Administrator

Administrator

Saturday, 26 March 2016 11:40

የኪነት ጥግ

(ስለ ተዋንያን)
ድራማን በተመለከተ ተሳስቻለሁ፡፡ ድራማ የሚባለው ተዋንያኑ ሲያለቅሱ ይመስለኝ ነበር፡፡ ድራማ ግን ተመልካቹ ሲያለቅስ ነው፡፡
ፍራንክ ካፕራ
ሰዎች በአንድ ነገር ብቻ መታወስ ለምን እንደሚይናድዳቸው ይገባኛል፡፡ ብዙዎቹ ተዋንያን ግን በምንም ነገር አይታወሱም፡፡ እኔ ለዚያ ደንታ የለኝም፡፡
ጁሊ ዋልተርስ
ተዋንያን የለውጥ ሃዋርያ ናቸው፡፡ አንድ ፊልም፣ ቲያትር፣ ሙዚቃ ወይም መጽሐፍ ልዩነት ይፈጥራል፡፡ ዓለምን ሊለውጥ ይችላል፡፡
ኢላን ሪክማን
የምጫወተው ገፀባህርይ ባለፈው ማክሰኞ ቁርሱን ምን እንደበላ የማውቅ ዓይነት ተዋናይ አይደለሁም፡፡
ሊያም ኒሰን
ተዋናዩ ዩኒቨርስን በእጁ መዳፍ ላይ መፍጠር መቻል አለበት፡፡
ሎውረንስ ኦሊቪዬር
ተዋናይ፤ ስለእሱ እያወራችሁ ካልሆነ በቀር የማያዳምጣችሁ ሰው ማለት ነው፡፡
ማርሎን ብራንዶ
ግሩም ተዋናይ መሆን ቀላል አይደለም፡፡ ሰው መሆን ደግሞ የበለጠ ከባድ ነው፡፡ ዕድሜዬ ከመጥለቁ በፊት ሁለቱንም ለመሆን እሻለሁ፡፡
ጄምስ ዲን
እያንዳንዱ ተዋናይ ሁሉንም ሰው ለመሆን ይሻል - ሁሉንም ገፀ ባህርያት መጫወት፡፡
ኬይሌ ቻንድለር
ሁሉም ተዋንያን ተንኮለኞች ናቸው፡፡ ሁላችንም ችግር ፈጣሪዎች ነን - አሰቃቂ፣ ትኩረት ፈላጊ ህፃናት፡፡ “እኔ…እኔ…እኔን ተመልከቱኝ” የምንል።
ሴይና ጉይሌሪ
እኔ ተዋናይ ነኝ፤ ኮከብ አይደለሁም፡፡ ክዋክብቱ በሆሊውድ የሚኖሩና የልብ ቅርጽ ያለው የመዋኛ ገንዳ ያላቸው ናቸው፡፡
አል ፓቺኖ
ግሩም ዳይሬክተር፤ ተዋናዩ ክንፍ አውጥቶ የመብረር ብርታት የሚያጐናጽፈውን ከባቢ ይፈጥራል፡፡
ኬቪን ቤከን
ሁለት ዓይነት ተዋንያን አሉ፡- ዝነኛ መሆን አልንፈልግም የሚሉና ውሸታሞች፡፡
ኬቪን ቤከን

