Saturday, 30 March 2013 13:27

ሦስት ግለሰቦች ራሳቸውን ያጠፉበት መፀዳጃ ቤት እንዲፈርስ ተጠየቀ

Written by 
Rate this item
(5 votes)

ራሳቸውን ለማጥፋት ከሞከሩት ስድስት ግለሰቦች ሦስቱ ተርፈዋል በኮልፌ ቀራኒዮ ክፍለ ከተማ ቀበሌ 25፣ በተለምዶ እሬሳ ማዞሪያ እየተባለ በሚጠራው ሠፈር ውስጥ ለበርካታ አመታት በህዝብ መፀዳጃ ቤትነት ሲያገለግል የቆየ ክፍል ውስጥ ሰሞኑን አንድ ረዳት ሳጅን ራሱን ሰቅሎ እንደተገኘ ምንጮች ገለፁ፡፡ ንብረትነቱ የቀበሌ በሆነው መፀዳጃ ቤት ውስጥ ስድስት ግለሰቦች ራሳቸውን ለማጥፋት ሞክረው ሦስቱ ሲሞቱ ሦስቱ ተርፈዋል፡፡ ወላጅ እናቱን በሞት ካጣ በኋላ በመንፈስ ጭንቀት ይሰቃይ የነበረው የ14 ዓመቱ ታዳጊ በ1999 ዓ.ም በዚህ መፀዳጃ ክፍል ውስጥ ራሱን እንዳጠፋ ነዋሪዎች ይናገራሉ፡፡ ነዋሪዎች በወቅቱ መፀዳጃው ቤት እንዲፈርስ መጠየቃቸውን ይናገራሉ፡፡

ሆኖም መፀዳጃ ክፍሉ ሳይፈርስ የታዳጊው አጎት እራሳቸውን ለማጥፋት ሞክረው ሠዎች ደርሠው አትርፈዋቸዋል፡፡ አንዲት ሴትም እራሷን ለማጥፋት ሞክራ በሠዎች እርዳታ ተርፋለች፡፡ ሌላ የአካባቢው ነዋሪ እንዲሁ በዚሁ መፀዳጃ ቤት ውስጥ እራሱን ለማጥፋት ያደረገው ሙከራ አልተሳካለትም፡፡ እነዚህ ግለሠቦች በሌሎች መፀዳጃ ቤቶች ራሳቸውን ለማጥፋት ሞክረው አግዳሚ እንጨቶቹ የበሠበሱ በመሆናቸው ሳይሳካላቸው እየቀረ ወደዚህ መፀዳጃ ክፍል እንደሚመጡ ነዋሪዎች ይናገራሉ፡፡ የ10ኛ ክፍል ተማሪ የነበረው የ18 ዓመት ወጣት በዚሁ መፀዳጃ ቤት ውስጥ ራሱን አጥፍቶ እንደተገኘ ነዋሪዎች ይናገራሉ፡፡

በሁኔታው የተማረሩ ነዋሪዎች መፀዳጃ ክፍሉን ለማፍረስ ሙከራ አድርገው የነበረ ቢሆንም ተጠቃሚው በርካታ በመሆኑና ሌላ አማራጭ ስለሌለ ሳይፈርስ ቀርቷል፡፡ ባለፈው ሳምንት ደግሞ አንድ ረዳት ሳጅን በተመሳሳይ ሁኔታ ራሱን ሰቅሎ ተገኝቷል፡፡ ወጣቱ በ2000 ዓ.ም ፖሊስ ለመሆን ስልጠና በመውሰድ ላይ ሳለ ባጋጠመው የአዕምሮ ህመም ምክንያት ሥልጠናውን አቋርጦ ወደ ቤተሠቦቹ ተመልሶ ነበር፡፡ አማኑኤል ሆስፒታል ገብቶ በተደረገለት ህክምና ካገገመ በኋላ ለተጨማሪ ህክምና በፖሊስ ሆስፒታል ሳለ ከሆስፒታሉ ህንፃ ላይ እራሱን ቢፈጠፍጥም ህይወቱ ተርፏል፡፡ ተመልሶ ወደ ማሠልጠኛው ገብቶም ስልጠናውን ጨርሶ ወደ ስራ የተሠማራው ወጣቱ፤ ለሦስት አመታት በሙያው ሲሠራ የቆየ ሲሆን ባለፈው ሳምንት እናቱ ቤት ምሳውን ከበላ በኋላ እናቱ ወደ ለቅሶ ቤት ሲሄዱለት ወደ መፀዳጃ ቤቱ በመሄድ ህይወቱን አጥፍቷል፡፡ በክስተቱ የተበሳጨ አንድ የአካባቢው ወጣት የመፀዳጃ ቤቱን በር በንዴት የገነጠለው ሲሆን ነዋሪዎች ለሚመለከተው ክፍል ችግሩን በመጠቆም መፍትሄ እንዲሰጣቸው መጠየቃቸውን ገልፀዋል፡፡

Read 5110 times