Administrator

Administrator

ፌስቡክ ታዋቂው የማህበራዊ ድረ ገጽ ዋትሳፕን የራሱ ለማድረግ ካከናወነው ግዢ ጋር በተያያዘ ለአውሮፓ ህብረት የተሳሳተ መረጃ ሰጥቷል በሚል በህብረቱ የንግድ ውድድር ተቆጣጣሪ አካላት 95 ሚሊዮን ፓውንድ ቅጣት እንደተጣለበት ዘ ጋርዲያን ዘግቧል፡፡
ፌስቡክ ከሶስት አመታት በፊት ዋትሳፕን በ19 ቢሊዮን ዶላር በመግዛት የራሱ ባደረገበት ወቅት የሁለቱን ማህበራዊ ድረገጾች ተጠቃሚዎች ኣካውንቶች ግንኙነት በተመለከተ ለህብረቱ ከሰጣቸው መረጃዎች ጋር በሚቃረን መልኩ ሲሰራ መገኘቱ በመረጋገጡ ቅጣቱ እንደተጣለበት ዘገባው ገልጧል፡፡
ፌስቡክ የራሱንና የዋትሳፕ ተጠቃሚዎችን አካውንቶች የግዢ ውሉ ላይ ከተጠቀሰው ውጭ ከስልክ ቁጥራቸው ጋር አስተሳስሮ አገልግሎት ሲሰጥ መቆየቱ ስህተት መሆኑን በማመን፣ ድርጊቱ ሆን ተብሎ የተፈጸመ አይደለም ሲል ቅጣቱ መተላለፉን ተከትሎ ባወጣው መግለጫ አስተባብሏል፡፡
ኩባንያው ድርጊቱን ሆን ብዬ አልፈጸምኩም ብሎ ያስተባብል እንጂ የተጣለበትን ከፍተኛ የገንዘብ ቅጣት በመቃወም ይግባኝ ይጠይቅ አይጠይቅ በግልጽ ያስታወቀው ነገር እንደሌለም ዘገባው አክሎ ገልጧል፡፡

  ባለፉት 2 አመታት ብቻ 170 ሺህ ያህል የተለያዩ አገራት ዜግነት ያላቸው ህጻናት ስደተኞች ወደ አውሮፓ አገራት በመግባት ጥገኝነት መጠየቃቸውንና በተጠቀሰው ጊዜ ውስጥ በአለም ዙሪያ ያለ ወላጅ ወይም ረዳት ብቻቸውን የተሰደዱ ህጻናት ቁጥር ከ300 ሺህ በላይ መድረሱን ዩኒሴፍ አስታውቋል፡፡
ድርጅቱ ባለፈው ረቡዕ ባወጣው መግለጫ እንዳለው፤ የአለማችን ህጻናት ስደተኞች ቁጥር በአምስት እጥፍ ያህል ያደገ ሲሆን፣ እየተባባሰ በመጣው ደጋፊና ረዳት የሌላቸው ብቸኛ ህጻናት ስደተኞች ላይ የሚሳተፉ ህገወጥ የሰዎች አዘዋዋሪዎች  በርካቶቹን ለባርነትና ለሴተኛ አዳሪነት እየዳረጉ ይገኛሉ፡፡
ባለፈው አመትና በዘንድሮው የፈረንጆች አመት የመጀመሪያ ወራት በጀልባ ተሳፍረው ወደ ጣሊያን ከገቡት ህጻናት ስደተኞች መካከል 92 በመቶ የሚሆኑት ብቻቸውን የተጓዙ ወይም ወላጅ ዘመዶቻቸውን በስደት ጉዞ ላይ ያጡ እንደሆኑና አብዛኞቹም የኤርትራ፣ ጋምቢያ፣ ናይጀሪያ፣ ግብጽ እና ጊኒ ዜግነት ያላቸው እንደሆኑ ዩኒሴፍ አስታውቋል፡፡
90 ሺህ ያህል የአፍሪካ ቀንድ አገራት ህጻናት በአገራቸው ውስጥና በአካባቢው አገራት ከተቀሰቀሱ የእርስ በእርስ ግጭቶች ለመሸሽ በአገር ውስጥ እና ከአገር ውጭ ብቻቸውን ለመሰደድ እንደተገደዱም ድርጅቱ ባወጣው መግለጫ አስታውቋል፡፡
በተያያዘ ዜናም፣ በደቡብ ሱዳን የቀጠለውን የእርስ በእርስ ግጭት በመሸሽ በየቀኑ 100 ያህል የአገሪቱ ህጻናት ብቻቸውን ድንበር አቋርጠው ወደ ኡጋንዳ እንደሚሰደዱ ወርልድ ቪዥን የተባለው አለማቀፍ ተቋም ማስታወቁን ሮይተርስ ዘግቧል፡፡
እነዚሁ የአገሪቱ ህጻናት ያለምግብና መጠጥ እንዲሁም ደጋፊ ወላጅ ዘመድ ድንበር አቋርጠው ለቀናት በአስቸጋሪ ሁኔታ እንደሚጓዙና ለተለያዩ የከፉ ችግሮች እየተጋለጡ እንደሚገኙም ዘገባው ገልጧል፡፡

 ከሶስት አመታት በፊት የተቀሰቀሰው አስከፊ የኢቦላ ቫይረስ ወረርሽኝ 49 ዜጎቿን ለህልፈተ ህይወት በዳረገባት ዲሞክራቲክ ሪፐብሊክ ኮንጎ አንዳንድ አካባቢዎች ሰሞኑን የኢቦላ ቫይረስ ዳግም መቀስቀሱንና ይህም አገሪቱን ለከፋ ስጋት እንደዳረጋት የአለም የጤና ድርጅት አስታውቋል፡፡
ከሰሞኑ በአገሪቱ ሰሜን ምስራቃዊ አካባቢ በተቀሰቀሰው የኢቦላ ቫይረስ የተጠቁ ሁለት ሰዎች መገኘታቸውን፣ ሶስት ሰዎች መሞታቸውንና ሌሎች 18 ሰዎችም በቫይረሱ ሳይያዙ እንዳልቀሩ በመጠርጠሩ የህክምና ክትትል እየተደረገላቸው እንደሚገኙ ድርጅቱ አስታውቋል፡፡
በቫይረሱ ከተጠቁ ሰዎች ጋር ንክኪ አላቸው የተባሉ ከ400 በላይ ሰዎችን በአፋጣኝ ወደ ህክምና ካፕም ማስገባትን ጨምሮ፣ በአገሪቱ ኢቦላ ዳግም በወረርሽኝ መልክ እንዳይከሰት በመጪዎቹ ስድስት ወራት የተለያዩ ስራዎች እንደሚከናወኑ የዘገበው አሶሼትድ ፕሬስ፣ ለዚህም 10 ሚሊዮን ዶላር ያህል ያስፈልጋል መባሉን ገልጧል፡፡
ቫይረሱ ከታወቀበት እ.ኤ.አ ከ1976 አንስቶ ለሰባት ጊዜያት በወረርሽኝ መልክ በተከሰተባት ኮንጎ ሰሞኑን በአዲስ መልክ የተቀሰቀሰውን የኢቦላ ቫይረስ ስርጭት ለመግታት ችግሩ በተከሰተባቸው አካባቢዎች የህክምና ማዕከል ማቋቋምን ጨምሮ ሌሎች ርብርቦች እየተደረጉ እንደሚገኙም አስረድቷል፡፡