       ዋና አሰልጣኝ ብርሃኑ ግዛው የኢትዮጵያ ሴቶች ብሄራዊ ቡድኑ ወደ አፍሪካ ዋንጫ ለማለፍ ጥሩ እድል እንዳለው ያምንበታል፡፡ ዛሬ በአዲስ አበባ ስታድዬም የመልስ ጨዋታ ያደርጋሉ፡፡ ከሁለት ሳምንት በፊት በአልጀርስ ተደርጎ በነበረው ጨዋታ ሉሲዎቹ በአልጄርያ አቻቸው 1ለ0 መሸነፋቸው ይታወሳል፡፡ ዛሬ ጥሎ በማለፍ ወደመጨረሻው የማጣርያ ምእራፍ ለመሸጋገር 2ለ0 እና ከዚያም በላይ ማሸነፍ አለባቸው፡፡
     አልጄርያ በሴቶች እግር ኳስ ጥሩ ደረጃ ላይ እንደሆነች ለስፖርት አድማስ የተናገረው ዋና አሰልጣኝ ብርሃኑ ግዛው፤ በሰሜን አፍሪካዊቷ አገር የሴቶች እግር ኳስ በተናጠል  ፌደሬሽን፤ ሊግ አስተዳደር፤ ስታድዬሞች መከናወኑ በረጅም ግዜ በተዘረጉ እቅዶች የሚካሄድ መሆኑን ልንማርበት ይገባል ሲል ያሰምርበታል፡፡ በአልጄርያ እግር ኳስ በሀ 17 እና በሀ 20 የሴቶች እግር ኳስ መንቀሳቀሱን እንደተምሳሌት በመውሰድም በኢትዮጵያ ልንሰራበት ይገባል ብሎም አስተያየት ይሰጣል፡፡
ሉሲዎቹ ዛሬ የሚገጥሙት የአልጄርያ ብሄራዊ ቡድን 12 ፕሮፌሽናል ተጨዋቾች እንዳሉበት የሚገልፀው ዋና አሰልጣኝ ብርሃኑ፤  በመጀመርያው ጨዋታ 1ለ0 መሸነፋቸው የሉሲዎችን ጥንካሬ እንደሚያሳይ አስገንዝቦ፤  በመልሱ ጨዋታ በሜዳችን፤ በአየራችን እና በደጋፊያችን ፊት ውጤቱን ለመቀልበስ ነው ተስፋ የምናደርገው በሁላችንም ትግልና ጥንካሬ ነው ሲል ይናገራል፡፡ የመልሱን ጨዋታ በከፍተኛ ጥንቃቄ  የምናደርገው ይሆናል ያለው ዋና አሰልጣኙ፤ ጥሩ ዝግጅት ማድረጋቸውን፤ በሜዳቸው ብዙ ዋጋ ሊያከፍል የሚችል ግብ እንዳይቆጠር መስራታቸውን  ለስፖርት አድማስ አብራርቷል፡፡
የሉሲዎቹ አባላት በስነምግባራቸው ጥሩ ደረጃ ላይ መሆናቸውን የሚገልፀው ዋና አሰልጣኝ ብርሃኑ ግዛው፤  እንደ ሎዛ አበራ አይነት ወጣትና ምርጥ የአጥቂ መስመር ተጨዋች፤ በአፍሪካ ዋንጫ ልምድ ያላቻቸው አጥቂዋ ረሂማ ዘርጋው፤  ግብ ጠባቂዋ ዳግማዊትና አምበሏ ብርቱካን ገብረክርስቶስ ቡድኑን በመምራት ባላቸው ከፍተኛ ሚና ደስተኛ ነው፡፡ በአጠቃላይ ቡድኑ በታዳጊ፤ በወጣት እና በአንጋፋ ተጨዋቾች ስብስብ የተገነባ መሆኑ ጠንካራ እንደሚያደርገውም ለስፖርት አድማስ በሰጠው ቃለምልልስ ዋና አሰልጣኝ ብርሃኑ ግዛው ተናግሯል፡፡ ለወደፊቱ ብሄራዊ ቡድኑ ለተጨዋቾቹ በቂ ጥቅም ሆነው የሚታዩ ማበረታቻዎችን፤ ለዝግጅት የሚያግዙ በቂ የወዳጅነት ጨዋታዎችን በማዘጋጀት ፌደሬሽኑ የቡድኑን ጥንካሬ ለማጎልበት መንቀሳቀስ አለበትም ሲል መልዕክቱን ያስተላልፋል፡፡ ስፖርት አድማስ ከሉሲዎቹ ዋና አሰልጣኝ ብርሃኑ ግዛው ጋር ያደረገው ልዩ ቃለምልልስ ከዚህ በታች የቀረበው ነው፡፡
በስፖርት ላይ የሚያተኩር ልዩ እና ፈርቀዳጅ መፅሃፍ አሳትመሃል ቃለምልልሱን በሱ ስንጀምርስ
አዎ፤ ልክ ነህ፡፡ በስፖርት ብቻ ሳይሆን በህይወት ታሪኬ ላይ የሚያተኩር መፅሃፍ ነው፡፡ “ከስደት መልስ እስከ ብሄራዊ ቡድን አሰልጣኝነት” በሚል ርእስ የተዘጋጀ ነው፡፡ ብዙ ወጣቶች በስደት ህይወት እንደሚባክኑ የሚታይ ቢሆንም በመፅሃፌ ከስደት ህይወት ተመልሶ ስኬት ማግኘት እንደሚቻል ለማስረዳት ሞክርያለሁ፡፡ በተጨማሪም መፅሃፉ በግል ህይወቴ ብቻ ሳይሆን ከስፖርቱ ጋር በተያያዘ እግር ኳስን በተጫዋችነት ከዚያም በአሰልጣኝነት እንዴት እንዳሳለፍኩ፤ ወደስልጠና ሙያ ለመግባት በምን አይነት ስነምግባር በርካታ ውጣውረዶችን እንዳለፍኩ የሚያወሳ ነው፡፡
የስፖርት መፅሃፍ አዘጋጅቶ ለገበያ ማቅረብ የተለመደ አይደለም፤ አንተን ምን አነሳስቶህ ነው?
መፅሃፉን ሳሰትም ዋናው ዓላማዬ የህይወት ተመክሮዬና በስፖርቱ ያሳለፍኩትን ጥረትና ልምድ ለህዝብ እንዲደርስ በማሰብ ነው፡፡ በመጀመርያው እትም የመፅሃፉ ብዛት ያን ያህል አርኪ አልነበረም፡፡ 1500 ኮፒ ብቻ ነበር ያሳተምኩት። ወዲያው ለገበያ እንደቀረበ ወርም ሳይሞላ ነበር ያለቀው፡፡ አሁን በቅርብ ጊዜ ሁለተኛ እትም ለማሳተም እየተንቀሳቀስኩ ነው። እንደእቅዴ ከሆነ ሁለተኛውን እትም በ4ሺ እና በ5ሺ ኮፒ ለማሳተም ነው፡፡
መፅሃፉን በምን ዓላማ ነው አሳተምከው፤  ታላላቅ አትሌቶችና የእግር ኳስ ባለታሪኮች በዚህ ረገድ ብዙም ሲንቀሳቀሱ አይታይም፤ ማንስ ነው መፅሃፍ የማዘጋጀት ሃላፊነት ያለበት ጋዜጠኞች ወይንስ ባለታሪኮቹ ስፖርተኞች?
እኔ እንደሚመስለኝ  ባለቤቱ ራሱ እንደመሆኑ ሃላፊነቱ የስፖርተኛው ነው፡፡ ያለፍክባቸውን የስፖርት ተመክሮዎች፤ የሰራሃቸውን ታሪኮች አስተማሪነት እንዳላቸው ካመንክበት በራስህ ጥረት ልታደርገው የሚገባ ስለሆነ ነው፡፡ ግን በስራ ዘመንህ ታሪኮችን በአግባቡ መሰነድ፤ በማስታወሻ እየከተብክ ማኖር እና ከተለያዩ አቅጣጫዎች በማገናዘብ አዘጋጅተህ ተግባራዊ ልታደርገው የምትችል ነው፡፡ እኔ መፅሃፉን ያሳተምኩት ልጄን ከወለድኩ በኋላ ስለሆነ ከዚያ እንደሁለተኛ ልጄ ነው የቆጠርኩት፡፡ መፅሃፍ ታሪክን የሚያስቀምጥ ነው፡፡ የሚመጣ ትውልድ ሊማርበት የሚችል ነው፡፡ ከታሪክህ ብዙ ስፖርተኛ አንብቦ ሊማር የሚችለው ብዙ ቁምነገር መኖሩን መገንዘብ አለብህ፡፡ በእኛ አገር ስፖርተኞች የተለመደው ጡረታ ከተወጣ በኋላ መፃፍ ነው፡፡ ነገር ግን እኔ እንደማስበው በስራ ዘመንህ፤ በህይወት ላይ ጉልበት እና ሞራል እያለህ በምታልፍባቸው የስራ ውጣውረዶች እና ጎዳናዎች ያሉህን ተመክሮዎች እየተገነዘብክ በየጊዜው መፃፉ አስፈላጊም ተገቢም ነው፡፡
