Administrator

Administrator

 ሚዩዚክ ሜይዴይ ከኢትዮጵስ ኮሌጅ ጋር በመተባበር ‹‹ዛሬም እንጉጎሮ›› በተሰኘው የፕሮፌሰር መስፍን ወ/ማሪያም የግጥም መፅሀፍ ላይ ነገ ከቀኑ 8፡00 ሰዓት ጀምሮ በብሄራዊ ቤተ- መፅሀፍትና ቤተ መዛግብት አዳራሽ ውይይት ይካሄዳል፡፡  ለውይይት የመነሻ ሀሳብ የሚያቀርቡት በደብረብርሀን ዩኒቨርሲቲ የስነ-ፅሁፍ መምህርና በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የፒ. ኤች.ዲ እጩ የሆኑት ደራሲ ታደለ ፈንታው እንደሆኑ የተገለፁ ሲሆን በውይይቱ ላይ የመሳተፍ ፍላጎት ያለው ሁሉ እንዲገኝ  ሚዩዚክ ሜይዴይ ጋብዟል፡፡

ዛይ ራይድ ሜትር ታክሲዎች፤ በመጪው ሳምንት ስራ ይጀምራሉ

      አዲስ አበባ ከኒውዮርክና ጀኔቭ ቀጥላ ሶስተኛዋ የዲፕሎማቲክ ከተማ ናት፡፡ እነዚህ ዲፕሎማቶችና ቱሪስቶች እንዲሁም የመዲናዋ ነዋሪዎች ደረጃውን የጠበቀ አገልግሎት ይፈልጋሉ፡፡ ከ15 ዓመት በፊት በጣት የሚቆጠሩ ደረጃቸውን የጠበቁ ሆቴሎች ነበሩ፡፡ ዛሬ፣ ከ100 በላይ ሆነዋል፡፡ አዲስ አበባ መሃሏ ነው እንጂ በአራቱም አቅጣጫ ሲመለከቱ፤ “እውነት አዲስ አበባ ናት!” በማለት ያስገርማሉ - በሪል እስቴቶችና በግለሰቦች የተገነቡት ዘመናዊ መኖሪያ ቤቶች፡፡
የመዲናዋ ከፍተኛ ችግርና ራስ ምታት የሆነው የትራንስፖርቱ ጉዳይ ነው፡፡ መንግስት ታክሲዎች በቀጠና ተሰማርተው እንዲሰሩ አደረገ፡፡ ነገር ግን ችግሩ ባሰበት እንጂ አልተቀረፈም፡፡ ሐይገር ባስ አስመጣ፤ ችግሩ ግን ያው ነው፡፡ ቅጥቅጥ ቺኳንታዎች፣ ከፍተኛ የህዝብ ማመላለሻ አውቶብሶችና የሲቪል ሰርቪስ አውቶቡሶች በድጋፍ ሰጪነት እንዲሰሩ ተደረገ፡፡ ምንም ጠብ አላለም፡፡ በስራ መግቢያና መውጫ እንዲሁም በስራ ሰዓት ረዣዥም ሰልፎች መመልከት የዘወትር ልማድ ከሆነ ሰነባብቷል፡፡
ይህንን ችግር ለመቅረፍ አሁንም መንግስት አዲስ ነው ያለውን ዘዴ ቀይሷል፡፡ አንዱ ረዥም ርቀት ተጓዥ አውቶቡሶችን ማቅረብ ነው፡፡ ችግሩን ምንም ያህል አልቀረፉም እንጂ 50 አውቶቡሶች ስራ ጀምረዋል፡፡ ሌላው ዘዴ ደግሞ የታክሲ ማኅበራት ተደራጅተው ዘመናዊ ታክሲዎች እንዲያስገቡ ማድረግ ነው፡፡
በብርሃን ባንክ የገንዘብ ድጋፍ 750 ታክሲዎች ተገዝተው ከቀረጥ ነጻ ሊገቡ ነው ተብሏል፡፡ በዚህ በሁለተኛው ዘዴ በመሳተፍ ችግሩን ለመቅረፍና የበኩሉን ሚና ለመወጣት ያሰበ ወጣት፤ የአሜሪካና የሌሎች አገሮችን ልምድ ይዞ ብቅ ብሏል፡፡ የዛይ ራይድ መስራችና ዋና ሥራ አስፈፃሚ ወጣት ሀብታሙ ታደሰ፡፡ ዛይ ራይድ የሚሰራው በሶፍትዌር ነው፡፡ የታክሲ አገልግሎት የፈለገ ሰው www.zayride.com ገብቶ ታክሲ እንዲመጣለት ጥሪ ያደርጋል፡፡  አገልግሎት ፈላጊው በአገልግሎት መጠየቂያ ፎርም ላይ ስምና አድራሻውን ይጽፋል፡፡ ከዚያም ታክሲው በጂፒኤስ እየተመራ፣ ወዲያው በአድራሻው ከች ይላል፡፡ ዛይ፤ በዝዋይ ሐይቅ ደሴት ላይ የሚኖሩ ዜጎች መጠሪያ ነው፡፡ወጣት ሀብታሙ ባሌ ውስጥ በጎባ ከተማ ነው የተወለደው፡፡  በአራት ዓመቱ ወደ አዲስ አበባ መጥቶ ት/ቤት ገባ፡፡ እስከ 7ኛ ክፍል ከተማረ በኋላ፣ በ1981 ዓ.ም ከቤተሰቦቹ ጋር ወደ አሜሪካ ሄዶ ቦስተን መኖር ጀመረ፡፡ 13ኛ ዓመት በዓሉን ያከበረው እዚያ ነው፡፡ ቦስተን ማሳቹሴት ት/ቤት 9ኛ ክፍል ገብቶ፣2ኛ ደረጃን አጠናቀቀ፡፡ ከዚያም ከማሳቹሴት ዩኒቨርሲቲ  በኢኮኖሚክስ የመጀመሪያ ዲግሪውን አገኘ፡፡ ፍላጎቱ በቢዝነስ መሰማራት ስለነበረ፣በተማረው ትምህርት ተቀጥሮ አልሰራም፡፡ ከታላቅ ወንድሙ ጋር ቦስተን ውስጥ “ባሻ” የተባለ የኢትዮጵያ ሬስቶራንት ከፍተው መስራት ጀመሩ፡፡ ሀብታሙ፤አዲስ አበባ ህዝቡን የሚያሳትፍ፣የተሟላ ደህንነት ያለው፣ዘመናዊና ርካሽ የትራንስፖርት ሲስተም ያስፈልጋታል ይላል፡፡ ከተማዋ እያደገች እንደሆነ ጠቅሶ፣ አዳዲስ፣ መብራታቸው የሚሰራ፣ ፍሬናቸው ያልተበላሸ፣ ነዳጅ በየመንገዱ የማያልቅባቸው፣ ሁልጊዜ ፍተሻና ሰርቪስ የሚደረግላቸው፣ … ዘመናዊ ታክሲዎች ያስፈልጋታል ብሏል፡፡ ስለዚህ በኢንተርኔት የሚሠራ ሲስተም አዘጋጅቷል፡፡ አዲሱ ሲስተም ሞባይል ስልክ ላይ የሚጫን አፕሊኬሽን ነው፡፡ የታክሲ አገልግሎት ፈላጊው በጣቱ ሲስተሙን ሲነካ፣ ታክሲው በጥቂት ጊዜ ውስጥ ፈላጊው ያለበት ቦታ ይመጣለታል፡፡ ታክሲው ሲመጣ፣ ታርጋው፣ የአሽከርካሪው ስምና ፎቶ ለፈላጊው ይደርሳል፡፡ ለአሽከርካሪው ደግሞ የአገልግሎት ፈላጊው  ስም፣ ስልክ ቁጥርና ፎቶ ይደርሰዋል፡፡ ታክሲ ፈላጊው ስብሰባ ቦታ ወይም ገበያ መኻል ወይም ቢሮ አካባቢ ቢሆን፣ታክሲ አሽከርካሪው የአገልግሎት ፈላጊውን ማንነት በቀላሉ እንዲያውቅ ይረዳዋል፡፡ የታክሲው ሰሌዳ ቁጥርም ፈላጊው ዘንድ ስላለ በቀላሉ ሊያውቀው ይችላል፤በማለት ሀብታሙ አስረድቷል፡፡ ይህ ሲስተም ሁሉንም ሰው ተጠቃሚ ያደርጋል ይላል፡፡ በአሁኑ ወቅት ከተማው ውስጥ ባሉ አሮጌ ላዳዎች ኅብረተሰቡ ካልተቸገረ በስተቀር አይጠቀምም፡፡ ምክንያቱ ደግሞ የሚጠይቁት ዋጋ በጣም ውድ ስለሆነ ነው፡፡ ለትንሽ ርቀት የሚጠይቁት 50 እና 60 ብር ነው፡፡ እኛ ግን የምናስከፍለው መንግስትና ማኅበራቱ በሚወስኑት ታሪፍ በኪ.ሜትር አስልተን ነው፡፡ በዚህ አይነት ህዝቡ በተመጣጣኝ  ዋጋ አገልግሎት ያገኛል፡፡ አሁን ያሉት ላዳ ታክሲዎች  ብዙ ጊዜ ቆመው ነው የሚውሉት፡፡ የእኛ ታክሲዎች ግን ብዙ ምልልስ ያደርጋሉ፡፡ ለምሳሌ ፒያሳ የሄደ ታክሲ ባዶውን አይመለስም፤ከሄደበት ሌላ ተጠቃሚ ይዞ ይመለሳል፡፡ አሁን የሚገቡት አዲስ ታክሲዎች 750 ናቸው፡፡ ለከተማው ህዝብ በሙሉ አገልግሎት ለመስጠት በቂ አይደሉም፡፡ ስለዚህ አሁን በአገልግሎት ላይ ያሉትንም አሮጌ ላዳዎች እንጠቀማለን፡፡ በዚህ ዓይነት ብዙ ምልልስ ሲያደርጉ ጥሩ ገቢ ያገኛሉ፤ መኪናቸውንም ይቀይራሉ፤የከተማዋንም እይታ ይለውጣሉ፡፡
በከተማዋ ካሉት 26 ማኅበራት ውስጥ ከ6ቱ ጋር ለመስራት ባለፈው እሁድ መፈራረሙን ሀብታሙ ገልጿል፡፡ አብዛኞቹ የተፈራረሙባቸው ጉዳዮች ስነ ምግባርን የተመለከተ ነው፡፡ ታክሲ እያሽከረከሩ ጫት መቃም፣ ሲራ ማጨስ፣ ቤንዚን ሳይሞሉ መጓዝና መንገድ ላይ ማቆም፣ መጠጥ ጠጥቶ  ማሽከርከር፣ … ተጠቃሚዎች ወደ ታክሲ እንዳይመጡ ስለሚያደርጉ ክልክል ናቸው፡፡ የተሳፋሪው ደህንነት እንዲጠበቅ፣ ዕቃ (ሞባይል፣ ገንዘብ፣--) ረስቶ ቢወርድ ሾፌሩ ተጠያቂ ይሆናል፡፡ በነዚህ ነጥቦች ላይ ነው ተስማምተው የተፈራረሙት፡፡ ሌላው የዛይ ራይድ ጥቅም ለተማሪዎች አገልግሎት መስጠት ነው፡፡ ሲስተሙ ላይ የተማሪዎች አፕሊኬሽን አለ፡፡ አንድ ወላጅ ልጆቹን ት/ቤት ማድረስ የማይችልበት ሁኔታ ቢፈጠር፣ ዛይ ራይድን ጠርቶ ት/ቤት እንዲያደርስለት ማድረግና ልጆቹ ት/ቤት እስኪደርሱ በስልካቸው መቆጣጠር ይችላል፡፡ ታክሲው የት ጋ እንደታጠፈ፣ ስንት ደቂቃ እንደፈጀበት፣ የት እንደደረሰ፣ ልጆቹ ከታክሲው ወርደው ት/ቤት ሲገቡ፣ በሲስተሙ ይከታተላል፡፡  
ዛይ ራይድ፤አዲሶቹ ታክሲዎች እስኪገቡ ድረስ አይጠብቅም፡፡ በሚቀጥለው ሳምንት በ130 ላዳ ታክሲዎች ሥራ እንደሚጀምር ሀብታሙ ተናግሯል፡፡ አሁን ባጃጆችን አልመዘገቡም እንጂ በቅርብ ጊዜ ውስጥ ከከተማ ወጣ ወዳሉ ኮንዶሚኒየሞች የሚያደርሱ ባጃጆችን ለማሰማራት ዕቅድ አለው፡፡ ይህን ሲስተም ለመስራት 2 ሚሊዮን ዶላር (40 ሚ.ብር ገደማ) ያህል በጀት መድበው ነበር የተነሱት፡፡ ነገር ግን በየጊዜው አዳዲስ ነገሮች ስለሚጨመሩና የተሰራውም በየጊዜው መሻሻል ስላለበት፣ወጪው ከተገመተው በላይ ከፍ ማለቱን ሀብታሙ ታደሰ ተናግሯል፡፡ ይህ ሲስተም ከተጀመረ አራት ወይም አምስት ዓመት ቢሆነው ነው፤ይላል ሀብታሙ፡፡ በአሜሪካ ማሳቹሴትስ ከተማ የጀመረው UBR የተባለ ኩባንያ ነው፡፡ ይህ ኩባንያ በዓመት 60 ቢሊዮን ዶላር ያንቀሳቅሳል፡፡ ሲስተሙ በጎረቤት አገር ኬንያም እየተሰራበት ነው፡፡ ሲስተሙ ከተጀመረ ወዲህ የኬንያ አሽከርካሪዎች ገቢ በሦስት እጥፍ ማደጉን ሃብታሙ ገልጿል፡፡ ለአዲስ አበባ የላዳ ታክሲ ባለቤቶችም ሆነ ለአዲሶቹ የታክሲ ባለንብረቶችና ሹፌሮች ተስፋ ሰጪ ዜና ይመስላል፡፡ አገልግሎቱ በፍጥነት ከተስፋፋ ደግሞ የከተማዋ ነዋሪዎችንም ከታክሲ ወረፋ ግፊያ ይገላግል ይሆናል፡፡     

