Administrator
Tuesday, 09 September 2025 07:01
ኢትዮጵያ ህዳሴን ለገደበችበት ካሳ መጠየቅ እንዳለባት ተገለጸ
የህዳሴው ግድብ ግንባታ ጠቃሚነቱ በተለይ ለታችኛዎቹ ተፋሰስ ሀገራት በመሆኑ ኢትዮጵያ በራሷ ፋይናንስ ግድቡን ለገደበችበት ካሳ መጠየቅ አለባት ሲሉ ኢንጂነር ጥላሁን ኤርዲኖ (ዶ/ር) ገለጹ፡፡
በአፍሪካ ቀንድና በመካከለኛው ምስራቅ የሃይድሮ ፖለቲካ ተንታኝ ኢንጂነር ጥላሁን ኤርዲኖ፤ ለኢፕድ እንደገለጹት፤ ከግድቡ ግብጽና ሱዳን ከፍተኛ ተጠቃሚ በመሆናቸው ኢትዮጵያ ግድቡን ለብቻዋ መገደብ አልነበረባትም።
የህዳሴ ግድብ ከሌሎች ጥቅሞቹ ባሻገር ግብጽ ውስጥ በከፍተኛ ትነት የሚባክን ውሃን አስቀርቷል ያሉት ኢንጂነር ጥላሁን፤ በዚህም በቀጠናው ተጨማሪ የውሃ ሀብት እንዲኖር ማስቻሉን ጠቁመዋል፡፡
እንደ ኢንጂነር ጥላሁን ገለጻ፤ ግድቡ መገንባቱ የታችኛው ተፋሰስ ሀገራት የሚደርስባቸውን አደጋ ማስቀረት ችሏል፤ ለአብነትም ጎርፍና የመሳሰሉትን ማንሳት ተገቢ ነው፡፡ በዚህም በዓመት ከሦስት እስከ አራት ጊዜ ያለምንም አደጋ ማምረት እንዲችሉ እድል ፈጥሯል፡፡
ግድቡ ከዚህ በተጨማሪም የተለያዩ ኢኮኖሚያዊ ጠቀሜታዎች እንዳሉት የጠቆሙ ሲሆን፤ ሀገራቱ አሁንም የዓባይ ተፋሰስ እንዲለማ ድጋፍ ማድረግ እንዳለባቸው አብራርተዋል፡፡
ኢትዮጵያ ውስጥ ውሃ ሲጨምር ሌሎች ሀገራት ላይ መጨመሩ የግድ መሆኑን የገለጹት ኢንጂነር ጥላሁን ኤርዲኖ፤ ህዳሴ በትነት የሚባክነውን ውሃ የሚቀንስ በመሆኑ በድርቅ ጊዜ ለቀጠናው ከፍተኛ እፎይታ የሚፈጥር ነው ብለዋል፡፡

Published in
ዜና
Tagged under
Tuesday, 09 September 2025 06:59
የረዳን ፈጣሪ አምላክ ይመስገን !!
መላዉ ኢትዮዽያዊን በሙሉ እንኳን ደስ አለን!!
የፅናታቻን ፣ የላባችን ፣ የደማችን ፣ የጥረታችን ዉጤት ፣ የዘመናት ቁጭታችን መደምደሚያ ፣ የብልፅግናችን መሰረት ፣ የአይበገሬነታችን ምልክት ለሆነዉ የታላቁ ህዳሴ ግድባችን ምረቃ እንኳን አደረሰን!!
ባንድነት ስንቆምና ስንተባበር የማችለዉም የለም !!
