Administrator

Administrator

 ከዕለታት አንድ ቀን አንዲት ቀበሮ፣ በአንድ ገበሬ ግቢ እየመጣችና የሚያረባቸውን ዶሮዎች እየሰረቀች በጣም ታስቸግራለች፡፡
ገበሬው ለፍቶ ለፍቶ ለቀበሮ መቀለብ ሲሆንበት፣ ከሚስቱ ጋር ለመማከር ይወስንና፤
‹‹ሰማሽ ወይ ውዴ?››
‹‹አቤት ጌታዬ››
‹‹የዚችን የቀበሮ ነገር ምን ብናደርግ ይሻላል?››
‹እኔም ግራ- እየገባኝ ምን እናድርግ ልልህ ነበርኮ››
‹‹አንቺ ምን አሳብ አለሽ?››
‹‹እኔማ ሠፈሩን እንረብሻለን ብዬ ፈርቼ ነው እንጂ፤ መሳሪያ እያለህ አንድ ቀበሮ መግደል ምን ችግር ነበረው?››
‹‹አይ ያሉትን ይበሉ እንጂ ዕውነትም ጠመንጃዬን ወልውዬ አድፍጩ ብጠብቃት አታመልጠኝም›› አለ ፍርጥም ብሎ፡፡
‹‹ግን  እንዲህ ብናረግስ?››
‹‹ምን?››
‹‹ለሰፈሩ አለቃ ብናሳውቅ? ሰውም ጥይት ሲሰማ እንዳይሸበር፣ ለሊቀ መንበሩ ብንነግር?››
‹‹ደግ ሀሳብ አመጣሽ፡፡ አሁኑኑ እነግረዋለሁ፡፡›› አለና ወደ ሊቀ መንበሩ ቢሮ ሄደ፡፡
ሊቀመንበሩ ግን ሀሳቡን አልተቀበለውም፡፡ ይልቁንም፤
‹‹ለምን በወጥመድ አትይዛትም?›› ሲል ጠየቀው፤
‹‹ወጥመድ የለኝም››
‹‹እኔ እሰጥሃለሁ፡፡››
በዚሁ በወጥመዱ ሀሳብ ተስማሙና፣ በገብሬው ወጥመዱን ተረከበ፡፡
ማታም ቀበሮዋ መግቢያ ላይ ወጥመዱን አስቀመጠና መጠበቅ ጀመረ፡፡ ወጥመዱን ያልጠረጠረችው ቀበሮ ዘው ብላ ገባች፡፡ ተያዘች፡፡
ገበሬው በጣም ተደሰተ፡፡ በምን እንደሚቀጣ ያሰላሰለ ጀመር፡፡ በመጨረሻ…
‹‹እንዲያ ስትጫወትብኝ… እንደከረመች በፍፁም አልምራትም›› አለ፡፡
ከዚያም ጭራዋ ላይ ጭድ አሰረና እሳት ለቀቀባት፡፡ ከወጥመዱ አውጥቶም ወረወራት። ቀበሮም ቃጠሎው ሲበዛባት… በአቅራቢያው ወደሚገኘው የገበሬው የበቆሎ እርሻ ገባች፡፡ በቆሎው የደረሰ አዝመራ ነው፡፡ በእሳት ተያያዘ፡፡ ሙሉ በሙሉ ነደደ፡፡
*   *   *
ቂም በቀል የሁለት-ወገን-ስለት አለው፤ ይላሉ ፈረንጆች፡፡ ለሌላው የሳሉት ሰይፍ ወደ ራስ ሊመጣ እንደሚችል ማስተዋል ጥበበኝነት ነው፡፡ ክፋት ማቆሚያ የለውም፡፡ የጥፋተኝነት ስሜቱም አዕምሮን ከመነቆር አይገላገልም፡፡ ‹‹ዳባ ራሱን ስለት ድጉሡን›› ማለት ነው- በአማርኛ አገራዊ እነጋገር፡፡ በሀገራችን የመልካም አስተዳደር ጥያቄ ዛሬ አንገብጋቢ እሳት ሆኗል- (Burning Issue እንዲሉ) በመልካም አስተዳደር ጉድለት፣ በሥልጣን መባለግ፣ የሀገርንና የህዝብን ጥቅም ለራስ ማዋል፣ ፖለቲካን የግል ንብረት በማድረግ ማስፈራሪያና ‹‹እኔ ብቻ ነኝ አድራጊ ፈጣሪ›› ማለት ወዘተ እጅግ ጎጂ ባህል ሆነው ከርመዋል፡፡ ያደረጉት ነገር በተጨባጭ ስህተት መሆኑ ታውቆ ለፍርድ ይቅረቡ የተባሉ አሉ፡፡ ይበል የተባለ እርምጃ መሆኑን የማይስማማ ያለ አይመስለንም፡፡ ሆኖም ዕውነቱን ፈልፍሎ የማውጣት ሥራ፣ ያለ ምንም ወገንተኝነት ህሊናዊ ንፅህናን የመጠበቁ ኃላፊነት እና የግብረ-አበሮችን ሰንሰለት መርምሮ፣ ፈለጉን የማግኘትን የመበጠስ ዕልህ - አስጨራሽ ጉዞ ሳያሰልሱ የመጓዝን ሂደት ከወዲሁ አስቦና አስልቶ መንቀሳቀስ ወሳኝ ነው። ጅምሮች በአጭር እንዳይቀጩ ከመርማሪ ፖሊስ እስከ ፍትህ አካላት የተባበረ ቅኝት ያስፈልጋቸዋል። ዲሞክራሲ ላጲስ አይደለም፤ ተጋጋዥ እንጂ ተጠፋፊ አይደሉም፡፡ ፖለቲካ የኢኮኖሚ ዕምቅ መገለጫ (Concentrated Expression) እንጂ ሌላ ላንቃ አይደለም፡፡ ሀቀኝነት ሳይኖር ፍትሃዊነት መጎናፀፍ አይቻልም፡፡ ለማኅበራዊ ምስቅልቅልነት መፍትሄው የመንግስትና ህዝብ ተቀራርቦ ሀገራዊ መተሳሰብን መፍጠር እንጂ ‹‹መንግስት ነኝና ልፈራ ይገባኛል›› የሚል አመለካከትና ጉልበታዊ ተግባር አይደለም፡፡ በመንግስት ውስጥ ያሉና ህዝብን በመበደል የሚኩራሩ ወገኖች ጊዜያዊ ድል እንጂ ዘላቂ ወንበር አይኖራቸውም፡፡ ያም ሆኖ እኒህንም አካላት ለፍርድ ሲቀርቡ ያለአድልዎ ዳኝነት የሚሰጥ አካል ሊኖር ይገባል። ህጋዊ ፍርድ በሀቅ ላይ የተመረኮዘ እስከሆነ ድረስ የመልካም አስተዳደር አለመጓደልን የሚያፈካ ብርሀን አለ ማለትን ማመን እንጀምራለን፡፡
የመልካም አስተዳደር ጉዳይ፣ በመልካም አስተዳደር ጉድለት እንዳይጨናገፍ ብርቱ ጥረት ያስፈልጋል፡፡ ሀገራችን የሰው አስተሳሰብ ልማት ያሻታል፡፡ ጠቃሚ የሆነ ነው የምንለውን የመዋቅር ለውጥ ለማምጣት፣ እስከ ቻርተር ማሻሻል ስንዘልቅ ዞሮ ዞሮ ወሳኙ ሁነኛ የሰው ኃይል መሆኑን አንርሳ! ተለውጧል ተሻሽሏል ማለት ብቻ ሳይሆን ከዕውነታው ያልራቀ መፍትሄ መሆኑን ማረጋገጥ ቁልፍ ነገር ነው!
በማናቸውም ግለሰብ ፣ በግል ኢንቬስተሮች፣ በቢሮክራሲ አባላት በንግዱ ማህበረሰብ፣ በሲቪክ ማህበረሰብ አባላት ወዘተ ላይ የምንሰነዝራቸውን ሂሶች፣ ውንጀላዎችና ፍረጃዎች ስናስብ፣ እኛስ ራሳችንን እንዴት እንገመግማለን? እንዴት እንፈርጃለን? እንዴትስ ስህተታችንን እናምናለን? የሚለውን ወሳኝ ጉዳይ ልብ - እንበል! ለዚህ የሚበጀን ዘዴ “ንስሓ ከኃጢአት፣ ውኃ ከእድፍ ያፀዳል!” የሚለውን ምሳሌ ለሊት ተቀን ማሰብ እና ስራ ላይ ማዋል ነው!

