Saturday, 07 September 2013 11:07

“..የነበራት ባልም ይፈታታል... ሌላ ባልም...”

Written by 
Rate this item
(5 votes)

“...እስከአሁን የማልረሳው አንድ አጋጣሚ አለኝ፡፡ አንዲት እናት በቤትዋ ሳለች ምጥ ጀምሮአታል፡፡ ከዚያም ይበልጥ ስትታመምባቸው እኔ ወዳለሁበት በሲዳማ ዞን ቦና ዙሪያ ወረዳ ባለው የጤና ጣቢያ ያመጡአታል፡፡ እኔም ስመለከታት የማህጸን መተርተር ደርሶባታል፡፡ አጋጥሞኝ ስለማያውቅ እጅግ በጣም ነበር የደነገጥኩት፡፡ በእርግጥ በኦፕራሲዮን ማህጸንዋ ይወጣል። ነገር ግን እሱም እርምጃ ቢወሰድ እና ሕይወቷ ቢተርፍ ማህጸንዋ ሲወጣ ወደፊት ልጅ መውለድ ስለማትችል ባለችበት ሕብረተሰብ አስተሳሰብ የምትገለል ትሆናለች፡፡ ምክንያቱም ልጅ ለወደፊቱ መውለድ ስለማትችል የነበራት ባልም ይፈታታል... ሌላ ባልም አያገባትም፡፡ በህብረተሰቡም ዘንድ ተቀባይነት ስለማይኖራት ዝም ብላ የምትኖር ትሆናለች፡፡ይሄንን ነገር ዛሬ ላይ ሳስበው ይቆጨኛል፡፡ ምክንያቱም እንደአሁኑ እውቀቱ ቢኖረኝ ኖሮ ወደከፍተኛ ሕክምና ጊዜ ሳልፈጅ አስተላልፌ በሴትየዋ ላይ የደረሰው ችግር ሊቃለል ይችል ነበር…”
ከላይ ያነበባችሁት ገጠመኝ ከአንድ የጤና መኮንን የቀረበ ነው፡፡ የጤና መኮንኑን ያገኘነው በሐዋሳ በኢትዮጵያ የጽንስና ማህጸን ሐኪሞች ማህበር እና በዞኑ የጤና መምሪያ እንዲሁም በፕላን ኢንተርናሽናል ኢትዮጵያ ትብብር WATCH (women & their child health) የእናቶችና ሕጻናት ጤናን ለማሻሻል በተነደፈው ፕሮጀክት ድጋፍ ስልጠና ሲወስድ ነበር፡፡ በኢትዮጵያ የጽንስና ማህጸን ሐኪሞች ማህበር WATCH (women & their child health) የተሰኘው ፕሮጀክት አስተባባሪ የሆኑት አቶ ቢንያም ጌታቸው እንደሚገልጹት ድጋፍ የሚገኘው ከካናዳ የጽንስና ማህጸን ሐኪሞች ማህበር ሲሆን በዋናነት የሚሰራውም የእናቶችን እና ሕጻናትን ሞት መቀነስ ነው፡፡ ስለዚህም ከዚህ ማህበር ጋር በመተባበር የኢትዮጵያ የጽንስና ማህጸን ሐኪሞች ማህበር Basic emergency obstetric & new born care (መሰረታዊ የሆነ አጣዳፊ የእናቶችና የህጸናትን ሞት መቀነስ) የሚባለውን የስራ እንቅስቃሴ ስልጠና እና ለጤና ጣቢያዎች የአቅም ድጋፍ የማድረግ ስራ እየሰራ ይገኛል፡፡ የWATCH ፕሮጀክት በኢትዮጵያ ውስጥ በሶስት ክልል ውስጥ በሚገኙ 8/ ስምንት ወረዳዎች ተግባሩን እያከናወነ ሲሆን ይኼውም በደቡብ ሲዳማ ዞን፣ በኦሮሚያ ጅማ ዞን፣ በአማራ ክልል በሰሜን ወሎ ዞን ነው፡፡