ፈጣሪ ኢትዮዽያና ህዝቦቿን ይባርክ
-ከንቲባ አዳነች አቤቤ-
የቴሌግራም ቻናልችንን በመቀላቀል የአዲስ አድማስን መረጃ ይከታተሉ…


Published in
ዜና
Tagged under
Tuesday, 09 September 2025 06:58
የህዳሴ ዋዜማ በድሮኖችና በጀልባዎች ትርኢት
የህዳሴ ዋዜማ በእግር ጉዞ፣ በድሮንና በጀልባዎች ትርኢት፣ በባሎንና በሰርከስ ሥራዎች ተጀምሮ እየተካሄደ ነው።
የታላቁ ህዳሴ ግድብ የምረቃ የዋዜማ ዝግጅት በዚያው በጉባ እየተካሄደ ይገኛል።
በምረቃ ዋዜማ ዝግጅቱ ላይ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድን ጨምሮ፣ ቀዳማዊ እመቤት ዝናሽ ታያቸው፣ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር አቶ ተመስገን ጥሩነህ፣ የቀድሞ ጠቅላይ ሚኒስትር አቶ ሃይለማርያም ደሳለኝ እንዲሁም ሌሎች የመንግስት የስራ ሃላፊዎች ተገኝተዋል።
በግድቡ መመረቂያ ዋዜማ ላይ የድሮኖች ትርኢት፣ የተለያዩ የሰርከስ፣ የመብራትና የጀልባ ትርኢቶች እየተካሄዱ ነው።
ቀደም ሲልም በግድቡ አናት ላይ የ1 ነጥብ 8 ኪሎ ሜትር የእግር ጉዞ መደረጉም ተዘግቧል፡፡
የቴሌግራም ቻናልችንን በመቀላቀል የአዲስ አድማስን መረጃ ይከታተሉ…





Published in
ዜና
Tagged under
Tuesday, 09 September 2025 06:56
የህዳሴው ግድብ ምርቃት ዋዜማ ላይ
የህዳሴው ግድብ ምርቃት ዋዜማ ላይ
የቴሌግራም ቻናልችንን በመቀላቀል የአዲስ አድማስን መረጃ ይከታተሉ…
Published in
ዜና
Tagged under
Tuesday, 09 September 2025 06:55
የሕዳሴ ግድብ ምረቃን በነፃ ኢንተርኔት ይከታተሉ
የታላቁ የኢትዮጵያን ሕዳሴ ግድብ መጠናቀቅ የድል ብስራት፣ በቀጥታ ስርጭት በነፃ ይከታተሉ ሲል ኢትዮ ቴሌኮም ብስራት አሰምቷል።
የዓመታት ሕልማችን በይፋ ዕውን የሚሆንበት ታላቅ ታሪካዊ የድል ብስራት፣ ነገ ዻጉሜ 4 ቀን 2017 ዓ.ም ከኢንተርኔት ክፍያ ነፃ በቀጥታ ስርጭት በኢቢሲ ይከታተሉ።
የቴሌግራም ቻናልችንን በመቀላቀል የአዲስ አድማስን መረጃ ይከታተሉ…
Published in
ዜና
Tagged under
Tuesday, 09 September 2025 06:47
ለህዳሴ ግድቡ 260 ሚ.ብር ያሰባሰቡት - ጊዜሽወርቅ ተሰማ
የኢትዮጵያ ታላቁ የህዳሴ ግድብ ሲነሳ መዘንጋት የሌለባቸው አንዲት ኢትዮጵያዊ እንስት አሉ - ወ/ሮ ጊዜሽወርቅ ተሰማ፡፡
በኢትዮጵያ በግሉ ዘርፍ በስራ ፈጠራና በንግዱ ዓለም በስኬታማነታቸው የሚታወቁ ባለሃብት ናቸው፡፡
በሀገራዊ የልማት ሥራዎች ላይ ትልቅ ተሳትፎ ያላቸው ወ/ሮ ጊዜሽወርቅ፤ ለታላቁ ሕዳሴ ግድብ ስኬት በቅንጅት የሚሰራውና "ትስስር ለሕዳሴ ግድብ" የተሰኘው ጥምረት መሥራች ናቸው፡፡
ስለግድቡ ግንዛቤን ለማሳደግ፣ በተበታተነ መልኩ የሚሰሩ ሥራዎችን ለማቀናጀትና ስለ ግድቡ ያለውን እውነታ ለዓለም ማህበረሰብ ለማስረዳት የሚንቀሳቀሰው ጥምረቱ፤ በአገር ውስጥና በውጭ ያሉ ምሁራን፣ የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ኃላፊዎች እንዲሁም የንግዱ ማህበረሰብ አባላት የሚሳተፉበት ነው።
ዲጂታል ቴክኖሎጂን በመጠቀም ስለ ታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ ስኬት የሚሰራ ጥምረት እንዲመሰረት ለዓመታት ሲሞግቱ የነበሩት ወ/ሮ ጊዜሽወርቅ፣ ጥምረቱ በ2013 ሲመሰረት፤ "የግድቡ ግንባታ በአሁኑ ወቅት ወሳኝ ምዕራፍ ላይ በመድረሱ፤ በተለይ ወጣቱ ቴክኖሎጂን በመጠቀም ኢትዮጵያን ማገዝ አለበት፤ ልክ እንደሠራዊቱ በበይነ መረብ የአገሬን ሉዓላዊነት አላስነካም ማለት አለበት" ሲሉ ተናግረዋል።
ወ/ሮ ጊዜሽወርቅ ተሰማ "ትስስር ለሕዳሴ ግድብ" የተሰኘውን ጥምረት መመሥረት ብቻ ሳይሆን በጥምረቱ ውስጥ የሀብት ማሰባሰብ ሥራውን በዋናነት መርተዋል፡፡
ወ/ሮ ጊዜሽወርቅ ከዚህ ቀደም ለታላቁ ህዳሴ ግድብ ከግሉ ዘርፍ 260 ሚሊዮን ብር አሰባስበው ለሕዳሴ ግድብ ሕዝባዊ ተሳትፎ ማስተባበሪያ ብሔራዊ ም/ቤት ገቢ በማድረግ ለሀገራቸውን ያላቸውን ፍቅር አስመስክረዋል።
በታላቁ የህዳሴ ግድብ የምረቃ በዓል ዋዜማ ላይ ሆነን እኒህን ሃገር ወዳድ እንስት ያነሳነውም ለሃገራቸው ላከናወኑት ትልቅ ተግባር በጥቂቱም ቢሆን መመስገንና መታወስ ስላለባቸው ነው፡፡
እንኳን ለታላቁ የኢትዮጵያ የህዳሴ ግድብ
መጠናቀቅና ምርቃት በሰላም አደረሰን!!
የቴሌግራም ቻናልችንን በመቀላቀል የአዲስ አድማስን መረጃ ይከታተሉ…
Published in
ዜና
Tagged under
Monday, 08 September 2025 07:46
"ሪፖርተር" 30 ዓመት የታመነ የመረጃ ምንጫችን
ሁሉም ነገር አንጻራዊ ነው። የ "ሪፖርተር" ጋዜጣ ለ30 ዓመት የታመነ የመረጃ ምንጭነትም እንዲሁ አንጻራዊ ይሆናል። እና በበኩሌ ላለፉት 30 ዓመታት በሪፖርተር ጋዜጣ ልክ መሐል ቆሞ መረጃን በታማኝነት የሚያከፋፍል የሚዲያ ተቋም አላውቅም። በመሐል ታይተው የጠፉ እንደ " አዲስ ነገር " ያሉ ጋዜጦች ይኖራሉ። እነሱ ቢኖሩም ቁጥራቸው ጥቂት ፣ እድሜያቸውም አጭር ነው።
