Saturday, 22 June 2013 11:47

እምቢኝ!

Written by  ዋሲሁን በላይ (አዋበ)
Rate this item
(1 Vote)

በእኔና በእነሱ መካከል ያለው ድልድይ ገና ጨረታ አልወጣለትም፡፡
እኔ የተፈለቀቅሁት ከገዛ ጥጥ ማሳዬ ነው፡፡
እነሱ ሊያባዝቱኝ ከንቱ ይደክማሉ፡፡
አለም ደግሞ (ቁሌታም) እንዝርት ናት፤….ለሰበቃት ጭን ምትገልጥ!....
እሷ……….
እኔ………..
እነ’ሱ…
ሥጋት ላይ ተወዝቼ እሰማለሁ እኔ…(እሷ ጆሮ ዳባ ብላለች፡፡)
እነሱ መች ያርፋሉ…ቅኝቱ እንደፈረሰ ሙዚቃ ጣም አጥተው፡፡
                         ***
ከጆሮዬ ጥግ ከዐይኔ ፊት ቆመው… “አንተ ደግሞ ሽንፈትን አሜን ብለህ ለመቀበል ትልሞሰሞሳለህ…!” ይሉኛል፡፡
ነፍሴ…እጅ እንደማትሰጥ አልገባቸውም፡፡
“ለኮረኮመህ ሁሉ ጉልበትህ እንዳገዳ ቅንጥስ የሚል ከሆነ፣ መቆምህ በራሱ መውደቅ ነው!” ይሉኛል፡፡
ነፍሴ…እጅግ ታጋሽ ሆና፣ ትዕግስትን፣ እንደመልካም ሰባኪ ከልቤ አውደምህረት ላይ ትሰብከኛለች፡፡
“መታገስ ማለት ምን ማለት ነው…! ማንን ነው ምትታገሰው…ጊዜ ጊዜ የሚሰጥህ ይመስልሃል…?! ወደ ኋላ ተመልሶ እጅህን እየጐተተ “ና” የኔ ውድ ያለፈህን አምሃ ላገናኝህ…እንዲልህ ትመኛለህ…! እ….” ወደፊት ካልተራመድክ በቆምክበት ሙጃ ይበቅልብሃል ይሉኛል፡፡…አንደኛችን በሌሎኛችን ኪሮሽ የምንደነተል ዳንቴሎች እንሆናለን…? ልክና መጠን የለንም እንዴ!
ነፍሴ….በጥሞና ትተነፍሳለች… “ተዋቸው…መሰንበት ደግ ነው በጤና ድጉስ ተለብጦ…” እያለች የትዕግስትን ጠበል ትፀብለኛለች፡፡
“ጊዜው የመንፈስም የአካልም ትግል በብርቱ የሚጠይቅ ነው!...ድከም ልፋ…ላብህን አትመልከት… ኋላ ላይ ላብህ ፍሬ ይሆናል…” ይሉኛል፡፡
ሰው ሆነን “ሰው አርገኝ እና ሰው ይግረመው” አይነት ቀሽም ጥቅስ ይጠቅሱልኛል፤ ባመንበት ቅንብብ ህይወት ደስታ ትገዛለች፡፡
ነፍሴ…”ምርጦች ፍጡር ነን” ትለኛለች፣ ነፍሴን አምናታለሁ…እሷ ግን ትጠረጥረኛለች፡፡ ከሀጢያት በቀር ሁሉም ተፈቅዷል፡፡ አውቃለሁ፡፡ ያውቃሉ። (እናውቃለን)
እኔ በቆምኩበት ልክ መቆም ሳይሆን በኔ መቆም ላይ መገኘት እስካልተቻለ ድረስ፣ ይሄ ነው ተብሎ እሚደመደም ምንም ሊኖር አይገባም፡፡
የኔ ልክ የገዛ ራሴ ብቻ ነው፡፡ ሚስቴ ራሷ በልኬ አልተሰፋችም!