   ጊፍት ሪል ኢስቴት በሲኤምሲ አካባቢ ከሚሰራቸው የመኖሪያ መንደሮች አንዱ የሆነውንና ከ850 ሚሊዮን ብር በላይ ወጪ የተደረገበትን የመንደር ሁለት ቤቶች ግንባታ ሙሉ በሙሉ አጠናቅቆ የዛሬ ሳምንት ለነዋሪዎች አስረከበ፡፡
ባለፈው ሳምንት ግንቦት 5 ቀን 2009 መሪ ሎቄ አካባቢ በሚገኘው የመንደር ሁለት ግቢ ውስጥ በተከናወነው የምረቃ ሥነ-ሥርዓት ላይ በተለያየ ዲዛይን የተሰሩ 350 ቪላዎች፣ ሮው ሃውስ፣ ታውን ሃውስና አፓርትመንቶች ለነዋሪዎች የተላለፉ ሲሆን በሥነ-ሥርዓቱ ላይ የኢፌዴሪ ፕሬዚዳንት፣ ከፍተኛ የመንግሥት ባለሥልጣናት፣ ጥሪ የተደረገላቸው ታዋቂ ሰዎችና የንግዱ ማኅበረሰብ አባላት ተገኝተዋል፡፡
የመንደር አንድ ግንባታን ሙሉ በሙሉ አጠናቅቆ ባለፈው ዓመት ለነዋሪዎች ያስተላለፈው ጊፍት ሪል ኢስቴት፣ በዘርፉ ከተሰማሩ ግንባር ቀደም ተቋማት አንዱ ሲሆን በሊዝ በተረከበው 16.3 ሄክታር መሬት ላይ የሚገነቡ 1500 ቪላ፣ ታውን ሃውስ፣ ሮው ሃውስና አፓርትመንት ቤቶች ግንባታ ጠቅላላ ኢንቨስትመንት 2 ቢሊዮን ብር እንደሚጠጋ የሪል ኢስቴቱ መሥራችና ማኔጂንግ ዳይሬክተር አቶ ገብረየሱስ ኢጋታ ገልጸዋል፡፡
እነዚህ የሦስት መንደር ልማት ፕሮጀክቶች ከ1500 በላይ ቤተሰቦችን ተጠቃሚ የሚያደርጉ ታውን ሃውስ፣ ሮሃ ሃውስና ቪላ ቤቶች፣ 44 ብሎክ አፓርትመንቶች፣ 12ና ከዚያም በላይ ፎቅ ያላቸው የንግድ ሕንፃዎችን የሚያካትቱ እንደሆኑ፣ ከ1,500 ለሚበልጡ ዜጎች ጊዜያዊና ቋሚ የሥራ ዕድል መፍጠሩን ማኔጂንግ ዳይሬክተሩ ተናግረዋል፡፡
በሚገነባቸው ቤቶች ጥራት በደንበኞች ዘንድ ምስጉን የሆነው ጊፍት ሪል ኢስቴት፤ በገባው ቃል ባለማስረከብ ይወቀሳል፡፡ የዚህንም ችግር አቶ ገብረየሱስ ሲናገሩ፤ ‹‹የመኖሪያ መንደሮች ግንባታ አልጋ በአልጋ አልነበረም፤ እጅግ ፈታኝና የድርጅቱን ሕልውና አደጋ ላይ የጣሉ፣ ደንበኞችንም ለስጋት የዳረጉ ክስተቶች አስተናግደናል። በተዋረድ በሚገኙ የአስተዳደር መዋቅሮች ውስጥ የነበሩ አንዳንድ ግለሰቦች በፈጠሩት ውስብስብ ችግሮች ድርጅቱ ለዓመታት አስተዳደራዊ አገልግሎት እንዳያገኝ ተከልክሎ ቆይቷል፡፡ ይህ እርምጃ በብዙ መልኩ ድርጅቱን ቢጎዳውም፣ ከደንበኞች ጋር የገባነውን ቃል ለማክበር ጥረት ስናደርግ ቆይተናል›› ብለዋል፡፡
ደንበኞች እስካሁን ለጠበቁት ጊዜ በቂ ማካካሽ ባይሆንም ድርጅቱ እንደ ምስጋና መግለጫ ይሆነው ዘንድ 14 ሚሊዮን ብር ወጪ በማድረግ በውል ላይ ከሰፈረው ውጪ በLTZ መሠራት የነበረባቸውን ታውን ሃውስና አፓርትመንት ቤቶች ሙሉ በሙሉ በአሉሚኒየም መቀየሩን፣ የውስጥ ለውስጥ መንገዶችን ሙሉ በሙሉ በአስፋልት መቀየሩን፣ ለነዋሪዎች ምቾትና ለግቢው ውበት ባለፏፏቴና በአረንጓዴ ዕፅዋት ያማረ መናፈሻ ማዘጋጀታቸውን ማኔጂንግ ዳይሬክተሩ ገልጸዋል፡፡
ጊፍት ሪል ኢስቴት ማኅበራዊ ኃላፊነቱን ከመውጣት አኳያ ለታላቁ ህዳሴ ግድብ ለገቢ ማሰባሰቢያ የሚውል መኖሪያ ቤት በመስጠት፣ ለቀይ መስቀል ማኅበርም በተመሳሳይ መኖሪያ ቤት በመስጠትና በማንኛውም ሀገራዊ የልማት ተግባር ንቁ ተሳትፎ በማድረግ ላይ እንደሚገኝ አቶ ገብረየሱስ ኢጋታ ተናግረዋል፡፡
ጊፍት ሪል ኢስቴት ብቻ ሳይሆን፣ በርካታ በተመሳሳይ የሥራ ዘርፍ የተሰማሩ ድርጅቶች፣ “እናስረክባለን” ባሉት ጊዜ ኃላፊነታቸውን ያለመወጣት ችግር አለባቸው፡፡ ሁለትና ሦስት ዓመት የመቆየት ችግር የተለመደ ነው፡፡ ፍ/ቤት ደጃፍም የረገጡም አሉ፡፡
ጊፍት ሪል ኢስቴት፣ “አስረክባለሁ” ባለው ጊዜ ባለማስረከብ፣ “ዘግይቷል” የሚለው ቃል አይገልጸውም። ምክንያቱም ሰባትና ዘጠኝ ዓመት የጠበቁ ደንበኞች ስላሉ ነው፡፡ ከሁለተኛው መንደር ቤት የተረከቡ ሰዎች ምን ይላሉ?
ዲያቆን ዳንኤል ክብረት፡- የነዋሪዎች ኮሚቴ ሊቀመንበር ነው፡፡ የቤት ርክክቡ በጣም ዘግይቷል። በመኻል  የቤት ባለቤቶች ኮሚቴ ተቋቁሞ ከድርጅቱ ጋር ብዙ ክርክሮች ተደርገዋል፡፡ በመጨረሻ የጠቅላይ ሚ/ር ጽ/ቤት፣ የአዲስ አበባ መስተዳደር ጽ/ቤትና የየካ ክፍለ ከተማ ወረዳ 13 ተጨምሮበት በተሰጠው አመራር፣ የቤቱን ግንባታ በትብብር በመሥራት በአንድ ዓመት ጊዜ ውስጥ እንዲያልቅ ስምምነት ላይ ተደርሶ፣ ይኸው እንግዲህ ባለፈው አንድ ዓመት በተደረገው ርብርብ የቤቱ ግንባታ አልቆ ልንረካከብ ችለናል፡፡
ችግሩ ምንድን ነው? የተባለ እንደሆነ፣ እኛ ቤት ለመረከብ ውል የገባነው በ18 ወር ነው፡፡ የፈጀው ግን 7 ዓመት ነው፡፡ ይታይህ፣ ይህንን መዘግየት አይገልጸውም። ያ አይደለም የሰዎቹ ጥያቄ፡፡ እሺ ዘገየ፤ መቼ ነው የሚያልቀው? የሚለው ጥያቄ ቁርጥ ያለ መልስ የለውም። ከ20 ዓመት በላይ ነው በሉንና ቁርጣችንን አውቀን ሌላ አማራጭ እንፈልግ። ወይም ከ20 ቀን በኋላ በሉንና ደስ ይበለን እያለ ነበር ሲወተውት የነበረው፡፡ በአንድ ዓመት ውስጥ ማለቅ አለበት ተብሎ እኛም ችግሮችን አብረን ሆንን እየፈታን ለመረከብ በቃን፡፡
የእኔ ቤት ታውን ሃውስ የሚባለው ስለሆነ ብዙም ችግር አልነበረውም፡፡ ነገር ግን የሌሎች ካላለቀ ምንም ትርጉም የለውም፡፡ ናይጄሪያውያን የሚሉት አንድ አባባል አለ፡- “ልጅን ለማሳደግ መንደር ያስፈልጋል” ይላሉ፡፡ የመንደሩ ቤቶች ካላለቁ የእኔ ቤት ብቻ ቢያልቅ ዋጋ ያለውም፡፡ ስለዚህ የእኛ ክርክር ሁሉም ቤቶች ይለቁ የሚል ነበር፡፡ ይኸው ዛሬ ሁሉም ቤቶች አልቀው ለመረከብ በቃን፡፡ ጥቂት ነገሮች ቢቀሩም ወደ መኖሪያነት ተቀይሯል፡፡ ውሃና መብራት ገብቶልናል፤ ዘጠና ከመቶ ተጠናቋል፡፡
ትልቁ ችግር የነበረው ዋጋው ነው፡፡ መጀመሪያው ከ7 ዓመት በፊት የነበረው ዋጋ፣ የእኛ ቤቶች ከ800 እስከ 1.2 ሚሊዮን ብር ነበር፡፡ በ1997 የዛሬ 12 ዓመት ማለት ነው፡፡ ያኔ የቀን ሠራተኛ ዋጋ 30 ብር ነበር፡፡ ዛሬ 140 ብር ሆኗል፡፡ ሌላ ሌላውም እንደዚሁ ጨምሯል፡፡ በተለይ ችግር የተፈጠረው ‹‹በየትኛው ዋጋ ነው የምንከፍለው?›› የሚል ነው። በተለይ ከፍለው የጨረሱት፡፡ ‹‹በዛሬ ዋጋ ክፈሉ›› ሲባሉ ‹‹እናንተ ባዘገያችሁት ለምንድነው በዛሬ ዋጋ የምንከፍለው?›› ይሉ ነበር፡፡ ችግሮች በሽምግልና በድርድር እየተፈቱ ዛሬ ጥሩ ቀን ላይ ደርሰናል፤ በማለት ገልዷል፡፡ አቶ አዲስ ሚካኤል፤ ‹‹ብዙ ሪል ኢስቴቶች ላይ ያሉ ችግሮች ጊፍት ሪል እስቴትም ላይ ይታያሉ። ዋናው ነገር በብዙ ችግሮች ውስጥ አልፎ እዚህ መድረሱ በጣም ደስ ይላል፡፡ እኔ ከዛሬ 8 ዓመት በፊት በ1.7 ሚሊየን ብር የገዛሁት ቤት ተጎራባች ወይም ታወን ሃውስ  የሚባለውን ነው፡፡ የጊፍት ሪል እስቴት ትልቁ ቁምነገሩ ቤቶችን በጥራት መሥራቱ ነው፡፡ እናም ከሌሎቹ ሪል ኢስቴቶች ጊፍትን መርጠን ቤት እንድንገዛ ያደረገን የጥራቱ አሠራር ነው፡፡
አሁን ሁሉም ነገር በሰላም አልቆ፣ ውሃና መብራት ገብቶላቸው ተረክበን እየኖርንበት ነው፡፡ የቤቶቹ ግንባታ የዘገየበት ብዙ ምክንያቶች አሉ፡፡ የቦታ ማለትም የወሰን ማስከበር፤ የባለሙያ፣… ችግር ነበረበት፡፡ ገዥዎችም ላይ በወቅቱ ያለመክፈል ችግር ይኖራል፡፡ በመጨረሻ ሁሉ ችግር አልፎ እዚህ መድረሱ በጣም ደስ ይላል፡፡›› ብለዋል።
ወ/ሮ ስርጉት ተክሉ፣ የሦስት ልጆች እናት ናቸው፤ ‹‹የተመዘገብኩት ከ7 ዓመት በፊት ሲሆን ቤቱን የተረከብኩት ደግሞ ካቻምና በ2007  ዓ.ም ነው፡፡ በፊት በመዘግየቱ ተከፍተን ነበር፡፡
አሁን ግን ቤቱን ተረክበን ገብተንበት ስናየው ቤቱን ሰርቶ (አቁሞ) እንዲያስረክበንና የውስጥ ዲዛይን እኛ በፈለግነው መንገድ እንድንጨርሰው ነበር፡፡
በውላችን መሠረት ቤቱን አስረከበን፤ እኛም በፈለግነው መሰረት የውስጥ ዲዛይኑን ጨርሰን ገባንበት። ምንም ቅር አላለንም፤ በዚህና በቤቱ ጥራት በጣም ደስተኞች ነን፡፡
የእኔ ቤት 370 ካሬ ላይ ያረፈ ቪላ ነው፡፡ 7 መኝታ ክፍሎችና፣ 2 ሳሎንና 2 ወጥ ቤት አለው፡፡ ውስጥ ዲዛይኑና ፊኒሽንጉ በራሴ በመሆኑ ሙሉውን አልከፈልኩም፡፡
ሁለት ሚሊዮን ብር ያህል ከፍያለሁ፡፡ በፊት ግንባታው በመዘግየቱ የተነሳ ብከፋም፤ አሁን ከገባሁበት በኋላ ግን ደስተኛ ነኝ፡፡ አየሩንም፣ ጎረቤቶቼንም፣ ጊፍትንም ወድጃቸዋለሁ። በጣም በደስታ ከልጆቼና ከባለቤቴ ጋር እየኖርኩ ነው፡፡›› ብለዋል፡፡

