Saturday, 27 April 2013 12:05

የማህጸን በር ካንሰርን ለመከላከል በጋራ መስራት...

Written by 
Rate this item
(2 votes)

Cervical cancer… የማህጸን በር ካንሰር ...80% ያህል በታዳጊ አገሮች ይከሰታል

የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ፣የኢትዮጵያ የጽንስና ማህጸን ሐኪሞች ማህበር እና ጀርመን የሚገኘው ማርቲን ሉተር ዩኒቨርሲቲ በኢትዮጵያ የማህጸን በር ካንሰርን ለመከላከል የሚያስችል ፕሮጀክት ተግባራዊ ለማድረግ በአዲስ አበባ ስብሰባ አካሂደዋል፡፡ እንደአውሮፓውያኑ የጊዜ ቀመር 10/4/2013 ማለትም ሚያዝያ 2/2005 በኢትዮጵያ የጽንስና ማህጸን ሐኪሞች ማህበር የስብሰባ አዳራሽ በተካሄደው ስብሰባ በጋራ አብረው ለመስራት የታሰቡት ድርጅቶች ተወካዮችና ከኢፊድሪ ጤና ጥበቃ ሚኒስርም እንግዶች ተገኝተው ነበር፡፡ ዶ/ር ተናኘ ጸጥአርጌ ከኢፊድሪ ጤና ጥበቃ ሚኒስር ስብሰባውን ሲከፍቱ እንደተናገሩት በኢትዮጵያ ከስነተዋልዶ ጤና ጋር በተያያዘ ለሴቶች ሞት በምክንያትነት ከሚጠቀሱት የማህጸን በር ካንሰር ይገኝበታል፡፡

ይህ በሽታ በብዙ ሴቶች ላይ የሚከሰትና በአስከፊነቱም በቀዳሚነት የተመዘገበ ነው፡፡ ማንኛዋም የግብረስጋ ግንኙነት የምትፈጽም ሴት በበሽታው ለመጠቃት እንደምትችል መረጃዎች እንደሚጠቁሙ ዶ/ር ተናኘ ተናግረዋል፡፡ ዶ/ር ካሳሁን ኪሮስ የጽንስና ማህጸን ሕክምና እስፔሻሊስትና በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ሜዲካል ፋኩልቲ በአንድ ወቅት እንደገለጹት የማህጸን ካንሰር አይነቱ ብዙ ሲሆን በአገራችን በብዛት የሚያጠቃውና ገዳይ የሆነው የማህጸን በር ካንሰር (Human Papiloma Virus) ሒዩማን ፓፒሎማ በተባለው ቫይረስ አማካኝነት የሚከሰተው ነው፡፡ በአሁኑ ጊዜ ለማህጸን በር ካንሰር መከላከያ የሚሆኑ ሁለት አይነት ክትባቶች የተገኙ ሲሆን አንዱ Gardasil ሲሆን ሁለተኛው Cervarix የተሰኘው ነው፡፡ Gardasil K Human Papiloma Virus ለማህጸን በር ካንሰር መንስኤ ለሆነው መከላከያ ክትባት ሲሆን አራት የቫይረስ አይነቶችን ማለትም 16...18...6...እና 11 የተባሉትን የቫይረስ አይነቶች የሚከላከል ነው፡፡ በተመሳሳይም Cervarix የተባለው ክትባት 16...እና...18 የተባሉትን ቫይረሶችን ብቻ የሚከላከል የክትባት አይነት ነው፡፡ የማህጸን በር ካንሰር 70 ኀያህሉ የሚከሰተው በእነዚህ በ16 እና 18 በተባሉ የቫይረስ አይነቶች መሆኑ ተረጋግጦአል፡፡