 ባለፉት 9 ወራት ብቻ 71 ያህል ዝነኞች ሞተዋል

      የመጨረሻዋ ቀን ላይ በሚገኘው የፈረንጆች አመት 2016፣ ባልተለመደ ሁኔታ ከፖለቲካ እስከ ስፖርት፣ ከፊልም እስከ ሙዚቃ በየሙያ መስኩ እውቅናን ያተረፉ በርካታ ዝነኞችና ታዋቂ ሰዎች ከዚህ አለም በሞት የተሰናበቱበት መሆኑ ተነግሯል፡፡
ሲኤንኤን በአለማቀፍ ደረጃ የተሰራ የጥናት ውጤት ጠቅሶ ሰሞኑን እንደዘገበው፣ እስካለፈው ጥቅምት ወር ድረስ በነበሩት የአመቱ 9 ወራት ብቻ፣ በተለያዩ የሙያ መስኮች ስማቸውን በአለም መድረክ ላይ ማስጠራት የቻሉ ከ71 በላይ የዓለማችን ታዋቂ ሰዎችና ዝነኞች ከዚህ አለም በሞት ተለይተዋል፡፡ ከስፖርቱ አለም ብንጀምር፣ እድሜ የማያዝላቸው፣ ህመም የማይረታቸው ከሚመስሉ ጠንካራ እጆቹ በሚወነጨፉ ቡጢዎቹ ብዙዎችን ያደባየው የአለም የከባድ ሚዛን ሻምፒዮናው መሃመድ አሊ፣ ባለፈው ሀምሌ ወር መጀመሪያ ላይ ነበር በተወለደ በ74 አመቱ ይህቺን ዓለም በሞት የተሰናበተው፡፡
ወደ ፖለቲካው ጎራ ስንል ደግሞ፣ አለማችን በአመቱ ካጣቻቸው ታላላቅ ሰዎች መካከል አንዱ የሆኑትን የቀድሞውን የተባበሩት መንግስታት ድርጅት ዋና ጸሃፊ ግብጻዊውን ቡትሮስ ቡትሮስ ጋሊን እናገኛለን። ቡትሮስ ጋሊ በወርሃ የካቲት ነበር በ93 ዓመታቸው በሞት የተለዩት፡፡ አለማችን በዓመቱ ካጣቻቸው ሌሎች ፖለቲከኞች መካከልም የኖቤል የሰላም ተሸላሚውን ሺሞን ፔሬዝን እናገኛለን፡፡ እስራኤልን በፕሬዚዳንትነትና በጠቅላይ ሚኒስትርነት ያስተዳደሩት ፔሬዝ፣ ባለፈው መስከረም ወር መጨረሻ ላይ ነበር በ93 ዓመታቸው ይህቺን አለም በሞት የተሰናበቱት፡፡
መስከረም ላይ ፔሬዝን የወሰደ ጨካኝ ሞት፣ በህዳር ዞሮ መጣና ሌላ የፖለቲካው መስክ ገናና ይዞ ሄደ፡፡ ኮሙኒስት ኩባን ለግማሽ ምዕተ አመት ያህል ያስተዳደሩት ፊደል ካስትሮ ሩዝ፤ በ90 አመታቸው ወደማይቀርበት መሄዳቸው ተሰማ፡፡ ከሙዚቃው መስክ ከተሰሙት አስደንጋጭ መርዶዎች መካከል ከሰሞኑ የተደመጠው የጆርጅ ማይክል ሞት አንዱ ነበር፡፡ ታዋቂው ድምጻዊ ጆርጅ ማይክል፣ በፈረንጆች የገና እለት ከዚህ አለም በሞት የመለየቱ መርዶ ተሰምቷል፡፡ በካንሰር ሲሰቃይ የቆየው እንግሊዛዊው የሮክ አቀንቃኝ ዴቪድ ቦዌም በዚሁ ጦሰኛ አመት ነበር በ69 ዓመቱ ይህቺን አለም በሞት የተሰናበተው፡፡
አመቱ ሊጠናቀቅ ጥቂት ቀናት በቀረበት ሁኔታ አለምን በድንጋጤ ክው ያደረገ ሌላ የመዝናኛው መስክ መርዶ ከሰሞኑ ተሰምቷል፡፡ በ”ስታር ዎርስ” ፊልም ላይ በመተወን የዓለምን ቀልብ ገዝታ የዘለቀቺው የፊልም ተዋናይትና ደራሲ ኬሪ ፊሸር፣ ባለፈው ሰኞ በልብ ድካም ህመም በ60 አመቷ አለምን ተሰናብታለች፡፡