እንግዲህ አንተ ባለህ የስራ ልምድ አብዛኛውን ድርሻ የሚወስደው በሴቶች እግር ኳስ ላይ ያለህ ተመክሮ ነው፡፡ ‹‹ከስደት መልስ እስከ ብሄራዊ ቡድን አሰልጣኝነት” በሚለው መፅሃፍህ በሴቶች እግር ኳስ ዙርያ ምን ምን ተወስቷል፡፡
በሴቶች እግር ኳስ አሰልጣኝነት መስራት ከጀመርኩ እንግዲህ 17 ዓመታት ተቆጥረዋል፡፡ በ17 ዓመት ውስጥ  የሴቶች እግር ኳስ ሲጀመር ማለትም ገና ሲፀነስ ነበርኩ፤ ከዚያም እርግዝናው ላይ ምጡ ላይም አለሁበት፡፡ ከዚያም ተወልዶ ዳዴ ብሎ ማደግ ሲጀምርም እየሰራሁበት ነው፡፡
የሴቶችን እግር  ኳስ ከጅምሩ እዚህ አገር ውስጥ ብዙም ተቀባይነት ስላልነበረው ከመጀመርያው ይህን ተቀባይነት ለማግኘት ብዙ ጥረት ማድረግ ነበረብን፤ ይገርምሃል ያኔ ከ17 ዓመታት በፊት ሜዳ ለወንድ ተጨዋቾች ሲለቀቅ ለሴት ኳስ ተጨዋቾች የሚለቅ ሁሉ አልነበረም፡፡ በሌላ በኩል የፋይናንስ እጥረት ነበር፡፡ ያኔ በገንዘብ በኩል ያለብንን ችግር ለመቅረፍ ይገርምሃል ሆያ ሆዬ፤ አበባየሁሽ እየጨፍርን ገቢ ለማግኘት እንጥር ነበር፤ ይህ እንግዲህ ከ14 ዓመታት በፊት ነው፡፡ ከሆያ ሆዬ እና ከአበባየሁሽ ጭፈራ በኋላም እኛ አሰልጣኞቹ እና ወጣቶቹ ሴት እግር ኳስተጨዋቾች የራሳችንን እጣ እንደበግ እና ሌሎች ሽልማቶች ያሉበትን ሎተሪ አዘጋጅተን እና ተዟዙሮ በመሸጥ ገንዘብ ለማግኘት ሁሉ ሰርተናል፡፡ እነዚህን ገቢ የማሰባሰብ ተግባራት በመጀመርያ ጃንሜዳ አካባቢ ጀምረነው ከዚያም፤ ወደ ፒያሳ መርካቶ ኮተቤ እየሄድን የምንሰራቸው ነበሩ፡፡ ወደ ተለያዩ ክልሎችም እየተንቀሳቀስን ገንዘብ ሰብስበናል፡፡ በእነዚህ እንቅስቃሴዎች የምናገኘውን ገንዘብ የምንሰበስበው ከልምምድ በኋላ ነበር፡፡ ድንችና ፓስታ ቀቅለን ተጨዋቾቻችንን እየመገብን ሁሉም ከየተሰማራበት አቅጣጫ የሰበሰበውን እንረከባለን፡፡ አምበሎች አማካኝነት የተሰበሰበው ገንዘብ ኳስ እና፤ ማሊያ የተለያዩ ትጥቆች ይገዙበታል፡፡ በአዲስ አበባ ከፍተኛ ዲቪዚዮን እና አንደኛ ዲቪዚዮን ውድድሮች ከፍለን በመመዝገብ ተሳትፎ ማድረግ እየቻልን መጣን። በእነዚህ ውድድሮች ለመሳተፍእስከ 1000 ብር መክፈል ነበረብን። ከ14 ዓመታት በፊት ይህ ብዙ ገንዘብ ነው፡፡ ለምሳሌ አንድ ሰው አንገቱ ላይ የወርቅ ሃብል አጥልቋል፡፡ ሰው ወርቁን ሲያይ ሊደንቀው ይችላል፡፡ ግን መጀመርያ ወርቁ የመጣበትን ወርቁ የተፈተነበትን፤ ወርቁ እንዴት ተቃጥሎ እንደመጣ የሚያቀው ወርቁ ራሱ ነው፡፡ ግን ከፈተና የወጣ  ሁል ጊዜ ማማር ይችላል። እኛ በሴቶችእግር ኳስያሳለፍነው ተመክሮ እንደዚህ የሚገለፅ ነው፡፡ የመጽሐፌም ይህን የመሰሉ ታሪኮች ተነስተዋል፡፡
በፌደሬሽኑ በኩል ያን ግዜ የምታደርጉትን እንቅስቃሴ የሚደግፍ አሰራር አልነበረም እንዴ
እንግዲህ ዓለም አቀፉ  የእግር ኳስ ማህበር በሴቶችእግር ኳስ ላይ ማተኮር የጀመረው ከ25 ዓመታት በፊት እንደሆነ ታውቃለህ፤ እናም እኛ በሴቶች እግር ኳስ መንቀሳቀስ ስንጀምር ከፊፋ የሚላክ ገንዘብ ቢኖርም በፌደሬሽኑ በኩል የነበረው ትኩረት ደካማ ስለነበር የሚመጣው የበጀት ድጋፍ ለወንዶቹ ውድድሮች ነበር የሚሰራጨው፡፡ እንደምታውቀው ፊፋ ለአባል ፌደሬሽኖች ከሚያበረክታቸው የገንዘብ ድጋፎ ለሴቶችና ወጣቶች የእግር ኳስ እንቅስቃሴ እስከ 250ሺ ዶላር በየውድድር ዘመኑ ይሰጣል፡፡ ይህ በጀት ወደ ውድድሮች ነው የሚሄደው በአንድ ታዳጊ አገር አቅሙ ባለመኖሩ የሚያስደነግጥ አይደለም፤ እኛ ስንጀምረው  በሴቶች እግር ኳስ አሰልጣኝነት የምንሰራ ባለሙያዎች ጥቂት ነበርን፡፡ ጋሽ ይተፋ፤ ያሬድ ቶሌራ፤ ደረጀ ነጋ፤ ፍቃዱ ማሙዬ እና እኔ በማሰልጠን እንሰራ በነበርነበት ጊዜ በጃንሜዳ አካባቢ የተወሰነ ነበር እንቅስቃሴያችን፡፡ ደረጃ ብቻ ነበር የካ አካባቢ ይሰራ ነበር። እኔ ማሰልጠኑን ስጀምር በወንዶችእግር ኳስ ነበር ለምሳሌ እነ አሉላ ግርማን የመሳሰሉ ተጨዋቾች ባፈሩ ፕሮጀክቶች እሰራ ነበር፡፡ ከግዜ በኋላ ግን በሴቶችእግር ኳስ ብዙ የሚሰራ ባለመኖሩ ወደዚያ መስክ ለመዞር በመወሰን የገባሁበት ነው፡፡ ብዙ ሙያተኞች በዚህ ውሳኒያችን ተገርመው ይንቁንም ነበር። በጃንሜዳ  የአዲስ አበባ ከፍተኛ ዲቪዝዮን በሚባል መደበኛ ውድድር ቡድኖቻችንን ይዘን እንሳተፍ ነበር፡፡