   ታዋቂው የኳታር አየር መንገድ ካተሪንግ አገልግሎት፤ አዲስ ዓለም አቀፍ ካተሪንግ (የምግብና የመጠጥ ዝግጅት) ‹‹የ2016 ምርጥ የአፍሪካ ምግብ አዘጋጅ›› በሚል ለሁለተኛ ጊዜ ሸለመ፡፡ ከአሁን ቀደምም በ2014 በተመሳሳይ መሸለሙ አይዘነጋም፡፡
የሚድሮክ ኢንቨስትመንት ግሩፕ አባል የሆነው አዲስ ዓለም አቀፍ ካቴሪንግ፣ ለኢትዮጵያና ለሌሎች አገሮች አየር መንገዶች፣ ለዓለም አቀፍ ጉባዔዎችና በአዲስ አበባ አካባቢ ለሚደረጉ ትላልቅ ዝግጅቶች ዓለም አቀፍ ደረጃ ያለው ምግብ ለማቅረብ በ1998 የተመሠረተ ተቋም ነው፡፡
በመላው ዓለም ከ150 በሚበልጡ መዳረሻዎች የሚበረው ባለ 5 ኮከቡ የኳታር አየር መንገድ፣ በሚበርባቸው አገሮች 105 የምግብና መጠጥ አዘጋጆች (ካተርስ) ሲኖሩት በአፍሪካ ወደ 24 መዳረሻዎች  ይበራል፡፡ የተሳፋሪዎችን አስተያየት፣ ወቅታዊ (ኦን ታይም) አቅርቦት፣ የተሳፋሪዎች ግብረ-ምላሽና ከምግብና ከደህንነት ጋር የተያያዙ በርካታ ጉዳዮችን የመዘኑ መሆኑን የጠቀሰው መግለጫው፤ ከምግብ አዘጋጆች ናሙና እንደሚወስዱ፣ መሳሪያዎች እንደሚመረምሩ፣ ግንኙነት እንደሚታይ፣ የአለቃ ሪፖርትና የአዘጋጃጀት ቅልጥፍና እንደሚታይ ተገልጿል፡፡
አዲስ ዓለም አቀፍ ካተሪንግ ከኳታር አየር መንገድ በተጨማሪ ቦሌ ዓለም አቀፍ አውሮፕላን ማረፊያ ለሚጠቀሙ ሌሎች ደንበኞች ለምሳሌ ለጂቢቲ፣ ለግብፅ፣ ለኢምሬትና ለኬንያ አየር መንገዶች አገልግሎት እንደሚሰጥ የጠቀሰው መግለጫው፤ ለቪአይፒ፣ ለኪራይና በግል ለሚንቀሳቀሱ አውሮፕላኖች፡- እንደ አቢሲኒያ ፍላይት ሰርቪስና እንደ ትራንስ ኔሽን ላሉ ትናንሽ በረራዎች አገልግሎት እንደሚሰጥ አስታውቋል፡፡  በተጨማሪም፣ አዲስ ዓለም አቀፍ ካተሪንግ፣ ለጀርመን ኤምባሲ ት/ቤት፣ ለዓለም አቀፍ ኮሙኒቲ ት/ቤት፣ ለየን ኻርት አካዳሚና ለሳንፎርድ ዓለም አቀፍ ት/ቤቶችን ጨምሮ በተለያዩ ኤምባሲዎች፣ ባንኮችና ለግል ዝግጅቶች አገልግሎት ይሰጣል ተብሏል፡፡

  ከሰባት ዓመት በፊት በ2002 ዓ.ም በ15 ሚሊዮን ብር ካፒታል የተቋቋመው ኢትዮ ሃይላንድ ማራቶን ኤቨንትስ ኦርጋናይዝ ኩባንያ ከነሐሴ 12-14 ቀን 2009 ዓ.ም በሚሌኒየም አዳራሽ የትራንስፖርትና ሎጂስትክስ ዓለም አቀፍ ኤግዚቢሽን እንደሚካሄድ አስታወቀ፡፡
አዘጋጆቹ ባለፈው ሳምንት በካሌብ ሆቴል ለጋዜጠኞች በሰጡት መግለጫ፣ ትራንስፖርት ያለ ሎጂስቲክ (የጭነት ዕቃ) የተሟላ አገልግሎት እንደማይሰጥ ሁሉ፣ ሎጂስቲክም ያለ ትራንስፖርት ብቻውን መቆም አይቻልም፤ ሁለቱ የተጣመሩና የተጎዳኙ ናቸው ብለዋል፡፡ ኤግዚቢሽኑን ያዘጋጁበት ዓላማ፣ ዘርፉ በሀገር ልማት ያበረከተውን አስተዋጽኦና መንግሥትን ጨምሮ ሁሉም ባለድርሻ አካላት የተጫወቱትን ሚና ለማሳየት፤ በትራንስፖርትና ሎጂስቲክስ ዘርፍ የተሰማሩ ተዋናዮችና ባለድርሻ አካላት ልምዶቻቸውንና ስኬቶቻቸውን የሚለወዋወጡበት መድረክ ለመፍጠር መሆኑን ገልጸዋል፡፡
ከዚህም በተጨማሪ በዘርፉ ውስጥ ያሉ አካላት ምርቶቻቸውንና አገልግሎታቸውን የሚያስተዋውቁበት ሰፊ የገበያ ዕድል ለመፍጠርና በኤግዚቢሽኑ የትራንስፖርትና የሎጂስቲክ ችግሮችና ተግዳሮቶች እንዲሁም ያሉት መልካም ጎኖች ተፈትሸው ጥናታዊ ጽሑፍ የሚቀርብበትን ወርክሾፕ ለማዘጋጀት ነው ብለዋል፡፡
ኤግዚቢሽኑ የአንድ ጊዜ ብቻ ሳይሆን፣ ኢትዮ ትራንስፖርትና ሎጂስቲክስ ፌር በሚል ስያሜ በየዓመቱ የሚቀጥል መሆኑን ጠቅሰው ጠቀሜታውንም ሲገልጹ፣ ዘርፉ ለአገር ኢኮኖሚ ያለውን ፋይዳ ለማሳደግ የሚያስችል ዕድል ይፈጥራል፣ በዘርፉ ያሉ ተዋናይና ባለድርሻ አካላት ምርትና አገልግሎታቸውን ያስተዋወቁበታል፣ ተዋናዮቹ፣ በጋራ ችግሮቻቸው ላይ ተቀራርበው በመነጋገር የመፍትሄ ሀሳቦችን ያፈልቁበታል በማለት አስረድተዋል፡፡
በዚህ ኤግዚቢሽን ላይ የትራንስፖርት ሚ/ር፣ የክልልና የከተማ አስተዳደር ትራንስፖርት ቢሮዎች፣ የሕዝብና የዕቃ ማጓጓዣ ትራንስፖርት አገልግሎት ሰጪዎች፤ የባህር፣ የአየር፣ የየብስ፣ የባቡር፣ የወደብ አገልግሎት ሰጪዎች፣ ዕቃ አስተላላፊዎች፣ ዕቃ የማሸግና ለጉዞ የማመቻቸት አገልግሎት ሰጪዎች፣ ልዩ ልዩ የተሽከርካሪ መለዋወጫ አምራቾች፣ አስመጪና ላኪዎች፣ ጋራዦች፣ የንግድ ወኪሎች፣ የነዳጅ ኩባንያዎች፣ ባንኮችና ኢንሹራንሶች፣ ጎሚስታዎች፣… እንደሚሳተፉ ተገልጿል፡፡