“ልጆች ባሉበት ሁሉ ምግብ ይኑር” በሚል መሪ ቃል፤ ዘላቂ የት/ቤት ምገባ ፕሮግራም ሲያካሂድ የቆየው የኢትዮጵያ ስኩል ሚል ኢንሼቲቭ (ኢ.ስ.ሚ.ኢ)፤ ተግባሩን ወደ አቅም ግንባታ ስራ ለማሸጋገር እየተንቀሳቀሰ መሆኑን ገልፆ፣ ማዕከሉን ሰቆጣ ለማድረግ ከዋግህምራ ዞን መስተዳደር ጋር በመጪው ማክሰኞ ስምምነት እንደሚፈራረም አስታውቋል፡፡
ህፃናት ተማሪዎችን በየትምሀርት ቤታቸው ሲመግብ የቆየው ማዕከሉ፤ ት/ሚኒስቴር በመጀመሪያ ደረጃ ት/ቤቶች ተመሳሳይ የምገባ ፕሮግራም መጀመሩን ተከትሎ ቀደም ሲል ድርጅቱ ለምገባ ሲጠቀምባቸው የነበሩ ማዕከላቱን ለሰርቶ ማሳያነት እንዲያገለግሉ በማድረግ፣ ፊቱን ወደ አቅም ግንባታ ማዞሩን ገልጿል፡፡
በዋግምሀራ  ዞን በተከሰተው ድርቅ ሳቢያ አካባቢው ይበልጥ ድጋፍ የሚያስፈልገው  ቢሆንም ረሀብን ማሸነፍ እንደሚቻል የተረጋገጠበት አካባቢ በመሆኑ፣ ዞኑ ለመጪዎቹ 3 ዓመታት የኢ.ስ.ሚ.ኢ የስራ ማዕከል ሆኖ የሚዘልቅበትን ስምምነት እንደሚፈረም ታውቋል፡፡


የኢትዮጵያ የፅንስና ማህፀን ሃኪሞች ማህበር 25ኛ ዓመቱን ያከብራል

የአፍሪካ ፅንስና የማህፀን ሐኪሞች ፌዴሬሽን ጉባዔ፣ በመጪው የካቲት ወር በአዲስ አበባ ከተማ ውስጥ ሊካሄድ ነው፡፡  ‹‹ዘላቂ የልማት ግቦች በአፍሪካ የስነ ተዋልዶ ጤና፣ ዕድሎችና ተግዳሮቶች›› ‹‹በሚል መሪ ሃሳብ በሚካሄደው በዚሁ አህጉር አቀፍ ጉባኤ ላይ የተለያዩ ጥናታዊ ፅሁፎች ይቀርባሉ፡፡
የአፍሪካ የፅንስና ማህፀን ሐኪሞች ፌዴሬሽን መስራችና አባል የሆነው የኢትዮጵያ ፅንስና ማህፀን ሃኪሞች ማህበር (ኢሶግ)፤ የተመሰረተበትን 25ኛ ዓመት በአሉን ያከብራል፡፡ ይህንኑ የማህበሩን የብር ኢዮቤልዩ በዓልና አህጉር አቀፍ ጉባዔውን እስመልክቶ ማህበሩ በነገው ዕለት በሒልተን ሆቴል ጋዜጣዊ መግለጫ እንደሚሰጥ ማህበሩ ለአዲስ አድማስ የላከው መረጃ ያመለክታል፡፡ በዚሁ ዕለትም የማህበሩ አባላት የሆኑ የህክምና ባለሙያዎች ደም እንደሚለግሱ ታውቋል፡፡