በዓለማችን በየሁለት ደቂቃ አንድ ሴት በየሰአቱ ደግሞ ሰላሳ ሴቶች በማህጸን በር ካንሰር ምክንያት ለህልፈት ይዳረጋሉ፡፡ በዓለም አሀዝ መሰረት በየአመቱ እስከ ግማሽ ሚሊዮን ሴቶች የማህጸን በር ካንሰር ያላቸው መሆኑን በምርመራ የሚያረጋግጡ ሲሆን ከእነዚህም እስከ ሁለት መቶ ሰባ አምስት ሺህ የሚሆኑት በዚሁ ህመም ምክንያት ሕይወታቸው ያልፋል፡፡ ዶ/ር ተናኝ ጸጥአርጌ ከኢፊድሪ ጤና ጥበቃ ሚኒስር እንደገለጹት በብሄራዊ ደረጃ በየአመቱ ወደ 7619/ ሰባት ሺህ ስድስት መቶ አስራ ዘጠኝ ሴቶች በማህጸን በር ካንሰር ሊያዙ እንደሚችሉና ከነዚህም ወደ 6081/ ስድስት ሺህ ሰማንያ አንድ የሚሆኑት ለህልፈት እንደሚዳረጉ ይገመታል፡፡ ይህ ቁጥር የሚያሳየው ምን ያክል ታማሚዎች እንዳሉና የሞት ቁጥሩም ቀላል እንዳልሆነ ሲሆን በተያያዠነትም ለጉዳዩ የተሰጠው ትኩረት ምን ያህል እንደሆነ እንዲሁም አገልግሎቱ መስፋፋት እንዳለበትም የሚጠቁም ነው፡፡

የኢፊድሪ ጤና ጥበቃ ሚኒስር በብሕራዊ ደረጃ ወደ 118/የሚሆኑ የጤና ተቋማት የማህጸን በር ካንሰርን በሚመለከት ትኩረት ሰጥተው እንዲሰሩ የሚያስችል አሰራር በመዘርጋት ላይ ነው፡፡ ስለዚህም ይህንን በሽታ ለመከላከል በቂ የሆነ የህክምና አገልግሎት መሰጠት በምእተ አመቱ የልማት ግብ ከታቀዱት መካከል የእናቶችን ሞት ለመቀነስ ይረዳል፡፡ እስከአሁን ባለው አሰራር ለ2015/ የታቀደውን የልማት ግብ ለማሳካት ከፍተኛ ጥረት እየተደረገ እና ውጤት የሚያስመዘግቡ ስራዎች እየታዩ ቢሆንም አሁንም ገና ብዙ መሰራት እንዳለበት ከሚጠቁሙት እውነታዎች መ..ከል የማህጸን በር ካንሰር ይኝበታል፡፡ ይህም በብሕራዊ ደረጃ ከታቀደው የስነተዋልዶ አካላት ጤና አጠበባበቅ ጋር የሚገናኝ ነው ብለዋል ዶ/ር ተናኘ፡፡ ዶ/ር ይርጉ ገ/ሕይወት የጽንስና ማህጸን ሕክምና እስፔሻሊስት በአ.አ ዩኒቨርሲቲ ሕክምና ፋክልቲ መምህር እና የኢሶግ ፕሬዝዳንት በትብብር መስራትን በሚመለከት በሰጡት ማብራሪያ .. ...እንደሚታወቀው በአብዛኛው ትኩረት የሚሰጠው አጣዳፊ ለሆኑት እና ተላላፊ በሽታዎች ቢሆንም ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ግን ይህ አዝማሚያ እየተለወጠ ሌሎች ከሰው ሰው በቀላሉ የማይተላለፉ ነገር ግን ሕይወትን አደጋ ላይ የሚጥሉ የጤና ችግሮችም ትኩረት እያገኙ በመምጣት ላይ ናቸው፡፡

