Administrator

Administrator

    ማልታ ጊነስ በአይነቱ ልዩ የሆነ የስኬት ቦርድ ውድድር ሰሞኑን በአዲስ ስኬት መዝናኛ ውስጥ አካሄደ፡፡ በ15 ተወዳዳሪዎች መካከል የተካሄደው የስኬት ቦርድ ውድድር፤ በአገራችን አምብዛም ያልተለመደውን የስኬት ስፖርት በስፋት እንዲለመድና ብቃት ያላቸው ተወዳዳሪዎችን ለማፍራት የበኩሉን እገዛ እንደሚያደርግ ተገልጿል።
ከአልኮል ነፃ በሆነው የማልታ ጊነስ ምርት ታጅቦ በተካሄደው በዚህ ውድድር ላይ ከ1-3 የወጡ ተወዳዳሪዎች የማልታ ጊነስ ምርት አምራች በሆነው ዲያጆ ኢትዮጵያ የተዘጋጀላቸውን ሽልማቶች ተቀብለዋል፡፡ ውድድሩ በራሳቸው የሚታማመኑና ብቃት ያላቸው የስኬት ቦርድ ስፖርተኞችን ለማፍራት እንደሚያስችል የማልታ ጊነስ ብራንድ ማናጀር አቶ አቤል አናጋው በውድድሩ ወቅት ተናግረዋል፡፡ በዚሁ የስኬት ቦርድ ስፖርት ውድድር ወቅትም ዲያጆ ኢትዮጵያ ለአዲስ ስኬት ፓርክ የ50ሺህ ብር ድጋፍ አድርጓል፡፡

    ስፔናዊው ቢሊየነር አማኒኮ ኦርቴጋ፤ባለፈው ሳምንት ረቡዕ እና ሃሙስ የማይክሮሶፍቱን መስራች ቢል ጌትስን በመብለጥ ለሁለት ቀናት ብቻ የአለማችን ቁጥር አንድ ቢሊየነር ሆነው እንደነበር ፎርብስ መጽሄት ዘግቧል፡፡ ታ
ዋቂውን ዛራ ጨምሮ የኦርቴጋ ኩባንያዎች ረቡዕ ዕለት የ2.5 በመቶ የአክስዮን ድርሻ ጭማሪ ማሳየታቸውን ተከትሎ፣ የቢሊየነሩ የሃብት መጠን በ1.7 ቢሊዮን ዶላር በማደግ 77.8 ቢሊዮን ዶላር መድረሱንና በዚህም ግለሰቡ የቤል ጌትስን ቦታ በመረከብ የአለማችን ቁጥር አንድ ቢሊየነር መሆን መቻላቸውን ዘገባው ገልጧል፡፡
አርብ ዕለት ማለዳ ግን፣ የእኒሁ ቢሊየነር ኩባንያዎች የአክስዮን ድርሻ በ2.8 በመቶ በመቀነሱ፣ ኦርቴጋ የአለማችን ቀዳሚ ቢሊየነርነቱን ስፍራ ለቢል ጌትስ በማስረከብ ወደ ሁለተኛ ደረጃቸው ተመልሰዋል ተብሏል፡፡
ኦርቴጋ ለመጀመሪያ ጊዜ የአለማችን ቁጥር አንድ ቢሊየነር ለመሆን የቻሉት ባለፈው የፈረንጆች አመት 2015 ጥቅምት ወር ላይ እንደነበር ያስታወሰው ዘገባው፣ በወቅቱ የተጣራ ሃብታቸው 80 ቢሊዮን ዶላር እንደነበርም ጠቅሷል፡፡

      የዛሬን አያድርገውና መስከረም አደይ ነስንሶ በችቦ እየሣቀ ሲመጣ በደስታ የማይፈለቀቅ ከንፈርና ልብ የለም፡፡ ጥሎብኝ እኔም ከመስከረም ጋር ለመሣቅ ነፍሴን ሞርጄ ነበር የምጠብቀው፡፡ ከልጅነቴ ጀምሮ ለአዲስ ዓመት የነበረኝ ፍቅር የትየለሌ ነው፡፡ ሀጫ በረዶ የመሠለው ጄረቴ… ጥርት ያለው ሠማይ፣ ድፍን ጨለማ ሀምሌ ውስጥ ሆኜ በዓይኔ ይመጣ ነበር፡፡… ዘንድሮ ግን ሣቄን የሚያጠፋ፤ ተስፋዬን የሚገፍ፤ ችቦዬን የሚነጥቅ ሀዘን ተፈጠረና የጭጋግ እንቁጣጣሽ አሣለፍኩ፡፡
ፕሮፌሰር መስፍን በ1958 ዓ.ም ተጠይቅ መስከረም ብሎ የፃፉት ግጥም ወደ ልቤ የመጣውም ይሄኔ ነው፤… እኔም በዕለተ እንቁጣጣሽ በJTV ያየሁትን ፕሮግራም አጥቅሼ ስለ ጀግንነትና ሀገር ወዳድነት፤ ስለተስፋና አዲስ ዘመን ጥቂት አሠኘኝ፡፡
መስከረም ተጠየቅ
ተናገር! አትሳቅ
ካልጋ ተቆራኝቶ ታሞ ለሚያጥረው
ወይ አይሞት ወይ አይድን ስቃይ ለታደለው
ለወላድዋ ድሃ ባልዋ ለሞተባት….
በፍርሃት በሥጋት ሥቃይ ለሚበሉት
ለላም አመጣህ ወይ ነፃነትና ሀብት?
ግጥሙ ጠበቅ ያለ ጥያቄ እየጠየቀ ይዘልቃል፡፡ እኔ ግን ወደ ራሴ ጥያቄ እመለሳለሁ፡፡ አዲስ ዓመት ምን አዲስ ነገር ይዞ መጣ ብቻ አይደለም፤እኛስ አዲሱ ዓመት አዲስ ዓይንና ጆሮ እንዲኖረው ምን አደረግን? ዓይነት!... ባለፈው ሰሞን በዚሁ ጋዜጣ ላይ ፖለቲካዊ ንዝረቴን ስለፃፍኩ፣ ዛሬ ወደ ማህበራዊውና ባህላዊው ጉዳይ ዘወር ማለት እፈልጋለሁ፡፡ በተለይ!... የሀገር መውደድ ትርጓሜያችንና በጐነታችንን በተመለከተ፡፡
ለመሆኑ ሀገር ጀግኖች ውስጥ መኖርዋን፣ሀገር በጀግኖች መፈጠርዋንና መቀረፅዋን እንረሣ ይሆን!... ይህንን ስሜትና ጥያቄ የፈጠረብኝ በጆሲ ኢን ዘ ሀውስ ላይ የተመለከትኩት የእንቁጣጣሽ የበዓል ዝግጅት ነው፡፡ ጆሲ ዓውደ ዓመቱን አስመልክቶ ወደ ተዘነጉ የኪነጥበብ ሰዎች ቤት በመሄድ፣ ዘሪቱ ጥላዬ ጨዋቃ፣ ግርማ አምሀ፣ኮሎኔል አብዲስ አጋ ቤተሰቦች ዘንድ ሙክት ይዞ በሥጦታ ታጅቦ፣ አበባየሁ ወይ ለምለም ከሚሉ ልጃገረዶች ጋር በር እያንኳኳ ጀግኖቻችንን ጠይቋል፡፡ በዓለም አደባባይ ያኮራንን የሴ/ኮለኔል አብዲሳ አጋን ታሪክ ፈትሾ፣ ከቤተሰቦቹ ጋር ሲያወጋ፣ በኢትዮጵያዊነቴ አፍሬያለሁ፡፡ ጀግናን ያለማክበር በሽታችን መች ይሆን የሚለቀን? ብዬ ራሴንና ትውልድን ጠይቄያለሁ፡፡
አብዲስ አጋ፤ በኢጣሊያ ሀገር ከእሥር ቤት አምልጦ ከተለያዩ ሀገር ዜጐች ጋር በመሆን የሠራው ጀብዱና ከዕብሪተኛው የሶማሊያ ሰራዊት ጋር ያደረገውን ጀግንነት የተሞላበት ጦርነት አስታውሼ፣ በአንፃሩ ደግሞ ይህንን ሁሉ ውለታ የዋለላት ሀገሩ፤ ለቤተሰቦቹ አንዲትም ጐጆ እንኳን ለመቀለስ ፍቃደኛ ያለመሆንዋ በእጅጉ ዘገነነኝ። ስንት ሕዝብ የዘረፉ ሰዎች ተንደላቅቀው በሚኖሩበት ሀገር፣ ያንን የመሠለ ጀግና ቤተሰቦች አንገታቸውን ደፍተው ሲኖሩ፣ በጊዜው የነበረው ደርግ ብቻ ሣይሆን አጠገቡ የነበሩ ኢትዮጵያዊያንስ እንዴት ዝም ብለው አዩ?-- የሚለው ነገር ጠዘጠዘኝ፡፡… የአብዲሳ አጋ ሕይወት እኮ የኢትዮጵያዊነት ክብር ነው፡፡… ግን አንድ ሁላችንም የምናውቀው በሽታ አለብን፤ በአብዛኛው እርሱ ምን ስለሆነ ነው? … የምትለዋ ዛሬም የተጣባችን ምቀኝነት አለች፡፡… ከሠለጠኑት ሀገራት ሸቀጥ ከምንሰበስብ በጐነትን ብንኮርጅ እንዴት ደግ ነበር… ግና እንዲያ አይደለም፡፡ እርሱ ምን ስለሆነ ነው? ለሚለው መልሱ ቀላል ነው፡፡ ጀግና ስለሆነ መከበር አለበት!!
