Friday, 18 January 2013 00:00

የአፍሪካ የእግር ኳስ ዋንጫ እንደ ድርሰትና ድራማ

Written by 
Rate this item
(2 votes)

የስፖርት ውድድርና የኪነጥበብ ዋጋ - በአየን ራንድ ፍልስፍና

ሕይወቱን የሚያፈቅር ሰው፣ ለሦስት ነገሮች ከሁሉም የላቀ ትልቅ ክብር መስጠት እንደሚገባው አየን ራንድ ስተምራለች። ከሁሉም የላቁ የተባሉት ሦስቱ እሴቶች እኚሁና፡ እውነታን አንጥሮ የሚገነዘብ የአእምሮ አስተውሎት (Reason)፣ የሕይወት አላማ (Purpose)፣ በራስ ብቃት መተማመን (selfesteem)። የኪነጥበብ ዋጋ እጅጉን  ልቅ የሆነው፤ እነዚህ እሴቶች ጎልተውና ጠርተው፣ በተጨባጭ ተቀርፀውና እውን ሆነው እንድናያቸው የሚያደርግ

ምናባዊ አለም ለመፍጠር ስለሚያስችል ነው። ሶስቱ የኪነጥበብ መሰረታዊ ባህርያትም፣ ከመሰረታዊዎቹ ሦስት እሴቶች ጋር (ከትኩረት፣ ከአላማ እና ከብቃት ጋር) የተሳሰሩ ናቸው። የኪነጥበብ ባሕርያት ከስፖርት ባሕርያት ጋር ምን ያህል እንደሚመሳሰሉ ተመልከቱ። 1. ኪነጥበብ፣ ዋና ዋና ቁም ነገሮችን ከትርኪምርኪ ለይቶና አጥርቶ ማሳየት ይችላል (selection and magnification)። ምርጥ የስፖርት ውድድር፤ በአላስፈላጊ ነገሮች ላይ ሳይሆን በዋና ዋና ነገሮች ላይ እንድናተኩር ያደርጋል። ስለ ተጫዋቾች ችሎታ እንጂ ስለ ዘመዶቹ ቁጥር ወይም ስለ ጥርሱ ብዛት አናወራም። በቀጥታ የሚተላለፈው ውድድር ላይ፤ ተጫዋቾች ተቀባብለውና አብዶ ሰርተው ሲያልፉ፣ ኳስ ሲመቱና ጎል ሲያስገቡ ነው ማየት የምፈልገው? ወይስ የሜዳው የሳር ቅጠል ስፋትና ርዝመት፤ የተጨዋቹ ገምባሌ ስፌትና የክር አይነት ለ90 ደቂቃ ማየት እንፈልጋለን? ዋና ዋና ቁም ነገሮቹ ናቸው ጎልተው የሚወጡት። ከገምባሌ ስፌት ይልቅ የጎሉን አገባብ ለይቶ ያሳየናል፤ ደጋግሞም እንድናየው ያቀርብልና - አጥርቶ አጉልቶ። (selection and magnification) 2. ኪነጥበብ፤ ብቃትን በተጨባጭ ስጋና ደም አልብሶና በአርአያነት ሊጠቀስ የሚችል ጀግናን ቀርፆ ማሳየት ይችላል (concretization and model building)። ምርጥ የስፖርት ውድድር፤ የሰውን ብቃት በእውን በተጨባጭ እንድናይ ያደርጋል። 3. ኪነጥበብ፤ የሩቁን አላማ በቅርበት እንድናጣጥመው የስኬት ጉዞውን አስተሳስሮ ማሳየት ይችላል (projection and recreation)። 

ምርጥ የስፖርት ውድድር፤ በትልቅና በከባድ አላማ እንዲሁ፤ በእልህ አስጨራሽ ትንቅንቅና ፉክክር ላይ የተመሰረ ነው - በዙር ጨዋታና በጥሎ ማለፍ ፉክክሩ ጦዞ በፍፃሜው ለዋንጫ ሲደረስ እናይበታለን። ምርጥ የስፖርት ውድድር እና ምርጥ ድራማ (ድርሰት) በጣም ተመሳሳይ ከመሆናቸው የተነሳ፤ ይዘታቸውም ይዛመዳል።