 - አምና 72ኛ የነበሩት ትራምፕ፣ ዘንድሮ 2ኛ ሆነዋል - ከ74 የአለማችን ሃያላን፣ አፍሪካውያን 2 ብቻ ናቸው

    ታዋቂው ፎርብስ መጽሄት 74 ሰዎች የተካተቱበትን የ2016 የአለማችን ሃያላን ዝርዝር ከሰሞኑ ይፋ ያደረገ ሲሆን፣ የሩስያው ፕሬዚዳንት ቭላድሚር ፑቲን፣ ተመራጩ የአሜሪካ ፕሬዚዳንት ዶናልድ ትራምፕ እና የጀርመን መራሂተ መንግስት አንጌላ መርኬል በቅደም ተከተል ከአንደኛ እስከ ሶስተኛ ደረጃን ይዘዋል፡፡
የቻይናው ፕሬዚዳንት ዢ ጂፒንግ፣ የሮማው ሊቀጳጳስ ፍራንሴስ እና የአሜሪካ የፌደራል ሪዘርቭ ሃላፊ ጃኔት የለን እስከ ስድስተኛ ያለውን ደረጃ ሲይዙ፣ የማይክሮሶፍቱ መስራች ቢል ጌትስ፣ የአልፋቤት ኩባንያ ዋና ስራ አስፈጻሚ ላሪ ፔጅ፣ የህንዱ ጠቅላይ ሚኒስትር ናሬንድራ ሞዲ እና የፌስቡኩ መስራች ማርክ ዙክበርግ በቅደም ተከተል እስከ አስረኛ ደረጃን ይዘዋል፡፡ አምና 72ኛ ደረጃ ላይ የነበሩት ትራምፕ፣ በሚገርም መሻሻል ዘንድሮ ሁለተኛ ደረጃ ላይ የተቀመጡ ሲሆን፣ አምና በ2ኛ ደረጃ ላይ ተቀምጠው የነበሩት ተሰናባቹ ፕሬዚዳንት ባራክ ኦባማ በአንጻሩ ዘንድሮ ወደ 48ኛ ደረጃ አሽቆልቁለዋል፡፡ በዘንድሮው የፎርብስ የአለማችን ሃያላን ዝርዝር ውስጥ ሁለት አፍሪካውያን ብቻ የተካተቱ ሲሆን፣ 44ኛ ደረጃን የያዙት የግብጹ ፕሬዚዳንት አብዱል ፈታህ አል ሲሲ፣ ከአፍሪካውያን መካከል ቀዳሚው ሃያል ሰው ሲባሉ፣ የአፍሪካ ቁጥር አንድ ቢሊየነር አሊኮ ዳንጎቴ 68ኛ ደረጃን በመያዝ ሁለተኛው ሃያል ሰው ሆነዋል፡፡
በፎርብስ የአመቱ ሃያላን ዝርዝር ውስጥ ለመጀመሪያ ጊዜ ስማቸው የተካተተ ግለሰቦች ቁጥር 11 እንደሆነ የጠቆመው መጽሄቱ፣ ከእነዚህም መካከል የእንግሊዟ ጠቅላይ ሚኒስትር ቴሬሳ ሜይ እና የፊሊፒንሱ ፕሬዚዳንት ሮዲሪጎ ዱሬቴ እንደሚገኙበት ገልጧል፡፡ ፎርብስ መጽሄት የአመቱን የአለማችን ሃያላን የመረጠባቸው መስፈርቶች በብዙ ሰዎች ላይ ተጽዕኖ የማሳደር ብቃት፣ የፋይናንስ አቅም፣ የተጽዕኖ ወሰን ስፋትና አቅምን የመጠቀም ብቃት የሚሉ እንደሆኑ አስታውቋል፡፡

- ቱርክ ፌስቡክ፣ ትዊተርና ዋትዛፕን ዘግታለች

      የጀርመን ሶሻል ዲሞክራቲክ ፓርቲ ሊቀመንበር ቶማስ ኦፐርማን ፌስቡክ ሃሰተኛ ዜናዎችን በአፋጣኝ ከድረገጹ ላይ የማያስወግድ ከሆነ በአንድ ሃሰተኛ ዜና 500 ሺህ ዩሮ ቅጣት እንዲጣልበት የሚያስገድድ ህግ እንዲወጣ ሃሳብ ማቅረባቸውን ዘ ኢንዲፔንደንት ዘግቧል። ፌስቡክ ግለሰቦችንና ተቋማትን ተጠቂ የሚደርጉ ሃሰተኛ ዜናዎችንና መረጃዎችን በተመለከተ የሚቀርቡለትን አቤቱታዎች በአግባቡ ተቀብሎ አፋጣኝ እርምጃ እየወሰደ አይደለም ያሉት ኦፐርማን፤ ይህን እንዲያደርግ የሚያስገድድ ህግ መውጣት እንዳለበት ተናግረዋል፡፡ ፌስቡክ መሰል ሃሰተኛ ዜናዎችንና መረጃዎችን በተመለከተ የሚቀርቡለትን አቤቱታዎች ተቀብሎ፣ በ24 ሰዓታት ጊዜ ውስጥ ከማህበራዊ ድረገጹ ላይ የማይሰርዝ ከሆነ፣ እስከ 500 ሺህ ዩሮ የሚደርስ ቅጣት ሊጣልበት ይገባል ብለዋል፡፡ በመሰል ዜናዎችና መረጃዎች ተጠቂ የሆኑ ግለሰቦችና ተቋማትም ከፌስቡክ ካሳ ሊሰጣቸው ይገባል ሲሉም አክለዋል፡፡
ፖለቲከኛው ያቀረቡት የቅጣት ሃሳብ፣ አገሪቱ በመጪው የፈረንጆች አመት 2017 ልታካሂደው ያሰበቺው ፕሬዚዳንታዊ ምርጫ በማህበራዊ ድረገጾች አማካይነት ሊረበሽ ይችላል በሚል የጀርመን መንግስት በድረገጾቹ ላይ ጥብቅ ክትትል ሊደረግ እንደሚገባ የያዘው አቋም አካል ነው ተብሏል፡፡
በተያያዘ ዜናም፣ ባለፈው ሰኞ በቱርክ የሩስያ አምባሳደር አንድሪ ካርሎቭ በጥይት መገደላቸውን ተከትሎ፣ የአገሪቱ መንግስት ፌስቡክ፣ ትዊተርና ዋትዛፕን መዝጋቱን ዘ ቴሌግራፍ ዘግቧል፡፡

