Saturday, 30 March 2013 15:23

በአውሮፓ ሊጎች የዋንጫ ፉክክር ቀዝቅዟል

Written by 
Rate this item
(3 votes)

በአውሮፓ 5 ታላላቅ ሊጎች የ2012 -13 የውድድር ዘመንን ሲጠናቀቅ ከሁለት ወር ያነሰ ጊዜ ሲቀረው በየሊጐቹ የሻምፒዮናነት ፉክክሩ ብዙም አጓጊ አይደለም፡፡ በእንግሊዝ ፕሪሚዬር ሊግ ማን ዩናይትድ፤ በስፔን ላሊጋ ባርሴሎና እንዲሁም በጀርመን ቦንደስ ሊጋ ባየር ሙኒክ የየሊጋቸውን የደረጃ ሰንጠረዥ በሰፊ የነጥብ ልዩነት በመምራት ወደ ሻምፒዮናነቱ ያለ ተፎካካሪ እየገሰገሱ ናቸው፡፡ በጣሊያን ሴሪኤ እና በፈረንሳይ ሊግ 1 ግን የዋንጫ ፉክክሩ ብዙም አልደበዘዘም፡፡ በአውሮፓ 5 ታላላቅ ሊጎች ላይ ለዋንጫዎች የሚደረግ ፉክክር በጥቂት ክለቦች መካከል ተወስኖ የየሊጎቹን ማራኪነት እየቀዘቀዘው መጥቷል፡፡ ለዚህም ባለፉት 10 ዓመታት በአምስቱ የአውሮፓ ሊጎች በሚወዳደሩ ክለቦች መካከል በፋይናንስ አቅም የተፈጠረው ልዩነት ዋና ምክንያት መሆኑ ይገለፃል፡፡ የጀርመኑ ቦንደስ ሊጋ እና የፈረንሳዩ ሊግ 1 በሚታይባቸው የፉክክር ደረጃ እና የክለቦች የተመጣጠነ አቋም አጓጊ እና ውጤታቸውን ለመተንበይ የሚያስቸግሩ ሊጎች ናቸው፡፡ የስፔኑ ላሊጋ ደግሞ በሁለት ክለቦች ብቻ በተወሰነ ፉክክር ሚዛኑ ያጣ እና የማይስብ ሊግ ሲባል የእንግሊዝ ፕሪሚዬር ሊግ ትርፋማ የጣሊያን ሴሪኤ ደግሞ ደካማ ሊጐች ተብለዋል፡፡

በ21ኛው የእንግሊዝ ፕሪሚዬር ሊግ እስከ 29ኛው ሳምንት በተደረጉ 296 ጨዋታዎች 837 ጎሎች ተመዝግበው ሊጉ በአንድ ጨዋታ በአማካይ 2.83 ጎሎች የሚቆጠሩበት ሆኗል፡፡ ማንችስተር ዩናይትድ ፕሪሚዬር ሊጉን ከ29 ጨዋታዎች በሰበሰባቸው 74 ነጥቦች እና 38 የግብ ክፍያዎች እየመራ ነው፡፡ ያለፈው ዓመት የፕሪሚዬር ሊግ ሻምፒዮን ማንችስተር ሲቲ በ59 ነጥብ እንዲሁም ቼልሲ በ55 ነጥብ ይከተላሉ፡፡ ባለፈው የውድድር ዘመን የእንግሊዝ ፕሪሚዬር ሊግ ሻምፒዮን በመጨረሻ ሳምንት ጨዋታዎች እንደታወቀ ሲታወስ ዘንድሮ ግን ሊጉ ከመጠናቀቁ ወር ቀደም ብሎ አሸናፊው ይለያል፡፡ ሰር አሌክስ ፈርጉሰን ክለባቸው በፍፁም የበላይነት የዋንጫ ፉክክሩን መጨረሱ የሚዲያዎችን ትኩረት ቢቀንስም እንዳስደነቃቸው ተናግረዋል፡፡ የፕሪሚዬር ሊጉ የዋንጫ ፉክክር ቢቀዛቀዝም በቀጣይ የውድድር ዘመን የሻምፒዮንስ ሊግ ተሳትፎ ለማግኘት በ7 ነጥብ ልዩነት አራት ክለቦች አስጨናቂ ፉክክር ውስጥ ናቸው፡፡ አራቱ ክለቦች ቼልሲ፤ ቶትንሃም፤ አርሰናልና ኤቨርተን ሲሆኑ በቂ ጨዋታዎቻቸው እስከ አራተኛ ደረጃ ለመጨረስ ወሳኝ ፍልሚያዎችን ያደርጋሉ፡፡

