Administrator
በአርባ ምንጭ የ5 ኪሎ ሜትር የጎዳና ላይ ሩጫ ተካሄደ
19ኛው የብሔሮች፣ ብሔረሰቦችና ሕዝቦች ቀን በዓልን ምክንያት በማድረግ የ5 ኪሎ ሜትር ታላቅ ሩጫ በአርባምንጭ ከተማ ተካሂዷል፡፡
ሩጫው በህዝብ ተሳትፎና በክልሉ መንግሥት ድጋፍ እየተገነባ ለሚገኘው የአርባ ምንጭ ዓለም ዓቀፍ ስታዲየም ግንባታ ገቢ ለማሰባሰብ እንዲሁም በከተማው የሚከበረውን የብሔር፣ ብሔረሰቦችና ህዝቦች ቀን በዓልን አስመልክቶ የተዘጋጀ መሆኑ ተጠቅሷል፡፡
በጎዳና ላይ ሩጫው የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ርዕሰ መስተዳድር ጥላሁን ከበደን ጨምሮ ከፍተኛ የክልልና የዞን የሥራ ሃላፊዎች፣ ታዋቂው አትሌት ሙክታር ኢድሪስ፣ የ12ቱም ዞኖች ተወካዮች እንዲሁም ከ10 ሺህ በላይ የህብረተሰብ ክፍሎች መሳተፋቸውን የጋሞ ዞን ኮሙኒኬሽን መረጃ ያመላክታል፡፡
መነሻውንና መድረሻውን ጋሞ አደባባይ ባደረገው የጎዳና ላይ ሩጫ በወንዶች አትሌት መክሊት መኮንን አሸናፊ ሲሆን፤ አትሌት ሙሉቀን ታደለ 2ኛ፣ አትሌት ሳሙዔል አብርሃም 3ኛ በመሆን አጠናቀዋል።
በሴቶች አትሌት ህሊና ሚልኪያስ 1ኛ በመውጣት ስታሸንፍ አትሌት በፀሎት አረጋ 2ኛ፣ አትሌት ሀገር ምንአለ 3ኛ በመውጣት የተዘጋጀላቸውን ሽልማት ተቀብለዋል።
የፊታችን ቅዳሜ፤ ህዳር 28 ቀን በ5ኛው የወር ወንበር ዝግጅት እንጠብቃችኋለን።
"ነጻነት" የተሰኘ የሥዕል ኤግዚቢሽንና ጨረታ የፊታችን ሐሙስ ይካሄዳል
https://t.me/AdissAdmas
የዱር አበባ
የአፍሪካ የሥነ-ጥበብ ሴቶች ሽልማት የ2024 የመጨረሻ እጩዎች ይፋ ሆኑ
24 ተማሪዎች ኢትዮጵያን ወክለው በቻይና ይወዳደራሉ
“AI ENJOY” ውድድር ላይ ያሸነፉ የወርቅ ሜዳልያ ተሸለሙ
የኢትዮ-ሮቦቲክስ መስራችና ዋና ሥራ አስፈፃሚ አቶ ሰናይ መኮንን፤ በቅርቡ በቻይና በሚካሄደው ዓለማቀፍ የ”ኮዲንግ ስኪል ቻሌንጅ” ላይ 24 ተማሪዎች ኢትዮጵያን ወክለው እንደሚሳተፉ ተናገሩ።
ውድድሩ በየዓመቱ በቻይና እንደሚካሄድ ለአዲስ አድማስ የገለጹት አቶ ሰናይ፤ ዘንድሮም በሻንጋይ ከተማ ከዲሴምበር 14-16 ቀን 2024 ዓ.ም ለሦስት ቀናት እንደሚደረግ አመልክተዋል።
ለዚህም ኢትዮ ሮቦቲክስ ባለፈው ቅዳሜ የኢንጆይ ኤአይ አገር አቀፍ የመጨረሻ ውድድር አካሂዷል። በውድድሩ ላይም ቲም ናይል፣ ቲም አልፋ፣ ቲም ዊነርስ፣ ቲም ላየንስ፣ ቲም ኤግል፣ ቲም አቢሲኒያና ሌሎች ስያሳች የተሰጣቸው የታዳጊ ቡድኖች ተሳትፈዋል፡፡
አሸናፊዎችን ለመለየት በታዳጊ ቡድኖቹ መካከል እልህ አስጨራሽ ፍልሚያ የተካሄደ ሲሆን፤ የማታ ማታ የላቀ ብቃት ያሳዩ ተማሪዎች አሸንፈዋል። ታዳጊዎቹ ስፔስ ትራቭሊንግ፣ ጋላክቲክ ዲፌንስ ባትል እና ክሎዚንግ ሰረሞኒ ኦቭ ስፖርትስ በተሰኙ ዘርፎች ለሦስት ዙር ተወዳድረዋል፡፡
