ለካ ከልቤ እወድሽ ነበር
ለካስ ከልቤ አፈቅርሻለሁ
ከእውነት እንደማስብሽ
ከአንጀቴ እንደናፈቅኩሽ
ዛሬን ለኔ አውቄዋለሁ፡፡
ዛሬን ነገን ትመጪ እያልኩ
ቀን ስቆጥር እየኖርኩኝ…
አንቺን ከማሰቤ ጋር
አንቺን ከናፍቆቴ ጋር
እያሰብኩሽ እያለምኩ
መልክሽን ይዤ እየዋልኩ
ሰውነትሽን ይዤ እያቀፍኩ
ሳወራልሽ እያደርኩኝ…
ዛሬ ነገ ላገኝሽ
ቀኔን ስቆጥር እየኖርኩኝ
ቀረች ቢሉኝ
መቼ ደርሰሽ
መች አግኝቼሽ
የልቤን ቃል
ላጫውትሽ፡፡
እስክትመጪ አጠራቅሜ
አስቀምጬ ያቆየሁሽን
የፍቅራችንን ምስጢር
ተቃቅፈን “ምናወራትን
ምንንሾካሾካትን
መቼ ደርሰሽ እያልኩ እኔ
ቀኑ ረዝሞ ሌ ቱ ጨንቆኝ
ላንቺ ብዬ ተካፍዬ
ለሌላ የማልነግረውን
ጭንቀቴን ሃሳቤን ሁሉ
ሳሰላስል የኖርኩትን
ሳላዋይሽ ቀረች ቢሉኝ
ምን ሊውጠኝ?
ታህሳስ 18/1980
(“ሶረኔ” ልዩ ልዩ የበረሃ ግጥሞች
ከሚለው መድበል የተወሰደ)
Published in
የግጥም ጥግ