ብዙ ዓመታትን በጃሜዳ የዲቪዚዮን ውድድሮች ካሳለፍን በኋላ የክልል ሻምፒዮናዎች መካሄድ ጀመሩ፤ ከዚያም ፕሪሚዬር ሊግ መጣ፡፡ የሚገርምህ በከፍተኛ ዲቪዝዮን ይጫወቱ የነበሩ ልጆች ኳስ ብዙም ገቢ ስለማይፈጥርላቸው ወደ አረብ አገራት መሰደድን ሁሉ የሚመርጡበት ሁኔታ ነበር፡፡ ፕሪሚዬር ሊግ ሲጀመር ግን  የሴቶች እግር ኳስ ከስደት የተሻለ ህይወት እና ገቢ የሚገኝበትን እድል ስለሚፈጥር ሁኔታው ሊቀየር ችሏል፡፡
እንግዲህ ባለፉት 14 ዓመታት የሴቶችእግር ኳስ ያለፉባቸውን ውጣውረዶች በመጠኑ ዳስሰሃቸዋል፡፡ አሁን ያለበትን ደረጃ የምትገልፀው እንዴት ነው
 አሁን የሴቶች እግር ኳስን  ህብረተሰቡ ተቀብሎታል፤ ቤተሰብምም ተቀብሎት የሚደግፈው ሆኗል፤ ከወንዶች የእግር ኳስ እንቅስቃሴ እኩልም ትኩረት እየተሰጠው ነው፡፡ አሁን ለምሳሌ በክፍለ ከተማ ደረጃ እንኳ የወንዶችም የሴቶችም ቡድኖች እየተመሰረቱ ናቸው፡፡ እግር ኳሱን እያሻሸለው ያለ አቅጣጫ ነው፡፡ ክለቦችም ከመቼውም ጊዜ በላቀ ሁኔታ ትኩረት ሰጥተው እየሰሩበት ናቸው፡፡ ድሮ ቡና ጊዮርጊስ ብለን ስለቡድኖቹ የምንሰማው በወንዶች ብቻ ነበር፣ አሁን ደግሞ በሴቶችም የሚታይ መደበኛ ተግባር እየሆነ ነው፡፡ በፕሪሚዬር ሊግ ደረጃ ክለቦች የየራሳቸውን ቡድኖች በማቋቋም መወዳደራቸው የሚያደስት ቢሆንም ግን አንዳንድ ክፍተቶች አሉ በታዳጊዎች ደረጃ እየተሰራ….
ይቅርታ ብርሃኑ የብሄራዊ ቡድን ዋና አሰልጣኝ እንደመሆንህ ያሉትን ክፍተቶች በግልፅ ልትናገራቸው ያስፈልጋል..
ልክ ነህ፡፡ ለሴቶች እግር ኳስ መለወጥ እና ማደግ ከፍተኛ መስዕዋትነት ከፍዬ የደረስኩበት ደረጃላይ የወደፊቱን ተስፋ የሚያደበዝዝ እና እድገቱን የሚያንቀራፍፍ ሁኔታ ከታዘብኩ እተቻለሁ፡፡ ክለቦች በፕሪሚዬር ሊግ ደረጃ የሴቶች ቡድኖችን መስርተው መወዳደር ሲጀምሩ ለተጨዋቾቻቸው የወንድ ትጥቆችን በማቅረብ፤ አነስተኛ በጀት በመመደብ ነበር፡፡ አሁን ግን ሁሉም ክለቦች በሴት ቡድኖቻቸው ምስረታ የእኔነት ስሜት በማዳበር መንቀሳቀሳቸው ትልቅለውጥ ይመስለኛል። ይህ ብቻውን ግን በቂ አይደለም፡፡ አሁን አንዳንድ ክለቦች የመሰረቷቸውን ቡድኖች ያለበቂ ምክንያት እያፈረሱ ናቸው፡፡ ለሴቶች እግር ኳስ ክብር የማይሰጡ ክለቦች አሉ፡፡ ለወንዶች  ከፍተኛ በጀት እየመደቡ የሚንቀሳቀሱ አንዳንድ ክለቦች የሴት ቡድኖቻቸውን እንደዘበት የሚያፈርሱት አካሄድ በፍፁም ልክ አይደለም፡፡ ሴቶች እኮ በየትኛውም መስክ ዋንኛ አካላት ናቸው። ምናልባት በየክለቡ ሴት አመራሮችም ይኖራሉ እና ታድያ የተመሰረተ ክለብን ማፈራረስ እና መበታተን ለምንድነው፡፡ ቡድኖቻቸውን ካፈረሱ ክለቦች መካከል  ወላይታ ዲቻና መድን ይጠቀሳሉ፡፡ በወላይታ ዲቻ በኩል ክልሉ፤ በመድን በኩል የክለቡ አስተዳደር ይህ ተግባር ለምን ዝም እንዳሉት አይገባኝም፡፡ በሌላ በኩል እንደወልዲያ ከነማ አይነት ክለቦች የሴቶች ቡድን እንዲመሰርቱ ፌደሬሽኑ ለምን አያስገድድም፡፡ የተመሰረቱ ቡድኖችን ማፍረስ፤ ከእነጭራሹ በሴቶች እግር ኳስ ያለመስራት ሁኔታዎች መጥፎ አዝማሚያዎች ይመስሉኛል፡፡ በትጋት በሚሰሩ ክለቦች ላይ የሚዛመቱ ችግሮች ስለሚሆኑም ስጋት አለኝ፡፡ የግንዛቤ እግር በአመራሮች ላይ ይታያል፡፡ ጠንካራ የሴቶች እግር ኳስ እንቅስቃሴን በሚያሳዩ እንደ ንግድ ባንክ፤ ደደቢት እና ዳሸን፤ ቡናና ጊዮርጊስ ያሉ ክለቦች ያለው ችግር ደግሞ በወንዶቹ የሚሰጡትን ትኩረት ያህል አለመስራታቸው ነው፡፡ በተለይ በታዳጊ ደረጃ ወርደው የሚሰሩ ክለቦች አለመኖራቸውነው የሚያሳስበኝ፡፡ በታዳጊ ደረጃመስራት ለነገው መሰረት መጣል ነው፡፡
በአጠቃላይ ክለቦች በሴቶች እግር ኳስ ታዳጊ ቡድኖችንም አቋቁመው ለመስራት መትጋት ይኖርባቸዋል፡፡ ከዚህ በተጨማሪ በፕሪሚዬር ሊጉ ተወዳዳሪ በሆኑ ክለቦች ለሴት ተጨዋቾች ተመጣጣኝ ደሞዝ የሚከፈልበት አሰራር መፈጠር ይኖርበታል፡፡ በእርግጥ በታዳጊዎች ላይ መስራት ብቻን መፍትሄ ላይሆን ይችላል፡፡ ከፕሪሚዬር ሊጉ ባሻገር የታዳጊ ውድድሮች ያፈልጋሉ፤ በስልጠና የሚሰሩ ብቁ ባለሙያዎችም ሊኖሩ ግድ ይላል፡፡ ለምሳሌ ባለሙያዎችንም ማብቃት የፌደሬሽኑ ስራ መሆን አለበት፤ ለምሳሌ እግር ኳስን ያቆሙ የቀድሞ ሴት ተጨዋቾች በየቤታቸው ተቀምጠዋል እነሱን ወደ ስልጠናው መስክ ለማስገባት የሚያስችሉ የአቅም ግንባታ ስልጠናዎች መፈጠር አለባቸው፡፡ ከዚያቀጥሎ ክለቦች ብቁ ባለሙያዎችን ይዘው የታዳጊ ቡድኖችን መስርተው መንቀሳቀስ ሲጀምሩ ውድድሮችን ለመፍጠር እና ለማካሄድ ብዙ የሚቸግር አይሆንም፡፡
በግሌ እምነት በሴቶችእግር ኳስ  በሁሉም ክለቦች ያሉት እንቅስቃሴዎች የሚያበረታቱ ቢሆንም በደደቢት እና በንግድ ባንክ ክለቦች እንዲሁም በዳሸን ያሉ ተግባራት እንደ ተምሳሌት ሊጠቀሱ የሚችል ነው፡፡ በእነዚህ ክለቦች ለሴት ተጨዋቾች ከወንዶቹ እኩል በቂ ትኩረት እየተሰጠ ነው፡፡ ተመጣጣኝ የደሞዝ ክፍያም እየተገበሩ ናቸው፡፡ በትጥቅ አቅርቦት፤ በአስተዳደር ትኩረት፤ በደሞዝ መሻሻሎች መኖርአለባቸው። እነዚህን አሰራሮች ሌሎች አንጋፋ ክለቦችም መከተል አለባቸው፡፡

