትህ ይዛባል። ከዚህ ጋር ተያይዞ የዳኝነት ኑሮ መሻሻል አለበት። ዳኛ ስለሚበላውና ቤተሠቡን ስለሚመግበው መጨነቅ የለበት፡፡ ሁሉም ሊሟላለት ይገባል፡፡ ሃሳቡ በሙሉ ዳኝነቱ ላይ መሆን አለበት፡፡ እኛ ሃገር ግን የምንታዘበው፤ የሞት ፍርድ የፈረደ ዳኛ፣ ከሰው ጋር ታክሲ ተጋፍቶ ሲሳፈርና በእግሩ ሲሄድ ነው፡፡ ይሄ መሆን የለበትም፡፡ የዳኞች ኑሮ በእጅጉ መሻሻል አለበት፡፡
እርስዎ እንደ ጠበቃ በዳኞች አካባቢ የሚታዩ ጉድለቶች ምንድን ናቸው ይላሉ?
በጣም ጠንቃቃና ችሎቱን ስነስርአት የሚያስይዙ ጎበዝ ዳኞች ያሉትን ያህል ዳኛ ይሁኑ ባለጉዳይ የማይለዩ፣ በአለባበሳቸውም ዳኛ የማይመስሉ ሰዎችም አሉ፡፡ በነገራችን ላይ በፍ/ቤቶች የአለባበስ መመሪያ መኖር አለበት፡፡ እኔ ከምታዘበው ነገር ከኔ ጀምሮ ችሎት ስንቆም ከረባት አናስርም፡፡ ይሄ ስህተት ነው። የአለባበስ መመሪያ የግድ አስፈላጊ ነው፡፡ በፍ/ቤት ስንቆም “የተከበሩ … ጌታዬ” የምንለው እኮ ግለሰቡን አይደለም፤ ተቋሙን ነው፡፡ እዚያ ተቋም ውስጥ ያለ ሰው ደግሞ ይሄን ክብር የሚመጥን ሆኖ መቅረብ አለበት፡፡ ሌላው ሳልናገር የማላልፈው በፍ/ቤቶች ያለው የመፀዳጃ ቤት ችግር፣ የካፍቴሪያ ችግር ነው። ዳኞቻችን ወደድንም ጠላንም ክብር ይገባቸዋል፤ በፓርላማ የተሾሙ የተከበሩ ሰዎች ናቸው፡፡ ይሄንን ክብራቸውን የሚመጥን አገልግሎት ነው በስራ ቦታቸው ማግኘት ያለባቸው፡፡ የላስቲክ ወንበር ላይ ተቀምጠው ልንመለከታቸው አይገባም። እኔ እንኳ ስለዚህ ነገር መናገር ከጀመርኩ ከዓመት በላይ ሆኖኛል፤ ግን ሰሚ የለም፡፡ ከፍ/ቤት በላይ ምን የሚከበር ተቋም ሊኖር ይችላል! የለም ስለዚህ ፍ/ቤቶች የሚገባቸውን ክብር የሚመጥን አደረጃጀትና አገልግሎት መስጫዎች ሊኖራቸው ይገባል፡፡
ሌላው የዳኞች ስነ ምግባር መታሰብ አለበት። አንዳንዶች ያመናጭቃሉ፣ ያልተገባ ንግግር ይጠቀማሉ፣ ሰዎችን ስሜታዊ ያደርጋሉ፤ እንዲህ ያሉ ዳኞች ሊታረሙ ይገባቸዋል፡፡
ሌላው በተደጋጋሚ የሚታየው ችግር የአሰራሮች አለመስተካከል፣ ደንበኞችን ማጉላላታቸው ነው። ከመቅረፀ ድምፅ ወደ ጽሑፍ ተገልብጦ ይቅረብ ይባልና የቀጠሮ ምልልስ ይፈጠራል፤ ይሄ ለፍትህ አሰጣጡ ተግዳሮት ነው፡፡ ሌላው የምታዘበው ነገር ባለጉዳይና ጠበቃ የሚመካከሩበት ቦታ የለም፡፡ ይሄ ትልቅ ጉድለት ነው፡፡ ፍ/ቤት አካባቢ የመመካከሪያ ቦታ ሊኖር ይገባል። በአጠቃላይ የፍ/ቤት ግቢዎች ለፍትህ አሰጣጡ አመቺ የሆኑ ነገሮች ተሟልተው የሚገኙባቸው አይደሉም፡፡ ይሄ አሳሳቢ ነው፡፡
ሌላው የፍ/ቤት ሰራተኞች ደንበኞች የማመናጨቅ፣ የመገፈታተርና የተለያዩ ችግሮች ይፈጥራሉ፤ ይሄ መታረም ያለበት ነው፡፡ ፍትህ ሊያገኝ ወደ ፍ/ቤት የመጣ ሰው ሊንገላታ አይገባውም፡፡

 ከዕለታት አንድ ቀን የዱር አራዊት አጠቃላይ ስብሰባ ያደርጋሉ፡፡ ሰብሳቢው የዱር አራዊት ሁሉ ሊቀመንበር አያ አንበሶ ነው፡፡ ስብሰባው እንዲኖር ያዘዘው ግን የሁሉም የበላይ የሆነው አምላክ ነው፡፡
አራዊቱ ሁሉ ንቅል ብለው ከጫካው መጥተዋል፡፡ አያ አንበሶ በነብሮ አማካኝነት የምዝገባ ቁጥጥር እንዲደረግ ጥብቅ ትዕዛዝ ሰጥቷል፡፡ የስብሰባ መቆጣጠሪያ ላይ ሁሉም ተገኝተው ኤሊ ግን አልመጣችም፡፡ የኤሊን መቅረት ለማጣራት የተወሰኑ አራዊት ተሰማሩ፡፡ ዝንጀሮና ጦጣ አንድ ላይ አገኟት፡፡
“እመት ኤሊ”
“አቤት”
“ከስብሰባው በመቅረትሽ የዱር አራዊት ሁሉ ተቀይመውሻል፤ ማንን ተማምና ነው? እያሉ ነው!”
“እኔ የተማመንኩት ተፈጥሮን ነው፡፡ እዚህ የድንጋይ መከላከያ ዋሻ ውስጥ ሆኜ ማን ይነካኛል?” አለች፡፡
“እሺ ይሄንን መልስሺን ለአምላክ እንነግራለን!” ብለዋት ይሄዳሉ!