   ‹‹በዩኒቨርሲቲ ለማጥናት የመጀመሪያ ምርጫዬ ህክምና ነው፤ ካልሆነ ስፔስ ሳይንስ ባጠና አይከፋኝም››

     ኦልማርት ሱፐር ማርኬት ከቅድስት ማሪያም ዩኒቨርሲቲና ከአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር የትምህርት ቢሮ ጋር በመተባበር “Excellence for Education” የተሰኘና በአዲስ አበባ የሚገኙ 20 የመንግስት መሰናዶ ት/ቤት ተማሪዎች
የሚወዳደሩበት የጥያቄና መልስ መርሀ ግብር አዘጋጅቶ ነበር፡፡ በዚህ መርሀ ግብር ለ6530 ተማሪዎች እድል ተሰጥቶ ሚያዚያ 26 ቀን 2009 ዓ.ም 3 ሺህ ተማሪዎች ለፈተና የቀረቡ ሲሆን ባለፈው ቅዳሜ ማጣሪያ ካለፉት 100 ተማሪዎች ምርጥ አስሩ ተለይተው፣ ባለፈው ሰኞ ምሽት በራዲሰን ብሉ ሆቴል ሽልማታቸውን ወስደዋል፡፡ በሽልማት ስነ ስርዓቱ ላይ የተገኘችው የአዲስ አድማስ ጋዜጠኛ ናፍቆት ዮሴፍ፤ በውድድሩ 1ኛ ከወጣውና የአየር ጤና መሰናዶ ት/ቤት ተማሪ ከሆነው የ19 ዓመቱ ወጣት አቤል ሽፈራው ጋር ተከታዩን ቃለ ምልልስ አድርጋለች፡፡