ከዕለታት አንድ ቀን አንድ አዕምሮውን ነካ ያደርገዋል የሚባል ሰው ቀን በጠራራ ፀሐይ ወደ አንድ የስልክ እንጨት (ምሰሶ) ይሄዳል፡፡ ከዚያም እንደ ስልከኛ ምሰሶው ላይ እግሩን አጠላልፎ መውጣት ይጀምራል፡፡
ሰው ምን ሊያደርግ ነው እያለ ዙሪያውን መክበብ ጀመረ፡፡ ዙሪያውን የከበበውን ሰው ያየ መንገደኛ ሁሉ ወደ ስብስቡ ተቀላቀለ፡፡ የሁሉም ሰው ጥያቄ፤
“ምን ሊያደርግ ይሆን?” የሚል ሆነ፡፡
ሰውየው መውጣቱን ቀጠለ፡፡ ህዝቡም መሰብሰቡን ቀጠለ፡፡
ከፊሉ - “ይሄ ሰውዬ ጫፍ ከደረሰ በኋላ ሊወረወር ነው፡፡ በጊዜ እናስወርደው” አለ፡፡
ከፊሉ - “ለማንኛውም ፖሊስ ብንጠራ ይሻላል”
ሌላው - “ፖሊስ ቢመጣ ምን ሊያደርግ ይችላል፡፡ በገመድ አይጠልፈው”
ሌላው - “ግዴላችሁም አንድ ሰው ተከትሎት ይውጣ”
“ተከትሎት ወጥቶ በእርግጫ ቢለውስ ዕብድ አይደለ እንዴ?”
“እባችሁ ምንም አይሆን፤ ዝም ብለን የሚያደርገውን እንይ”
“ለምን አንጠይቀውም?”
“ምን ብለን ልንጠይቀው ነው፤ እኛ ቴሌ ኮሙኒኬሽን አደለን”
“ለምን ለሚመለከተው መስሪያ ቤት አንነግርም”
“መሥሪያ ቤቱ ንብረቴ ነው ካለ እራሱ ይምጣ እንጂ እኛ ምን ቤት ነን?”
ዕብዱ ሰው መውጣቱን ቀጠለና ጫፍ ደረሰ፡፡
ቀጠለና ከኪሱ እስክሪቢቶና ወረቀት አወጣ፡፡
ታች ያለው ሰው ግምቱን አወጋ-
“ይሄዋ ኑዛዜውን እየፃፈ ነው”
“ዕብድ ደሞ ምን ኑዛዜ ይኖረዋል?”
“ምን ይታወቃል? ሰውኮ ሊሞት ሲል የሚናገረው ነገር ይበዛል”
“እባክህ፤ መንግሥትን ሊሳደብ ይሆናል”
“መንግሥት ለመሳደብ ምሰሶ ጫፍ ላይ መውጣት አለብህ እንዴ?”
ዕብዱ ሰው ጽሑፉን ጨረሰ፡፡ በፕላስተር ምሰሶው ጫፍ ላይ ለጠፈው፡፡
እየተንሸራተተ ወደ መሬት ወረደ፡፡
ታች ከተሰበሰበው ህዝብ አንዱ፤
“ምን ብለህ ጽፈህ ነው የለጠፍከው?” አለና ጠየቀው፡፡
ዕብዱ ሰውም
“ወጥቶ ማየት ነዋ!” ብሎ ሄደ፡፡
ከህዝቡ ማህል አንደኛው፤
“ወጥተን እንየው እንጂ” አለ፡፡
ሁሉም “አንድ ሰው ይውጣ” አለ፡፡
አንድ ጐበዝ ከማህል ወደ ስልክ እንጨቱ ሄደ፡፡
ሁሉ ሰው አበረታታው፡፡ “ጐበዝ ውጣ!” “ቀጥል ጀግናው!” “ይሄ ነው ወንድ!” “ግፋ!”
ሰውየው እግሩን እየሳበ ወጣ ወጣና ጫፍ ደረሰ፡፡ ወረቀቱ ላይ የተፃፈውን አየ፡፡
ታች የለው ህዝብ “አንብብልን!” ብሎ ጮኸ፡፡
ጐበዙ ሰው ጮክ ብሎ አንበበው፤
“የምሰሶው ጫፍ እዚህ ጋ ነው!”
*   *   *
ማንኛውም ሰው ህዝብን እንዳሻው ለመንዳት ከቻለ ሀገር ላይ ችግር አለ፡፡ ያ ሰው ዕብድ ከሆነ ደግሞ የባሰ ችግር አለ፡፡ አሳሳቢ ሆነ ማለት ነው፡፡ ጥርጣሬ ላይ የወደቀ ህዝብ ይዋልላል፡፡ በመንግሥት፣ በተቋማትና በማህበራት ላይ ዕምነት አይኖረውም፡፡ ዕምነት ያጣ ህዝብ ከመምራት ዕምነት የለው የልቡን የሚናገር ተቃዋሚ ህዝብ መምራት ይሻላል ይላሉ ፀሐፍት፡፡
ኢትዮጵያን በተለየ መንገድ ለማሳደግ ህዝብ በአጭበርባሪዎች እንዳይታለል ተቆጣጥሮ ህጋዊነትን ማስከበር ያሻል፡፡ ህዝብ ሙሉ ዕምነት ሊኖረው ያስፈልጋል፡፡
ተቋማቱን አስተማማኝና እርግጠኛ ፍቃደ ልቡና ይለግሳቸው ዘንድ እንዳይመዘበር፣ እንዳይበዘበዝ ጥበቃ ሊደረግለት ይገባል፡፡ ለዚህም የአስተሳሰብ ብልጽግና፣ የግንዛቤ ጥራት፣ የልብ ለልብ መግባባትና የመቻቻል ምንነት በግልጽ የገባው ሊሆን ያሻል፡፡ ከጦርነት ይልቅ ሰላምን የሚመርጥበት ምክንያት ከልምድ ከተማረው በተጨማሪ ወቅታዊ ንቃት እንዲኖረው ያስፈልጋል፡፡
ሙስናን ለመቋቋም እየሰጋን መሆን የለበትም፡፡ መታሠር ያለበት ህገ ወጥ ሰው ከሆነ የፍርድ ቤት ጉዳይ እንጂ የእከሌ ከእከሌ አማራጭ መፍጠር ወይም “አጥፊው ስለበዛ እንተወው” መፍትሔ አይሆንም፡፡ ሁሉም የየድርሻውን ማግኘቱ የፍትሕን መጉላትና መጠንከርን እንደሚያሳይ አለመዘንጋት ነው፡፡ በተለይ በህዝብ ላብ የሚቀልድ ማንም ይሁን ማን ሊተው አይገባም፡፡ በተለይም በልዩ መዋቅር ተሳስሮ ጀርባው ደንደን ያለውን መተው፣ ኮሳሳውን ማጥቃት ለፍትሕ ጐጂ ባህል ነወ፡፡ ይህን የሚያስከብሩ ተቋማት መጠንከር አለባቸው። ይህም ሲባል ተቋማቱ ግዑዝ አይደሉምና የሚመሯቸው ሰዎች በሚሠሩት አምነውና ጠንክረው ይጓዙ ማለታችን ነው፡፡
አበሻ አደባባይ ያምናል፡፡ ለአበሻ ሚዲያ መንግሥት ነው፡፡ ስለሆነም ለማናቸውም ሚዲያ ተጠቃሚ ተአማኒ ነው፡፡ ሚዲያ ላይ የቀረበ፤ አንድም መንግሥታዊ ነው፣ አንድም የታመነ ነው!  ቴሌቪዥን አይቶ፣ ሬዲዮ ሰምቶ የማያውቅ ሰው እንኳ ቢሆን በቴሌቪዥን ታየ፣ በሬዲዮ ተነገረ ካሉት የዕምነቱን ዣንጥላ ይዘረጋል፡፡ በአደባባይ የታየው፣ የተሰማው ነገር ህጋዊ ነው እንደማለት ነው! የዛሬ ዘመን የ “ቢዝነስ” ሁኔታ የደራሲ አቤ ጉበኛን “ጐብላንድ አጭበርባሪው ጦጣን” የሚያስታውሰን ነው፡፡ ለነገሩ የተመዘበረው ብር ብዛት ሲታይ እሰው እጅ ያለው ገንዘብ ኤሎሄ ያሰኛል፣ እንደ ልብ ደረቅ ቼክ መፃፍ፣ ባንክ ውስጥ በቂ ገንዘብ የለውም መባል፤ የወትሮ ነገር ሆኗል፡፡ ዲቪ የደረሰው ቀርቶ ያልደረሰው ይሄዳል በሚባልበት፣ ኮንዶምኒየም የደረሰው ቀርቶ ያልደረሰው ይኖርበታል በሚባልበት፣ ፖለቲካው ግራ ሲያጋባንና የምሁርነት ጥልቀት እያደር እንደ ውሃችን ቱቦ ሲደፈን
“እንተኛም ካላችሁ፣ እንገንደሰው
መኝታ እንደሆነ ቀርቷል ካንድ ሰው”
የሚል ዘፈን በምናቀነቅንበት ሀገር፤ ፖለቲካ ሁሉ የመሬት ጉዳይ ቢሆን ብዙ የሚያስደምም ሁኔታ አይሆንም፡፡ ጠቅላይ ሚኒስትራችን ለምሁራን ታዳሚዎች እንዳሉት፤ “እኛም እናንተም ችግር አለብን፡፡…ህብረተሰቡም እልከኛ ነው”…ይህንን የችግር ሶስት ማዕዘን (Triangular problem) መቼ እንደምንገላገለው ማሰብ ይጠበቅብናል፡፡
ችግሩ ባለቤት እንጂ ሁልቆ መሣፍርት የለውም፡፡ ዘርዝሮ ማየት እንጂ ችግር አለብን ብቻ መፍትሔ አይሆነንም፡፡ “የኤሊት ግሩፕ ቱጃር እየፈጠርን መጓዝ አንችልም” ያሉት ግን ሊሰመርበት የሚገባ ሀቅ ነው፡፡ “የመላዕክት ስብስብ አይደለንም” ያሉትም ሌላው ሀቅ ነው፡፡
በተደጋጋሚ የምናሰማው እሮሮ መጠነ ሰፊ ሆኗል፡፡ ሙስና አጠጠ፣ ት/ቤቶች ጥራት የላቸውም፡፡ መሠረተ - ጤና እንደምንፈልገው አልተስፋፋም፡፡ ተቋማት ይቋቋማሉ እንጂ አፈፃፀም የላቸውም፡፡ ባንኮች ንፅህናቸው አልተፈተሸም የከፍተኛ አመራሩ ችግር አለበት፡፡ ከፖለቲካ ልዩነት፤ ከሃይማኖት ልዩነት፣ ከዘር ልዩነት ነፃ ነን እንበል እንጂ ጣጣው አልለቀቀንም፡፡ “ሃጢያቱ ከተደጋጋመ ፅድቅ ይመስላል” ይሏልና፣ ቆም ብለን ተግባር ላይ እናተኩር!!