አምላክ የኤሊን ነገር ሲሰማ “ትምጣና ፍርዷን ትስማ” አለ፡፡
ኤሊ የግዷን እየተንጓፈፈች መጣች፡፡
አምላክም፤
“ለፈፀምሺው ከፍተኛ ድፍረት አንድ ከባድ ፍርድ ይገባሻል፡፡ በዚህም የዱር አራዊት ሁሉ ትምህርት ሊያገኙ ይገባል፡፡ በዚህ መሰረት እመት ኤሊ ከዛሬ ጀምሮ እሸሸግበታለሁ ያልሺውን ድንጋይ ለብሰሽ ኑሪ! ይህ ህግ የማይሻር የማይለወጥ ይሁን” አለ፡፡
ብዙዎቹ የዱር አራዊቶች የፍርድ ማቃለያ ጠየቁላት፤ አንዳንዶቹ፤ “አውቃ ሳይሆን ተሳስታ ነው” አሉ፡፡
ከፊሎቹ፤
“የድንጋይ ዋሻ የመጨረሻው መጠለያዋ መስሏት ነው” አሉ፡፡
ሌሎቹ፤ “ስለ አምላክ ታላቅነት ያላት ዕውቀት ውሱን በመሆኑ ነው” አሉና ተማፀኑ፡፡ አምላክ ግን “ትምህርት ማግኘት አለባት” አለ፤ ኮስተር ብሎ፡፡ ከዚያን ጊዜ ወዲህ ኤሊ ዕድሜ ልኳን ድንጋይ እንደለበሰች ትኖራለች፡፡
*   *   *
በዚህም ሆነ በዚያ ከህግ መሸሽ ያስጠይቃል፡፡ ያስቀጣልም፡፡ ይግባኝ የሌለው ከባድ ቅጣት! ታስቦ፣ ወንጀል ልፈፅም ተብሎ፣ ሁነኛ ጥፋት ተደርጎ የተፈፀመ ድርጊት ነው! ማጣፊያው የሚያጥረውም ለዚህ ነው!
የየትኛውም ወገን የፖለቲካ ድርጅቶች እንዴት ትልቁን ስዕል (The Bigger Picture) ማየት እንደሚችሉ የገባቸው አይመስሉም፡፡ ብዙ ግትር የሚመስሉ የፖለቲካ ፓርቲዎች ተንኮታኩተዋል! ያሉ ሲመስላቸው የሉም፡፡ ተፅዕኖ ያሳደሩ ሲመስላቸው ዜሮ ግፊት ብቻ (Zero degree pressure) ነው ያላቸው፡፡ የመግባባት አቅማቸው ደካማ መሆኑ ብቻ ሳይሆን፣ ሁኔታዎችን ጠንቅቆ አውቆ የመጠቀም ዘዴ ከቶም የእነሱ ባለመሆኑ ነው፡፡ የድንጋይ ምሽግ ይዣለሁ ብሎ መተማመንና ማን ይነካኛል ማለት “ባለቤቱን ካልናቁ አጥሩን አይነቀንቁ” የሚለውን የጠዋት ተረት እየናቁ መውደቅ ነው፡፡ በወገናዊነት መረብ (በኔትዎርክ) አገር አይገነባም፡፡ ምክንያቱም ኔትዎርኩን ለመበጣጠስ ደፋ-ቀና ሲባል ሊሰራ የሚገባው ቁልፍ ቁልፍ ሥራ ሳይከናወን ይቀራል፡፡ አገር ወደ ኋላ ትቀራለች፡፡ የጉዳዮችን ቅደም ተከተል ማበጀት አንዱ ወሳኝ እንቅስቃሴ ነው፡፡ ይህም ብልህነትን ይጠይቃል፡፡ የህዳሴው ግድብ ዐቢይ ራዕይ መሆኑን ማንም አይስተውም፡፡ ሆኖም ከሥሩ መከናወን ያለባቸውን ሌሎች ቁልፍ ተግባራት የምንሸፍንበት ወይም ድክመታችንን  ላለማሳየት ጭምብል የምናጠልቅበት (masking one’s own weaknesses) ዘዴ መሆን የለበትም፡፡ በየአደባባዩ መሪ መፈክሮችን በማስገርና ጠላቶቻችን ያልናቸውን በማውገዝ፣ የራሳችንን ጥፋት ለመከለል መሞከር አንድ ቀን መጋለጡ አይቀሬ ነው፡፡ (They shout at most against the vices they themselves are guilty of እንዲሉ ፈረንጆቹ) የቡድነኝነትም ሆነ የመንገኝነት ስሜት ለሀገር አሉታዊ እንጂ አዎንታዊ ግብዓት አይፈጥሩም፡፡ ይልቁንም የገነባነውን ይሸረሽራሉ፡፡
ዶ/ር  አበራ ጀምበሩ፤ ‹‹ብቸኛ ሰው›› ጽሁፋቸው ላይ ፀሐፌ ትዕዛዝ ተፈራ ወርቅ ኪዳነወልድ ቅሬታቸውን ሲገልጡ፤ ‹‹የሥራ ቅንነት፣ ትጋትና ግለት እየቀዘቀዘ መሄድ፤ ተረስቶና ሞቶ የነበረው የቤተ - መንግሥት ተንኮል እንደገና ነፍስ ዘርቶ፣ ለብዙ መልካም ስራዎች እንቅፋት መሆኑ፣ የወገን የመከፋፈል መንፈስ በብዙ ሰዎች ማደሩ ነበር፡፡ ያም ሆነ ይህ ለመማር ዝግጁ ከሆንን አሁንም ጊዜ አለ፡፡ ውሃ ወቀጣውን እንተው፡፡ ሁልጊዜ የእነ እገሌ ጥፋት ነው ማለትን በርትተን እናስወግደው፡፡ ራሳችንን ለማዳን ኳሱን ወደ ሌሎች በመወርወር የተሻለ ፍሬ አናፈራም፡፡ ይልቁንም የወረወርነው ቀስት መልሶ ወደ ራሳችን ይመለስና ይወጋናል- ቡመራንግ (Boomerang)፡፡ አዳዲስ ሹማምንት ሥልጣን ላይ በተቀመጡ ቁጥር በአሮጌዎቹ ባለሥልጣናት ላይ እንከንና አቃቂር በማውጣት፣ የራስን ንፁህነት ለማሳየት መጣጠር ለጊዜው የዋሐንን ይማርክ እንደሆን እንጂ ዘላቂ የልማት መሳሪያ አይሆንም፡፡ ውስጣችን ከፊውዳላዊ አስተሳሰብ ሳይፀዳ ዲሞክራሲያዊነትን፤ ብሎም ፍትሐዊነትን ከዚያም ልማታዊነትን ማፍራት አይቻልም፡፡ በዘመነ በዛንታይን፣ የሮማን መንግሥት የካቶሊክ ስርዓት ፀሐፍት ሲተቹ፤ “The Holy Roman Empire is neither Holy nor Roman nor an Empire” ይሉ ነበር፡፡ ቅዱስ ሮማዊ ግዛት ተባለ እንጂ ቅዱስም አልነበረም፡፡ ሮማዊም አልነበረም፡፡ ግዛትም አልነበረውም ማለታቸው ነው፤ በስላቅ! ከውሃ ወቀጣው ግምገማ መውጣት አለብን፡፡ አዲስ አመለካከት እናምጣ፡፡ ለአስተሳሰብ ፈጣሪዎች (Thinkers) ዕድል እንስጥ፡፡ አለበለዚያ አሮጌው አመለካከት አረንቋ ውስጥ እንደተቸከልን እንቀራለን፡፡ ‹‹አንድን ግንድ አሥር ዓመት ውሃ ውስጥ ብታስቀምጠው አዞ አይሆንም›› የሚባለው ለዚህ ነው!