      ከመጀመሪያ አንስቶ አየር ጤና ነው ትምህርትህን የተከታተልከው?
አየር ጤና አካባቢ ባሉ ት/ቤቶች ነው የተማርኩት፤ የተወለድኩት ግን መሀል አዲስ አበባ አራዳ ክ/ከተማ ውስጥ ነው፡፡ ቤተሰቦቼ በቤት ኪራይ ይኖሩ ስለነበር፣ ከዚያ ቤት ሰርተው ወደ ወለቴ ሄድን፣ አንደኛ ደረጃም ሆነ ሁለተኛ ደረጃ ትምህርቴን የቀጠልኩት ከ1-10ኛ ክፍል ካራ ቆሬ ረጲ 1ኛና መለስተኛ ሁለተኛ ደረጃ ት/ቤት ሲሆን ለመሰናዶ ትምህርት ነው አየር ጤና መሰናዶ የገባሁት፡፡
የቤተሰብህ የኑሮ ሁኔታ ምን ይመስላል?
ቤተሰቤ እንደ ማንኛውም ኢትዮጵያዊ ቤተሰብ ተቸግረው ነው ያስተማሩኝ፡፡ እነሱ በቅጡ ባልተማሩበትና ባልተደላደሉበት ሁኔታ ውስጥ ሆነው ነው፣ እኔንም ሆነ ከእኔ በላይና በታች ያሉ እህትና ወንድሞቼን እያስተማሩ ያሉት፡፡ እነሱ ለእኔ አርአያዎቼ ናቸው፤ እኔም የእነሱ ውጤትና መገለጫ ነኝ፡፡ በጣም ነው የማመሰግናቸው፡፡
ከ1ኛ ክፍል ጀምሮ እስካሁን በትምህርት ውጤትህ እንዴት ነህ?
የሚገርምሽ ከ1ኛ ክፍል ጀምሬ ጎበዝ ተማሪ ነበርኩ፤ በተለይ ከ3ኛ ክፍል ጀምሮ በከፍተኛ ትኩረት ነው ትምህርቴን ስከታተል የነበረው። ከዚያን ጊዜ ጀምሮ በሁሉም የትምህርት አይነት ጥሩ ውጤት በማምጣት የደረጃ ተማሪ ሆኜ ነው የቀጠልኩት፡፡ አሁንም ወደ ዩኒቨርሲቲ ለመግባት በዝግጅት ላይ ነኝ፤ የ12ኛ ክፍል ፈተናዬን በደንብ ለመስራት በመትጋት ላይ እገኛለሁ፡፡
እንደነገርከኝ እድሜህ 19 ዓመት ነው፡፡  16 እና 17 ዓመት ወጣቶች በአቻዎቻቸው ግፊት ወደ ብዙ ነገሮች የሚገቡበት እድሜ ነው፡፡ አንተ ይህን ተቋቁመህ ጎበዝ ተማሪ የሆንክበት ምስጢር ምንድን ነው?
በጣም ከባድ ጊዜ ነው፡፡ እንደምታውቂው ጊዜው የግሎባላይዜሽን ነው፡፡ ይህ ማለት ብዙዎቻችን በውጭ የኑሮ ዘይቤ ተፅዕኖ ውስጥ ነው ያለነው። ይህንን ተፅዕኖ ተቋቁሞ ማለፍ ራሱን የቻለ ሌላ ፈተና ነው፡፡ እኔ በበኩሌ፤ ከዚህ ፈተና ለማምለጥ ስል ከሚዲያ የራቅኩ ነኝ፡፡ ኢንተርኔትና ፌስቡክ ሁሉንም አልጠቀምም፤ ትኩረቴን ወደ ትምህርት ነው ያደረግሁት፡፡ ስልክ እንኳን ለመደወልና ለጥሪ ብቻ ነው የምጠቀመው፡፡ እነዚህን ነገሮች ልጠቀም ብዬ  ቤተሰቤን ብጠይቅ፣  የራሳቸውን ነገር ወደ ጎን አድርገው እንደሚያሟሉልኝ አምናለሁ፡፡ ግን በዚህ ወቅት ላይ ለእኔ አስፈላጊ ስላልሆነ አልፈልግም በሚል ወደ ትምህርቴ አዘንብያለሁ፡፡ በአጠቃላይ በትምህርቴ ላይ ተፅዕኖ የሚያሳድር ማንኛውንም ነገር ትቼ፣ ትምህርቴ ላይ ማተኮር ቅድሚያ የምሰጠው ተግባሬ ነው፡፡
ኦልማርት ያዘጋጀውን ውድድር እንዴት አገኘኸው ወይስ ኦልማርትን ከዚህ በፊት ታውቀው ነበር?
እውነት ለመናገር ኦልማርትን ከዚህ በፊት አላውቀውም፤ እንዲህ የሚባል ድርጅት ስለመኖሩም መረጃ አልነበረኝም፡፡ ውድድሩ ተዘጋጀ ተብሎ ለፈተና ልንቀመጥ ሲቀበሉን በጣም ነበር የገረመኝ። የሄድንበት አውቶቡስ፣ የአዘጋጆቹ ትህትና፣ በአጠቃላይ የሰጡን ዕድል ከእኔ ግምት በላይ ነው፡፡  በቀጣይ ትልልቅ ፈተና ለሚጠብቃቸው የመንግሥት የ12ኛ ክፍል ተማሪዎች ይህ ፈተና መዘጋጀቱ ትልቅ ዕድል ነው፤ ምክንያቱም ለዋናው ፈተና ያነቃቃቸዋል፡፡ በሌላ በኩል ሽልማቱና ከዚህ ሁሉ ሰው አንደኛ ሆኖ መውጣት ትልቅ እድልና በራስ  ይበልጥ መተማመንን ያጎለብታል። በሌላ በኩል ከተመለከትነው እኛ ይህን ዕድል በኦልማርት ማግኘታችንና እዚህ በመድረሳችን ለሌሎች ተማሪዎች መነቃቃትን ይፈጥራል፡፡ በጣም የገረመኝ ከ1-10 የወጣነውን የሸለሙን ባለ 5 ኮከብ ሆቴል ውስጥ በትልቅ ክብር ነው፡፡ ይህንን ሁሉ ስመለከተው እንኳን 1ኛ ወጥቼ አይደለም ተሳታፊ ሆኜ ብሸኝ እንኳን ለእኔ ለቤተሰቤም ኩራት ነው። በአጠቃላይ ውድድሩ እንዲህ ደረጃውን የጠበቀ ይሆናል ብለን አልጠበቅንም፡፡ እኔም ሆንኩ ከኔ ቀጥሎ እስከ 10ኛ የወጡት ልጆች በጣም ደስተኞች ነን፡፡
አንደኛ እወጣለሁ ብለህ ጠብቀህ ነበር?
አልጠበኩም፡፡
ለምን አልጠበክም?
ምክንያቱም የሌሎች ጎበዝ ተማሪዎችን ውጤት መገመት ይከብዳል፡፡ የዛሬ ሳምንት ቅዳሜ ምርጥ 10ሮቹ ውስጥ መግባታችን ሲነገረን፣ ማንኛችን አንደኛ እንወጣ ይሆን በሚል ስጨነቅ ነበር፤ ሆኖም ምርጥ 10 ውስጥ መግባቴን ራሱ እንደ ቀላል ውጤት አልቆጠርኩትም፡፡ ለምን ቢባል መጀመሪያ ከሶስት ሺህ ተማሪ ምርጥ መቶዎቹ ውስጥ መግባት በራሱ ትልቅ ነው፡፡
ከዚያ ምርጥ አስሩ ውስጥ በመጨረሻም አንደኛ መውጣት በጣም ያስደስታል፡፡ ያልጠበቀኩት ነገር ስለሆነ እኔ ብቻ ሳልሆን ቤተሰቦቼ በጣም ተደንቀዋል፡፡ አባቴና ሌሎች ቤተሰቦቼ እዚህ አዳራሽ ይገኛሉ፡፡ መወዳደሬን ራሱ ምርጥ 10 ውስጥ ከገባሁ በኋላ ነው የነገርኳቸው፡፡ በተለይ አባቴ ደስታውን መቆጣጠር አቅቶታል፡፡ ቤተሰቦቼም እንዲህ ትልቅ ውድድር መሆኑንና አንደኛ ይወጣል ብለውም አልጠበቁም ነበር፡፡
የፈተናው ሂደት ምን ይመስል ነበር፡ የቅድስት ማሪያም ዩኒቨርስቲ የፈተና አወጣጥ እንዴት ነበር? ጥያቄዎቹ ከባድ ናቸው ቀላል? ምን ምን ያህል ጥያቄዎችና ምን ያህል ሰዓት ነበር የተመደበው? እስኪ ጠቅለል አድርገህ መልስልኝ?
ቅድስት ማሪያም ዩኒቨርሲቲ ጥያቄዎቹን ያወጣው የፈተኑን ደረጃውን በጠበቀ መልኩ ነው። ማንኛውም አገር አቀፍ ፈተና ስንፈተን የሚሟላው ነገር ተሟልቷል፡፡ በራሳቸው መምህራን ነው የፈተኑን፡፡ ፈተናውም ከታሸገበት እዚያው ፊት ለፊታችን ነው የተቀደደው፡፡ ፈተናዎቹ በጣም ደስ ይላሉ፡፡ ሌላ ፈተና ለመስራት ያነቃቃሉ፣ ከዝግጅታቸው ጀምሮ ጥሩ የፈተና ሂደቶችን እንድናልፍ አደርገዋል፡፡ ወደ መፈተኛ ቦታው ስንሄድ ራሱ የተጓጓዝንበት አውቶቡስ ያነቃቃ ነበር፤ ያለማጋነን ነው የምነግርሽ፡፡ የምሰጠው አስተያየት በተለይ የሂሳብ ጥያቄዎቹን ትንሽ ጠንከር አደርገው ቻሌንጅ ቢያደርጉን ጥሩ ነበር፡፡ ምክንያቱም እዚህ ፈተና ላይ የተቀመጠው ሁሉም ተማሪ ብቃት ያለው ነው፡፡ ጥያቄዎቹ በእኔ እይታ ትንሽ ላላ ብለዋል፤ ይሄ የእኔ የግል አስተያየት ብቻ ነው፡፡ ጥያቄዎቹን በተመለከተ በተለይ ሁለተኛው ፈተና ላይ ውጤት ባይነገረንም ሂሳብ ምንም የከበደኝና የሳትኩት ጥያቄ እንደሌለ እርግጠኛ ነኝ፡፡ እንግሊዝኛ ትንሽ ከበድ የሚሉ ጥያቄዎች ነበሩት፡፡ የጥያቄው ብዛት እንግሊዝኛ መቶ ጥያቄ ሲሆን ሂሳብ 60 ጥያቄ ነው የቀረበልን፡፡ 2፡30 ለሂሳብ፣ ሁለት ሰዓት ደግሞ ለእንግሊዝኛ ተፈቅዶልናል፡፡ በዚህ ሰዓት ነው ሰርተን ያጠናቀቅነው፡፡ ትንሽ እንግሊዝኛ ላይ  ብዙዎቻችን የተቸገርን ይመስለኛል ምክንያቱም እርስ በእርሳችን የምንግባባው በአማርኛ ነው፡፡ በተረፈ ግን ይህ ፈተና ወደ ዩኒቨርሲቲ የሚያስገባንን ዋናውን ፈተና በምን ያህል አቅምና ዝግጅት እንሰራለን የሚለውን ያሳየንና ራሳችንን የለካንበት በመሆኑ፣ አዘጋጁንና አጋሮቹን ደጋግሜ ማመስገን እፈልጋለሁ፡፡
ከዚህ በፊት እንዲህ አይነት የውድድር እድሎች ገጥመውህ ያውቃሉ?
በፍፁም ተወዳድሬ አላውቅም፡፡ ይሄ የመጀመሪያዬ ነው፡፡ በእርግጥ ወደ 10ኛ ክፍል እንዳለፍኩ ስኮላርሺፕ የሚሰጥ አንድ ድርጅት መጥቶ ውጤቴን አስገብቼ ነበር፤ የመፈተን እድል ግን አልገጠመኝም፡፡ ለመጀመሪያ ጊዜ ነው እንዲህ አይነት ቦታ መጥቼ ይህን እድል ያገኘሁት፡፡
ከትምህርት ውጭ ሌላ ምን ዝንባሌ ወይም ተሰጥኦ አለህ?
ሌላ ተሰጥኦ ለጊዜው የለኝም፡፡ ቀደም ብዬ እንደነገርኩሽ ሙሉ ትኩረቴን የማደርገው ትምህርቴ ላይ ነው፡፡ በእርግጥ ት/ቤት ውስጥ ተሰጥኦም ባይባል ርዕሰ መምህራንንና መምህራንን ለማገዝ አንዳንድ ጥረቶችን አደርጋለሁ፡፡ አየር ጤና መሰናዶ ት/ቤት ውስጥ በጣም ብዙ ተማሪ ነው ያለው፡፡ መምህራንና ርዕሰ መምህራን ያንን ሁሉ ተማሪ ለመግራትና ብቁ ዜጋ ለማድረግ የሚወጡት የሚወርዱት መከራ፣ የሚያሳልፉት ስቃይ በጣም ያሳዝነኛል፡፡ እውነት ለመናገር እንደነዚህ ያለ ለዜጋ የሚቆረቆሩ መምህራን አይቼ አላውቅም፡፡ እኔንም ለዚህ ስላበቁኝ ክብር ይገባቸዋል፡፡ ያበረታቱናል፤ በተቻላቸው አቅም የእኛን ባህሪና ውጤት ለማሻሻል ይደክማሉ፡፡ ይህን የሚያደርጉት ብዙ ነገር ባልተሟላበት የመንግስት ት/ቤት በመሆኑ ክብርና ሽልማት ይገባቸዋል፡፡ ከዚህ ት/ቤት የሚወጡ ብዙ ተማሪዎች በጥሩ ውጤት ነው ትምህርታቸውን የሚጨርሱት፡፡ ይህ ሁሉ የመምህራኑና የማኔጅመንቱ ልፋት ነው፡፡
ወደ ዩኒቨርስቲ ለመግባት የሚያስችልህን ፈተና ለመፈተን ጥቂት ቀናት ናቸው የቀሩህ፡፡ ምን ያህል እየተዘጋጀህ ነው?
በጥሩ ዝግጅት ላይ ነኝ፡፡ ት/ቤትም የሞዴል ፈተናዎችን እየተፈተንን ነው ያለነው፡፡ አሁን ተወዳድሬ ያለፍኩበትም ፈተና ጥሩ መነቃቂያ ሆኖልኛል፡፡
ዩኒቨርስቲ ስትገባ ማጥናት የምትፈልገው ምንድ ነው?
እግዚአብሔር ፈቅዶ ጥሩ ውጤት አምጥቼ ዩኒቨርሲቲ ከገባሁ፣ ለማጥናት የመጀመሪያ ምርጫዬ ህክምና ነው፤ ይሄ የምንጊዜም ህልሜ ነው፡፡ ቢሳካልኝ ደስ ይለኛል፡፡ ይህ ካልሆነ ስፔስ ሳይንስ በጣም ስለምወድ እሱን ባጠና አይከፋኝም፡፡
በውድድሩ 1ኛ በመውጣትህ 15 ሺህ ብርና ለትምህርት የሚረዳ ታብሌት ኮምፒዩተር ተሸልመሀል፡፡ ብሩን ምን ልታደርግበት አስበሀል?
እኔ እንደዚህ አይነት ብር በእጄ ይዤ አላውቅም። ከብር ጋር የተነካካ ነገርም የለኝም፡፡ ያው ቤተሰቦቼ የሚፈልጉትን ሊያደርጉበት ይችላሉ። ግን በመሸለሜ ደስተኛ ነኝ፡፡ ታብሌት ኮምፒዩተሩ አሁን አያስፈልገኝም፡፡ ወደፊት ስለምጠቀምበት አስቀምጠዋለሁ፡፡
በመጨረሻ ማለት የምትፈልገው ካለ?
በመጀመሪያ ለዚህ ያበቃኝን ልዑል እግዚአብሔርን አመሰግናለሁ፡፡ በመቀጠል ብርቱዎቹን ቤተሰቦቼን አመሰግናለሁ፡፡ ታላላቅ ወንድሞቼ ለእኔ አርአያ ናቸው፡፡ ታላላቅ ወንድሞቼ በርትተው ተምረው ጥሩ ደረጃ ላይ ደርሰዋል፡፡ እኔም ውጤታማ እንድንሆን ለሚያደርጉት ድጋፍ አከብራቸዋለሁ፡፡
እናቴና አባቴ በጣም መልካም ሰዎች፣ ልጆቻቸውን በጥሩ ስነ ምግባር የሚያንፁ ናቸው፡፡ ያው እኔም ነፀብራቃቸው እንድሆን ለፍተዋልና አመሰግናለሁ፡፡ ይህንን ውድድር አመቻችቶ፣ በዚህ ሁኔታ የሸለመንን ኦልማርትንና አጋር ድርጅቶቹን አመሰግናለሁ፡፡ ኦልማርት በዚህ ረገድ በር ከፋች ነው፡፡ በቀጣይ ሚኒስትሪ ለሚፈተኑም የ8ኛ ክፍል ተማሪዎች ጭምር ይህን እድል ቢያመቻችላቸው ጥሩ ነው የሚል አስተያየት አለኝ ሁሉንም ግን አመሰግናለሁ፡፡   