Saturday, 26 March 2016 11:01

የዘላለም ጥግ

(ስለ መምህራን)
• ግሩም መምህር ተስፋን ሊያነቃቃ፣ ፈጠራን
ሊያቀጣጥል፣ የመማር ፍቅርን ሊያሰርፅ
ይችላል፡፡
ብራድ ሄነሪ
• ጐበዝ አስተማሪ እንደ ጐበዝ አዝናኝ፣
በመጀመሪያ የአድማጮቹን ትኩረት መያዝ
አለበት፤ ከዚያ በኋላ ትምህርቱን ማስተማር
ይችላል፡፡
ጆን ሄንሪክ ክላርክ
• ትምህርት ለህይወት ስኬት ቁልፍ ነው፤
መምህራን በተማሪዎቻቸው ህይወት ውስጥ
ዘላቂ ተፅዕኖን ይፈጥራሉ፡፡
ሰሎሞን ኦርቲዝ
• የዘመናዊ መምህር ተግባር ደኖችን መቁረጥ
አይደለም፤ በረሃውን በመስኖ ማጥገብ እንጂ፡፡
ሲ. ኤስ. ሌዊስ
• ከመምህራን እገዛን ልታገኙ ትችላላችሁ፤ ነገር
ግን በራሳችሁ ብዙ መማር አለባችሁ፤ በባዶ
ክፍል ውስጥ ብቻችሁን በመቀመጥ፡፡
ዶ/ር ሴዩስ
• ጆሮ ከሰጣችሁት ሁሉም ሰው አስተማሪ ነው፡፡
ዶሪስ ሮበርትስ
• ግሩም መምህር ቁርጠኛ ሰው ነው፡፡
ጊልበርት ሂግሄት
• እንዴት ማሰብ እንዳለባቸው የሚያውቁ፣
አስተማሪ አያስፈልጋቸውም፡፡
ማሃትማ ጋንዲ
• ትክክለኞቹን መካሪዎችና መምህራን
በትክክለኛው ጊዜ በማግኘቴ ዕድለኛ ነበርኩ፡፡
ዴምስ ሌቪን
• የተዋወቅኋቸው፣ አብረውኝ የሰሩ ወይም
ታሪካቸውን ያነበብኩላቸው ሰዎች ሁሉ በአንድ
ወይም በሌላ መንገድ አስተማሪዎቹ ነበሩ፡፡
ሎሬታ ያንግ
• ስኬት ቀሽም አስተማሪ ነው፡፡ ብልህ ሰዎች
አንሸነፍም ብለው እንዲያስቡ ያማልላል፡፡
ቢል ጌትስ
• ልዩነት የሚፈጥረው መምህሩ እንጂ መማሪያ
ክፍሉ አይደለም፡፡
ማይክል ሞርፑርጐ