 በኢትዮጵያም ይሁን በሌሎች አገሮች ቅድመ እርግዝና የጤና ምርመራ አልተለመደም። ለዚህ እንደ አንድ ምክንያት የሚቆጠረው ደግሞ ቅድመ እርግዝና ምርመራ ሊደረግ ይገባዋል የሚለው እውቀት በብዙዎች ዘንድ አለመኖሩ ነው።
                ዶ/ር ድልአየሁ በቀለ የ
                ጽንስና ማህጸን ሕክምና እስፔሻሊስት
      ዶ/ር ድልአየሁ በቀለ በቅዱስ ጳውሎስ ሆስፒታል ሚሊኒየም ሜዲካል ኮሌጅ የጽንስና ማህጸን ሕክምና እስፔሻሊስትና መምህር ለዚህ እትም እንግዳ ናቸው። እሳቸው እንዳሉትም ሴቶች እርግዝናን ሲያስቡ አስቀድመው ሊዘጋጁባቸው  ከሚገባቸው ነገሮች መካከል ዋናው የጤና ጉዳይ ነው። አንዲት እናት ከማርገዝዋ በፊት ሙሉ የጤና ምርመራ ብታደርግ እጅግ በጣም ጥሩ እርምጃ ይሆናል። ነገር ግን ይህንን የሚያደርጉት እናቶች በኢትዮጵያም ብቻ ሳይሆን በሌሎችም በአደጉት አገሮች ጭምር በጣም ጥቂቶች ናቸው። ከዚህም ምክንያቶች አንዱ ከ50% በላይ እርግዝ ናዎች ሳይታቀዱ የሚከሰቱ መሆኑ ነው። ለእርግዝና እቅድ ሳይያዝለት የሚከሰት ሲሆን ደግሞ ምንም አይነት ቅድመ ዝግጅት ሳይደረግ መሆኑ እሙን ነው። በጤናው ፣በማህበ ራዊው ፣በኢኮኖሚው ጭምር ከእርግዝና ቀጥሎ ምን ሊደረግ ነው? የሚለው እርግዝና መኖሩ ከታወቀ በሁዋላ የሚደረግ ምክክር መሆኑ የተለመደ ነው። ነገር ግን ይህ በከፊል እናቶች በሰላም የእርግዝና ጊዜያቸውን ጨርሰው እንዲወልዱ ሲችሉ ብዙዎች ደግሞ የተለያዩ ችግሮች እንዲገጥማቸው ያደርጋል።
ዌብ ሜድ የተሰኘው ድረገጽ እንደሚያመለክተው ከእርግዝና በፊት የጤና ምርመራ ማካሄድ ለሚወለደው ልጅ ከመወለዱ በፊትና ከተወለደ በኋላም ለሚኖረው ጤናማ የሆነ ሕይወት እጅግ ጠቃሚ ነው። እርግዝናው ከተፈጠረ በሁዋላ የተለያዩ የጤና ችግሮች መኖራቸው ቢታወቅ ከጽንሱ ጋር በተያያዘ የእናትየውንም ሕይወት ውስብስብ ችግር ላይ ይጥላል።
ጤናን በተመለከተ ለእናትየው የሚደረገው ቅድመ ምርመራ እና ለሴትየዋ ከሚደረግላት ቅድመ ጥንቃቄዎች መካከል የሚከተሉት ይገኙበታል።
ሴትየዋ እርግዝናውን ሙሉ በሙሉ ጤነኛ ሆና እስከመጨረሻው ድረስ በሰላም ትደርሳለች ወይ የሚለውን አስቀድሞ ለማወቅ ይረዳል።
እርግዝና ሲመጣ ቀድሞ የነበሩ የጤና ጉዳዮች ካሉ እነዚያን ሕመሞች ተቆጣጥሮና አስተካክሎ ለእናትየውም ሆነ ለጽንሱ ችግር እንዳይገጥማቸው ቅድመ ጥንቃቄ ለማድረግ ይረዳል።
ቅድመ እርግዝና ባሉ ሕመሞች ምክንያት የሚወሰዱ መድሀኒቶች ከእርግዝናው ጋር አብረው መቀጠል የማይችሉ ከሆነ እነዚያን መድሀኒቶች ለማስተካከል ይረዳል። ብለዋል ዶ/ር ድልአየሁ በቀለ።
ብዙ ጊዜ እርግዝና ለምን ሳይታቀድ ይከሰታል የሚል ጥያቄ ሲነሳ በተለይም ባልና ሚስት ከሆኑ መቼም ይምጣ መቼ ...ትዳር የመሰረትነው ልጅ ለመውለድ ስለሆነ ስጋት የለብንም ሊሉ ይችላሉ። አንዳንድ ጊዜ ጋብቻ የፈጸሙ ሰዎች ሁሉ መውለድ አለባቸው ከሚል ድምዳሜ የሚደረስበት ሁኔታም ይታያል። አንዳንዶች በተለይም በኢትዮጵያ ማርገዝ ልቻል አልቻል ሳላውቅ ምርመራ ምን ያደርጋል የሚባልበት ሁኔታም ይስተዋላል። እንዲያውም አንዳንዶች እርግዝናው ገፍቶ እስኪታወቅ ድረስ ወደሐኪም ቤት መሔድ የማይፈልጉም አሉ። ነገር ግን ይህ ትክክል አይደለም እንደ ዶ/ር ድልአየሁ። ስለዚህ ሳያቅዱ መውለድ ባይለመድ እና ከእርግዝና በፊት ቅድመ እርግዝና ማድረግ ተገቢ መሆኑን ቢያውቁ ሁሉም ሴቶች ቅድመ እርግዝና የጤና ምርመራ ሳያደርጉ ማርገዝን አይደግፉም።
የተለያዩ ሕመሞች እርግዝናን ከዳር አድርሶ ልጅ ለመቀበል ሳያበቁ ወይ ጽንሱ እንዲቋረጥ አለዚያም በእናትየው ሕይወት ላይ አደጋ ሊያስከትሉ የሚችሉበት ሁኔታ አለ። ስለዚህም ቅድመ እርግዝና የህክምና ድጋፍ ከሚያስፈልጋቸው የህመም አይነቶች የሚከተሉት የተወሰኑት ናቸው።
የስኩዋር ሕመም፡-
አንዲት እናት ከማርገዝዋ በፊት የስኩዋር ሕመም ካለባት እና ስኩዋሩ በጥሩ ቁጥጥር ላይ ባለበት ሁኔታ ካላረገዘች የሚያመጣው ተጽእኖ አስከፊ ነው። ከስኩዋሩ ጋር በተገናኛ ጽንሱ ላይ ሊከሰት የሚችለው የአፈጣጠር ጉዳቶች ሁሉ አስቀድሞውኑ ቁጥጥርና ክትትል ከተደረገ ይቀንሳል።
ደም ግፊት፡-
አንዲት እናት የደም ግፊትዋ ጥሩ ቁጥጥር ላይ እያለ ካረገዘች ጽንሱም ላይ ሆነ እራስዋ ላይ ችግር የመፈጠሩ አጋጣሚ በጣም ይቀንሳል። አንዳንድ የደም ግፊት መድሀኒቶች በእርግዝና ጊዜ የማይመከሩ ሲሆን እነዚህ መድሀኒቶች በተለይም የመጀመሪያዎች የእርግዝና ሳምንታት ላይ ጽንሱ ላይ ችግር ያመጣል ተብሎ ስለሚታሰብ ቀድማ ለምርመራ ከቀረበች ግን ሁኔታዎች ሊስተካከሉ ይችላሉ።
የደም መርጋት፡-
የደም መርጋት ችግር ያለባቸው እናቶች ከሚወስዱዋቸው መድሀኒቶች ውስጥ የተወሰኑት በተለይም የመጀመሪዎች የእርግዝና ወራት ላይ ባይወሰዱ ይመከራል። ይህንን በአስፈላጊ መድሀኒት ለመለወጥ መወሰን የሚቻለው ግን እናትየው ቅድመ እርግዝና ምርመራ ለማድረግ ወደሆስፒታል ከሄደች ነው።
ቅድመ እርግዝና ምርመራ ማድረግ ተገቢ የሚሆንባቸው ሌሎችም ብዙ ሕመሞችና የሚወሰዱ መድሀኒቶች አሉ። ለምሳሌም እንደልብ ሕመም ያሉት የእናትየውንም ሕይወት አስጊ ሁኔታ ላይ የሚጥሉ በመሆናቸው ጥንቃቄ ማድረግ ይገባል። አንዳንድ ጊዜ እንዲያውም የታወቁ እና ከፍተኛ የህክምና ክትትል የሚደረግባቸው ሕመሞች ያሉአት ሴት እነዚህ ሕመሞች ያሉበት ደረጃ ስለመስተካከላቸው የሐኪም የይሁንታ መልስ እስኪያገኙ ድረስ እርግዝናው እንዳይከሰት ለማድረግ ጥንቃቄ የሚያስፈልግበት ሁኔታም ይኖራል።
ዌብ ሜድ የተሰኘው ድረገጽ እንደሚገልጸው ቅድመ እርግዝና የጤና ምርመራ በሚደረግበት ወቅት እናቶች ለሐኪማቸው ሊመልሱት የሚገባ የተለያየ ጥያቄ ይነሳል።
ከስነተዋልዶ ጤና ጋር የተያያዘ ጥያቄ፡-
የመጀመሪያው ከወር አበባ ጋር የተያያዘ ነው። ለመሆኑ የወር አበባ መቼ እንደሚመጣ የምታውቅበት ቀን መቁጠሪያ አዘጋጅታለች?
