Print this page
Saturday, 22 June 2013 11:56

በፎቆቹ ውስጥ ጐጆ እና ዋሻ እንዳይኖሩ …

Written by  ሌሊሣ ግርማ
Rate this item
(0 votes)

                 የማደግ መብታቸው ተከብሮላቸዋል። መንገዶቹ፣ ቤቶቹ፣ የቴሌኮሙኒኬሽን አማራጮቹ፣ የገቢ እና የወጪ ልኮቹ፣ ግድቦቹ … የማደግ መብታቸው ተከብሮላቸዋል፡፡ ተይዘው ነበር፣ ደንዝዘው ነበር፣ ሞተው ነበር…የማደግ መብታቸው በሰው አማካኝነት ተከብሮላቸዋል፡፡ ከመያዝ፣ ከመደንዘዝ፣ ከመሞትም በኋላ አፈር ልሶ መነሳት ይቻላል፡፡ ለእነሱ መብታቸውን ያስከበረላቸው ያ የፈረደበት ሰውስ? የማደግ መብቱ ተከብሮለታል?... በእነዚህ በስልጡን ቤቶች ውስጥ ገብቶ እንዲኖር የታሰበው ሰው በሰለጠነ መንገድ የሚያስብ መሆን አለበት፡፡ በታደሰ ቋንቋ መናገር አለበት፡፡ ከተነሳበት እስከሚደርስበት ለመጓዝ ፈጣን መኪና ገዝቶ ፈጣን መንገድ አጥቶ ተጨነቀ፤ ጭንቀቱ መፍትሔ እያገኘ ነው፡፡ ፈጣኑን መኪና፣ በፈጣኑ መንገድ ላይ የሚያሽከረክረው የህዳሴው ዘመን ሰው፤ ከመኪናው ፍጥነት እኩል ማሰብ … ከጥያቄው ወደ መልሱ መድረስ ካልቻለ…ለአኗኗር ዘይቤው የማደግ መብትን ሰጥቶ ለራሱ ግን የነፈገ ሞኝ ሆኗል፡፡

ተሸውዷል! (ምናልባት የትራፊክ አደጋዎቹ የበዙት በዚህ ምክንያት ይሆን? የመኪናውንና መንገዱን ያህል ያልፈጠነ፣ ያልሰለጠነ፣ ያልታደሰ አሽከርካሪ እያሽከረከራቸው ይሆን?...መልሱ፡- እንዴታ! የሚሆን ይመስለኛል፡፡ ከመሰለኝ ደግሞ ነው!) በጎጆ ቤት ኑሮውን የሚገፋ ጐጆ ቤትን መሳይ (የግርግም) አስተሳሰብ ያለው ሰው መሆኑ አያጠያይቅም፡፡ (ካጠያየቀም፤ ተጠያያቂዎቹ ከጥያቄው ክብደት ጋር የማይመጥኑ ናቸው፡፡) በዋሻ ውስጥ ይኖር የነበረው የኒያንደርታይል ዝግመት ዘመን ሰው፣ ወደ ጐጆ ቤት ከገባ…እንደ መሬት አራሾቹ ገበሬዎች ራሱን አሳድጐ መኖር አለበት፡፡ መንጋት እና መምሸትን ብቻ ሳይሆን ወቅቶችንም መቁጠር መጀመር ይኖርበታል፡፡ ከቤቱ እድገት ጋር ተመሳስሎ መሰልጠን ግዴታው ነው፡፡ ካልሆነ ጐጆው ውስጥ የገባው የዋሻ አውሬነቱን ይዞ ይሆናል፡፡

ፎቅ ቤት ውስጥ ለመኖር የተዘጋጀ ትውልድን ወደ ጐጆ ወይንም ወደ ዋሻ ማስገባት አይቻልም። ኑሮው እና ነዋሪው አይመጣጠኑም፡፡ በፎቅ ቤት ቋንቋ ጐጆ ውስጥ ማውራት የሳር ቤቱ ላይ እሳት ለመለኮስ ነው፡፡ ለኩሶ ቢያቃጥለው ጥሩ ነው፤ የሚመጥነውን ቤት በፋንታው ይሰራል፡፡ በዚህ እይታ የእድገትን ነፃነት እንደ አርዕስት አንስተን መወያየት እንችላለን፡፡ የከተማ መልክ ያወጣ ሰው ፊት፣ ከተማውን መስሎ መኖር መቻሉን የፊቱ ስልጡንነት አመልካች ነው፡፡ ከተማ ውስጥ ኩታ እና ተነፋነፍ አድርጐ የሚዞር ሰው እየኖረ ያለው በድራማ እስክሪፕት ውስጥ ነው፡፡ የድራማ እስክሪፕቱም “ትራጃይክ ኮሜዲ” ተብሎ ይጠራል፡፡ የፈረንሳዩ ፈላስፋ ዴካርት እና በጊዜው የነበሩ ተከታዮቹ (Such as cordemey) አንድ ፍጡር መስተሐልይ እንዳለው ማረጋገጥ የሚቻለው (በአይን ከሚታየው የራስ ቅሉ ባሻገር) የቋንቋ አጠቃቀሙ ላይ ነው፡፡ አዳዲስ ሀሳብን እና ሐሊዮቶችን የሚገልጽ እና ገለፃውን መሸከም የሚችል ቋንቋ ሲኖረው ነው፤ ይላሉ፡፡ ከዴካርት እና ካርቲዣኖቹ ጋር ካልተስማማን ጃጄ ሩሶ ይጨምርበታል፡፡