ለምሳሌ..የውስጥ አካላት ሕመሞች...የደም ግፊት...የስኩዋር ሕመም የመሳሰሉት ከሰው ሰው በመተላለፍ ጉዳት የማያስከትሉ ቢሆንም ሰዎችን ግን ጤናቸውን የሚያቃውሱ በመሆኑ በአለም አቀፍ ደረጃ አትኩሮትን ያገኙ ናቸው፡፡ በዚሁ ረገድም ከስነተዋልዶ አካላት ጋር ተያይዘው የሚገኙ የተለያዩ የካንሰር አይነቶችን በሚመለከት የበለጠ ግንዛቤ የሚገኝበት የችግሩም ስፋት የሚታወቅባቸው መድረኮች እየተፈጠሩ ነው፡፡ የኢትዮጵያ የጽንስና ማህጸን ሐኪሞች ማህበር አባላት አብዛኞቹ በቀጥታ ከጽንስና ማህጸን ሕክምና ጋር የተያያዘ የህክምና አገልግሎት የሚሰጡ እንደመሆናቸው ታማሚዎችን በህክምናው አገልግሎት የመርዳት ስራ ይሰራሉ፡፡ በዚህም እንደሚታየው አብዛኞቹ የማህጸን በር ካንሰር ታማሚዎች ወደህክምናው የሚመጡት በሽታው ስር ከሰደደና ከተሰራጨ በሁዋላ በመሆኑ በቀላሉ ለማከምና ለማዳን እጅግ ፈታኝ ሁኔታዎች ይገጥማሉ፡፡ ስለዚህ ይህንን ሁኔታ ለመለወጥ ምን ማድረግ ያስፈልጋል የሚለውን ለመነጋገር የተፈጠረው የምክክር መድረክወደ ሶስት ነገሮችን ማድረግ እንደሚቻል አሳይቶአል፡፡

ግንዛቤ የማስጨበጥ ስራ መስራት ... ሴቶች በችግሩ ስር በሰደደ እና በከፋ ሁኔታ ከመጠቃታቸው በፊት ሊታከሙ በሚችሉበት የህክምና ተቋም በመሄድ ሕክምና እንዲያደርጉ ያስችላል የሚል ግምት አለ፡፡ የችግሩን ስፋትና ጥልቀት ማወቅና የዚያኑ ያህል ተመጣጣኝ የሆኑ እንቅስቃሴ ዎችን ማድረግ አስፈላጊ በመሆኑ አንዳንድ የዳሰሳ ጥናቶችን ማድረግ፣ይህም የሚሰሩ ስራዎች በትክክለኛ መረጃ ላይ የተመሰረተ ከሆነ የተጀመረውን ፣ መሰራት የሚገባውንና ከአመታት በሁወላ ሊደረስበት የሚገባውን ደረጃ ለማወቅ ይረዳል፡፡ ቅድመ ካንሰር ሁኔታውን አስቀድሞውኑም ማወቅ የሚቻልበት የህክምና አሰራሮች ስላሉ ይህንን አገልግሎት በቀላሉና በስፋት እንዴት ማዳረስ ይቻላል የሚለውን ስብሰባው ተመልክቶአል፡፡ ለዚህም ተቋሞችን በሰለጠነ የሰው ኃይል እና በተገቢው መሳሪያ ማጠናከር እና አስፈላጊው ግብአት የሚገኝበትን ሁኔታ ስብሰባው ተነጋግሮአል፡፡ የካንሰር ሕክምና እስከአሁን የሚሰጠው ውስን በሆኑ የህክምና ተቋማት በተለይም በጥቁር አንበሳ ሆስፒታል ሲሆን ነገር ግን የሆስፒታሉ አቅም ውስን በመሆኑ ታካሚዎች በጣም ለረጅም ጊዜ ህክምናውን ለማግኘት ወረፋ የሚጠብቁበት ሁኔታ ይታያል፡፡ ይህንን ለውጦ ተደራሽነትን ለማስፋት እንዴት ይቻላል የሚለው መልስ እንዲያገኝ ክህሎትን የማሳደግና ግብአትን የማሟላት ስራ መስራት አስፈላጊ መሆኑ ተጠቁሞአል፡፡

