Administrator

Administrator

  የኡጋንዳ ፖሊስ ባለፈው ረቡዕ የዓለም የፕሬስ ነጻነት ቀንን ለማክበር በመዲናዋ ካምፓላ ወደሚገኙ ጎዳናዎች ከወጡ የአገሪቱ ጋዜጠኞች መካከል ስድስቱን ማሰሩን ኒውስዊክ ዘግቧል፡፡
የዓለም የፕሬስ ነጻነት ቀን የት ይከበር በሚለው ጉዳይ ላይ በኡጋንዳ የጋዜጠኞች ማህበር አመራሮች መካከል ልዩነት መፈጠሩን ተከትሎ፣ የተወሰኑ የማህበሩ አባላት ዕለቱን ለማክበር ወደ አደባባይ ወጥተው በአመራሮቻቸው ላይ ተቃውሟቸውን ባሰሙበት ወቅት የከተማዋ ፖሊስ “ሰልፉን ለማካሄድ ህጋዊ ፈቃድ አላገኛችሁም” በሚል ስድስት ያህል ጋዜጠኞችን ማሰሩን ዘገባው ጠቁሟል፡፡
የከተማዋ ፖሊስ በፕሬስ ነጻነት ቀን በጋዜጠኞች ላይ የወሰደው እርምጃ የመንግስት ባለስልጣናትን ማስቆጣቱን የጠቆመው ዘገባው፣ ባለስልጣናቱ ባስተላለፉት ፈጣን ትዕዛዝ ጋዜጠኞቹ ክስ ሳይመሰረትባቸው በሰዓታት ልዩነት ከእስር እንዲለቀቁ መደረጉንም ዘገባው አክሎ ገልጧል፡፡
ሪፖርተርስ ዊዝአውት ቦርደርስ የተባለው አለማቀፍ ተቋም ባለፈው ሳምንት ባወጣው የ2017 የአለማችን አገራት የፕሬስ ነጻነት ደረጃ  መሰረት፤ ኡጋንዳ በፕሬስ ነጻነት ከአለማችን 180 አገራት 112ኛ ደረጃን መያዟንም ዘገባው አስታውሷል፡፡

  በፌስቡክ የማህበራዊ ድረገጽ በኩል ጽንፈኝነትን የሚያስፋፉና አንባቢያንን የሚያሸብሩ መልዕክቶችን የሚያሰራጩ ተጠቃሚዎችን የሚያድኑና እርምጃ የሚወስዱ ተጨማሪ 3 ሺህ ተቆጣጣሪ ሰራተኞችን ቀጥሮ ሊያሰማራ እንደሆነ ዘ ጋርዲያን ዘግቧል፡፡
ከቅርብ ጊዜ ወዲህ የፌስቡክ ተጠቃሚዎችን ወደ ጽንፈኝነት የሚስቡና የፍርሃትና የመሸበር ስሜትን የሚፈጥሩ መልዕክቶችና ቪዲዮዎች በከፍተኛ ሁኔታ እየተበራከቱ መምጣታቸውን ተከትሎ፣ የኩባንያው መስራች ማርክ ዙከርበርግ ጉዳዩን ለመግታት በማሰብ፣ ተጨማሪ ተቆጣጣሪዎችን ቀጥሮ ወደ ስራ እንደሚያስገባ ባለፈው ረቡዕ አስታውቋል፡፡
ተጠቃሚዎች መሰል መልዕክቶችንና ቪዲዮዎችን በፌስቡክ ላይ ሲያገኙ በአፋጣኝ ለኩባንያው 4ሺህ 500 ያህል ተቆጣጣሪዎች ጥቆማ መስጠት የሚችሉበት አሰራር ተቀይሶ እየተሰራበት እንደሚገኝ የተነገረ ሲሆን ኩባንያው ድርጊቱን በፈጸሙ ተጠቃሚዎች ላይ አፋጣኝ እርምጃ እንደሚወስድም ተነግሯል፡፡
ፌስቡክ በየሳምንቱ በሚሊዮኖች የሚቆጠሩ መሰል ጥቆማዎችና የቅሬታ መልዕክቶች እንደሚደርሱት የዘገበው ዘ ጋርዲያን፣ እነዚህን በርካታ ጉዳዮች አጣርቶ አፋጣኝ ምላሽ ለመስጠት እንዲችል እስከ አመቱ መጨረሻ ድረስ ተጨማሪ 3 ሺህ ያህል ተቆጣጣሪዎችን ለመቅጠር ማቀዱንም ገልጧል፡፡

 አቶ ዳጂ ጃራ ኩምቢ በተባሉ ባለሀብት በአዳማ ከተማ ወንጂ መታጠፊያ ላይ የተሰራውና 55 ዘመናዊ የመኝታ ክፍሎች ያሉት ደንበል ቪው ኢንተርናሽናል ሆቴል ዛሬ ይመረቃል፡፡ ሆቴሉ ሁሉም ነገር የተሟሉለት ሱትስ፣ 2 ደሉክስ ቲውን፣ 21 ደሉክስ ስታንዳርድ፣ 13 ሲንግል ስታንዳርድና 12 ሲንግል ክፍሎች ሲኖሩት፣ ከ30 እስከ 300 ሰዎች ማስተናገድ የሚችሉ 4 አዳራሾች አሉት፡፡ ክፍሎቹ፣ ቲቪ፣ ስልክ፣ ጠረጴዛና ወንበር፣ ሶፋ፣ ሻወር፣ ነፃ ዋይፋይ … ያሉት ሲሆን እንግዶችን የሚያረካ አገልግሎትና መስተንግዶ ለመስጠት እየተጠባበቀ ነው ተብሏል፡፡