“የሰው ልጅ የማንነቱ ብቸኛ መለያ ራሱን ማሻሻል እና ወደ ፍፁምነት ለመድረስ መሞከርን መቻሉ ነው” ይላል፡፡ “Faculty of self – perfection which with the aid of circumstance, successively develops all the others, and resides among us as much in the species as in the individual” ራስን እና የሰው ልጆችን ወደ ፍፁማዊነት መምራት የባህላዊ ህዳሴን በማካሄድ የሚለው ሃሳብ በዴካርት አልተጠቀሰም፡፡ የተጠቀሰው በ “ሩሶ” ነው፡፡ የሁለቱን ፈላስፎች እይታ ጨርፌ ማቅረቤ ማረጋገጫ ይሆነኛል ብዬ አይደለም፡፡ ማጣቀሻ ወይንም መንደርደሪያ እንጂ ለሌላ አይሆኑም፡፡ ምክንያቱም እነዚህ ፈላስፎችም ዘመናዊ ፍልስፍና ከደረሰበት ስልጣኔ አንፃር እንደ ጐጆ ቤት የሚታዩ ናቸው፡፡ ነገር ግን ከእነዚህ ጐጆ ቤቶች ተነስተው ነው ምዕራባዊያኑ ወደ ሰማይ ጠቀስ የአስተሳሰብ ህንፃዎቻቸው የተሸጋገሩት፡፡ እኛም እስቲ እንደነሱ ለሙከራ ያህል እናስብና ወደ ዘመናዊ ስልጣኔያችን ይዘን የምንገባቸውን ቋንቋዎች እንፈብርክ፡፡ ኃይል ማመንጫዎቻችን የሚያመነጩትን ሜጋ ዋት የሚመጣጠኑ ሐሳቦችን የሚያመነጩ ቋንቋዎችን፡፡ ግን እንዴት ነው የምፈበርከው? … ነፃነት ከሌለ። አዳዲሶቹ መንገዶች እና ፎቆች ከዛጉ ቆርቆሮ ቤትነታቸው እንዲያድጉ የተደረጉት የማደግ ነፃነት ተሰጥቷቸው ነው፡፡ ቋንቋ እንዲያድግም ነፃነት ያስፈልገዋል፡፡

ቋንቋ ማለት ሀሳብ ነው፡፡ የሐሳብ እድገት በነፃነት ብቻ ይመጣል፡፡ ፎቆቹ እንዲያድጉ፣ ካለማደግ ባርነት ሰንሰለታቸውን እንደ ጤዛ በትኖ የለቀቃቸው አካል፤ ቋንቋንም እንዲያድግ መፍቀድ አለበት፡፡ በቋንቋ፣ በማሰብ፣ ራስን በመግለጽ፣ በመወያየት፣ በመቃወምና በመስማማት…ውስጥ ነፃነቱን ይቀዳጃል፡፡ ቋንቋ ነፃ ከተለቀቀ ማደጉ አይቀርም፡፡ ማደጉ የአእምሮ ማደግንም ጠቅልሎ ነው፡፡ የሚያድገው ደግሞ ፎቆቹ ወዳደጉበት አቅጣጫ መሆኑ አያጠራጥረኝም፡፡ ከተማው የማደግ ነፃነቱ ሲከበርለት ፎቅ ሆኖ ከበቀለ…የከተማ ነዋሪው አስተሳሰብ የማደግ ነፃነት (ራሱን በነፃነት በመግለጽ) ረገድ ክብር ሲሰጠው ወደ ጐጆ ቤት ወይንም ወደ ጫካ(ፍሬ ለቀማ) ኑሮ የሚገባ አይመስለኝም፡፡ በዋሻ ውስጥ አውሬ ሆኖም አይጮህም፡፡ ወደ ኋላ የሚያድግ አይመስለኝም፤ ካደገ ግን ከፍተኛ አይ - አዎ (Paradox) ነው የሚሆነው፡፡ አንድም፡- ፎቅ ቤት፤ እና መንገድ፤ እንደዚሁም ግድብ… ስልጣኔ አይደሉም፤ ወይንም ስልጣኔ ለደሀ ህዝብ አያስፈልግም ማለት ነው፡፡ ደሀ ምን ማለት እንደሆነ ድህነትን ብንጠይቀው ይነግረናል፡፡

እድገት ስልጣኔ ነው፡፡ እድገት ያስፈልጋል ማለት የሰው ልጅ ያስፈልጋል ማለት ነው፡፡ የሰው ልጅ ታሪክ የእድገት እና የስልጣኔ እንደመሆኑ መጠን፡፡ ስለዚህ የፎቅ መብቀል ክፉ ነገር ሊሆን አይችልም፡፡ ክፉ የሚሆነው ወደ ፎቅ ቤቱ ይዘን የምንገባው የድሮ ኋላቀርነታችንን በጥንቱ የአስተሳሰብ አንቀልባችን አዝለን ከሆነ ነው፡፡ የአስተሳሰብ ስልጣኔ በእውቀት ብቻ ይጨበጣል፡፡ እውቀት፤ ….ቃላትን ወደ ቋንቋ፣ ቋንቋን ወደ ሃሳብ፣ ሃሳብን ወደ ሐሊዮት፣ ሐሊዮትን ወደ ሙከራና ተግባር በመቀየር የሚገኝ ነው፡፡ በድሮ እውቀት የምንቀረው የድሮው ማንነታችን ውስጥ ነው፡፡ አዲስ እውቀት ላይ ደርሰን የሰራነው ህዳሴ እንዲስማማን … ሃሳባችንን ከስልጣኔው ፍጥነት ልክ ማስማማት አለብን፡፡ ቁሳቁሶች እንዲሻሻሉ በተሰጣቸው ነፃነት አንፃር የማሰብ መብትም ነፃ ቢሆኑልን ምኞቴ ነው፡፡ ለ “ሁሉም በጄ ሁሉም በደጄ” ማመልከቻ አቀርባለሁ፡፡

Read 1768 times