(ዋስትናውን እኔ ወስዳለሁ … እኔ ነኝ ያልኩት)፡፡
ጥርሴ ላይ የተነቀስኩት (ድዴ ላይ) የተዘጋባትን ተስፋ ነው፡፡
ወሬ አይኑን ሥር ኩል በደማቁ ተኩሎ…ከንፈሩን በቀለም አሳብዶ ጆሮ ጥግ የሐጢያት ዘፈኑን ያቀነቅናል፡፡
                          ***
እንዲህ ስልቹ ሰው እንደዘመዘመው ነጠላ…ጊዜ በከፋው ቁጥር ብስክስክ እያለ ባለበት ጊዜ “ሰው” እንዴት ከለሰለሰ እና ከረሰረሰ ብሎም ደጋግሞ ከታረሰ ምቹ ገላ ላይ እየተንፈላሰሰ…ሁለት ሆኖ ወድቆ…ሶስት መሆን ያቅተዋል…? እልና…
ነፍስ…
ህሊና…
ሥጋ…
ሙግት ውስጥ ገብተው ለጠብ ሲዳረጉ መገላገል ያቅተኛል፡፡
ነፍሴ... የተበጀችበትን ጉልህ ጠብታ አባዝታ ባህር ማድረግ እንደምትችል እየገባት እንዳልገባት ሆና፣ ያልገባውን ህሊናዬን በስስ ሥጋ ተለብጦ እያየችው ትስቅበታለች፡፡ ህሊናና ሥጋ ቀለማቸው የመንታ መንገድ ነው፡፡አንድ ይሆኑና አንድ ያይደሉ…በአንድ ግንድ የበቀሉ ቅጠሎች (ልምላሜው እንደሚለያይ አይነት፡፡)
ነፍስ ከሳቀች ደግሞ ሥጋት ነው፡፡ ሥጋ በተስፋ መቁረጥ ራሱን መጐሰም ይሳነዋል፡፡
ህሊናዬ…የሚያየውን እና የሚሰማውን ለነፍሴ ከማቀበሉ በፊት በጣም ለሚወደው ስሜቴ ያማክረዋል፡፡ …ስሜቴ የወጣለት ዱርዬ ነው! (ሥጋ ቅብ ነገር) ከሴት ልጅ የተለያዩ ብልቶች የተሰራ ይመስል…ሴት” ሲባል ብቻ መላ አካሉ ዐይን ሆኖ ይባትታል፡፡ እሚያመዛዝንበት ጭንቅላትም ይሁን ልብ ስላጣ በ“ነገ” ልስልስ ምንጣፍ ለመቀመጥ “ዛሬ”ን ማጨንገፍ አይመቸውም፡፡
ስሜቴ በቅንፍ መኖር ያዘወትራል፡፡
በሥጋ ተገዢነት አንቀልባ ላይ መኖር ጅልነት ነው፡፡
ነፍሴ ግን ድሎቷን ረግጣ ጠፍንጋ ለመቀየድ እስከ ጥጉ ጥግ ድረስ ትሰደዳለች፡፡
በቆምኩበት መጠን ሳይመጠኑ…ያለ እረፍት ይወተውቱኛል፡፡
እንዳገባ…እንድወልድ…(ትዳር ስለቱ ሶስት ነው)
ቀለሙም ከቀስተደመና ያይላል…(እይታ ያሻዋልና…)
ሞኞቹ…ትዳር እንዴት ነው ሲሏቸው “በጊዜ ግባና ፍርፍር ይበዛዋል” ይላሉ፡፡ በሶስት ቀለም ባሸበረቀ ጥለት እቅፍ ውስጥ መኖር ደግሞ ጣዕሙ እንደ ኗሪውና አኗኗሪው ነው፡፡ ጣዕሙን ለመግለጽ ለማብራራት እማይችሉት እንደጡብ ድርድር ስትር ያለ፣ የማዕዘን ድንጋዩን አርአያነት መመልከት ነው። በተለያየ አቅጣጫ፡፡ ቀለሙ እንዲህና እንዲያ ይገለጣል፡፡
አንደኛ…በጋራ ህይወትን ለመኖር ነው…(እየኖርኩ እየኖርን ነን…)
ሁለተኛ…ፍትወተ ሥጋን ለመፈፀም ነው…(ለጋ ቂቤ ጣል ያለበት ጣት ሚያስልስ ፍትፍት እስኪመስለኝ(ን) ተመችቶኛል (ናል)
ሶስተኛው…ዘርን ተክቶ ለማለፍ ነው…(ማን ዘርቶ መሰብሰብ ይጠላል)…
እንግዲህ “እምቢልኝ”! ያቃተኝ ጉዳይ ይሄው ነው፡፡ ዘር ዘርቶ ፍሬ ለመልቀም መልካም ገበሬዎች የዘሩትን (ፍሬ) መመልከትም ሌላ (ፍሬ) ነው፡፡ መዝራት ያልቻሉ ደካሞች (የዘር ፍሬ) የሌላቸው…በተዘሩት፣ የዋናው ገበሬ ፍሬዎች መደመም ይችላሉ፡፡ በግድ ያለጊዜውና ያለወቅቱ በማጨጃ ጊዜ መዝራት ሳይቻልስ…በዘር ጊዜ ለማጨድ…ያለደንቡ…?!...
                                    ***
ተደባልቆባቸው…
በቆምኩበት ቦታ ላይ ያልተለኩ…ይጠዘጥዙኛል፤
ኧረ ተውኝ ወዳጆቼ…”እሺ” የሚለው ቃል ምላሴ ላይ የተነቀሰ ይመስል ያሉኝን (ያለችኝን) “እሺ” ከማለት የዘለለ ምንም አማራጭ የለኝም። “እሺ” ደግሞ ብዙ የቆሰሉ ስህተቶችን የማከም ጥበብ አለው፡፡ ያለቦታው ሲገኝ ብቻ ነው “እሺ” መረር የሚለው፡፡ ልክ ገመዱን እንደበጠሰው ጐሽ!...
“አግባ እንጂ”
“ምነው እስከዛሬ…”
“ቆሞ መቅረት አማረህ”
“አማርጣለሁ ስትል ተመርጠህ እንዳትቀር”
“አግባ…አግባ አግባ” ሲሉኝ የነበሩት ሁሉ የቡና መጠጫ ሲኒ አላዋጡም፡፡ እምንሰጠው የምንችለውን ብቻ ሳይሆን ተቀባዩም መቻል አለመቻሉን ማወቅ ይኖርብናል፡፡ ያለፈው … ሳያንሳቸው “የዳይፐር” ዋጋ መናሩን ሳያውቁ (ከዚህ ጋር አንድ የሃገሬ የፊልም ዳይሬክተር ትዝ አለኝ፡፡ ሩጫዬ በዳይፐር ነው ያለው)
“ውለድ እንጂ … ተው ኋላ ትቆጫለህ!” ይሉኛል (ናል)፡፡
ሥጋዬ (ህሊናዬም አብሯት አለ) ነጋሪት ሥትጐሥም … ነፍሴ ፀሎት ላይ ናት፡፡ (ብቻዋን ተደማ)፡፡
የዘንድሮ ልጅ እንደ እኛ ዘመን በአንሶላ ቅዳጅ የሚያድግ መሠላቸው … እንዴ …? በአንሶለ ቅዳጅ ማደጉን ቢያውቅ ፍርድ ቤት ከመገተር ወደ ኋላ አይልም፡፡ በጨርቅ አሻንጉሊት ሠርተን ብንሠጠው … ራሱን አያጠፋም …?
እኛ የኔታ ጋ በሳርም ሆነ በአሳር ካርቶን ላይ በተለጠፈች ፊደል … የዛሬ እንጀራችንን ቆጥረናል። ዳዊት … ውዳሴ ማርያም … ብዙ ሌላ ነገሮች ሸምድደናል፤ አንዳንድ በማይመለከታቸው በሆነ ባልሆነው በኩርኩም ሲቆጉን … ፊደሎቹ ከአንጐላችን ዛፍ ላይ እየረገፉ መነመኑ እንጂ፡፡
እና … የአሁን ልጅ (ትውልድ) ፊደል ያዝና በሥንጥር እየጠቆምክ “ተማር” ብንለው በሥንጥሩ አይናችንን አይጠነቁለውም…!