   - ከ26 በላይ ሰዎች ሲገደሉ፣ 45 ያህል ቆስለዋል - የ92 አመቱ ሙጋቤ በቀጣዩ ምርጫም ይወዳደራሉ

      የዲሞክራቲክ ሪፐብሊክ ኮንጎ ፕሬዚዳንት ጆሴፍ ካቢላ የስልጣን ዘመን ገደባቸው መጠናቀቁን ተከትሎ ስልጣን ለመልቀቅ ፍላጎት አለማሳየታቸው የቀሰቀሰው ከፍተኛ ተቃውሞ፣ በአገሪቱ ከፍተኛ ውጥረት የፈጠረ ሲሆን  የመንግስት የጸጥታ ሃይሎች እስካለፈው ረቡዕ ድረስ ከ26 በላይ ሰዎችን መግደላቸው ተዘግቧል፡፡
የፕሬዚዳንቱ የስልጣን ዘመን ቆይታ ባለፈው ማክሰኞ ቢያበቃም እስከ 2018 በስልጣናቸው ላይ እንደሚቆዩ በፓርቲያቸው ከተገለጸ በኋላ  የአገሪቱ የተቃዋሚ ፓርቲ አመራሮች የጠሩት ሰላማዊ ተቃውሞ ወደ ግጭት ማምራቱን የጠቆመው ዘገባው፤ በርካታ ተቃዋሚዎች ባለፈው ማክሰኞ የገዢውን ፓርቲ ቢሮ ማቃጠላቸውን ተከትሎ፣ በፖሊስና በተቃዋሚዎች መካከል ግጭት መከሰቱንና የጸጥታ ሃይሎች ቤት ለቤት አሰሳ በማድረግ በርካታ ዜጎችን ማሰራቸውን ገልጧል፡፡
በመዲናዋ ኪንሻሳ የተጀመረው ተቃውሞው ወደተለያዩ የአገሪቱ አካባቢዎች እየተስፋፋና ውጥረቱ እየተባባሰ መምጣቱን ያመለከተው ዘገባው፤ ተመድ 45 ያህል ተቃዋሚዎች በተተኮሰባቸው ጥይት መቁሰላቸውን ባለፈው ረቡዕ ማስታወቁንና በአገሪቱ የተሰማራው የተመድ የሰላም አስከባሪ ሃይልም ግጭቱ ወደ እርስ በእርስ ግጭት እንዳያመራ መስጋቱንና ውጥረቱን ለማርገብ እየተንቀሳቀሰ እንደሚገኝ አብራርቷል፡፡
አሜሪካ ፕሬዚዳንት ካቢላ ምርጫ እንዲካሄድ በማድረግ ስልጣናቸውን ለማስረከብ ተነሳሽነት አለማሳየታቸው አሳዝኖኛል ማለቷን የጠቆመው ዘገባው፤ በአገሪቱ ባለፈው ወር ላይ ምርጫ መደረግ ቢገባውም የምርጫ ኮሚሽኑ ሰበብ አስባብ በማብዛት ምርጫውን ማራዘሙ ካቢላን በስልጣን ላይ ለማቆየት የታሰበ ሴራ ነው የሚል ቁጣ መፍጠሩንም ገልጧል፡፡
ከ2001 አንስተው አገሪቱን በመምራት ላይ የሚገኙት የ45 አመቱ ጆሴፍ ካቢላ፣ በህገመንግስቱ በተደነገገው መሰረት ለሶስተኛ የስልጣን ዘመን መወዳደር የማይችሉ ቢሆንም፣ ፕሬዚዳንቱ ግን 74 አባላት ያሉት የሽግግር መንግስት በማቋቋም እስከ 2018 ድረስ አገሪቱን በመምራት ለመቀጠል አቋም መያዛቸውን ዘገባው አስረድቷል፡፡
በተያያዘ ዜናም፣ ከ36 አመታት በላይ ዚምባብዌን የመሩትና አገሪቱን ወደከፋ ኢኮኖሚያዊ ቀውስ ስላስገቧት ስልጣን ይበቃቸዋል የሚል ጫና ከውስጥም ከውጭም የበረታባቸው የ92 አመቱ የአገሪቱ ፕሬዚዳንት ሮበርት ሙጋቤ፤ ከአንድ አመት በኋላ በሚካሄደው ፕሬዚዳንታዊ ምርጫ እንደሚወዳደሩ ፓርቲያቸው አስታውቋል፡፡ ሙጋቤ በ2018 ምርጫ ለፕሬዚዳንትነት እንደሚወዳደሩ ይፋ መደረጉን ተከትሎ፣ የአገሪቱ ተቃዋሚ ሃይሎች የፓርቲውን ውሳኔ በማውገዝ አገሪቱን ወደ ከፋ ስራ አጥነት፣ የገንዘብ ቀውስና የኢኮኖሚ ድቀት ያስገቧት ሙጋቤ ስልጣን የሚይዙ ከሆነ የከፋ ቀውስ ይከተላል ሲሉ ማስጠንቀቃቸውን ዘ ጋርዲያን ዘግቧል፡፡
ፓርቲያቸው ዛኑ-ፒኤፍ ከሰሞኑ ባደረገው ጉባኤ ላይ በፓርቲው የወጣቶች ክንፍ፣ ሙጋቤ እስከ ህልፈተ ህይወታቸው የአገሪቱ መሪ ሆነው ይቀጥሉ የሚል ሃሳብ መነሳቱን ቢቢሲ ዘግቧል፡፡ በርካታ የአገሪቱ ዜጎች ባለፉት አመታት የሙጋቤን አምባገነናዊ ስርዓት በማውገዝ ተቃውሟቸውን አደባባይ ወጥተው ሲያሰሙ እንደነበርም ዘገባው አስታውሷል፡፡
በሌላ ዜና ደግሞ በቅርቡ በተካሄደው ምርጫ የተሸነፉትና ስልጣናቸውን እንዲለቁ በምዕራብ አፍሪካ አገራት ጫና ሲደረግባቸው የሰነበቱት የጋምቢያው ፕሬዚዳንት ያያ ጃሜህ፤ የማንም ጫና ከስልጣኔ አያስለቅቀኝም ሲሉ በድጋሚ በአቋማቸው መጽናታቸውን ዘ ጋርዲያን ዘግቧል፡፡ ፕሬዚዳንቱ ባለፈው ማክሰኞ በሰጡት መግለጫ፣ ከፈጣሪ በቀር ስልጣኔን ሊያስለቅቀኝ የሚችል አንዳች እንኳን ምድራዊ ሃይል የለም በማለት እቅጩን ተናግረዋል፡፡