   ‹‹ለሠራተኞቻችን በምንሰጠው ልዩ ትኩረት እንለያለን››
                      
     በእንግዶች፣ በሠራተኞችና አብረውት በሚሰሩ ባለድርሻ አካላት ተመራጭ እንዲሆን በትጋት እንደሚሰራ የጠቆመው ሳፋሪ አዲስ ሆቴል፤ የዛሬ ሁለት ሳምንት በይፋ ሥራ እንደሚጀምር ተገልጿል።
የሳፋሪ አዲስ ሆቴል ልዩ አማካሪ አቶ ዜናዊ መስፍንና የሆቴሉ ማኔጅመንት አባላት ባለፈው ማክሰኞ በቦሌ መንገድ ከቴሌ ዝቅ ብሎ በሚገኘው የሆቴሉ አዳራሽ ለጋዜጠኞች በሰጡት መግለጫ፤ የሆቴሉ ዓላማ ልዩ አገልግሎት በመስጠት በሆቴል ኢንዱስትሪው ላይ ከፍተኛ አስተዋጽኦ ማድረግና የአገሪቱን ቱሪዝም ገጽታ መቀየር ነው ብለዋል፡፡
በ1,3000 ስኩዌር ሜትር ላይ ያረፈው የዚህ ሆቴል ግንባታ 6 ዓመት እንደፈጀ የጠቀሱት የሆቴሉ ልዩ አማካሪ አቶ ዜናዊ፣ አሁን ዝግጅቱን አጠናቅቆ ግንቦት 5 በይፋ ስራ ይጀምራል ብለዋል፡፡
ሳፋሪ ማለት እንደ ወርቅ፣ አልማዝ፣ ፐርልና መሰል ማዕድናት የከበረ ድንጋይ ስያሜ ነው ያሉት ልዩ አማካሪው፤ ላለፉት 30 ዓመታት በወርቅና የከበሩ ድንጋዮች ንግድ ላይ ተሰማርተው የቆዩት የሆቴሉ ባለቤት አቶ ፍስሐ አባይ፣ ለሥራቸው ክብርና ማስታወሻ ይሆን ዘንድ ሆቴሉን ‹‹ሳፋሪ›› ብለው መሰየማቸውን ገልጸዋል፡፡
ሆቴሉ ዓለም አቀፍ ደረጃቸውን የጠበቁ 64 ደሉክስ፣ 8 ባለ ሁለት አልጋ (ትዊንስ)፣ 26 ሱትና 24 ስታንዳርድ የመኝታ ክፍሎች ሲኖሩት፣ ረዥም ጊዜ የሚቆዩ እንግዶች፣ ምግባቸውን የሚያዘጋጁባቸው 8 አፓርትመንት ክፍሎች ከተሟላ የወጥ ቤት ዕቃዎች ጋር ተደራጅተው ይጠብቋቸዋል፡፡
2 ሬስቶራንቶችና 3 ባሮች ያሉት ይኼው ሆቴል፤ ከ20-50 ሰዎች ማስተናገድ የሚችሉ አራት አዳራሾች ያሉት ሲሆን በሆቴሉ ላረፉ እንግዶችና ለውጭ ተጠቃሚዎች የጂምናዚየምና የስፓ  (ስቲም፣ ሳውና፣ ጃኩዚ ማሳጅ) አገልግሎት በባለሙያ ይሰጣል፡፡  ለወንዶችና ለሴቶች የፀጉር ውበት፣ የእጅና የእግር ጥፍር ማስዋቢያ አገልግሎት እንደሚሰጥም ታውቋል፡፡
ሆቴሉ፣ 60 መኪኖችን ማቆም የሚችል ስፍራ ሲኖረው፤  ቦታው በሆቴሉ ለሚያርፉና ለውጭ እንግዶች ይበቃል ወይ? ተብለው የተጠየቁት አቶ ዘናዊ ሲመልሱ፤ ‹‹ሆቴሉ ቢዝነስ ስታይል ነው። በርካታ መኪና ማቆሚያ የሌላቸው የዚህ ዓይነት ሆቴሎች በአሜሪካም ሆነ በሌሎች አገራት በብዛት አሉ›› ብለዋል፡፡
በግንባታ ወቅት ለ700 ሰራተኞች የሥራ ዕድል እንደፈጠረ የጠቀሱት ልዩ አማካሪው፤ ‹‹ ግንባታው ሙሉ ለሙሉ ተጠናቅቆ በሙሉ አቅሙ ሥራ ሲጀምር ከ200-230 ለሚሆኑ ዜጎች የሥራ ዕድል ይፈጥራል፤ ሳፋሪ አዲስ፤ ለሠራተኞቹ የላቀ ልዩ ትኩረት ይሠጣል›› ብለዋል፡፡
እኛን ልዩ ከሚያደርጉን ነገሮች አንዱ፣ ከእንግዳውም በላይ ለሰራተኞቻችን የምንሰጠው የቅድሚያ ትኩረት ነው፡፡ ምክንያቱም በማኔጅመንቱ አስተዳደር ደስተኛ ያልሆነ ሰራተኛ፤ እንግዶችን በጥሩ ሁኔታ አያስተናግድም፡፡ ስለዚህ ሠራተኞቹ፣ የባለቤትነት ስሜት ተሰምቷቸው፤ ‹‹ሆቴሉ የኛ ነው›› ብለው እንዲቀበሉ፣ ከደሞዝና ከደረጃ ዕድገት በተጨማሪ የተለያዩ ጥቅማ ጥቅሞችን ያገኛሉ፡፡ የስራ ላይና ከውጭ አገር ባለሙያ አስመጥተን ሥልጠና እንሰጣቸዋለን፡፡ በዚህ ዓይነት የሠራተኞችን ፍልሰት እንቀንሳለን ብለን እናምናለን›› ብለዋል- አቶ ዜናዊ፡፡
‹‹ከሠራተኞች 40 በመቶ ያህሉ ከዚህ በፊት ምንም ዓይነት የሆቴል ሥራ ልምድ የሌላቸውና እኛው እዚሁ ያሰለጠንናቸው ናቸው፡፡ የቀጠርናቸው ሰራተኞች ከትምህርና ከሥራ ልምድ ባሻገር ከ7 የሚበልጡ ዓለም አቀፍ ቋንቋዎች አቀላጥፈው የሚናገሩ ናቸው›› በማለት አስረድተዋል፡፡
ምናልባትም በአዲስ አበባ የመጀመሪያው እንደሆነ የሚነገርለት ግዙፍና እጅግ ዘመናዊ መሳሪያዎች የተገጠሙለት የላውንደሪ ክፍሉ፤ ለሠራተኞች ዩኒፎርም፤ ለእንግዶችና ለውጭ ተጠቃሚዎች አገልግሎት ይሰጣል ብለዋል፡፡

 በጋዜጠኛ ደራሲና የቋንቋ መምህር ደሳለኝ ማሰሬ የተሰነደው ‹‹የፍቅር ሳቅ›› የግጥም ስብስብ መፅሀፍ ገበያ ላይ ዋለ፡፡ መፅሀፉ ወጣቱን መሰረት ባደረጉ ማህበራዊ፣ ባህላዊና ፖለቲካዊ ጉዳዮች ላይ የሚያጠነጥኑ ከ60 በላይ ግጥሞችን ማካተቱ የመፅሀፉ አዘጋጅ ጋዜጠኛ የቋንቋ መምህርና ደራሲ ደሳለኝ ማስሬ
ለአዲስ አድማስ ገልጿል፡፡ በ96 ገፅ የተቀነበው መፅኀፉ በ40 ብር ከ50 ሳንቲም እየተሸጠ ሲሆን ደራሲው በቅርቡ ለንባብ የሚያበቃው የቋንቋ መፅሀፍ በመጠናቀቅ ላይ መሆኑንም ገልጿል፡፡

