Monday, 18 November 2013 11:16

“የአፍሪካ መሪዎች የዓለም አቀፍ ፍርድ ቤቱ ላይ ሲጮሁ አፍራለሁ”

Written by  ኤልሳቤጥ እቁባይ
Rate this item
(5 votes)

የጋምቢያው ፕሬዚዳንት ያያ ጃሜ “ኤች አይቪን አድናለሁ” በማለታቸው
ለረጅም ጊዜ ከሚዲያ ዘገባ የማይጠፉ ፕሬዚደንት አድርጓቸው ነበር፡፡
በቅርቡ ደግሞ አገራቸው ከኮመንዌልዝ አባልነቷ መውጣቷን በድንገት ማወጃቸውን ተከትሎ የዓለም መነጋገሪያ ሆነዋል፡፡ ፕሬዚደንቱ ከ“ኒው አፍሪካን” መፅሄት ጋር ያደረጉት ቃለምልልስ ለጋዜጣው በሚመች መልኩ ተጠናቅሮ እንደሚከተለው ቀርቧል፡፡

ጋምቢያ ከኮመን ዌልዝ አባልነቷ መውጣቷ የመነጋገሪያ ርአስ ሆኗል፡፡ ከአርባ አምስት አመት በኋላ ከአባልነት ለመውጣት ለምን ወሰኑ?
ዜናው አነጋገሪ ሊሆን አይገባም ነበር፡፡ ጋምቢያ ይህን ውሳኔ የወሰነችው ከቅኝ ግዛት ጋር ከተያያዙ ነገሮች ነፃ መሆን ስለምትፈልግ ነው፡፡ በተለይም ምንም አዲስ ነገር በሌለበት ሁኔታ ውሳኔ የሚሰጠው ከአንድ ወገን ብቻ ሲሆን አባል መሆን ለምን ይጠቅማል፡፡ እኛን ሳያዳምጥ “ይህን አድርጉ” እያለ በሚያዝና ብቻውን በሚወስን ተቋም አባል ከመሆን መውጣቱ የተሻለ ነው፡፡ ስለዚህ ነፃነታችንን ካገኘን ከአርባ ስምንት አመት በኋላ ቅኝ ግዛት እና እንግሊዝ በቃን ብለናል፡፡ ወደኋላ መለሱን እንጂ የትም አላደረሱንም፡፡ የዚህ አመት ዋናው መፈክራችን “እንደ ባህላችንና እንደ ሀይማኖታችን እንኑር” የሚል ነው፡፡ ስለዚህ ኮመን ዌልዝ ሀይማኖታችንም ባህላችንም አይደለም፡፡ ከቅኝ ግዛት ጋር ንኪኪ ባላቸው ተቋሟት አባል መሆን አንፈልግም፡፡ በጋምቢያውያንነታችን መቀጠል እንፈልጋለን፡፡
በመንግስታቱ ድርጅት ያደረጉት ንግግር በመገናኛ ብዙኀን በአሉታዊ መንገድ መዘገቡን ተከትሎ አባልነትዎን መሰረዝዎስ?