በምን አባቴ(ታችን)… እንዲህ አይነት ኃላፊነት ውስጥ እገባለሁ … (እንገባለን?) ፍርሃት መፍትሔ እንዳይደለ ይገባኛል ገብቶኝም ያንገበግበኛል። ይህው … ተከራይቼበት ካለሁት ጊቢ የአከራዮቼ የልጅ ልጆችና እንደኔ የተከራዩ ልጆቻቸው ሲጫወቱ … የኔ ቢጤው የወለዳቸው … “አስር አረንጓዴ ጠርሙሶች በግድግዳ ላይ…” እያሉ በዜማ ሲጫወቱ እነዛ የአመት ቀለብ መግዣ ለአንድ ወር ተከፍሎላቸው “ወዛም” ትምህርት ቤት የሚማሩት የአከራዩን የልጅ ልጆች በስጨት ብለው … “ኤጭ የምን አስር አረንጓዴ ነው … አስር ላፕቶፖች በሉ…” ሲሏቸው አብሬ ከልጆቹ ጋር ተሸማቀቅሁ … አንጀቴ ተንቦጫቦጨ … ጨዋታ ለመቀየር ብለው … “እቴሜቴ የሎሚ ሽታ …” አሁንም እነዛ “ወዛም” ልጆች ተበሳጩ “ቢዮንሴ የት ሔዳ ነው … እቴሜቴ የምትሉት…?” የጐረቤቴ ልጆች የወፍጮ ቤት ግድግዳ መሠለ ፊታቸው፡፡
እሚያውቁትን ለማለት እንኳ መብት አጡ … “በዛ በበጋ በዛ በሙቀት … እጮኛ ጠፍቶ በፍለጋ…” ግጥምና ዜማውን ሳይጨርሱት “ወዛሞቹ” እጮኛ ምንድነው …? ማለት … ለሥንቱ ጥያቄ መልሥ ይኖራል …? …
የዚህ ዘመን ትውልድ ባንድ ተቃኝቶ የተዘበራረቁ የኑሮ ዜማ የሚያወጣ … በዋለበት የትምህርትም ( ) እማይሞላ ቅንፍ አዝለን … ከፍታውን የሚያጐላ … ማን ዝቅን ይወዳል፡፡
ነፍስ …
ህሊና …
ሥጋ …
በ “እምቢኝ” ማለት ሙግት ውስጥ ቡጢ ተቧቅሠው በሥጋት የምሥቅበት ጥርሴ ረግፏል፡፡ ግማሽ ሰብዕና የት ድረስ ያስኬዳል …?
ቅድመ ጋብቻ … ጓደኛ በሽበሽ! … ወሬው ቋንጣ ፍርፍር ይመስል … ይጥም ነበር፡፡ ምክር ባይነት ባይነት እንደገፍ ይሠነዘራል … “ነበር” ባይሆን፡፡፡
የልቤ የሚሉት ጓደኛ … ልብዎን ሰጥተውት ልቡን የሚያውቁት … ካገባ በኋላ የሚስቱን ሻሽ (ተሻሽቶ) አስሮ … እንዴት አድርጋ ብታስፈራራው እንደሆነ ባልታወቀና ባልተጠና ጥናት … ለማማከርም … እንትፍ እንትፍ የሌለውን የጓደኝነት ንጡ ጠላ ለመጐንጨት በሚስት የማስፈራራት ቡጢ ትከሻው ኮስምኖ … አለመገኘትን ያዜማል፡፡ (ሚስቶች ግን ለምን እንዲህና እንዲያ ይሆናሉ…?!) “እንዴት …?” እንዳትሉኝ!
                                 ***
“አግባ እንጂ” ማግባቴን ያላወቁ፡፡
“አገባሁ እኮ” እየተሽኮረመምኩ እመልሳለሁ፡፡
“ወለድክ” ቃሉ ካፈጣጠኑ እንደ ኩርኩም ያማል፡
“አ.ል.ወ.ለ.ድ.ኩም፡፡” አቀርቅሬ በዐይኔ መሬት እየጫርኩ እመልሳለሁ፡፡
ራስን መሆን …
ራስን ማዜም …
ለራስ ጊዜ ሠጥቶ … ራስን ብቻ መቃኘት አይቻልም …?
