Print this page
Monday, 27 May 2013 15:16

የካንሰር ሴሎች እብዶች ናቸው

Written by 
Rate this item
(4 votes)

ከላይ የምትመለከቱት የጡት ስእል የጡትን ተፈጥሮአዊ አቀማመጥ የሚያሳይ ነው፡፡ ስአሉን ለእይታ የጋበዝናችሁ ያለምክንያት አይደለም፡፡ የጡት ካንሰርን መሰረታዊ አመጣጥና ለመከላከልም ምን መደረግ ይገባዋል ከሚል የባለሙያ ትንታኔን ልናስነብባችሁ ነው፡፡ ዶ/ር አበበ ፈለቀ በጥቁር አንበሳ ሆስፒታል የቀዶ ሕክምና ባለሙያና አሲስታንት ፕሮፌሰር ለርእሱ ማብራሪያ ሰጥተውናል። ከዚያ በማስቀደም በኢንካርታ ኢንሳይክሎፔድያ ላይ ያገኘነውን መረጃ እነሆ፡፡ “በጥንት ጊዜ በህክምና መታወቅ ወይንም መለየት ከተቻሉት የካንሰር ዓይነቶች ውስጥ አንዱ የጡት ካንሰር ነው፡፡ ይህ መሆን የቻለው ደግሞ የበሽታው ምልክቶች በግልጽ መታየት በመቻላቸው ነው፡፡ ጥንት ከተጻፉ መረጃዎች ውስጥ ከክርስቶስ ልደት በፊት በ1500/ ግብጻውያን የህክምና ባለሙያዎች ፓፒረስ ላይ ያሰፈሩት የኤድዌን ስሚዝ የቀዶ ጥገና መጽሐፍ ላይ ስለጡት ካንሰር ያሰፈሩት መረጃ ያሳያል፡፡

የታሪክ ተመራማሪዎች እንደሚሉት ከሆነ መነሻ የሆነው ለመረጃ የተቀመጡ የስምንት ሰዎች የጡት ካንሰር በሽታ ታሪክ ሲሆን የህሙማኑ የህክምና ምርምር ውጤት ሴቶቹ ጡት ላይ እጢ እንዳለ ያሳይ ነበር፡፡ በዚህ ምክንያት በሽታው ምን እንደሆነ ቢታወቅም በሽታው ህክምናና መድሀኒት ግን የለውም ተብሎ ተደምድሞ ቆይቶአል፡፡ ለበርካታ ዘመናትም የነበሩ የህክምና ባለሙያዎች ያሰፈሯቸው መረጃዎች እንደሚያስረዱት ከሆነ የጡት ካንሰር ምንም አይነት ህክምና እንደሌለው የሚያሳዩ ናቸው፡፡ ለበሽታው መከሰት ምክንያት የሚሆኑ ጉዳዮችን እራሱ ጥንት የነበሩት የህክምና ባለሙያዎችና ተመራማሪዎች አያውቋቸውም ነበር፡፡” ከላይ ያስነበብናችሁ ጥናታዊ ስራዎች ለንባብ ከሉዋቸው ውስጥ የመረጥነውን ነው፡፡ ዶ/ር አበበ ፈለቀ እንደሚገልጹት የጡት ካንሰር ማለት ጡት ከተሰራባቸው ክፍሎች የሚነሳ ሕመም ነው፡፡ ካንሰር ማለት ጤነኛ የነበረ የሰው ልጅ ሴል ጤነኛ ወዳልሆነ ሁኔታ ሲለወጥ ማለት ነው፡፡

ይህም ማለት አንድ ሴል ስራውን በትክክል የማይሰራ፣ በትክክል የማያድግ ወደመሆን ሲለወጥ ማለት ነው፡፡ ስለዚህ ጤነኛ የነበረው ሴል የሚኖረው ስራ ሲቋረጥ ወይንም ከቁጥጥር ውጪ ሲራባ አለዚያም ሲያድግ እና ከጎረቤቱ ያለውን ሴል ስራና ጤንነት ሲበጠብጥ የሚፈጠረው በሽታ ነው ካንሰር ማለት፡፡ ካንሰር አንድ ቦታ ሲፈጠር እዛው በነበረበት ቦታ አይቆይም፡፡ ወደ ሳንባ ወደጉበት እና ወደሌሎችም የሰውነት ክፍሎች ይሄዳል፡፡ ወደተለያዩ የሰውነት አካሎች ከሄደ በሁዋላም እድገቱን በመቀጠል የሰውነት ክፍሎችን ይበጠብጣል፡፡ ባጠቃላይም ካንሰር እንደእብድ ሰው የሚቆጠር ሕመም ነው፡፡ አንድ ሰው እብድ ነው ሲባል የተፈጥሮ ሕግ በትክክለኛው መንገድ እንዲመራ ስለማያዙትና ሁሉንም ነገር እንደፈቀደው ከተፈጥሮ ስርአት ውጪ የሚከውን ሲሆን ሴልም ወደ ካንሰርነት ሲለወጥ በዚህ መልክ ሊገለጽ ይችላል፡፡ የካንሰር ሴሎች ቁጥራቸው መጠናቸው በተፈጥሮ ሕግ መሰረት ሳይሆን እንደተመቸው ይጨምራል፡፡ መስራት የሌለባቸውን ስራ ይሰራሉ፡፡