     የርሃብ ተጎጂ ለሆኑ ዜጎች ከውጭ አገራት የተገዛ 450 ሺህ ሜትሪክ ቶን የእርዳታ ስንዴ በጅቡቲ ወደብ በተፈጠረ የመርከቦች መጨናነቅና ወረፋ ሳቢያ በወቅቱ ወደ አገር ውስጥ ገብቶ ለተረጂዎች ሊከፋፈል አለመቻሉን ብሉምበርግ ዘገበ፡፡
ኢትዮጵያ ከውጭ አገራት የምትገዛው ስንዴ መጠን እያደገ መምጣቱን ተከትሎ በጅቡቲ ወደብ ከፍተኛ መጨናነቅ ተፈጥሯል ያለው ዘገባው፣ የእርዳታ እህሉን የጫኑ አስር ያህል መርከቦች ጭነታቸውን ለማራገፍ ወረፋ እየጠበቁ እንደሚገኙ ከጅቡቲ ወደብ አስተዳደር ያገኘውን መረጃ ጠቅሶ ገልጧል፡፡
“ሴቭ ዘ ችልድረን” የእርዳታ እህሉን ከመርከቦቹ ለማራገፍ 40 ቀናት ያህል ጊዜ ይፈጃል ማለቱን የጠቆመው ዘገባው፣ በኢትዮጵያ የ“ሴቭ ዘ ችልድረን” ዳይሬክተር ጆን ግርሃምም፣ የእርዳታ እህል የጫኑ በርካታ መርከቦች በጅቡቲ ወደብ ወረፋ እየጠበቁ እንደሚገኙና እህሉን ለማራገፍ በቂ ሁኔታዎች አለመመቻቸታቸውን እንደተናገሩ አስረድቷል፡፡
የኢትዮጵያ መንግስትም በጅቡቲ ወደብ መጨናነቅ መኖሩን አምኖ፣ ለማዳበሪያና ለስንዴ ቅድሚያ ተሰጥቶ የማራገፍ ስራው እየተከናወነ እንደሚገኝ መግለፁን ዘገባው አመልክቷል፡፡

     የተከለከለ አበረታች ንጥረ ነገር ተጠቅማለች በሚል ባለፈው ነሃሴ ወር ላይ ከውድድር እንድትታገድ የተወሰነባት ትውልደ ኢትዮጵያዊቷ አትሌት ኢቫን አቢይ ለገሰ  ውሳኔው የተላለፈብኝ ያለአግባብ ነው በሚል አለማቀፉን የአትሌቲክስ ፌዴሬሽኞች ማህበር መክሰሷን ሲኤንኤን ዘገበ፡፡
ለቱርክ የምትሮጠው አትሌቷ እ.ኤ.አ በ2005 እና 2007 በተከናወኑት የአለም ሻምፒዎናዎች በተደረጉላት የሽንት ምርመራዎች የተከለከለ ንጥረ ነገር መገኘቱን ተከትሎ፣ በቱርክ የአትሌቲክስ ፌዴሬሽን ከውድድር መታገዷን ያስታወሰው ዘገባው፣ በምርመራዎቹ ላይ የቴክኒክ ስህተቶች ተፈጽመዋል በሚል በሞናኮ የአስተዳደራዊ ፍርድ ቤት ክስ መመስረቷን ጠቁሟል፡፡
የአትሌቷ ወኪል ኦንዴር ኦዝባይለን በበኩላቸው፤ በአለማቀፉ የጸረ አበረታች እጽ ተቋም እውቅና በተሰጠው አንድ የምርመራ ላቦራቶሪ ውስጥ የሚሰሩ ባለሙያ በጉዳዩ ዙሪያ የሰጧቸውን መረጃዎች መሰረት በማድረግ፣ ክሱን እንደመሰረቱና በምርመራው ወቅት ዘጠኝ ያህል የቴክኒክ ስህተቶች መፈጸማቸውን አናዶሉ ኤጀንሲ ለተባለ የዜና ወኪል ተናግረዋል፡፡ ፍርድ ቤቱ ጉዳዩን መርምሮ ስህተቶቹ መፈጸማቸውን ካረጋገጠ፣ የአለማቀፉ የአትሌቲክስ ፌዴሬሽኖች ማህበር በአትሊቷ ላይ ያሳለፋቸው ውሳኔዎች ውድቅ እንደሚደረጉም ወኪሉ ገልጸዋል።
አትሌቷ ባለፈው አመት የተባለውን አበረታች ንጥረ ነገር አለመጠቀሟንና እንዲህ አይነት ህገወጥ ተግባር ለመፈጸም አስባ እንደማታውቅ መናገሯን የጠቆመው ዘገባው፣ ኦሳካ ላይ በተካሄደው የ2007 የአለም ሻምፒዮና በአስር ሺህ ሜትር ውድድር የብር ሜዳሊያ ማግኘቷንም አስታውሷል፡፡

     የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት ስራ አስኪያጅ ሊቀ ማእምራን የማነ ዘመንፈስ ቅዱስ ለልጃቸው ሕክምና
የገንዘብ ርዳታ የወሰኑላቸውን የእንጦጦ ኪዳነ ምሕረት ገዳም 10 የአስተዳደር ኮሚቴ አባላትን
ከሥራና ከደሞዝ ያገዱ ቢሆንም ፓትርያርኩ እግዱን ሽረውታል፡፡ ሥራ አስኪያጁ፣ “ለታማሚ ልጃቸው ማሳከሚያ” በሚል ገንዘብ በማሠባሰብ ላይ እንደነበሩ መዘገቡ የሚታወስ ሲሆን፤ ከእንጦጦ ኪዳነ ምህረት ገዳም ብቻ ግማሽ ሚሊዮን ብር በገዳሙ አስተዳደር ኮሚቴ እንዲሰጣቸው ቢወስንም፤ የገዳሙ ሒሳብ ሹም ክፍያውን አልፈጽምም በማለታቸው ውዝግብ ተፈጥሮ እንደነበር ይታወቃል፡፡ ከትላንት በስቲያ በሥራ አስኪያጁ  እግድ ተላልፎባቸው ከነበሩት የአስተዳደር ኮሚቴ አባላት አንዱ፣ ሥራ አስኪያጁ በፅ/ቤታቸው ጠርተዋቸው ሁሉንም የአስተዳደር አካላት “ስሜን ለማስጠፋት ሆን ብላችሁ ሳላዛችሁ የሰራችሁት ነው፤” በሚል ቃለ ጉባኤውን በቃለ ጉባኤ ካልሻራችሁ፤” በሚል ሁሉንም ማገዳቸውን እንዳሳወቋቸው ለአዲስ አድማስ አስረድተዋል፡፡ “ሥራ አስኪያጁ እገዳውን ካስተላለፉብን በኋላ የታገድንበትን ደብዳቤና የገንዘብ ርዳታውን የወሰንበትን ቃለ ጉባኤ ይዘን ቅዱስ ፓትርያርኩ ጋር በመግባት አስረዳናቸው፤” ያሉት የአስተዳደር ኮሚቴው አባላት፤ በሌሎች አድባራትና ገዳማት እንደተደረገው ሁሉ እርዳታውን የሰጡት ለዚሁ ዓላማ ተዋቅሮ በተላከ ኮሚቴ በተጠየቁት መሠረት መሆኑን ለፓትርያርኩ ማሳወቃቸውን
ገልጸዋል፡፡ አቤቱታውን ያዳመጡት ፓትርያርኩ፤ የሀገረ ስብከቱን ሥራ አስኪያጅና የገንዘብ ርዳታ የወሰኑትን አቤቱታ አቅራቢዎች ገሥጸው፣ የሥራ አስኪያጁን እገዳ በማንሳት የገዳሙ የአስተዳደር ኮሚቴ
አባላት ወደ መደበኛ ሥራቸው እንዲመለሱ ለሀገረ ስብከቱ ጽ/ቤት በላኩት ደብዳቤ ማዘዛቸው
ታውቋል፡፡  