የሪፖርተር መስራችና ማኔጂንግ ኤዲተር አቶ አማረ አረጋዊ ከሕወሓት ነባር ታጋዮች መሐል አንዱ የነበረ ነው። ያም ሆኖ ስለ ሕወሓት የጓዳ ምሥጢሮች ሳይቀር የምንሰማው ከሪፖርተር ነበር ፤ ነው። በቂ አልሆነ ይሆናል። አንጻራዊ ነው ብለናል። በሀገሪቱም ሆነ አቶ አማረ በታገለለት ሕወሓት አንኳር ጉዳዮች ላይ " በሚዛናዊነት " ሪፖርተር የሰጠንን ማንም አልሰጠንም።
ሕይወታችን ስላደረግነው አይታወቀን ይሆናል እንጂ እጅግ የምንበዛው በፖለቲካ፣ በብሔር ፣ በሀይማኖት ፣ በአስተሳሰብ ጽንፈኞች ነን። እንደ ሕዝብም የዴሞክራሲ ልምምድ የለንም። ከለመድነው መውጣት ፣ ከምንፈልገው በተቃራኒ የሆነን መስማት ልምምዱ የለንም። እኛ የሪፖርተር ጋዜጣ ወሳኝ ሰው ብንሆን ከምናደርገው አቶ አማረ አረጋዊ ብዙ ርቆ ሄዷል።
አቶ አማረ አረጋዊ ጣፋጩን የወጣትነት ክሬሙን ጊዜ የሰጠው ሕወሓት ለሚመራው ትግል ነው። ይሁንና በሕወሓት ክፍፍል ጊዜ ( አሁንም በአንጻራዊ መልኩ ) የሁለቱንም ጎራ ሀሳቦች በእኩልነት የምናነበው ከሪፖርተር ነበረ። አምነን የምናነበው ሪፖርተርን ነበረ። በምርጫ 97 ወቅት ሁሉም ብዙሀን መገናኛ ለሁለት የተከፈለበትና እንደ ዘመነ ቀይ/ነጭ ሽብር " ከኢሕአዴግ ወይም ከተቃዋሚዎች " የተባለበት ጊዜ ነበረ። መሐል ለመሆን የሚሞክር " ወያኔ " የሚባል ታፔላ የሚለጠፍበት ጊዜ ነበረ። ዜና ሲሰራም ትንሽ ተቃዋሚዎችን ከነካ ወይም መንግሥትን ( ሕግን ) የደገፈ ከመሰለ " የመንግሥት ዜና " የሚባልበትና በራሱ በፕሬሱ የሚዘመትበት ጊዜ ነበረ። ዋንኛው የቀድሞ " ወያኔ " አቶ አማረ የሚያሳትመው ሪፖርተር ጋዜጣ ነበረ የግራውንም ፣ የቀኙንም በእኩልነት (በመጠኑ ለተቃዋሚዎች ድምጽ እየሆነ ) ያቀርብ የነበረው።
የመንግሥትን አይነኬ ቦታዎች በመረጃና በማስረጃ ላይ ተመስርቶ የሚነካው ሪፖርተር ነው። ሪፖርተር ትላልቅ መረጃዎችንና ማስረጃዎችን ከ " ትላልቅ " ሰዎች ጭምር ማግኘቱ ብቻ ሳይሆን ያገኘውንም በአግባቡ የሚጠቀምበት ኃላፊነት የሚሰማው ጋዜጣ ነው። በወቅቱ በግሉ ፕሬስና በተቃዋሚዎች " ለወያኔ ያደላል " ሲባል በሕወሓት ሰዎች ደግሞ " እንደ ሌላው ፕሬስ ሁሉ ለተቃዋሚዎች ያደረና ኢሕአዴግን ለመጣል ከተባበሩት ጋር የወገነ " ተደርጎ ነበረ የሚቆጠረው። ይሁንና በኢሕአዴግም ሆነ በተቃዋሚዎቹ " ታምኖ " የሚነበበውም ሪፖርተር ጋዜጣ ነበረ። " ሪፖርተር ምን አለ ? " የሚባል ነው። ይሄ ጋዜጣ ነው በህትመት ላይ እያለ 30 ዓመት የደፈነው።