ከራሳቸው አልፈው ከጎረቤት ያለውን ሴል ይበጠብጣሉ። ይህ በእንግሊዝኛው Carcinogenesis በመባል ይታወቃል፡፡ ዶ/ር አበበ እንደገለጹት ከ/100/የጡት ካንሰር ታማሚዎች ውስጥ /90/ያህሉ ሴቶች ሲሆኑ ወንዶች /10/ ብቻ ናቸው፡፡ ስለዚህ የጡት ካንሰር በብዛት የሚታየው ሴቶች ላይ ነው፡፡ የዚህ ምክንያቱም የጡት መጠኑ ሴቶች ላይ ትልቅ ሲሆን የወንዶች ጡት ግን ትንሽ እና በአይን የማይታይና በእጅ የማይዳሰስ በመሆኑ በካንሰር የመያዝ እድሉም ዝቅተኛ ነው፡፡ ይህ ማለት ግን በጥቅሉ ትልቅ ጡት ያላቸው በካንሰር ሲያዙ ትንህ ጡት ያላቸው ግን አይያዙም ለማለት አይደለም፡፡ ሴቶች በተፈጥሮአቸው ጡታቸው ላይ ብዙ ሴሎች የሚገኙ ሲሆን ወንዶች ግን እንደጡታቸው ማነስ ሴሎቹም ትንሽ ናቸው፡፡

ሴሎች ሲፈጠሩ አስቀድሞውኑ ፕሮግራም ያላቸው በመሆናቸው በዚህ ጊዜ ይህን ያህል ማደግ፣ ይህን ያህል ጊዜ መኖር እንዲሁም በዚህ ጊዜ መሞት የሚል የጊዜ ቀመር አላቸው፡፡ ነገር ግን ሴሎቹ በካንሰር ሲያዙ ይህ በተፈጥሮ የተመደበላቸው የአኑዋኑዋር ባህርይ ይለወጥና ከቁጥጥር ውጪ የሆነ ባህርይን ያመጣሉ፡፡ ስለዚህ የጡት ካንሰር ሲጀምር በጡት እና አካባቢው ቀድሞ ያልነበረ እብጠት ይታያል፡፡ እብጠቱም ጊዜ እየጨመረ በሄደ ቁጥር እያደገ በመሄድ ለዳሰሳም አስቸጋሪ ከማይሆንበት በግልጽ ከሚታወቅበት ደረጃ ይደርሳል፡፡ ዶ/ር አበበ አክለውም ሁሉም የጡት ክፍል በካንሰር የመያዝ እድል ቢኖረውም ነገር ግን 60 ኀያህል የጡት ካንሰር የሚያድገው በብብት ስር ነው ብለዋል፡፡ አንዳንድ ጊዜ ካንሰር ሴሎቹ መሰራጨት ሲጀምሩ ጡቱ ላይ ከሚያብጠው እጢ በተጨማሪ እጅ ስር ያሉት እጢዎች አብረው ማበጥ ይጀምራሉ፡፡ በግዜ ካልተደረሰበትና በጣም ሲያድጉ ወደሌሎች የሰውነት ክፍሎች ይሄዳሉ፡፡ ለምሳሌ ሳንባ ላይ ሲሄድ ሳል ፣ደም የቀላቀለ አክታ ፣የደረት ውጋት ፣አየር ማስወጣትና ማስገባትን መከልከል የመሳሰለውን ጉዳት ያስከትላል፡፡ የካንሰር ሴል ወደ አጥንት ከሄደ በተለይም ጀርባ ላይ ያለው አከርካሪ አጥንት ላይ ከፍተኛ ሕመም ያስከትላል፡፡ ስለዚህ በጡት አካባቢ እብጠት እስኪያድግ መጠበቅ ሳይሆን አስቀድሞውኑ ክትትል በማድረግ እርምጃ መውሰድ ይገባል፡፡ ዋናው የጡት ካንሰር መለያ እብጠት ነው፡፡ ከዚህ ሌላ ምንም አይነት ምልክትም ይሁን ስሜት ስለሌለው አስቀድሞ ማወቅ አስቸጋሪ ነው፡፡ እብጠቱ ገና ከአንድ ሳንቲ ሜትር በታች እያለ በአንዳንድ ምርመራዎች ማወቅ ሲቻል ከአንድ እስከሁለት ሴንቲ ሜትር ሲደርስ ግን በዳሰሳ ማወቅ ይቻላል፡፡