“ኢትዮጵያዊነት” እያልን ስናቅራራ አፋችን ገደብ የለውም፡፡ ይሁን እንጂ ጀግኖቻችንን አኝከን አኝከን፣ በየደሳሳ ጐጆ ውስጥ ጥለናቸዋል፡፡ ጆሲ ወደተጣሉትና ወደታሰሩት ሰዎች ቤት ጐራ ባለ ቁጥር ነውራችንም አብሮ እየተገለጠ ነው፡፡ አደባባይ ላይ እጃችን ጢስ እስኪያወጣ ያጨበጨብንላቸው ሰዎች፣ሲወድቁ ዘወር ብለን አናያቸውም!... ነገር ግን እኛ ኢትዮጵያዊያን መልካም ነን ብለን በየመጠጥ ቤቱና በየአደባባዩ ስናቅራራ አንደኛ ነን …. ጀግናን ወርውሮ ማቅራራት ምን የሚሉት አመል ነው? ይልቁኑ ለመተቸት አንደኛ ነን፤ሰው የሠራውን ለማሽሟጠጥ ገደብ የለንም፡፡ ሰው ቢሠራ መከራ፣ ባይሠራም መከራ ነው!
ጋዜጠኞች፤ ጀግኖችን የፕሮግራም ማዋዣ ለማድረግ ሩጫችን ዳር የለውም፤… ከዚያ ባለፈ ግን ከሀብታምና ጊዜ ከሰጠው ጋር ሽር ጉድ ከማለት ያለፈ ሕልም የለንም፡፡ ጆሲ ግን ይህንን አድርጐታል፤ የአንድ ቀን እንግዶቹን ጉዳይ ለመፈፀም ስንት ቢሮ እንደደወለ፣ ስንቱን ደጅ እንደጠና እናውቀዋለን፡፡ (ከቢሮ ፀሐፊ ጀምሮ ያለውን ውጣ ውረድ መገመት አያዳግተንም፡፡)
ታዲያ የጆሲ ሥራ እነዚህን የሀገር ቅርሶች ከማገዝ ባሻገር ለቀጣይ ዘመን የሚያመጣው ውጤት አለ፡፡ ያም ዛሬ ጆሲን የሚያዩ ሕፃናትና ወጣቶች፤ ነገ ከኛ  የተሻለ ወገንን የመርዳት፣ ጀግኖችን የማክበር ዘር እንዲፀንሱ ያደርጋል፡፡ መልካም ነገር መሥራት ክብር እንደሆነ ያስተምራል፡፡ እንደ ብዙዎቻችን “ሀገሬ!” እያሉ ከንፈር ላይ ከሚተንን ወሬ የላቀ ውጤት ያመጣል!
የኛ ዘመን ከጀግና ይልቅ ሸቀጥን ያተለቀ፣ ከሀገር ይልቅ ሆድን ማዕከል ያደረገ መሆኑን ለማወቅ መፃሕፍት ማገላበጥ አያስፈልግም፡፡ በየጊዜው ብብታችን ሥር የሚፈለፈሉት “ሆዳሞች” ወገናቸውን ለቅንጣት ኑሮ ብለው እንደሚሸጡ፣ በሚፈስሰው ደሙ ላይ አበባ ነስንሰው እንደሚደንሱ በዐይኖቻችን አይተናል፡፡… ይህ ለኛ ብርቅ አይደለም። … በዚህ መሀል ግን አንዳንዱ ይጮሃል… አንዳንዱ ደወል ይደውላል፡፡ ሆዳሙ ግን መስሚያ የለውም፤… ጆሮው ላይ የሚያፋጨው ሆድ ነው፡፡ መብላትም መጠጣትም ነው፤ የሕይወቱ ግብ፡… ሰውነቱም እንደ በሬ ሥጋ መሸከም ብቻ ነው!!... እዚህ ጋ የዶክተር ፈቃደ አዘዘን ግጥም ልዋስ መሠለኝ፡- “ከበዳ ወደ በዳ” ይላል (“ዳ” ላላ ተደርጋ ትነበብ)
ይጮሃል ደራሲ
ይጮሃል አዝማሪ
ይጮሃል ከያኒ
ግን ማንስ አደምጦ
ኸረ ማንስ ሰምቶ?
ሁሉም እጆሮው ላይ በሆዱ ተኝቶ
አንድ ጣሳ አረቄ አንድ በርሚል ጠላ
ጠጅ ጠጅ አንቡላ
ከአሥራ አሥር ክትፎ ጋር አሥር ኪሎ ሥጋ
ቢጐምድ ቢሰለቅጥ ቢቸልስ ቢለጋ
ይመርጣል ዘመኑ
ጥበብ ለሱ ምኑ?
እውነት ነው፤መብላት መጠጣትና ቅንጦት የሰው ልጅ የኑሮ መለኪያ ሆኗል፡፡ ዶክተር ፈቃደ አዘዘ፤ ከያኔውንም እንደ ተቆርቋሪና ጉበኛ /ሀገር ተቆርቋሪ/ አድርጐ ቆጠረው እንጂ ዋና ባንዳዎቹ፣ ከያኒ ነን ባዮቹ ሆነዋል፡፡ ከስንት አንድ ነው ለሀገሩና ለወገኑ ተቆርቋሪ?... ብዙዎቹ ሆዳቸው አምላካቸው ነው፡፡ … ንባብ የለ፤ እውቀት የለ … ሽቀላ ብቻ… “ሆዳም” ሰው ደግሞ ፍቅር አያውቅም!... ስለዚህ ሀገሩንና ወገኑን ለመሸጥ ቅንጣት አይሳሳም፡፡
… ጆሲ ግን ቢያንስ ጀግኖቻችንን ከየሥርቻው ፈልጐ፣ ሕሊናችንን በፀፀት ጅራፍ ይገርፈዋል፡፡ ይህ ጅራፍ ቀጣዩን ትውልድ እንዳይገርፈው፣ጀግና አክባሪ ትውልድ ያሰለጥንልናል፡፡… ለዛራና ቻንድራ ፍቅር ከንፈሩን የሚመጠውና ለሀገሩ ጉዳይ ባይተዋር የሆነውን ሰው ያነቃቃልናል፡፡ አንዳንድ ሆድ ዓምላኩዎች ይህም ሊያስቀናቸው ይችላል። “ስፖንሰር ፍለጋ ነው!” ብለው በጐ ሥራው ላይ ጥላሸት ከመቀባት አይሳሱም፡፡ እኛ ጋ ግን እንዲህ እንላለን!... አንድ ቀን እንኳን ጀግኖችን መች አስባችሁ ታውቃላችሁ? ባለ ውለታዎችን ማክበርስ መች አስተማራችሁን? …
እኛስ ራሳችን ጀግኖቻችንን የማናከብረው እስከ መቼ ነው? … ብለን ራሳችንን ብንጠይቅ፣ መልሱ፡- እስክንሰለጥን የሚል እንደሆነ ጥርጥር የለኝም። ለጊዜው ግን አንዳች ጨለማ ጋርዶናል፤ አንዳች ዳፍንት ውጦናል!...