 70ኛው ግጥምን በጃዝ ረቡዕ ግንቦት 2 ቀን 2009 ዓ.ም ከምሽቱ 12 ሠዓት ጀምሮ በራስ ሆቴል ይካሄዳል፡፡
በዚህ ምሽት ላይ የስነፅሁፍ ምሁሩ ዶ/ር በድሉ ዋቅጅራ፣ ገጣሚ ተርጓሚና ጋዜጠኛ ነብይ መኮንን፣ ዲያቆን ዳንኤል ክብት፣ ፍቃዱ ተ/ ማርያም፣ ይታገሡ ጌትነት እና ኤልያስ ሽታሁን ይሣተፋሉ ተብሏል፡፡ በእለቱ በሽመልስ አበራ እና እታፈራሁ መብራቱ የተዘጋጀ አጭር ተውኔት እንደሚቀርብም ተጠቁሟል፡፡

  አራቱ የ1980ዎቹ ኮከብ ድምፃውያን ከሮሃ ባንድ ጋር ዘፈኖቻቸውን ያቀርባሉ

    ግንቦት 12ቀን 2009 ዓ.ም በግዮን ሆቴል ይካሄዳል በተባለው በዚህ የሙዚቃ ኮንሰርት ላይ በወቅቱ ‹‹ሁሉም ቢተባበር›› በሚለው የጋራ ዜማቸው ከፍተኛ ተወዳጅነትን ያተረፉትና የ1980ዎቹ አራት ምርጥ ድምፃውያን፡- አረጋኸኝ ወራሽ፣ ፀሐዬ ዩሐንስ፣ ፀጋዬ እሸቱና ንዋይ ደበበ እንደሚሳተፉበት የኮንሰርቱ አዘጋጅ ከትናንት በስቲያ በአዚማን ሆቴል በሰጡት ጋዜጣዊ መግለጫ ላይ ገልፀዋል፡፡
የኮንሰርቱ አዘጋጅ ታምር ማስታወቂያ ድርጅት ዋና ሥራ አስኪያጅ አቶ ሰለሞን መለሰ እንደገለፀው፤ የሙዚቃ ኮንሰርቱ በአገራችን ዘመናዊ የሙዚቃ ታሪክ ውስጥ ጉልህ ሥፍራ የነበራቸው ድምፃውያን ከሮሃ ባንድ ጋር በመሆን ያን ዘመን የሚያስታውሱ ሥራዎችን በሺዎች ለሚቆጠሩ አድናቂዎቻቸው ያቀርባሉ፡፡
የሙዚቃ ኮንሰርቱ ከተለመደው የሙዚቃ ኮንሰርት የተለየ መሆኑን የገለፀው አቶ ሰለሞን፤ ከእነዚህ ጉዳዮች መካከል በኢትዮጵያ የሙዚቃ ታሪክ ውስጥ ‹‹ወርቃማው ዘመን›› እየተባለ በሚጠራው የ1980ዎቹ ዓመታት ያለፉ በዘመኑ ምርጥ የተባሉ የሙዚቃ ሥራዎችን ሲያጣጥሙ የነበሩ አድናቂዎች ከሚወዷቸው ድምፃውያን ጋር የሚገናኙበትን እድል የሚፈጥር መሆኑ ዋንኛው ነው ብሏል፡፡ ድምፃውያኑ ከሮሃ ባንድ ጋር በጋራ በሚያቀርቡት በዚህ የሙዚቃ ኮንሰርት ላይ ከ10ሺ በላይ ታዳሚዎች ይገኙበታል ተብሎ ይጠበቃል፡፡ ከኮንሰርቱ ገቢ 10 በመቶ አገር በቀል ለሆኑ የእርዳታ ድርጅቶች ለመስጠት መታሰቡንም አቶ ሰለሞን ተናግረዋል፡፡
ከኮንሰርቱ መጠናቀቅ በኋላ የኢትዮጵያን ዘመናዊ ሙዚቃ ታሪክ የሚያስታውስና በተለይም በ1970ዎቹና 80ዎቹ መጨረሻ ድረስ ባለው ጊዜ ላይ ትኩረቱን አድርጎ የሚዘጋጅ የአንድ ሰዓት ትኩል ዘጋቢ ፊልም እንደሚዘጋጅና ሲዲውም ከኮንሰርቱ መጠናቀቂያ በኋላ በሚዘጋጅ የምስጋና ፕሮግራም ላይ እንደሚመረቅ የኮንሰርቱ አዘጋጆች በጋዜጣዊ መግለጫ ላይ ተናግረዋል፡፡ በአዲስ አበባ የሚዘጋጀው ኮንሰርት ከተጠናቀቅ በኋላ በ3 ዋና ዋና የክልል ከተሞች ተመሳሳይ የሙዚቃ ኮንሰርት ለማዘጋጀት ዕቅድ መያዙንም አቶ ሰለሞን ተናግረዋል፡፡

   · “ይሄ ማዕከል ተሰርቶ በነጋታው በሞትኩ” (አርቲስት ፋንቱ ማንዶዬ)
                      · “በሁሉም ከተሞች የአረጋውያን ማዕከላት ይገነባሉ”

          ሜሪ ጆይ የልማት ማህበር የዛሬ 8 ዓመት የአረጋዊያን ሁለገብ አገልግሎት ማዕከል ለመገንባት በሀዋሳ ከተማ 6 ሺህ ካ.ሜ ቦታ የተረከበ ሲሆን በ2003 ዓ.ም ግንባታው ተጀምሮ ዘንድሮ ተጠናቅቋል፡፡ የምረቃ ስነ-ስርዓቱ በመጪው ግንቦት 12 ይካሄዳል ተብሏል፡፡ የዛሬ ሁለት ሳምንት ቅዳሜ ከተለያዩ ሚዲያዎች የተውጣጡ ጋዜጠኞች ማዕከሉን ከጎበኙ በኋላ የድርጅቱ መስራችና ዋና ዳይሬክተር ሲስተር ዘቢደር ዘውዴ፣ ጋዜጣዊ መግለጫም ሰጥተዋል፡፡
   በስፍራው የተገኘችው የአዲስ አድማስ ጋዜጠኛ ናፍቆት ዮሴፍ፤ ስለ ማዕከሉ ግንባታ አጠቃላይ ሂደት፣ ለአረጋውያን ስለሚሰጣቸው አገልግሎቶች፣ በድሬደዋና በአርባ ምንጭ ሊገነቡ ስለታቀዱት የአረጋዊያን ማዕከላትና ተያያዥ ጉዳዮች
አንስታ ሲስተር ዘቢደርን አነጋግራቸዋለች፡፡