በካናዳ የጽንስና ማህጸን ሐኪሞች ማህበር አማካኝነት በተዘረጋው በዚህ ፕሮጀክት ከውጭ በመጡ ባለሙያዎች የኢትዮያ የጽንስና ማህጸን ሐኪሞች ማህበር አባል ለሆኑ ከፍተኛ ሐኪሞች ስልጠና ተሰጥቶ የነበረ ሲሆን እነዚህ የሰለጠኑ ባለሙያዎችም ከተለያዩ ወረዳዎች ለመጡ የጤና ባለሙያዎች መሰረታዊ የሆነ አጣዳፊ የእናቶችና የህጸናትን ሞት በመቀነስ ረገድ ክህሎትን እያስጨበጡ ይገኛሉ ብለዋል የፕሮጀክቱ አስተባባሪ አቶ ቢንያም ጌታቸው፡፡
በማሰልጠን ተግባር ላይ ከተሰማሩት የጽንስና ማህጸን ሕክምና እስፔሻሊስትና በሐዋሳ ዩኒቨርሲቲ መምህር የሆኑት ዶ/ር ይፍሩ ብርሀን እንደሚሉት ለእናቶች ሞት ምንክያት የሚሆኑት ነገሮች በሶስት ወይንም በአራት ሊከፈሉ ይችላሉ፡፡
1/ እናቶችና ቤተሰቦቻቸው የጤና አገልግሎት ለማግኘት አለመፈለግ፣
እነዚህ እናቶች የጤና ችግር ሲያጋጥማቸው በአካባቢው አዋላጅ ነርሶች አማካኝነት ለመውለድ መዘጋጀት ወይንም ምንም ክትትል አለማድረግ እንዲሁም የጤና ችግር ሲገጥማቸው በአፋጣኝ ወደ ጤና ተቋም ወይንም ሆስፒታል አለመምጣት ነው፡፡
2/ በሚኖሩበት አካባቢ የህክምና አገልግሎት የሚሰጥ ተቋም አለመኖር ፣
3/ ወደጤና ተቋም ከመጡ በሁዋላ የጤና ባለሙያው የደረሰባቸውን ችግር ለይቶ አለማወቅ፣...ይህ በአሁኑ ወቅት እንደከፍተኛ ችግር የሚቆጠር ነው፡፡ ምክንያቱም ይህ የሚያሳየው የእውቀት ችግር መኖሩን ሲሆን በዚህም ምክንያት ለእናቶቹ በጊዜው አስፈላጊው ሕክምና የማይሰጥ እና ወደከፍተኛ ሕክምና እንዲተላለፉ አለመደረጉን ነው፡፡ አንዳዶች ሕመም ሲጠናባቸው ወደአቅራቢያው ጤና ተቋም ሲሄዱ በዚያ በሚፈጠረው አላስፈላጊ መዘግየት ምክንያት ሕይወታቸው ከአደጋ ላይ ይወድቃል፡፡ አልፎ አልፎም አግባብ ያልሆነ ሕክምና የሚሰጥበት አጋጣሚ ስለሚኖር ይህንን ክፍተት የሚሞላ አሰራር መኖር አለበት፡፡ ስለዚህም እስከአሁን ባየነው የስልጠና ሂደት ሰልጣኞቹ ሲመጡ የነበራቸው የእውቀት ደረጃ እና ሲጨርሱ የሚኖራቸው ደረጃ በጣም ይለያያል ብለዋል ዶ/ር ይፍሩ ብርሀን፡፡
ሌላው አሰልጣኝ ዶ/ር እንዳለ ሲሳይ ይባላሉ፡፡ ዶ/ር እንዳለ በሐዋሳ ዩኒቨርሲቲ የማህ ጸንና ጽንስ ሐኪምና አስተማሪ ናቸው።
“...ይህ ሆስፒታል ሪፈራል ሆስፒታል ስለሆነ ከሌሎች የህክምና ተቋማት የተላኩ ታካሚ እናቶችን ያስተናግዳል፡፡ ነገር ግን በአብዛኛው የሚመጡ እናቶችን ለማዳን በጣም ፈታኝ የሚሆን ሲሆን ይህም ወደሆስፒታሉ የሚልኩ የጤና ተቋማት ጊዜን በአግ ባቡ አለመ ጠቀማቸው ነው፡፡ ለባለሙያዎቹ ስልጠና የሚሰጠው በሚሰሩበት ጤና ተቋማት ባላቸው አቅም ሊያክሙ የሚችሉትን እንዲያክሙና ከአቅማቸው በላይ የሆነውን ግን ጊዜ ሳይ ፈጁ ወደከፍተኛ ሕክምና እንዲልኩ የሚያስችል ነው። ምን አይነቱ የጤና ችግር በጤና ጣቢያ ሊታከም ይችላል? የሚለውን የመለየትና አቅምን የማወቅ ክህሎት አብሮ በስል ጠናው ይሰጣል፡፡ በእርግጥ ስልጠናው አዲስ እውቀትን ከመስጠት የሚጀምር ሳይሆን የነበራቸውን እውቀት እንዴት በስራ ላይ እንደሚያውሉት አቅጣጫ የሚያሳይ ነው፡፡ ነገር ግን ሰልጣኞች አንዳንድ ጊዜ በሚሰጣቸው የልምምድ ተግባር አድናቆት ሲያሳዩ ይታያሉ፡፡ ምክንያቱም በተግባር እንዴት እንደሚፈጽሙት አያውቁምና ነው፡፡ አንዲት እናት እነርሱ ወዳሉበት ጤና ተቋም ስትመጣ በምን መንገድ እንደሚረዱዋት ወይንም በፍጥነት ወደከፍተኛ ህክምና ተቋም እንደሚልኩዋት ሳይንሳዊ በሆነ መንገድ ያለውን አሰራር በሚያዩበት ጊዜ እንደ አዲስ ትምህርቱን ሲቀበሉ ይታ ያሉ፡፡ ይህ ማለት ቀደም ብሎ የነበራቸው ልምድ ምን ያህል እንደነበርና አሁን ምን ያህል እውቀት እንዳገኙ የሚያሳይ ስለሆነ በተዘዋዋሪ መንገድ ክፍተት እንደነበረ የሚያ ረጋግጥ ነው፡፡ ልምምድ የሚያደርጉት በሞዴልነት በተሰሩ የሰውነት ክፍሎች ሲሆን ወደሰው ከመቅረባቸው በፊት ተገቢውን ያህል ስራ እንዲሰሩ ይደረጋል። ከዚያም ወደሆ ስፒታሉ በመግባት ከባለሙያዎች ጋር በመሆን ሰዎችን እንዲረዱ ይደረጋል፡፡ በዚ ህም ከቀን ወደቀን የመስራት ፍላጎትና ብቃታቸው እያደገ ሲሄድ ይስተዋላል፡፡ ስለ ዚህ ስል ጠናው የብዙ እናቶችና ሕጻናት ሕይወት እንዲተርፍ ያስችላል የሚል እምነት አለ ብለዋል ዶ/ር እንዳለ ሲሳይ፡፡
ከሲዳማ ዞን ሸበዲኖ ወረዳ የመጣ ክሊኒካል ነርስ ቀደም ሲል በስራው አለም የገጠ መውን ሲያስታውስ፡-
“...እኔ በምሰራበት ጤና ተቋም አንዲት እርጉዝ ሴት ከእግር እስከራስዋ እየተንቀጠቀጠች እራስዋን ስታ በሰዎች ሸክም ትመጣለች፡፡ እርግዝናው ቀኑን የገፋ ነው፡፡ አብረዋት የመጡ ቤተሰቦችዋ እርስ በእርስ አልተስማሙም፡፡ ገሚሱ የቤት ጣጣ ነው ይላል፡፡ ገሚሱ ደግሞ ለጸበሉ ይደረስበታል መጀመሪያ ሐኪም ይያት ይላል፡፡ እኔ ግን እንደዚያ አይነት ነገር አይቼ ስለማላውቅ ግራ ገባኝ፡፡ ነገር ግን ለማንኛውም ብዬ... ግፊትዋን ስለካ ደምዋ በጣም ከፍ ብሎአል፡፡ በጊዜው ለእሱ የሚሆን መድሀኒትም አልነ በረኝም፡፡ ጊዜ ወስጄ...ያለውን ነገር ፈላልጌ እንደምንም ሰጥቼ በስተመጨረሻው እጄ ላይ ሳትሞትብኝ ወደሆስፒታል ይዘው እንዲሄዱ አደረግሁኝ፡፡ ነገር ግን ሆስፒታል ስትደርስ ሁኔታው እጅግ አስቸጋሪ እንደነበር አውቄአለሁ፡፡ አሁን እንደተማርኩት ቢሆን ኖሮ ...ሁኔታው ከእኔ አቅም በላይ ስለሆነ ምንም ጊዜ ሳልፈጅ በአስቸኳይ ወደከፍተኛ ሕክምና እልካት ነበር፡፡ ወደፊት ግን በሰለጠንኩት መሰረት የምችለውን ሕክምና እሰጣለሁ...እኔ የማልችለውን ግን አላስፈላጊ መዘግየትን አስወግጄ ቶሎ ወደ ከፍተኛ ሕክምና እልካለሁ...” ብሎአል፡፡