ገፀ ባሕርያትና ተጫዋቾች ስፖርታዊ ውድድር ደማቅና ማራኪ የሚሆንልን፤ በብቃት የገነኑና ከባድ አላማ የያዙ ተፎካካሪ ተጫዋቾች የሚታዩበት ከሆነ ነው።

ድርሰትም ውብ እና መሳጭ የሚሆንልን፤ በጀግንነት የገነኑና ፈታኝ አላማ የያዙ ተቀናቃኝ ገፀባሕርያትን መቅረፅ ሲችል ነው። በግጭት እየጦዘ የሚሄድ የድርጊት ሰንሰለት (ሴራ) ምርጥ ስፖርታዊ ውድድር ቁጭ ብድግ

የሚያሰኘን፤ ተጫዋቾች በእያንዳንዷ ደቂቃ አላማቸው ላይ አነጣጥረው የሚጣጣሩበት ታሪክ ስለምናይበት ነው። አታልሎ ማለፍ፣ ጎል ማስገባት፣ ማሸነፍ፣ ዋንጫ መውሰድ... የተጫዋቾቹ ድርጊት በሙሉ፣ ፉክክሩና ጥሎ ማለፉ ሁሉ እርስ በርስ የተሳሰሩ ናቸው። በአላማ ላይ ያነጣጠረ የፍልሚያ፣ የግጭት፣ የፉክክር መርሃ ግብር የምርጥ ስፖርታዊ ውድድር መለያ ነው - በግብግብ እየጦዘ የሚሄድ የውድድር ሰንሰለት (ሴራ) ልንለው እንችላለን።

ምርጥ ድርሰት ልብ ሰቅሎ የሚያጓጓን፤ ገፀባሕርያት በእያንዳንዷ ደቂቃ አላማቸው ላይ አተኩረው ሲታገሉ፣ ሲወጡና ሲወርዱ የሚያሳይ ታሪክ ስለሚያቀርብልን ነው። መውጪያ ወይም መግቢያ ቀዳዳ መፈለግ፣ ማምለጥ ወይም ማሳደድ፣ መያዝ ወይም ነፃ መውጣት... የገፀባሕርያቱ እንቅስቃሴ በሙሉ አላማን ለስኬት ለማብቃት

የሚደረግ ነው። ሁሉም ድርጊቶች የተሳሰሩ ናቸው - በአላማ ላይ ያነጣጠረ የትንቅንቅ፣ የግጭትና

የፉክክር ታሪክ ነው - በግጭት እየጦዘ የሚሄድ የድርጊት ሰንሰለት (ሴራ)። የአቀራረብ ዘይቤ (ስታይል)

የስፖርታዊ ውድድሮች አቀራረብ በአዘጋጆቹ መንፈስና ዝንባሌ ይለያይ የለ? በድርሰትም እንደዚያው ነው። የሁለት ድርሰቶች ታሪክ ተመሳሳይ ቢሆን እንኳ እንደደራሲዎቹ መንፈስ አቀራረባቸው ሊለያይ ይችላል። የአንዱ ደራሲ የአቀራረብ መንፈስ (ስታይል) እንደ አፍሪካ ዋንጫ በወግ የደበዘዘ በጥሬ ስሜት የተንዘፈዘፈ ይሆናል። የሌላኛው

