Administrator

Administrator

የዚህ ዓምድ ትኩረት ሥነ-ጥበብ፡ በዋነኝነትም የኢትዮጵያ ሥነ-ጥበብ ነው። በተለይም ዘመንኛው(Contemporary) የኢትዮጵያ
ሥነ-ጥበብላይ አጽንኦት በመስጠት ወቅታዊና በመታየት ላይ ያሉ ትርዒቶችን ይዳስሳል፡ ገለጻ ያቀርባል፡ ያትታል፡ ይመረምራል፡ ሂስ
ያቀርባል። ግለሰቡን ሳይሆን ስራውን በመተቸት የሂስ ባሕልን ለማዳበር ይጥራል፡፡ የዓምደኛውን እይታ መሬት በያዙና ሚዛን በሚደፉ
አመክንዮች በማስደገፍ ግለሰብ አንባቢ ስለ ሥነ-ጥበብና ስለ ኢትዮጵያ ሥነ-ጥበብ ግንዛቤ እንዲጨብጥ፡ የዕይታ ባሕሉ(Visual Culture)
እንዲዳብር፡ የሥነ-ጥበብ አድናቆቱ ከፍ እንዲል፡ ሥነ-ጥበብን የሕይወት ዘዬው(Life Style) አድርጎ እንዲወስደው መንገድ ለመክፈት
ይጥራል። በማኅበረሰብና በሃገር ደረጃም ልክ እንደ ኤኮኖሚያዊ፡ ፖለቲካዊ፡ ማኅበራዊ፡ ባሕላዊና ትውፊታዊ እንዲሁም ታሪካዊ
እንቅስቃሴዎች ሁሉ ሥነ-ጥበብን የሰፊው የሕይወት መር(Mainstream) አካል እንዲሆን ይተጋል።

የሥዕል ትርዒት ዳሰሳ (Exhibition Review)
የትርዒቱ ርዕስ፡
እልፍ ሲናፈቅ
ሠዓሊ፡
ደረጀ ደምሴ
የትርዒቱ አይነት፡
የግል፤ የቀለም ቅብ ስራዎች
ብዛት፡
15 የቀለም ቅብ፤ 7 የብዕር ቀለም
በወረቀት ላይ ስራዎች
የቀረበበት ቦታ፡
ጉራምዓይኔ የሥነ-ጥበብ
ማዕከል(ፒያሳ ራስ መኮንን ድልድይ፡
ወደ አፍንጮ በር በሚወስደው
መንገድ፣ ከሰባ ደረጃ ፊት ለፊት፡
ለመጎብኘት ከማክሰኞ-እሁድ ከጠዋቱ 4:00-
ምሽቱ 12:00 ለአቅጣጫ+251911702953)፡
አዲስ አበባ
የሚታይበት ጊዜ፡
ከግንቦት 18-ሰኔ 27, 2008 ዓ.ም
ዳሰሳ አቅራቢ፡
ሚፍታ ዘለቀ(የሥነ-ጥበብ አጋፋሪ)
እልፍ ሲናፈቅ