በመጨረሻም፣ ከየዘርፉ ከ1ኛ እስከ 3ኛ የወጡ አሸናፊዎች የወርቅ፣ የብርና የነሐስ ሜዳልያ እንዲሁም የምስክር ወረቀት ተሸልመዋል፡፡ የወርቅ ተሸላሚ የሆኑት ሦስት ቡድኖች የሚከተሉት ናቸው።
ቲም ኤግል -በ120 ነጥብ በክሎዚንግ ሰረሞኒ ኦቭ ስፖርትስ
ቲም ስፓርታ - በ630 ነጥብ በስፔስ ትራቭሊንግ ዘርፍ
ቲም ናይል - በ100 ነጥብ በጋላክቲክ ዲፌንስ ዘርፍ
ለአሸናፊዎቹ የወርቅ ሜዳልያ የሸለሙት የቴክኖሎጂና ኢኖቬሽን ሚኒስትሩ ተወካይ አቶ ሰላምይሁን አደፍርስ ባደረጉት ንግግር፤ ኢትዮ ሮቦቲክስ ከወትሮው ውድድር በተለየ የኤአይ እና ዲጂታል ስኪል አቀላቅሎ መምጣቱን አድንቀው፤ የድርጅቱ መሥራች አቶ ሰናይ ዘርፉን ለማሳደግ በየጊዜው እያደረገ ስላለው ጥረት አመስግነዋል፡፡
አክለውም፤ ውድድሩ ሰፋ ብሎ እንዲካሄድና ተደራሽ ይሆን ዘንድ የሚኒስቴር መ/ቤታቸው ለኢትዮ ሮቦቲክስ የሚያደርገውን እገዛና ድጋፍ አጠናክሮ እንደሚቀጥል ቃል ገብተዋል፡፡
የኢትዮ ሮቦቲክስ መሥራች አቶ ሰናይ፤ በቅርቡ በቻይና የሚደረገውን የኮዲንግ ስኬል ቻሌንጅ አስመልክቶ በሰጡት ማብራሪያ፤ በእስካሁኑ ተሞክሮአችን ቻይናውያኑ ታዳጊዎች የተሻለ ልምድ ያላቸው በመሆኑ፤ በየዓመቱ ውድድሩን በአንደኝነት ነው የሚያጠናቅቁት ብለዋል፡፡
እንዲያም ሆኖ ታዳጊ ኢትዮያውያን ከዓመት ዓመት ቁጥራቸውን በመጨመርና ደረጃቸውን በማሻሻል በዓለማቀፍ ውድድሮች ላይ ኢትዮጵያን እያስጠሩ ነው- ብለዋል። የዲጂታል ኢትዮጵያ ተስፋዎችም እንደዚህ ዓይነቶቹ ታዳጊዎች መሆናቸውን ጨምረው ገልፀዋል።
የሪል እስቴትና የቤት ኤክስፖ ይከፈታል
7ኛው ዓመታዊ የሪል እስቴትና የቤት ኤክስፖ ታህሳስ 18 ቀን 2017 ዓ.ም በሸራተን አዲስ ሆቴል ይከፈታል፡፡ ለሦስት ቀናት የሚቆየው ኤክስፖው ከፍተኛ አልሚዎችን፣ ባለሀብቶችን፣ የፋይናንስ ተቋማትን፣ የቤት ገንቢዎችንና የቤተ ውበት ባለሙያዎችን ጨምሮ፣ የሪል እስቴትና የኮንስትራክሽን ኢንዱስትሪውን ከፍተኛ ባለድርሻ አካላት በአንድ ላይ እንደሚያሰባስብ ተነግሯል፡፡
የ251 ኮሙዩኒኬሽንና ማርኬቲንግ መሥራች አቶ አዲስ አለማየሁ እንደተናገሩት፤ የዘንድሮው ኤክስፖ በኢትዮጵያ ሪል እስቴት ዘርፍ ትልቅ ፋይዳ ያለው ክስተት ሲሆን፤ በኢንዱስትሪው ውስጥ ከፍተኛ ተደማጭነት ያላቸውን ተዋናዮች ያሰባስባል። አቶ አዲስ አክለውም፤ “ዘላቂ ልማትን፣ ፈጠራንና ኢንቨስትመንትን የሚያበረታታ መስተጋብራዊ መድረክ በመፍጠር የዘርፉን እድገት ለመደገፍ ቁርጠኛ ነን።” ብለዋል፡፡