በማወቅም ይሁን ባለማወቅ የምንወረውራቸው የቃል ጠጠሮች የብዙኃኖችን ዐይን ያጠፋሉ። የቀኙን ለግራው … የግራውን ለቀኙ ሥናደርግ የሚመጣው መንሻፈፍ አይነት!
“ለምን ታዲያ አልወለድክም እስከዛሬ…?”
“በፒን ኮድ ቆልፋው!” እላለሁ … በቀልድ እነሱን ለማሳቅ ራሴን ከማሳቀቅ ለመታደግ፡፡
እርግጥ ነው … የወንድ ልጅ ፍላጐት የፈለገ የደን ሠደድ እሣት ቢሆን በሴት ልጅ አለመፈለግ ጥቂት ምራቅ ይጠፋል፡፡
“እና ፒን ኮዱን ማወቅ አቃተህ…? ታዲያ አንተ ምኑን ወንድ ሆንከው!”
ይሔ ሥድብ ነው…? ምክር ነው…? መልካም ምኞት?...
ነፍስ … እውነቷን ለማንም አሣልፋ አትሠጥም፡፡
ህሊና … ይሉኝታ ያሸንፈዋል፡፡
ሥጋ … ልክሥክሥ ነው፡፡
ነፍስ፣ ህሊና፣ ሥጋ፣ ማንንም አትስሙ
በነቀፌታ እንቅልፍ … ደንዝዟል አለሙ፡፡
                                     ***
በታመመው ሰው አልጋ ላይ መተኛት ህመሙን መጋራት ማለት አይደለም፡፡ በባለ ጉዳዩ ሰንጠረዥ ውስጥ ማጥቆር …
እንደ ዝንጀሮ መጐርመሱን ለማወቅ እንደሚሻው፣ ባባቱ መዳፍ ምልክት መዳፉን ለክቶ ሲገጥምለት ለመጋጠም (በትዕቢት) እንደሚያጓው … ብዙ ብዙ ብንልም ህይወት እንዲህ አይደለችም፡፡
ባለመግባት ውስጥ ያለውን ነፃነት የሚያውቀው ለነፃነቱ የታመነው ነው፡፡
በመውለድና ባለመውለድ መካከል ያለው ገደል የትኛውም ተራራ ከየትም ሀገር ተነቅሎ መጥቶ ቢጠቀጠጥ አይሞላውም፡፡ ሸራፋ ደስታ አለ…? ህይወት እንዲህ አይደለችም!!!
ራስን መውለድ ይቻላል፡፡ አጥብቀው ያሰሩትን ሲፈቱት የታሰረበት ቦታ መልክ አለው፡፡ ፊት ላይ ያለ ጠባሳ ማለት ነው፡፡ እንደማይከልሉት፡፡
“እምቢኝ” የምለው (ንለው) አብረን ከሆነ … ከጥያቄው ውስጥ መልሱ አለ፡፡ በማንም ቡሃቃ ማንም ሊጥ አያቦካም፡፡ እያንዳንዱ ቡሃቃ … ልክ እና አዛዥ አለው፡፡
“እምቢኝ” ሥሜት ወለድ ምክርን!
“እምቢኝ” የሥጋት ጥሪን …!
“እምቢኝ” ብዙ ፍሬፈርስኪ ነገሮችን …!
“እምቢኝ” ቅን አልባነትን …! እምቢኝ … እምቢኝ!
“እሺ” ነፍሴን አምናታለሁ፡፡
                                  ***
ቀናት ያልፋሉ ሳምንትን ፀንሰው
ወር እየወለዱ ባመት ሊያሳድጉ፣
ዘር መተካት ብቻ ነው
የሰው ልጅ ማዕረጉ፡፡

Read 3603 times Last modified on Saturday, 22 June 2013 12:04