ሠዓሊ : ደረጀ ደምሴ፡፡ ርዕስ፡ ጀምበር፡፡ የአክሬሊክ ቀለም በሸራ
ላይ፡፡ መጠን፡ 70 X 90ሳ.ሜ፡፡ 2008 ዓ.ም

የሰው ልጅ ፍጥረቱና ሕይወቱ ብቻውን እንዳልሆነ፤ ብቻውንም እንደማይቀጥል አመላካች አመክንዮዎች፣ ገዥ ስሜቶችና ሃሳቦችን መደርደር ይቻላል፡፡ ሆኖም፡ ዝንጋኤው ሲበረታ ሁሉን እየረሳ ‘ብቻውን’ አንግሶ ለመኖር ይታትራል፡፡ ‘የብቻ’ ንግስናው ባዶ መሆኑን ሲረዳ ደግሞ ‘እኔ’ ማለቱን ገሸሽ አድርጎ፣እኔነትን ለመጋራት ከመሰሎቹ የሰው ልጆች፣ የአካባቢውን፣ የተፈጥሮውን፣ የባሕሉን አውራ (aura) ለመላበስ ይማስናል፡፡ ሚዛኑን ለመጠበቅ ይሟሟታል፡ በዚያውም ይኗኗራል፡፡ እንዲህ እንዲያ እያለ እዚህ ደርሰናል፡፡
ይህ የሠዓሊ ደረጀ ደምሴ ‘እልፍ ሲናፈቅ’ የተሰኘውን የሥዕል ትርዒት፣ መረዳት የሚያስችሉን መሰረታዊ እሳቤዎች እነሆ፡
እልፍ፡ ተቆጥሮ የማያልቅ፣ ጊዜ የማይሽረው፣የማይቆም፣ የሚሻገር፣ የማይሞት፣ የዘልዓለማዊነት ኅላዌ ያለው እሳቤ ሁሉ እልፍ ሊባል ይችላል፡፡ እልፍነት በሰው ልጅም ሆነ በተፈጥሮ ላሉ፤ የሰው ልጅ በፈጠራቸው ቁስ አካላትም ሆነ እሳቤዎች ውስጥም መገኘት ይችላል፡፡ ደረጀ እልፍነትን በተለያዩ መንገዶች በስራዎቹ ሲያስስ የኖረ ሠዓሊ ነው፡፡ የተመስጦውን ትኩረት የሰው ልጅ ከአካባቢው በተለይም ከተፈጥሮ ጋር ያለውን ትስስር እንዲያጤን በመግራት፣ስራዎቹን ሲያበራይ ከአስራ አምስት አመታት በላይ ዘልቋል፡፡ ይህን እሳቤ ማብላላት ሲጀምር ቅርብ ከሆኑ ባሕላዊ፣ ኃይማኖታዊ፣ ተፈጥሮአዊና ሌሎች ሁነቶችን መሰረት አድርጎ ነበር፡፡ ጸበል አንደኛው ነው፡፡
ኃይማኖታዊ መሰረቱ እንዳለ ሁሉ፣ ከተጠናወታቸው እኩይ መንፈስ ለመንጻትም ሆነ ጥሩ መንፈስ ለመላበስ ሰዎች ጸበል ይጠመቃሉ፡፡
 በውሃ የመዳን ሚስጥርን የመረዳት ብሎም የማጥናት ፍላጎቱ የሰው ‘ሰውነት’ ከተፈጥሮ ጋር ያለውን ተዛምዶ በጥልቀት እንዲመረምር ወገግታ ሆነው፡፡ የስራዎቹን መነሻ ወደ ኋላ ተመልሰን ለማየት ከሞከርን ደግሞ የልጅነት እድገቱንና በሥነ-ጥበብ ት/ቤት ቆይታው አማካኝነት የገጠመውን መቃኘት ይኖርብናል፡፡  
የልጅነት ጊዜውን ያሳለፈው ጉለሌ(ፓስተር፡ ሸጎሌና) ቀራኒዮ አካባቢዎች ሲሆን የሁለተኛ አመት ተማሪ ሳለ በውሃ ቀለም መልክዓ-ምድር እንዲስሉ የቤት ስራ ይሰጣቸዋል፡፡ ደረጀ ሸጎሌን ነበር የመረጠው፡፡ ቦታው ሲደርስ ግን የሚያውቃቸው ዛፎች ተቆርጠው፤ ውሃዎች ቆሽሸው፣ ያ የሚያውቀው ቦታ ተቀይሮና ሸጎሌ ‘ጉድ’ ሆና ነበር የጠበቀችው፡፡ ይህ የሆነበት ምክንያቱ ደግሞ ብዛት ያላቸው ሰዎች አካባቢው ላይ በመስፈራቸው ነበር፡፡ ይህ አጋጣሚ ተፈጥሮ፣ የሰው ልጅ አድራጐትና መልክዓ-ምድር ያላቸውን ግንኙነት እንዲፈትሽ እድል ሰጥቶታል፡፡ ይበልጡን ግን የተፈጥሮ ኃያልነት የተገለጸባቸው ቦታዎችን እንዲናፍቅ አድርጐታል፡፡
ጸበል ውሃ፣ መልክዓ-ምድር፤ መልክዓ-ምድርና የሰው ልጅ ማንነት፤ አንደኛው ሌላኛው ላይ ያላቸው በጎም ሆነ አሉታዊ ተጽዕኖ፤ ማንነትን ከኖርንበት አካባቢና ከተፈጥሮ ጋር ማዛመድና ዝምድናውን መፈተሽ፤ኑሮና ሕይወትን ከአካባቢና ከተፈጥሮ ጋር በማያያዝ ማንነትን በመፈለግ ጉዞ ውስጥ ያላቸውን ሚና ማሰስ የደረጀ ጥበባዊ አሻራ ሆነው ዘልቀዋል፡፡ ይህም ሲሆን አንዳች ያልተጨበጠ፡ ነገር ግን ያለና ሕያው የሆነ እሳቤ ላይ ለመድረስ የሚያደርገውን ትግል በስራዎቹ መመልከት እንችላለን፡፡ የመስተጋብሮቹንም ሚስጥራዊነት ያመላክተናል፡፡ ይህንንም የሚከውነው የመስተጋብሩን የእልፍነትና የዘላለማዊነት ክብደት በብርቱ  የሚወክሉ  በተፈጥሮ የሚገኙ ቅርጾችን በመጠቀም ነው፡፡ ከዚህ በተጨማሪም ለምሳሌ ከቅርጹ፡ ከአገነባቡ ጀምሮ ለአርባ አመታት አገልግሎ ተፈጥሮአዊ ሂደቱን ጠብቆ የሚፈርሰው የዶርዜ ባሕላዊ የቤት አሰራርን የሰው ልጅ ራሱ የፈጠራቸውና ከተፈጥሮ ጋር በሚዛንና በስምምነት ለመኖር ለሚያደርገው ጥረት እንደ አንድ ማሳያ አድርጎ በማጥናት የስራዎቹ አካል ያደርጋቸዋል፡፡ ስራዎቹ እልፍ የሆነው የሰው ልጅ ፍላጎት፣አካባቢውንና ተፈጥሮን ለመቆጣጠርም ሆነ ተስማምቶ ለመኖር የሚያደርገውን ሙከራ ያስቃኘናል፡፡ የተፈጥሮና የሰው ልጅ መስተጋብር እልፍነትን ለአመታት ሲያጠናና ሲዳስስ ቢኖርም፣ የሁለቱ ኅላዌ ሌላ እልፍ አእላፍ ተመስጦና አድማስ ይከፍትለት እንጂ መቋጫ አበጅቶለት፣አንድ ሲደመር አንድ ሁለት ይሆናል የሚል አይነት ድምዳሜ አያስቀምጥም፡፡ ምናልባት ሂደቱና ዑደቱ ላይ የደረሰባቸውን መገለጦች እያበረከትልን ይሆናል እንጂ! በዚሁ ግን የተፈጥሮና የሰው ልጅ መስተጋብር ኅላዌ በእልፍ አእላፍ፡ ዘላለማዊ፡ የጊዜ ገደብ በሌለው፡ ጊዜ በማይሽረው ፍስሰት መታጀቡን ያስታውሰናል፡፡የሰው ልጅ ፍጥረትና ሕይወት ብቻውን እንዳልሆነ አበክሮ ያሳስበናል፡፡ ከየትኛውም ቦታ በሚታዩ ተራሮች በታጠረችውና በማያቋርጥ ግንባታ አበሳዋን እየበላች ባለችው አዲስ አበባ መሐል ቢኖርም፣ በልጅነት ያሳለፈባቸው ከከተማው ዳር የሚገኙት አካባቢዎች በዕዝነ ልቦናው መቆየታቸው፣ ተፈጥሮን በቅርበት እንዲያስታውስ ምክንያት እንደሚሆነው ማገናዘብ፣ ስራዎቹ በዚህ እሳቤ እንዲቆዩ አጋዥ አመክንዮ ነው፡፡  
የዚህ ትርዒት ዋነኛ ትኩረት ደግሞ ይህ እልፍ የሆነው የተፈጥሮና የሰው ልጅ መስተጋብር፣ በዘመንኛዊ የኑሮና የሕይወት ጅረት ውስጥ መስተጋብሩ እየሳሳ፡ እየቀጠነ፡ እየላላና እየደበዘዘ የመጣበትን ሂደት የሚያመላክቱ አዲስ መልክ ያላቸው ስራዎቹንና ከጀርባቸው ያሉ ምክንያቶችን መዳሰስ ነው፡፡
ዘመንኛዊው አኗኗራችን ከደረስንበት የስልጣኔ ምጥቀት ተቃራኒ በሆነ መልኩ ከተፈጥሮ ጋር ያለንን ዝምድና ይበልጥ ከማቅረብ ይልቅ እያራቀው፡ እየገፋውና እየሸሸው ይገኛል፡፡ እልፍ የሆነው ቁርኝት፣ እልፍ ወደሆነ ተጓዳኝነት እየተለወጠ ይመስላል፡፡ ለዚህ ምክንያት የሚሆኑ እሳቤዎች በእያንዳንዷ የዘመንኛዊ ኑሮአችን ጠብታ ውስጥ በጉልህ ይስተዋላሉ፡፡ ለዘመንኛዊ ኑሮ ወሳኝ አድርገን ከምንቆጥረውና ከምንደክምለት መሃከል ቁስ ዋንኛው ነው፡፡ በኑሮ ሂደት ውስጥ ያለቁስ መኖር የማይቻል በመሆኑ፣ የቁስ ሃብት መሰረታዊና አስፈላጊ ነው፡፡ ሆኖም ትኩረታችን ወደዚህኛው ሚዛን እየደፋ፣ሌሎች እኩል ወይም በላጭ ዋጋ ላላቸው እሴቶች የምንሰጠው ቦታ እዚህ ግባ የማይባል እየሆነ ከመምጣቱም ባሻገር፣በሚታይና በማይታይ መልኩ ጉዳት እያስከተለብን ይገኛል፡፡ እንገነባለን፡ ነገር ግን ግንባታችን እስከ ምን እንደሆነ አይታሰበንም፡፡ በተለይ በሃገራችን ዓውድ፣ቁስ ለመሰብሰብም ሆነ ለመገንባት ያለን ጥማት ሌሎች ነገሮችን ለማሰብ እድል ሳይሰጠን፣የዕውር ድንብራችንን እየዳከርን እንገኛለን፡፡ በዚህም እልፍ የሆነው የተፈጥሮና የሰው ልጅ ቁርኝት፣ እየላላና እየደከመ ብቻ ሳይሆን አቅጣጫውን እየሳተ፣ ጉዳቱ እየበረታ መምጣቱን ይጠቁማል፡፡
አዳዲሶቹና የቅርብ ጊዜ የደረጀ ስራዎች፣ይህን እውነት እንደ ተረት ተረት አይተርኩልንም፡ እንደ መረጃም አያባንኑንም፡፡ ይልቅስ ከዚህ በፊት እንደሚሰራው ሁሉ በቅርጽ ደረጃ አንድም ነገር ሳያጓድሉ፣የተፈጥሮና የሰው ልጅ ቁርኝትን ከሚወክሉ ሃሳባዊ፣ ስሜታዊ፣ ባሕላዊ፣ ማኅበራዊ፣ ትውፊታዊ፣ ሃገራዊና ተፈጥሮአዊ እሳቤዎች ጋር እያሰናኘ፣ የስራዎቹን የለውጥ መንፈስ እንድናጤንና እንድንመረምር ይጋብዘናል፡፡ እራሳችንን ስራዎቹ ውስጥ እንድንከት መስህብ ያላቸው የድርሰት አወቃቀሮችን፡ ውሳኔውን እንድንረዳ የሚያግዙና የቁርኝቱን እልፍ አእላፍነት አመላካች የሆኑ መስመሮችን እየዘረጋልን፡ ግዘፍ የሚነሱ ተፈጥሮአዊ ቅርጾችን እያተወልን፤እነዚህን ሁሉ የተፈጥሮና የሰው ልጅን መስተጋብር የሚያትቱ ውህዶች በዘመንኛዊ አኗኗራችን እየሳሱ፡ እየሰለሉና እየበነኑ መምጣታቸውን ደግሞ በተቆጠቡ ቀለማቶቹ ይጠቁመናል፡፡ የመስተጋብሩን ሚስጥራዊነት፤ የሚስጥራዊነቱን ጥልቀትና ርቅቀትም ሹክ ይሉናል፡፡
ናፍቆት የሰው ልጅን ስሜት፣ ሃሳብ፣ ነብስ፣ ስጋ፣ መንፈስና ባጠቃላይ ሕልውናውን የሚያዳክምና የሚያዝል ኃይል አለው፡፡
በሌላ ጎኑ፡ ናፍቆት የብርታት፣ የጽናትና ማንነትን የማስታወስ ልዩ ብቃትም አለው፡፡
የወደፊቱንም እንድናስብ፡ እንድንቀምር፡ እንድንናፍቅ ያነሳሳናል፡፡
 ናፍቆት የተቃርኖ ውጤት ነው፤ አንድም ካለንበት እውነታ ባሻገር እንድናይ፡ አንድም ባለንበት እውነታ ብቻ ሳንወሰን፣ አስፈላጊ የሆነውን ግን ደግሞ በተለያዩ ምክንያቶች  ልናገኘው ባለመቻላችን እንድንናፍቅ፣እንድንፈልገው እንድናስበውና እንድንጓጓለት የሚያደርግ፡ ናፍቆታችንን እንድናረካ፣ በሰላ አእምሮ እንድናስብና አስፈላጊውን መስዋዕት እንድንከፍል የሚያጸና ኃይል አለው፡፡
ናፍቆት የሰው ልጅ ፍጥረቱና ሕይወቱ ‘ብቻውን’ እንዳልሆነ ብቻ ሳይሆን የሕይወት ጉዞው ጤነኛ እንዲሆን ሊያካትተው የሚገባቸውን መስተጋብሮች ልብ እንድንል፡ ሚዛናችንን እንድንጠብቅ ያስታውሰናል፡፡ ደረጀ በተለይ በዘመንኛዊ አኗኗራችን ውስጥ እልፍ የሆነውን የተፈጥሮና የሰው ልጅን ዑደት ሲያሰላስል፣ ከአኗኗራችን የጎደለ ነገር እንዳለ፡ መጓደሉ እንደታወቀውና እንደተሰማው ብቻ ሳይሆን፣ ያ እልፍ ዑደት እንደናፈቀው ከአዳዲሶቹ ስራዎቹ መረዳት እንችላለን፡፡
 እልፍ ናፍቆት፡ እልፍ እንድናስብ የሚኮረኩሩ ስራዎች አቅርቦልናል፡፡
 እልፍ ሲናፈቅ ምን እንደሚመስል ማየት፣ መረዳትና ማጤን የኛ ድርሻ ነው፤ልብ ያለው ልብ ይላል!
ቸር እንሰንብት!









Saturday, 25 June 2016 12:36

የኪነት ጥግ

(ስለ ኮሜዲ)
- ህይወት በቅርብ ርቀት ስትታይ ትራጄዲ ናት፤
በረዝም ርቀት ስትታይ ግን ኮሜዲ ናት፡፡
ቻርሊ ቻፕሊን
- የኮሜዲ ዓላማ ሰዎችን እያዝናኑ
ከስህተታቸው ማረም ነው፡፡
ሞልዬር
- ኮሜዲ ለመስራት የሚያስፈልገኝ አንድ
መናፈሻ፣ አንድ ፖሊስና አንድ ቆንጆ ልጃገረድ
ብቻ ነው፡፡
ቻርሊ ቻፕሊን
- ትክክለኛ ኮሜዲ ሰዎች እንዲስቁና
እንዲያስቡ ብቻ አያደርግም እንዲስቁና
እንዲለወጡም ጭምር እንጂ፡፡
ሳም ኪኒሶን
- ኮሌጅ ከመግባት ይልቅ ኮሜዲ መስራትን
መረጥኩኝ፡፡
ቦ በርንሃም
- የኮሜዲ ዓላማ የሰዎችን ጥፋት ማረም
እንደመሆኑ መጠን ማንም ሰው
የሚታለፍበት ምክንያት አይታየኝም፡፡
ሞልዬር
- አስቂኝ መሆን የማንም ሰው የመጀመሪያ
ምርጫ አይመስለኝም፡፡
ውዲ አለን
- ኮሜዲ የሚመነጨው ከውዥንብር ነው፡፡
ቪር ዳስ
• ኮሜዲ ለመስራት፣ በመጀመሪያ ደረጃ ጎበዝ
ተዋናይ መሆን አለብህ፡፡
ሮበርት ዌብ
- መከራ ኮሜዲን ይፈጥራል፡፡
ዳሬን ስታር
- ለኮሜዲ ቁልፉ የራስህን ዝምታ ማድመጥ
ነው፡፡
ኢላይኔ ቡስለር
- ኮሜዲ ለሰው ልጅ ብቸኛው ተስፋው ነው፡፡
ሮዝአኔ ባር
- ኮሜዲ የሚፈጠረው ከግጭት ነው፤ ከጥላቻ፡