 በድርቁ የተጎዱ፣የምርጥ ዘርና የማዳበሪያ መግዣ አጥሯቸዋል
     በባሌ ዞን አጋርፋ ወረዳ ኢላጊጎዳሪ ቀበሌ ማዳበሪያ ሲገዙ ያገኘናቸው ወ/ሮ ከበቡሽ መንግሥቱ ገበሬ ናቸው፡፡ የ45 ዓመቷ ወይዘሮ፤5 ልጆቻቸውን የሚያሳድጉት አርሰው በሚያገኙት ገቢ ነው፡፡ አምና ብዙ አርሶ አደሮች በድርቁ ሲጎዱ፣ ወ/ሮ ከበቡሽ ጥሩ ምርት ማግኘታቸውን ይናገራሉ፡፡ ‹‹አምና ድርቅ አልጎዳኝም፤ ጥሩ ምርት አግኝቻለሁ፡፡ 4 ሄክታር መሬት ነው ያለኝ፤ ከአንድ ሄክታር 50 ኩንታል አግኝቻለሁ፡፡
‹‹በዚህ ዓመትም የተሻለ ጥሩ ምርት ለማግኘት ጥሩ ዝግጅት እያደረግን ነው፡፡ የእርሻ መሬቴን አራት ጊዜ አርሻለሁ፣ አንድ ጊዜ ነው የሚቀረኝ፡፡ አምና ዩሪያና ዳኘ ነበረ የተጠቀምኩት፡፡ ዛሬ የገዛሁት ዳፕ ነው፤ዩሪያ አላገኘሁም፡፡ ዳፑን 650 ብር ነው የገዛሁት፡፡ ምርጥ ዘርም ኩንታሉን በ800 ብር ገዝቻለሁ፡፡ የግብርና ባለሙያዎች ጥሩ ምርት እንድናገኝ ያሠለጥኑናል፤ በመስመር እንድንዘራ ይመክሩናል፤የመሬቱ ለምነት እንዲጨምር ዳፕና ዩሪያ ደባልቀን እንድንጠቀም፣ አረምና እንክርዳድ እንዳይወጣ ኬሚካል ያቀርቡልናል፡፡ በአጠቃላይ አብረን ነው የምንሠራው ማለት እንችላለሁ›› ብለዋል፡፡
አርሶ አደር አደም ሁሴን፤በአጋርፋ ወረዳ የአሊ ቀበሌ ነዋሪ ናቸው፡፡ አቶ አደምን ያገኘነው ለመኸር እርሻ መሬታቸውን ሲያዘጋጁ ነው፡፡ አቶ አደም በግላቸው 6 ሄክታር መሬት አላቸው፡፡ በኮንትራትና በእኩል ክፍያ የወሰዱት መሬት ስላለ፣ በአጠቃላይ 15 ሄክታር እያለሙ ነው፡፡ የቀበሌው ዋነኛ ምርት ስንዴ በዓመት አንዴ ነው የሚመረተው፡፡ ምክንያቱ ደግሞ በአካባቢው በቂ ዝናብ አይጥልም፡፡ ‹‹በበልግ የሚዘራው ገብስ፣ በቆሎ፣ ጤፍ፣ አተር፣… ናቸው፡፡ በአሁን ሰዓት የሚታየው የእነዚህ ሰብሎች ቡቃያ በጣም ጥሩ ነው፡፡ ባለፈው ዓመት የተከሰተው ድርቅ፤ አሊ ቀበሌ ይሻላል እንጂ ከጎናች ባሉ ቀበሌዎች አማለማ፣ ኤልምዲ፣አንድ ሌላ ቀበሌ ድርቅ ያስከተለው ጉዳት ከፍተኛ ነው፡፡ እህል ጠፋ፤ ከብቶች ተጎዱ፣ ሞቱ፡፡
 በዚህ ዓመት የዝናቡ አመጠጣጥ ጥሩ ስለሆነ፣ የእኛም ዝግጅት እንደዚያው ያማረ ነው፡፡ ማሳው አራቴ ታርሷል፣ ዘርና ማዳበሪያ ተገዝቷል፣ አንዴ አርሰን ለመዝራት ዝግጁ ነን፡፡›› ብለዋል፡፡
መንግሥት፣ የግብአት (ምርጥ ዘር፣ ማዳበሪያ…) አቅርቦት ቢያሟላም ጥቂት ችግሮች መኖራቸውን አቶ አደም አልሸሸጉም፡፡ ‹‹ማዳበሪያው ቢቀርብም አምና ስላላረስን መግዣ ገንዘብ አጥሮናል፡፡ ዘርም በግብርና ቢሮ በኩል ቢዘጋጅም እንደየፍላጎታችን አይደለም፤ ለሁሉም አልደረሰም፡፡ ነዋሪው ማዳበሪያና ምርጥ ዘር መግዣ ገንዘብ የለውም፡፡ ወረዳው እያደረገ ያለው ጥረት ቢኖርም ለሁሉም ማዳረስ አይችልም፤ በጣም አነስተኛ ነው፡፡ በድርቁ በጣም ተጎድተን ስለነበር መንግሥት ድጋፍ እንዲያደርግልን እንጠብቃለን፡፡›› በማለት አስረድተዋል፡፡ ስለ ማዳበሪያ ዋጋ መወደድ ሌሎች አርሶ አደሮችም ተናግረዋል፡፡
 አምና በአቶ አደም ማሳ አካባቢ መጠነኛ ዝናብ ጥሎ ስለነበር ብዙ አልተጎዱም፡፡ ‹‹ከሌሎች የተሻልኩ ነኝ›› ይላሉ፡፡ ዘንድሮ የአየር ሁኔታው ጥሩ ስለሆነና በዚሁ ዓይነት ከቀጠለ በሄክታር ከ80-90 ኩንታል እንደሚጠብቁ ገልጸዋል፡ ‹‹አምና ምንም ምርት አልነበረም ማለት ይቻላል፡፡ በሄክታር ከ20-30 ኩንታል ነው የተገኘው፡፡ ካቻምና (2006) ከ80-90 ኩንታል ስላገኘን ዘንድሮም እንደዚያ ነው የምንጠብቀው፡፡›› በማለት አጠቃለዋል፡፡
አቶ ጁሐር ጀማል፤ የአጋርፋ ወረዳ ግብርና ጽ/ቤት ም/ኃላፊ ነው፡፡ ወረዳው ዝናብ አጠር እንደሆነ ጠቅሶ አምና መጀመሪያ ላይ ዝናቡ ጥሩ ስለነበር፣ 12ሺህ ሄክታር መሬት መታረሱን፣ ነገር ግን ወደ ኋላ ላይ ዝናቡ ስለጠፋ ከፍተኛ ጉዳት ማስከተሉን፤ ዘንድሮም በመጋቢትና ሚያዝያ የጣለው ከፍተኛ ዝናብ ባስከተለው ጎርፍ 851  ሄክታር መሬት መጎዳቱን ገልጿል፡፡ የዘንድሮ በልግ ዝናብ አመጣጥና አጣጣል  ጥሩ ነው፡፡ በበልግ የተዘራው እህል በአንድ ማሳ እያደገ፣ በሌላው ደግሞ እየደረቀና እየታጨደ ስለሆነ፣ ከአምናው የተሻለ 300 ሺህ ኩንታል እህል ይገኛል ብሎ እንደሚገምት ተናግሯል፡፡  