ይህ እቅድ ከተሳካ በሚቀጥሉት ሁለት አመታት ውስጥ ጠንካራ ስራዎችን መስራት ይቻላል ተብሎ ይታሰባል፡፡ ይህ እሳቤ እውን ከሆነ በሁዋላም የማህጸን በር ካንሰርን የመከላከል ስራ በፕሮጀክት ተይዞ የሚቀጥል ሳይሆን ከተወሰኑ የጊዜ ሂደቶች በሁዋላ እንደማንኛውም መሰረታዊ የጤና ሁኔታ ተይዞ በአገር አቀፍ ደረጃ በተሙዋላ አገልግሎቱን መስጠት ይቻላል የሚል እምነት አለ፡፡ የካንሰር ህክምና በሶስት ደረጃ ተመጣጥኖ የሚሰጥ ነው፡፡ እሱም የጨረር ፣የቀዶ ሕክምና እና በመድሀኒት የሚሰጥ በመሆኑ ከፍተኛ ወጪን የሚጠይቅ ነው፡፡ አሰጣጡም ለየትኛው ታማሚ ምን አይነት ሕክምና ያስፈልገዋል የሚለው በምርመራ አማካኝነት የሚወሰን ሲሆን ወጪው ለምርመራ የሚረዱ መሳሪያዎችን ከማሟላት አንጻር ብቻ ሳይሆን የሙያተኞች እና የሚወሰዱ መድሀኒቶችን ጭምር ያካትታል፡፡ የምርመራ መሳሪያዎችን ሁኔታ ስንመለከት ደግሞ እጅግ ዘመናዊ የሆኑ መሳሪያዎች በአለም ገበያ ላይ የሚገኙ ሲሆን በሌላ በኩል ደግሞ ዋጋቸው ተመጣጣኝ የሆነ ብዙ ሰዎችን ለመርዳት የሚያስችሉም አሉ፡፡ ስለዚህ በከፍተኛ ደረጃ የሚገኘውን የክኖሎጂ ውጤት የምንጠብቅ ከሆነ አቅምም ስለማይፈቅድ ተጠቃሚ የሚሆኑትም ውስን ተቋማት ናቸው፡፡

ዝቅተኛ ወጪ የሚያስወጡ አማራጭ የምርመራ ዘዴዎችን የምንጠቀም ከሆነ ግን አሰራሩን በስፋት እስከጤና ጣቢያ ድረስ መዘርጋት የሚያስችል ሁኔታ ይፈጠራል፡፡ በአገራችን ያለውን የእናቶች ሞት መጠን ለመቀነስ እንዲያስችል አገልግሎቱን በስፋት ማዳረስ አማራጭ የሌለው አሰራር መሆኑን አምኖ በተመጣጣኝ ዋጋ በስፋት ሊዳረስ የሚችለውን መሳሪያ እና ግብአት ወደሀገር በማስገባት የብዙ ሴቶችን ሕይወት ማትረፍ ተገቢ ነው በሚል ከስምምነት የተደረሰበት ነበር የጋራ ምክክሩ ብለዋል ዶ/ር ይርጉ ገ/ሕይወት የኢሶግ ፕሬዝዳንት፡፡ ማንኛዋም ሴት በተለይም እድሜዋ ከሰላሳ አመት በላይ ከሆነ ቢቻል በየአመቱ ባይቻል በየሶስት አመቱ አለበለዚያም በየአምስት አመቱ የቅድመ ካንሰር ምርመራ ብታደርግ ካንሰርን አስቀድሞ መከላከል ይቻላል፡፡ መጥፎ ጠረን ያለው የማህጸን ፈሳሽ ከግብረስጋ ግንኙነት በሁዋላ ወይንም ብልትን በማጽዳት ወቅት እንዲሁም ሰውነት በመንካት ወቅት ደም መፍሰስ ካሳየ ወዲያውኑ ወደሐኪም ሄዶ መፍትሔ ማግኘት ይቻላል፡፡

Read 5582 times