ደራሲ ስታይ ደግሞ፣ እንደ አሜሪካ የቅርጫት ኳስ ዋንጫ ያሸበረቀና የተሽቀረቀረ ይሆናል። የአንዱ

ደራሲ፤ እንደ ጀርመኑ ቡንደስ ሊጋ ቆጠብ ደደር ያለ፤ የሌላኛው እንደ እንግሊዝ ፕሪሚዬር ሊግ የተጯጯኸና የተቀወጠ። ስፖርታዊ ወድድርና ድርሰት፣ ሌላ ተመሳሳይ ተፈጥሮ አላቸው። ሁለቱም፤ በቅጡ የሚታወቅ ጭብጥ (ጥቅል ሃሳብ) ሊኖራቸው ይገባል። ጭብጥ፡ የምን ጨዋታ የምን ድርሰት? ስለተጫዋቾችም ሆነ ስለ ዋንጫ፤ ስለ ጥሎ ማለፍም ሆነ ስለ ፉክክሩ ጡዘት፣ አልያም ስለውድድሩ የአቀራረብ መንፈስ መነጋገር የምንችለው፤ በቅድሚያ የውድድሩን ምንነት ስናውቅ ነው። በአጭሩ የውድድሩ ይዘት፣ ሂደትና

አቀራርብ፤ በውድድሩ ምንነት ላይ የተመሰረተ መሆን ይገባዋል። “የ2013 የአፍሪካ እግርኳስ ዋንጫ”፣ “የ2012 ኦሊምፒክ”፣ “የ2014 የአለምአትሌቲክስ ሻምፒዮና”፣ “የሰፈር ልጆች የእግር ኳስ ግጥሚያ”፣ “የባለስልጣናትና የነጋዴዎች የእግር ኳስ ጨዋታ”... እነዚህ ሁሉ አንድ አይነት ይዘት ወይም አቀራረብ ሊኖራቸው አይችልም። የውድድሩን ጭብጥ ለይተን በጥቅሉ ስናውቅ ነው፤ ምን አይነት ተጫዋቾችና ዋንጫ፣ ምን አይነት ትንቅንቅና

የውድድር መርሃ ግብር እንደሚኖር በአጠቃላይ የውድድሩ ይዘትና ሂደት ምን መምሰል እንዳለበት

መምረጥና መወሰን የሚቻለው። የውድድሩ ይዘት፤ ሂደትና አቀራረብ፤ በውድድሩ ጭብጥ ይወሰናል

ማለት ነው። የወዳጅነት ወይም የእርዳታ ማሰባሰቢያ ውድድርንና የአለም ዋንጫንና ኦሊምፒክን በአንድ አይነት መንፈስ ማቅረብ አይቻልም፤ ውድድሮቹና ተጫዋቾቹም ይለያያሉ።

 

በድርሰትም እንዲሁ፤ ገፀባሕርያቱንና አላማቸውን፣ ግጭቱንና ሴራውን ለመምረጥና ለመወሰን፣ በቅድሚያ ደራሲው በምን ዙሪያ ለመፃፍ እንደሚፈልግ ጭብጡን ለይቶ ማወቅ ይጠበቅበታል። ለምሳሌ የዴርቶጋዳ ጭብጥ፤ “በጥንታዊ መሰረት ላይ ለኢትዮጵያ ትንሳኤ የሚባትሉ ዜጎች” የሚል ነው። “የሰዎችን ህይወት የሚያሰናክልና የሚያዋርድ ኋላቀር ህብረተሰብ ውስጥ የሚኖሩ ሚስኪን ፍቅረኞች” ... ይሄ ደግሞ የፍቅር እስከ መቃብር ጭብጥ ነው። “ድሆችን የሚበድል ፍትህ የተጓደለበት ስርዓት ውስጥ የሚኖር ጀግና” ... ዘ ሚዘረብልስ የተሰኘ መፅሃፍ። “አገርን የሚዋጅና ፍትህን የሚፈፅሙ ጀብደኞች” ... ዘ ስሪ ማስከቲርስ። “ፍቅሩንና ነፃነቱን ተቀምቶ ፈተና ውስጥ የገባ ቅን ሰው” ... ዘ ፍዩጀቲቭ የተሰኘ ፊልም። የጭብጡ ስፋትም ሆነ ጥልቀት የደራሲው ምርጫ ነው። ቅልብጭ ያለ እና የሾለ ሊሆን ይችላል። የእውቀቱንና የአቅሙን ያህል የሚመጥን፣ የዝንባሌውንና የፍላጎቱን አዝማሚያ የሚጣጣም መሆን አለበት።