ለማንኛውም ሰዓሊና ገጣሚ ገብረ ክርስቶስ ደስታ፤ ”ሀገር” በሚለው ግጥሙ ከተቀኘው ጥቂት ስንኞችን ልዘምር፡-
አገሬ ውበት ነው
ለምለምና ነፋስ የሚጫወትበት
ጸሐይ የሞላበት ቀለም የሞላበት
አገሬ ቆላ ነው ደጋ ወይና ደጋ
እዚያ ብርሃን አለ ሌሊቱ ሲነጋ
ተስፋ አለኝ ይነጋል፡፡ ጀግኖች የሚኮሩበትን ሀገር እንፈጥራለን ብዬም አምናለሁ፡፡       

• ኢህአዴግ እንደ ገዢ ፓርቲ፣በአጠቃላይ ኢትዮጵያ ውስጥ ተቀባይነት አጥቷል
• ለህዝብ ጥያቄ ምላሹ እስራትና ግድያ ከሆነ፣ ችግሩን የበለጠ ያወሳስበዋል
• ተቃዋሚዎችና ምሁራን በገዢው ፓርቲ ፍራቻና ተጽዕኖ ሥር ናቸው
• ኢህአዴግም በያዘው መንገድ ችግሩን ይፈታል የሚልም እምነት የለኝም

በ97 ምርጫ ማግስት የፖለቲካ ቀውሱን ተከትሎ ታስረው ከተፈቱ በኋላ “አንድነት” ፓርቲን በመመስረትና በፕሬዚዳንትነት በመምራት የሚታወቁት አንጋፋው የተቃዋሚ ፓርቲ አመራር ኢ/ር ግዛቸው ሽፈራው፤ላለፉት ሁለት ዓመታት ራሳቸውን ከየትኛውም የፓርቲም ሆነ የፖለቲካ  እንቅስቃሴ አግልለው ቆይተዋል፡፡ በወቅታዊ አገራዊ ጉዳዮች ላይ ሃሳባቸውን ለመስጠት ግን ፈቃደኛ ሆነው፣ከአዲስ አድማስ ጋዜጠኛ አለማየሁ አንበሴ ጋር ተከታዩን ቃለምልልስ አድርገዋል፡፡

   በኦሮሚያና በአማራ ክልል ለወራት የዘለቁት የህዝብ ተቃውሞዎች መንስኤ ምንድን ነው ይላሉ?
ኢትዮጵያ አሁን ያለችበት ሁኔታ እጅግ አሳሳቢ ነው፡፡ በአማራና በኦሮሚያ ክልል ባለፈው አመት የታየው ተቃውሞ በኢትዮጵያ የወደፊት የማደግ፣ የመልማትና የህልውና ሁኔታ ላይ ትልቅ ጥያቄ የሚያስነሳ ነው፡፡ ለዚህ ሁሉ ዋናው መንስኤ ባለፉት 25 ዓመታት የዲሞክራሲ፣ የፍትህና የነፃነት እጦት ስለነበረ ነው፡፡ የዲሞክራሲ እጦት ነው የምልበት አንደኛው ማሳያ፣ ኢህአዴግ ያፀደቀውን ህገ መንግስት እንኳ እያከበረ አለመሆኑ ነው፡፡ ከየትኛውም ግለሰብም ሆነ ቡድን በላቀ ሁኔታ ህገ መንግስቱን የተፃረረው ኢህአዴግና የሚመራው መንግስት ነው፡፡ ለዚህ ማስረጃ ጥቀስ ከተባልኩ፣ በኢትዮጵያ ውስጥ ፓርቲዎች እንዲደራጁ ህገ መንግስቱ ይፈቅዳል፤ኢህአዴግ ግን በተግባር ፖለቲካውን የሚያንቀሳቅስ ፓርቲ እንዳይኖር የተለያዩ የአፈና መንገዶችን ሲጠቀም ቆይቷል። በመጀመሪያ አካባቢ በርካታ ፓርቲዎች ነበሩ፤ አሁን የሉም ማለት በሚቻልበት ደረጃ ላይ ናቸው፡፡ ያሉትም ከቢሮ ስራና ከመግለጫ ባሻገር እንቅስቃሴ የላቸውም፡፡ ለነዚህ ፓርቲዎች መቀጨጭ አንዱ መንስኤ በእርግጠኝነት የኢህአዴግ አፈና ነው፡፡ ስለዚህ ህገ መንግስቱ በጥሩ ቋንቋ ያስቀመጠውና የፈቀደው የመደራጀት መብት በኢህአዴግ መንግስት አልተተገበረም፡፡ ሌላው የሚዲያ ሁኔታ ነው፤ ከ97 ምርጫ በፊት በርካታ ነፃ ሚዲያዎች ነበሩ፡፡ አሁን ያሉት ከ5 የሚበልጡ አይደሉም። ብዙ ጋዜጠኞች ተሰደዋል፤ ቀሪዎቹም እስር ቤት ተወርውረዋል፡፡ ስለዚህ የቀሩት ጋዜጠኞች በፍርሃት ራሳቸውን ቆልፈው፣ ራሳቸውን በራሳቸው እየገደቡ የሚንቀሳቀሱ ናቸው፡፡ የመንግስት መገናኛ ብዙሃን የኢህአዴግ ልሳን እስከመሆን ደርሰዋል። የኢትዮጵያን ህዝብ ድምፅ የሚያንፀባርቁ አልሆኑም። የብዙሃኑን ድምፅ አያስተጋቡም፡፡ ይህ ባልሆነበት ሁኔታ ህዝብ የታፈነ ብሶቱን አደባባይ ወጥቶ ቢተነፍስ የሚደንቅ አይሆንም፡፡
ሌላው በሦስተኛ ደረጃ የፍትህ ስርአቱ ድክመት ነው፡፡ ብዙ ፖለቲከኞችና የህዝብ አፍ የሆኑ ጋዜጠኞች ወደ እስር ቤት ተወርውረዋል፡፡ እነ አንዷለም አራጌ፣ እነ እስክንድር ነጋ፣ እነ በቀለ ገርባ፣ እነ ኦላና----እስር ቤት ነው ያሉት፡፡ ይሄን ሁኔታ አብዛኛው ሰው ያውቃል፡፡ ህገ መንግስቱ የሰጣቸውን መብት ሲጠቀሙ ነው አሸባሪ ተብለው እስር ቤት የገቡት፡፡ ሌላው የሲቪል ተቋማትና የሙያ ማህበራት፣ እንደምናውቀው ያለ ኢህአዴግ ቡራኬ መንቀሳቀስ አይችሉም፡፡ ስለዚህ ለዲሞክራሲ ወሳኝ የነበሩት የሲቪክ ተቋማት፣ አሁን በጣም ቀጭጨው ነው ያሉት፡፡ ሌላው የምርጫ አስተዳደሩ ነው። ምርጫው ሙሉ በሙሉ በኢህአዴግ ቁጥጥር ስር ነው ያለው፡፡ ባለፉት 25 ዓመታት የተካሄዱት 5ቱም ምርጫዎች ዲሞክራሲያዊ፣ ፍትሃዊና ነፃ አልነበሩም፡፡ ትንሽ የተለየ ነገር የታየው በ1997 ምርጫ ነው፡፡ ከዚያ በኋላ ሁሉም ነገር ተዘግቷል። ኢህአዴግ መጀመሪያ በ99.6 በመቶ፣ ከዚያ መቶ በመቶ በሆነ ድምጽ አሸነፍኩ አለ፡፡ በምንም መመዘኛ በየትኛውም አለም ታይቶ የማይታወቅ ውጤት ነው የተመዘገበው፡፡ ብዝሃነት ያላት ሀገር ብትሆንም፣ የብዙሃኑ ድምፅ የሚስተጋባበት እድል አልተፈጠረም፤ በምርጫ ስርአቱ፡፡ በፓርላማው አንድ አይነት ቋንቋ ነው የሚነገረው፡፡ ህዝቡ ትክክለኛ ውክልና ኖሮት፣ ድምጹ እየተሰማ አይደለም፡፡ በጣም ዲሞክራሲያዊ የሆኑት የአውሮፓ ሀገሮች እንኳ 50 በመቶ ውጤት ማምጣት እየተሳናቸው፣ የጥምር መንግስት ነው እያቋቋሙ ያሉት፡፡ የህዝብ እምቢተኝነት የመጣው በእነዚህ ምክንያቶች ነው፡፡ መስከረም 30 አዲስ መንግስት በምርጫ ተመርጧል ተብሎ ተመስርቶ፣ተቃውሞው በሁለተኛ ወሩ በህዳር ነው በኦሮሚያ የጀመረው፡፡ እንዴት በ100 ፐርሰንት የተመረጠ መንግስት፣በዚህ ቅጽበት ተቃውሞ ሊገጥመው ቻለ? ይሄ መሰረታዊ ጥያቄ ነው፡፡ በሁለቱም ክልሎች የታዩት ተቃውሞዎች የተቀባይነት ማጣት ማሳያዎች ናቸው፡፡ ድርጅቶቹ እንዴት የህዝብ ተቀባይነት ማግኘት ተሳናቸው? በሁለቱ ክልሎች ህዝብ ኦህዴድና ብአዴንን አልተቀበላቸውም ማለት ነው፡፡ ይሄ የረጅም ጊዜ ብሶቶች ድምር ውጤት ነው፡፡
የህዝብ ተቀባይነት ማጣት እንዴት ተከሰተ?
