በደራሲ ሚካኤል ይበይን እና ዳይሬክተር ኤልያስ ወርቅነህ የተሰራው "የኛ ቤተሰብ" የቤተሰብ ኮሜዲ ፊልም ባለፈው ረቡዕ በብሔራዊ ትያትር በልዩ ፕሮግራም ተመረቀ፡፡ ፊልሙ እሁድ እለት በአዲስ አበባና በክልል ከተሞች የግል ሲኒማ ቤቶች እንደተመረቀም ለማወቅ ተችሏል፡፡ ጋላክሲ ፊልም ፕሮዳክሽን ለአዲስ አድማስ በላኩት መግለጫ፤ ፊልሙን ሰርቶ ለማጠናቀቅ አራት ወር እንደፈጀና ከ350ሺ ብር በላይ ወጪ እንደተደረገበት አስታውቋል፡፡
1 ሰዓት ከ30 ደቂቃ ርዝመት ባለው በዚህ ፊልም ላይ አበበ ወርቁ፣ ካሣሁን ፍስሃ (ማንዴላ)፣ ዳንኤል ገበየሁ፣ ወለላ አሰፋ እና ሌሎችም ወጣትና አንጋፋ ተዋንያኖች ተውነውበታል፡፡