በጣም የሚገርመኝ ነገር አለ፡፡ ከአንድ ሰውጋር ያለሽን ግንኙነት ለማቋረጥ በመጀመሪያ ከዛ ሰው ጋር ችግር መፈጠር አለበት የሚል አስተሳሰብ አለ። ይህ ለኔ ትክክል አይደለም፡፡ ችግር ካለ ችግሩን መፍታት ነው፡፡ እኔ እያልኩ ያለሁት ኮመን ዌልዝ የቅኝ ግዛት ተቋም ነው፡፡ ስለዚህ ከአሁን በኋላ አባል አይደለንም፡፡ በነገራችን ላይ ከኮመን ዌልዝ ብቻ ሳይሆን ከቅኝ ግዛት ጋር ግንኙነት ካለውና የቅኝ ግዛት ዘመንን ከሚያስቀጥል ማንኛውም ተቋም ጋር ግንኙነት አይኖረንም፡፡ ምክንያቱም ከቅኝ ግዛት ያተረፍነው ድህነት፤ ኋላቀርነት፤ብዝበዛ እና ባርነትን ነው፡፡
በዚህ ዘመን ለባርነት ተጠያቂ ከሆኑ አገሮች ጋር ትስስር ሊኖረን አይገባም፡፡ አይሁዳውያን እና ሌሎች ህዝቦች ለደረሰባቸው በደል ካሳ ተከፍሏቸዋል፡፡ አፍሪካን ግን ማንም ዞር ብሎ አላያትም፡፡ ባርነትንና ቅኝ ግዛትን ያመጣችብን እንግሊዝ ካሳ ልትከፍለን ቀርቶ ይቅርታም አልጠየቀችንም፡፡ ጋምቢያውያን በቅኝ ግዛት ቀንበር ስር በነበሩባቸው አመታት ማንም ሳይንቲስቶች እና ዶክተሮች እንዲሆኑ ስልጠና አልተሰጣቸውም፡፡ ለሌሎችም አፍሪካውያን እድል አልተሰጠም፡፡ እኛ ልክ እንደ ሌላው የሰው ዘር አይደለንም?
ምእራባውያኑ አሁንም አፍሪካ ኋላ እንድትቀር ይፈልጋሉ ብለው ለምን ያምናሉ?
አንቺ አለምን እየዞርሽ የምታይ ጋዜጠኛ ነሽ፡፡ ልክ እንደ ዱባይ ወይም የመካከለኛው ምስራቅ አገራት በቀድሞ ቅኝ ገዢያቸው ያደጉ የአፍሪካ አገሮችን ልትነግሪኝ ትችያለሽ? ሌሎችን የምትከተይ ከሆነ መምራት አትችይም፡፡ እኛ አፍሪካውያን ለዘመናት ስንከተላቸው ኖረናል፡፡ አሁንም እየተከተልናቸው ነው፡፡ በቃ ካላልን ወደፊትም እንከተላቸዋለን፡፡ ኋላ የቀረነውም ለዚህ ነው፡፡ ለአፍሪካ ያለኝ መልእክት መከተሉን አቁመን መሪ እንሁን ነው፡፡ በአፍሪካ እና በምእራባውያኑ ግንኙነት አፍሪካ ተጠቃሚ እየሆነች አይደለም፡፡ ተጎጂ ናት፡፡ እኔ እና ጋምቢያ ማንንም መከተሉን ትተን የራሳችንን ሀይማኖት፣ ባህል እና እምነቶች መከተል ጀምረናል፡፡ አፍሪካ በተፈጥሮ ፀጋ የታደለች አህጉር ሆና ለምን ድሀ ሆነች? አውሮፓውያኑ ምን ስለሆኑ ነው አፍሪካውያን ምን መስራት እንዳለባቸው የሚያስተምሩት? ከቅኝ ግዛት አንስቶ እስካሁን ራሳቸውን የአፍሪካ ፈጣሪ አድርገው ያስባሉ፡፡ ጋምቢያ በቃ እያለች ነው፡፡ በሙዚቃቸው መደነስ ስታቆሚ አምባገነን ይሉሻል፡፡
ሌሎች የአፍሪካ አገሮች የእርስዎን ውሳኔ የሚከተሉ ይመስልዎታል?
የሚጠቅመንን መከተል ጥሩ ውሳኔ ነው፡፡ ወደ ኋላ የሚመልስሽን የምትከተይ ከሆነ፣ አላዋቂ ብቻ ሳይሆን የምትሆኚው በህዝብሽ ፍላጎት እየሰራሽ አይደለም ማለት ነው፡፡ ቅኝ አገዛዝና የእጅ አዙር ቅኝ አገዛዝ በማንኛውም መልኩ ከአፍሪካ መወገድ አለባቸው፡፡ ምክንያቱም ትርፉ ውርደት እና ስድብ ነው፡፡
የሌሎች ድርጅቶች አባልነትዎን ግን አልተዉም?