ሁለቱ ድርጅቶች ኢህአዴግን ወክለው በአማራና በኦሮሚያ ክልል የሚንቀሳቀሱ ናቸው፤ይሁንና ህዝቡን በሚፈልገው መጠን አላረኩትም፡፡ እምነት አልጣለባቸውም፡፡ እነኚህ ድርጅቶች ህዝቡን በነፃነት ማስተዳደር አልቻሉም፡፡ የፌደራል ስርአቱ የሚለው፣ህዝቡ በራሱ ተወካዮች ይተዳደራል ነው። አሁን ጥያቄው፤እነዚህ ድርጅቶች ህዝቡን በአግባቡ ወክለውታል ወይ? የሚለው ነው፡፡ እነዚህ ድርጅቶች የማዕከላዊ መንግስት ተፅዕኖ አለባቸው፡፡ በሌላ በኩል የኢኮኖሚ ፍትሃዊ ተጠቃሚነት ጉዳይና የማንነት ጥያቄም አለ፡፡ የብአዴን አመራሮች፣ ፍላጎታችንን ማሟላት አልቻሉም ነው የሚለው ህዝቡ፡፡ ኦህዴድም የኦሮሚያን ህዝብ ሁለንተናዊ ፍላጎት እያሟላ አይደለም የሚል ነው መሰረታዊ ጥያቄው፡፡
ሁለቱ ድርጅቶች የህዝባቸውን ፍላጎት ማሟላት ያልቻሉበትን ምክንያት ዘርዘር አድርገው ሊነግሩን ይችላሉ?
ራሱ ኢህአዴግ እኮ የተወሰኑ ሰዎችና የህውሓት የበላይነት የሚታይበት ድርጅት ነው፡፡ ይሄ ጥሬ ሃቅ ነው፡፡ የኦሮሚያንና የአማራን ህዝብ የሚወክሉት ፓርቲዎች ከዚህ በመነሳት የሚወክሉትን ህዝብ በእኩል ቁመና በአግባቡ ሊወክሉት አልቻሉም፡፡ በኢኮኖሚ ተጠቃሚነት፣ በተለያዩ መሰረተ ልማቶች ተገቢውን ተጠቃሚነት እያገኙ አለመሆኑን ራሳቸው ይናገራሉ። ኢህአዴግ ውስጥ ዲሞክራሲያዊ አሰራር ስለሌለ፣ የበላይነት ያለው አካል አድራጊ ፈጣሪ ነው የሚሆነው። እነሱ ራሳቸው በቅርቡ ጥሩ አመራር ያገኘ ክልል ጥሩ ይለማል፤ ጥሩ ያላገኘ ይጎዳል ብለዋል፡፡ ይሄ መሸፋፈን ነው፡፡ እነዚህ ክልሎች ራሳቸውን በፈለጉት መንገድ ማስተዳደር ይችላሉ ወይ ሲባል እንደማይችሉ እያየን ነው፤ ህዝቡም ፊት ለፊት እየነገራቸው ነው፡፡ “የህውሓት የበላይነት ይቁም” የሚል ጥያቄ ታዲያ ከየት የመጣ ነው? ምክንያቱ ይሄው ነው፡፡ የበላይነት ያለው አካል፣ በክልሉ ቀርቶ ከክልሉ ውጪም ሁሉን ነገር ለመጠቅለል ፍላጎት ይኖረዋል፡፡
የህዝባዊ ተቃውሞውን ባህሪ እንዴት ገመገሙት?
የህዝቡ እምቢተኝነት አሁን ጎልቶ የወጣው በኦሮሚያና በአማራ አካባቢ ቢሆንም በሌላው አካባቢም ተመሳሳይ ነገር አለ፡፡ መጀመሪያ ኦሮሚያ ነበር፤ ወደ አማራ ሄደ፤ አዲስ አበባም ተሞክሮ ነበር። ይሄ ነገር ሁሉም ጋ የመነሳት አዝማሚያ ያለው ይመስላል፡፡ በደቡብ ኮንሶ አካባቢ ጥያቄዎች አሉ። በአዲስ አበባ አብዛኛው ህዝብ ዘንድ፣መንግስት በሚገባ ሀገር እያስተዳደረ አይደለም የሚል አመለካከት አለ፡፡ ይሄን በዳሰሳ ጥናት ማረጋገጥ ይቻላል፡፡ ጎልቶ የመታየትና ያለመታየት ጉዳይ ነው እንጂ እንደኔ ችግሩ አገር አቀፍ ነው፡፡ እንደ ገዢ ፓርቲ ኢህአዴግ በአጠቃላይ ኢትዮጵያ ውስጥ ተቀባይነት አጥቷል፡፡
ህዝባዊ ተቃውሞው የሚቀጥል ከሆነ፣ መጨረሻው ምን የሚሆን ይመስልዎታል?
እሱ በጣም አሳሳቢ ነው፡፡ ይሄ ይሆናል የሚል ሃሳብ እንደ ማቅረብ እንዳይሆንብኝ እንጂ ችግሩ በጊዜ መፍትሄ ካላገኘ (አያድርገውና) ሀገሪቱ ወደ ግጭት ልትገባ ትችላለች የሚል ፍራቻ አለኝ፡፡ ምክንያቱም የዲሞክራሲ፣ የፍትህ እጦት፣ የኢኮኖሚ ፍትሃዊ ተጠቃሚነት፣ የስራ አጥነትና የብሄረሰብ ግጭት የመሳሰሉት አስጊ ናቸው፡፡ የሀገሪቱን አጠቃላይ የመንግስት አስተዳደር የሚጎዳና የሀገሪቱን ህልውና የሚፈታተን ይመስለኛል፡፡ አሁን ያለው ሁኔታ በሚገባ ካልተስተናገደ ሀገሪቱ አደጋ ላይ ነች ብዬ እገምታለሁ፡፡
መንግስት ለችግሩ መፍትሄ አበጃለሁ እያለ ነው። መንግስት ችግሩን የተረዳበትና የመፍትሄ አሰጣጡን እንዴት ያዩታል?
መንግስት በመሰረቱ ችግሩን አውቆታል፤ የመፍትሄው አቅጣጫ ግን ወቅታዊና ችግሩን ያገናዘበ አይደለም፡፡ መግለጫ አውጥቷል፣ አንጋፋዎቹ አመራሮችም በሚዲያ ተናግረዋል፡፡ ሰዎቹ ችግሩን ያውቁታል፤ ግን አካሄዳቸው ለችግሩ መፍትሄ በሚሰጥ አግባብ አይደለም፡፡ ችግሩን እያወቁ በቀጥታ ለችግሩ መፍትሄ ከመስጠት ይልቅ ሌላ ከችግሩ ጋር የማይገናኝ መፍትሄ ማስቀመጥ፣ የበለጠ ነገር ማወሳሰብና ማባባስ ነው፡፡ መንግስት ችግሩን በተረዳበት መንገድ ትክክለኛ መፍትሄ መስጠት አለበት፡፡ የጉልበት መፍትሄ ዘላቂ አይሆንም፡፡ በኃይል በመሳሪያ፣ በደህንነት የሚሰጥ ምላሽ የህዝብን ጥያቄ አያቆምም፡፡ በመሳሪያ የሚሰጠው ምላሽ ችግሩን ይበልጥ ያባባሰው ይመስለኛል። ለህዝብ ጥያቄ ምላሹ እስራትና ግድያ ከሆነ መፍትሄው ይወሳሰባል፡፡ አሁን የተገደሉት 1ሺ ነው ይባላል፡፡ ጉዳዩ የቁጥር ጉዳይ አይደለም። አንድም ሰው መሞት የለበትም፡፡ ህዝቡ ባዶ እጁን ሰላማዊ ሰልፍ እስከወጣ ድረስ ሰላማዊ መስተንግዶ ማግኘት ህገ መንግስታዊ መብቱ ነው፡፡ ባለፈው ዚምባቡዌ ሰላማዊ ሰልፍ ነበር፤ አንድም ሰው አልሞተም፡፡ በኛ ሀገር ሰላማዊ ሰልፍ ለምንድነው አሳሳቢ የሆነው? ለምንድን ነው አስፈሪ የሚሆነው? የሚሰጡትም ምክንያቶች አንዳንዴ አሳፋሪ ናቸው። ራሳቸው ሰልፈኞቹ ታጥቀዋል ይባላል። ግን በሁለቱም አካባቢዎች፣ ኦሮሚያና ባህርዳር ላይ ያ ሁሉ ሰው ሲሞት የታጠቀ ሰልፈኛ አልነበረም፡፡ ፍቃድ ያልተሰጠው ሰልፍ የሚባል ነገር ደግሞ አለ። ይሄ ህገ መንግስቱን በግልፅ መፃረር ነው፡፡ ፍቃድ አያስፈልግም፤ ማሳወቅ በቂ ነው፡፡ ስለዚህ መንግስት ራሱ ችግሩን በደንብ እያወቀው፣ የሚያስቀምጠው መፍትሄ ግን መስመሩን የሳተ ነው፡፡
አንጋፋ የቀድሞ የኢህአዴግ ታጋዮች (የጦር ጀነራሎች) ሀገሪቱን ከውድቀት ለመታደግ በሚል የመፍትሄ ሃሳቦች እያቀረቡ ነው፡፡ በመፍትሄ ሃሳቦቹ ላይ የእርስዎ አስተያየት ምንድን ነው?
