የአዲስ አበባ ፖሊስ ኮሚሽን የወንጀልና ትራፊክ አደጋ ምርመራ ምክትል ኮሚሽነር ኮማንደር ግርማ ካሳ የቀድሞ የፍትህ ሚንስትር በነበሩት በአቶ ብርሃን ሃይሉ ቦታ ተተክተው ከሚቀጥለው ወር ጀምሮ እንደሚሰሩ ምንጮች ገለፁ፡፡ በተለያዩ ክፍለ ከተሞች በመምሪያ ሃላፊነት ሲሰሩ ቆይተው የከተማዋ ፖሊስ ምክትል ኮሚሽነር እንዲሆኑ የተሾሙት ከሰባት አመት በፊት ነው፡፡ በህግ ሁለተኛ ዲግሪ የያዙት ም/ኮሚሽነር ግርማ ካሳ፤ የፍትህ ሚንስትር ሆነው ከዜጐች የሚቀርቡ አቤቱታዎችን ማዳመጥና ችግሮችን በቅርበት የማየት ልምድ አላቸው ተብለው ለፍትህ ሚኒስትርነት እንደተመረጡ ምንጮች ተናግረዋል፡፡
የተፈፀሙ ወንጀሎች በፍጥነት እልባት እንዲያገኙ ለመርማሪዎች ተጨማሪ ድጋፍ ይሰጣሉ እንደተባለም ምንጮች ገልፀዋል፡፡ በኮማንደር ግርማ ቦታ የአዲስ አበባ ፖሊስ ምክትል ኮሚሽነር ይሆናሉ ተብለው የሚጠበቁት የፖሊስ ኮሌጅ የስራ ሃላፊ፣ ም/ኮማንደር ተከታይ ያዜና እንዲሁም የአራዳ ክፍለከተማ ፖሊስ መምሪያ ሀላፊ ረ/ኮሚሽነር እሸቱ አበበ እንደሆኑ ምንጮች ጠቁመዋል፡፡