    ማዕከሉን ገንብቶ ለማጠናቀቅ ምን ያህል ጊዜና ገንዘብ ወሰደ?
በጎ ፈቃደኞች በሙያቸው የለገሱትን ገንዘብ ሳይጨምር 12.5 ሚ. ብር ወስዷል፡፡ የህንፃ ዲዛይኑን አርክቴክት አሰፋ ገበየሁ በነፃ ነው የሰሩልን። በወቅቱ በነበረው ገበያ ዲዛይኑ 350 ሺህ ብር የሚያወጣ ነበር፡፡ ህንፃው ተጀምሮ እስኪያልቅ የክትትልና የማማከር ስራውን ለ6 ዓመት የሰሩልን ወጣቶች፣ MDC የተባለ የህንፃ ስራ አማካሪዎች ናቸው፡፡ ስራ አስኪያጁ ዳዊት ይባላል፡፡ እነዚህ ልጆች ከማማከር ባለፈ የግንባታ እቃ ሲያልቀብን ከራሳቸው እያቀረቡ በነፃ ሲረዱን ቆይተዋል፡፡ የእነዚህ ልጆች እገዛ በገንዘብ ሲሰላ ከግማሽ ሚሊዮን ብር በላይ ይሆናል። የሀዋሳ ከተማ የግንባታ እቃ ባለ ሱቆች፣ከሴራሚክ ጀምሮ የተለያየ ቁሳቁስ ድጋፍ አድርገውልናል፡፡ የተለያዩ የመገናኛ ብዙኃን፣ አርቲስቶች፣ ባለሀብቶችና ባለሙያዎች እገዛ ባይጨመርበት ኖሮ፣ አጠቃላይ ህንፃው ከ20 ሚ. ብር በላይ ይፈጅብን ነበር፡፡ ማእከሉ ከሚለይባቸው ዋናውና አንዱ በኢትዮጵያዊያን መገንባቱ ነው። በዚህ የብዙ ኢትዮጵያዊያን አሻራ ባረፈበት ህንፃ መጠናቀቅ የብዙ ሰዎች ደስታ ተገልጿል፡፡ ብዙ ተስፋ አስቆራጭ ጊዜያትን አሳልፈን ነው ያጠናቀቅነው፡፡
ማዕከሉ ለአረጋዊያን መጠነ ሰፊ አገልግሎት ይሰጣል ተብሏል፡፡ እስቲ ዋና ዋናዎቹን ይንገሩን …
ከመጀመሪያው ጀምሮ ማዕከሉን ለመገንባት ስንነሳ፣ አንድ አረጋዊ ምን ያስፈልገዋል የሚለውን አጥንተን ነው፡፡ ስለዚህ የተሟላ ክሊኒክ አለው፡፡ ምግብ ያስፈልጋቸዋል፤ ለዚህም ካፍቴሪያ አላቸው። ቤተ መፅሀፍት፣ ኮምፒዩተር ላብ፣ ዶክሜንቴሽን ማዕከል፣ ጌም ሴንተር፣ ቴሌቪዥን መመልከቻ ክፍል አለው፡፡ ሲደክማቸው የሚያርፉበት የወንድና የሴት ክፍሎችም አሉት፡፡ ብቻ አንድ አረጋዊ ያስፈልገዋል ተብሎ የሚታሰበው ነገር ሁሉ ተሟልቶለታል፡፡
የማዕከሉ ክፍሎች በተለያዩ ባለሀብት ድርጅቶች ስም የተሰየሙበት ምክንያት ምንድን ነው?
እንግዲህ “50 ሎሚ ለአንድ ሰው ሸክም ነው፤ ለ50 ሰው ጌጡ ነው” ይባላል፡፡ እኛም ህንፃው ተገንብቶ ራዕያችን እንዲሳካ፣አንድ ሰው ወይም አንድ ድርጅት ገንዘብ እንዲሰጠን ከማስጨነቅ፣  የተለያዩ ባለሀብቶችና የሀዋሳ ከተማ የመንግስት መስሪያ ቤቶች ስም በመሰየም ክፍሎቹን በገንዘብ እንዲደግፉ ነው ያደርገነው፡፡ ለምሳሌ ጂምናዚየሙን  - ይርጋለም ኮንስትራክሽን፣ ሻወር ቤቱን - ዋሽንግተን ዲሲ የሚገኙ የማሪያም ማህበርተኞች (በአምስት ሺህ ዶላር)፣ ሴራሚኩን - የሀዋሳ ከተማ ሴራሚክ ሱቆች፣ ሰርቶ ማሳያውን አንዱን ክፍል - ንፋስ ስልክ ቀለም ፋብሪካ፣ ሌላኛውን አንበሳ ጫማ፣---- ስፖንሰር አደረጉ፡፡
በሌላ በኩል ሁለቱንም የማረፊያ ክፍሎች፣ ናርዶስ ወ/ሰንበት የተባለች ዱባይ የምትገኝ ባለሀብት፣ ሱቁን - የጂት መቻል የተባለ የሀዋሳ ነዋሪ፣ በሱቁ አንዳንድ ነገር ለሚሰሩበት ሶስት ሲንጀርና 32 ሺህ ብር - አበባ የተባለች ግለሰብ ለግሳለች፡፡