ዋረን ሚሼል
- ኮሜዲ በሌሎች ሰዎች ላይ የሚከሰት
ትራጀዲ ነው፡፡
አንጄላ ካርተር

“በአብደላ ህልፈት ያዘንኩት ለሥነጽሁፋችን ነው”



አንጋፋው ደራሲና ጋዜጠኛ አበራ ለማ ከሦስት አሰርት ዓመታት በላይ በዘለቀው የደራሲነት ዘመኑ በርካታ የሥነጽሁፍ ሥራዎችን
ለንባብ አብቅቷል፡፡ ከእነሱም መካከል ”ሽበት”፣ “ሕይወትና ሞት”፣ “መቆያ”፣ “የማለዳ ስንቅ”፣ “አውጫጭኝ” (የግጥም ስብስብ)፣
“ሞያዊ ሙዳየ ቃላት”፣ “ጥሎ ማለፍ”፣ “ታሪካዊ ልቦለድ” እና በቅርቡ ደግሞ “ቅንጣት” የተሰኘው ሥራው ይጠቀሳል፡፡
ደራሲው በዚህ ቃለምልልስ የሚያወጋን ስለ ራሱና ሥራዎቹ አይደለም፡፡ ይልቁንም በቅርቡ በሞት ስላጣነው አንጋፋው ሃያሲ
አብደላ እዝራ ነው፡፡ ትውውቃቸው ከ30 ዓመታት በላይ ይሆናል፡፡ ሥነጽሁፍ ቢያስተዋውቃቸውም ግንኙነታቸውን ወደ ጓደኝነትና
ዝምድና አሳድገውታል፡፡ የአዲስ አድማሱ ደረጀ በላይነህ፤አንጋፋውን ደራሲ አበራ ለማን፣በአብደላ እዝራ ሥነጽሁፋዊ አስተዋጽኦ
ዙሪያ እንደሚከተለው አነጋግሯቸዋል፡፡

ከአብደላ ጋር የመጀመሪያ ትውውቃችሁ በየመን እንደነበር ስትናገር ሰምቻለሁ፡፡ እስቲ እንዴት ነው የተገናኛችሁት?
በሕዳር 1974 ዓ.ም የመን ሰንዓ፣ በዐረብ ደራሲያን ማሕበር ጉባኤ ላይ የኢትዮጵያ ደራሲያን ማህበርን ወክዬ ተገኝቼ ነበር፡፡ ያኔ ነው አብደላ እዝራ በቴሌቪዥን ሰምቶ ሊፈልገን የመጣው፡፡ በአረብ ደራሲያን ጉባኤ ላይ ከ23 ሀገራት የመጡ ተሳታፊዎች እንዳሉና ከኢትዮጵያ ደራሲያን ማሕበርም ተወካዮች መምጣታቸውን ሲሰማ፣ ሌላ መሀመድ የሚባል ጓደኛውን ይዞ ጉባኤው እሚካሄድበት ሸራተን ሆቴል ድረስ መጣ፡፡ እንግዳ መቀበያው ጋ ሄዶም፤“ኢትዮጵያዊ የጉባኤ ተወካይ መጥቷልና እባካችሁ አገናኙኝ” ይላል፡፡ ከዚያ የሆቴሉ ሠራተኞች፣ፍቃደኛነቴን   ጠየቁኝ፡፡
 እኔም፤“ኢትዮጵያዊ ብሎ የሚመጣማ!” ብዬ ያረፍኩበት ክፍል እንዲልኩት ነገርኳቸው፡፡ ሲመጡ ሁለት ወጣቶች ናቸው፡፡ ተዋወቅን፡፡ አማርኛቸውም በጣም የሚገርም ነው፡፡ ከዚያ አብደላ አባቱ የመናዊ እንደነበረና ኢትዮጵያ ውስጥ ሲያርፍ፣ ቤተሰቦቹ ወደ የመን እንደመጡ ነገረኝ፡፡ መሀመድ የሚባለውም እንደሱ ግማሽ ኢትዮጵያዊና ግማሽ የመናዊ ነው፡፡
ይህን ከተነጋገርን በኋላ እንዴት ልትፈልጉኝ መጣችሁ? ብዬ ጠየቅኋቸው፡፡ “እኔ ለሥነ ጽሑፍ ፍቅር ያለኝ ሰው ነኝ፡፡ ስብሀትን ታውቀዋለህ?” አለኝ፤አብደላ፡፡ “ወዳጄ ነው” አልኩት፡፡ ስለ ብርሃኑ ዘሪሁን፣ ስለ በዓሉ ግርማ አነሳ፡፡ ስለ ኢትዮጵያ ስነ ጽሑፍ ብዙ ያውቅ ነበር፤ በጥልቀትም አወራኝ፡፡ በመጨረሻ ፖስታ ሳጥን ቁጥር ተለዋውጠን ተለያየን፡፡
እዚህም ከመጣሁ በኋላ የሚፈልጋቸውን መጽሐፎች በሙሉ በፖስታ ቤት ላኩለት፡፡
የተላኩለትን መጽሐፍት አንብቦ በተለይ “ሕይወትና ሞት” የሚለውን የኔን መጽሐፍ ተንትኖ፣ ለ”አዲስ ዘመን” ጋዜጣ ላከውና ወጣለት፡፡ መጽሐፉ በድህረ አብዮት የመጀመሪያው አጭር ልቦለድ ነበር፡፡ አብደላ አልአራሲ እያለ ነበር የሚፅፈው፡፡ አልአራሲ የቤተሰቡ ስም ነው፡፡ በኋላ ነው አብደላ እዝራ እያለ መጠቀም የጀመረው፡፡
በዚያው መፃፉን ቀጠለ፡፡ ከሰንዓ እያለ ሲፅፍ አንባቢ፤“ማነው?” ማለት ጀመረ፡፡ አማርኛው ረቂቅ ሆነባቸው፡፡
በጣም ታዋቂና ተወዳጅ ሆነ፡፡ እዚህ ሲመጣ ቀጥታ ወስጄ ከእነ ደበበ ሰይፉ፣ ከእነ ጋሽ አማረ ማሞ ጋር አስተዋወቅሁት፡፡ ከብዙ ደራሲያን ጋር ተዋወቀ፡፡ ለ”ዛሬይቱ ኢትዮጵያ” ጋዜጣ፣ ለ”የካቲት” መጽሔት ፅሁፍ መላክ ጀመረ፡፡ በአጭር ጊዜ ውስጥ ወደ ደራሲያንና ሥነ ጽሑፍ አምባ ጠልቆ ገባ፡፡ እሱ ግን እንደ ሌላው የሥነ ጽሑፍ ሰው ዝነኛ ለመሆን ጊዜ አልፈጀበትም፡፡
በላቀ ደረጃ ሰርቷቸዋል ብለህ የምታስታውሳቸውን ስራዎች ልትጠቅስልኝ ትችላለህ?
“ኦሮማይ” በታተመበት ጊዜና “ጥቁር ደም” የሚለውን የአንዳርጌ መስፍን መጽሐፍ እኔ፣ መስፍን ሀብተማርያምና እሱ በኢትዮጵያ ሬዲዮ ላይ ጥልቅ ትንተና ሰጥተንበታል፡፡ እሱን አልረሳውም፡፡ “ጥቁር ደም” ላይ ብቻውንም የሰጠው ትንታኔ ነበር፡፡ ከሀይሉ ልመንህና ከደረጀ ጥላሁን ጋር በጥልቀት ነበር ያወራው፡፡
በአጫጭር ልቦለዶች ጎራ እነ አዳም ረታ የመሳሰሉትን አደባባይ ላይ ለማውጣት ትልቁን ድርሻ የተጫወተው አብደላ እዝራ ነበር፡፡
 ለኢትዮጵያ ሥነ ፅሁፍ ዕድገት ትልቅ ሚና ተጫውቷል፡፡ በእነ ሲሳይ ንጉሱ “ሰመመን”፣ በጋሽ በዓሉና በሌሎች ላይ ብዙ ሰርቷል፡፡ ወደ ግጥሞች ከመጣን፣ እርሱ አሻራውን ያላሳረፈበት አይነ ግቡ የሆነ ግጥም የለም፡፡
ሌላው ትልቁ የአብደላ ስራ ወጣቶችን ማበረታታት ነው፡፡ ብዙ ወጣቶች ያኔ በደራሲያን ማሕበር ዙሪያ ይሰባሰቡ ነበር፡፡
እዚያ የሚመጡትን ወጣቶች ለማወያየትና ለማበረታታት ጊዜውን ይሰጥ ነበር፡፡ እኔ ህዝብ ማመላለሻ በምሰራበት ወቅት ከስራ ውጭ የነበረው ጊዜ ሁሉ የእነርሱ ነበር፡፡ የእረፍት ሰዓት ሳይቀር ለወጣቶች የተሰጠ ነው፡፡ እነ “ፍካት”ን የመሳሰሉትን ማህበራት እየተረዳዳን እናሰለጥን ነበር፤ያልተሞከረ ነገር አልነበረም፡፡
ከአንጋፋዎቹስ ጋር እንዴት----ነበር?-
ከእነ ደበበ ሰይፉ ጋር ውይይት ማድረግ ይወድ ነበር፡፡ አብደላ ደስ የሚለው ዘር አይመርጥም፣ ፆታ አይመርጥም፣ ሃይማኖት አይመርጥም፡፡ ለሁሉም ቅን ሆኖ ስራዎቻቸውን የሚታደግ ሰው ነበር፡፡ ለሁሉም ራሱን ዘግኖ ሲሰጥ የኖረ ሰው ነው፡፡ እንደ ሰብዓዊ ፍጡርም ብዙዎችን ይረዳ ነበር፡፡ ወጣቶችን የሚያግዝ፣ የኢኮኖሚ ችግር የነበረባቸውን እንደ ጋሽ ስብሀት ገብረ እግዚአብሔር ያሉ ሰዎችን የሚታደግ ሰው ነው፡፡ ጥሩ ጥሩ ወዳጆቹን ከነቤተሰቦቻቸው ሲደግፍ ነው የኖረው፡፡  
የእኔን ልጆች ስም ያውጣውም እርሱ ነው፣ የመጀመሪያ ልጄ “መቅድም”፣ ሁለተኛዋ “ምስጢር” ነበር ስማቸው፡፡ ሁለቱንም ቀይሮ ሶስና እና ፌቨን ብሎ አወጣላቸው፡፡ ሁለቱንም ደግሞ ከመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ ነው፡፡ እስከ አሁንም የሚጠሩት እሱ ባወጣላቸው ስም ነው፡፡ እስከ ዛሬ ድረስም ተንከባክቦ ያሳደጋቸው እርሱ ነው፡፡ እንደ አጎት በፍቅር ነው ያሳደጋቸው፡፡
እንዳልከው አብደላ፣በኢትዮጵያ ሥነ ጽሑፍ ውስጥ ጉልህ ስፍራ የነበረው ሰው ነው፡፡ የእሱ አለመኖር ትልቅ ክፍተት አይፈጥርም ?
ተገቢ ጥያቄ ነው፡፡ አብደላ ባህር የሆነ ክፍተት ነው የሚፈጥረው፡፡ ምክንያቱም የእርሱ ሂሳዊ ንባብ አካሄድ ለየት ያለ ነው፡፡ “ቼሆቪያን አይ” (Chekovian eye) ይሉታል ፈረንጆቹ፡፡ ቼሆቭ የአጭር ልቦለድ ደራሲ ነው፡፡
የሚያነሳቸው ጭብጮችና ጉዳዮችም ሌሎች ሰዎች የማያዩትን ነው፡፡ አብደላ የቼሆቭን አይነት ምልከታ፣ ራዕይ ያለው ሰው ነው፡፡
ሕይወትን ነቅሶ ሲያወጣ፣ ከተደበቀችበት ጎልጉሎ አውጥቶ ፀሐይ ላይ ሲያሰጣት አቻ የለውም፡፡ በኢትዮጵያ ሥነ ጽሑፍ አምባ እንደዚህ አይነቱን ሰው ማጣት በጣም ት-ል-ቅ ት-ል-ቅ  ጉዳት ነው፤ያንን ክፍተት እንዴት በዘመናት ውስጥ እንደምንሞላው አላውቅም፡፡
 በተለይ ግጥምና አጫጭር ልቦለድን ደፍሮ የሚያሄስ ሰው የለም፡፡ በጣም ጥቂት ናቸው፡፡ እርሱ ደግሞ ከጥቂቶቹም ላቅ ያለውን ቦታ የያዘ ነበር፡፡
አዲስ አድማስ ላይ “ተናዳፊ ግጥም” በሚል አንዳንድ ዘለላ ግጥሞች እየመረጠ ሲያቀርባቸው የነበሩ ትንተናዎችን ስንመለከት፣አዲስ መንገድ ነው ያሳየን፡፡ በመጨረሻ ያነበብኩት በዶ/ር በድሉ ዋቅጅራ ግጥም ላይ የሰራውን ትንተና ነበር፡፡ እና አንድ አብደላን ብቻ አይደለም ያጣነው፡፡ ብዙ ዓይነቱን አብደላ ነው፡፡ በነገራችን ላይ አብደላ ምስጢር የሆነ ሰው ነው፡፡ ገና ተገልጦ ያላለቀ ቅኔ፡፡ እርሱ ስለ ሌሎች ሲጨነቅ ውጫዊ ማንነቱን እንጂ ውስጡን አናውቅም፡፡ ውስጡን ጠልቀህ ማወቅ አትችልም፡፡ አብደላ ረቂቅ ሰው ነው፡፡ በአንድ በኩል የፊዚክስ፣ በሌላ በኩል የሂሳብ፣ ጥሩ የቴክኖሎጂ እንዲሁም የባዮሎጂ ዕውቀት ያለው ሰው ነበር፡፡ ስለ ሃይማኖት ብታወራው፣ጥልቅ ትንታኔ ሊሰጥ የሚችል ሰፊ ገበታ ነው፡፡ ግን ባልጠበቅነው ሰዓት ሞት ድንገት ከእጃችን ነጠቀን፡፡ ያዘንኩት ገና ማደግ ላለበት ሥነ ጽሑፋችን ነው፡፡ ብዙ ትሁት ሃያሲያን በሌሏት፣ አንዱን ገድሎ፣አንዱን አድኖ ማኄስ በተለመደባት ሀገር ላይ፣እንደ አብደላ ዓይነት ከቡድን አስተሳሰብ ነፃ የሆነ ሰው ማግኘት ቀላል አይደለም፡፡ እንዲህ ያለ ሚዛናዊ ሰው ማጣት በእጅጉ ይጐዳል፡፡
ይሄን ታላቅ የጥበብ ሃያሲ ለማሰብና ለመዘከር ምን መደረግ አለበት ትላለህ?
አሁን ይህን ሰው አንመልሰውም፡፡ ይልቅ የእርሱን ብሄራዊ ተዋፅኦ፣ የእርሱን የሀገር ፍቅርና የሥነ ጽሑፍ ፍቅር ለማስታወስ፣ ለእርሱ መታሰቢያ የሚሆኑ ነገሮች መስራት ይኖርብናል፡፡ ከነዚህም አንዱ ስራዎቹን ሰብስቦ ማሳተም ነው፡፡ በደበበ ሰይፉ ስራዎች ላይ ጥናታዊ ዳሰሳ እየሰራ እንደነበር ነግሮኛል፡፡ እሱን አጠቃልሎት ከሆነ ማየት፣ካላለቀ ደግሞ የሚቋጭበትን መንገድ ---- ኮሚቴም ቢሆን አቋቁሞ ማሰብ ያስፈልጋል፡፡
አንዲት ሴት ልጅ ናት ያለችው፡፡ ገና ጨቅላ ስለሆነች ምን እናግዝሽ? እያልን በእሷ አስተባባሪነት የምንሰራውን ነገር ማሰብ ያስፈልጋል፡፡
ለእርሷና ለቤተሰቧ ድጋፍ በመሆን፣ አብደላን ከመቃብር በላይ ለማዋል መሞከር ይኖርብናል፡፡ በየመን መኖሪያ ቤቱ ውስጥ ብዙ የመፃህፍት ስብስቦች አሉት፡፡ መጻህፍቱ መጥተው ለእርሱ መታሰቢያ የሚሆን ነገር የሚበጅበትን ሁኔታ መፍጠርና በስሙ መሰየም ትልቅ ፋይዳ ይኖረዋል፡፡
 ይህን ዓይነቱን ስራ  እኔና አንተን ጨምሮ ሌሎችም በመሆን ከዳር ማድረስ ይጠበቅብናል ብዬ አምናለሁ፡፡  ከዚህ በተጨማሪ ብዙ ወርክሾፖችና ሲምፖዚየሞች በስሙ መዘጋጀት ይኖርባቸዋል፡፡
ለእንዲህ ያለ ጉዳይ የኢትዮጵያ ደራሲያን በሙሉ ቅኖች ናቸው፡፡ ለብዙ ሰዎች ሲያደርጉት ስለነበር ለአብደላም የማያደርጉት ነገር ይኖራል ብዬ አላስብም፡፡ ይህን ሰው ማሰብ ማለት፣ የራሳችንን ቅርስ ለቀጣዩ ትውልድ ማስተላለፍ ስለሆነ፣ የሁላችንም ሃላፊነት ነው ብዬ አምናለሁ፡፡




