Saturday, 27 July 2013 14:36

የማንዴላ ፊልም ከወር በኋላ ለእይታ ይቀርባል

Written by 
Rate this item
(0 votes)

“ኤ ሎንግ ዎክ ቱ ፍሪደም” በተሰኘው የኔልሰን ማንዴላ ግለታሪክ መፅሃፍ ላይ ተመስርቶ የተሰራው አዲስ ፊልም ከወር በኋላ በመላው ዓለም መታየት እንደሚጀምር ተገለፀ፡፡ ፊልሙ የደቡብ አፍሪካውያንን የነፃነት ትግል ለመላው ዓለም ለማስተዋወቅ ታልሞ የተሰራ ነው ተብሏል፡፡
በጉበት ኢንፌክሽን በጠና ታመው በሆስፒታል ህክምና ሲደረግላቸው የቆዩት ኔልሰን ማንዴላ፤ ከሳምንት በፊት 95ኛ ዓመት የልደት በዓላቸው የተከበረላቸው ሲሆን አሁን ከህመማቸው ማገገማቸው ታውቋል፡፡
“ማንዴላ፡ ኤ ሎንግ ዎክ ቱ ፍሪደም” በሚል ርእስ በተሰራው ፊልም ላይ የማንዴላን ገፀባህርይ የሚተውነው እንግሊዛዊው ተዋናይ ኤድሪስ ኤልባ እንደሆነ ታውቋል፡፡ የ40 ዓመቱ ኤዲሪስ ኤልባ በፊልሙ ላይ ልዩ የትወና ብቃት እንደሚያሳይ ከወዲሁ የተነበየው ዘ ጋርድያን፤ ይሄም ለኦስካር ሽልማት ሊያሳጨው እንደሚችል ግምቱን አስፍሯል። “ማንዴላ፡ ኤ ሎንግ ዎክ ቱ ፍሪደም” የተሰኘው ፊልም በነፃነት ታጋዩ የልጅነት፤ የአስተዳደግና የትምህርት ሁኔታ እንዲሁም የ27 ዓመታት የእስር ቆይታ እና ደቡብ አፍሪካን በፕሬዝዳንትነት እስከመሩበት ጊዜ ድረስ ያለውን ሂደት የሚተርክ መሆኑን “ዘ ስዌታን” ጠቁሟል፡፡ እ.ኤ.አ በ1994 ዓ.ም በማንዴላ ተፅፎ ለንባብ የበቃው ግለ ታሪክ መፅሃፍ በመላው ዓለም ከ15 ሚሊዮን በላይ ቅጂዎች እንደተሸጡ ለማወቅ ተችሏል፡፡

Read 2278 times