ክሊኒኩን ሃዋሳ የሚገኘው ያኔት ሆስፒታል ስፖንሰር አድርጓል፡፡ በሳምንት ሁለት ቀን በሆስፒታሉ ያሉ ስፔሻሊስቶች፤ አረጋዊያንኑን እዛው ወስደው ሊያክሙልን ቃል ገብተዋል፡፡ አለነታላንድ የተባለው የንግድ ድርጅት - መታሻ ክፍሉን፣ ጁፒተር ኢንተርናሽናል ትሬዲንግ - አንዱን መታሻ ክፍል፣ ታካሚዎች ቁጭ ብለው ህክምና የሚጠብቁበትን ክፍል - ዋሪት ሙሉ ጥላ (አቶ ለገሰ ዘሪሁን) ስፖንሰር ሲያደርጉ፣ ሎቢውን በ360 ሺህ ብር ዮድ አቢሲኒያ አድርገውታል፡፡ ኢታብ ሳሙና በ260 ሺህ ብር - ካፍሬቴሪያውን ስፖንሰር አድርገዋል፤ የማናጀሩ ቢሮ፣ የፀሀፊው፣ የበጎ ፍቃደኞቹ ቢሮና ሌሎችም በስፖንሰሮች ተሰርተው በስማቸው ተሰይሟል፡፡ አጥሩን እንኳን የከተማው ከንቲባ ፅ/ቤት ነው፣በ900 ሺህ ብር ያጠረው፡፡ ግቢውን እያስዋበ ያለውም የከተማው ማዘጋጃ ቤት ነው፡፡ ጋትስ አግሮ ኢንዱስትሪ፤ቤተ መፅሀፍቱን ስፖንሰር ሲያደርጉ ሌዊ ሪዞርት በበኩሉ፤ ኮምፒዩተር ላቡንና ዶክሜንቴሽን ክፍሉን ስፖንሰር አድርጓል፡፡ ብቻ በአጠቃላይ ለዚህ ማዕከል እውን መሆን፣ ቅን ልብ ያላቸው በርካታ ግለሰቦችና ተቋማት ከፍተኛ ትግል አድርገዋል፡፡ ይሄ እንግዲህ የሚዲያውም አስተዋፅኦ ታክሎበት ነው ለዚህ የበቃው፡፡ ሁሉንም እናመሰግናለን፡፡
ማዕከሉ ስራ ሲጀምር ምን ያህል አረጋዊያንን ያስተናግዳል?
እያንዳንዱ አገልግሎት ቢያንስ መቶ ሰው ያስተናግዳል፡፡ ጠቅላላው አገልግሎቱ ተጠቃሚ ያደርጋል የሚል እምነት አለኝ፡፡ ቀደም ብዬ እንዳልኩት፤ ይህን ማዕከል ልዩ የሚያደርጉ ብዙ ነገሮች አሉ፡፡ ከነዚህ ውስጥ አንደኛው በኢትዮጵያዊያን ብቻ መሰራቱ ሲሆን ሁለተኛው በተለያዩ ስፖንሰር አድራጊ ባለሀብቶችና ግለሰቦች እያንዳንዱ ክፍል መሰየሙ ነው፡፡ ሶስተኛው በሃዋሳ ከተማ የሚገኙ የአልጋ ቁራኛ አረጋዊያንን እያሰሰ፣ ምግብ ለሌላቸው ምግብ ያቀርባል፤ ይህን የሚሰሩ በጎ ፈቃደኞን አሰልጥነናል፡፡ በሌላ በኩል በቀደመውና በአሁኑ ትውልድ መካከል ክፍተት እንዳይኖር አረጋዊያን ለወጣቱ ልምዳቸውንና፣ እውቀታቸውን የሚያካፍሉበት አዳራሽ ከማዕሉ ጀርባ ይገነባል። በኪነ ጥበብ፣ በታሪክና መሰል ጉዳዮች ዙሪያ በመወያየት ወጣቶች አገራቸውን እንዲያውቁ ይደረጋል፡፡ ኢትዮጵያውያንን አስተባብረን  ነው አዳራሹን የምንገነባው፡፡ አዳራሹ ከ500 ሰው በላይ የሚይዝ ትልቅና ዘመናዊ ነው የሚሆነው። ለሰርግ፣ ለጉባኤና ለስብሰባዎች እየተከራየ፣ ማዕከሉን ይደግፋል የሚል እቅድ ይዘናል። ሌላው ጥናትን መሰረት ያደረገ ዘላቂ የአረጋዊያን ድጋፍ ለመስጠት፣ ‹‹ኮሚዩኒቲ ሰርቪስ›› በሚለው ዲፓርትመንታቸው በኩል ከሃዋሳ ዩኒቨርስቲ ጋር በንግግር ላይ ነን፤ ይሄም የሚሳካ ጉዳይ ነው፡፡ በዚህ አጋጣሚ የሙያና ቴክኒክ ትምህርት ቤቱ፤ ለ30 አረጋዊያን በነፃ ስልጠና ሰጥቶልናል፡፡ ሜሪ ጆይ፤ ቫይረሱ በደማቸው ያለባቸው አረጋዊያን ማህበርን አቋቁሟል፤ ስልጠናውም ቅድሚያ የተሰጠው ለእነሱ ነው፡፡ ከስልጠናው በኋላ ስራ እየሰሩ ራሳቸውን እንዲችሉ አድርገናቸዋል፡፡
ማዕከሉ ሥራ ሲጀምር ዓመታዊ በጀቱ ምን ያህል ይሆናል?
አመታዊ በጀቱ 1.5 ሚ ብር ነው፡፡ ይህንን ገንዘብ ከባለሀብቶች፣ ከታዋቂ አርቲስቶች፣ ከመንግስትና ከንግዱ ማህበረሰብ ነው የምናሰባስበው፡፡ አሁን ያቀድነው ለአንድ አመት የሚሆነውን በጀት ዘግተን ለመጀመር ነው፤ ማሰባሰብም ጀምረናል፡፡ ለምሳሌ ግርማዬ ፈረደ የተባሉ ባለሀብት ወይም ሲጂኤፍ ኢንተርናሽናል ትሬዲንግ - 130 ሺህ ብር፣ ቢጂአይ ኢትዮጵያ - 300 ሺህ ብር ለመነሻ የሰጡን ሲሆን የደቡብ ክልል መስተዳደር 750 ሺህ ብር ሊሰጠን ቃል ገብቶልናል፡፡
ሜሪ ጆይ በአርባ ምንጭና በድሬደዋ ተመሳሳይ ማዕከላትን ለመገንባት ከዓመታት በፊት እንቅስቃሴ መጀመሩን አውቃለሁ፡፡ ከምን ደረሰ?