የምግብ ፌስቲቫሉ አለማቀፍ ተቃውሞ ገጥሞታል

   በደቡባዊ ቻይና ከ10 ሺህ በላይ ውሾች ለምግብነት የሚቀርቡበት አመታዊው የዩሊን የምግብ ፌስቲቫል ከእንስሳት መብት ተከራካሪዎች አለማቀፍ ተቃውሞ ቢገጥመውም ባለፈው ማክሰኞ በይፋ ተጀምሯል፡፡
11 ሚሊዮን የሚደርሱ የእንስሳት መብት ተከራካሪዎችና እንስሳት ወዳጆች የምግብ ፌስቲቫሉ በእንስሳት ላይ የሚደረግ የግፍ ጭፍጨፋ ነው በሚል፣ ፌስቲቫሉ እንዳይካሄድ የተቃውሞ ፊርማቸውን አሰባስበው ባለፈው ሳምንት ለቻይና መንግስት ቢያቀርቡም አቤቱታቸው ሰሚ ማጣቱንና ፌስቲቫሉ በይፋ መጀመሩን ቢቢሲ አመልክቷል፡፡
ለአስር ቀናት በሚቆየው በዚህ የምግብ ፌስቲቫል ላይ ከ10 ሺህ በላይ ውሾችና በሺህዎች የሚቆጠሩ ድመቶች በጅምላ እየተገደሉ ለምግብነት እንደሚውሉ የጠቆመው ዘገባው፣ምንም እንኳን ቻይናውያን ውሻን መመገብ ከጀመሩ 500 አመታት ያህል ቢያስቆጥሩም፣ በዚህ መጠን በአንድ ሳምንት እንስሳቱን መጨፍጨፍ አግባብ አይደለም የሚል ተቃውሞ በስፋት ተስተጋብቷል፡፡ በሳምንቱ መጨረሻ እንስሳትን በጭካኔ መጨፍጨፍ አግባብ አይደለም በሚል በርካታ የፌስቲቫሉ ተቃዋሚዎች በእንግሊዝ በሚገኘው የቻይና ኢምባሲ ደጃፍ የተቃውሞ ሰልፍ ቢያደርጉም፣ኤምባሲው ተቃውሞውን እንዳልተቀበለ ተዘግቧል፡፡
ሂውማን ሶሳይቲ ኢንተርናሽናል የተባለው የመብት ተሟጋች ተቋምና የእንስሳት ወዳጆች የሆኑ በርካታ ግለሰቦች በፌስቡክ በከፈቱት ዘመቻ፣ በፌስቲቫሉ ለእርድ ሊቀርቡ የነበሩ 1 ሺህ ያህል ውሾችን ገዝተው ወደ ቤታቸው በማስገባት ከሞት ማዳናቸውን ዘ ኢንዲፔንደንት ዘግቧል፡፡