ስትጠቀም የነበረው የእርግዝና መከላከያ አይነት ምንድነው?
ከአሁን ቀደም በግብረስጋ ግንኙነት ምክንያት የሚተላለፍ በሽታ ታማ ታውቃለች?ወይንስ? የሚሉትና የመሳሰሉት ጥያቄዎች ትክክለኛ መልስ ማግኘት አለባቸው።
ከእርግዝና ጋር የተገናኙ ጥያቄዎች ፡-
ከዚህ በፊት የነበረው እርግዝና በምን ሁኔታ ተቋጨ? ተወልዶአል አልተወለደም? ውርጃ ነበረ? ...ወዘተ
ከዚህ በፊት ከእርግዝና በፊት፣ በእርግዝና ጊዜ ፣ከወሊድ በሁዋላ ተፈጥሮ የነበረ የመንፈስ ጭንቀት አለ?ወይንስ?
ከዚህ በፊት የተወለደ ልጅ ካለ የጤናው ጉዳይ ምን ይመስላል? የጤና እክል አለ?ወይንስ?
የመሳሰሉት ጥያቄዎች ሊነሱ ይችላሉ። እነዚህ ችግሮች ትክክለኛውን መልስ ካገኙ በድጋሚ እንዳፈጠሩ ጥረት ይደረጋል።
የጤና ሁኔታ ጥያቄዎች፡-
በጤና ጉዳይ የሚነሱ ጥያቄዎች ብዙ ናቸው። ነገር ግን ዋና ዋናዎቹ አስም ፣የደም ግፊት ፣ስኩዋር ፣የልብ ሕመም ፣የደም መርጋት የመሳሰሉት ሲሆኑ ከዚህ በተጨማሪም ከአሁን ቀደም የተደረጉ ቀዶ ሕክምናዎች ካሉ እና ከማደንዘዣ ጋር የተገናኘ አለመስማማት ከነበረ አስቀድሞ መታወቅ አለበት።
ሕክምና በሚደረግበት ወቅት ከሚሰጡ መድሀኒቶች አለመስማማት መኖር አለመኖሩም መረጋገጥ ይገባዋል። ከአሁን ቀደም ከምትወስዳቸው መድሀኒቶች ውስጥ የትኞቹ አለመስማማት ወይንም አለርጂክ እንደፈጠረባት ታውቆ ወደእርግዝናው ከመግባትዋ በፊት የሚስማማት መድሀኒት ካልተለወጠላት ወይንም መጠኑ ዝቅ ወይንም ከፍ ማለት የሚገባውም ከሆነ አስቀድሞ ካልተስተካከለ ለጽንሱ አስጊ ሊሆን ይችላል።
ከላይ የተጠቀሱትና ሌሎች ጥያቄዎችን ከእርግዝና በፊት ለሐኪሙ ማስረዳት የእናትየውንም ሆነ የጽንሱን ሕይወትና ሙሉ ጤነኛነት ለማረጋገጥ ያስችላል።

  በደቡብ ሱዳን ለአራት አመታት ያህል በዘለቀው የእርስ በእርስ ግጭት ሳቢያ በአገራቸው እና ከአገራቸው ውጪ የተፈናቀሉ የአገሪቱ ህጻናት ቁጥር ከ2 ሚሊዮን በላይ መድረሱን የተባበሩት መንግስታት ድርጅት ማስታወቁን አልጀዚራ ዘግቧል፡፡
በአገሪቱ በታህሳስ ወር 2013 በተቀሰቀሰውና ይህ ነው የሚባል ዘላቂ መፍትሄ ሳይገኝለት ለአመታት በቀጠለው የእርስ በእርስ ግጭትና የፖለቲካ ቀውስ ሳቢያ ከ1.8 ሚሊዮን በላይ የአገሪቱ ዜጎች ወደ ኡጋንዳ፣ ኬንያ፣ ኢትዮጵያና  ሱዳን እንዲሰደዱ ማድረጉን  የጠቆመው ዘገባው፤ ከእነዚህ ስደተኞች መካከልም ከ62 በመቶ ወይም ከአንድ ሚሊዮን በላይ የሚሆኑት ህጻናት መሆናቸውን ገልጧል፡፡
የእርስ በእርስ ጦርነቱ ሌሎች ከ1 ሚሊዮን በላይ ደቡብ ሱዳናውያን ህጻናትንም በአገራቸው ውስጥ ከመኖሪያ ስፍራቸው ማፈናቀሉን የተባበሩት መንግስታት ድርጅት የህጻናት መርጃ ድርጅትና የስደተኞች ጉዳይ ከፍተኛ ኮሚሽን ማስታወቃቸውን ዘገባው አስረድቷል፡፡
የእርስ በእርስ ግጨቱ ከጀመረበት ጊዜ አንስቶ በአስር ሺዎች የሚቆጠሩ ደቡብ ሱዳናውያን መገደላቸውን ያስታወሰው ዘገባው፤በአገር ውስጥ እና ከአገር ውጭ የተፈናቀሉ አጠቃላይ ዜጎች ቁጥርም 3.5 ሚሊዮን እንደሚደርስ አስታውቋል፡፡

መዝናኛው ኢንዱስትሪ የምታገኘውን ገቢ በከፍተኛ ሁኔታ ለማሳደግ ያቀደቺው ሳኡዲ አረቢያ፣ በአይነቱ ልዩ የሆነና የላስ ቬጋስን ያህል ስፋት ይኖረዋል የተባለውን ግዙፍ የመዝናኛ ከተማ ግንባታ ከስድስት ወራት በኋላ እንደምትጀምር መነገሩን ዘ ኢንዲፔንደንት ዘግቧል፡፡
ከመዲናዋ ሪያድ በስተደቡብ አቅራቢያ በሚገኝ 334 ስኩየር ኪሎ ሜትር ስፋት ያለው ስፍራ ላይ የሚቆረቆረውና በሚሊዮኖች የሚቆጠር ዶላር ወጪ የሚደረግበት ይህ ልዩ የመዝናኛ ከተማ፤ ለነዋሪዎችና ለውጭ አገራት ጎብኝዎች የተለያዩ የመዝናኛ፣ የስፖርትና የባህላዊ ትርዒቶች አገልግሎት እንደሚሰጥ ዘገባው አስታውቋል፡፡
እጅግ ማራኪ ፓርኮች እንደሚኖሩት የተነገረለት ይህ ግዙፍ መዝናኛ ከተማ፣ አለማቀፍ ተፈላጊነት እንደሚኖረውና ለአገሪቱ ከፍተኛ ገቢ ያስገኛል ተብሎ እንደሚጠበቅም ዘገባው አክሎ ገልጧል፡፡