ችግሩ አሳስቧቸው የመፍትሄ ሃሳብ ሲያቀርቡ እያየን ነው፡፡ እነሱም ኢህአዴግ አምባገነን ሆኗል፤ አደጋ ከመምጣቱ በፊት የምርጫ ምህዳሩን አስፍቶ ሁሉም በምርጫው ተሣታፊ መሆን አለበት ብለዋል። መልካም ነገር ነው፤ ቢያንስ ግማሽ መንገድ ሄደዋል፡፡ እነሱ የሚሉት ጠቅለል ተብሎ ሲታይ፣ ኢህአዴግ እንዳለ ሆኖ ጥገናዊ ለውጥ ያድርግ ነው። ግን ህዝቡ በኢህአዴግ ላይ ምን ያህል እምነት አለው? የሚለውን አልተገነዘቡም፡፡ ለዚህ ነው ግማሽ መንገድ ሄደዋል ያልኩት፡፡
ኢህአዴግ በተሃድሶ ከተጋረጡበት ችግሮች የመውጣት ልምድ አለው፤አሁንም ስር ነቀል ተሃድሶ አድርጎ ችግሮችን እንደሚፈታ እየተነገረ ነው፡፡ እርስዎ ምን ይላሉ?
እርግጥ ነው በ1993 ተሃድሶ አካሂደዋል፡፡ በወቅቱ የተካሄደው ተሃድሶ ምክንያቱ፣ የኢትዮ-ኤርትራ ጦርነት የፈጠረውን ልዩነት ያስታከከ ነው እንጅ የህዝብ ቁጣ አልነበረም፤ የስልጣን ሽኩቻ ተሃድሶ ነው ያደረጉት። አሁን ደግሞ ህዝብ እምቢ ሲል ተሃድሶ እናደርጋለን ማለታቸው የእሣት ማጥፋት ዘመቻ ነው፡፡ ችግራቸውን  በሚገባ አልፈተሹም፡፡ የአመራር ችግር እንዳለባቸው ለመገንዘብ 15 አመት ሙሉ ምን አስጠበቃቸው? ተሃድሶ እኮ ችግር ሲመጣ ብቻ አይደለም፤በእቅድ በየጊዜው መደረግ አለበት፡፡  
አንዳንድ ወገኖች ከእንግዲህ ይህ መንግስት አብቅቶለታል ይላሉ፡፡ አሁን የተቀሰቀሰው ተቃውሞ መንግስት እስከመቀየር የሚያደርስ ይመስልዎታል?
በጣም አስቸጋሪ ነው፡፡ እርግጥ ይሄ መንግስት አበቃለት የሚሉ የተለያዩ ወገኖች አሉ፡፡ ግን ይሄ ሁኔታ ከስሜታዊነት የመጣ ይመስለኛል፡፡ ምክንያቱም የመንግስት መዋቅር ደካማ ቢሆንም የመኖር ጉልበት አለው፡፡ ጉልበቱ እስኪያልቅ ሊኖር ይችላል፡፡ አሁን አበቃለት፣ አለቀለት ማለት አያስችልም፡፡ መንግስት ችግሩን ተረድቶ ትክክለኛ መፍትሄ ካልሠጠ ግን ሁኔታዎቹ ወደዚያ ነው የሚያመሩት፡፡
በእንዲህ ያለ የቀውስ ወቅት ተቃዋሚ ፓርቲዎችና ምሁራን ሚናቸው ምን መሆን አለበት?
ይሄን በእውነት በአሳዛኝ መልኩ ነው የማየው። በአጠቃላይ ምሁራኑ ራሳቸውን ከኢትዮጵያ ፖለቲካ አግልለው ነው ያሉት፡፡ ምሁራን ለሃገር እድገትና ለውጥ መሰረት ናቸው፡፡ ይሄ ግን ለኢትዮጵያ ቅንጦት ሆኗል። ከአገሪቱ አሳሳቢ ችግር ራሱን አግልሎ ነው ያለው ምሁሩ። ይህም የሆነበት ምክንያት የዲሞክራሲ እጦት ነው፡፡ የመናገር ነፃነቱን፣ የመደራጀት ነፃነቱን ለመተግበር ምሁሩ ከፍተኛ ፍራቻ አለበት፡፡ ኢህአዴግ አካባቢ ምሁራንን የማሳተፍ ችግር አለ፡፡ ይሄ ነገር ግን ከሃላፊነት ራስን ማሸሽ ነው፡፡ መማር ማለት ትክክለኛ የሆነውንና ያልሆነውን የመለየት ክህሎት መላበስ ነው፡፡ ስለዚህ ትክክል የሆነውን ትክክል፤ ትክክል ያልሆነውን አይደለም ብለው በድፍረት መናገር አለባቸው፡፡
ተቃዋሚ ፓርቲዎችን በተመለከተ በኔ በኩል በተግባር የሚንቀሣቀስ ፓርቲ አለ ብዬ አላምንም። ፓርቲ ማለት ህዝብ የሚያደራጅ፣ ችግር ሲኖር ሠላማዊ ሰልፍ የሚጠራ፣ መንግስትን የሚፎካከር ነው፡፡ ከዚህ አንጻር ፓርቲዎች አሁን ያሉበት ደረጃ እጅግ የቀጨጨ ነው፡፡ ጋዜጣዊ መግለጫ በመስጠት ነው የተወሰኑት፡፡ ለዚህ ሁሉ መንስኤ ግን የገዥው ፓርቲ ተፅዕኖና ፍራቻ ነው፡፡ ተቃዋሚዎችም ምሁራንም አሁን ካላቸው ፍርሃት ተላቀው የሚገባቸውን ሚና መጫወት አለባቸው፡፡  
ብዙዎች አሁን ያለው የሃገሪቱ ሁኔታ በእጅጉ እንደሚያሳስባቸው ይናገራሉ፡፡ እርስዎ መፍትሄው ምንድን ነው ብለው ያስባሉ?