     የአዲስ አበባ ከተማ መስተዳድር ጤና ቢሮ ከአስትራዜንካ ጋር በመተባበር በሳምንቱ አጋማሽ ላይ በስድስት ክፍለ ከተሞች  ነፃ የደም ግፊት ምርመራዎችን አከናወነ፡፡ በአዲስ አበባ የተለያዩ ክፍለ ከተሞች የተካሄደው የነፃ ምርመራ አገልግሎት በአህጉራዊው ተቋም አስተርዜንካ ልዩ ፕሮግራም ሔልዚ ኸርት አፍሪካ (HHA) አማካኝነት ሲሆን በመላው ዓለም ከሚከበረው የዓለም የደም ግፊት ቀንን ምክንያት በማድረግ የተከናወነ ነው፡፡
“በደም ግፊት ማም ሰው መሞት የለበትም” በሚል መርህ የሚንቀሳቀሰው አስትራዜንካ፤ ከኢትዮጵያ የጤና ጥበቃ ሚኒስቴር ጋር በአጋርነት ለመስራት ስምምነት ያደረገው ባለፈው ዓመት ሲሆን በኸልዚ ኸርት አፍሪካ ፕሮግራሙ፣የደም ብዛት በሽታን ለመዋጋት የሚደረገውን እንቅስቃሴ ለማገዝ እንዲሁም በሽታውን ለመከላከል የሚያስችሉ የአሰራር መዋቅሮችን ከአገሪቱ የጤና አስተዳደር ጋር አጣጥሞ ለማከናወን ድጋፍ እየሰጠ ይገኛል፡፡
በዚህ መሰረትም ከዓመት በፊት ከመላ አፍሪካ የተውጣጡ ታዋቂ የህክምና ባለሙያዎች ወደ ኢትዮጵያ መጥተው በአገር አቀፍ ደረጃ በመንቀሳቀስ ለሃኪሞችና ሌሎች የጤና ባለሙያዎች እንዲሁም የህክምና ተቋማት የግንዛቤ ማስጨበጫና የስልጠና መድረኮችን በማዘጋጀት ሰርተዋል፡፡ የአስትራዜንካ ኸልዚ ኸርት አፍሪካ ፕሮግራም ከኢትዮጵያ በፊት በጎረቤት  አገር ኬንያ ተግባራዊ በመሆን ከፍተኛ ውጤት እንደተገኘበትም ለማወቅ ተችሏል፡፡ ሰሞኑን ‹‹የዓለም የደም ግፊት ቀን››ን ምክንያት በማድረግ በተከናወነው ነፃ የደም ግፊት ምርመራ ተጠቃሚ የሆኑት የጤና ማዕከላት በየካ፤ በልደታና አብነት፤ በአዲሱ ገበያ፣ፒያሳና ቀጨኔ፤ በሩፋኤል ማዞርያ በቃሊቲና አቃቂ የሚገኙ እንደሆኑ ታውቋል፡፡ አስትራዜንካ  የኸልዚ ኸርት አፍሪካ ፕሮግራምን በማከናወን ለ900 የጤና ባለሙያዎችና የህክምና ድጋፍ ሰጪዎች ስልጠና የሰጠ ሲሆን በሰባት የአገሪቱ ክልሎች በሚገኙ 12 ሆስፒታሎችና 36 የጤና ማዕከላት የተቀናጀ የአሰራር መዋቅርን መዘርጋቱ ታውቋል፡፡
ባለፈው አንድ ዓመት ለ100ሺ ሰዎች ነፃ የደም ግፊት ምርመራ በማካሄድ 13ሺ ግለሰቦች በሽታው እንዳለባቸው ለመጀመርያ ጊዜ ያረጋገጠው ፕሮግራሙ፤ከደም ግፊት ጋር በተያያዘ ደረጃውን የጠበቀ ህክምና፤ እንክብካቤና የተሟላ አገልግሎት የሚሰጥበትን ሁኔታ በመላው ኢትዮጵያ ለማስፋፋት በትኩረት እየሰራ እንደሚገኝ ለአዲስ አድማስ በላከው መግለጫ አስታውቋል፡፡
የደም ግፊት ለልብ ህመምና ሌሎች ተያያዥ በሽታዎች የሚያጋልጥ ሲሆን የዓለም ጤና ድርጅት እንደሚያመለክተው፤በአፍሪካ ከደም ግፊት ጋር በተያያዘ ያለው የግንዛቤ ማነስ በበሽታው የሚከሰተውን የሞት አደጋ አሳሳቢ አድርጎታል፡፡  

Sunday, 21 May 2017 00:00

ጉድ‘ኮ ነው! አሰፋ ጫቦ

  ሲያስቡት? ጉድ! እንዲያው ጉድ እኮ ነው!
ያንዱ ሥጋ ወነፍስ፣
የሌላው ቀለብ፣ ድግስ፤
ምሳ ራት ቁርስ፡፡
እኔኮ የሚገርመኝ፣
የሚከነክነኝ፣
      ይኸ ሰርቶ አፍራሹ
ፈጣሪው ደጋሹ     
ከያሊው ፈዋሹ፡፡
ያኔ ሲነገር፣ ስንማር፣ ስንመከር፣
ምሉእ በኩሌሐ
ወይትባረከ ሰመ ስብቲሐ
እስመ አልቦ ነገር አሚረ ኩሉ
መአቱ የራቀ ምህረቱ ሙሉ
ብለው አሳምነው አልነበር?
ያልነገሩን ተረፈሪ ሚስጥር ነበረ?
ምነው ልቤ ጠረጠረ?
ሰማይን ያለባላ፣ ያለምሶሶ
ምድርን ያለካስሚያ፣
የዘረጋ፣ የወጠረ፣
ኁልቆ መሳፍርቱን የፈጠረ፣
ዝንፍ፣ እልፍ የማይል
      የማይልበት
የወርቅ ሚዛን ያለው፣
     የሚለካበት፣
የውሃ ልክ ያለው የሚለስንበት፣
             የተባለለት፡፡
አድሎ የሌለበት፣
ከዘላለም በፊት የነበር፣
ከዘላለም በኋላም የሚኖር፣
ህጸጽ አልባ ሚስጢር፣
ነው-ው-ው! ተብየም አልንበር?!
እና!? እኮ!? ያ ሁሉ የት ሔደ?
እንደጉም በነነ? እንደኬላ ተናደ?
ይኸው ነው የዚያ ሁሉ ስብከት ውጤት?
አንዱ የሌላ ቁርስ ምሳ ራት
ማነው ስቶ ያሳተኝ?
ካናቱ ወደ ደቀ መዛሙርታት?
 
ልቤ የሚጠረጥረው?
እንዲያው ድንገት ለምናልባት፣
ባራያ በምስሉ የፈጠረን ለት፣
ሲወጥር፣ ሲተክል፣
ሲያቆም ሲጥል፣ ሲነቅል፡፡
ሲዘረጋ፣ ሲሸበሽብ፣
ጎንበስ ቀና እስኪያልብ፡፡
ቀና ደፋ ሲል ደክሞት፣
ታክቶት፣ ሰልችቶት፣
የሰአት እላፊም ደርሶበት፣
ሲጣደፍ ኮታ ለመሙላት፣
ጀምበር ጠልቆ፣ መሽቶበት፡፡
አላልቅ ብሎ ሲጣደፍ፣
ለሚኒሞው ገረፍ ገረፍ፣
በዊክ ኤንድ ለማረፍ፡፡
በድንግዝግዙ ለድንገት ዞር ባለበት፣
ሚዛኑ ላፍታ፣ ለድንገት
ደፋ፣ ቀና፣ አለበት?
ተንጋዶ? ሔድ መለስ አለበት?
ላንዳች ቅጽበት፣ ሰውን ፈጠርኩ ባለበት?
እንጅማ!
እንደ መሸታ ስራ ሠንካላ፣
በቅጡ ያልበሰለ ያልተብላላ፣
ተሟሽቶ ያልተሞከረ፣ ያለየ፣
ጉዳት ጠቀሜታው ያልታየ፣
ሰንካላ፣ ግርድፍ፣ ያልተበራየ፡፡
በቃ ሂድ፣ ወግዱ፣
ከዚህ ጥፉ፣
ብሉ፣ ተባሉ፣
ምድርንም አጥፉ!
ይኸውልህ! እች ያንተ ነፍስ፣
ትሁን ለነንትና ድግስ፤
ምሳ፤ራት፣ቁርስ፣
ነውር አይደለም እንዴ በኔ ሞት!?
ተፈቶ ይለቀቃል እንዴ መጠፋፋት?
መተላለቅ መሟሟት?
ደሞም!
ስራውን አያቅም፤
አይችልምም አልተባለም!!
እኔማ የሚገርመኝ
መንጋ ጉሮሮ ከፍቶ፣
መዝጊያ፣ መቀርቀሪያ ሳይሰራ ትቶ
ግበረ-በላ አብዝቶ፣ ለቆ ፈቶ፣
ቀለብ ሳይሰራለት፣ ሳይቀርጥለት፣ ሳይሰፍርለት፣
እንዲኖር ተናንቆ፣
ተነጣጥቆ፣
ተጠባብቆ፡፡