ኤክስፖው በሪል እስቴት ዘርፍ ውስጥ ያሉ አዳዲስ እድገቶችን፣ ፈጠራዎችንና የኢንቨስትመንት እድሎችን ለማሳየት ያለመ ሲሆን፤ በኢንዱስትሪ መሪዎች መካከል ትስስርና ትብብርን ይፈጥራል ተብሏል።
በ7ኛው አመታዊ ሪል እስቴትና የቤት ኤክስፖ ላይ ከኤግዚቢሽኑ በተጨማሪ በኢንዱስትሪው ላይ ከሚገኙ ዋና ባለድርሻ አካላትና ከመንግስት ተወካዮች ጋር የመገናኘት እድል የሚፈጠር ሲሆን፤ የፓናል ውይይትም እንደሚደረግ ተጠቁሟል፡፡
የመጀመሪያው የቡና ፌስቲቫል ዛሬ በሸራተን ተከፈተ
10 ታዋቂ የቡና አምራች ኩባንያዎች ይሳተፋሉ
ለኢትዮጵያ የመጀመሪያው ነው የተባለለት የቡና ፌስቲቫል (ኮፊ ፌስት) ዛሬና ነገ እሁድ በሸራተን አዲስ ሆቴል ፋውንቴይኑ አካባቢ እንደሚካሄድ ተገለጸ፡፡ በፌስቲቫሉ ላይ አሥር የሚደርሱ ታዋቂ የቡና አምራችና ላኪ ኩባንያዎች ይሳተፉሉ፡፡
የቡና አምራች ኩባንያዎቹ የተለያዩ ዓይነት የቡና ምርቶቻቸውን የሚያቀርቡ ሲሆን፤ ለኤክስፖርት የተዘጋጁ የቡና ምርቶችን ጨምሮ ለሸያጭ ይቀርባሉ ተብሏል፡፡ የቡና ቀመሳ ሥነስርዓትም ይካሄዳል፡፡
ለሁለት ቀናት የሚካሄደውን የመጀመሪያውን የቡና ፌስቲቫል አስመልክቶ የኹነቱ ጠንሳሾችና አዘጋጆች ከትላንት በስቲያ ሐሙስ በሸራተን አዲስ ሆቴል ጋዜጣዊ መግለጫ ሰጥተዋል፡፡ ከፌስቲቫሉ ግንባር ቀደም ስፖንሰሮች አንዱ የሖነው የሸራተን አዲስ ዋና ሥራ አስኪያጅ - በመግለጫው ላይ የተገኙ ሲሆን፤ በኢትዮጵያ የመጀመሪያው የቡና ፌስቲቫል በሆቴሉ መዘጋጀቱ ልዩ ደስታና ጉጉት እንደፈጠረባቸው ገልጸዋል፡፡
የኢትዮጵያ ቡና ፌስቲቫል አስፈላጊነትን ያብራሩት አዘጋጆቹ፤የኢትዮጵያን ቡና በሚገባው ልክ ለማክበርና ለማጉላት ነው ብለዋል፡፡ ”እኛ ኮፊ ፌስትን እንደ በዓል ነው የምንቆጥረው፤ቡናችንን የምናከብርበትና የምናጎላበት ታላቅ በዓል ነው፡፡” ሲሉም አስረድተዋል፡፡
እንደ ጀርመን ያሉ አገራት በኦክቶበር ፌስት (ዓመታዊ የቢራ ፌስቲቫል) እንደሚታወቁ የጠቀሱት አዘጋጆቹ፤ ኢትዮጵያም በቡና ፌስቲቫል (ኮፊ ፌስት) መታወቅ አለባት ብለው እንደሚያምኑ ተናግረዋል፡፡
የወቅቱ ጥቅስ
ያሸነፍን ሲመስለን መሸነፍን እንረሳለን
የተሸነፍን እንደሆነ
ማሸነፍ የኛም አይመስለንም
ሁለቱ መካከል ግን
አንድ አዲስ ልጅ እንወልዳለን፡፡› (የአገሬ ገጣሚ)
በሲቪል ድርጅቶች ላይ የተጣሉ ዕገዳዎች አሳሳቢ እንደሆኑ ተገለጸ
“እገዳው ከባድ ጫና እየመጣ መሆኑን ጠቋሚ ነው”
ለሰሞኑ በ3 የሲቪል ማህበረሰብድርጅቶች ላይ የተጣለው ዕገዳ ከሲቪል ማሕበረሰብ ዓዋጅ ያፈነገጠ መሆኑ እንደሚያሳስብ “ቅድሚያ ለሰብዓዊ መብቶች” የተሰኘው ተቋም ገልጿል። ተቋሙ እንደገለጸው፤ ሕጉ በሚያዘው መሰረት ብቻ መርምሮ ለታገዱት የሲቪል ድርጅቶች ተገቢ መፍትሔ እንዲሰጣቸው ጠይቋል።