አቶ ጁሐር ለመኸሩ ከፍተኛ ዝግጅት መደረጉን፣ መጪውን የአዝመራ ወቅት አስመልክቶ በጽ/ቤቱ ውይይት መደረጉን፣ ለግብርና ባለሙያዎችና ለአርሶ አደሮች ምን ማድረግ እንዳለባቸው፣እንዴት በዘመናዊ መንገድ ማረስ እንደሚገባቸው ሥልጠና መሰጠቱንና የቴክኒክ ድጋፍ መደረጉን ገልጿል፡፡ በወረዳው ካሉት 13,500 አርሶ አደሮች መካከል 93 በመቶ ለሚሆኑ ሥልጠና መሰጠቱን፣ ከታቀደው 18 ሺህ ኩንታል ማዳበሪያ ውስጥ 11 ሺህ ኩንታል በቀበሌ ማኅበራት በኩል በየቀበሌው እንዲደርስ እየተደረገ መሆኑን፣ ከኦሮሚያ ምርጥ ዘር ኢንተርፕራይዝ የተገኘ ምርጥ ዘር በወረዳው በሁለት ማዕከል ቀርቦ አርሶ አደሮች እየገዙ መሆናቸውን፤ በድርቁ ጉዳት የደረሰባቸውና በወረዳው አነስተኛ ገቢ ያላቸው 1,440 አርሶ አደሮች  ተለይተው፣ ከኦሮሚያ አነስተኛና ብድርና ቁጠባ፤ ብድር እንዲያገኙ እየተመቻቸ መሆኑን እንዲሁም ባለፈው ዓመት በድርቅ ለተጎዱ አርሶ አደሮች መንግሥት 4 ሺህ ኩንታል እህል ሰጥቶ መከፋፈሉን ተናግሯል፡፡
ም/ኃላፊው፤ በተለያዩ ምርቶች 89 ክላስተሮች ለማደራጀት አቅደው፣82 ክላስተሮች በማደራጀት ልጠና መሰጠታቸውን፤ በአራት ቀበሌዎች አርሶ አደሩ በገበያ ተፈላጊ የሆኑ ምርቶች እንደሚያመርት፣ አምና በተለያዩ ቀበሌዎች ያባዙት 7,921  ኩንታል ዘር ስላለ፣. ይህንን ዘር ከኦሮሚያ ምርጥ ዘር ኢንተርፕራይዝ ከገዙት ጋር እንዲጠቀሙ እንደሚደረግ ገልጿል፡፡ አንዳንድ አርሶ አደሮች የማዳበሪ ዋጋ ተወዷል ያሉትን አቶ ጁሐር አይቀበለውም፤ እንዲያውም ከአምናው የቀነሰ ነው ብሏል፡፡
ከዘንድሮ እርሻ 13 ሚሊዮን ኩንታል አንጠብቃለን
በዶዶላ ወረዳ ከባድ ዝናብ ጥሎ ኮረብታ ሰር ባለው በቀጨማ ጨፌና ገነታ ቀበሌዎች በ198 ሄክታር መሬት ላይ የተዘራ የስንዴ ማሳያ ያወደመው ሐምሌ 9 ቀን 2008 ዓ.ም ነው፡፡ ዝናቡ ከባድ መሆኑን፣ 2 ኪ.ሜ ከፍ ብሎ የሚገኘውን ወንዝ ድልድይ ሰብሮ ማሳዎቹን ማጥለቅለቁን በአደጋው ማግስት ከባሌ ዞን ስንመለስ በስፍራው ተገኝተን ተመልክተናል፡፡
ወ/ሮ ዲንሾ ብርቢሳ ማሳቸው በጎርፍ ከወደመባቸው አርሶ አደሮች አንዷ ናቸው፡፡ ድጋሚ ጎርፍ መጥቶ እርሻቸውን እንዳያወድም ከቤተሰቦቻቸው ጋር በማሳቸው አናት ቦይ ሲሰሩ ነው ያገኘናቸው፡፡ የወ/ሮ ዲንሾ መሬት 3 ሄክታር ተኩል ነው፡፡ 3 ኩንታል ማዳበሪያ ተጠቅመው ነበር ምርጥ ዘር ስንዴ የዘሩት፡፡ አሁን በእጃቸው ምንም ገንዘብ ያላቸውም፡፡ ወቅቱ ሳያልፍባች መልሰው ለመዝራት የመንግሥትን ድጋፍ ነው የሚጠብቁት፡፡ የ12 ልጆች እናት የሆኑት ወ/ሮ ዲንሾ በምን ያህል ገንዘብ እንዲሸጡ አያስታውሱም እንጂ ከአምናው እርሻ 190 ኩንታል እህል ነው ያገኙት፡፡ጎርፍ የተከሰተው ሌሊት ነው፡፡ ጧት ሰዎች መጥተው የሆነውን ነገሩን፡፡ ከግብርና ባለሙያዎች ጋር መጥተን ስናየው በ198 ሄክታር መሬት ላይ የተዘራው ሰንዴ ወድሟል፡፡ ያለው የዶዶላ ወረዳው ም/አስተዳዳሪና የግብርና ጽ/ቤት ኃላፊ አቶ ፌኔት አማን ነው፡፡ እነዚህን አርሶ አደሮች ጊዜው ሳያልፍባቸው መልሰው እንዲዘሩ ወራዳው ዘርና ማዳበሪያ በነፃ ለመስጠት ወስኗል፡፡ ስለዚህ ማሳቸው የወደመባቸውን አርሶ አዳሮች እየለየን ነው ብሏል፡፡
ከዘንድሮ እርሻ 13 ሚሊዮን ኩንታል እህል እንጠብቃለን ያሉት ደግሞ የምዕራብ አርሲ አስተዳደርና የግብርና ጽ/ቤት ኃላፊ አቶ ቶላ ገዳ ናቸው፡፡ አቶ ቶላ ስለ አምናው ድርቅ፣ ለዘንድሮው እርሻ አርሶ አደሩ እያደረገ ያለውን ዝግጅት ፤ ስለግብአት  አቆርቦት እንዲህ ሲሉ አጫውተውናል፡፡አምና በምዕራብ አርሲ ዞን ከ12 ወረዳ 7ቱ በድርቅ የተመቱ ነበር፡፡ ሁለት ወረዳዎች ደግሞ በዝናብ ብዛት ተጎድተዋል፡፡ አምናል በድርቅ የተጠቁ 126 ቀበሌዎች ሲሆኑ 307 ሺህ ሕዝብ ተጎድቷል፡፡ ሕዝቡ ከቤቱ እንዳይፈናቀል፤ ከቤቱ ርቆ እዳይሰደድ ከመንግሥትና መንግሥታዊ ካልሆኑ ድርጀቶች ጋር ብዙ ሥራ ሰርተረናል፡፡ ሕዝቡ በምግብ እጥረት እንዳይጎዳ በተለይ ሴቶችና ሕፃናት የምግብ አቀርቦት እንዲያገኙ ተደርጓል፡፡ ዘንድሮ በድርቅ ለተጎዱት ቀበሌዎች ምርጥ ዘርና ማዳበሪ በነፃ ሰጥተናል፡፡ በአጠቃላይ በእኛ ዞን 28 ሚሊዮን ብር ተመድቦ ስንዴ፣ በቆሎ፣ ጤፍ፣ ገብስ፣… የመሳሰሉን እህሎች ገዝተን ለዘር ሰጥተናል፡፡ መንግሥታዊ ያልሆነ ድርጅቶችም ይህን ያህል ገንዘብ አዘጋጅተው 13,600 ኩንታል ምርጥ ዘር በሁሉም ወረዳ አከፋፍለናል፡፡