ከላይ እንደተጠቀሰው፤ የድርሰት ዋና አላባዊያን 1. ጭብጥ፣ 2. የገፀባሕርያት አሳሳል (አላማን ጨምሮ)፣ 3. ሴራ (ግጭትን ጨምሮ)፣ 4. የአቀራረብ ዘይቤ (ስታይል) ናቸው። በስፖርታዊ ውድድርም ውስጥ፤ አላባዊያኑ ተመሳሳይ ናቸው። እስቲ በገፀባሕርያት አሳሳልና በሴራ ላይ በማተኮር ተመሳሳይነታቸውን በደንብ ለመመልከት እንሞክር።

የገፀ ባሕርያት አሳሳል፡

ከ31 አመት በኋላ ወደ አፍሪካ ዋንጫ የተመለሰ፤ ባለፈው የአፍሪካ ዋንጫ የወሰደ፤ በማጣሪያው ያለፈ፤ በፕሮፌሽናል ተጫዋቾች የተገነባ፣ በውዝግብ የተበጠበጠ፤ በሽልማት ቃል የተገባለት፣ ብዙ ፈተና ያለበት ... የቡድን አወቃቀርና አመራር፣ የስፖርተኞች ብቃትና ዝግጅት፣ የአሰልጣኝ ብቃትና ዝግጅት ... ዋና ዋና ነገሮች ላይ ማተኮር። ለምሳሌ የፊዚክስ ሳይንቲስት፣ የአውሮፕላን ኢንጂነር፣ የአንጎል ሃኪም፣ የፋብሪካ ምርጥ ማኔጀር፣ የቢዝነስ ጥበበኛ፣ ምርጥ አልሞ ተኳሽ .... ላይ አናተኩርም። በዘመድ፣ በጓደኝነት፣ በጉቦ፣ በእጣ፣ በሃይማኖት ተከታይነት፣ በብሄረሰብ፣ ... አጓጉል ሃሳቦችን አናመጣም። በጉዳይህ ላይ ዋና ዋና ነገሮችን ለይቶ ማወቅና እነሱን በትኩረት ማስተዋል... የተዘበራረቀ፣ የተንሸዋረረ፣ የዘፈቀደ፣ የፈዘዘ፣ የደነዘዘ፣ የተደናበረ አስተሳሰብ እንዳይኖረን ያደርጋል።

የተወዳዳሪ ቡድኖች፣ የአሰልጣኞች፣ የተወዳዳሪዎች ... ማንነት፣ አላማ፣ ብቃት፣ አቅም፣ ዝንባሌ... የተወሰነ መረጃ “ከኤክስፖዚሽን” እናገኛለን። እንግዲህ የስፖርታዊ ውድድር ኤክስፖዚሽን የሚቀርበው፤ በማጣሪያ ውድድሮች ላይ፣ በዝግጅትና በልምምድ ወቅት፣ እንዲሁም በሚዲያ ዘገባዎች አማካኝነት ነው። የገፀባሕርያቱ ማንነት እየጎላ የሚመጣውና እየጠራ የሚታየን ግን... ታሪኩ ከጀመረ በኋላ ወይም በግጭት የተወጠረ የድርጊት ሰንሰለት ውስጥ (ሴራው ውስጥ) ነው። የተጨዋቾቹ ማንነትና ብቃት በግላጭ የምናየውም፤ ጨዋታው ከጀመረ በኋላ በትንቅንቅ የከረረ በውድድሩ ሂደት ውስጥ (በሴራው ሰንሰለት ውስጥ) ነው። ይሄኔ መሪውና ተቀናቃኝ ፍንትው ብለው ይወጣሉ። የገፀባሕርያቱ ልዩ መልክ ነጥሮ ይወጣል - ዋና መሪ ገፀባሕርይ፣ ዋና ተቀናቃኝ ገፀባሕርይ፣ ደጋፊ ገፀባሕርያት፣ እኩይ ገፀባሕርያት...