ሳኡዲ አረቢያ አዳዲስ የገቢ አማራጮችንና የኢኮኖሚ መስኮችን በማስፋፋት ኢኮኖሚዋን ከነዳጅ ጥገኝነት ለማላቀቅ አቅዳ እየሰራች እንደምትገኝ የጠቆመው ዘገባው፤ የዚህ ጥረት አንዱ አካል የሆነው የግዙፍ የመዝናኛ ከተማ ግንባታ ፕሮጀክት በአራት አመታት ጊዜ ውስጥ ይጠናቀቃል ተብሎ እንደሚጠበቅም አመልክቷል፡፡

  የዚምባቡዌው ፕሬዚዳንት ሮበርት ሙጋቤ በተለያዩ ብሄራዊ፣ አህጉራዊና አለማቀፍ ስብሰባዎች ላይ በተደጋጋሚ ሲያንቀላፉ የሚያሳዩ ፎቶግራፎችንና ቪዲዮዎችን በማህበራዊ ድረ ገጾች የሚያሰራጩና በታላቁ መሪያችን ላይ የሚያላግጡ ሰዎች ተሳስተዋል፣ ሙጋቤ በስብሰባዎች ላይ አይናቸውን ገርበብ ስለሚያደርጉ ያንቀላፉ ይመስላሉ እንጂ በጭራሽ አይተኙም ሲሉ የፕሬዝዳንቱ ቃል አቀባይ አስተባብለዋል፡፡
“ታላቁ መሪያችን አይኖቻቸው የብርሃን ጨረሮችን የመቋቋም አቅም ስለሌላቸው በተደጋጋሚ አይኖቻቸውን ገርበብ ስለሚያደርጉና ጎንበስ ስለሚሉ ያንቀላፉ ይመስላሉ እንጂ፣ ብዙዎች በማህበራዊ ድረገጾች እንደሚያብጠለጥሏቸው ስብሰባቸውን አቋርጠው አያንቀላፉም” ሲሉ የፕሬዚዳንቱ ቃል አቀባይ ጆርጅ ቻራምባ፣ ሄራልድ ለተባለው የአገሪቱ መንግስት ጋዜጣ ተናግረዋል፡፡ እርጅና ተጫጭኗቸው አቅም ቢከዳቸውም በቀጣዩ አመት በሚካሄደው የአገሪቱ ፕሬዚዳንታዊ ምርጫ ለመወዳደር ታጥቀው መነሳታቸውንና ስልጣናቸውን እንደዋዛ ለማንም እንማያስረክቡ ያስታወቁት የ93 አመቱ ፕሬዚዳንት ሙጋቤ፤ ሰሞኑን ለአይን ህክምና ወደ ሲንጋፖር ማቅናታቸውንም ቢቢሲ ዘግቧል፡፡
ሙጋቤ የተባበሩት መንግስታት ድርጅት ጠቅላላ ጉባኤ፣ የአፍሪካ ህብረት የመሪዎች ስብሰባ እና የአረብ-አፍሪካ ጉባኤን ጨምሮ በበርካታ አህጉራዊና አለማቀፋዊ ስብሰባዎች ላይ እንቅልፍ ወስዷቸው የሚያሳዩ አስቂኝ ፎቶግራፎችና የቪዲዮ ምስሎች በተለያዩ ድረገጾች ላይ በስፋት ተሰራጭተው ይገኛሉ፡፡

    የተለያዩ የአፍሪካ አገራት ዜጎች የሆኑ ስደተኞችን አሳፍረው ከሊቢያ በመነሳት በሜዲትራኒያን ባህር ወደ አውሮፓ በመጓዝ ላይ በነበሩ ሁለት ጀልባዎች ላይ ሰሞኑን በደረሱ አደጋዎች በድምሩ 250 ያህል ስደተኞች መሞታቸውን ዘ ኢንዲፔንደንት ዘግቧል፡፡
ጀልባዎቹ ከመጫን አቅማቸው በላይ በርካታ ስደተኞችን አሳፍረው በመጓዝ ላይ ሳሉ ባለፈው እሁድና ሰኞ ከሊቢያ አቅራቢያ በሚገኙ የሜዲትራኒያን ባህር አካባቢዎች የመስጠም አደጋ እንዳጋጠማቸው የጠቆመው ዘገባው፣ ባለፈው እሁድ ከሊቢያ አቅራቢያ አደጋ በደረሰባት ጀልባ 163 ያህል ስደተኞች መሞታቸውን የተመድ የስደተኞች ኮሚሽን ባለፈው ማክሰኞ ማስታወቁን ገልጧል፡፡
የተወሰኑ ስደተኞች ከአደጋዎቹ ተርፈው የህክምና ክትትል እየተደረገላቸው እንደሆነ የጠቆመው ዘገባው፣ ለህልፈተ ህይወት ከተዳረጉት አፍሪካውያን ስደተኞች መካከል ህጻናት እንደሚገኙበትና የሴት ስደተኞች ቁጥርም በርካታ መሆኑን አመልክቷል፡፡
ባለፉት አምስት ወራት ብቻ ከ1 ሺህ 300 በላይ አፍሪካውያን ስደተኞች ከሊቢያ በመነሳት ሜዲትራኒያን ባህርን አቋርጠው ወደ አውሮፓ ለመግባት በአስቸጋሪ የጀልባ ጉዞ ላይ ሳሉ ለህልፈተ ህይወት መዳረጋቸውን ያስታወሰው ዘገባው፣ ባለፈው ሳምንት ብቻ ከ6 ሺህ በላይ አፍሪካውያን ስደተኞች ሜዲትራኒያን ባህርን አቋርጠው ወደተለያዩ የአውሮፓ አገራት መጓዛቸውን አስረድቷል፡፡
ባለፉት አምስት ወራት ብቻ ወደ አውሮፓ የተጓዙ አፍሪካውያን ስደተኞች ቁጥር ከ43 ሺህ በላይ መድረሱንም የተመድ የስደተኞች ኮሚሽን ባለፈው ማክሰኞ ባወጣው መግለጫ አስታውቋል፡፡

 ባለፈው ማክሰኞ…
ከወደ ዋይት ሃውስ አንድ አስደንጋጭና ያልተጠበቀ ዜና ወጣ…
አነጋጋሪው የአሜሪካ ፕሬዚዳንት ዶናልድ ትራምፕ ከዋይት ሃውስ ባወጡት መግለጫ፣ ከጆርጅ ደብሊው ቡሽ እስከ ክሊንተን፣ ከኦባማ እስከ ትራምፕ የአገዛዝ ዘመናት በአነጋጋሪነት የዘለቁትን ታዋቂውን የኤፍቢአይ ዳይሬክተር ጄምስ ኮሚን ከስራ ገበታቸው ማባረራቸውን አስታወቁ፡፡