በአምናው ድርቅ የሞተ ሰው የለም፡፡ በጎርፍ ግን ዘጠኝ ሰዎች ሞተዋል፡፡ 806 አባወራዎች ከቤት ንብረታቸው ተፈናቅለዋል፡፡ በአሁኑ ወቅት ወደ ቤታቸው መመለስ ያልቻሉ 39 አባወራዎች አስፈላጊውን ድጋፍ እያደረግን ነው፡፡ በጎርፍ የተጠቁ ወረዳዎች ሻላ፣ ሰራሮ በከፊል ሻሸመኔ በተወሰነ ደረጃ ደግሞ ዶዶላ እንዲሁም በዚህ ሳምንት የተከሰተ በገደብ አሳሳ ወረዳዎች ነው፡፡ በምርጥ ዘርና በማዳበሪያ አቅርቦ ምንም ችግር የለም ማለት ይቻላል፡፡ የማደበሪያ አቅርቦት ትንሽ ዘግይቶ ነበር፡፡ በአሁኑ ወቀት ከአቅዳችን 91 በመቶ አስገብተን 64 በመቶ ደግሞ አከፋፍለናል፡፡
በምርጥ ዘር በኩል ምንም ችግር የለም፡፡ በዞኑ 252,445 አርሶ አደር አለ፡፡ በበልግ 1.3 ሚሊዮን ኩንታል አንጠብቅ ነበር፡፡ ነገር ግን በድርቁ ምክንያት 900 ሺህ ኩንታል ነው ያገኘነው፡፡ በመኸር 13 ሚሊዮን ኩንታል እህል ለማግኘት አቅደናል፡፡ በዚህ ደግሞ በቂ ዝግጅትና ክትትል አድርገናል፡፡ ለዚህ የክረምት ወቀት 346 ሺህ ሄክታር መሬት የተዘጋጀ ሲሆን ከዚህ ውስጥ 97 በመቶው ታርሷል፤ 61 በመቶው ተዘርቷል፡፡ ቀሪውን ደግሞ በቀጣይ ጊዜ እንሸፍናለን፡፡›› ሲሉ ገልጸዋል፡፡

    የደቡብ ሱዳን ፕሬዚዳንት ሳልቫ ኬር፣ ባለፈው ሳምንት ከምክትል ፕሬዚዳንትነታቸው ካነሷቸው ተቀናቃኛቸው ሬክ ማቻር ጋር ግንኙነት አላቸው የሚሏቸውን ስድስት ሚኒስትሮች፣ባለፈው ማክሰኞ ከስልጣናቸው ማባረራቸውን ሮይተርስ ዘገበ፡፡በአገሪቱ ተቀናቃኝ ሃይሎች መካከል የተደረሰውን የሰላም ስምምነት በሚጻረር መልኩ ሹም ሽር አድርገዋል በሚል ሲተቹ የሰነበቱት የአገሪቱ ፕሬዚደንት ሳልቫ ኬር፤እነዚህን ሚኒስትሮች ማባረራቸው አገሪቱን ወደ ከፋ ቀጣይነት ያለው ግጭት ሊያስገባት እንደሚችል እየተነገረ ነው ብሏል ዘገባው፡፡ ፕሬዚዳንት ሳልቫ ኬር ከስልጣናቸው ያባረሯቸው ሚኒስትሮች፡- የአገሪቱ የነዳጅ፣ የከፍተኛ ትምህርት፣ የአገር ውስጥ ጉዳይ፣ የሰራተኞች፣ የውሃ እንዲሁም የመሬትና የቤቶች ልማት ሚኒስትሮች እንደሆኑ የጠቆመው ዘገባው፤ሚኒስትሮቹ እንዲባረሩ ሃሳብ ያቀረቡት ከሰሞኑ በፕሬዚዳንቱ አነጋጋሪ ውሳኔ በምክትል ፕሬዚዳንትነት የተሾሙት ታባን ዴንግ ጋኢ መሆናቸውንም ገልጧል፡፡ባለፉት 2 አመታት በአገሪቱ በተከሰቱ ግጭቶች፣በመቶ ሺህዎች የሚቆጠሩ ዜጎች መሰደዳቸውን ያስታወሰው የተባበሩት መንግስታት ድርጅት፤ከሶስት ሳምንታት በፊት በሁለቱ ሃይሎች መካከል ዳግም ግጭት ማገርሸቱን ተከትሎም ተጨማሪ 60 ሺህ ያህል ደቡብ ሱዳናውያን አገር ጥለው ተሰደዋል ማለቱን ዘገባው ገልጧል፡፡

ደራሲ ጄምስ ፓተርሰን በ95 ሚ. ዶላር ቀዳሚነቱን ይዟል
    ታዋቂው ፎርብስ መጽሄት፤በድርሰት ስራዎቻቸው ከፍተኛ ገቢ ያገኙ የአመቱ የዓለማችን እጅግ ሃብታም ደራሲያንን ዝርዝር በሳምንቱ መጀመሪያ ላይ ይፋ ያደረገ ሲሆን ባለፉት 12 ወራት ብቻ 95 ሚሊዮን ዶላር ገቢ ያገኘው ታዋቂው ደራሲ ጄምስ ፓተርሰን በአንደኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል፡፡ በወንጀል ነክ ድርሰቶቹ የሚታወቀው ጄምስ ፓተርሰን፤ ባለፉት ሶስት አመታት በፎርብስ የሃብታም ደራሲያን ዝርዝር ውስጥ ቀዳሚነቱን ይዞ መዝለቁን የጠቆመው መጽሄቱ፤ይሄው ደራሲ በቀጣዩ አመትም ክብሩን እንደጠበቀ ይዘልቃል ተብሎ እንደሚገመት አስታውቋል፡፡