ደቡበ ሲዳማ ዞን ሐዋሳ ውስጥ ስልጠና ሲወስዱ ከነበሩት መካከል አቶ ሳምሶን ሰንበቶ ከቦና ዙሪያ ወረዳ እንደገለጸው የእናቶችን ጤንነት በተመለከተ በሐዋሳ ሪፈራል ሆስፒታል እየ ሰለጠኑም ተግባሩንም ከቀደምት ሐኪሞች ጋር በመሆን በመስራት ተገቢውን ልምምድ እያደረጉ ነው፡፡ በተለይም የእናቶችንና የህጸናትን ጤንነት በተመለከተ የተሰጠው ስልጠና መሰረታዊና ህብረተሰቡንም ለማገልገል የሚያስችል ነው እንደ አቶ ሳምሶን ሰንበቶ አስተያየት፡፡ እኔ ባለሁበት አካባቢ እናቶችም ሆኑ ጨቅላ ሕጻናቶች ብዙውን ጊዜ የሚሞቱት ከወሊድ ጋር በተያያዘ ሲሆን በዚህ ምክንያት የሚፈጠረውን ክፍተት ለመዝጋት ሙሉ በሙሉ ባይሆንም በተቻለ መጠን የሚያግዝ እውቀትን ጨብጠናል ብዬ አምናለሁ ብሎአል አቶ ሳምሶን ሰንበቶ፡፡
የWATCH ፕሮጀክትን ተግባራዊ በማድረግ ረገድ ከESOG ጋር በትብብር የሚሰራው የፕላን ኢንተርናሽናል ኢትዮጵያ የደቡብ ማስተባበሪያ ጽ/ቤት የፕሮጀክቱ አስተባባሪ ገዳምነሽ ደስታ ትባላለች፡፡ ፕላን ኢንተርናሽናል ኢትዮጵያ ከፕላን ካናዳ እና ከሲዳ ያገኘውን ብር Berehan integrated community development organization በመስጠት ይህ ፕሮጀክት በተያዘለት አላማ መሰረት በሲዳማ ዞን በሶስት ወረዳ ላይ በትክክል በመሰራት ላይ መሆኑን ይቆጣጠራል፡፡ የኢትዮያ የጽንስና ማህጸን ሐኪሞች ማህበርም ቴክኒካል አማካሪ በመሆን በሶስቱ ወረዳዎች ለሚገኙ እና በዞኑ የጤና መምሪያ ክትትል ምርጫው ተካሂዶ ሰልጣኞች ሲላኩ የስልጠናውን ሂደት በማከናወን የድርሻውን ይወጣል፡፡ በተጨማሪም ሰልጣኞቹ ወደሚሰሩበት ጤና ጣቢያ በሚመለሱበት ጊዜ ስራ ላይ የሚያውሉትን የህክምና መገልገያ መሳሪያና መድሀኒትን ግዢ በሚመለከትም ESOG ያማክራል፡፡ ስለዚህም ፕሮጀክቱ በአሁኑ ወቅት የሚሰራው ሁለት ነገር ላይ ሲሆን አንደኛው አቅም ማጎልበት እንዲሁም ሌላው ደግሞ በመንግስት ተዘርግቶ ባለው የጤና ስርአት ውስጥ ያሉ ክፍተቶችን ማሟላት ነው። ስለዚህም እናቶችና ሕጻናት የሚገጥ ማቸውን የጤና ችግር ለማቃለል በትብብር መሰረታዊ ስራ እየተሰራ ያለበት ደረጃ ላይ ነን ብለዋል ከፕላን ኢንተርናሽናል ኢትዮጵያ ገዳምነሽ ደስታ፡፡
ይቀጥላል

Read 4164 times