ቼልሲ እና ቶትንሃም በቀሪ ግጥሚያዎቻቸው ከባድ ተጋጣሚዎእች ያሉባቸው ሲሆን አርሰናልና ኤቨርተን ቀለል ባሉ ጨዋታዎች የሻምፒዮንስ ሊግ ተሳትፏቸውን ለማሳካት ተስፋ ያደርጋሉ፡፡ ኪውፒአር ሬዲንግ እና ዊጋን በወራጅ ቀጠና ውስጥ እየዳከሩ ሲሆን አስቶንቪላ፤ ሳውዝ ሃምፕተንና ሰንደርላንድ በዚሁ አደጋ አፋፍ ላይ ሆነው በቀጣዮቹ አምስት ሳምንታት ከመውረድ ለመዳን ይታገላሉ፡፡ በእንግሊዝ ፕሪሚዬር ሊግ የዓመቱ ኮከብ ተጨዋች ፉክክር የማን ዩናይትዱ ቫን ፒርሲ፤ የቶትንሃሙ ጋሬዝ ባሌ እና የሊቨርፑሉ ሊውስ ስዋሬዝ ዋና እጩዎእች ናቸው፡፡ የኮከብ ግብ አግቢነቱን ፉክክር ደግሞ የሊቨርፑሉ ሊውስ ሱዋሬዝ በ22 ጎሎች ሲመራ የማን ዩናይትዱ ቫንፒርሲ በ19 ጎሎች ዱካውን ይዞታል፡፡ በታሪኩ ለ82ኛ ጊዜ እየተካሄደ በሚገኘው የስፔኑ ላሊጋ እስከ 28ኛው ሳምንት 283 ጨዋታዎች ተደርገው 791 ጎሎች ከመረብ አርፈዋል፡፡

ይህም የላሊጋውን አንድ ጨዋታ በአማካይ 2.83 ጎሎች የሚመዘገቡበት አድርጎታል፡፡ በላሊጋው ባርሴሎና ባደረጋቸው 28 ግጥሚያዎች 74 ነጥብ እና 54 የግብ ክፍያ መሪነቱን እንደያዘ ሲሆን ያለፈው ሻምፒዮን ሪያል ማድሪድ በ13 ነጥብ ተበልጦ ሁለተኛ ደረጃ ላይ ነው፡፡ በኮከብ ግብ አግቢ ፉክክር ደግሞ የባርሴሎናው ሊዮኔል ሜሲ በ42 ጎሎቹ የሚመራ ሲሆን የሪያል ማድሪዱ ክርስትያኖ ሮናልዶ በ27 ጎሎች በርቀት ይከተለዋል፡፡ በ50ኛው የጀርመን ቦንደስ ሊጋ እስከ 26ኛው ሳምንት በተደረጉ 234 ጨዋታዎች 665 ጎሎች ተመዝግበው ሊጉ በአንድ ጨዋታ በአማካይ 2.84 ጎሎች የሚያሳይ ሆኗል፡፡ ባየር ሙኒክ ባደረጋቸው 26 ጨዋታዎች 69 ነጥብ እና 58 የግብ ክፍያ በማስመዝገብ ቦንደስ ሊጋውን በሁለተኛ ደረጃ ከሚገኘው ቦርስያ ዶርትመንድ በ20 ነጥብ ልዩነት መሪነቱን ይዞ ወደ ሻምፒዮናነት እየገሰገሰ ነው፡፡ በኮከብ አግቢ ፉክክር የቦርስያ ዶርትመንዱ ሮበርት ሌዋንዶውስኪ በ19 ጎሎች እየመራ ሲሆን የባየር ሌቨርኩዘኑ ስቴፈን ኪዬብሊንግ በ16 ጎሎች እንዲሁም የባየር ሙኒኩ ማርዮ ማንዱዚክ በ15 ጎሎች ይከተሉታል፡፡

በ81ኛው የጣሊያን ሴሪ ኤ እስከ 29ኛው ሳምንት በተደረጉ 289 ጨዋታዎች 772 ጎሎች የገቡ ሲሆን ይህም በሴሪኤው በአንድ ጨዋታ በአማካይ 2.67 ጎሎች ሲቆጠሩ ቆይተዋል፡፡ ያለፈው አመት የሴሪኤ ሻምፒዮን ጁቬንትስ ዘንድሮም የስኩዴቶውን ክብር የመውሰድ እድሉን እያሰፋ ሲሆን ባደረጋቸው 29 ጨዋታዎች 65 ነጥብና 39 የግብ ክፍያ በመያዝ ይመራል፡፡ ናፖሊ በ56 ነጥብ እንዲሁም ኤሲ ሚላን በ54 ነጥብ እየተከተሉ ናቸው፡፡ በሴሪኤው የኮከብ ግብ አግቢነቱን ፉክክር የሚመራው የናፖሊው ኤዲሰን ካቫኒ በ20 ጎሎች ነው፡፡ በ75ኛው የፈረንሳይ ሊግ 1 እስከ 29ኛው ሳምንት በተደረጉ 290 ጨዋታዎች 735 ጎሎች ሲቆጠሩ ይህም ሊጉን በአንድ ጨዋታ በአማካይ 2.53 ጎሎች የሚገቡበት አድርጎታል፡፡ በሊግ 1 ባደረጋቸው 29 ጨዋታዎች 58 ነጥብ እና 33 የግብ ክፍያ በማስመዝገብ ፓሪስ ሴንትዠርመን እየመራ ቢሆንም ሊዮን በ53 እንዲሁም ማርሴይ በ51 ነጥብ በሁለተኛ እና ሶስትኛ ደረጃ እየተፎካከሩ ናቸው፡፡ በኮከብ ግብ አግቢነት ፉክክሩ የፓሪስ ሴንትዠርመኑ ዝላታን ኢብራሞቪች በ25 ጎሎች ይመራል፡፡

Read 5242 times