ጎብዝ! እኔ የምለው!
ምነ አንድ እድል ቢሰጠን፣
ያለፈውን፣ ያለውን፣
ሙከራ ነበር! ተሞክሮ ነበረ፤
አልተሳካም ከሸፈ ከሰረ!
ፋይሉም ፋብሪካውም ይዘጋ፣
ይቆጠር እንዳልነበረ፡፡
እናም እንዳያዳግም፣ እንዳያደጋግም፣
በትርፍ ሰአት ክፍያም ቢሆንም፡፡
ስድስቱ ቀን ቀርቶ፣
አዲስ ተዘርቶ፣ ታጭዶ፣ ተወቅቶ፣
አብሲት ተጥዶ፣ በቅጡ ቦክቶ፣
ስምንትም ይሁን ሰማኒያ ቀን ተፈጭቶ፣ ተፋጭቶ፣
ሰውን የሚያክል ነገር አደል?
የፍጥረታት የበላይ አካል?
የሚፈጠር ባምላክ አምሳል?
አዲሱ ሰው ይሰራ ቢባል!?
አንገቱን ረዘም መለል ማሰኘት፣
ተነቃናቂ ተጣጣፊ ብሎ ማስገባት፣
ለስላሳ ኩሺኔትም ጨምሮ መክተት፣
ዙርያ-ገቡን ሁሉ-ገቡን እንዲያይበት፣
እዝነ ልቦናውም አይነ ልብናውም፤
ዳጎስ፣ ጎላ ቢልለት፤
የሰማው ያየው፤ እንድያርበት፣ እንዲያድርለት፤
እንዲሰነብት፤ እንዲሰነባብት፡፡፡
ዘኃለፈ ሰርየትም እንዲለበት፣
ከማት አምጭነት እንዲታቀብበት!
ሰፋፊ ልብም፣ ልቦናም የሰጠው!
ትልቁ ቱቦ፣ ትልቅ ቧንቧ ያለው፤
ሰው የሚሔድበት፤
ሰው የሚመጣበት፡፡
ሰው የሚመላለስበት፣
ሰው አድሮ የሚውልበት፣
ሰው የሚታቀፉበት፣
ሰው የሚታቀቡበት፣
…. የሚሰነባብትበት!
የሰራ አካላቱ እንዲሁ፣
…. ዚኒ ከማሁ፡፡

ወይስ ከነአካቴው!
እንበል እንዴ ሰሪም ተሰሪም፣
ፈጠሪም ተፈጣሪም አልነበረም!?
ይኽ ክርቲካል ማስ ያሉት ሲገጣጠም፤
ሰኔና ሰኞ ፍጥምጥም!
አስቀድሞ የነበር፣ ያልነበር አንድ ትልቅ ዝም!
አንድ ቀን ቡም! ቡም! ቡ-ም-ቡ-ም!
………… ቡምቡም!
መሰባሰብ! መጠረቃቀም!
ከመሀል አልቦ የትም!
ወደዝንተ አለም ምንም!
ወደ ዘላለም እርም!
…. አበስኩ! ገበርኩ!
April 1,1995
Los Angeles, California, USA