እ.ኤ.አ በ2013 በያኔው የአሜሪካ ፕሬዚዳንት ባራክ ኦባማ ተመልምለው ኤፍቢአይን ለአስር አመታት በዳይሬክተርነት ሊመሩ የተመረጡት የ56 አመቱ ሪፐብሊካን ጄምስ ኮሚ፣ ገና ሶስት አመት ከመንፈቅ ብቻ እንደሰሩ፣ ባለፈው ማክሰኞ ባልተጠበቀው የትራምፕ ውሳኔ ታላቁን ተቋም ከመምራት ታገዱ፡፡
የትራምፕ አስተዳደር የኤፍቢአይ ዳይሬክተሩን ጄምስ ኮሚ ከስራ ለማባረር የወሰነው፣ በሄላሪ ክሊንተን የኢሜይል ቅሌት ዙሪያ ኤፍቢአይ ያከናወነውን ምርመራ በፊታውራሪነት የመሩት ሰውዬው፣ ምርመራውን በሚያከናውኑበት ወቅት በርካታ ስህተቶች መፈጸማቸውንና ብቁ አለመሆናቸውን በማረጋገጡ እንደሆነ አስታውቋል። ባለፈው የአሜሪካ ፕሬዚዳንታዊ ምርጫ የመጨረሻው ወሳኝ ምዕራፍ ላይ ድንገት ብቅ ብለው ባወጡትና በወቅቱ ከተቀናቃኛቸው ዶናልድ ትራምፕ ጋር እልህ አስጨራሽ የፍጻሜ ፍልሚያ ላይ የነበሩትን ሄላሪ ክሊንተንን የማሸነፍ ዕድል የከፋ አደጋ ላይ የጣለ በተባለው የዳግም የኢሜይል የቅሌት ምርመራ ውሳኔ ብዙዎችን አስደንግጠው ነበር - አነጋጋሪው ኮሚ፡፡
ሄላሪን አደጋ ላይ የጣለውን ይህን አደገኛ ውሳኔ ለመላው አለም ይፋ ማድረጋቸውን ተከትሎ፣ ተፎካካሪያቸው ዶናልድ ትራምፕ፣ ጠላቴን ድባቅ መታልኝ ያሏቸውን ጄምስ ኮሚን፣ ለፍትህ የቆመ ጀግና ሲሉ በአደባባይ አሞካሽተዋቸው ነበር፡፡ ይህ ከሆነ ከወራት በኋላ ታዲያ፣ እነሆ ባለፈው ማክሰኞ ዶናልድ ትራምፕ በአንድ ራስ ሁለት ምላስ ሆነው ብቅ አሉና፣ ያሞካሹትን ሰው መልሰው ለማዋረድና ለመወረፍ ደፈሩ- “ታላቁን ተቋም በቅጡ የመምራት ብቃት የሌለው ሰው ነው!... በአፋጣኝ ስራውን ይለቅ ዘንድ ፈርደንበታል!” በማለት፡፡
ጄምስ ኮሚ ከዳይሬክተርነታቸው መነሳታቸው በይፋ መነገሩን ተከትሎ፣ ዶናልድ ትራምፕ አስደንጋጩን ውሳኔ ለማሳለፍ ያነሳሳቸውን ሰበብና የውሳኔውን ስረ መሰረት በተመለከተ የተለያዩ አስተያየቶችና ትንተናዎች እየተሰጡ ይገኛሉ፡፡ ብዙዎች ውሳኔውን የሚያያይዙት ደግሞ ባለፈው የአሜሪካ ፕሬዚዳንታዊ ምርጫ ዘመቻ ወቅት ሩስያ ጣልቃ በመግባት ትራምፕን አግዛለች የሚለውን ጉዳይ በተመለከተ ኤፍቢአይ የጀመረውን ምርመራ የሚመሩት ጄምስ ኮሚ ከመሆናቸው ጋር ነው፡፡
ብዙዎች እንደሚሉት፤ ትራምፕ በኮሚ ላይ ውሳኔውን ያሳለፉት፣ በምርመራው ሂደት እኔን ሊጎዱ የሚችሉ ድርጊቶችን ሊፈጽሙ ይችላሉ ከሚል ስጋት በመነጨ ነው፡፡
ጄምስ ኮሚ ኤፍቢአይን በዳይሬክተርነት በመሩባቸው አመታት፣ የተሸናፊዋን ፕሬዝዳንታዊ ዕጩ የሄላሪ ክሊንተንን የኢሜይል ቅሌት ጨምሮ ቁልፍ የተባሉ የምርመራ ስራዎችን ያከናወኑ ሲሆን፣ ሰውዬው በሚይዟቸው አቋሞችና በሚያስተላልፏቸው አወዛጋቢ ውሳኔዎች በአንዳንዶች ብቁ መሪ በሚል ቢሞገሱም፣ ብልጣብልጥ በሚል የሚተቿቸውም አያሌ ናቸው፡፡
የሰውዬውን አወዛጋቢነት ከፍ ካደረጉት ሁነቶች መካከል አንዱ፣ ባለፈው የአሜሪካ ፕሬዚዳንታዊ ምርጫ የመጨረሻ ወሳኝ ምዕራፍ ሰሞን የሰሩት አነጋጋሪና አደገኛ የተባለ ያልተጠበቀ ድርጊት ነው። ሄላሪ ከትራምፕ ጋር በእልህ አስጨራሽ የምርጫ ፉክክር ውስጥ አልፈው ወደመጨረሻው ምዕራፍ በተሸጋገሩበት በዚያ ወሳኝ ወቅት ላይ ነበር፣ ጄምስ ኮሚ ድንገት ብቅ ብለው አነጋጋሪውን ውሳኔ ይፋ ያደረጉት፡፡
ኤፍቢአይ በሄላሪ ክሊንተን የኢሜይል አጠቃቀም ዙሪያ የጀመረውን ምርመራ ማስረጃ ስላልቀረበበት መዝጋቱን በሃምሌ ወር በይፋ ያስታወቁት ኮሚ፣ ሄላሪ ከትራምፕ ጋር ትንቅንቅ ላይ በነበሩበትና አንደኛቸው የሌላኛቸውን የቆየ ስህተትና የከረመ ድብቅ ጉድ እየፈለፈሉ በአደባባይ በማሳጣትና ደጋፊ በማሳጣት በተጠመዱበት ወሳኝ ጊዜ ላይ ብቅ ብለው፣ በሄላሪ የኢሜል ቅሌት ዙሪያ ጀምረን ትተነው የነበረውን ምርመራ እንደገና ከፍተነዋል አሉ፡፡
የፕሬዝዳንታዊ ምርጫ ፉክክሩ በተጧጧፈበትና ቀጣዩ የአሜሪካ መሪ ማን ይሆን የሚለው ጥያቄ መልስ ሊያገኝ የ11 ቀናት ዕድሜ ብቻ በቀረበት በዚያ ወሳኝ ወቅት ይፋ የተደረገው ድንገተኛው የኮሚ መግለጫ፣ ሄላሪንና ደጋፊዎቿን በድንጋጤ ክው ሲያደርግ፣ ትራምፕንና ደጋፊዎቹን አስፈነጠዘ። ጄምስ ኮሚ በወሳኝ ወቅት ላይ አጉል ሴራ ይዘው ከተፍ ያሉ መሰሪ ተብለው በሄላሪ ሰዎች ሲብጠለጠሉ፣ በትራምፕ ሰዎች ደግሞ ለእውነት ተሟጋች ድንቅ ባለሙያ ተብለው ተወደሱ፡፡