በዚህ ደረጃ ያለ የካንሰር እጢ ገና ያልተሰራጨ እና ማዳን የሚቻል ነው፡፡ ስለዚህም ከእብጠት ውጪ ሌላ ምልክት ስለሌለው ሴቶች እድሜያቸው ከአርባ አመት ከዘለለ እብጠት ቢኖርም ባይኖርም በየአመቱ ምርመራ አድርጎ ሁኔታውን ማወቅ ያስፈልጋል የሚባለው ፡፡ እንደ ዶ/ር አበበ ፈለቀ ማብራሪያ የጡት ካንሰር ደረጃ አለው፡፡ ደረጃውም ከአንድ እስከ አራት ይከፈላል፡፡ 1ኛ ደረጃ የሚባለው የጡት ካንሰር መጠኑ እጅግ ያነሰና በጡት ላይ ብቻ ያበጠ እጢ ነው፡፡ 2ኛ ደረጃ የሚባለው የጡት ካንሰር ጡት ላይ ያለው እጢም አደግ ይላል፡፡ እንደገናም ብብት ስር እብጠቶቹ ሊዳሰሱ ይችላሉ፡፡ 3ኛ ደረጃ የሚባለው የጡት ካንሰር ጡት ላይ ያለው እጢም ትልቅ ሲሆን ብብት ስር እና ዙሪያውን ያሉት እጢዎችም በጣም ጠንንራ እና ያደጉ ሆነው ይዳሰሳሉ፡፡ 4ኛ ደረጃ የሚባለው የጡት ካንሰር ከጡትም ከብብት ስርም አልፎ ወደሌሎች የሰውነት ክፍሎች የተሰራጩ ሲሆን ነው፡፡ ከ1995ዓ/ም እና ከ2000 ዓ/ም በፊት እንደአውሮፓውያኑ የጊዜ አቆጣጠር የጡት ካንሰር አደገኛ ነበር፡፡ በቅርብ ጊዜ ግን በመላው አለም የእኛን አገር ጨምሮ የጡት ካንሰርን ማዳን ተችሎአል፡፡ ስለዚህም ደረጃ አንድ እና ሁለትን ማዳን ወይንም በደንብ መቆጣጠር ከሚቻልበት የህክምና ጥበብ ተደርሶአል፡፡ ደረጃ ሶስትና አራት ትንሽ የሚከብዱ እና ማዳን ባይቻልም እድገታቸውን ግን መግታት ተችሎአል፡፡ በሕክምናው እርዳታም ሕይወትን በደንብ ማራዘም ይቻላል፡፡ የጡት ካንሰር የህመም ስሜት የሚገለጸው ጡት ላይ እብጠት ተገኘ ከሚል በስተቀር ሌላ ምንም ስሜት የለውም፡፡

ነገር ግን አልፎ አልፎ ማለትም ከመቶ አስር ያህል ታማሚዎች ጡት ላይ የህመም ስሜት አለኝ ወይንም ወተት በሚወጣበት ጫፍ ላይ ፈሳሽ ይታየኛል የመሳሰሉትን ስሜቶች ይገለጻሉ፡፡ ከዚህም በተጨማሪ አንዳንዴ ጡት መጠኑንና ቅርጹን ቀየረ የሚሉ እና ቆዳው ላይ አንደሚፈርጥ ነገር ወይንም ደም መሳይ ነገር አገኘሁበት የሚሉ ምክንያቶችም ለሐኪም ይቀርባሉ፡፡ ይህ ሁሉ ግን በጊዜው ህክምና ከተደረገለት ምንም ችግር የለውም፡፡ ችግር አለው የሚባለው ውስጥ ውስጡን በተለያዩ አካሉች ላይ ሲሰራጭ ነው፡፡ አንዳንድ ጊዜም በጣም ችላ ከተባለ ጡቱ ላይ ያለው እጢ እያደገ ሲመጣ እዛው ጡቱ ላይ ይቆስላል፡፡ ያ ከሆነ ኢንፌክሽን በመፍጠር ሽታ ያለው ፈሳሽ እና ደም ያመጣል፡፡ ለዚህም የሚሰጠው ሕክምና ቀደም ሲል በተቀመጠው ደረጃ መሰረት አንደኛ እና ሁለተኛ ደረጃ ላይ ከሆነ ኦፕራሲዮን እንዲሁም ኬሞራፒ መስጠት እና እንደአስፈላጊነቱ የጨረር ሕክምና ማድረግ ሲሆን እንደምግብ የሚያገለግሉ ሆርሞኖች በተለይም ኢስትሮጂን የሚባለው ከሰውነት ውስጥ እንዲጠፋ የሚዋጥ መድሀኒት ይሰጣል፡፡

ይሄ ሁሉ የህክምና ዘዴ በአገራችን የሚገኝ ሲሆን ነገር ግን ሕክምናው የሚሰጠው ውስን በሆነ ቦታ ማለትም በጥቁር አንበሳ ሆስፒታል መሆኑ እንደአንድ ችግር ይጠቀሳል፡፡ ኦፕራሲዮኑ የትኛውም ሆስፒታል ሊሰጥ የሚችል ነው፡፡ በኢትዮጵያ ውስጥ ያለው ዋናው ችግር ሕክምናው ያለመኖሩ ሳይሆን ህክምናው የሚሰጥባቸው ቦታዎች ያለመስፋፋታቸው ነው ብለዋል ዶ/ር አበበ ፈለቀ /አሲስታንት ፕሮፌሰር/ የቀዶ ሕክምና ባለሙያ ፡፡

Read 10088 times
Administrator

Latest from Administrator