አንዳንድ ሰዎችና ድርጅቶች ከሚሰነዝሯቸው ሃሳቦች መፍትሄ መሠል ነገር አያለሁ፡፡ ግን መንግስት ያንን ተግባራዊ ያደርጋል ወይ? የሚለው የሁሉም ጥያቄ ነው። የሽግግር መንግስት፣ የባለአደራ መንግስት፣ የእርቅ መንግስት የመሣሠሉትና ጀነራሎቹ የሚሰነዝሯቸው የመፍትሄ ሃሳቦች ሁሉ መፍትሄ ሊሆኑ ይችላሉ፡፡ ግን ችግሩ እንዴት ነው የሽግግር መንግስት የሚቋቋመው? እንዴት ነው ባለአደራ መንግስት የሚቋቋመው? በማን አዘጋጅነት ነው የፖለቲካ ውይይት የሚደረገው? የሚሉት ላይ የቀረቡ ማብራሪያዎች የሉም፡፡ የመፍትሄ ሃሳቦቹ የአፈፃፀም ሁኔታ እጅግ ከባድ ነው፡፡ በአብዛኛው ኳሱ ያለው በኢህአዴግ እጅ ነው፡፡ ኢህአዴግ የሽግግር መንግስት ማቋቋም ፍላጎት አለው ወይ? በጭራሽ የሚያስበውም አይመስለኝም፡፡ ምህዳሩን ነፃ ያደርጋል ወይ? አይመስለኝም፡፡ አስተሳሰባቸው ይሄን ለማድረግ አይፈቅድላቸውም፡፡ መፍትሄ በእጃችን ነው የሚል አመለካከት ነው ያላቸው፡፡
እኛ ብቻ ነን የምናውቀው ነው የሚሉት፡፡ ነፃ ምርጫ ይካሄድ የሚለውን የጀነራሎቹን መፍትሄ ምናልባት ይቀበሉታል ብንል እንኳ ምርጫው ገና 4 ዓመት ይቀረዋል፡፡ የህዝቡ ጥያቄዎች እንዴት ነው 4 ዓመት የሚቆዩት? ወይም ምርጫው ወደዚህ መምጣት አለበት። ያንን ለማድረግ ቁርጠኝነት አለ ወይ? እነዚህ ከባድ ጥያቄዎች ናቸው፡፡ ከሁሉም ወገን የሚቀርቡ መፍትሄዎች መልካም ናቸው፤ ግን አተገባበር ላይ ለአፍ እንደሚቀሉት አይሆኑም፡፡ ስለዚህ በኔ ግምት ሁኔታው እየተባባሰ ሊሄድ ይችላል፡፡ ኢህአዴግም በያዘው መንገድ ለህዝብ ጥያቄ መልስ ሰጥቶ፣ ችግሩን ይፈታል የሚልም እምነት የለኝም፡፡ እኔ እንዲህ ነው የምለው መፍትሄ አላስቀምጥም፡፡ አሁን ያለው ሂደት ራሱ፣ የራሱን መፍትሄ ያመጣል የሚል እምነት ነው ያለኝ። መፍትሄው በሂደት ከእንቅስቃሴዎች የሚገኝ ነው የሚሆነው፡፡

ከ292 ሺህ በላይ የአገሪቱ ስደተኞች በኢትዮጵያ ይገኛሉ

      ባለፈው ሳምንት ብቻ ከ11 ሺህ በላይ የሚሆኑ ደቡብ ሱዳናውያን ስደተኞች በጋምቤላ ክልል በኩል ወደ ኢትዮጵያ እንደገቡ የተባበሩት መንግስታት ድርጅት የስደተኞች ኮሚሽን ትናንት ባወጣው መግለጫ አስታወቀ፡፡
በአገሪቱ እየተባባሰ የመጣው ግጭትና ውጥረት በርካታ ዜጎች አገራቸውን ለቀው ወደ ጎረቤት አገራት እንዲሰደዱ እያስገደዳቸው ነው ያለው ኮሚሽኑ፤ ባለፈው ሳምንት በስደት ወደ ኢትዮጵያ የገቡት ከ11 ሺህ በላይ ደቡብ ሱዳናውያን በኢትዮጵያ የሚገኙ የአገሪቱ ስደተኞችን ቁጥር ከ292 ሺህ በላይ እንዳደረሱት አስታውቋል፡፡
አብዛኞቹ ስደተኞች ናስር፣ ማባን፣ ማቲያንግና ማዩት በተባሉት የደቡብ ሱዳን አካባቢዎች የተጠናከረ ወታደራዊ እንቅስቃሴ በማየታቸውና አዲስ ግጭት ይከሰታል ብለው በመስጋት ስደትን የመረጡ ደቡብ ሱዳናውያን እንደሆኑም አስረድቷል፡፡
ባለፈው ሳምንት በጋምቤላ ክልል ድንበር አቋርጠው ወደ ኢትዮጵያ ከገቡት ደቡብ ሱዳናውያን ስደተኞች፤ አብዛኞቹ ሴቶችና ህጻናት ናቸው ያለው ኮሚሽኑ፣ ብዙዎቹም የኑዌር ጎሳ ተወላጆች እንደሆኑና 500 ያህሉ ስደተኞች ያለ ወላጅ ብቻቸውን ስደት የወጡ ህጻናት እንደሆኑ ገልጧል፡፡
በደቡብ ሱዳን የእርስ በእርስ ግጭት ሳቢያ ወደ ጎረቤት አገራት የተሰደዱ የአገሪቱ ዜጎች ቁጥር ከአንድ ሚሊዮን በላይ መድረሱን ያስታወቀው ተቋሙ፤ ከእነዚህም መካከል ከ185 ሺህ በላይ የሚሆኑት ካለፈው ሃምሌ ወር ወዲህ ስደት የወጡ እንደሆኑ አክሎ ገልጿል፡፡

    የአለማቀፉ የገንዘብ ተቋም አይኤምኤፍ ማኔጂንግ ዳይሬክተር ክርስቲያን ላጋርድ፣ ኢትዮጵያዊውን ኢኮኖሚስት አቶ አበበ አእምሮን የተቋሙ የአፍሪካ ክፍል ዳይሬክተር አድርገው መሾማቸውን ተቋሙ ከትናንት በስቲያ በድረ-ገጹ ባወጣው መግለጫ አስታወቀ፡፡ ላለፉት 22 አመታት በአለማቀፉ የገንዘብ ተቋም የሰሩት አቶ አበበ አእምሮ በተቋሙ፣ በነበራቸው ቆይታ፣ ሃላፊነታቸውን በአግባቡ መወጣታቸውን የገለጸው ተቋሙ፤ በተለያዩ የስራ መደቦች ላይ ባከናወኗቸው ውጤታማ ተግባራት የካበተ ልምድ እንዳላቸውም ጠቁሟል፡፡
“አቶ አበበ በተቋሙ በነበራቸው ቆይታ አብዛኛውን ጊዜያቸውን ከአህጉሪቱ ፖሊሲ አውጪዎች ጋር በቅርበት ሲሰሩ እንደመቆየታቸው የአፍሪካን ፈተናዎች በተመለከተ ጥልቅ ግንዛቤ አላቸው፡፡ በአመራር፣ በማስተባበርና በሌሎች መስኮች ያላቸውን ብቃት በተግባር ማረጋገጣቸው ለዚህ የስራ ሃላፊነት እንዲመረጡ አድርጓቸዋል” ብለዋል የተቋሙ ማኔጂንግ ዳይሬክተር፤ ክርስቲያን ላጋርድ፡፡
አቶ አበበ አእምሮ በተቋሙ ቆይታቸው፣ የአፍሪካ ክፍል የኡጋንዳ ከፍተኛ ተወካይና የደቡብ አፍሪካ ተልዕኮ ሃላፊ ሆነው ከመስራታቸው በተጨማሪ የአህጉሪቱ የኢኮኖሚ ትንበያን ጨምሮ በኮትዲቯር፣ ጋና፣ ኬንያ፣ ቡርኪናፋሶ፣ ጊኒ፣ ላይቤሪያና ሴራሊዮን በተለያዩ የስራ መደቦች ላይ ስኬታማ ስራ ማከናወናቸውንም ተቋሙ አስታውቋል፡፡
በተቋሙ የስትራቴጂ፣ ፖሊሲና ግምገማ ክፍሎች በተለያዩ ሃላፊነቶች ላይ በነበራቸው የስራ ቆይታ የአመራር ብቃታቸውን በተግባር ያስመሰከሩት አቶ አበበ፤ በአይ ኤም ኤፍ የአውሮፓ ክፍል፣ በቱርክ፣ ፖላንድና ፖርቹጋል ለረጅም አመታት መስራታቸውንና የተለያዩ ተልዕኮዎችን በአግባቡ እንደተወጡም ገልጧል፡፡ ከሲቲ ኦፍ ለንደን ፖሊቴክኒክ ተቋም በኢኮኖሚክስ የመጀመሪያ ዲግሪያቸውን ያገኙት ኢትዮጵያዊው የኢኮኖሚክስ ባለሙያ አቶ አበበ አእምሮ፤ ከለንደን ስኩል ኦፍ ኢኮኖሚክስ ደግሞ በኢኮኖሚክ ሂስትሪ የሁለተኛ ዲግሪያቸውን እንደተቀበሉ ተቋሙ ባወጣው መግለጫ አክሎ ገልጿል፡፡