በ2016 የአለማችን ሃብታም ደራሲያን ዝርዝር ውስጥ ሁለተኛ ደረጃን የያዘው 19.5 ሚሊዮን ዶላር ያገኘው የህጻናት መጽሃፍት ደራሲው ጄፍ ኬኒ ሲሆን  ሃሪ ፖተር በሚለው ተከታታይ መጽሃፏ አለማቀፍ ዝናን ያተረፈቺው ጄ ኬ ሮውሊንግ ደግሞ በ19 ሚሊዮን ዶላር ሶስተኛ ደረጃን ይዛለች፡፡ ጆን ግሪሻም በ18 ሚሊዮን ዶላር አራተኛ፣ ስቴፈን ኪንግ፣ ዳንኤላ ስቲልና ኖራ ሮበርትስ ደግሞ በተመሳሳይ በ15 ሚሊዮን ዶላር አመታዊ ገቢ አምስተኛ ደረጃን ይዘዋል፡፡ በዝርዝሩ ውስጥ ከተካተቱት ሌሎች ደራሲያን መካከልም ጆን ግሪን፣ ዳን ብራውንና ቬሮኒካ ሮዝ ይገኙበታል ተብሏል፡፡
የተለያዩ የአለማችን አገራትን ደራሲያን አመታዊ የመጽሃፍ ሽያጭና ገቢ በማስላት የላቀ ገቢ ያገኙ ደራሲያንን ዝርዝር ይፋ የሚያደርገው ፎርብስ መጽሄት፤ባለፉት 12 ወራት ከፍተኛ ገቢ ያገኙ በሚል በዝርዝሩ ያካተታቸው 14 የተለያዩ የአለማችን አገራት ደራሲያን በድምሩ 269 ሚሊዮን ዶላር ማግኘታቸውን አስታውቋል፡፡

የወርቅ ዋጋ መናር ለትዳር ፈላጊ ወንዶች ፈተና ሆኗል ተብሏል
     በግብጽ የወርቅ ዋጋ በከፍተኛ ሁኔታ እየናረ መምጣቱን ተከትሎ፣ የአገሪቱ ወንዶች ለሚያገቧት ሴት የወርቅ ጥሎሽ የሚሰጡበት ባህላዊ ልማድ እንዲቀር ለማድረግ የተጀመረው ዘመቻ ተቀባይነት እያገኘ መሆኑን ቢቢሲ ዘገበ፡፡ሻብካ በተባለው የግብጻውን ባህላዊ የሰርግ ልማድ መሰረት፣ አንድ ወንድ ሊያገባት ለሚፈልጋት ሴት የወርቅ ጌጣ ጌጦችን መስጠት እንደሚጠበቅበት የጠቆመው ዘገባው፣ አሁን አሁን ግን የወርቅ ዋጋ እየናረ መምጣቱ ለትዳር ፈላጊ ወንዶች ፈተና መሆን መጀመሩን ገልጧል፡፡በግብጽ የአንድ ግራም ባለ 24 ካራት ወርቅ ዋጋ 50 ዶላር ያህል መድረሱን የጠቆመው ዘገባው፤ይህም የትዳር ፈላጊ ወንዶችን አቅም እየተፈታተነ በመሆኑ በማህበራዊ ድረገጾች የወርቅ ጥሎሽ ባህሉ እንዲቀር ዘመቻ እንዲጀመር ምክንያት መሆኑን አስታውቋል፡፡ ዘመቻው መጀመሩን ተከትሎ በሺዎች የሚቆጠሩ ግብጻውያን፣ልማዱ አንዲቀር ድጋፋቸውን ማሳየታቸውን የጠቆመው ዘገባው፤የዘመቻው ደጋፊዎች በወርቅ ምትክ ብር ወይም ሌላ ውድ ያልሆኑ ጌጣጌጦች በጥሎሽ መልክ ቢሰጥ መልካም ነው ሲሉ አስተያየታቸውን እንደሰነዘሩ ገልጧል፡፡የወርቅ ጥሎሽ እንዲቀር ድጋፋቸውን የሰጡ አብዛኞቹ የዘመቻው ተሳታፊዎች ወንዶች ቢሆኑም፣በርካታ ግብጻውያን ሴቶች ይህንን ሃሳብ በመደገፍ ከወንዶች ጎን መሰለፋቸውንም ቢቢሲ ዘግቧል፡፡

   ከዕለታት አንድ ቀን፤ አንድ መንደር ውስጥ በርካታ የአይጥ መንጋ ይፈላና አካባቢውን ይወርረዋል፡፡ ይህን ችግር ለማስወገድ የሚቻለው ድመት ወዳለው ሰው ሄዶ ድመቱን ተውሶ አይጦቹን እንዲያስወግድ ማድረግ ነው፡፡
ስለዚህ የሰፈሩ ሰው መክሮ ተመካክሮ ድመት  ወዳለው ሰው ዘንድ ሄዶ፤
“ጌታ፤ እንደምታውቀው መንደራችን በአይጥ ተወሮ መድረሻ አሳጥቶናል፡፡ የአንተ ቤት ከዚህ ችግር ነፃ ነው፡፡ ድመት ስላለህ፡፡ የእኛ ግን አሁንም እንደተወረረ ነው፡፡ ስለዚህ፤ ድመትህን አውሰንና ሴት ድመቶችን አስወልዶ፡- አርብተን ከአይጥ ችግር ነፃ እንሁን?!” አለው፡፡
ባለ ድመቱም፤ ደግና አርቆ አሳቢ ሰው ኖሮ፤
“ዕውነት ነው፡፡ የእኔ ቤት ብቻ ከአይጥ ነፃ መሆን ችግሩን አያስወግደውም፡፡ ነገ የእናንተ ቤት አይጦች ወደ እኔ ቤት መምጣታቸው አይቀርም፡፡ ችግሩ ዙሪያ ገጠም (Vicious circle) ነው፡፡ ስለሆነም በሁሉም የሰፈሩ ሰው ቤት ያሉትን አይጦች ማስወገድ ነው የሚሻለው”፤ አለና ድመቱን አዋሳቸው፡፡
ድመቱ ስራውን ሰራ፤ ብዙ ድመት አስወለደ፡፡ አድገው አይጦቹን አሳደው በሉ፡፡ መንደሩ ከአይጥ ፀዳ! ሰላም ወረደ፡፡ ሜዳው ሁሉ ስጥ የሚሰጣበት እህል እንደ ልብ ፀሐይ እንዲመታው ሰሌን ላይ የሚዘረጋበት ወቅት ሆነ! ጥጋብ የአደባባይ ጉዳይ ሆነ!
ያም ድመት ቀን ወጣለት፡፡ እንደ ልቡ መብላት፣ መጠጣት፣ በየቤቱ ምግብ ማግኘት ዕድሉ ሆነ፡፡ ከሌላ ሰፈር ድመቶች ጋር ስሪያ፣ መዳራት፣ ማስረገዝ፣ ማስወለድ ሆነ ስራው፡፡ ምድር ሰማዩ በድመት ተሞላ!    
“ደሞ በድመት ብዛት ምሬት መጣ! “እነዚህ ድመቶች ወደ አጎራባች አገሮች በጉዲፈቻ እንስጣቸው!” ተባለ፡፡ ሁሉም ተስማማ፡፡ ሰፈሩ ከድመት ነፃ ሆነ፡፡ ዋናው ባለ ድመትም የራሱን ድመት ከእንግዲህ እንዳይወልድ አኮላሸው!
