Saturday, 20 July 2013 09:54

“B787” የከፋ ችግር የለውም ተባለ

Written by 
Rate this item
(1 Vote)

የቦይንግ ኩባንያ ዘመናዊ ምርት የሆነው የኢትዮጵያ አየር መንገድ ድሪም ላይነር አውሮፕላን (“B787”) ባለፈው አርብ ለንደን ደርሶ ካረፈ በኋላ ጭራው አካባቢ እሳት ተነስቶበት መለብለቡ የሚታወስ ሲሆን፤ የቃጠሎው መነሻ ከሬዲዮ መገናኛ አንቴና ጋር የተያያዘ እንደሆነ በምርመራ ተረጋገጠ፡፡ የእንግሊዝ የአየር አደጋ ምርመራ ክፍል ትናንት ባወጣው ሪፖርት፤ ከአውሮፕላኑ ጭራ አካባቢ የተተከለው አንቴና በመደበኛ በረራ ላይ አገልግሎት የማይሰጥ መጠባበቂያ አንቴና መሆኑን ገልጿል፡፡ የራሱ አነስተኛ ባትሪ ጋር የተገጠሙ አንቴና ላይ በሽቦዎች መጠላለፍ አልያም ባትሪው ላይ በተፈጠረ አንዳች እክል እሳት እንደተፈጠረ የምርመራ ክፍሉ ገልፆ፤ በተጨማሪ ምርመራ ትክክለኛው መንስኤ ከነመፍትሔው እስኪታወቅ ድረስ፣ መጠባበቂያውን አንቴና ለጊዜው በማላቀቅ አውሮፕላኖች ያለ ስጋት መብረር ይችላሉ ብሏል፡፡

አዲሱና ዘመናዊው ድሪም ላይነር (“B787”) ከወራት በፊት በዋናው የባትሪ ማስቀመጫ ቦታ እሳት በመነሳቱ፣ በመላው አለም ሁሉም “B787” አውሮፕላኖች ከበረራ ታግደው መቆየታቸው ይታወሳል፡፡ ባትሪው ላይ የዲዛይን ማሻሻያ ተደርጐ አውሮፕላኖቹ ወደ በረራ ከተመለሱ በኋላ እንደገና ተጨማሪ ችግር መፈጠሩ የቦይንግ ኩባንያን እና እንደ ኢትዮጵያ አየር መንገድ የ (“B787”) ቀዳሚ ተጠቃሚ ደንበኞች በእጅጉ አሳስቧቸው ነበር፡፡ ባለፈው አርብ የተፈጠረው ችግር ለክፉ የሚሰጥ እንዳልሆነ በምርመራ ተረጋግጦ ትናንት በይፋ ከተነገረ ወዲህ፣ የቦይንግ የአክሲዮን ዋጋ ወዲያውኑ እንዳንሰራራ ተገልጿል፡፡

Read 16957 times Last modified on Saturday, 20 July 2013 10:09