እንደ ጥሩ ድርሰት ሁሉ፤ ጥሩ ስፖርታዊ ውድድርም ቢያንስ ሁለት ጀግና ገፀባሕርያት (ጠንካራ ተፎካካሪዎች) ያስፈልጉታል። ነገር ግን፣ ጀግኖቹ እንደ የብቃታቸውና እንደ የዝንባሌያቸው፤ አላማቸውን ለማሳካት የሚመርጡት መንገድ ይለያያል። መጥፎ ነገር የመስራት አባዜ አልተጠናወታቸውም። ግን፤ አንዱ በፅናት ትክክለኛውን መንገድ የሚከተል፣ ሌላኛው ግን አንዳንዴ ወደ ስህተት ለመግባት የሚቃጣው ሊሆን ይችላል - ለምሳሌ ሰዓት ማባከንና ተጠለፍኩ ብሎ የውሸት መውደቅ። ቢሆንም፤ በጨዋታው ህግ እየተዳኙ የሚጫወቱ ናቸው። ሜዳ ውስጥ የገቡት፣ በሰዓት ማባከን ችሎታ ወይም ተጠለፍኩ ብሎ ዳኛ በማታለል ጥበባቸው አይደለም። የእግር ኳስ ብቃታቸውና ጥረታቸው ነው ዋናው ነገር። ዋና አላማቸውም ማታለልና ማሰናከር አይደለም። ዋና አላማቸው ተጫውቶ ማሸነፍ ነው። የተለያዩ ጉድለቶች ቢኖሯቸውም፣ በጥቅሉ ጀግኖች ናቸው። እንደየጉድለታቸው መጠንም ችግር ይገጥማቸዋል።

1. ዋናው መሪ ገፀባሕርይ (ፕሮታጎኒስት)፡ እንግዲህ በላቀ ብቃትና በጥሩ ጨዋታ እያሸነፈ ዋንጫ ለመውሰድ ቆርጦ የተነሳ ነው ዋናው መሪ ገፀባሕርይ። በምርጥ አጥቂዎች ላይ የተገነባ ቡድን ነው እንበል። (ከድርሰት አለም ውስጥ አንድ ሁለት ፕሮታጎኒስቶችን ብንጠቅስስ? ለምሳሌ የባንክ ዘራፊውን አሳድዶ ለመያዝ የሚፈልግ ፖሊስ፣ ወይም ፍቅረኛውን ከአጋቾች ለማዳን የሚፈልግ እጮኛ)

2. ዋናው ተቀናቃኝ ገፀባሕርይ (አንታጎኒስት)፡ የተወሰኑ ጉድለቶች እንዳሉት በማመን በመከላከል ላይ አተኩሮ ለማሸነፍ በእልህ የሚጫወት ቡድን ሊሆን ይችላል። (በድርሰቱ አለም ደግሞ፤ የባንክ ዘራፊውን ለመያዝ ግብረአበሮቹን ማግባባት አለብን የሚል ፖሊስ፤ አልያም ከአጋቾቹ ጋር በመደራደር ታጋቿን ለማስለቀቅ የሚጣጣር አባት...)

ተጨማሪ ገፀባህርያት

1. ደጋፊ ገፀባሕርያት፡ ዳኞች፣ አሰልጣኞች፣ ተመልካቾች፣ አድናቂዎች፣ ጋዜጠኞች፣ ሸላሚዎች...

2. እኩይ ገፀባሕርያት (ቪሌይን)፡ ተሳዳቢ ቲፎዞ፣ አድሏዊ ዳኛ፣ የሚያዛባ ጋዜጠኛ፣ የቁማር ማፊያ፣ በዘርና በአገር ተቧድኖ ውድድሩን የሚበጠብጥ ጋጠወጥ፣ ኳስ መጫወትም ሆነ ማየት የለባችሁም የሚል አክራሪ፣ ከኳስ ደስታ ይልቅ ለችግረኞች ሃዘኔታ ቅድሚያ እንስጥ የሚል ዘመነኛ ባህታዊ... ወዘተ