ቅድሚያ ለሰብዓዊ መብቶች ባለፈው ሐሙስ ሕዳር 19 ቀን 2017 ዓ.ም. ባወጣው መግለጫ፤ የሲቪል ማሕበረሰብ ድርጅቶች ባለስልጣን፤ በመብቶችና ዴሞክራሲ ዕድገት ማዕከል (ካርድ)፣ የሕግ ባለሞያዎች ለሰብዓዊ መብቶች እና በስብስብ ለሰብዓዊ መብቶች በኢትዮጵያ በተባሉት ድርጅቶች ላይ የተጣሉ ዕገዳዎች የሲቪል ማሕበረሰብ እንቅስቃሴ “የሚያቀጭጩ ናቸው” ሲል ስጋቱን ገልጿል። በሲቪል ማሕበረሰብ ድርጅቶች ዓዋጅ መሰረት፤ ዓዋጁን እና ሌሎች ሕጎችን ለሚጠቀሱ ድርጅቶች ባለስልጣኑ በጽሑፍ ማስጠንቀቂያ እንደሚሰጥ፣ እንዲህም ባለስልጣኑ በሲቪል ድርጅቶች ላይ ምርመራ በሚያካሂድበት ወቅት ከባድ የሕግ ጥሰት መፈጸሙን ሲያረጋግጥ፣ ጊዜያዊ ዕግድ ሊጥል እንደሚችል መደንገጉን አብራርቷል።
ይሁን እንጂ በታገዱ ድርጅቶች ላይ በዓዋጁ መሰረት ቢሮ ድረስ በመምጣት ባለስልጣኑ ክትትል አለማድረጉን ማስጠንቀቂያ አለመስጠቱን፣ እንዲሁም ምንም ዓይነት ምርመራ አለመጀመሩንና “አስተካክሉ” የተባሉበት መነሻ ሳይኖር፣ ቀጥታ እግድ መጣሉን “ቅድሚያ ለሰብዓዊ መብቶች” ለመረዳት መቻሉን አትቷል። “መንግስት ዓዋጁን ሳይከተሉ የሚወሰዱ እርምጃዎች ለሲቪል ማሕበረሰብ እንቅስቃሴ እጅግ የሚጎዳና የሚያቀጭጭ መሆኑን ተረድቶ፣ ጉዳዩን ሕጉ በሚያዘው መሰረት ብቻ መርምሮ ተገቢ መፍትሔ እንዲሰጣቸውና ወደፊትም ተገቢ ጥንቃቄ እንዲደረግ እንጠይቃለን” ሲል ጥሪ አቅርቧል።
የ”ቅድሚያ ለሰብዓዊ መብቶች” ዋና ሃላፊ አቶ ተስፋዓለም በርሄ ለአዲስ አድማስ ሲናገሩ፣ “በእነርሱ ላይ የተጣለው ዕገዳ ለእኛም የማይመጣበት ምክንያት የለም” ብለዋል። አያይዘውም፣ ተቋማቸው መርህን መሰረት በማድረግ በሦስቱ የሲቪል ድርጅቶች ላይ የተጣሉትን ዕገዳዎች መቃወሙን አስታውቀዋል።
“የሲቪል ማሕበረሰብ ድርጅቶች ዓዋጅ መሻሻልን ተከትሎ፣ በሲቪል ድርጅቶች በኩል ጥሩ እንቅስቃሴ ሲደረግና ዕንቅስቃሴያቸውም ሲስፋፋ ነበር” ያሉት አቶ ተስፋዓለም፣ “አሁን ግን ፖለቲካዊ ጫናዎች እየመጡ፣ ብዙ የሲቪል ድርጅት መሪዎች ከአገር ወጥተዋል” ሲሉ ተናግረዋል። በሶስቱም ሲቪል ድርጅቶች ላይ የተጣለው ዕገዳ ከባድ የሆነ ጫና እየመጣ መሆኑንና የመንቀሳቀሻ ምህዳሩ እየጠበበ መምጣቱን የሚያሳይ ነው ሲሉም ስጋታቸውን አጋርተዋል።
ይህ በእንዲህ እንዳለ፤ የሲቪል ማህበረሰብ ድርጅቶች ባለስልጣን ከሰሞኑ ዕገዳ በተላለፈባቸው ሦስት የሲቪል ማህበረሰብ ድርጅቶች ላይ በአጭር ጊዜ ውስጥ የመጨረሻ ውሳኔ እንደሚያስተላልፍ አስታወቋል። ከሲቪል ማህበረሰብ ድርጅቶች ጋር በተያያዘ በሚፈጠሩ አንዳንድ ክስተቶች ምክንያት የሲቪል ምህዳሩ “ጠብቧል” ብሎ መደምደም ተገቢ አለመሆኑን የባለስልጣኑ ምክትል ዋና ዳይሬክተር አቶ ፋሲካው ሞላ በዕገዳው ዙሪያ በሰጡት ጋዜጣዊ መግለጫ ተናግረዋል።