   ደቡብ ሱዳን ለአመታት በእርስ በእርስ ጦርነት ስትታመስ፣ በርካታ ዜጎቿ ሲሞቱና ለስደት ሲዳረጉ፣የአገሪቱ ፕሬዚደንት ሳልቫ ኬር እና ተቀናቃኛቸው ሬክ ማቻር ግን፣በሚሊዮኖች ዶላር የሚቆጠር የህዝብ ሃብት ወደ ግል ካዝናቸው በማስገባት ቅሌት ተጠምደው እንደነበር አልጀዚራ ዘግቧል፡፡
ተቀማጭነቱ በአሜሪካ የሆነው ዘ ሴንትሪ የተባለ ተቋም በሳምንቱ መጀመሪያ ባወጣው የምርመራ ሪፖርት፣ ደቡብ ሱዳን በሁለቱ ተቀናቃኝ ሃይሎች የእርስ በእርስ ጦርነት ስትታመስ በቆየቺባቸው አመታት፣ ሳልቫ ኬርና ማቻር የህዝቡን ሃብት ሲዘርፉና በጎረቤት አገራት ባቋቋሟቸው የሪልእስቴትና ሌሎች ኩባንያዎች ጠቀም ያለ ትርፍ ሲያካብቱ ነበር ብሏል፡፡
“ዎር ክራይምስ ሹድንት ፔይ” የሚል ርዕስ ያለውና ለሁለት አመታት የዘለቀውን የተቋሙን ምርመራ መሰረት አድርጎ የተጠናከረው ሪፖርት እንደሚለው፤ሁለቱ የአገሪቱ ቀንደኛ የፖለቲካ መሪዎች በአስር ሺህ የሚቆጠሩ የአገሪቱ ዜጎችን ለሞት በዳረገው አስከፊ ጦርነት እጅግ ከፍተኛ የህዝብ ገንዘብ ወደ ግል ካዝናቸው አስገብተዋል፡፡ ሳልቫኬር ህጋዊ አመታዊ ደመወዛቸው 60 ሺህ ዶላር ቢሆንም፣ እጅግ ከፍተኛ ገንዘብ እንደሚያገኙና በአገራቸውም ሆነ በውጭ አገራት በድብቅ ታላላቅ ኩባንያዎችን እንደሚያንቀሳቅሱ ተደርሶባቸዋል። ቤተሰቦቻቸውም በአገሪቱ የነዳጅ፣ የማዕድንና የሌሎች ዘርፍ ንግድ ጠቀም ያለ ድርሻ አላቸው ብሏል- ሪፖርቱ፡፡
የቀድሞው የአገሪቱ ምክትል ፕሬዚደንት ሬክ ማቻርና ቤተሰቦቻቸውም አገሪቱ በጦርነት ስትታመስ፣የግል ሃብት በማካበት ተጠምደው ነበር የኖሩት፣ህዝቡ መከራውን ሲያይ እሳቸውና ቤተሰቦቻቸው ግን በናይሮቢ ባስገነቡት እጅግ ዘመናዊ ቤት ውስጥ የቅንጦት ኑሮን ሲመሩ ነበር ብሏል- ሪፖርቱ፡፡ 1.2 ሚሊዮን ደቡብ ሱዳናውያን በጦርነቱ ሳቢያ አገራቸውን ጥለው ሲሰደዱ፣ ሳልቫ ኬር እና ማቻር የግል ሃብት በማካበት ቅሌት ተጠምደው እንደነበር በተጨባጭ ማስረጃዎች አረጋግጫለሁ ብሏል ተቋሙ፡፡
በሺህዎች የሚቆጠሩ ደቡብ ሱዳናውያን ህጻናት የሚልሱ የሚቀምሱት አጥተው በርሃብ ሲቆራመዱ፣አራቱ የፕሬዚዳንት ሳልቫ ኬር ልጆች በናይሮቢ በሚገኝ እጅግ ውድ ትምህርት ቤት ውስጥ 10 ሺህ ዶላር እየተከፈለላቸው ተንደላቀው ይማራሉ ተብሏል፡፡ የደቡብ ሱዳን መንግስት ቃል አቀባይ በበኩላቸው፤ሪፖርቱን ረብ የለሽ ሲሉ ያጣጣሉ ሲሆን መንግስታቸው፣ ሪፖርቱን በአዘጋጀው ተቋም ላይ ህጋዊ እርምጃ ለመውሰድ ማቀዱን አስታውቀዋል፡፡

 ከታዋቂው ማህበራዊ ድረገጽ ፌስቡክ መስራቾች አንዱ የሆነው ቢሊየነሩ ደስቲን ሞስኮቪትዝ፣ ዶናልድ ትራምፕ የአሜሪካ ቀጣዩ ፕሬዚዳንት ሆነው እንዳይመረጡ ለማድረግ የሚውል 20 ሚሊዮን ዶላር መመደቡን ፎርብስ መጽሄት ዘግቧል፡፡
ሞስኮቪትዝ እና ባለቤቱ ለዲሞክራት ፓርቲ ደጋፊ ቡድኖች 20 ሚሊዮን ዶላር በመለገስ፣ ቅስቀሳዎችን በዘመቻ መልክ እንዲያጧጡፉና ሄላሪ ክሊንተን ትራምፕን በመርታት፣ቀጣዩዋ የአሜሪካ ፕሬዚዳንት እንዲሆኑ ለማስቻል ድጋፍ እንደሚያደርጉ አስታውቀዋል፡፡ ዶናልድ ትራምፕ በምርጫ አሸንፈው የአሜሪካ ፕሬዚዳንት ከሆኑ፣ አገሪቱ ወደ ውድቀት ማምራቷ አይቀርም፡፡ በአንጻሩ ሄላሪ ቢያሸንፉና ስልጣን ቢይዙ አገሪቱ ልእለ ሃያልነቷን አስጠብቃ ወደፊት ትጓዛለች፣ ስለዚህም ትራምፕ ወደ ዋይት ሃውስ የጀመሩትን ጉዞ ለማደናቀፍ፣እኔና ሚስቴ 20 ሚሊዮን ዶላር መድበናል ብሏል፤ሞስኮቪትዝ፡፡
ሞስኮቪትዝ ለትራምፕ ያለውን ተቃውሞ በይፋ ሲያስታውቅ ይህ የመጀመሪያ ጊዜው አይደለም ያለው ዘገባው፤ ባለፈው ሃምሌ ወር የትራምፕ መመረጥ የቴክኖሎጂ ፈጠራን አደጋ ላይ ይጥለዋል በሚል ፊርማቸውን ካሰፈሩ 145 ታዋቂ የቴክኖሎጂው ዘርፍ ባለሃብቶችና ተመራማሪዎች አንዱ  እንደነበርም አስታውሷል፡፡

   ከዕለታት አንድ ቀን በአንድ ትምህርት ቤት ውስጥ አንድ የድርሰት አስተማሪ ለተማሪዎቹ፤ “አንድ ታሪክ ፃፉ፡፡ ከዚያም ያ ታሪክ የሚሰጠንን ትምህርት ወይም ግብረገብነት ታስረዳላችሁ” ሲል ይገልጻል፡፡
ተማሪዎቹ ሁሉ የመሰላቸውን ድርሰት ይፅፋሉ፡፡ ሶስት ተማሪዎች ይመርጥና ታሪኮቻቸውን እንዲያነብቡ ይጠይቃል፡፡ የመጀመሪያዋ ልጅ፤ “አባቴ አንድ እርሻ አለው፡፡ የዶሮ እርባታም አለው፡፡ ዶሮዎቹ እንቁላል ሲፈለፍሉ ወደ ገበያ ወስደን እንቁላል እንሸጣለን፡፡ ጥሩ ገንዘብ እናገኛለን፡፡ አንድ ቀን ግን ከእርሻ ወደ ገበያ ስንሄድ መኪናችን ከሌላ መኪና ጋር ተጋጨና፣ ቅርጫት ውስጥ የነበሩት እንቁላሎች በሙሉ መሬት ላይ
ወድቀው ተሰባበሩ!” አለችና ጨረሰች፡፡ አስተማሪውም፤ “ከዚህ የምናገኘው ትምህርት ምንድነው?” ሲል ጠየቀ፡፡ ልጅቷም፤ “እንቁላሎቻችንን በሙሉ አንድ ቅርጫት ውስጥ አናስቀምጥ” ስትል መለሰች።