በሰከንድ 93 ትሪሊዮን ስሌቶችን መስራት ይችላል

    ቻይና በፍጥነቱ አቻ የማይገኝለትን የአለማችን እጅግ ፈጣን ሱፐር ኮምፒውተር መስራቷንና በአለም አገራት የበርካታ ፈጣን ኮምፒውተሮች ባለቤትነት ደረጃ ቀዳሚውን ስፍራ መያዟን አሶሼትድ ፕሬስ ዘገበ፡፡
ባለፈው ሰኞ በጀርመን በተካሄደው አለማቀፍ የሱፐር ኮምፒውተሮች ጉባኤ ላይ ይፋ የተደረገውና ታይሁላይት የሚል ስያሜ የተሰጠው አዲሱ እጅግ ፈጣን ቻይና ሰራሽ ኮምፒውተር፣ በሰከንድ 93 ትሪሊዮን ያህል ውስብስብ ስሌቶችን የመስራት አቅም እንዳለው ዘገባው ገልጧል፡፡
ናሽናል ሪሰርች ሴንተር ኦፍ ፓራለል ኮምፒውተር ኢንጂነሪንግ ኤንድ ቴክኖሎጂ የተባለው የአገሪቱ የምርምር ተቋም የፈጠራ ውጤት የሆነው ኮምፒውተሩ፣ ሙሉ ለሙሉ የተሰራው በቻይና ቁሳቁሶችና የኮምፒውተር ቴክኖሎጂዎች ሲሆን በተለያዩ የምህንድስና፣የአየር ንብረትና በሌሎች የሳይንስና የመረጃ ጥናት የምርምር ፕሮጀክቶች ውስጥ ጥቅም ላይ እንደሚውል ተገልጧል፡፡  
    ባለፈው ሰኞ በተካሄደው አለማቀፍ የሱፐር ኮምፒውተሮች ጉባኤ ላይ እንደተገለጸው፣ በየመንፈቅ አመቱ ይፋ በሚደረገው የበርካታ ሱፐር ኮምፒውተሮች ባለቤት አገራት ዝርዝር ውስጥ ቻይና ቀዳሚነቱን ከአሜሪካ ተረክባለች፡፡
 የ167 ሱፐር ኮምፒውተሮች ባለቤት የሆነቺው ቻይና፤ በአለማቀፍ የበርካታ ሱፐር ኮምፒውተሮች ባለቤትነት ደረጃ ቀዳሚውን ስፍራ ስትይዝ፣ አሜሪካ በ165 ሱፐር ኮምፒውተሮች ሁለተኛ ደረጃን፣ ጃፓን ደግሞ በ28 ሱፐር ኮምፒውተሮች ሶስተኛ ደረጃን መያዛቸው ተነግሯል፡፡

• የበሽታው ተጠቂ በ24 ሰዓት ህክምና ካላገኘ ለሞት ሊዳረግ ይችላል



ፌስቡክ በአሜሪካ
አንዲት አሜሪካዊት እንዲህ ብላ ፖስት አደረገች፡- “ሀይ ጋይስ! rly ዛሬ በጣም ጨንቆኛል፡፡
ከሳምንት በፊት አንዲት ጓደኛዬ ፍቅረኛዋን አስተዋውቃኝ ነበር፡፡ ግን ድንገት ሳላውቅ ከልጁ ጋር
ፍቅር ያዘኝ፡፡ እንዳልነግረው ደሞ የጓደኛዬ ፍቅረኛ ስለሆነ ፈራሁ፡፡ በጣም ጨንቆኛል፤ ሀሳባችሁን
አካፍሉኝ”
አሜሪካውያን ኮሜንት መስጠት ይጀምራሉ፡-
Johnson= አይዞሽ ቆንጆ፤እንደዚህ አይነት ነገር ያጋጥማል፤more ደሞ ከቤተሰቦችሽ ጋር
ብትንጋገሪበት ጥሩ ይመስለኛል፡፡
Anita Brown= oh! እኔም እንደዚህ አይነት ነገር አጋጥሞኝ ያውቃል፡፡ ነገር ግን ከልጁ ጋር
በመነጋገር ችግሩን ለመፍታት ችያለሁ፡፡ አንቺም ለልጁ ብትነግሪው ሊቀልሽ ይችላል፡፡
Michael= በውይይት የማይፈታ ነገር የለም፡፡ so ሶስታችሁም ቁጭ ብላችሁ ብትወያዪ ጥሩ
ይመስለኛል፡፡ ጭንቀት ግን ለጤናሽ ጥሩ አይደለም፡፡
Devid Jackson= ብዙም አትጨነቂ፤ይሄ እኮ ምንም ማለት አይደለም፡፡ ለሰው መናገር ከፈራሽ
ደሞ የተለያዪ የሳይኮሎጂ መፅሀፎችን በማንበብ እራስሽን ለማረጋጋት ሞክሪ፡፡

ፌስቡክ በኢትዮጰያ

አንዲት ኢትዮጵያዊት ደግሞ በተመሳሳይ የሚከተለውን ፖስት አደረገች፡-
“ሀይ፤ ስሜ ቅድስት ይባላል፡፡ የምኖረው እዚሁ አዲስ አበባ ነው፡፡ ባልጠበኩት መንገድ ከጓደኛዬ
ፍቅረኛ ጋር ፍቅር ያዘኝ፡፡ ምን ማድረግ እንዳለብኝ ግራ ገብቶኛል፡፡
በናታችሁ ሀሳባችሁን አካፍሉኝ፡፡”
ኢትዮጵያውያን ኮሜንት መስጠት ጀመሩ፡-
Alemayew Kasahun= ወይ ስምንተኛው ሺ! ደሞ አፍ አለኝ ብለሽ ታወሪያለሽ እንዴ? ወራዳ!
Selam Habeshawit= ኧረ ስንት አይነት ሰው አለ ግን በጌታ! በናትሽ እንደዚህ አይነት ወሬ
እያወራሽ እኛ ሴቶችን አታሰድቢ፡፡
Biniyam Ye Ortodox Lij= እግዚኦ ማህርና ክርስቶስ!! ምን አይነት ዘመን ላይ ነው ግን ያለነው፡፡
እሱ ይቅር ይበልሽ፡፡
Yonas Fikru= እውነት ግን አንቺ ኢትዮጵያዊት ነሽ?
Teddy Man= ታዲያ እኛ ምናገባን? የቤትሽን አመል እዛው! እኛ እንደዚህ አይነት ነገር
አይመቸንም፡፡
Jemal Seid= ያ አላህ!! እንደዚህ በቁሜ ከምዋረድ ብሞት ይሻለኛል፡፡
Betelhem kiros= ደሞ ስምሽን ማነው ቅድስት ብሎ ያወጣልሽ?? እርጉም ቢሉሽ ይሻል ነበር፡፡
በእውነት አፈርኩብሽ፡፡ አምላኬ ሆይ የሚያደርጉትን አያውቁምና ይቅር በላቸው፡፡
Daniel Love= ወይ ሴቶች በቃ መጨረሻችሁ እንደዚህ ሆነ ማለት ነው? ሴት በዛ ጎመን ጠነዛ አሉ!
ምንጭ፦ Kalid Alfarsi Ahmed
(ከማፉዝ መሃመድ ፌስቡክ)



=========================================
በመጀመሪያ እና በመጨረሻ

በመጀመሪያ – አግቡ እንጂ። ልጅም በልጅነት
ሲሆን ነው የሚያምረው።
ከዚያ – ውለዱ እንጂ። ቤት ያለ ልጅ አይሞቅም።
ከዚያ – ሲወለድ ድገሙ እንጂ። አብረው ያድጋሉ።
ከዚያ – አንድ ሲወለድ፣ ለሴቷ እህት
ያስፈልጋታል።
ከዚያ – ወንድ ከተወለደ፣ ግድ የለም ድገሙ ፈጣሪ
ያውቃል።
ከዚያ – አሁንም ወንድ ከሆነ፣አንድ ሞክሩና ካልሆነ
ይቀራል።
ከዚያ – አምስት ሲሆኑ ግን በዚህ የኑሮ ውድነት
አምስት ልጅ አልበዛም? (በሹክሹክታ) እንግዲህ
ገቢያቸውን የሚያውቁት እነሱ ናቸው።
በመጨረሻም – ሳይቸግራቸው ቀፍቅፈው
ቀፍቅፈው ይኸው ማጣፊያው አጠራቸው። ለስሙ
ተምረው የለም? እንግዲህ ከመምከር አልፈን አልጋ
ልንለያቸው አንችልም። እኛ የማንወልደው ልጅ
ጠልተን ነው? ፈጥሮ በሰው ነፍስ መጫወት!
(ከቴዎድሮስ ተ/አረጋይ ፌስቡክ)