ውሳኔዬ ወደ ሌላ መተርጎም የለበትም፡፡ እኔ ያልኩት በጣም ግልፅ ነው፡፡ ከቅኝ ግዛት እና ከእጅ አዙር ቅኝ አገዛዝ ጋር ከተያያዘ ማንኛውም ተቋም ጋር ግንኙነት አንፈልግም፡፡ ይህ ማለት ግን ሌሎች የአለም አቀፍ ተቋማትን ያጠቃልላል ማለት አይደለም፡፡ ኮመንዌልዝ የእጅ አዙር ቅኝ አገዛዝ ተቋም ብቻ ሳይሆን የምርጫ ሂደትም የለውም፡፡ አንድ ግለሰብ የህይወት ዘመን መሪ ነው፡፡ ይሄ ምን አይነት ዲሞክራሲ ነው? ተረዳሽኝ?
እንግሊዞቹ በነሱ ላይ ብቻ የዘመቱ አይመስላቸውም?
እንግሊዞቹ ኮመንዌልዝ የነሱ እንደሆነ ካሰቡ ለመውጣታችን ጥሩ ምክንያት ይሆናል፡፡ ለምንድነው የራሳቸው እንደሆነ የሚያስቡት?
ሌላው ተመሳሳይ ድርጅት ደግሞ አለም አቀፉ የወንጀለኞች ፍርድ ቤት አንዱ ነው፡፡ ድርጅቱን ከሚመሩት መካከል በእርስዎ መንግስት ያገለገሉት ፋቱ ቤንሶዳ ይገኙበታል፡፡ ድርጅቱ ከአፍሪካ መሪዎች ተቃውሞ እየገጠመው ነው፡፡ በፍርድ ቤቱ ላይ ያለዎት አስተያየት ምንድን ነው?
እኔ እስከሚገባኝ ድረስ ፍርድ ቤቱ የቅኝ ገዢ ተቋም አይደለም፡፡ በቅርቡ ነው የተቋቋመው፡፡ ነገር ግን በሌሎቹ ተቋሟት ላይ እንደምናደርገው አባል ለመሆን እጅግ በጣም ፈጣኖች ነን፡፡ አባል እንሆንና ካፀደቅነው በኋላ ምን እንደሚል ማንበብ እንጀምራለን፡፡
ከዛ ነገሮችን ወደ ኋላ ለመመለስ አስቸጋሪ ይሆንብናል፡፡ ዘለን ከአንዱ ወደ አንዱ አንሳፈር ብዬ ጓደኞቼን አስጠንቅቄያለሁ፡፡ ሁሉም አውቶብስ ውስጥ መዳረሻውን ሳናውቅ እንሳፈራለን። ሾፌሩ በመሀል ላይ “አፍሪካውያን ውረዱ” ሲል ለምን ተሳፈርን ብለን መጠየቅ እንጀምራለን። ከአለም አቀፉ የወንጀለኞች ፍርድ ቤት አባላት መካከል አፍሪካ ብዙውን ድርሻ ትይዛለች፡፡ ፍርድ ቤቱ በእግሩ እንዲቆም ያደረገችው አፍሪካ ናት፡፡ እኔ መጀመሪያም ተናግሬ ነበር፣ዝም ብለን ከመቀላቀላችን በፊት ምን እንደሚል በጥሞና እንየው፡፡ ከዚህ በፊት በተደጋጋሚ በራሳችን ፈቃድ ተጎጂ የምንሆንበትን ጉዳይ ቀድመን ተስማምተናል። የፕሬዚደንት አልበሽርን ክስ አንዳንድ የአፍሪካ አገሮች ሲቃወሙት፣ አንዳንዶች ደግፈውታል፡፡ ፍርድ ቤቱ የአፍሪካ ህብረትንም ሳያሳውቅ መሪዎችን እንዲከስ ይስማማሉ፡፡ ድርጅቱ የአውሮፓ አገራት መሪዎችን ያለ አውሮፓ ህብረት ፈቃድ መክሰስ ይፈቀድለታል? ይህ ትልቅ ስድብ ነው፡፡ አንድ ክስ የሚቀርበው ወይ በክስ አቅራቢ አገር ወይም በፀጥታው ምክር ቤት ውሳኔ ነው፡፡ የአፍሪካ መሪዎች ፍርድ ቤቱ ላይ ሲጮሁ አፍራለሁ፣ምክንያቱም ከአልበሽር ጉዳይ በስተቀር የሌሎቹ ክስ የቀረበው በራሳቸው በአፍሪካ መንግስታት ነው፡፡ ራሳችን ክስ እናቀርብና መልሰን አይሲሲ ዘረኛ ነው እንላለን፡፡
ስለዚህ አይሲሲ አፍሪካውያንን ያድናል በሚለው አይስማሙም?