      በኢትዮጵያዊቷ የሙዚቃ ቀማሪና የክላሲካል ፒያኖ ተጫዋች እማሆይ ጽጌ ማርያም ገብሩ የህይወት ታሪክና የሙዚቃ ስራዎች ዙሪያ የሚያጠነጥን አዲስ ፊልም እየተሰራ እንደሚገኝ “ኪክስታርተር” የተባለው ድረገጽ ዘገበ፡፡ በእማሆይ ጽጌ ማርያም የሙዚቃ ፋውንዴሽን እየተሰራ የሚገኘው ይህ ፊልም፣ የ93 አመት የዕድሜ ባለፀጋዋን ያላቸውን የሙዚቀኛ የህይወት ጉዞ የሚያስቃኝ ሲሆን በሙዚቃው ዘርፍ ያላቸውን ተሞክሮና የሙያ ስኬት የሚዳስስ ነው ተብሏል፡፡
በአሁኑ ወቅት በእየሩሳሌም በሚገኝ ገዳም ውስጥ የሚኖሩትን የእማሆይ ጽጌ ማርያም ገብሩን ታሪክ የሚተርከው የዚህ ፊልም የቅድመ ፕሮዳክሽን ስራ መከናወኑን የገለጸው ድረገጹ፤ የፕሮዳክሽን ስራውም በቅርቡ በእየሩሳሌምና ሙዚቀኛዋ በኖሩባቸው የኢትዮጵያ የተለያዩ አካባቢዎች እንደሚካሄድ ገልጿል፡፡
የፊልሙ የድህረ ፕሮዳክሽን ስራ በመጪው ሃምሌ ወር ላይ እንደሚጀመር የተነገረ ሲሆን፣ ፊልሙን በተሳካ ሁኔታ ሰርቶ ለእይታ ለማብቃት ፋውንዴሽኑ ለለጋሾችና ለአጋሮች የገንዘብ እርዳታ ጥሪ ማስተላለፉንም ድረገጹ ባወጣው ዘገባ አስረድቷል፡፡

የሰሜን ጐንደር ዞን አሣ አስጋሪዎችና ነጋዴዎች ወደ ሱዳን የደረቀ የአሣ ቋንጣ እየላኩ ሲሆን በዘንድሮ አመት በ6 ወር ጊዜ ውስጥ ከ12 ሚሊዮን ብር በላይ ገቢ ማግኘታቸው ታውቋል፡፡
አሣ አስጋሪዎቹና ነጋዴዎቹ ከጣና ሃይቅ የሚያሰግሩት እርጥብ አሣ በአካባቢው ባለው የገበያ ችግር ውሎ ሲያድር ይበላሽባቸው እንደነበር ገልፀው ለሱዳን ገበያ አሣውን አድርቀው በቋንጣ መልክ ማቅረብ መጀመራቸው ከኪሣራ አላቆ ትርፍ በትርፍ እንዳደረጋቸው ገልፀዋል፡፡
በሰሜን ጐንደር ዞን በጣቁሣ ወረዳ ዶልጊ ከተማ የሚገኙት አስጋሪዎችና ነጋዴዎቹ ምርታቸው በሱዳን ገበያ በእጅጉ ተፈላጊ እየሆነ መምጣቱን ጠቁመዋል፡፡
ወደ 200 የሚሆኑት አስጋሪዎቹና ነጋዴዎቹ በግማሽ አመቱ 4 መቶ ሺህ ኪሎ ግራም የአሣ ቋንጣ አዘጋጅተው በመተማ በኩል ለሱዳን ማቅረባቸውም ከመንግስት ኮሙኒኬሽን ጉዳዮች ጽ/ቤት የተገኘው መረጃ ጠቁሟል፡፡  

Saturday, 19 March 2016 11:19

የዘላለም ጥግ

(ይቅርታ ስለመጠየቅ)
- ይቅርታ መ ጠየቅ ግ ሩም ነ ው፤ ነ ገር ግ ን ም ንም
የሚለውጠው ነገር የለም፡፡ ለውጥ የሚያመጣው
ምን እንደሆነ ታውቃላችሁ? ተግባር!
ስቴላ ያንግ
- ደስታ ለሚሰጥህ ማንኛውም ነገር ፈፅሞ ይቅርታ
መጠየቅ የለብህም፡፡
ጄሲ ጄ.
- ተኝተህ እንኳን እኔን ለማሸነፍ አልመህ ከሆነ፣
ተነስተህ ይቅርታ ብትጠይቅ ይሻልሃል፡፡
ሙሃመድ አሊ
- ለማስፈራራት የሚሞክሩ ሰዎችን ይቅርታ
አልጠይቅም፡፡
ኪንኪ ፍሪድማን
- ስህተት ስሰራ ይቅርታ እጠይቃለሁ፡፡
ዶናልድ ትረምፕ
- ለቀልድ ይቅርታ አንጠይቅም፡፡ እኛ ኮማኪዎች
ነን፡፡ እዚህ ያለነው እናንተን ለማሳቅ ነው፡፡ ቀልዱ
የማይገባችሁ ከሆነ አትመልከቱን፡፡
ጆአን ሪቨርስ
- ጌታው፤ ፈፅሞ ይቅርታ አትጠይቅ፤ የደካማነት
ምልክት ነው፡፡
ጆን ዋይኔ
- ይቅር ስትል ነፍስህን ነፃ ታደርጋለህ፤ ይቅርታ
ስትጠይቅ ግን ሁለት ነፍሶችን ነፃ ታወጣለህ፡፡
ዶናልድ ኤል ሂክስ
- ማንኛውም ጥሩ የይቅርታ ጥያቄ ሦስት ክፍሎች
አሉት፡- 1) ለተከሰተው አዝናለሁ 2) ጥፋቱ የእኔ
ነው 3) የተበላሸውን ለማስተካከል ምን ላደርግ
እችላለሁ፡፡
አብዛኛው ሰው ሦስተኛውን ክፍል ይዘነጋዋል፡፡
ምንጩ ያልታወቀ
- ደካማ ሰው ፈፅሞ ይቅርታ ማድረግ አይችልም፤
ይቅር ባይነት የጠንካራ ሰው ባህርይ ነው፡፡
The Fresh quotes
- ያልተጠየከውን ይቅርታ መቀበል ስትማር
ህይወት ቀላል ይሆናል፡፡
ሮበርት ብራውልት
- ደግመህ የምትፈፅመው ከሆነ ይቅርታ
አትጠይቅ።
ምንጩ ያልታወቀ
- በንግግሬ ለተቀ የሙኝ ሁሉ ልባዊ ይቅርታ
እጠይቃለሁ፡፡
ዊሊያም ቦይኪን