አቶ አማረ አረጋዊ በአንድ በኩል በሌላው ዘንድ " ወያኔ " እየተባለ፣ በ " ወያኔዎቹ " ዘንድ ደግሞ በተቃዋሚነት ተፈርጆ እስከማውቀው ድረስ " ትግራይ አይረግጥም " የተባለ ( እንደሰማሁት ) ሰው ነበር። በሕወሓት ሰዎች ዘንድ " የእኛ " የማይባል ሰው እንደነበረ አውቃለሁ። ከአቶ መለስ ዜናዊም ፣ ከደህንነት ሹሙ ክንፈ ገ/መድህንም ጋር ግንኙነት ያለው ሆኖም በአቶ አማረ አረጋዊ ቦታ ላይ መገኘት ትልቅ የሞራል ድፍረትን የሚጠይቅ ነው። በባለስልጣን መጨበጥ ስንቱን አቅልጦ እንዳስቀረው አይተናል። የአቶ አማረ የለውጥ ሰውነት በሪፖርተር ጋዜጣ ላይ የመጣ ሳይሆን ከዚያ ቀደም ብሎም የነበረ ነው።
ጋዜጠኛ ዘካሪያስ ኃ/ማርያም ( ነፍስ ይማር ) በአንድ ወቅት የነገረኝን ላስታውስ። አቶ መለስ ዜናዊ በለውጡ ዓመታት አካባቢ የዘመን መለወጫ ለመላው የኢትዮጵያ ሕዝብ የእንኳን አደረሳችሁ ንግግር ያደርጋሉ። በወቅቱ የኢትዮጵያ ቴሌቪዥን የዋዜማ የመዝናኛ ዝግጅቶች በርከት ያሉ ነበርና የፕሮግራም መጣበብ ያጋጥማል። ከፕሮግራሞቹ አንዱ ደግሞ ምሽቱን የሚተላለፈው የአቶ መለስ ዜናዊ የእንኳን አደረሳችሁ መልዕክት ነው። ይህን ያየው የቴሌቪዥን ጣቢያው ስራ አስኪያጅ አቶ አማረ የወሰነው የአቶ መለስን ንግግር ቀንሶ በማግስቱ እንዲተላለፍ ማድረግ ነበር። " ' ይሄ ነገም ቢተላለፍ ችግር አያመጣም ፤ዛሬ በዓል ስለሆነ ሕዝቡ ይዝናናበት ' አለን" ነው ያለኝ።
ሪፖርተር " እንከን የለሽ " ጋዜጣ ነው እያልኩ አይደለም። የሰውም ፣ የአሰራርም ፣ የአመራርም ስህተቶች ይኖሩበታል። ይህ ያለና የሚጠበቅ ነው። የምናወራው ስለ ፍጽምና አይደለም። ፍጽምናም የለም። በእኔ እምነት ከ1984 በኋላ በዚህ ሀገር ከመጡ የግል ይሁን የመንግሥት ብዙሀን መገናኛዎች በሪፖርተር ልክ ለፕሬስ ነጻነት የቆመ ፣ የመንግሥትን እንከን ያሳየ ፣ ቱባ ባለስልጣናትን በመረጃ የደፈረ ፣ ብልሹ አሰራሮችን በድፍረትና በመረጃ የተጋፈጠ አለ ማለት አልደፍርም። ይህን ሀሳብ ብዙዎች ላይቀበሉት እንደሚችሉ አስባለሁ። ይሁንና እነዚያ ሰዎች ይህን ሁሉ ከሪፖርተር በተሻለ ያደረገ ማንንም አይጠሩም። የታመነ የዜና ምንጭ የሆነ ፣ ለበርካታ ዜጎች የስራ ዕድል የፈጠረ ፣ ራሱ አቶ አማረ መርካቶ ወስዶ በነጻ ጭምር ይሰጠው ከነበረው የጳጉሜ 6/1987 ዕትም ጀምሮ እስከ ዛሬ ጳጉሜ 2/2017 በጽናት የዘለቀው አንጋፋውና ብቸኛው የግል ጋዜጣ "ሪፖርተር" እንኳን ለ30ኛ ዓመትህ አደረሰህ።