አዎ አልስማማም፡፡ አፍሪካ ችግር ካለባት ችግሯን በራሷ መፍታት አለባት፡፡ ችግሩን ወደ አፍሪካ ህብረት ከማምጣት ይልቅ ወደ አይሲሲ መውሰድ አያሳፍርም?
ጋምቢያዊቷ ሚስ ቤንሶውዳ በፍርድ ቤቱ እያከናወኑት ባለው ተግባር ይኮራሉ ማለት ነው?
እሷ አለም አቀፍ ሰራተኛ ናት፡፡ ኩራት የሚሰማኝ ጋምቢያዊት ስለሆነች ሳይሆን የአፍሪካ ሴት ስለሆነች ነው፡፡ ይህ ቦታ ቀደም ሲል በአፍሪካውያን የሚታሰብ አልነበረም፡፡ ዛሬ በአፍሪካዊት ተይዟል፡፡ ስለዚህ ከተቋሙ ጋር መተባበር አለብን፡፡ ለአይሲሲ ስል ሳይሆን ለእውነት ስል፡፡
ስምዎ ብዙ ጊዜ በጥሩ አይነሳም፡፡ እ.ኤ.አ በ1994 ዓ.ም ስልጣን ከያዙ በኋላ ምን ሰራሁ ይላሉ?
ከጥቂት አመታት በፊት ምንም ዩኒቨርሲቲ አልነበረም፡፡ ኮመንዌልዝን የተውንበት አንዱ ምክንያት ይሄ ነው፡፡ እንግሊዞቹ አራት መቶ አመታት ሲገዙን፣ አንድ ሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤት ብቻ ነው የሰሩት፡፡
እውነትዎትን ነው?
እየነገርኩሽ፡፡ ነፃ ከወጣን በኋላ ለ30 ዓመታት ያስተዳደረው መንግስት ይባስ ብሎ አንድም ት/ቤት ወይም ሆስፒታል አሊያም ዩኒቨርስቲ አልገነባም፡፡ የብሪቲሽ ቅኝ አገዛዝ ቢያንስ አንድ ት/ቤት ሰርቷል - ለጥቂቶች ቢሆንም፡፡ እንግዲህ ብሪቲሾች በአራት መቶ አመት ውስጥ አንድ ትምህርት ቤት ከሰሩ ኮሌጅ ወይም ዩኒቨርሲቲ ለመስራት ስንት ተጨማሪ አመታት የሚፈልጉ ይመስልሻል? ወደ አንድ ቢሊዮን አመት፡፡ ከኮመንዌልዝ ለመውጣት ስለመወሰናችን ማንንም እንዳላማከርን ቢቢሲ ዘግቧል፡፡ እነሱ የሚፈልጉት በቅድሚያ ነግረናቸው ፈቃዳቸውን እንድናገኝ ነው፡፡ እኛ የማንም አገልጋይ አይደለንም። እኛ በየአመቱ ከኮመንዌልዝ ከምናገኘው ጥቅም ይልቅ የምንከፍለው ይበልጣል፡፡
በምእራብውያኑ መገናኛ ብዙሀን እና በተቃዋሚ ፖለቲከኞች ዘንድ አምባገነን ተብለው ነው የሚታወቁት፡፡ የግብረሰዶማውያን መብትን ጨምሮ በሰብአዊ መብቶች አያያዝ ጥሰት ይወቀሳሉ፡፡ እርስዎ ምን ይላሉ?