ጠንካራ ሴራ፡ የጀግኖች ግጭት

ሁለቱ ጀግና ገፀባሕርያት (በወኔ የታነፀው ፖሊስና ትእግስት የተላበሰው ባልደረባው) አላማቸው ተመሳሳይ ቢሆንም ተቀናቃኝ መሆናቸው አይቀርም። ሁለቱም ጀግኖች ስለሆኑም ግጭታቸው ጠንካራ ይሆናል - (የፍፃሜ ውድድር ላይ እንደሚገናኙ ተፎካካሪ ቡድኖች ማለት ነው)።

ለምሳሌ ዘ ሚዘረብልስ የተሰኘው የቪክቶር ሁጎን ድርሰት መጥቀስ ይቻላል። ዋናው ገፀባሕርይ ፍትሕ ለማግኘት የሚታትር ነው። ተቀናቃኙ ደግሞ፣ ህግ መከበር አለበት ይላል - ዣቬር። ለያዙት አላማ ፅኑ ናቸው፤ ብቃታቸውን ተጠቅመው ይፋጫሉ። ዣቬር ባይኖር የዣን ቫልዣ ታሪክ ይኮሰምናል። ጠንካራ ተፎካካሪ እንደሌለው የፍፃሜ ውድድር፤ እርባና ቢስ ታሪክ ይሆናል።

ታዲያ በሁለቱ ጀግኖች ግጭት መሃል፤ ዣን ቫልዣን እንደ አባት የምትወደው ወጣት ሴት አለች። ይህችን ሴት በመጠቀም ዣን ቫልዣን ለመዝረፍና ለመጉዳት የሚፈልጉ መናኛ እኩይ ገፀባህርያትም ይኖራሉ። ግን የዣን ቫልዣ ትንቅንቅ ከመናኛና ከእኩይ ገፀባሕርያት ጋር አይደለም። ከጠንካራውና ከጀግናው ዣቬር ጋር ነው ትግሉ። ድርሰቱ ከምዕተ አመት በኋላም እግጅ ተወዳጅ ታሪክ ለመሆን የበቃበት ትልቁ ሚስጥር ይሄው ነው።።

ከዘመኑ ፊልሞችም አንድ ምሳሌ መጥቀስ ይቻላል - ሃሪሰን ፎርድ የሚሰራበት ዘ ፊጁቲቭ የተሰኘው ፊልም። ሚስትህን ገድለሃል ተብሎ በሃሰት የተፈረደበት ሃኪም ከእስር ሲያመልጥ ነው ታሪኩ የሚጀምረው። ሚስቱን የገደሉበትና በተንኮል ለእስር የዳረጉትን ሰዎች አጋልጦ ንፁህነቱን ሳያስመሰክር ወደ እስር መመለስ አይፈልግም። ይህን አላማ ማሳካት አለበት። ኮምጫጫው ህግ አስከባሪ ደግሞ፤ ከእስር ያመለጡ ሰዎችን የገቡበት ገብቶ መያዝና ማሰር ስራው ነው። ህግ መከበር አለበት ባይ ነው። የሁለቱም አላማ ትክክል ነው፤ ፅናት አላቸው። አላማቸውን የሚያሳኩበት ብቃትና ብርታት አላቸው። ፍጭቱ ሃይለኛ ነው። ፊልሙ ደግሞ እጅግ መሳጭ ታሪክ።

መናኛዎቹ እኩይ ገፀባሕርያት፣ በራሳቸው አቅም የታሪኩን አቅጣጫ የመቀየር አቅም የላቸው - ጀግኖቹ ገፀባሕርያት ደካማ ካልሆኑና ካልፈቀዱላቸው በቀር። የጀግኖቹ ግጭት ተባብሶና ጦዞ እልባት ላይ ሲደርስ፤ እኩዮቹ ገፀባሕርያት እርቃናቸውን ይቀራሉ። በእግር ኳስ ውድድርም ተመሳሳይ ነው። ጨዋታው የሚያምረው፣ ከፍተኛ ብቃት ባላቸው ምርጥ ተጫዋቾች ሲወዳደሩ ነው።