-ቴዎድሮስ ተ/አረጋይ-
የቴሌግራም ቻናልችንን በመቀላቀል የአዲስ አድማስን መረጃ ይከታተሉ…



Published in
ህብረተሰብ
Tagged under
Monday, 08 September 2025 07:31
ጣና ነሸ ፪ ጣና ሐይቅ ላይ መንሳፈፍ ጀመረች
ለአገልግሎት ዝግጁ የሆነችው ጣና ነሸ ፪ ጀልባ ጣና ሐይቅ ላይ መንሳፈፍ ጀመረች።
ጣና ነሸ ፪ ጀልባ በጣና ሐይቅ የትራንስፖርት አገልግሎት ከመስጠት በተጨማሪም የቱሪዝሙን ዘርፍ የበለጠ ታጠናክራለች ተብሎ ይጠበቃል።
የቴሌግራም ቻናልችንን በመቀላቀል የአዲስ አድማስን መረጃ ይከታተሉ…



Published in
ዜና
Tagged under
Monday, 08 September 2025 07:30
ሚኒስትሯ በአንጋፋው ድምጻዊ መኖሪያ ቤት ተገኙ
በህብር ቀን የአዲስ አመት መባቻን ምክንያት በማድረግ፣ የባህልና ስፖርት ሚኒስትር ሸዊት ሻንካ፣ አንጋፋው ድምጻዊ መሀሙድ አህመድ መኖሪያ ቤት በመገኘት እንኳን አደረሳችሁ ብለዋል።
"ታላላቆችን ማክበር፣ መጠየቅ፣ መርዳትና መንከባከብ ነባር ባህላዊ ዕሴቶቻችን ናቸው። በዓላትን ማብሰርና ማክበር አንዱ ተልዕኮው የሆነው ሚኒስቴሩ፣ ይህንን ማስቀጠልና ከትውልድ ወደ ትውልድ ማስተላለፍ የሚቀጥል ስራ ነው" ያሉት ሚኒስትሯ፤ ጋሽ መሀሙድ ቤት በአካል ተገኝተው እንኳን አደረሳችሁ ማለታቸውና ያላቸውን ክብር መግለፃቸው እንዳስደሰታቸው ገልፀዋል።
የባህልና ስፖርት ሚኒስትር ደኤታ ረ/ፕ ነብዩ ባዬ በበኩላቸው፤ "ጋሼ ለዛውና ቃናው የማይጠገብ ለሰላም የቆመ አርበኛ፤ለሀገርና ለህዝብ መቆምንና ሀገር መውደድን ኖሮ ያሳየ ድንቅ የጥበብ ንጉስ ነው" ሲሉ ተናግረዋል፡፡
አንጋፋው ድምጻዊ መሀሙድ አህመድ፤ "በዛሬው ቀን ሰለተሰጠኝ ክብር የተሰማኝ ደስታ ይህ ነው አልለውም ፤እድሜ ነው የጨመርኩት። ወጣቶች፣ አድናቂዎቼና አዲሱ ትውልድ ለህዝብ ምን ባቀርብ ነው የሚቀበለኝ በማለት ሊሰራ ይገባዋል" ብለዋል።
ድምጻዊው፤ አዲሱ ትውልድ ሀገሩንና ህዝቡን የሚያስቀድም ሰላም ወዳድ እንዲሆን መልዕክት በማስተላለፍ፤ አዲሱ ዓመት የሰላም፣ የፍቅር፣ የአንድነትና የፍሰሀ ዘመን እንዲሆን መልካም ምኞቱን አስተላልፏል፡፡
የቴሌግራም ቻናልችንን በመቀላቀል የአዲስ አድማስን መረጃ ይከታተሉ…





Published in
ዜና
Tagged under