“ድር ቢያብር አንበሳ ያስር!” የሚለው ምሳሌያዊ አነጋገር በአገራችን ሥር የሰደደ አብሮ የመሥራት ባህል እንዳለ ጥሩ ማሳያ ነው፡፡ በርግጥም ኢትዮጵያውያን እንደ አብሮ መብላት ሁሉ አብሮ በመሥራትና በመተጋገዝ ክፉ ቀንን የማለፍ  ልማድ እንዳላቸው አይነተኛ ማሳያ ነው፡፡ አብሮ ለመስራትና ለመተጋገዝ አስኳል ከሆኑት ማህበራዊ እሴቶቻችን መካከል እድርና መሰል ቀደምት ማህበራዊ ተቋማት ይገኙበታል፡፡
የማህበራዊ ሳይንስ ምሁራን እንደሚሉት፤ የሰው ልጆች ማህበራዊ፣ ኢኮኖሚያዊና ፖለቲካዊ ፍላጎት የተመሳሰለና የተሳሰረ  እንደመሆኑ መጠን፣ በተናጠል መኖር የማይቻል ነገር ነው፡፡  በአገራችን ያሉ ዕድሮችም የዚሁ እውነት ነፀብራቆች ናቸው፡፡ ስለ ዕድሮች ታሪካዊ አመጣጥ እስካሁን በተመራማሪዎች ዘንድ ስምምነት ላይ ባይደረስም፣ ዕድሮች በአገሪቷ የቆዳ ስፋት ልክ የተሰራጩና ዛሬ ላይ ምናልባትም በጣም ሩቅ የሆኑ አካባቢዎች ካልሆኑ በቀር ዕድር የሌለበትን መንደር ማሰብ አዳጋች ነው፡፡ የአዲስ አበባ ከተማ የዕድሮች ምክር ቤት መረጃ እንደሚያሳየው፤ በከተማዋ ብቻ ሕጋዊ ዕውቅና ያላቸው 7,5ዐዐ ዕድሮች ይገኛሉ፡፡  
እነኚህ ማህበረሰቡ ይሁነኝ ብሎ የሚያቋቁማቸው የማህበረሰብ ምሥርት ተቋማት ዓይነታቸው ቢለያይም (ለምሣሌ የአንድ አካባቢ ነዋሪዎች፣ የሥራ ባልደረቦች፣ ወዘተ) ተብለው ቢሰየሙም በቀደመው ጊዜ የሁሉም ዓላማ ተመሳሳይ ነበር፡፡ ይኸውም “ከሩቅ ዘመድ የቅርብ ጎረቤት” እንዲሉ፣ አባላት በራሳቸው ወይም በቤተሰባቸው ላይ እክል ሲገጥማቸው ፈጥኖ በመድረስ፣ የገንዘብ ድጎማ በማድረግ፣ በጉልበት በማገዝና በማፅናናት ሀዘንተኞቹ የገንዘብ ችግር ሳይገጥማቸው ሀዘናቸውን ረስተው፣ ወደ ቀድሞ ህይወታቸው እንዲመለሱ ማበረታታት ነው፡፡ አንድ ግለሰብ ወይም ቤተሰብ በሚኖርበት ወይም በሥራ ቦታ አካባቢ ከሚገኙ እድሮች አባል ካልሆነ በአባልነት እንዲታቀፍ ይበረታታል፡፡ ስለዚህም ቢያንስ የአንድ ዕድር አባል መሆን የውዴታ ግዴታ ነው፡፡ መቼስ የዕድሮችንና የዕድርተኞችን ምንነት ለዚህ ፅሁፍ አንባቢ መንገር ለቀባሪው ማርዳት ስለሚሆን በዚሁ ይበቃናል፡፡ እናስ እጅ ከምን?
በአሁኑ ወቅት በርካታ እድሮች ከዘመኑ ጋር ዘምነው፣ ዓላማቸውንና ተደራሽነታቸውን አሳድገውና አስፋፍተው፣ ህብረታቸውን አጠናክረው በተለያዩ የልማት ተግባራት ውስጥ በመሳተፍ፣ በአባላቶቻቸው ብቻ ሳይገደቡ ሌሎች የህብረተሰብ ክፍሎችንም ተደራሽ በማድረግ፣ ጉልህ የሆነ ማህበረ-ኢኮኖሚያዊ ሚና ሲጫወቱ ይስተዋላሉ፡፡ ለእድሮቹ የቀደመ አቋም መለወጥ ከሚጠቀሱት ምክንያቶች አንዱ ኤችአይቪ/ኤድስ ለመከላከልና ተያያዠ ጉዳቶችን ለመቀነስ የሚደረገው ጥረት እንደነበር ጥናቶች ያሳያሉ፡፡ በአገራችን ኤችአይቪ/ኤድስ ተስፋፍቶ በርካታ ህይወት ይቀጥፍና የአልጋ ቁራኛ ያደርግ በነበረበት በዚያ አስከፊ ወቅት የችግሩ ሰለባ የሆኑትን ግለሰቦችና ቤተሰቦች የአካባቢያቸው ዕድሮች በሞት ብቻ ሳይሆን በህይወት ሊደርሱላቸው ቆርጠው ተነሱ፡፡ በዚያ አጋጣሚ ገርበብ ብሎ የተከፈተው የዕድሮች በር፤ ዛሬ በሰፊው ተከፍቶ ለበርካታ የልማት ሥራዎች እልፍኝ ሆነኗል፡፡
ይህ ክስተት መንግሥትን ጨምሮ የበርካታ ተቋማትን ዐይን በመሳቡ አለንላችሁ ባይም በዚያው ልክ ጨምሯል፡፡ የእድሮች ዋነኛ የልማት መሣሪያ የመሆን አቅማቸውም በመንግሥትም ሆነ መንግሥታዊ ባልሆኑ ድርጅቶች ከመቼውም ጊዜ በተሻለ ትኩረት የተሰጠው መሆኑን እንደ ሳንድራ ጆሀንሰን (2ዐ1ዐ) ያሉ ጥናቶች ይገልጻሉ፡፡ በዚህ መሰረት፤ አያሌ ቁጥር ያላቸው መንግስታዊና መንግስታዊ ያልሆኑ ድርጅቶች እድሮችንና መሰል ማህበራትን ለልማት አንቀሳቅሰዋል፡፡
ለአብነትም ኢየሩሳሌም የህፃናትና ማህበረሰብ ልማት ድርጅት (ኢ/ህ/ማ/ል/ድ) በተለይም ከ1990ዎቹ ጀምሮ ከማንም በላይ ማህበረሰባቸውን ጠንቅቀው የሚያውቁትን ዕድሮችና ማህበራትን ወይም የማህበረሰብ ምሥርት ተቋማትን ሁነኛ አጋሮቹ በማድረግ በርካታ የማህበረሰብ ልማት ስራዎችን በመስራት ላይ ይገኛል፡፡
በተለይ ከ1996 ዓ.ም ወዲህ ኢ/ህ/ማ/ል/ድ ከተለያዩ ድጋፍ ሰጪ ተቋማት ጋር በመተባበር የበርካታ ማህበረሰብ ምሥርት ተቋማትን (ዕድሮች፣ የዕድሮች ህብረት፣ አፎሻ፣ የሴቶች ማህበራት፣ የአካባቢ ተወላጆች ማህበራት፣ ወዘተ) ተቋማዊና ኢኮኖሚያዊ አቅም በማጠናከር ሥራ ላይ ተጠምዷል፡፡ በምላሹም ተቋማቱ የማህበረሰባቸውን ችግር በመፍታት በተለይም ህፃናትን ጨምሮ ለችግር የተጋለጡትን የህብረተሰብ ክፍሎች በመደገፍ ኑሮዋቸውን የማሻሻልና ብቁ ዜጋ የማድረግ ሥራ ላይ ተሰማርተዋል፡፡  
እስከዛሬም ድረስ ኢ/ህ/ማ/ል/ድ በ22 የተለያዩ የሀገሪቱ ከተሞች ውስጥ የሚገኙ ወደ 885,ዐዐዐ የሚጠጉ የሕብረተሰብ ክፍሎችን ከሚወክሉ ከ142 የማህበረሰብ ምሥርት ተቋማት ጋር በመተባበር በመስራት ላይ ይገኛል፡፡ በአማራ፣ በኦሮሚያ፣ በደቡብ ብሔር ብሔረሰቦችና ሕዝቦች፣ እንዲሁም በአዲስ አበባና በድሬዳዋ ከተማ አስተዳደር የሚገኙት እነኚህ የማህበረሰብ ምሥርት ተቋማት፣ በኢ/ሕ/ማ/ል/ድ የተለያዩ ፕሮጀክቶች አማካኝነት በየጊዜው ጠቃሚ የሆነ የገንዘብና የቴክኒክ እገዛ ያገኛሉ፡፡ ቴክኒካዊ እገዛው ሥልጠና፣ የልምድ ልውውጥና ክትትልን የመሳሰሉ የአቅም ልማት ሥራዎችን ያካተተ ነው፡፡
በአጠቃላይ የኢህማልድ ፕሮጀክቶች ተቋማቱ የአሠራር ሥርዓታቸውን ከማዘመን ጎን ለጎን በራሳቸው ፕሮጀክት ቀርፀው በተለያዩ የገቢ ማስገኛ ሥራዎች ላይ እንዲሠማሩ በማስቻል ትልቅ ጠቀሜታ ሰጥተዋል፡፡ ይህም ድጋፍ ተቋማቱ ከፍተኛ ችግር ያለባቸውን የህብረተሰብ ክፍሎች ህይወት ዘላቂነት ባለው መልኩ ለማሻሻል የሚያስችል አቅም እንዲገነቡ ለማገዝ፣ በተለይም የመኖሪያ አካባቢዎችን ለህፃናት ሁለንተናዊ ዕድገት ምቹ ለማድረግ እንዲተጉ ለማበረታታት የታለመ ነው፡፡ በምላሹም  እያንዳንዱ የማህበረሰብ ምሥርት ተቋም እንደየአካባቢው ተጨባጭ ሁኔታ መፍትሄ በማስቀመጥ በስፋት እየተንቀሳቀሰ ነው፡፡ ከተመዘገቡት ውጤቶች መካከልም የሚከተሉት ይገኙበታል፡-
በርካታ ወላጆቻቸውን ያጡና ለችግር የተጋለጡ ሕጻናት ትምህርታቸውን ያለ ችግር መከታተል ችለዋል፤ ማህበራዊና ስነ-ልቦናዊ መረጋጋትም አግኝተዋል፡፡
በርካታ ወጣቶች እራሳቸውንና ቤተሰባቸውን ማስተዳደር ችለዋል፡፡ ከዚያም ባለፈ በአካባቢው ላሉ ሌሎች ወጣቶች አርአያ በመሆን ተነሳሽነትን ፈጥረዋል፡፡
የገቢ ማስገኛ ሥራ ውስጥ የገቡ ብዛት ያላቸው የህጻናቱ አሳዳጊዎች በራሳቸው ገቢ ማግኘት ጀምረዋል፤ ልጆቻቸውንም ያለችግር ለመመገብና ለማስተማር በቅተዋል፡፡
የሴቶችን የልማት ተሳትፎ ከፍ ለማድረግ ትኩረት ተሰጥቶ እየተሠራ ነው
ጧሪ ቀባሪ የሌላቸው አረጋውያን፤ ወርሀዊ የገንዘብ ድጎማና እንደአስፈላጊነቱም የመኖሪያ ቤት ጥገና ተደርጎላቸዋል፡፡
ለበርካታ የህብረተሰብ ክፍሎች በጤና፣ በግልና በአካባቢ ጥበቃ፣ በልጆች አስተዳደግ ወዘተ የግንዛቤ ማስጨበጫ ሥራ ተሠርቷል፡፡ ሌላም ሌላም ሌላም፡፡
ለዋቢነት ይሆን ዘንድ በሀዋሳ ከተማ ከሚገኙ አጋር ማህበራት እንዱን እንዘክር፤ በሀዋሳ ከተማ ዳካ ቀበሌ የሚገኘው የሴራሚክስ አካባቢ ነዋሪዎች መረዳጃ ዕድር ልማት ማህበር በ1988 ዓ.ም
እንደተለመደው ሁሉ አባላት ዕክል ሲደርስባቸው ለማቀባበር፣ ለማስተዛዘንና መጠነኛ የገንዘብ ድጎማ ለማድረግ ተቋቋመ፡፡ ይህ ዕድር ከኢ/ህ/ማ/ል/ድ ጋር አጋርነት በመፍጠር ወደልማት ከገባ ከሁለት ዓመታት በላይ አስቆጠሯል፡፡ በኢ/ህ/ማ/ል/ድ ለዕድሩ አመራሮች የተለያዩ ሥልጠናዎች በመስጠትና በተለያዩ አካባቢዎች ከሚገኙ ዕድሮች ጋር የልምድ ልውውጥ እንዲያደርጉ በማመቻቸትና እንዲሁም ተገቢው የአሰራር ለውጥ ማሻሻያ እገዛ በማድረግ  አሠራራቸውን እንዲያሻሽሉ ተደርጓል፡፡