በሁለቱም ቦታዎች እንቅስቃሴ ጀምረናል፡፡ በአሁኑ ወቅት አርባ ምንጭ ላይ ወደ 2 ሚ. ብር አለን፡፡ ድሬደዋ እንቅስቃሴው በጣም ሄዷል፤ እንዲያውም ፀደቀ የተባለ ወጣት ባለሀብት፣ 600 ሺህ ብር አውጥቶ አጥሩን አጥሮታል፡፡ እዛ የምንሰራው ከዳዊት አረጋዊያን ማህበርና ከከተማው ፅ/ቤት ጋር ነው፡፡ በቅርቡ ግንባታ ይጀመራል፡፡ ግንባታው የሚካሄደው በ5 ሺህ ካሬ ሜትር ላይ ነው፡፡ የአርባ ምንጩን ግንባታ ለመጀመር ጠረጋ ተጀምሯል፡፡ የአርባ ምንጩ በ10 ሺህ ካሬ ሜትር ላይ የሚያርፍ ነው፡፡ እንደ እግዚአብሔር ፈቃድ እነዚህም ማዕከላት እንደ ሀዋሳው እውን ይሆናሉ፡፡ ሶስቱ ማዕላት ስራ ላይ ሲሆኑ ለየከተማዎቹ አረጋዊያን እያንዳንዳቸው በወር ለ5 ሺህ ሰው አገልግሎት ይሰጣሉ፡፡ በአጠቃላይ በወር 15 ሺህ አረጋዊያን የአገልግሎቱ ተጠቃሚ ይሆናሉ ማለት ነው፡፡
ሜሪ ጆይ ዋና ፅ/ቤቱ ያለው አዲስ አበባ ነው። በሌላ በኩል ታዋቂና አንጋፋ አርቲስቶች በበጎ ፍቃደኝነት የሚደግፉት ነው፡፡ ሁላችሁም ደግሞ አረጋዊ ወደመሆኑ እየሄዳችሁ ነው፡፡ መጀመሪያ ለራሳችሁ ማረፊያ አዲስ አበባ ላይ ማዕከል ሳታቋቁሙ እንዴት ወደ ክልል ሄዳችሁ?
መጀመሪያ አዲስ አበባ ላይ ለመገንባት ነበር እኮ እንቅስቃሴ የጀመርነው፡፡ ቦታ አጥተን ነው፤ ለአዲስ አበባ የመደብነውን 2 ሚ. ብር ይዘን ሀዋሳ የሄድነው። ቦታ ጠይቀን በጣም ረጅም ጊዜ ሲፈጅብን ሀዋሳ ሄደን፣ አቶ ሽፈራው ሽጉጤን ስንጠይቅ፣ “ይሄ ተገኝቶ ነው” ብለው፣ በ10 ቀናት ውስጥ ነው ያየሽውን አይን የሆነ ቦታ የሰጡን፡፡ ቦታው በዛን ጊዜ በጠቅላይ ሚኒስትሩ ተከልክሎ ነበር፡፡ አቶ ሽፈራው ግን ከጠቅላይ ሚኒስትሩ ጋር ተነጋግረው፣ በ10 ቀናት ውስጥ ካርታ አገኘን፤ ይሄ ሞራል ሰጠን። የአዲስ አበባን ብር ይዘን፣ እዛ ጀመርን፤ ይሄው ለመጠናቀቅ በቃ፡፡
አሁንስ የአዲስ አበባውን ማዕከል ለመገንባት የቦታው ጉዳይ ተስፋ ሰጪ ነው?
አዎ መገንባቱ አይቀርም፤ ካልሆነ ሜሪ ጆይ የራሱ ቢሮ ግቢ ውስጥም ቢሆን በጣም ዘመናዊ ማዕከል ይገነባል፡፡ እንዳልሺው ያው እኛም ወደ አረጋዊነቱ እያመራን በመሆኑ ነገ ማረፊያ ያስፈልገናል፡፡ ለአዲስ አበባ አረጋዊያንና ለራሳችን ማዕከሉን ለመገንባት፣ ከአርቲስት በጎ ፈቃደኞቻችንና አጋሮቻችን ጋር በምክክር ላይ ነን፡፡
ከብዙ ውጣ ውረድና ፈተና በኋላ ማዕከሉ ተጠናቅቆ ማየት ምን ዓይነት ስሜት ይፈጥራል?
በጣም ደስ ብሎኛል፤ ያው አንዳንዴ ደስታን በቃላት መግለፅ ያስቸግራል፤ እንደውም አርቲስት ፋንቱ ማንዶዬ ለዚህ ማዕከል ገንዘብ ለማሰባሰብ በሚደረገው እንቅስቃሴ ብዙ ፈተና ገጥሞታል። ግማሹ እያለ የለም ሲያስብለን፣ ሌላው በሩን ሲዘጋብን እሱ፣ ብዙ ችግር ከእኔ ጋር አሳልፏል። መጨረሻ ላይ የምንሰራበት ብር ሁሉ አጥተን፤ ‹‹እንደው ይሄ ማዕከል ተሰርቶ በነጋታው በሞትኩ›› ብሎ ነበር፡፡ ነገር ግን እግዚአብሔር ትልቅ ነው። አንዳችንም በቁጥር ሳንጎድል ማዕከሉ ተጠናቀቀ። ሲጀመር የነበራችሁ ጋዜጠኞች፣ ባለፈው ቅዳሜ ቦታው ላይ ተገኝታችሁ በማዕከሉ ጋዜጣዊ መግለጫ ስሰጥ፣ከምቆጣጠረው በላይ የሆነ ደስታ ተሰምቶኛል፡፡ በመጨረሻ ለዚህ ህልም እውን መሆን ከፍተኛ ድርሻ ያላቸውን አርቲስቶች፤ የሀዋሳ ከተማ የመንግስት መስሪያ ቤቶች፣ ነጋዴዎች፣ በአዲስ አበባና በውጭ የሚገኙ ባለሀብቶችና ግለሰቦች፣ በጎ ፈቃደኛ ወጣቶችና መገናኛ ብዙሀን ትልቅ ምስጋና ይገባቸዋል፡፡ አብረውን የደከሙትን ሁሉ ብድራታቸውን ፈጣሪ ይክፈላቸው እላለሁ፤ አመሰግናለሁ፡፡ “ይቻላል” የሚለውን መንፈስ አዳብረናል፤ አይደለም በሶስት ከተሞች በአገራችን በሁሉም ከተሞች የአገር ባለውለታዎች የሚዝናኑበት፣ የሚታከሙበት፣ የሚጨዋወቱበት ማዕከላት ይገነባሉ፡፡