ሦስቱ የኪነጥበብ ባሕርያት ሲጓደሉ

ዋና ዋና ነገሮች ላይ አለማተኮር ማለት ምን ማለት እንደሆነ ለመገንዘብ ምሳሌዎችን ልጥቀስላችሁ። ያህል ይሉሃል ይሄ ነው። የተፈነከተ ተመልካች ላይ የሚደረግ የረቀቀ ህክምና ስናይ ብንውል? አጥቂው እያታለለ ሲያልፍ ለአፍታ አሳይቶ ከዚያ በኋላ ለ10 ደቂቃ ያህል የሜዳውን የሳር ቅጠል ብዛትና ስፋት ከተለያየ አቅጣጫ እየቀረፀ ቢያሳየንስ? አንድ ሁለት ተቀባብለው፣ ወደ ግራ ክንፍ አሻግረው፣ ወደ ግብ... ካሜራው ይህንን አቋርጦ ጨዋታው እስኪያልቅ ድረስ የተጨዋቹ የገምባሌ ስፌት እና የፀጉሩ ቀለም ከተለያየ አቅጣጫ እየደጋገመ ቢያሳየንስ? በቲቪ በቀጥታ የሚተላለፈው ጨዋታው ሳይሆን፤ የአሰልጣኞችን ክርክርና ዛቻ ወይም የተጫዋቾችን ተረብና የቅፅል ስም አጠራር ቢሆንስ? ወይም፤ በትንታኔና በቲዎሪ ፉክክር ብቻ ነገሩ ቢጠናቀቅስ? ተጨባጭ ታሪክ ሳይኖረው፤ በገለፃና በትንታኔ የታጨቀ ድርሰትም፤ ከሬድዮ ቶክ ሾው የተሻለ ዋጋ አይኖረውም።

ብቃት የማያስፈልገው ውድድር ቢሆንና ማጣሪያና ምርጫ ባይኖርስ? ለምሳሌ በእጣ ሊሆን ይችላል። እግር ኳስ ማየት፤ የሎተሪ እጣ ሲወጣ ከማየት የተለየ አይሆንም ነበር። የተጫዋቾችን ብቃት መመዘን ባንችል ኖሮስ? ስለ ቼዝ የማናውቅ ከሆነ የቼዝ ጨዋታ ለማየት እንጓጓም። ምክንያቱም የተጨዋቾችን ብቃት መመዘን አንችልም። ማሸነፍና ዋንጫ ማግኘት የሚቻለው በእርዳታ ቢሆንስ ኖሮ? አንዱ ቡድን በባዶ እግር በአምስት ሰው ብቻ እንዲጫወት የሚፈረድበት ቢሆን?ተጫዋቾች በብቃታቸው የማይመረጡ ቢሆንስ? ስማቸው በ”ኤ” የሚጀምርና በውድቅት ሌሊት የተወለዱ ብቻ የሚካፈሉበት ውድድር ቢሆንስ? ብቃትን አጉልቶ የማያወጣ ውድድር፤ ከንቱ ልፊያ ይሆናል። ይህ ነው የሚባል ብቃት በሌላቸው ገፀባሕርያት የታጨቀ ድርሰትም እንደዚያው ነው።

ግብ እና ዋንጫ ባይኖርስ? (7 ቁጥሩ ለ9 አሳለፈ፣ ጠለዘ፣ ነዳ ... ይህንን ለስንት ደቂቃ ሳይሰለቸን ማየት እንችላለን? አሸናፊው ተለይቶ የሚታወቀው በቲፎዞ ብዛት ቢሆንስ? ጎል ሲያገባ እንደ ዳኛው ፍላጎት፣ ለሌኛው ቡድን ነጥብ ቢሰጥስ? ለማሸነፍ ባይጫወቱስ? በይሉኝታ መሸነፍ፣ ለሌላው አዝኖ ራስን መስዋዕት ማድረግ፣ ያሸነፈ ቡድን ራስ ወዳድ ተብሎ ቢወገዝስ? የዘንድሮው ሻምፒዮና፣ በስህተት በራሱ ላይ ብዙ ግብ ያስቆጠረ ቡድን ነው ቢባልስ?

Read 6423 times