“የኢሕማልድ ፕሮጀክት ማህበረሰባችንን አስተዋወቀን፡፡ ከችግሩ ጋር አብረን እየኖርን ችግሩን አናውቀውም ነበር፡፡” የሚሉት ከሴራሚክ እድር አመራር አባላት አንዱ የሆኑት አቶ ተስፋማርያም ደሳለኝ፤ “ይገርማችኋል በቀን አንዴ እንኳ መብላት የማይችሉ እዚሁ እስራችን ነበሩ፤ በተደረገላቸው ድጋፍም ከፍተኛ መሻሻል አሳይተዋል፡፡ ዛሬ በፕሮጀክቱ የታቀፉት የህብረተሰብ ክፍሎች በህይወታቸው ላይ ጉልህ የሆነ መሻሻል እያሳዩ ነው፡፡ የእነሱን ለውጥ በማየትም ሌሎች የአካባቢያችን ነዋሪዎች ተስፋቸው እያንሰራራ ነው”  በማለት በተደምሞ ስሜት ገልጸዋል፡፡
እንደ አቶ ተስፋማርያም ገለፃ ከሆነ፤ ከኢ/ሕ/ማ/ል/ድ በተገኘው የገንዘብ ድጋፍ ወላጆቻቸውን ላጡና ለችግር ለተጋለጡ ህፃናት የትምህርት መርጃ ቁሳቁስ፣ የትምህርት ቤት የደንብ ልብስ፣ የዘወትር አልባሳት፣ የስፖርት አልባሳት በመስጠት እንዲሁም ለአሳዳጊዎቻቸው መሠረታዊ የንግድ ሥራ ክህሎት ሥልጠና እና ለንግድ ሥራ መነሻ የሚሆን መጠነኛ የገንዘብ ድጎማ በማድረግ፣ ህፃናቱ ያለ ችግር ትምህርታቸውን እንዲከታተሉ አስችለዋል፡፡ በተጨማሪም ዕድሩ በተለያዩ የህፃናት አስተዳደግ፣ በጤና፣ በቆሻሻ አወጋገድ፣ ለችግር የተጋለጡ ህፃናትና አረጋውያን እንክብካቤ እንዲሁም የማህበረሰብ ግልጋሎትና መልካም ሥነ-ምግባር በመሳሰሉ ርዕሶች ላይ ከ5ዐዐ በላይ የሚሆኑ ሰዎችን አስተምሯል፤ ግንዛቤያቸውንም አዳብሯል፡፡  ማህበረሰባቸውን ከችግር ለማውጣት ቆርጠው የተነሱት የዕድሩ አመራሮች፤ አባላቶቻቸውን በማሳመንና በማነሳሳት ከመደበኛ ወርሃዊ መዋጮ በተጨማሪ ወላጆቻቸውን ላጡና ለችግር ለተጋለጡ ህፃናት እንዲሁም ጧሪ ቀባሪ ላጡ አረጋውያን መደገፊያ የሚሆን መዋጮ ጀምረዋል፡፡ እሰየው የሚያሰኝ ትልቅ እመርታ፤
“አሁን ትምህርቴን ለመቀጠል ድጋፍ አግኝቻለሁ፡፡ ዋናው ትኩረቴም እሱ ነው፡፡ የትርፍ ጊዜ የጥናት ፕሮግራም እየተከታተልኩ ውጤቴን አሻሽላለሁ፡፡ ወደፊት ሀኪም ሆኜ ኤችአይቪ/ኤድስ እና ሌሎች ህመሞችን ለመዋጋት እመኛለሁ፡፡” የምትለን ደግሞ የ1ዐ ዓመቷ ታዳጊ፤ ፀደይ አበራ (ለዚህ ፅሁፍ ሲባል ስሟ መቀየሩን ልብ ይሏል) ናት፡፡ ወላጆቿን በኤችአይቪ/ኤይድስ ምክንያት ያጣችው ይህች የባህር ዳር ከተማ ታዳጊ የቀን ጨለማ ውስጥ በነበረችበት ሰዓት “ጎህ ለሁሉም” የተሰኘው በአካባቢዋ የሚገኝ የማህበረሰብ ልማት ማህበር እንደደረሰላት ታወሳለች፡፡ የትምህርት መርጃ መሣሪያዎች፣ አልባሳት፣ የማጠናከሪያ ትምህርት፣ የንፅህና  ቁሳቁሶችና የህይወት ክህሎት ሥልጠናዎች ማህበሩ ከኢ/ሕ/ማ/ል/ድ ባገኘው ድጋፍ አማካኝነት ለፀደይ ካበረከታቸው ድጋፎች ውስጥ ይጠቀሳሉ፡፡ ፀደይም በአንደበቷ እንዳስረገጠችው፤ ተስፋዋ ለምልሞ በትምህርቷም መሻሻልን እያሳየች ነው፡፡
የአምስት ልጆች እናት የሆኑት የ4ዐ ዓመቷ ወይዘሮ መሪማ መሀመድ፤ በቡታጅራ ከተማ የቀበሌ ዐ5 ነዋሪ ናቸው፡፡ ከዚህ ቀደም ወይዘሮ መሪማ እንጀራ ጋግሮ በመሸጥ ልጆቻቸውን ያሳድጉ ነበር፡፡ በወቅቱ የነበረባቸውን ችግር ሲናገሩ፤ ለጤፍ መግዣ የሚሆን ገንዘብ ስለማይኖራቸው ሁልጊዜ በብድር ነበር የሚሠሩት፡፡ “ከሀብታም ገንዘብ ለመበደር እኮ ወይ ቤት ሊኖር ይገባል ወይ ተያዥ የሚሆን ሌላ ሀብታም ማወቅ ያስፈልጋል፡፡ ስለዚህ ድሀ በተለይም የእኔ ቢጤዎቹ ሴቶች በጣም እንቸገር ነበር” ይላሉ ወይዘሮዋ፡፡ ሆኖም በነፀብራቅ የሴቶችና ህፃናት የልማት ማህበር ሥር ከታቀፉ በኋላ ወይዘሮ መሪማ ለችግራቸው መፍትሄ አገኙ፡፡ ከነፀብራቅ በተቀበሉት የንግድ ሥራ ክህሎት ሥልጠናና ከወለድ ነፃ የሆነ ብድር አማካኝነት የእራሳቸውን ንግድ በመጀመር፣ ልጆቻቸውን ማስተማር በአጠቃላይም ቤተሰባቸውን ያለችግር ማስተዳደር ችለዋል፡፡
የ23 ዓመቱ የቢሾፍቱ ከተማ ወጣት ተስፋሁን አበራ ታሪክ ደሞ እንዲህ ነው፡፡ ተስፋሁን ገና የሁለተኛ ደረጃ ተማሪ እያለ ነበር አባቱን በሞት የተነጠቀው፡፡ በእንቅርት ላይ ጆሮ ደግፍ እንዲሉ፣ እናቱም ታመው አልጋ ላይ ዋሉ፡፡ ስለዚህ ተስፋሁን ከእናቱና ከእህቶቹ ጋር በድህነት ሕይወቱን እንዲገፋ ተገደደ፡፡ “ስላሳለፍኩት ውስብስብ ህይወት ምንም የሚያውቁት ነገር ሳይኖር ሰዎች ሥራ በማጣቴ፣ እንደ ዕድሜ እኩዮቼ ዩኒቨርሲቲ ባለመግባቴ ይኮንኑኝ ነበር፡፡ ስለዚህ እኔም እራሴን የተረገምኩ አድርጌ እቆጥር ነበር፡፡” ይላል ተስፋሁን የቀድሞውን ሲያስታውስ፡፡ ይህ በእንዲህ እንዳለ ተስፋሁን በትጋት የልማት ማህበር በመታቀፍ፣ የኮምፒዩተርና የመረጃ ቴክኖሎጂ ሥልጠና ወሰደ፡፡ ሥልጠናውን ካጠናቀቀ በኋላም በፎቶግራፍ ማንሳትና እጥበት ሥራ በቋሚነትና በትርፍ ጊዜ በመሠማራት ጠቃሚ ገቢ ለማግኘት በቅቷል፡፡ ከዚሁ ጎን ለጎን ዛሬ የእራሱ ስቱዲዮ ያለው ሲሆን ወደፊትም ኢንተርኔት ካፌ ለመክፈት አቅዷል፡፡ ዛሬ ከእራሱና ከቤተሰቡ አልፎ ለሌላም ለመትረፍ ያስባል፡፡ “አሁን አንገቴን ቀና አድርጌ መሄድ እችላለሁ፡፡ ምክንያቱም በጎረቤቶቻችን ዘንድ ጠንካራ ሠራተኛ ተብዬ ተቀባይነትን አግኝቻለሁ፡፡ ወደፊትም ችግረኛ ህፃናትንና ሴቶችን ለመደገፍ እምችለውን ሁሉ አደርጋለሁ፡፡” ብሏል፡፡
ባጠቃላይ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ወደ ልማት ፊታቸውን በማዞር፣ የሕብረተሰባቸውን ችግር ለመፍታት ደፋ ቀና የሚሉት የማህበረሰብ ምሥርት ተቋማት፣ ነባራዊውን ሁኔታ ለመረዳት የበለጠ ቅርብ ስለሆኑ በነሱ አማካኝነት በርካታ ተጠቃሚዎችን በቀላሉ መለየትና መድረስ እንደሚቻል አያጠያይቅም፡፡ ማህበራቱም የአካባቢያቸውን ህብረተሰብ ችግር ለአንዴና ለመጨረሻ ጊዜ ለመፍታት  ትልቅ ራዕይ እንደሰነቁ በተለያዩ ጊዜያቶች አስመስክረዋል፡፡ እንዲያም ሆኖ ራዕያቸውን እውን ለማድረግ  የሚያደርጉት ጥረት ተጠናክሮ እንዲቀጥልና ለዘለቄታው እራሳቸውን እንዲችሉ ከመንግሥትም ሆነ ከሌሎች ባለድርሻ አካላት የተቀናጀ ድጋፍ ያስፈልጋቸዋል፡፡ ይህንኑ መነሻ በማድረግ ኢ/ህ/ማ/ል/ድ በየዓመቱ የማህበረሰብ ምሥርት ተቋማት መልካም ተሞክሮ ቀንን በማክበር፣ ተቋማቱ እርስበርስ እንዲተዋወቁ፣ ልምድ እንዲለዋወጡ፣ እንዲሁም ከመንግስትና ሌሎች የልማት አጋሮች ጋር  መልካም ትብብርና ትስስር እንዲፈጥሩ ልዩ መድረክ እያመቻቸላቸው ይገኛል፡፡ ዘንድሮም ሰኔ 23 ቀን 2ዐዐ8 ዓ.ም በቢሾፍቱ ከተማ በሚገኘው የድርጅቱ “ጄክዶ ኦፖርቹኒቲ ፎር ቼንጅ” የሥልጠና ማዕከል የመንግሥት፣ መንግሥታዊ ያልሆኑ ድርጅቶችና የንግዱ ማህበረሰብ ተወካዮች በተገኙበት “የማህበረሰብ ምሥርት ተቋማት አጋርነት ለዘላቂ ልማት” በሚል መሪ ቃል በደማቅ ሁኔታ ለማክበር ዝግጅቱን አጠናቅቋል፡፡ ዝግጅቱ ማህበራቱ የስራ ውጤቶቻቸውን በትዕይንትና በድምጽ የሚያስተጋቡበት፤ ከተለያዩ የሀገራችን ክፍሎች የተውጣጡ 6ዐ የማህበረሰብ ምሥርት ተቋማት በማህበረሰብ ልማት ዘንድ ላደረጉት አስተዋፅኦ ዕውቅና የሚሰጥበት፤ ከዚህ በተጨማሪ የላቀ አፈፃፀም ላስመዘገቡ የማህበረሰብ ምሥርት ተቋማት ልዩ ሽልማት የሚበረከትበት የማህበራቱ ዝግጅት ነው፡፡
የእንደዚህ ያለ ውጥን ዋና መልእክት፤ የማህበራትን ልማታዊ ፋይዳ በማጉላት ተገቢውን እገዛና ትብብር ለማህበራቱ መሻት ነው፡፡ ስለሆነም ከግለሰብ እስከ ተቋም፤ ከልጅ እስከ አዋቂ…. እርስ በርስ በመደጋገፍ፣ በአንድነት በመተባበር እንደ ማህበረሰብ ምስርት ተቋማት ያሉ የህብረተሰብ አጋዦችን ማገዝ ከተቻለ፣ የማህበረሰብን ችጋር ማባረር ብሎም ከሥልጣኔና ከብልፅግና ማማ ላይ መውጣት ይቻላል፡፡  በመተባበር የማይናድ የችግር ጋራ፣ በመተጋገዝ የማይገፈፍ የችጋር ደንቃራ፤ ተቀናጅቶ በመስራት የማይቀረፍ ልማታዊ ፈተና የለምና ሁሉም ያብር፡፡ “ድር ቢያብር አንበሳ ያስር!” ነውና ብሂሉ፡፡