  በጥንት ዘመን የነበረ አንድ ንጉሥ ታላላቅ፣ ጠበብት፣ መኳንንት፣ መሣፍንት እንዲሁም የጦር ኃይል አባላትን ጨምሮ ህዝቡን ሰበሰበና አገር ለማዳንና ህልውናዋ ተጠብቆ እንድትቆይ ወሳኝ እኔ ነኝ የሚል እጁን ያውጣና ምክንያቱን ያስረዳኝ አሉ፡፡
በመጀመሪያ የጦር አበጋዙ ተነስቶ፤
“አገር የማድን፣ የአገርን ህልውና የማስጠብቅ እኔ ነኝ” አለ፡፡
ሁለተኛ የተነሳው ምሁሩ ነበር፤
“ያለ እኔ ዕውቀት አገር ደህንነቷና ህልውናዋ አይጠበቅም፡፡ ምንም ነገር ስትሰሩ፣ እኔን ያማክሩ አለ፡፡ ስለ ጦር መሳሪያም ቢሆን መሰረቱ የእኔ እውቀት ነው!” አለ፡፡
ሦስተኛው ገበሬው ነው፡፡
“እኔ ካላመረትኩ ሁሉም ከንቱ ነው ንጉሥ ሆይ፡፡ ስለዚህ በልተው ካላደሩ፣ ምንም አይሰሩ!” አለ፡፡
ነጋዴው ተነሳ፡-
“የጦር መሳሪያውንም፣ የምሁራኑንም የምርምር ዕቃ፣ የገበሬውንም ምርት የሚያንቀሳቅሰው የእኔው የንግድ ሥራ ነው! በእኔ ኃይል ነው የአገርን ደህንነትና ህልውና የሚያቆዩት ንጉሥ ሆይ!” አለና ተቀመጠ፡፡
የቢሮ ኃላፊው እጁን አውጥቶ ተነሳና፤
“ንጉሥ ሆይ! የተናገሩት ሁሉ ዕውነት ነው፡፡ ነገር ግን የጽህፍት ሥራና የቢሮክራሲ ደም - ሥር ካልታከለበት ከንቱ ነው፡፡ የእኔን ቢሮክራሲ የማያከብር ዋጋ አይኖረውም!”
የጥበብ ሰው ተነስቶ - “አገርን የሚያሽር የጥበብ ሥራ ነው! ምንም ነገር ተነስቶ ጥበብ ካልተጨመረበት ዐይን አይገባም፡፡ ህይወት አይኖረውም!” አለ፡፡
የፋይናንስ አላፊው፤
“ንጉሥ ሆይ! ምንም አያሳስብም፡፡ ያለ ሂሳብ፣ ያለ ፋይናንስ ማንም የትም አይንቀሳቀስም! እኔ ሂሳብ ከተቆጣጠርኩ፤ አገር አማን ናት!” አለ፡፡
በመጨረሻ አንዲት ምስኪን ሴት ተነስታ፡- “ንጉሥ ሆይ! ምንም ተባለ ምን፣ ወሳኙ ፍቅር ነው፡፡ ፍቅር ነው ገዢው!” አለች፡፡
ንጉሡ አሰቡ አሰቡና፤ “ያለ ፍቅር ምንም ነገር ከንቱ ነው፡፡ አማካሪዬ ትሆኛለሽ” አሉና ደመደሙ፡፡
*           *        *
“እስከ ዛሬ ጥሩ ጦርነት አልነበረም፡፡ መጥፎ ሰላምም ታይቶ አያውቅም!” ይላል ፍራንክሊን፡፡ ታላቅ ጦርነት አንድ አገር ላይ ሦስት አሻራ ትቶ ያልፋል፡-
ሀ. የአካል ጉዳተኞች ሠራዊት
ለ. የሐዘንተኞች ሠራዊት
እና     ሐ. የሌቦች ሠራዊት
የጀርመናውያን ተረት
ይሄ ሁሉ የፍቅር መጎናፀፊያ በሌላት አገር የሚከሰት ነው፡፡ ከቤተሰብ እስከ ህብረተሰብና እስከ ጎረቤት አገር ፍቅር ከሌለ የሚከሰት ብዙ ጎዶሎ ሥፍራ አለ፡፡ ያንን ለመሙላት የሞቀ ፍቅር ያስፈልጋል፡፡ ጦር፣ ትምህርት፣ ምርት፣ ንግድ፣ ቢሮክራሲ፣ ጥበብ፣ ፋይናንስ ወዘተ … ሁሉም የፍቅር ተገዢ መሆን አለባቸው - አለዛ ሰላም አይኖርም!
የዓለም ኢንፎርሜሽን ቀን እናከብራን፡፡
የፍትሕ ቀን እናከብራለን፡፡
የፕሬስ ቀን እናከብራለን፡፡
የአረጋውያን ቀን እናከብራለን፡፡
የወጣቶች ቀን እናከብራለን፡፡
የቫላንታይን ቀንም እናከብራን፡፡
የእጅ መታጠብ ቀንም እናከብራለን!
ምኑ ቅጡ! አያሌ የምናከብራቸው ቀናት አሉ፤ ይኖራሉም፡፡ ወደንም ይሁን ሳንወድም! የዓለምም ይሁን የአገር! ወጣም ወረደ፤ ሁሉም ፍቅር ይፈልጋሉ፡፡ ፍቅሩን በዛ አድርጎ ይስጠን!
ክፉ ክፉውን በማሰብ አገር አናድንም፡፡ መግባባት፣ መናበብ፣ መቀራረብ፣ ውዝግብን ከየሆዳችን ማውጣት፣ ለመፋቀር መዘጋጄት … የአገር ፍቅር መሰረት ነው፡፡ የጀግንነት ምልክት ፍቅርን መላበስ ነው!
ለወታደሩ ፍቀር ይስጠው፡፡ ለምሁሩ ፍቅር ይስጠው፡፡ ለሂሳብ አዋቂው ፍቅር ይስጠው፡፡ ለነጋዴው ፍቅር ይስጠው! ለጥበብ ሰው ፍቅር ይስጠው! አገር በፍቅር ትድን ዘንድ ለሁላችንም ፍቅር ይስጠን፣ ብርታት እና ፅናቱን ይስጠን!
ኮስተር ብለን ካሰብን ምርት ያለ ፍቅር አይመጣም፡፡ ዕድገት ያለፍቅር አይመጣም፡፡ የመንፈስ ተሐድሶ ፍቅርን ይሻል፡፡ ለውጥ ፍቅርን ይሻል፡፡ A change is equal to rest የሚለው የአይንስታይን አባባል መለወጥ ማረፍ ነው እንደማለት ነው፤ ትርጉሙ እያደር ሊገባን ግድ ነው፡፡ እረፍት የሰላም መደላድል ነው፡፡ ለውጡ እየገተባን፣ ለአዲሱ ሁኔታ ተገዢ መሆንን ይጠይቃል! Resist conservatism! እንደሚሉት ነው ፈረንጆቹ፡፡ “ወግ - አጥባቂነት ይውደም” የሚለው የዱሮ መፈክር ይበልጥ ይገልጠው ይሆናል! መንገዶች ሁሉ ወደ ለውጥ ያመሩ ዘንድ ዐይናችንን እንግለጥ!!
ለውጥ ፍቅር ይፈልጋል፡፡ ምነው ቢሉ ፍቅር ያላት አገር ሽለ-ሙቅ ናት (Fertile) ወላድ ናትና! ምርታማ ናትና! ለዚያ ያብቃን!