ሁለተኛው ልጅ የሚከተለውን ታሪክ አነበበ፤ “የእኔ አባት የዶሮ እርባታ አለው፡፡ በየሳምንቱ እንቁላሎቹን ማስፈልፈያ ሳጥን (ኢንኩቤተር) ውስጥ እንከታቸዋለን፡፡ ባለፈው ሳምንት ከአሥራ ሁለቱ እንቁላሎች ስምንቱ ብቻ ጫጩት ፈለፈሉ” አለ፡፡ አስተማሪው፣ “ከዚህ ታሪክ የምናገኘው ትምህርት ምንድነው?” ሲል ጠየቀ፡፡
ልጁም፤ “እንቁላሎቻችሁ ጫጩት ከመፈልፈላቸው በፊት አትቁጠሯቸው፡፡ ጫጩቶቹን ቁጠሩ”
ሶስተኛው ልጅ፤ “አባቴ ጦርነት ውስጥ ገብቶ ያውቃል፡፡ አውሮፕላን አብራሪ ነው፡፡ አውሮፕላኑ ተመታ። በጠላት ወረዳ ከመውደቁ በፊት ግን አባቴ በፓራሹት ወረደ፡፡ አንድ ጠመንጃ፣ አንድ ጎራዴና አንድ ሳጥን
ቢራ ይዞ ነበር የወረደው፡፡ መንገድ ላይ ቢራውን ጠጣው፡፡ እንደ ክፉ አጋጣሚ መቶ የሚሆኑ
የጠላት ወታደሮች መጡበት፡፡ አንድ ሰባ የሚሆኑትን በጥይት ጣላቸው። ጥይት ጨረሰ፡፡ ጎራዴውን
መዞ ሃያ የሚሆኑትን አንገታቸውን ቀላ፡፡ የጎራዴው ስለት ተሰበረ፡፡ በባዶ እጁ የቀሩትን ጣላቸው”
ሲል ጨረሰ፡፡
አስተማሪው፤
“ከዚህ የምናገኘው ትምህርት (ግብረገብነት) ምንድነው?” አለው፡፡
ተማሪውም፤
“አባቴ ከጠጣ በኋላ አይቻልም! ያኔ ከሱ ጋር መቀለድ አደገኛ ነው” አለ፡፡
*          *        *
ከየአንዳንዱ የህይወት እንቅስቃሴ የምናገኘው ትምህርት መኖር አለበት፡፡ ዕንቁላሎቻችንን ሁሉ፤ በአንድ ቅርጫት ውስጥ አለማስቀመጥ አደጋ በመጣብን ጊዜ ሁሉንም በአንዴ እንዳናጣ ይበጀናልና ትልቅ ጠቀሜታ አለው፡፡ አንድም ደግሞ ገበያችን ላይ ብቻ በማተኮር ለግጭት መዳረግ የለብንም፡፡ በዕንቁላሎቻችን ቁጥር ልክ ሁሉ ጫጩት እናገኛለን ብለን መገመትም የዋህነት ነው፡፡ የተቀፈቀፈው ሁሉ አይወለድም!! የታሰበው ሁሉ ፍሬ ላያፈራ ይችላል። የኢንኩቤተር ሙቀት ስላለ ብቻ ሁሉም ጫጩቶች እንደፈለግናቸው አይፈለፈሉም፡፡ ግምቶቻችንም መሰረት ያላቸው ሊሆኑ ይገባል ማለት ነው፡፡ ባለፉት ወራት እስከ አዲሱ ዓመት ድረስ ተከስተው የነበሩ የእንቅስቃሴ ሁኔታዎች አንዳንድ ትምህርትና ግብረ ገብነትን አስጨብጠውን ማለፍ አለባቸው! የህዝብ ብሶት ምሬትና ያልተመለሰ ጥያቄ ከጠባብ ንፍቀ ክበብኝነት ተነስቶ አገሩን ሊያዳርስ እንደሚችል ያመላክታል፡፡ መንግሥት ውጪያዊ ሰበብ መፈለጉን (externalization) እና በሌሎች ማላከኩን (Blame-shifting) ትቶ ራሱን ወደ ውስጥ እያየ መፈተሽ እንዳለበት መገንዘብ እንደሚገባው አይተናል፡፡ ግምገማዎቹን የለበጣ እንዳያደርጋቸው ታላቅ ኃላፊነትን የሚጠይቅ ሁኔታ ውስጥ መግባቱን አስተውለናል፡፡
አመራሮች ራሳቸውን ባልለወጡ ጊዜ ባለስልጣናትን ካንድ ወንበር ሌላ ወንበር ማሸጋገር ቢሮክራሲያዊ ሽርሽር ብቻ ነው! ጥፋትን እንደማንሸራሸር ነው! “የኔ ክልል ካንተ ክልል ይሻላል” ማለትም የእኩልነትን መርህ የጣሰ አመለካከት እንደሆነ ልብ ብለናል፡፡ ህዝብ ባለቤቱ የሆነን ጉዳይ፣ “ባለቤት የሌለው እንቅስቃሴ ነው” ማለት እንቅስቃሴውን እንዳላቆመውም አስተውለናል! የመንግስትን ስልጣን ለግል ጥቅም ማዋል፣ የአዘቦት ቀን ወግ ሆኖ ሳለ፤ ለእንቅስቃሴም ወሳኝ ጨዋታ ነው ብለን ማሰብም የዋህነት መሆኑን ተገንዝበናል፡፡ ለህዝብ ጥያቄ አፋጣኝ ምላሽ አለመስጠት አንድም ዳተኝነት ሳይሆን ተዓብዮ (arrogance)፤ አንድም ደግሞ ጠባብ አመለካከት ከመያዝ (Narrow Nationalism) የሚመነጭ፣ “ሁለት ጥፉ ካገር ጥፉ”፤ ሂደት ነበር፡፡ የክልል
ጠባብነት፣ አንድ ልዩ አደጋ እንደሆነ አንርሳ!
(Provincialism እንዲሉ)፡፡ ከሁሉም በላይ በቅራኔ ውስጥ መሸብለቃችንን አንርሳ። ባንድ ወገን “የህዝቡ ጥያቄ ትክክል ነው - አፋጣኝ መልስ ይሻል” እያልን፤ በሌላ ወገን “ህገ መንግስታዊ መብት ተጥሶ ሁከትና ብጥብጥ አያስፈልግም” ብለናል፡፡ ለምን? እንዴት? እንበል ጎበዝ! ዕውነተኛ ግምገማ መሰረቱ በህዝብ ማመን ነው! ጥልቅ ተሐድሶ መሰረታዊ ለውጥ የማምጣቱ ጉዳይ ካልሆነ ከንቱ ድካም ይሆናል!
የኢትዮጵያ መልክ እንዲለወጥ የአመራሮች አስተሳሰብ በግድ መለወጥ አለበት! ለውጥ ድንገቴ ሳይሆን ሂደት ነው! ገጠመኝም አይደለም!
እንግዲህ ለውጥ እንፈልጋለን ካልን፣ ኢትዮጵያ የ1966 ዓመተ ምህረትን ዓይነት፤ “ጉልቻ ቢለዋወጥ
ወጥ አያጣፍጥም” መሪ መፈክር አይሰራም ብላ ማመን ግዷ ነው!! ያየናቸው ጉልቻዎች በቂ
ናቸውና፡፡ ጎበዝ! ከስህተት እንማር! የተሻለ ስህተት እንሥራ - አሁንም አልረፈደም - ጉዟችን ገና
ነው - ምርጥ ስህተት እንስራ!!

በምግብ ዝግጅት ባለሙያዋ አዝመራ ካሳሁን የተፃፈውና ከ6 ወር ህፃን፣ ት/ቤት እስከ ሚቋጠር የልጆች ምግብ አዘገጃጀት ያስተምራል የተባለው “ከቤት እስከ ት/ቤት” የተሰኘ የህፃናት ምግብ አዘገጃጀት መፅሐፍ ዛሬ በካሌብ ሆቴል ከረፋዱ 4፡00 ጀምሮ ይመረቃል፡፡
በ51 ገፆች የተቀነበበውና በ50 ብር ለገበያ የቀረበው መፅሀፉ፤ የትኛውም ወላጅ በአካባቢው በቀላሉ በሚገኙ የምግብ ጥሬ ዕቃዎች ለልጆቹ እንዴትና በምን ሁኔታ ምግብ በማዘጋጀት መመገብና ጤናማ ማድረግ እንደሚችል ያሳያል ተብሏል፡፡በምርቃት ስነ - ስርዓቱ ላይ ወላጆች፣ የት/ቤቶች ባለቤቶች ህፃናት ላይ የሚሰሩ ድርጅቶችና በርካታ ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች እንደሚገኙ የመፅሀፉ አዘጋጅ ወ/ሮ አዝመራ ካሳሁን ተናግረዋል፡፡