ለጥቂት አመታት ከአይጥ - ነፃ የሆነ ኑሮ ቀጠለ፡፡ ሆኖም አይጦቹ ጊዜ ጠብቀው መንደሩ በተዘናጋባት ሰዓት ከች አሉ፡፡ እህል ተበላ፡፡ ልብስ ተቀረጠፈ፡፡ መጽሀፍ ተከረተፈ፡፡ ችግር አጠጠ፡፡
እንደገና ህዝቡ ወደ ባለ ድመቱ መጣ፡፡
“እባክህ እንደ ካቻምናው ድመትህን አውሰን? ሴት ድመቶችን ያጥቃልን?” ሲሉ በትህትና ጠየቁት፡፡
“አዬ ወዳጆቼ! እኔስ ድመቱን በሰጠኋችሁ በፈቀድሁ፡፡ ግን አይጠቅማችሁም፡፡ ምክንያቱም፤ ዛሬ ድመቴ ተኮላሽቷል፡፡ አሁን አማካሪ (consultant) ሆኗል፡፡ የምክር አገልግሎት ብቻ ነው ሊሰጥ የሚችለው” አላቸው፡፡
*         *         *
ዛሬ ከስራ አስኪያጅነት ወደ አማካሪነት የሚመደቡ አያሌ ናቸው! በውሰት ችግርን ለመፍታት መሞከር ዘላቂ ሂደት አይሆንም፡፡ አንድ ጊዜ በዘመቻ የፈታነው ችግር መሰረታዊ መፍትሄ አገኘ ማለትም አይደለም፡፡ ሥር - ነቀል መፍትሄ ማግኘት ካስፈለገ፣ በቂ አቅም በገዛ ሀብት መፍጠር የግድ ነው፡፡ ይህን ለማድረግ ደግሞ ስራን በሙሉ ልብ የምንሰራበት ሁኔታ ማመቻቸት ግዴታ ይሆናል፡፡ ከዚህ ውስጥ አንዱ የተማረ ኃይልን በአመርቂ ሁኔታ ማሳተፍ ነው፡፡ አሳታፊ መድረክ መፍጠር ያስፈልጋል፡፡ ምሁራን አድርባይ፣ ተጠራጣሪና ፈሪ ከሆኑ የስራ ሁኔታው የስጋት እንጂ የልበ - ሙሉነት አለመሆኑን ነው የሚያመላክተን፡፡ ይህ ማለት ደግሞ ሙሉ  አቅማቸውን ለተፈለገው ግብ አያውለውም፣ አልፈው ተርፈውም እንቅፋት እስከመሆን ይደርሳሉ ማለት ነው። “መሳም ፈልገሽ፣ ጢም ጠልተሸ አይሆንም” የሚለውን ተረት አለመዘንጋት ብልህነት ነው። አሳታፊ መድረክ መፈጠር አለበት ሲባል፤ ዲሞክራሲያዊ መሆን አለበት፡፡ አሳታፊ መድረክ ይፈጠር ሲባል ፍትሐዊ፣ ኢ-ወገናዊ (non-nepotistic) ሁኔታ መኖር የለበትም ማለት ነው፡፡ አሳታፊ መድረክ ይኑር ሲባል፤ ስራ በብቃት፣ በጥራት፣ ጊዜን ቆጣቢ በሆነ መልኩ ያለብክነት የሚተገበርበት ሁኔታ ይፈጠር ማለት ነው፡፡ አሳታፊ መድረክ ይኑር ሲባል፤ ከታማኝነት አስቀድሞ የስራ ክህሎት መመዘኛ ይሁን ማለት ነው፡፡ አሳታፊ መድረክ ይኑር ሲባል፣ ግልፅነትና ተጠያቂነት፣ እገሌ ከእገሌ ሳይባል ሥራ ላይ ይዋል ማለት ነው፡፡ አሳታፊ መድረክ ይኑር ሲባል፣ ከሰራተኛው አማካሪው (consultant) አይብዛ ማለት ነው፡፡ ከሌላ ቦታ በድክመት የተነሳ፤ አማካሪ አይሁን ማለትም ነው፡፡ አሳታፊ መድረክ ይኑር ሲባል፤ የቅራኔና የእልህ መድረክ ሳይሆን ለሀገርና ለህዝብ ደህንነትና ዕድገት ሁሉም ፈትል ከቀስም ሆኖ በአንድነት የሚሰራበት መድረክ ይፈጠር ማለት ነው፡፡፡ አሳታፊ መድረክ ሲባል፣ ሙስና አልባ መድረክ መፍጠር ማለት ነው፡፡
ከቶውንም ዛሬ በሀገራችን ስራ በማንኪያ መብል በአካፋ የሆነበት ዘመን ነው፡፡ ይኸውም ባቋራጭ መክበርን እንደ ርዕዮተ ዓለም ይዞ የሚንቀሳቀስበት ዘመን ሆኗል፡፡ ዕድገት እየፋጠነ ነው እየተባለ የቦጥቧጩ፤ የሸርሻሪው ከአፍ እስከ ገደፍ መሆን፤ በግልም፣ በመንግስትም፣ መንግስታዊ ባልሆነ ድርጅትም ያለ ምህረት ምዝበራን ማካሄድ በአዋጅ የታዘዘ ይመስላል፡፡ እርግጥ አዋቂዎች፤ ዝመና (modernization) እና ሙስና ቁራኛ ናቸው ይላሉ፡፡ “ሙስና ከዝመና ጋር የሚመጡት የግለኝነትና የህዝብ ሀብት ልዩነት ውጤት ነው፡፡ አንድም ደግሞ ስኬታማ ያልሆነ የፖለቲካ ተቋማ አለመኖር ምልክት ነው፡፡ … ሙስና ህዝባዊ ሚናን ከግል ጥቅም ማምታታትንም ያሳያል፡፡ የህብረተሰቡ ባህል ንጉሱን እንደ ግለሰብ ሚናውን ካልለየና ንጉሱን እንደ ንጉስ ሚናውን ካልለየ፤ ንጉሱ የህዝብ ገንዘብ ለግል ጥቅማቸው አውለዋል ብሎ ሊከሳቸው አይቻለውም፡፡ የንጉሱ አካሄድ አግባብ ነው፣ አደለም ብሎ መፍረድም ያዳግተዋል!” በእኛ አገር አንፃር ሲታይ፤ ግልፅ ሌብነት ይፋ እየሆነ ከመጣ ውሎ አድሯል፡፡ እነ ናይጄሪያን ባንተካከልም በራሳችን የሚታይ፣ ያፈጠጠ፣ ያገጠጠ ሙስና አለን፡፡ ኤም.ጂ ስሚዝ የተባሉ ፀሐፊ፤ “ብሪታኒያው ሙስና የሚለውን፣ አውሳው ግፍ ይለዋል፡፡ ናይጄሪያዊው ፍላኒ ግን አስፈላጊና ባህላዊ ተግባር ነው ይለዋል” ይሉናል። ዞሮ ዞሮ እየዘመንን ስንመጣ፣ ሙስናችን ዳር ድንበሩን እደጣሰ ታዝበናል፡፡ አስከፊው ነገር ደግሞ ሃይ ባይና ተቆጪ ብሎም ቀጪ፤ አለመኖሩ ነው፡፡ ሁሉ ተነክሮበት ማ፣ ማንን ይቅጣ? “እኔ ትንሽ ብቻ ነው የወሰድት” የሚሉ ሹማምነት እንዳሉ ቢሰማም ጆርጅ በርናርድ ሾ እንዲህ ይመልስላቸዋል፡- There is no little pregnancy! - የእርግዝና ትንሽ የለውም ማለቱ ነው፡፡ የሙስናም ትንሽ የለውም፡፡ ኃጢያት ከኃጢያት ማወዳደር ሳይሆን ከኃጢያት መንፃት ነው ታላቁ ቁም ነገር! ማንም ከህግ በላይ አይደለም ካልን፤ “all men are equal but some men are more equal” “ሁሉም ሰው እኩል ነው፤ አንዳንድ ሰዎች ግን የበለጠ እኩል ናቸው” ማለትን ምን አመጣው?! ከዚህም እንንፃ!

