Saturday, 19 November 2011 13:51

የገጠር ህፃናት ችግር ልዩ ትኩረት ይፈልጋል ተባለ

Written by  መታሰቢያ ካሣዬ
Rate this item
(0 votes)

ጥናቱ ከተካሄደባቸው 3ሺ ህፃናት መካከል 78 ያህሉ ሞተዋልበህፃናት ድህነት ተለዋዋጭ ገፅታ ላይ ጥናት በማድረግ የማሻሻያ እርምጃዎችን ለመውሰድ እንዲያስችል ታስቦ “ያንግ ላይቭስ” በተባለ ድርጅት የተደረገ ጥናት፤ የገጠር ህፃናት ችግር ከከተማ ህፃናት ችግር የባሰ መሆኑን ያመለከተ ሲሆን የጥናቱ ውጤት ትላንት ለህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አባላት ተገለፀ፡፡ በኢትዮጵያ ልማት ምርምር ኢንስቲቲዩት ውስጥ በሚገኘው የ”ያንግ ላይቭስ” የምርምር ቡድን የተደረገው 3ኛ ዙር የዳሰሣ ጥናት እንደሚያመለክተው፤ በህፃናቱ ህይወት ላይ መሻሻሎች ቢኖሩም በቂ ሊባሉ የሚችሉ አይደሉም፡፡ ለህፃናቱ የሚሰጠው የትምህርት አቅርቦት ጥራት አሣሣቢ እንደሆነ የጠቆመው ጥናቱ፤ መንግስት በመዋእለ ህፃናትና በመጀመሪያ ደረጃ ትምህርቶች ላይ ትኩረት ማድረግ እንደሚገባው አመልክቷል፡፡

አዲስ አበባን ጨምሮ በትግራይ፣ በአማራ፣ በኦሮሚያና በደቡብ ክልሎች ውስጥ በተመረጡ 26 አካባቢዎች በተሰባሰቡ 3000 ህፃናት ላይ የተደረገውን ጥናት አስመልክቶ የጥናቱ ዋና አስተባባሪ ረዳት ፕሮፌሰር ጣሰው ወልደሃና ሲናገሩ፤ ጥናቱ በህፃናቱ ጤና፣ የዕድገት ደረጃና የትምህርት አቀባበል ችሎታ ላይ ትኩረት አድርጐ መካሄዱንና በአማካይ ደረጃ ካሉ የኢትዮጵያ ቤተሰቦች ጋር ሲነፃፀሩ የባሰ ድሃ በሚባሉና የምግብ እጥረት ባለባቸው ዝናብ አጠር አካባቢዎች ውስጥ በሚገኙ ህፃናት ላይ ያተኮረ መሆኑን ጠቁመዋል፡፡ ቡድኑ በህፃናት ላይ የሚያደርገውን ጥናት የጀመረው በ1993 ዓ.ም ሲሆን ዕድሜያቸው ከስድስት ወር እስከ አስራ ስድስት ወር የሆናቸው 1ሺ999 ህፃናትና ዕድሜያቸው ከ7.5 እስከ 8.5 ዓመት ድረስ የሆናቸው 1000 ህፃናትን አካቷል፡፡ በመጀመሪያው ዙር የጥናት ዳሰሳ ላይ ከነበሩት ህፃናት መካከል 78 ያህሉ ለ3ኛው ዙር የዳሰሳ ጥናት ለመድረስ ሣይችሉ ቀርተዋል፡፡ ለዚህም ዋነኛው ምክንያት የተለያዩ በሽታዎች፣ የተመጣጠነ ምግብ እጥረትና የንፁህ ውሃ አቅርቦት ማጣት እንደሚገኙበት ተጠቁሟል፡፡ በህፃናቱ ላይ በመጀመሪያው ዙር የተደረገው ጥናት በ3ኛው ዙር ላይ ያሳየውን መሻሻል አስመልክቶ ረዳት ፕሮፌሰር ጣሰው ሲናገሩ፤ ለእድሜያቸው የሚመጥን ቁመት ላይ ባለመድረስ ክፉኛ የተጠቁ ህፃናት ቀላል የማይባል መሻሻልን አሳይተዋል፡፡ ይሁን እንጂ ህፃናቱ ወደፊት ተገቢውን ዕድገት እንዲያሳዩ አልሚ ምግቦችን ከወዲሁ ማግኘታቸውን ማረጋገጥ ወሳኝ ጉዳይ ነው፡፡ ችግሩም ከከተሞች ይልቅ በገጠር ከፍተኛ ሆኖ ታይቷል፡፡ ጥናቱ በተደረገባቸው አካባቢዎች በሀብት ደረጃ፣ ፍጆታና ድህነት፣ የአገልግሎቶች ተደራሽነት፣ ጤናና አልሚ ምግብ እጥረት፣ የትምህርት አቅርቦት፣ የህፃናት ሥራና የጊዜ አጠቃቀም እንዲሁም የግል ደህንነት ላይ ህፃናቱ ያሉበትን ደረጃ ለማየት ተሞክሯል፡፡ “ያንግ ላይቭስ” በኢትዮጵያ፣ በህንድ፣ በፔሩና በቬትናም ውስጥ ባሉ ህፃናት የድህነት ተለዋዋጭ ገፅታ ላይ ምርምር በማካሄድ ላይ የሚገኝ ፕሮጀክት ነው፡፡

 

Read 4567 times Last modified on Tuesday, 22 November 2011 14:00