አዎ የልማት አምባገነን ነኝ፡፡ የለውጥ አምባገነን ነኝ፡፡ በሌሎች ትእዛዝ የማይሰራ አምባገነንም ነኝ፡፡ ጋምቢያ ውስጥ ግን የህዝብ አገልጋይ ነኝ፡፡ ረጅም መንገድ መጥተናል፡፡ ገና ረጅም መንገድ ይቀረናል። የምንመካው በፈጣሪ እና እንደ ሰው በሚቆጥሩን አገሮች ነው፡፡ ግብረሰዶማዊነትን ጋምቢያ ውስጥ በፍፁም አንፈቅድም፡፡ የመንግስት አስተዳደርን በተመለከተ ደግሞ እነሱ አፍሪካን ይገዙ በነበረ ጊዜ አፍሪካውያን በምርጫ ተሳትፈው ያውቃሉ? ሰብአዊ መብት፣ ነፃነትና መልካም አስተዳደር ቅኝ ገዢዎችን የሚመለከት አይመስልም እኮ፡፡
ተቃዋሚዎችንና ጋዜጠኞችን በመግደልም ይወነጀላሉ---
ሰውን ሰቅሎ መግደል አፍሪካ ውስጥ የመጣው በቅኝ ገዢዎች ነው፡፡ ከቅኝ ግዛት በፊት አፍሪካ ውስጥ የነበረው ክፍያ ነው፡፡ ሰው የሚሞተው በጦርነት ላይ ብቻ ነበር፡፡ የጭካኔ አይነት አፍሪካውያን ላይ ሲፈፅሙ ኖረው የሰብአዊ መብት አስተማሪ መሆን ይፈልጋሉ፡፡ አፍሪካውያንን በአንድ መርከብ ላይ እንደ ሰርዲን አሽጎ ወስዶ፣ አሜሪካን ገበያ ላይ በጨረታ ከመሸጥ፣ ከዛም ከውሻ ያነሰ ኑሮ እንዲኖሩ ከማድረግና አህጉሪቱን ከመዝረፍ በላይ ምን የመብት ጥሰት አለ? ለዚህ ኢ-ሰብአዊ ድርጊታቸው ይቅርታ እንኳን ያልጠየቁ፣ አፍሪካን ስለ ዲሞክራሲ እና ሰብአዊ መብት ሊያስተምሩ ይችላሉ?
ጋምቢያ የነዳጅ ሀብት አላት?
አዎ አለን ፡፡ ጥቅም ላይ ያላዋልናቸው ማእድኖች እና ነዳጅ አለን፡፡ እስከ ዛሬ ነዳጃችንን ያላወጣነውም አምስት በመቶ ብቻ ለእኛ ተሰጥቶ የቀረው ሌሎችን ተጠቃሚ በሚያደርግ ስምምነት መገዛት ስለማልፈልግ ነው፡፡
የተፈጥሮ ሀብትን ለልማት ማዋልንን እና ግሎባላይዜሽንን እንዴት ያዩታል?
ግሎባላይዜሽን ማለት የተፈጥሮ ሀብትን ዝም ብሎ መስጠት አይደለም፡፡ ሁሉም ኩባንያዎች መጥፎ ናቸውም አላልኩም፡፡ ምርጫ ሊሰጠን ይገባል፡፡ ሞራል ካላቸው ሀብቱ የአፍሪካውያን እንደሆነ ከሚያምኑ ጋር እንሰራለን፡፡ ቻይና ያለምንም ቅድመ ሁኔታ ለአፍሪካ አምባገነኖች እርዳታ ታደርጋለች የሚል ተደጋጋሚ ስሞታ እንሰማለን፡፡ ግን እነሱ ራሳቸው የቻይናን ካፒታል ኢንቨስትመንት ይቀበላሉ፡፡ የቻይና የአፍሪካ አጋር ሆኖ መምጣት ለአፍሪካ ምርጫ ሰጥቷል፡፡ የቻይናን ስም የሚያጠፉትም ለዚህ ነው፡፡ አሁን ደግሞ ብሪክስ አገሮች እየመጡ ነው፡፡ ዋናው ነገር ከሚጠቅመን ጋር መስራት ነው፡፡ ሁሉም ምእራባውያን ደም መጣጮች አይደሉም፡፡

Read 4571 times