  በሰሃራ በረሃ ውስጥ በሚገኘውና አልጀሪያንና ሞሮኮን በሚያዋስነው ተራራማ አካባቢ ከ37 አመታት በኋላ ለመጀመሪያ ጊዜ ባለፈው ሰኞ ማለዳ ላይ ያልተጠበቀ በረዶ መጣሉን የእንግሊዙ ሜትሮ ጋዜጣ  ዘግቧል፡፡ በረዶው ለአንድ ቀን ያህል ከቆየ በኋላ መቅለጡን የጠቆመው ዘገባው ፤ በሰሃራ በረሃ በረዶ ሲጥል ይህ በታሪክ ለሁለተኛ ጊዜ እንደሆነ በማስታወስ ክስተቱ ከአየር ንብረት ለውጥ ጋር ተያያዞ የመጣ ሊሆን እንደሚችል መነገሩንም ገልጧል፡፡
ከዚህ በፊት በሰሃራ በረሃ በረዶ ጥሎ የነበረው እ.ኤ.አ በ1979 ወርሃ የካቲት ላይ እንደነበር ያስታወሰው ዘገባው፤ በወቅቱ የጣለው በረዶ ለግማሽ ሰዓት ያህል ቆይቶ መቅለጡን በመጠቆም፣ ከዚያ ጊዜ ወዲህ ግን አንዲትም የበረዶ ቅንጣት በበረሃው ክልል ውስጥ ታይታ እንደማትታወቅም አክሎ ገልጧል፡፡

