Saturday, 30 March 2013 15:28

ዋልያዎቹ የዓለም ዋንጫ ጉዟቸውን እያመቻቹ ነው

Written by 
Rate this item
(1 Vote)

ባለፈው ሳምንት በአዲስ አበባ ስታዲየም በዓለም ዋንጫ የሶስተኛ ዙር የማጣሪያ ጨዋታ የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን የቦትስዋና አቻውን 1ለ0 በማሸነፍ የምድቡን መሪነት አጠናከረ፡፡ ዋልያዎቹ በዚሁ ጨዋታ ከቦትስዋና ያልጠበቁት ከባድ ፉክክር የገጠማቸው ሲሆን ብቸኛዋን የማሸነፊያ ጎል ባለቀ ሰዓት የደደቢቱ ጌታነህ ከበደ አስቆጥሮ ሙሉ ሶስት ነጥብ ሊመዘገብ ችሏል፡፡ በሌላ የምድብ 1 ጨዋታ መካከለኛው አፍሪካ ሪፖብሊክን በኬፕታውን ያስተናገደችው ደቡብ አፍሪካ 2ለ0 አሸንፋለች፡፡

ከዓለም ዋንጫ የሶስተኛ ዙር የማጣሪያ ጨዋታ በኋላ የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን በ7 ነጥብ እና በ3 የግብ ክፍያ መሪነቱን ማስጠበቅ የቻለ ሲሆን ደቡብ አፍሪካ በ5 ነጥብ ሁለተኛ ደረጃን ይዛለች፡፡ ከሶስተኛ ዙር የማጣሪያ ጨዋታ በፊት ሁለተኛ ደረጃ ላይ የነበረችው መካከለኛው አፍሪካ በደቡብ አፍሪካ ከተሸነፈች በኋላ በሶስት ነጥብ ወደ ሶስተኛ ደረጃ ስትወርድ በኢትዮጵያ የተሸነፈችው ቦትስዋና በአንድ ነጥብ በነበረችበት የመጨረሻ ደረጃ ላይ ረግታለች፡፡

ኢትዮጵያ በምድብ 1 በሁለት ነጥብ ልዩነት መሪነቷን መቀጠሏ ወደ ዓለም ዋንጫው የማለፍ ተስፋ ካላቸው ቡድኖች ተርታ እንዳሰለፋት በተለያዩ ዘገባዎች ተገልጿል፡፡ በተመሳሳይ ዲ.ሪፖብሊክ ኮንጎ፤ አይቬሪኮስት፤ ካሜሮን፤ ሴኔጋልና ቱኒዝያ በየምድባቸው መሪነት ጉዟቸውን በስኬት ቀጥለዋል፡፡ በ2014 ብራዚል ለምታስተናግደው 20ኛው የዓለም ዋንጫ ለማለፍ የሚደረገው የምድብ ማጣርያ በአራተኛ ዙር ከ4 ወራት በኋላ ይቀጥላል፡፡ ኢትዮጵያ ሰኔ ወር ላይ ከሜዳዋ ውጭ ከቦትስዋና እና በሜዳዋ ከደቡብ አፍሪካ ጋር ትገናኛለች፡፡ በእነዚህ የ4ኛ እና የ5ኛ ዙር የማጣርያ ጨዋታዎች ካሸነፈች በ6ኛ ዙር ከሜዳዋ ውጭ ከመካከለኛው አፍሪካ የምታደርገውን የመጨረሻ ጨዋታ ሳትጠብቅ ምድብ አንድን በመሪነት በማጠናቀቅ ለመጨረሻው የጥሎ ማለፍ ማጣርያ ታልፋለች፡፡

በተያያዘ በ2013 የአፍሪካ ክለቦች ሻምፒዮንስ ሊግ እና ኮንፌደሬሽን ካፕ አንደኛ ዙር ማጣርያ ተጋጣሚዎቻቸውን የረቱት ቅዱስ ጊዮርጊስ እና ደደቢት የመልስ ጨዋታቸውን ከሳምንት በኋላ ያደርጋሉ፡፡ በአፍሪካ ሻምፒዮንስ ሊግ የአንደኛ ዙር ማጣርያ የመጀመርያ ግጥሚያውን በሜዳው ያደረገው ቅዱስ ጊዮርጊስ የማሊውን ዲጆሊባ 2-0 ማሸነፉ ሲታወስ፤ በኮንፌዴሬሽን ካፕ ደግሞ የአንደኛ ዙር የማጣርያ ጨዋታውን ከሜዳው ውጭ ወደ ሱዳን ተጉዞ አልሼንዲን የገጠመው ደደቢት 1-0 በሆነ ጠባብ ውጤት እንዳሸነፈ አይዘነጋም፡፡ የአንደኛ ዙር ማጣርያ የመልስ ጨዋታዎች ሲቀጥሉ ሁለቱ የኢትዮጵያ ክለቦች ወደ ሁለተኛ ዙር የማጣርያ ምእራፍ ለመሸጋገር የሚያስችል ዕድል ይዘዋል፡፡ ቅዱስ ጊዮርጊስ በሻምፒዮንስ ሊጉ ከሜዳው ውጭ በባማኮ የማሊውን ዲጆሊባ ሲፋለም ማሸነፍ እና አቻ መውጣት የሚበቃው ሲሆን ዲጆሊባ ጊዮርጊስን ጥሎ ለማለፍ በሜዳው የሚያደርገውን ግጥሚያ 3-0 ማሸነፍ ይኖርበታል፡፡ በሌላ በኩል በኮንፌደሬሽን ካፕ አዲስ አበባ ላይ የሱዳኑን አልሼንዲን የሚያስተናግደው ደደቢት በሜዳውና በደጋፊው ፊት በሚያደርገው የመልስ ጨዋታ በማሸነፍ የማለፍ እድሉን ይወስናል፡፡

Read 4469 times