ባለፈው ረቡዕ ሁለት ሚሳኤሎችን አስወንጭፋለች

ሰሜን ኮርያ በተመድ የጸጥታው ምክር ቤት የተጣለባትን እገዳ በመጣስ ባለፈው ረቡዕ ማለዳ ሁለት አደገኛ የመካከለኛ ርቀት ሚሳኤሎችን ማስወንጨፏን ተከትሎ፣ የአገሪቱ መንግስት በፈጸመው ድርጊት አለማቀፍ ተቃውሞ  ገጥሞታል፡፡
የጃፓን የመከላከያ ሚኒስትር ጄን ናካታኒ፤የሚሳኤል ሙከራዎቹ ሰሜን ኮርያ ወታደራዊ አቅሟን በማሳደግ ደቡብ ኮርያን፣ ጃፓንንና ሌሎች አካባቢዎችን ለመምታት የሚያስችሉ መሳሪያዎችን ማምረቷን የሚያሳዩ እንደሆኑ ጠቁመው፣ እያደገ የመጣው የሰሜን ኮርያ ወታደራዊ ሃይል  ለአገራቸውም ሆነ ለአካባቢው አገራት ከፍተኛ አደጋ ነው ማለታቸውን ዘ ጋርዲያን ዘግቧል፡፡
የጃፓኑ ጠቅላይ ሚኒስትር ሺንዞ አቤ፤ ድርጊቱ የጸጥታው ምክር ቤትን እገዳዎች የጣሰ ህገወጥ ተግባር መሆኑን ጠቁመው፣ አገራቸው ከአሜሪካና ከደቡብ ኮርያ ጋር በመተባበር ለድርጊቱ ምላሽ እንደምትሰጥ አስታውቀዋል፡፡
የኔቶ ዋና ጸሃፊ ጄንስ ስቶልንበርግ በበኩላቸው፤ሰሜን ኮርያ ሚሳኤሎቹን ማስወንጨፏን በጽኑ እንደሚቃወሙት ጠቁመው፣ አገሪቱ መሰል ጸብ አጫሪ ድርጊቶችን ከመፈጸምና የባለስቲክ ሚሳኤል ቴክኖሎጂዎችን በመጠቀም ሚሳኤሎችን ከማስወንጨፍ እንድትቆጠብ አስጠንቅቀዋል፡፡
የአሜሪካ መንግስት ቃል አቀባይ ጆን ኪርቢ፤የሰሜን ኮርያን ድርጊት አስጊና ጸብ አጫሪ በመሆኑ በጽኑ እንቃወመዋለን፤ ራሳችንንም ሆነ ጃፓንና ደቡብ ኮርያን የመሳሰሉ አጋሮቻችንን ከመሰል ስጋቶች ለመከላከል የያዝነው ጽኑ አቋም አሁንም እንደጸና ነው ብለዋል፡፡


Saturday, 25 June 2016 12:12

የዘላለም ጥግ

- በጥበብ መፅሃፍ ውስጥ የመጀመሪያው
ምዕራፍ ሃቀኝነት ነው፡፡
ቶማስ ጄፈርሰን
- እውነቱን የምትናገር ከሆነ ምንም ነገር
ማስታወስ አይኖርብህም፡፡
ማርክ ትዌይን
- ስለ ራስህ እውነቱን የማትናገር ከሆነ፣ ስለ
ሌሎች እውነቱን ልትናገር አትችልም፡፡
ቪርጂንያ ውልፍ
- በመጠራጠር ወደ ጥያቄ እናመራለን፣
በመጠየቅ ወደ እውነቱ እንደርሳለን፡፡
ፒተር አቤላርድ
- እውነት ነፃ ያወጣሃል፤ መጀመሪያ ግን
አሳርህን ያበላሃል፡፡
ጄምስ ኤ. ጋርፊልድ
- እውነት ጫማዋን ስታጠልቅ፣ ውሸት
የዓለምን ግማሽ ልትጓዝ (ልታዳርስ)
ትችላለች፡፡
ቻርለስ ስፐርጊዮን
- የትምህርት ግብ ዕውቀትን ማስፋፋትና
እውነትን ማሰራጨት ነው፡፡
ጆን ኤፍ.ኬኔዲ
- አብዛኞቹ ቀልዶች መራር እውነትን
ይገልፃሉ፡፡
ላሪ ጌልባርት
- ተፈጥሮን መርምር፣ ተፈጥሮ የእውነት
ጓደኛ ናት፡፡
ኢድዋርድ ያንግ
- ለሰዎች ሃቁን የምትነግራቸው ከሆነ
አስቂኝ ሁን፤ ያለበለዚያ ይገድሉሃል፡፡
ቢሊ ዋይልደር
- ህይወት ሞትን እንዲህ ስትል ጠየቀችው፡
- “ለምንድነው ሰዎች እኔን የሚወዱኝ፤
አንተ ግን የሚጠሉህ?”
ሞትም መ ለሰላት፡- “ ምክንያቱም አ ንቺ
ውሸት ነሽ፤ እኔ ደግሞ መራር እውነት
ነኝ”
ያልታወቀ ተናጋሪ
- እውነቱን ተናገር፤ አሊያም ሌላ ሰው
ይናገርልሃል፡፡
ስቴፋኒ ክሌይን
(ስለ እውነት



ከ65.3 ሚ የአለማችን ስደተኞች፣ ግማሽ ያህሉ ህጻናት ናቸው
   በአለማችን የተለያዩ አካባቢዎች የሚገኙ ስደተኞች ብዛት በታሪክ ከፍተኛውን ቁጥር ያስመዘገቡ ሲሆን እስካለፈው የፈረንጆች አመት 2015 መጨረሻ  በስደተኝነት የተመዘገቡ፣ ጥገኝነት የጠየቁ ወይም በአገር ውስጥ የተፈናቀሉ ሰዎች ቁጥር 65.3 ሚሊዮን መድረሱን ተመድ አስታወቀ፡፡የአለማችን ስደተኞች ቁጥር በ2014 ከነበረበት የ10 በመቶ ጭማሪ ማሳየቱን የገለጸው የተመድ የስደተኞች ኮሚሽን፣ በአለማችን ከሚገኙ ስደተኞች መካከል 54 በመቶ የሚሆኑት የሶርያ፣ የአፍጋኒስታንና የሶማሊያ ዜጎች መሆናቸውን ጠቁሞ 10 ሚሊዮን ስደተኞች ያሏት ሶርያ ቀዳሚውን ስፍራ ይዛለች ብሏል፡፡በአለማችን ከ113 ሰዎች መካከል አንዱ ስደተኛ እንደሆነ የጠቆመው ኮሚሽኑ፤በፈረንጆች 2015 በአንድ ደቂቃ 24 ያህል ሰዎች አካባቢያቸውን ጥለው እንዲሰደዱ መገደዳቸውንና ግማሽ ያህሉ የአለማችን ስደተኞች ከ18 አመት በታች የሚገኙ ህጻናት መሆናቸውን አስታውቋል፡፡
ዓምና ባህር አቋርጠው ወደ አውሮፓ የገቡ ስደተኞች ቁጥር ከ1 ሚሊዮን በላይ እንደነበር ያስታወሰው ኮሚሽኑ፤በርካታ ስደተኞችን በመቀበል ከአለማችን አገራት ቀዳሚውን ስፍራ የያዘችው ቱርክ መሆኗንና በአገሪቱ 2.5 ሚሊዮን ያህል የሌሎች አገራት ስደተኞች እንደሚገኙ ገልጧል፡፡