የድምፃዊ ቴዎድሮስ ካሣሁን (ቴዲ አፍሮ) “ኢትዮጵያ” የተሰኘው 5ኛ ዓልበም ባለፈው ረቡዕ ከ50 ብር እስከ 100 ብር መሸጡ ታውቋል፡፡
አልበሙን በ10 ዶላር ለኢንተርኔት ሽያጭ ያቀረበው “cdbaby” የተሰኘው ድረ ገፅ በበኩሉ፤ የድምፃዊው አልበም የኢትዮጵያን የሙዚቃ አልበም በሽያጭ ክብረ ወሰን የሰበረ መሆኑን አስታውቋል፡፡
በአጠቃላይ በመጀመሪያው ዙር ግማሽ ሚሊዮን የሙዚቃ አልበም ታትሞ መሰራጨቱ የተገለፀ ሲሆን አልበሙ ለሲዲ አዟሪዎች መልካም የገበያ ዕድል እንደፈጠረላቸው ታውቋል፡፡
ቦሌ ድልድይ አካባቢ ረቡዕ ጠዋት 2 ሰዓት ገደማ የድምፃዊውን አልበም ሲሸጥ አግኝተን ያነጋገርነው አዟሪ፤ ቀደም ሲል መፅሃፍ እያዞረ ይሸጥ እንደነበረ ጠቁሞ፤ መደበኛ ስራውን ለጊዜው በመተው የድምፃዊውን አልበም እየሸጠ መሆኑን ገልጿል፡፡ ከማለዳው 11 ሰዓት ጀምሮ እስከ ጠዋቱ 1 ሰዓት ድረስ ከ50 በላይ አልበሞችን እያንዳንዱን በመቶ ብር ሂሳብ መሸጡንም ጠቁሟል፡፡ የተወሰኑ አልበሞችንም በ80 እና በ70 ብር መሸጡን ተናግሯል፡፡
አልበሙን ገዝቶ በታክሲ ውስጥ እያዳመጠ ያገኘነው የታክሲ ሹፌር በበኩሉ፤ ባለፈው ረቡዕ አልበሙ ሊያልቅ ይችላል በሚል ስጋት ጠዋት 12 ሰዓት ላይ አውቶብስ ተራ አካባቢ በ100 ብር መግዛቱን ገልፆ ይህን ያደረገውም ድምፃዊውን ስለሚያደንቀውና ታሪካዊውን አልበም እንዳያጣ በመስጋት መሆኑን ተናግሯል፡፡
“እውነተኛው የኦሮሞ እና አማራ ታሪክ” በተሰኘ አነጋጋሪ መፅሃፋቸው የሚታወቁት ፕ/ር ፍቅሬ ቶሎሣ በፌስቤክ ገፃቸው ባሰፈሩት አስተያየት፤ “ቴዎድሮስ ካሣሁንንና ሙዚቃውን ለምን ህዝብ ይወዳቸዋል?” በሚል ርዕስ ባሰፈሩት ማስታወሻ፤ ሙዚቃዎቹ ባለፉት 25 ዓመታት እንደ ሰደድ እሳት የተዛመተውን ዘረኝነት የሚቃወሙና ኢትዮጵያዊነትን የሚያቀነቅኑ በመሆናቸው ብለዋል።
በርካታ የፌስቡክ ተከታይ ያለው ዘውዳለም ታደሰ በበኩሉ፤ ድምፃዊው “አፄ ቴዎድሮስ” በሚለው ዘፈኑ፤ አፄ ቴዎድሮስን ዳግም እንዳነገሳቸው ፅፏል፡፡ በዚህ ዘፈን ኢትዮጵያዊነት ከፍ ብሎ እንደተሰበከም ገልጿል፡፡ አብዛኞቹ የአርቲስቱ አድናቂዎች ሀገራዊ ይዘት ያላቸውን ሙዚቃዎች እንደወደዷቸው በፌስቡክ ገፃቸው ላይ አስፍረዋል፡፡
ዱከም ኢንዱስትሪ ዞን ውስጥ አዲስ በተቋቋመው “ቆልያ ሲዲና ዲቪዲ አምራች” ድርጅት በተመረተውና በቀላሉ ኮፒ ለማድረግ ያስቸግራል በተባለው ሲዲ የታተመው የቴዲ አፍሮ “ኢትዮጵያ” አልበም ከወጣበት ካለፈው ረቡዕ ጀምሮ በሲዲ ማዞር ስራ ላይ ተሰማርተው የማያውቁ ግለሰቦች ሳይቀሩ ሲዲውን በፍጥነት እየሸጡ መሆኑን በተዘዋወርንባቸው ፒያሳ፣ አራት ኪሎ፣ መርካቶ፣ መስቀል ፍላወርና ካዛንቺስ አካባቢዎች ለማረጋገጥ ችለናል፡፡ አልበሙን ለማከፋፈል ባለፈው ማክሰኞ የክልልና የአዲስ አበባ ነጋዴዎች ረጅም ወረፋ ሲጠብቁ እንደነበር የገለፁት ምንጮቻችን፤ አልበሙን ለማከፋፈል ለምዝገባ ሲመጡ የሚፈልጉትን የሲዲ መጠን ግማሽ ክፍያ በባንክ ቅድሚያ ከከፈሉ በኋላ ለመውሰድ ሲመጡ ደግሞ ሙሉ ክፍያ የከፈሉበትን የባንክ ደረሰኝ ያሳዩ እንደነበር ምንጮቻችን ጨምረው ገልፀዋል፡፡
አልበሙ መውጣት ከነበረበት ሁለት ሳምንት ዘግይቶ መውጣቱ የሚታወቅ ሲሆን ለዚህም ምክንያቱ ሲዲው በተለመደው ከቨር ለገበያ ቢቀርብ ለአየር ብክለት ጉዳት ይጋለጣል በመባሉ አሁን ባለው የካርቶን ከቨር ለመለወጥ ሲባል ሁለት ሳምንት መዘግየቱን የጠቆሙት ምንጮቻችን፤ ይህንንም ስራ በፍጥነት ለመሰራት 200 ያህል ጊዜያዊ ሰራተኞች ተቀጥረው ከቨሩንና ግጥም የተፃፈበትን ቡክሌት ሲያጥፉ እንደቆዩ ምንጮች ገልፀዋል፡፡ 500 ሺህ ከቨርና ቡክሌቱ እያንዳንዱ በአራት አራት ብር የተሰራ ሲሆን የተቀጠሩት ጊዜያዊ ሰራተኞች አንዷን ከቨር ለማጠፍ በ20 ሳንቲም ሂሳብ መስማማታቸውንም ምንጮች ገልፀዋል፡፡ ለከቨሩ እና ለቡክሌቱ ስራ በጠቅላላ ወደ 5 ሚ. ብር መውጣቱም ተገልጿል፡፡