    ኢትዮጵያ ለኬንያ የኤሌክትሪክ ሃይል ለመሸጥ የያዘቺው እቅድ ዋነኛ አካል የሆነውና 1.2 ቢሊዮን ዶላር ወጪ የሚደረግበት የኤሌክትሪክ ሃይል ማስተላለፊያ መስመር ግንባታ በዚህ ሳምንት መጀመሩን ስታንዳርድ ሚዲያ ዘገበ፡፡1 ሺህ 45 ኪሎ ሜትር ርዝመት ያለውንና 2 ሺህ ሜጋ ዋት የኤሌክትሪክ ሃይል የማስተላለፍ አቅም እንዳለው የተነገረለትን የዚህን የማስተላለፊያ መስመር ግንባታ የሚያከናውነው ቻይና ኤሌክትሪክ ፓዎር ኢኩፒመንት ቴክኖሎጂ የተባለው ኩባንያ እንደሆነ የጠቆመው ዘገባው፣ ግንባታው በታህሳስ ወር 2018 ይጠናቀቃል ተብሎ እንደሚጠበቅ ገልጿል፡፡ኬንያ ከኢትዮጵያ 400 ሜጋ ዋት የኤሌክትሪክ ሃይል ለመግዛት ስምምነት መፈጸሟን የዘገበው ሱዳን ትሪቢዩን በበኩሉ፣ በቀጣይም የምትገዛውን የኤሌክትሪክ ሃይል መጠን በብዙ እጥፍ ለማሳደግ ማሰቧን አስነብቧል፡፡በሁለቱ አገራት መካከል የሚዘረጋው ይህ የኤሌክትሪክ ሃይል ማስተላለፊያ መስመር፣ በ2018 ዓ.ም ለ870 ሺህ አወዎራዎች የኤሌክትሪክ ሃይል አቅርቦት ያሟላል ተብሎ እንደሚጠበቅ የአፍሪካ ልማት ባንክ ማስታወቁንም ዘገባው ጠቁሟል፡፡
በተያያዘ ዜናም ግልገል ጊቤ ሶስት የኤሌክትሪክ ሃይል ማመንጫ ግድብ፣ 800 ሜጋ ዋት ሃይል ማመንጨት መጀመሩን የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ሃይል ዋና ስራ አስፈጻሚ ኢንጂነር አዜብ አስናቀ ተናግረዋል፡፡
የግልገል ጊቤ ሶስት የኤሌክትሪክ ሃይል ማመንጫ ግድብ ግንባታ፤ 96 በመቶ እንደደረሰም ኢንጂነር አዜብ አስታውቀዋል፡፡

    በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የአይን ህክምና መምህሮች የተቋቋመው “ዲማ” የአይን ህክምና ክሊኒክ፤ሙሉ በሙሉ ስራ መጀመሩን አስታወቀ፡፡ ክሊኒኩ ከሌላው የአይን ህክምና በተለየ በአይን ቆብና በእንባ መፍሰስ ህክምና ላይ ትኩረት አድርጎ እንደሚሰራና በአገሪቱ ሁለቱ ህክምናዎች ላይ ስፔሻላይዝድ ያደረጉ ሁለት ኢትዮጵያዊያን ዶክተሮች ብቻ እንዳሉ የክሊኒኩ መስራች አባል ዶ/ር መሰረት እጅጉ ሰሞኑን ለጋዜጠኞች በሰጡት መግለጫ አስታውቀዋል፡፡ በአሁኑ ወቀት የእንባ መፍሰስ፣ የአይን ቆብና የአይን ቆብ አካባቢዎችን በማከም ትኩረት ያደረገው ክሊኒኩ፣ ሌሎችንም የአይን ህክምናዎች እግረ መንገዱን እንደሚሰጥና በተለያዩ አደጋዎች አይናቸውን ያጡ ሰዎች፣ በቀዶ ጥገና አርቴፊሻል አይኖችን እንደሚተክሉ ዶ/ር መሰረት ተናግረዋል፡፡

በአለማቀፍ የስማርት ፎን ገበያ ቀዳሚነትን ይዞ የዘለቀውና አይፎን ስልኮችን አምርቶ ለአለማቀፍ ገበያ ማቅረብ ከጀመረ ዘጠኝ ያህል አመታትን ያስቆጠረው ታዋቂው የቴክኖሎጂ ኩባንያ አፕል፤በእነዚህ አመታት 1 ቢሊዮን የአይፎን ስልክ ምርቶቹን ለደንበኞቹ መሸጡን ባለፈው ረቡዕ አስታወቀ፡፡
የአፕል ኩባንያ ዋና ስራ አስፈጻሚ ቲም ኩክ የሰጡትን መግለጫ ጠቅሶ ኤንቢሲ ኒውስ እንደዘገበው፤የአይፎን ስልክ ምርቱን እ.ኤ.አ በ2007 በሰኔ ወር ላይ ለመጀመሪያ ጊዜ ለሽያጭ ያቀረበው ኩባንያው፣ ከዚያ ጊዜ አንስቶ ባሉት አመታት በድምሩ አንድ ቢሊዮን አይፎኖቹን ለደንበኞቹ ሽጧል፡፡
ኩባንያው የአይፎን ምርቶቹን ጥራትና የቴክኖሎጂ ደረጃ ከጊዜ ወደ ጊዜ በከፍተኛ ሁኔታ እያሻሻለ በአለም የስማርት ስልኮች ገበያ ውስጥ ቀዳሚ ሆኖ መዝለቁን ያስታወሰው ዘገባው፤በ2016 ሶስተኛ ሩብ አመት ብቻ 40.4 ሚሊዮን አይፎኖችን መሸጡን ገልጧል፡፡
አፕል ኩባንያ ባለፈው ረቡዕ 1 ቢሊዮንኛዋን አይፎን ስልክ መሸጡን እንዳስታወቀ የጠቆመው ዘገባው፤ስልኳ የተሸጠችበትን አገርና መደብር በተመለከተ ግን ያለው ነገር የለም ብሏል፡፡