Saturday, 29 June 2013 11:11

የብሔራዊ ባንክ ክበብ ሠራተኞች በደል እንደሚፈፀምባቸው ተናገሩ

Written by 
Rate this item
(1 Vote)

የብሔራዊ ባንክ ክበብ ሠራተኞች በደል እንደሚፈፀምባቸው ተናገሩ የብሔራዊ ባንክ ክበብ አስተዳደር፣ በሠራተኞቹ ላይ በደል እንደሚፈፅምና ያለ ህግና ማስጠንቀቂያ ከሥራ እንደሚያባርር በደል ደረሰብን ያሉ የክበቡ ሠራተኞች ገለፁ፡፡ የባንኩ የሠራተኞች ክበብ ከባንኩ ሠራተኞች በተጨማሪ ለውጭ ተጠቃሚዎች አገልግሎት በመስጠት እንዲሁም የሠርግ ፕሮግራሞችን በማዘጋጀት ላለፉት 20 ዓመታት ሲሠራ የቆየ ሲሆን በክበቡ ውስጥ በተለያዩ ሙያዎች ተቀጥረው በቋሚነት ሲያገለግሉ የቆዩ 92 ሠራተኞች ለረዥም ዓመታት ዕድገትና የደሞዝ ጭማሪ አግኝተው እንደማያውቁ ምንጮች ይናገራሉ፡፡ የአመት እረፍት፣ የህመም ወይም የወሊድ ፈቃድ የሚባል ነገር ያልተለመደና እንደ መብትም እንደማይቆጠር ነው በቅርቡ ከስራቸው የተባረሩ የክበቡ ነባር ሠራተኞች የገለፁት፡፡

ሠራተኞቹ በህመምና በሐዘን ምክንያት ከሥራቸው ሲቀሩ በጥበቃ ሠራተኞች ወደ ውስጥ እንዳይገቡ እንደሚከለከሉና በሥራ ላይ እያሉ ለሚደርስባቸው አደጋና የአካል ጉዳት ምንም ዓይነት ህክምና እንደማያገኙ ተናግረዋል፡፡ በሥራ ላይ እያለች እግሯ ላይ ቢላ ወድቆ በደረሰባት ጉዳት ለከፍተኛ ህመም የተዳረገችው የክበቡ ሠራተኛ፤ ከጉዳቷ ጋር በተገናኘ የሥራ ገበታዋ ላይ ባለመገኘቷ ደሞዟ እንደተቆረጠባት ሠራተኞቹ ይናገራሉ፡፡ ሌለው የክበቡ ሠራተኛም ፔርሙዝ ይዞ ደረጃ ላይ ሲወጣ ተንሸራቶ በመውደቁ እግሩ ቢሰበርም የሰበረውን ፔርሙዝ ሂሣብ እንዲከፍል ተደርጐ ከሥራ መሰናበቱን እነዚህ ሠራተኞች ይገልፃሉ፡፡ በክበቡ ውስጥ ለ15 ዓመታት በወጥ ቤት ኃላፊነት የሰሩትና ከህግና ስርዓት ውጭ ያለ ማስጠንቀቂያ የተባረሩት አቶ ቀፀላ ተሾመ፤ የበዓላት ቀናትን ጨምሮ የተለያዩ የትርፍ ጊዜ ሥራዎችን ቢሠሩም የሚያገኙት የትርፍ ሰዓት ክፍያ በሰዓት 3 ብር ብቻ እንደነበር ተናግረዋል፡፡

ያለ አንዳች ማስጠንቀቂያ ከሥራ ገበታቸው ላይ እንዲታገዱ ከተደረጉ በኋላም ወደ ውስጥ ገብተው ዕቃቸውን ለማውጣት እንኳን መከልከላቸውን የገለፁት አቶ ቀፀላ፤ ቀሪ ደመወዛቸውን ለመውሰድ ወደ መ/ቤታቸው ቢሔዱም ወደ ውስጥ መግባት እንደማይችሉ ተነግሮዋቸዉ፣ ገንዘብ ከፋይዋ ውጪ ድረስ ወጥታ እንደከፈለቻቸው ተናግረዋል፡፡ ከአቶ ቀፀላ ተሾመ ጋር ከሥራ ከታገዱት ሠራተኞች መካከል ወ/ሮ ሰላም አማኑኤል እና ወ/ሮ መሠረት ደምሴ በበኩላቸው፤ የክበቡ አስተዳደር ለሠራተኛው ደንታ የሌለውና የሠራተኛውን መብት ለማክበር ፈፅሞ የማይፈልግ መሆኑን ጠቁመው፤ መብቱን የጠየቀ ሠራተኛ እጣ ፋንታው ከሥራ መታገድ ብቻ እንደሆነ ተናግረዋል። በክበቡ ውስጥ ለሃያ ዓመት የሠሩ ሠራተኞች ቢኖሩም ሁሉም ሠራተኛ ቋሚ አይደለም እየተባለ ኃላፊዎች በፈለጉት ጊዜና ሰዓት ከሥራው ሊያፈቅናሉት እንደሚችሉ ስለሚያስፈራሩ መብታቸውን ለማክበር ወደ ፍርድ ቤት የሚሄዱ ሠራተኞች አለመኖራቸው፣ ለሃላፊዎቹ የልብ ልብ ሰጥቶ እንደፈለጉ እንዲገዙን አድርጓቸዋል ብለዋል - ተበዳዮቹ፡፡ የሠራተኞቹን ቅሬታ አስመልክቶ ምላሽ እንዲሰጡን የክበቡን የሥራ ኃላፊዎች ለማግኘት ባደረግነው ጥረት ከብዙ እንግልት በኋላ የክበቡ ሥራ አስኪያጅ አቶ ታደሰ መሰረትን ብናገኝም ጥያቄዎችን ማቅረብ ከመጀመራችን “ሥራችንን እያወካችሁ ነው” በማለት በጥበቃ ሠራተኞች ከቢሮአቸው ተገደን እንድንወጣ አድርገዋል፡፡

Read 4505 times