ታዋቂው የድረገጽ ኩባንያ ያሁ፣ ከ1 ቢሊዮን በላይ የያሁ አካውንቶች የኢንተርኔት መረጃ ዘራፊዎች ከሶስት አመታት በፊት የፈጸሟቸው የሚስጥራዊ መረጃ ዝርፊያ ጥቃቶች ሰለባ መሆናቸውን አስታውቋል፡፡
ያሁ ከሰሞኑ ባወጣው መግለጫ እንዳለው፣ እ.ኤ.አ በ2013 በተፈጸሙ ጥቃቶች ከአንድ ቢሊዮን በላይ የድረገጹ ተጠቃሚዎች ስም፣ የስልክ ቁጥር፣ ሚስጥራዊ የይለፍ ቃል፣ የኢሜይል አድራሻ እና ሌሎች ሚስጥራዊ መረጃዎች በዘራፊዎች ተሰርቀዋል፡፡ የኢንተርኔት ዘራፊዎች የተጠቀሱትን ሚስጥራዊ መረጃዎች ቢዘርፉም፣ የባንክና የክፍያ መረጃዎችን አለመዝረፋቸውን ኩባንያው አክሎ ገልጧል፡፡ ያሁ ባለፈው መስከረም ባወጣው መረጃ፣ በ2014 ላይም 500 ሚሊዮን ያህል አካውንቶች የመሰል ጥቃቶች ሰለባ መሆናቸውን እንዳስታወቀ ያስታወሰው ዘገባው፤ ኩባንያው ሰሞኑን ባወጣው መግለጫም የያሁ ተጠቃሚዎች ከመሰል አደገኛ የመረጃ ዘረፋዎችና ጥቃቶች ራሳቸውን ለመጠበቅ፣ የአካውንቶቻቸውን ሚስጥራዊ የይለፍ ቃሎችና የደህንነት ማረጋገጫ ጥያቄዎች እንዲቀይሩ ኩባንያው አሳስቧል፡፡
ተቀማጭነቱን በካሊፎርኒያ ያደረገው ያሁ፣ ከአንድ ቢሊዮን በላይ ወርሃዊ ተጠቃሚዎች እንዳሉት የጠቆመው ዘገባው፣ ዘራፊዎች የፈጸሙበት ጥቃት ቨሪዞን የተባለው ተቋም ያሁን ለመግዛት በጀመረው ድርድር ላይ አሉታዊ ተጽዕኖ ይፈጥራል የሚል ስጋት መፈጠሩንም አክሎ ገልጧል፡፡

 - ታዋቂ ድምጻውያን በበዓለ ሲመቱ ላይ አንዘፍንም ብለዋል
                        - ለመዝፈን ቃል የገባችው አንዲት ድምጻዊት ብቻ ናት

     ታዋቂዋ ድምጻዊት ሴሌን ዲዮን ተመራጩ የአሜሪካ ፕሬዚዳንት ዶናልድ ትራምፕ ከአንድ ወር በኋላ በዋሽንግተን ዲሲ በሚከናወነው በዓለ ሲመታቸው ላይ የሙዚቃ ስራዎቿን እንድታቀርብ ያቀረቡላትን ግብዣ አልቀበልም ማለቷ ተዘግቧል፡፡
ትራምፕ በበዓለ ሲመት አዘጋጆቻቸው በኩል ለሴሌን ዲዮን በክብር ግብዣ ቢያቀርቡላትም፣ ድምጻዊቷ በፕሮግራሙ ላይ ተገኝታ ለመዝፈን ፈቃደኛ አለመሆኗን እንደገለጸች ዘራፕ ድረገጽ ከትናንት በስቲያ ዘግቧል፡፡ ከሴሌን ዲዮን በተጨማሪ የትራምፕን ግብዣ አልቀበልም ያሉ ሌሎች አለማቀፍ ዝናን ያተረፉ ድምጻውያን መኖራቸውን የጠቆመው ድረገጹ፤ ከእነዚህም መካከል ኤልተን ጆን፣ ጋርት ብሩክስና አንድሪያ ቦሴሊ እንደሚገኙበት ገልጧል፡፡
አንዳንድ ድምጻውያን ፈቃደኝነታቸውን በመግለጽ በበዓለ ሲመቱ ላይ ለመዝፈን ቀጠሮ ቢይዙም፣ የትራምፕ ተቃዋሚ የሆኑ አድናቂዎቻቸው ባደረጉባቸው ጫና ሳቢያ ከሰሞኑ ሃሳባቸውን እንደቀየሩ የጠቆመው ዘገባው፤ አብዛኞቹ ድምጻውያን ግብዣውን ያልተቀበሉት በበዓለ ሲመቱ ላይ ተገኝተው በመዝፈን ለትራምፕ ፕሬዚዳንትነት እውቅና መስጠት ባለመፈለጋቸው ነው መባሉንም ጠቅሷል፡፡
በበዓለ ሲመቱ ላይ እንዲዘፍኑ ግብዣ ከተደረገላቸው ድምጻውያን መካከል እስካሁን ድረስ በፕሮግራሙ ላይ እንደምትገኝ ለአዘጋጆቹ ማረጋገጫ የሰጠቺውና በዝግጅቱ ላይ የአሜሪካን የህዝብ መዝሙር ለመዘመር ቀጠሮ የተያዘላት የ16 አመቷ ታዳጊ ድምጻዊት ጃኪ ኢቫንቾ ብቻ ናት ተብሏል፡፡