የኮሚ አነጋጋሪነት የሚጀምረው የአሜሪካ የፍትህ ሚኒስቴር ከፍተኛ ባለስልጣን በነበሩበት በጆርጅ ደብሊው ቡሽ የስልጣን ዘመን ነው፡፡ በወቅቱ ከኤሌክትሮኒክ ቁጥጥር ፕሮግራም ጋር በተያያዘ የሚያራምዱት አቋምና የሚያስተላልፉት ውሳኔ ብዙዎችን ያስገርም እንደነበር ይነገራል፡፡ ይህም ብቻ አይደለም፣ በቀድሞው የአሜሪካ ፕሬዚዳንት ቢል ክሊንተንና በሞኒካ ሊዊንስኪ ቅሌት ውስጥም የጄምስ ኮሚ ስም አብሮ ሲነሳ የሚኖር የአገሪቱ አነጋጋሪ የቅሌት ታሪክ አካል ነው፡፡
ጄምስ ኮሚ ባለፈው ረቡዕ ለኤፍቢአይ በጻፉት የስንብት ደብዳቤ፣ ትራምፕ ለምን ይህን ውሳኔ አስተላለፉብኝ የሚለውን ጉዳይ በማጣራት የማጠፋው ጊዜ አይኖረኝም ብለዋል፡፡

   ከደርባ ሲሚንቶ በስተቀር ከግሉ ዘርፍ ከአፍሪካ ልማት ባንክ ብድር ወስዶ የሚሰራ ድርጅት እንደሌለ የተገለፀ ሲሆን፣ ባንኩ ከግል ኢንቨስተሮች ጋር ለመሥራት ፈቃደኛ መሆኑን አስታውቋል፡፡
የአፍሪካ ልማት ባንክ ም/ፕሬዚዳንት፤ የግል፣ የመሰረተ ልማትና የኢንዱስትሪ ዘርፍ ኃላፊ ሚ/ር ፒየር ጉስሌይን፣ በኢትዮጵያ ለ3 ቀን ያደረጉትን ጉብኝት አስመልክተው ባለፈው ማክሰኞ በራዲሰን ብሉ ሆቴል በሰጡት ጋዜጣዊ መግለጫ፣ ከመንግሥት ከፍተኛ ባለሥልጣናት፣ ከገንዘብና ኢኮኖሚ ልማት፣ ከኢንዱስትሪና ከንግድ ሚኒስትሮች ጋር፣ እንዲሁም የግል ዘርፉን ጨምሮ ከሚመለከታቸው ባለድርሻ አካላት ጋር ያደረጉት ውይይት ፍሬያማ እንደነበር ገልጸዋል፡፡
ሚ/ር ጉስሌይን፤ ድርጅታቸው በ2001 ዓ.ም ለደርባ ሲሚንቶ 55 ሚሊዮን ዶላር ያበደረ ብቸኛው የግል ባንክ መሆኑን ጠቅሰው፣ ደርባን ሲሚንቶን ሲጎበኙ፣ ጥራት ባለው እንቅስቃሴውና ለአህጉሩ የኢኮኖሚ ዕድገት በሲሚንቶ አቅርቦት እያደረገ ባለው አስተዋጽኦ መርካታቸውን ገልፀዋል፡፡
ሌሎች የግል ኢንቨስተሮች ከባንኩ ጋር የማይሰሩትና የማይበደሩት፣ ባንኩ፣ ለግሉ ዘርፍ እንደሚያበድር ግንዛቤው ስለሌላቸው እንደሆነ ጠቅሰው፣ “በተለይ በኤክስፖርት ዘርፍ ከተሰማሩ የግል ኢንቨስተሮች ጋር ለመስራት ገንዘብ አዘጋጅተን እየተጠባበቅን ነው፤ ኑ አብረን እንሥራ!” በማለት ጋብዘዋል፡፡
ም/ፕሬዚዳንቱ በኢትዮጵያ ስላደረጉት ጉብኝት በሰጡት መግለጫ፣ ተደጋጋሚ ድርቅ፣ ዓለም አቀፍ የምርት ፍላጎት መቀነስና የሸቀጦች ዋጋ መውደቅ ቢያጋጥማትም፣ ኢትዮጵያ ጠንካራና እውነተኛ አጠቃላይ የአገር ውስጥ ምርት (ጂዲፒ) ዕድገት ስላሳየች፣ የትራንስፎርሜሽን እቅዷን ታሳካ ዘንድ ባንኩ፣ በኢትዮጵያ የሚያደርገውን ድጋፍ ይቀጥላል ብለዋል፡፡
“ባንኩ፣ ለአፍሪካ ያለው አመለካከት፣ ቅድሚያ በሚሰጣቸው አምስት ስትራቴጂዎች ይጠቃለላል” ያሉት ሚ/ር ጉስሌይን፣ “እነሱም፣ አፍሪካን የመብራትና የኃይል ተጠቃሚ ማድረግ፣ አፍሪካን መመገብ፣ አፍሪካን በኢንዱስትሪ ማበልጸግ፣ አፍሪካን አንድ ማድረግና የአፍሪካን ህዝብ ኑሮ ጥራት ማሻሻል ነው” ብለዋል፡፡
የአፍሪካ ልማት ባንክ ከኢትዮጵያ መንግሥት ጋር መስራት የጀመረው ከ42 ዓመት በፊት በ1975 ሲሆን እስከ አሁን ወጪያቸው በአጠቃላይ 4.6 ቢሊዮን ዶላር የሆነ 130 ፕሮጀክቶች (በመሰረተ ልማት፣ በኃይል፣ በውሃና ሳኒቴሽን) በማህበራዊ፣ በእርሻና በግሉ ዘርፍ ተከናውነዋል፡፡ ባንኩ፣ በአሁኑ ወቅት በ2 ቢሊዮን ዶላር 26 ፕሮጀክቶችን ተግባራዊ እያደረገ መሆኑ ታውቋል፡፡
ባንኩ፣ ከኢትዮጵያ ጋር ባለው ተሳትፎ አመርቂ ውጤት እየተመዘገበ መሆኑን የጠቀሱት ም/ፕሬዚዳንቱ፤ ኢትዮጵያና ጅቡቲን ለሚያገናኘው ስትራቴጂያዊ የኃይል አቅርቦት፣ ኢትዮጵያ - ኬንያን ለሚያገናኘው የመንገድ ፕሮጀክት፣ ለገጠር የኤሌክትሪክ አቅርቦትና መቀሌን ከዳሎል ለሚያገናኘው የኃይል ማሰራጫ መስመር፣ ባንኩ፣ 900 ሚሊዮን ዶላር ኢንቨስት ማድረጉን ተናግረዋል። እንዲሁም ባንኩ፣ የምስራቅ አፍሪካን የኃይል ፕሮጀክት እየደገፈ ነው፡፡ እነዚህ ተግባራት፣ የገጠርና የከተማ ቤቶች፣ የኢንዱስትሪ ዞኖች፣ የማዕድን ማዕከላት ኤሌክትሪክ እንዲያገኙ ማስቻል፣ አፍሪካን ብርሃናማ ማድረግና ለአፍሪካ ኃይል (ፓወር አፍሪካ) ቅድሚያ መስጠት ይሆናል ተብሏል፡፡