 እንዴት ሰነበታችሁሳ!
ሰውየው መሥሪያ ቤት ውሎ ቤቱ ይገባል፡፡ መሥሪያ ቤት ደግሞ ስብሰባ ነበር፣ ለሦስተኛ ቀን። ቤቱ ሲገባ ሚስት ሆዬ ግንባሯን ከስክሳ “ማነሽ፣ እራት አቅርቢለት…” ብላ የአቴዝና ባህርን  መጨረሻ ለማየት ቴሌቪዥኗ ላይ ማፍጠጥ፡፡
እሱ ሆዬ “ኤሊፍን ስንገላገል ባህር የሚሏት መጣችብን!” እያለ ቀመስ፣ ቀመስ አድርጎ መኝታ ቤት ይገባል፡፡ የዕለት ማስታወሻውን ያወጣል…ይጽፋልም፡፡ ይሄ የዕለት ማስታወሻ ከዕለታት አንድ ቀን ‘ለልማት ተብሎ የሚፈርስ ጎጆ ስር’ (ቂ…ቂ…ቂ…) መገኘቱ አይቀርም፡፡ ቀኑ ይጻፋል፣ ይጀመራልም፡፡
ደከሞኛል በጣም ደክሞኛል፡፡ ሰሞኑን በስብሰባ ተንበሸበሽናል፡፡ የስብሰባ ብዛት አንገት ቀና የሚደረግ ቢሆን ኖሮ ይሄኔ አንገታችን ፕሉቶ ማዶ አዲስ ወደተገኘችው ፕላኔት ይደርስ ነበር፡፡ ምን ላድርግ፣ ልቀልድ እንጂ!
በአሁኑ ሰዓት የምፈልገው መኝታዬ ውስጥ ገብቼ ጥቅልል ብዬ መተኛት ነበር፡፡ ግን የዕለት ማስታወሻዬን መጻፍ አለብኝ፡፡ ምክንያቱም…እንደ እውነቱ አሁን ስምንተኛው ሺህ ለመድረሱ እርግጠኛ ነኝ፡፡ ስምንተኛው  ሺህ ባይደርስ ኖሮ እንዲሀ መጫወቻ አንሆንም ነበራ!
የአዳራሹ ግድግዳ ጨርቅ ላይ በተጻፉ መፈክሮች ተዥጎርጉሯል፡፡ ጠረዼዛው በባንዲራና በወረቀት መፈክሮች ተብለጭልጯል፡፡
‘የተጀመረውን ልማት አጠናከረን ለማስቀጠል በቁርጠኝነት እንሠራለን…’ ይላል ትልቀኛው መፈክር። ደግነቱ “እስከ ዛሬ የምትሠሩት በቁርጠኝነት አልነበረማ!” ብሎ የሚመጣ ቢኖር ምን እንል ይሆን ብሎ የሚጨነቅ የለም፣ ጠያቂ አይኖርማ!  የጊዜው የስብስባ ‘ኮምፐልሰሪ’ መፈክር ከተለጠፈ በቂ ነው፡፡  ስብሰባ አዳራሹ በሰው ጢም ብሏል…‘የቀረ ሰው ይጠቆራል’ ስለተባለ የቀረ የለም፡፡ በሰበብ አስባቡ የሚያስጠቁር በበዛበት ዘመን ማን ጥርስ ውስጥ ይገባል! ደግሞ ዘንድሮ ስብበሳ አዳራሽ የምንቀመጠው እየበዙ በሄዱ ‘መለኪያዎቻችን’ በመፈላላግ ሆኗል፡፡ እንደ አንድ መሥሪያ ቤት የሥራ ባልደረቦች ሳይሆን እንደ ቤተ ዘመድና እንደ ‘አገር ልጅ’ ተፈላልገን ትከሻ ለትከሻ መግጠም የጋራ መግባቢያ አይነት ነገር የሆነ ይመስላል፡፡ በተለይ ይቺ ‘የአገር ልጅነት’ መፈላለግ በየስፍራው እየገባች ግራ እያጋባችን ነው፡፡
ሦስት ሰዓት የተጠራው ስብሰባ አራት ሰዓትም አልተጀመረም፡፡ የክብር እንግዳው አልመጣማ! የእሱ መክፈቻ ንግግር ከሌለበት ስብሰባው ለአቅመ የምሽት ዜና አይበቃማ!
አብዛኛውን ጊዜ የክብር እንግዳ የሚባሉት ወይ የመሥሪያ ቤቱ ሥራ አስኪያጅ ወይም ዳይሬክተር ናቸው፡፡ ቆይማ…ሰዎቹ በድርጀቱ ፔይሮል ላይ እየፈረሙ ደሞዝ የሚነጩ ሠራተኞች አይደሉም እንዴ! ታዲያ ‘የክብር እንግዳ’ የሚለው ቅጥያ ምን አመጣው! በገዛ ቤታቸው!
እንደዛም ሆኖ ሰዓት አክብሮ ቢመጣ ጥሩ፡፡ እሱ ልክ ለአራት ሰዓት ሰባት ደቂቃ ሲቀረው ይመጣል፡፡ (አርፍዶ መምጣት ‘የክብር እንግድነት’ አንዱ መለያ የሆነ ይመስላል፡፡) እናማ…ጭብጨባ ይጀመራል። ከበሩ ጀምሮ መቀመጫው እስኪደርስ ድረስ በጭብጨባ እናጅበዋለን፡
የሰለቸኝ ይሄ ጭብጨባ ነው፡፡ የአሥር ሺህ ሜትር ሬከርድ አልሰበረ!… ማራቶን ከሁለት ሰዓት በታች አልገባ! በቃ፣ እንደኛው የድርጅቱ ቅጥር ሠራተኛ ነው፡፡ እንደውም በየቢሯችን ስለ እሱ የምንንሾካሾከው ነገር አደባባይ ቢወጣ፣ ካሊም ተከናንቦ ቤቱ ይከረቸም ነበር፡፡ ለነገሩ አብዛኞቻችን የምናጨበጭበው ‘ላለመጠቆር’ ነው፡፡ ሰው ሁሉ ሲያጨበጭብ እኛ ዝም ብለን ከቆምን አለቀልና! የዚህ አገር ነገር እንደዚህ ሆኗላ! “ትጉህ ሠራተኛ ነው?” ከማለት ይልቅ “ትጉህ ደጋፊዬ ነው?” የሚለው ጥያቄ ይቀድማላ!
ቀጥሎ የስብሰባ መሪው የአስተዳደርና የፋይናንስ ኃላፊው ወደ መናገሪያው ሲሄድ እሱንም በጭብጨባ እናጅበዋለን፡፡ ቲማቲም ሲወደድ ጭብጨባ የረከሰባት አገር! …ቂ…ቂ…ቂ…
መሥሪያ ቤቱ ውስጥ የምድር ኑሯችንን የገሀነም የሰቆቃ ኑሮ አደረግብን የምንለው አንዱ የአስተዳደርና የፋይናንስ ኃላፊው ነው፡፡ የስብሰባ መሪ ሆኖ ሳንወድ ያስጨበጭበናል! እሱ በ‘ውሀ ቀጠነ’ ደሞዝ የቆረጠብን ሰዎች ብንሰባሰብ አንድ ዕድር መመስረት እንችላለን፡፡ የዛሬ ዓመት የደሞዜን እሩብ ሲገነድስብኝ “ሆድ ይፍጀው” ብዬ ዝም ብያለሁ፡፡ ዝም ባልልስ ምን እንዳላመጣ!
ጉሮሮውን አሥር ጊዜ ያጠራል፡፡
ታዲያላችሁ…የክብር እንግዳውን ልክ በሆነ ነገር ኦስሎ ላይ የኖቤል ሽልማት ተሸልሞ የተመለሰ ይመስል አናታችን ላይ ይቆልለዋል፡፡ “ውድ ጊዜዎን ሰውተው በዚህ ስብሰባ ላይ በክብር እንግድነት በመገኘትዎ በድርጅቱ ሠራተኞችና በራሴ ስም የከበረ ምስጋናዬን አቀርባለሁ፣...” ይላል፡ እንደፈረደብን አዳራሹን በጭብጨባ እናናጋዋለን፡፡ ወይም… ‘ከስብሰባ የቀረ አስተዳደራዊ እርምጃ ይወሰድበታል’ የሚለው ማስጠንቀቂያ ተሻሽሎ… ‘ከስብሰባ የቀረ፣ ተገኝቶም ያላጨበጨበ’ በሚል ይስተካከል፡፡ ሌላ ጊዜ “በቃሪያ ጥፊ ባጠናገርኩት እንዴት ደስ ይለኝ ነበር!” የምንለውን ሰው በጭብጨባ ትከሻው ላይ የኮከብ መአት እንደረድርለታለን፡፡
ሌላው ደግሞ ሥራ አስኪያጁ “ውድ ጊዜዎን ሰውተው…” ብሎ ነገር ምን ማለት ነው! እሱም እንደ እኛ የመስሪያ ቤቱ ሠራተኛ አይደለም እንዴ!….የእሱ ጊዜ ‘ውድ’ ሲሆን የእኛ ‘ርካሽ’ ነው ማለት ነው! እናማ…ብዙ ጊዜ የክብር እንግዶች ለስብስባው የሚያመጡት የተለየ ግብአት የለም፡፡ ያው “የዛሬውን ስብሰባ ልዩ የሚያደርገው…”
“በተያያዝነው የእድገት ጎዳና…”
“ከመካከለኛ ገቢ አገሮች ጎን ለመሰለፍ…ምናምን የሚሉ ሀረጋትን መደርደር ነው፡፡
የእኛም ሥራ አስኪያጅ ሁሉም በገዛ ድርጅታቸው ‘የክብር እንግዳ’ የሆኑ ሥራ አስኪያጆች የሚያደርጉት ንግግር ይደርጋል፡፡ በአንድ ሺህ አንድ ችግሮች የተተበው መሥሪያ ቤታችን፤ “በእውነቱ የሠራተኛው የሥራ ፍላጎትና ትጋት ለሌሎች ምሳሌ የሚሆን ነው፣” ይላል፡፡ ምነው፣ ስንተዋወቅ! የእኛ ድርጅት ለሌላው ምሳሌ ከሆነ፣ በርከክ ያለች አገር አንደኛዋን በእንትኗ ዘጭ ነው የምትለው፡፡
ሌላ ግራ የሚገባኝ ነገር ደግሞ የዘንድሮ ‘የስብሰባ ቋንቋ!’ “መሥሪያ ቤቱ የእድገት አጀንዳውን ለማስቀጠል ከባለድርሻ አካላት ጋር በጋራ ሆኖ ለስኬት ለማብቃት…” ምናምን የሚሉት ፈሊጥ አለ፡፡ እኔ የምለው…ለምን በሌላ አቀራረብ ሊሉት አይሞክሩም! ለምን ድግምግሞሽ እንደሚያሰለች አውቀው ለየት ለማለት አይሞክሩም! ሁሉም ሰው “ደመቅሽ አበባዬ…” እያለ መዝፈን አለበት እንዴ! አሀ… አንዱ “ደመቅሽ አበባዬ…” ካለ ሌላኛው  “አገሯ ዋርሳ መገና…” ለምን አይልም!
ስብሰባው ዛሬ ሦስተኛ ቀኑ ነበር፡፡ ነገ ያልቃል ተብሏል፡፡ ሥራ አስኪያጁ ትናንት ከ‘በላይ አካል’ ምን እንደተባለ እንጃ ዛሬ ሲያንጫጫን ዋለ፡፡ ስብሰባውን ሲከፍት ለሌሎች ምሳሌ እንደምንሆን ሲነግረን የነበረ ሰው፣ ዛሬ ቀኝ ኋላ ዞሮ የእኛንም ናላ አዞረው፡፡ “በዘንድሮ ዓመት ድርጀቱ የእቅዱን ሀምሳ ሦስት ነጥብ ሰባት በመቶ አሳክቷል፡፡”
አጨበጨብን፣ ልባችን እስኪጠፋ አጨበጨብን። ምን! ለሀምሳ ሦስት በመቶ ጭብጨባ! እንደውም ከእቅዳቸው ከሰማንያ በመቶ በታች የሚያስመዘግቡ ሁሉ አይደለም ማጨብጨብ በሀዘን የአንድ ደቂቃ የህሊና ጸሎት ማድረግ ነበረባቸው፡፡
ከዚያም አለቃችን “በመሆኑም፣ ድርጀቱ በዚህ ዓመት ቦነስ መስጠት አይችልም፡፡”
አናጋነዋ! አዳራሹን በተቃውሞ ጫጫታ አናጋነዋ! አይደለም ሀምሳ ሦስት ለምን ሀያ ሦስት በመቶ አይሆንም… ለምንድነው ቦነሳችንን የሚከለክሉን! ለእሱ በየወሩ መኪና ይለዋወጥለት የለ እንዴ! በዓመት ውስጥ የቢሮው ምንጣፍ ስንቴ ነው የተለወጠው!  ለሥራ ጉዳይ ተብሎ ስንት አገር እየዞረ ሲዝናና ከርሞ የለም እንዴ!  
ይሄ ሁሉ ገንዘብ ከየት መጣ?
ማጉረመረማችን ጠንከር ሲል አለቃችን… “ይህ እኮ የስብሰባ ቦታ ነው፣ መርካቶ አይደለም..” ብሎ ሲቆጣ በአብዛኛው ድምጻችን ቀነሰ፡፡ ጥቂት ሰዎች ግን ማጉረመረማቸውን ቀጠሉ፡፡ ይሄኔ… “እዚህ አዳራሸ ውስጥ ሆነ ብለው ስብሰባውን ለመረበሽ የሚፈልጉ የእነእንትና ተላላኪዎች አሉ…” ሲል የሰፈነው ጸጥታ ትንኝ ብታነጥስ ይሰማ ነበር፡፡ ነገ ስብሰባው ይዘጋል፡፡ ምን በሚባል ሆቴል የእራት ግብዣ አለን ተብሏል፡፡
“ለእኛ ቦነስ የጠፋ ገንዘብ ለግብዣ ከየት መጣ?” ብለን አንቃወምም፡፡“ከእቅዳቸን ሀምሳ ሦስት በመቶ ብቻ አሳካን ተብሎ የምን በገንዘብ ጨዋታ ነው!” አንልም፡፡
“ለእራት የሚወጣው ገንዘብ ለተሰባበሩት ወንበሮችና ጠረጴዛዎች መጠገኛ አይውልም!” አንልም፡፡
እንበላለን፡ እንጠጣለን፡፡ የአለቆቻችንን የዘወትር ኑሮ እኛ በዓመት አንድ ምሽት ብናየው ምናለበት!
ደግሞ…አይ ባለቤቴ እየመጣች ነው፡፡ ይበቃኛል። ምነው የእሷ ፊትም እንደኔው ቀጨመ! ያ አቴዝ ባህርን ደግሞ ምን አድርጓት ይሆን! ልጄ… ስንት የደላው አለ!
እንግዲህ ይኸው ነው… እንሰበሰባለን፣ እናጨበጭባለን ‘እንክት አድርገን’ እራት እንበላለን! ቀን በነገር የምንሞላው ሳያንስ… ማታ በእራት ‘ሆዳችንን የሚሞሉልን’ እንደ ቦነስ እየቆጠሩት ይሆን እንዴ!
እንዲህም ሆኖ የዕለት ማስታወሻው ተገባደደ፡፡ አራት ነጥብ፡፡
ደህና ሰንብቱልኝማ!