አፍሪካን አንድ ማድረግ ወይም ማስተሳሰር በሚለው የባንኩ ስትራቴጂ፣ በትራንስፖርት ዘርፍ አገራዊና አኅጉራዉ ትስስርን ለመፍጠር ለምሳሌ የኢትዮ - ኬንያ ትራንስፖርት ኮሪደር ፕሮጀክት፣ የኢትዮጵያ አየር መንገድና የቦሌን አለም ዓቀፍ አየር ማረፊያ ደረጃ ለማሳደግ፣ ለበርካታ መንገዶች መገንቢያና ማደሻ፣ ባንኩ አንድ ቢሊዮን ዶላር ኢንቨስት ማድረጉ ታውቋል፡፡
የእርሻውን ዘርፍ ለመደገፍና ለማዘመን፣ 7, 000 ሄክታር የሚሸፍነውንና 77 ሚሊዮን ኪዩቢክ የመያዝ አቅም ያለውን የካጋ መስኖ ፕሮጀክት፣ በእርሻው ዘርፍ ዝናብ ላይ የሚታየውን ጥገኝነት ለመቀነስና የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ፣ ባንኩ ለኢትዮጵያ 630 ሚሊዮን ዶላር ድጋፍ ማድረጉ ታውቋል። እንዲሁም የኢትዮጵያን የኢንዱስትሪ አቅም ለማጎልበት በተለይም በሲሚንቶ ምርትና በማዕድን ዘርፍ 160 ሚሊዮን ዶላር በብድር ተሰጥቷል፡፡ እንዲሁም ባንኩ፣ ለውሃ አቅርቦትና ለሳኒቴሽን 340 ሚሊዮን ዶላር፣ ለበጀት ድጎማ፣ ለማኅበራዊ አገልግሎት፣ ለትምህርት፣ ጤናና ሌሎች መሰረታዊ አገልግሎቶችን ለማሻሻልና ለመደገፍ 1.2 ቢሊዮን ዶላር ኢንቨስት ማድረጉ ተገልጿል፡፡ 

 መሰረቱን በአሜሪካ አገር ካሊፎርኒያ ከተማ ውስጥ ያደረገና በአራት ኢትዮጵያውያን ባለሙያዎች የተቋቋመው ‹‹አሪፍ ዘፈን›› የቴክኖሎጂ ኩባንያ፣ የኢንተርኔት አልበም ሽያጭ በቴዲ አፍሮ አዲስ አልበም መጀመሩን አስታወቀ፡፡
የኩባንያው የማርኬቲንግና ህዝብ ግንኙነት ኃላፊ ወ/ሪት ምዕራፍ ክፍሌ ለአዲስ አድማስ እንደገለጸችው፤ ኩባንያቸው  በአይነቱ አዲስ የሆነውን ይህንን ቴክኖሎጂ ወደ አገር ውስጥ በማምጣት፣ ህብረተሰቡ ተጠቃሚ እንዲሆን ለማድረግ በማሰብ ወደ ሥራው ገብተናል ብላለች፡፡ ኩባንያው ከኢትዮ ቴሌኮም ጋር ባደረገው የሥራ ስምምነት መሰረት፣ አገልግሎቱን ለሚፈልጉ ደንበኞች ከስልካቸው ሂሳብ ላይ ተቆራጭ በማድረግ አገልግሎቱን እንዲያገኙ ለማድረግ የሚያስችል አሠራር መጀመሩን ወ/ሪት ምዕራፍ ተናግራለች፡፡ እንደ ኃላፊዋ ገለጻ፤ ከገቢው 40 በመቶ የሚሆነው ለኢትዮ ቴሌኮም የሚከፈል የአገልግሎት ክፍያ ሲሆን ከቀሪው 60 በመቶ ላይ ቫትና የሾርት ኮድ ክፍያ ተቀናሽ ሆኖ ቀሪው ለባለመብቱ አርቲስት ተከፋይ ይሆናል፡፡ የአልበሙን ሽያጭ አርቲስቱ እራሱ በኢንተርኔት የሚከታተል ሲሆን የተሸጠውን ዘፈን መጠን፣ የተሸጠበትን ጊዜና ሰዓት ሁሉ በቀጥታ መከታተል የሚያስችል መሆኑ አሰራሩን ተመራጭ ያደርገዋል ብላለች፡፡  የአሰራር ሲስተሙ ደንበኛው በግዥ ያገኘውን ዘፈን ለሌላ 3ኛ ወገን ለማስተላለፍ እንዳይችል በሚያግድ መልኩ የተበጀ ሲሆን ይህም የቅጂ መብትን በማስከበሩ ረገድ ከፍተኛ ጠቀሜታ ይኖረዋል ብላለች፡፡ ለተጠቃሚውም ከአንድ አልበም ላይ የሚፈልገውን ሙዚቃ ብቻ መርጦ ለመግዛት የሚያስችል ከመሆኑ ባሻገር የሚፈልጋቸው ዘፈኖች በአንድ ቦታ ላይ (ጥቅል ውስጥ) ተሰባስበው መቀመጣቸው ለአጠቃቀም ምቹ ሁኔታን ስለሚፈጥር ተመራጭ ያደርገዋል ስትል አስረድታለች፡፡  
በአዲሱ የቴዲ አፍሮ አልበም ወደ ሥራ የገባው አዲሱ “አሪፍ ዘፈን” አፕሊኬሽን፤ የቅጅ መብትን በማስጠበቅና አድማጭም ጥራት ያለውን ትክክለኛ ክፍያ የተፈፀመበትን የሙዚቃ ሥራ መጠቀም እንዲችል የሚያደርግ ከመሆኑም ሌላ ለሙዚቃ ኢንዱስትሪ የሚያበረክተው አስተዋፅኦ በቀላሉ የሚገመት አለመሆኑን ወ/ሪት ምዕራፍ ገልፃለች፡፡ በቀጣይም ከሌሎች ድምፃውያን ጋር ስምምነቶችን በመፈፀም ዘፈኖቻቸውን በኢንተርኔት ለሽያጭ እንደሚያቀርቡም ሃላፊዋ አስታውቃለች፡፡